
Administrator
የከተማችን ግዙፍ ሆቴል ከሁለት ሳምንት በኋላ ስራ ይጀምራል
“ማንኛውም ሰው ንጹህ ውሃ በነጻ መውሰድ ይችላል” ይላል የሆቴሉ የውሃ ቧንቧ ላይ ተለጥፎ ያየነው ማስታወቂያ ። ሆቴሉ በራሱ ወጪ አስቆፍሮ ያወጣውንና ለሆቴሉ አገልግሎት የሚጠቀምበትን የከርሠ ምድር ውሃ የአካባቢው ማህበረሰብ ለ 24 ሰዓት እንዲጠቀምበት ፈቅዷል ።በደቡብ አፍሪካ በስደት የቆዩት ወ/ሮ ህይወት አየለ እና በባለቤታቸው አቶ ዳግማዊ መኮንን የተገነባው ግዙፉ ስቴይ ኢዚ ፕላስ ሆቴል ለእንጦጦ ቅርብ በሆነ አካባቢ ተገንብቷል ።
ስቴይ ኢዚ ፕላስ ሆቴል 103 የመኝታ ክፍሎች፣ ከ15 እስከ 1,500 ሰዎችን ማስተናገድ የሚችሉ ስድስት የስብስባና፣ የሰርግ አዳራሾች እንዲሁም የኪነጥበብ እና ሌሎች ዝግጅቶች የሚሆኑ ሰፋፊና ምቹ አዳራሾች አሉት።
ከእንጦጦ ፓርክና ቦታኒክ ጋርደን ለሚመጡ ጉብኚዎች እንዲሁም በእንጦጦ እና ሱልልታ የሩጫ ልምምድ ለሚያደርጉ አትሌቶች በቅርብ የሚገኝ ደረጃውን የጠበቀ ሆቴል እንደሆነ የተነገረለት ይኸው ሆቴል በግልና በቡድን ለሚመጡ የአገር ውስጥና የውጭ አገር አትሌቶች ምቹና አስተማማኝ አገልግሎት ለመስጠት እንዲያስችል ሆኖ መዘጋጀቱም ተጠቁሟል ።
ሆቴሉ በሰዓት ከ30,000 ሺ ዳቦ በላይ ማምረት የሚችል ዘመናዊ ማሽን ያሉት ሲሆን ለአካባቢው ማህበረሰብ ዳቦ በተመጣጣኝ ዋጋ ለማቅረብ መዘጋጀቱም ተነግሯል ። ከ 250 በላይ ለሚሆኑ ዜጎችም የስራ ዕድል መፍጠር ችሏል። ከመሀል ከተማ ፒያሳ በመኪና አስር ደቂቃ ብቻ የሚወስድ ሲሆን ፀጥ ያለ እና ነፋሻማ ስፍራ ላይ የሚገኝ ሆቴል ነው።ሆቴሉ በአጠቃላይ የያዘው ስፍራ 2,250 ሜትር ስኩዬር ሲሆን በ1,700 ሰኩዬር ላይ ሆቴሉ ተገንብቷል።
የኤሌትሪክ መኪና ይዘው ለሚመጡ ደንበኞቹ ኤሌትሪክ ቻርጅ ማድረጊያ ቦታ ያለው ሲሆን በቅርቡ በሚጠናቀቁት የማስፋፊያ ፕሮጀክቱ ሰፖርት መስሪያ ጂም ፣የሴትና የወንድ ለየብቻ (በFloor) ሳውና እና ስቲም ባዝ ፣ መዋኛ ገንዳ፣የዮጋ አዳራሽ በተጨማሪም የባህል ሬስቶራንትና የሙዚቃ አዳራሽ ይኖረዋል። በተጨማሪም እስቴ ኢዚ ፕላስ ሆቴል የከርሰ ምድር ውሃ ያለው ሲሆን በሰከንድ አምስት ሊትር ውሃ ማመንጨት የሚችል ሲሆን ለማህበረሰቡ ለ24 ሰዓት በነፃ እየሰጠ ማህበረሰባዊ ኃላፊነቱን እየተወጣ የሚገኝ ሆቴል ነው፡፡
ስቴይ ኢዚ ፕላስ ሆቴል ከእዚህ በፊት 22 አካባቢ በነበረው ሆቴሉ አማካኝነት በበርካታ የበጎ አዶራጎት ስራውች ላይም በመሣተፍ ሀላፊነቱን ሲወጣ ቆይቷል።
መሰናክሎች፤ መልካም ዕድሎች ናቸው!
በጥንት ጊዜ ነው፡፡ አንድ ንጉስ ቋጥኝ ድንጋይ ሆን ብሎ ዋናው መንገድ ላይ ያስቀምጣል፤መንገዱን ዘግቶ ማለት ነው፡፡ ከዚያም ተደብቆ በዚያ ከሚያልፉ ሰዎች መካከል ያንን ቋጥኝ ከመንገዱ ላይ ማን እንደሚያነሳው በጉጉት መመልከት ይጀምራል፡፡
መጀመሪያ ላይ ለንጉሱ ቅርብ የሆኑ ሃብታም ነጋዴዎችና ባለሟሎች መጡ፡፡ ነገር ግን ያ መንገዱን የዘጋው ቋጥኝ ድንጋይ ፈጽሞ አላሳሰባቸውም፡፡ ከአነ መኖሩም ትዝ ያላቸው አይመስሉም፡፡ በራሳቸው ወሬ በእጅጉ ተጠምደው ድንጋዩን ታከው አለፉት፡፡
በዚያ መንገድ ያለፉ በርካታ ሰዎች ግን፤ “ለምን ንጉሱ ይሄን ቋጥኝ ድንጋይ አያስነሳውም?!” ብለው በእጅጉ አማረሩ፡፡
አንዳቸውም ግን በግልም ሆነ ተባብረው ያንን ድንጋይ ከጎዳናው ላይ ለማንሳት አልሞከሩም፡፡ አማረው ብቻ ነው የሄዱት፡፡
በመጨረሻ ግን አትክልት የተሸከመ አንድ ገበሬ መጣ፡፡ መንገድ ዘግቶ የተቀመጠውን ቋጥኝ ድንጋይ እንደተመለከተም፣ የተሸከመውን አትክልት ከራሱ ላይ አውርዶ መሬት አስቀመጠና፣ከቋጥኙ ጋር ብቻውን ይታገል ገባ፡፡ ረዥም ጊዜ ወሰደበት፡፡ ከብዙ ልፋትና ድካም በኋላም ተሳካለት፡፡ ድንጋዩን ከመንገዱ ላይ ገፍቶ ገፍቶ ዳር ላይ ማድረግ ቻለ፡፡
ከዚያም መሬት ላይ ያስቀመጠውን አትክልት አንስቶ ሊሸከም ሲል፣ ቋጥኙ ድንጋይ ተቀምጦ የነበረበት ቦታ ላይ አንድ ቦርሳ ተቀምጦ ተመለከተ፡፡ ቦርሳው በብዙ ወርቆች የተሞላ ነበር፡፡ ገበሬው ደነገጠም፤ ተገረመም፡፡ ዙሪያ ገባውን ቃኘና፣ ቦርሳውን ልውሰድ አልውሰድ በሚል ሃሳብ ለአፍታ ተጨነቀ፡፡
ወዲያው ግን የንጉሱ መልዕክት የሰፈረበት ብጫቂ ወረቀት እዛው ቦርሳው ውስጥ አገኘ፡፡ “ይህን ቦርሳ፤ ቋጥኙን ከመንገድ ላይ ያነሳ ሰው ይውሰደው፤ ሽልማቱ ነው” ይላል፤የንጉሱ ማስታወሻ፡፡
ሁሌም በመንገዳችን ላይ የሚገጥሙን ፈተናዎችና መሰናክሎች፣ ህይወታችንን ለማሻሻል የሚጠቅሙን መልካም ዕድሎችና አጋጣሚዎች ናቸው፡፡ ሰነፎች በገጠሟቸው ፈተናዎችና መሰናክሎች ሲያማርሩና ሲያለቃቅሱ፤ ጎበዞች ግን ችግሮችና ፈተናዎችን ወደ መልካም አጋጣሚ በመቀየር ስኬት ይቀዳጁበታል፡፡
“ሰይጣንን የሚያናድደውስ ማነው?
ሰውየው ሞተ፡፡ ሰማይ ቤት ሲደርስ ሚዛን ጠበቀው፡፡ ምድር ላይ ያቆመው መልካም ስራውና ሃጢአቱ ተመዘነ፡፡ ዕኩል ተዕኩል ሆነ፡፡
“ከእኔም ካንተም አልሆነም”… አለ እግዜር፡፡
“ምን ይሻላል?”… ጠየቀ ዲያብሎስ፡፡
“ወደመጣበት እንመልሰውና እንየው”
“ለምን አንፈትነውም?”
“እንደሱም ይቻላል”
አምስት፣ አምስት ጥያቄዎች አዋጥተው ፈተኑት። ፈተናውን ካለፈ ገሃነም፣ ከወደቀ ገነት እንዲገባ ተስማሙ፡፡ ዲያብሎስ ያወጣቸው ጥያቄዎች በጣም ቀላል ነበሩ - ሰውየውን ለማሳለፍ፡፡ የእግዜር ደግሞ በእጅጉ ከባድ ሆነ - ሰውዬው እንዲወድቅለት፡፡… ውጤቱ ዕኩል ተዕኩል ሆነ - እንደ በፊቱ፡፡
“ምን ይሻላል?”…ጠየቀ እግዜር፤ በተራው፡፡
“እኔ እንጃ!” አለ አጅሬው፤ ትከሻውን እየነቀነቀ።
የነሱን ንግግር ያዳመጠው ሟች፤ “በገዛ ፍቃዴ ገሃነም መግባት ነው እምፈልገው” አላቸው፡፡
“መብትህ ነው” አለ ዲያብሎስ፡፡
“ምክንያቱን ማወቅ እንፈልጋለን” … አለ እግዜር።
“ከኛ በላይ ሃይማኖተኛ የለም፤ ያዙን ልቀቁን የሚሉ በተግባር ግን እዚህ ግቡ የማይባሉ አስመሳዮች ምድር ላይ አበሳዬን ሲያሳዩኝ ነው የኖርኩት፡፡ እዚህ ግን ከእንደነሱ አይነት ጋር መኖር አልፈልግም፡፡” አለ ሟች፡፡
“ምን በወጣህ፣ ካልፈለግህ አልፈለግህም ማለት ነው”…. አጅሬ ነበር፡፡
“እሱ ያንተ ፈቃድ ነው፡፡ ምርጫህ የተሟላ እንዲሆንልህ ግን ሁለቱንም ቦታዎች አይተህ ብትወስን አይሻልህም?” ሃሳብም፣ ጥያቄም አቀረበለት፤ እግዜር፡፡
“እሽ” አለ ሰውየው፡፡
አጅሬውም፤ “በጣም ጥሩ” በማለት ተስማማ፡፡
ሦስቱም ተያይዘው ወደ ገሃነም አቀኑ - ቅርብ ከነበረው ለመጀመር፡፡ እዛ እንደደረሱ ሁለቱ አለቆች በር ላይ ቀርተው ሰውየው ደርሶ እንዲመጣ ላኩት። ሟች ወደ ውስጥ እንደዘለቀ የሚያየው ነገር ሁሉ አስደሰተው፡፡፡ አስመሳዮች፣ ጉበኞች፣ ዘረኞች፣ የመሳሰሉት አልነበሩም፡፡ የሚመለከተው ሰው ሁሉ ቅን፣ ደጋግና አስተዋይ ከመሆኑም በላይ መንገዱ፣ አትክልቱ፣ ምንጣፉ ልዩ ነው፡፡
ጉብኝቱን ጨርሶ ሲመለስ…
“እህሳ፣ እንዴት አገኘኸው?”…አጅሬ ጠየቀው፡፡
“ቆይ እስቲ አትቸኩል፤ ያኛውንም ይይና አንድ ላይ ይነግረናል”… አለ እግዜር፡፡
“አይ በቃ…ምንም ችግር የለም፡፡ ባላየውም ይሄኛውን መርጫለሁ፤ ቻዎ ጌታው” ብሎ ዲያብሎስን ተሰናበተ - ሰውየው፡፡ እግዜር ምንም አላለም፡፡ የሟችን እጅ ይዞ ወደ ገነት ሲያመራ…
“ቡዳ!” አለ፤ አጅሬ ጮክ ብሎ፡፡
እግዜር ሳቀ፡፡…
“ማንን ነው እሚሳደበው?.... የፈለግከውን ምረጥ አይደል እንዴ ያላችሁኝ?”…ጠየቀ ሰውየው፡፡
“ዓመሉ ነው…አርቴፊሻል ገነት አዘጋጅቶ ሊያታልልህ መሞከሩ ስለተነቃበት ነው፡፡” …አለ እግዜር፡፡
“እንዴ?... ያ ሁሉ ውበት፣ ያ ሁሉ ምቾት የውሸት ነበር?”
“አዎ…አንድም ዕውነት የለበትም፡፡”
“ታዲያ እኔ መች አወቅሁ?... እንዲያውም እዛ መቅረት ፈልጌ ነበር፡፡ ምን እንደነካኝ እንጃ እንጂ…”
“እንዳትቀር ያደረግሁህ እኔ ነኝ፡፡”
“እንዴት?”
“ሀሳብህ ሆንኩ፣ አንተን ራስህን ሆንኩ፡፡”
“አልገባኝም”
“እንኳን ያንተን የሟቹን፣ የሱን ሃሳብ በማወቄ አይደል፣ አዘጋጅቶ ስላሳየህ ውሸት የነገርኩህ!”
“ሃሳብማ ከሆንክ…ይኽ ሁሉ ድካም ለምን?”
“ገብቶኛል”… አለ እግዜር ሳያስጨርሰው። ቀጠለናም፤ “…እሱ ሊያታልልህ ባይሞክርና ዕውነተኛውን ገሃነም ቢያሳይህ ኖሮ፣ እኔም ሀሳብህን አልሆንም ነበር፡፡ ምርጫው ያንተና ያንተ ብቻ በሆነ”
“ታዲያ ለምን ዝም አልከው?”
“ቻይ መሆን ያስፈልጋል፤ ያለ ተቃራኒ መኖር አይቻልም፣ እሱ ባይኖር እኔን ማን ያውቀኛል?”
“አቦ ይመችህ፣ ምድር ላይ ነው እንጂ… እዚህ ፍትሃዊ ትመስላለህ”…አለ ሰውየው፡፡
እግዜር እየሳቀ፣ በሩን ከፍቶ አስገባውና ተመለሰ።
ወዳጄ፤ እግዜር “ያለ ተቃራኒ መኖር አይቻልም፤ ተቀናቃኝ ባይኖረኝ እኔን ማን ያውቀኛል” ማለቱ ዕውነትነት አለው፡፡ ሰይጣን ባይኖር የእግዜር ደግነት፣ ርህሩህነት፣ አሳቢነትና ፍትሃዊነት በምን ይታወቃል? ... “እግዜር ይመስገን፣ ለሱ ምን ይሳነዋል፣ በሱ ቸርነት እንዲህ ሆኛለሁ፣ በሱ ፈቃድ እዚህ ደርሻለሁ ምስጋና ይግባው...፣” የምንለውን ያህል…ግጭት በሚኖርበት፣ ጠብ በሚነሳበት ጊዜ “ሰይጣን መሃል ገብቶ ነው”፣ ክፋትና ተንኮል ሰርተን “ሰይጣን አሳስቶኝ ነው፤ ሰይጣ ገፋፍቶኝ ነው፤ ያ ከይሲ ነው ጉድ ያደረገኝ” እንላለን፡፡
አንድ የቆየች ቀልድ እነሆ፡- በገዳም የሚኖሩ እማሆይ፤ ዕንቁላል መብላት አማራቸው፡፡ በዓቢይ ፆም ወቅት ነበር፡፡ አንድ እንቁላል አነሱና፤ “ጌታዬ ይቅር በለኝ” አሉ፡፡ እሳት ማቀጣጠል፣ መጥበሻ መጣድ ፈሩ፡፡ ጧፍ ለኮሱና ጠፍጣፋ ድንጋይ አጋሉ፡፡ እንቁላሏን ቀጭ አድርገው ሲያፈሱበት፣ አሪፍ ኦምሌት ሆነላቸው፡፡… ሽታ የለ፣ ምን የለ!... ከጫፉ ቆረስ አድርገው ቀመስ ሲያደርጉ፣ ከዚህ መጡ የማይባሉ መነኩሴ ከች አሉ፡፡
“እግዚኦ! እግዚኦ! ምነው? ምነው እማሆይ?” እራሳቸውን ይዘው ጮሁ፡፡…
እማሆይ ክው፤ ድርቅ አሉ፡፡ ነፍሳቸው ስትመለስ፤ “አባቴ ይቅር በሉኝ፣ ያ ከይሲ አሳስቶኝ ነው” አሉ፡፡ አጅሬ እዛ አካባቢ ሆኖ ሲያደርጉ የነበረውን ሁሉ ይመለከት ነበርና ሳቁን መቆጣጠር አልቻለም፡፡ “እንኳንስ ላሳስታቸው፣ እንቁላል እንደዚህ እንደሚጠበስ ለመጀመሪያ ጊዜ በማየቴ ገርሞኛል” አለ አሉ፡፡ የሰይጣንን ነገር ካነሳን አይቀር፣ ካህሊል ጂብራን “ሳታን” በማለት የፃፋት ትንሽ መጽሐፍ አለች፡፡ እዛ ላይ “…አጅሬው ታሞ ከመንገድ ዳር ተኝቶ ያቃስታል፣ በሰው ተመስሎ፡፡ ለስርዓተ ፀሎት የሚጣደፉ አባ በዚያ በኩል ሲያልፉ፡-
“አባቴ አይለፉኝ፣ በጠና ታምሜአለሁ” አላቸው፡፡
እሳቸውም፤“ልጄ ቸኩያለሁ፣ እግዜር ይማርህ” በማለት ሲጣደፉ፤ “ትተውኝማ እንዳይሄዱ፣ በኋላ እንዳይቆጭዎት፣ ልሞት እችላለሁ፤ እኔ ከሞትኩ ደግሞ ስራዎን ያጣሉ፣ ይራባሉ፣ እስከ ዛሬ ድረስ የሚሰብኩት፣ የሚናገሩት ነገር ሁሉ ዜሮ ይሆናል።” አላቸው፡፡
“እ … ምን አልክ?....” አሉ አባ፤ በመገረም፡፡ ቀጥለውም፤ “ማነህ አንተ ለመሆኑ?” … ሲሉ ጠየቁ።
“እኔማ ሰይጣን ነኝ” አላቸው፡፡
አባ ደንግጠው፤ “በስመአብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ፣ አንት ከይሲ…”
አላስጨረሳቸውም፡፡
“እሱን ተወውና ዕውነቱን እንነጋገር፡፡ … ሁሉን ነገር በኔ ታሳብባላችሁ፣ እኔ ባልኖር የናንተ ስራ ምንድነው? ይሄ ሁሉ ቤተ እምነት፣ ይሄ ሁሉ መስጂድ፣ … ይሄ ሁሉ አዳራሽ ምን ይደረግበት ነበር? … ስምንት ሺ ዓይነት እምነት አለ፡፡ በነዚህ ተቋማት የሚተዳደሩ ሁሉ ምን ይሆኑ ነበር? … የሚገባህ ከሆነ የምኖረው ለናንተ ነው፡፡ ደግሞ ባንተ ብሶ …” እያለ ሲቆጣና ሲዘረዝር አባ ቀዘቀዙ፡፡ አሰቡ፣ አሰቡናም “እውነት ነው” አሉ፤ለራሳቸው፡፡ “… አንተ ብትሞት ምን እናስተምራለን? ሐጢአታችንን በማን እናሳብባለን? ደግሞስ ምን እንበላለን?” እያሉ በሆዳቸው… አጅሬውን ደግፈው፣አንስተው እንዳይሞትባቸው ሊንከባከቡት ወደ ቤታቸው ተመለሱ” .. ይለናል ፤ ካህሊል ጂብራን፡፡
ወዳጄ፤ “…አቤት የሰው ነገር፣ አበሻ ሲባል …” ምናምን እያልን፣ ጥፋታችንን በሌላው ላይ ስናላክክ ዘመናት አለፉ፡፡ ለስህተታችን ኃላፊነት የምንወስደው መቼ ነው? … ‹ሰው› የምንለው ሰው፣ የት ጋ ነው ያለው? … ‹ሀበሻ› የምንለው ሀበሻ፣ ማን ነው? … እኛው አይደለን?
ቅዱስ መጽሐፍ … “ከናንተ መሃል ሃጢአት ያልሰራ እሱ ይውገራት” በማለት የሰጠው ምሳሌ ለምን ይመስልሃል? … በነገራችን ላይ እኛ በሰይጣን እንናደዳለን፡፡ … ሰይጣንን የሚያናድደውስ ማነው?
ሠላም!!!
***
ውድ አንባቢያን፡- ጽሁፉ ከአዲስ አድማስ “የሃሳብ መንገድ” የተሰኘ አምድ ተወስዶ በድጋሚ የታተመ መሆኑን ልንገልጽ እንወዳለን፡፡
የ”ሰላም ኢትዮጵያ” የ25 ዓመት የሙዚቃ ጉዞ
“ሰላም ኢትዮጵያ” የዛሬ 25 ዓመት ገደማ በስዊድን ስቶክሆልም፣ በኢትዮጵያዊው የሙዚቃ ባለሙያ ተሾመ ወንድሙ፣ የተቋቋመ ስመ-ጥር ተቋም ነው፡፡ የተቋሙ አላማም፣ የመላውን ዓለም ሙዚቃ፣ ባህልና እሴት ለስዊድን ማስተዋወቅ ሲሆን፤ በ25 ዓመት ጉዞውም የምእራቡን ዓለም፣ የአፍሪካንና የካሪቢያንን ሙዚቃና ባህል ለስዊድን ሲያስተዋውቅ መቆየቱን አቶ ተሾመ ወንድሙ ያስረዳሉ፡፡ የዓለም ታላላቅ ሙዚቀኞች ስዊድን ስቶክሆልም ውስጥ በሚገኘውና የኖቤል ሽልማት ሥነሥርዓት በሚካሄድበት ‹‹ኮንሰርት ሀውስ›› የተባለ ታላቅ አዳራሽ ውስጥ በሰላም ኢትዮጵያ አማካኝነት ሥራዎቻቸውን አቅርበዋል፡፡ ከሀገራችን አንጋፋ ሙዚቀኞች መካከል ደግሞ አንጋፋዋ ድምጻዊት አስቴር አወቀ፣ የኢትዮ ጃዝ አባት ሙላቱ አስታጥቄ፣ ዝነኛው አርቲስት ቴዎድሮስ ካሣሁን (ቴዲ አፍሮ) እና ሌሎችም በዚህ ሥፍራ ሙዚቃቸውን ማቅረባቸውን ነው የሰላም ኢትዮጵያ መሥራች የሚናገሩት፡፡ ሰላም ኢትዮጵያ ከዚህ በተጨማሪም፣ ‹‹ሙዚቃዊ›› የተሰኘ የሙዚቃ አሳታሚ ድርጅት ከፍቶ የተለያዩ ወጣትና አንጋፋ አርቲስቶችን የሙዚቃ ሥራዎች እያሳተመ ይገኛል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፣ከሰላም ኢትዮጵያ መሥራቹ አቶ ተሾመ ወንድሙ ጋር በተቋሙ አመሰራረት፣ በአጠቃላይ የሥራ እንቅስቃሴውና በሙዚቃ ሙያቸው እንዲሁም በህልምና ራዕያቸው ዙሪያ አነጋግራቸዋለች፡፡ እንዲህ ቀርቧል፡-
==========
እስቲ እራስዎትን ለአንባቢያን በአጭሩ ያስተዋውቁልን?
ተሾመ ወንድሙ እባላለሁ፤ ተወልጄ ያደግኩት አዲስ አበባ ውስጥ ነው፡፡ እስከ 10ኛ ክፍል ድረስ በዳግማዊ ምኒልክ ት/ቤት ነው የተማርኩት፡፡ የሙዚቃ ህይወቴም ከዚህ ት/ቤት ነው የሚጀምረው፡፡ ከልጅነቴ ጀምሮ የሙዚቃ ፍቅር ነበረኝ፡፡ በድሮ ጊዜ በየት/ቤቶቹ የሙዚቃ መሳሪያዎች መጫወት ይቻል ነበርና፣ እኔም ገና የአንደኛ ደረጃ ተማሪ ሳለሁ፣ ክላርኔት የተባለውን የሙዚቃ መሳሪያ በመጫወት፣ የት/ቤቱ ማርቺንግ ባንድ አንዱ አባል ነበርኩኝ፡፡ ባልሳሳት ያን ጊዜ ሙዚቃ ስጀምር፣ 12 ዓመት ገደማ ነበር እድሜዬ፤ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ይሄው እስካሁን በሙዚቃ ውስጥ አለሁ፡፡
ለሙዚቃ ትምህርት ወደ ሩሲያ ተጉዘው እንደነበር ሰምቻለሁ፡፡ እስቲ ስለሱ ትንሽ ያጫውቱኝ?
እንዴት መሰለሽ ልክ አስረኛ ክፍል ጨርሰን እያለ የኢትዮጵያ ባህር ሀይል ሙዚቀኞችን ለመቅጠር ወደ አዲስ አበባ መጡ፡፡ የድሮ ባህር ሃይሎች አስመራ ምፅዋና አሰብ ነበር የነበሩት። ታዲያ ምኒሊክ ት/ቤት የነበርነውን ሙዚቀኞች አስራ ምናምን እንሆናለን ቀጥረውን አስመራ ይዘውን ሄዱ፡፡
መቼ ማለት ነው?
በኢትዮጵያ አቆጣጠር 1973 ዓ.ም መሆኑ ነው፡፡
ከ42 ዓመት በፊት ማለት ነው፡፡ እሺ ይቀጥሉልኝ?
42 ዓመት ሆነው? በስመአብ! ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ባህር ሀይል ቀጠሩን፡፡ ምክንያቱም እኛ ኦልሬዲ ሙዚቃ መጫወት ጀምረን ስለነበር ለእነሱ ቀላል ነው፡፡ አስመራ እንደሄድን የባህር ሃይልን ዲስፕሊን እንድናውቅ ትምህርት ተሰጠንና የባህር ሀይል ሙዚቀኞች ሆንን፡፡ በባህር ሀይል የማርቺንግ ባንድ ሙዚቀኞች ሆነን ስንሰራ እንደገና የምሽት ክበብም ነበር፤ እዛም እሰራ ነበር፡፡ ለማርቺንግ ባንዱ ክላርኔት ለምሽት ክበቡ ባንድ ደግሞ ሳክስፎን ተጫዋች ነበርኩኝ፡፡ ይህ እንግዲህ ከ1973 እስከ 1980 ዓ.ም ለሰባት ስምንት ዓመት ይመስለኛል፣ ካገለገልኩ በኋላ ባህር ሀይል ነፃ የትምህር እድል ሰጥቶኝ ነው ለትልቅ ትምህርት ወደ ራሽያ የሄድኩት፡፡ የገባሁት ራሽያ ውስጥ በዓለም ላይ ትልቅ የተባለ የሚሊታሪ የሙዚቃ ት/ቤት ሲሆን እንዳጠና የተላኩት ደግሞ ‹‹ኮንዳክቲንግ›› ነው፡፡
‹‹ኮንዳክቲንግ›› ማለት ማርቺንግ ባንዱን ከፊት ለፊት ሆኖ የሚመራው ሰው የሚማረው ነው?
ትክክል ነው፤ ማርቺንግ ባንዱን የሚመራው ሰው ነው ትምህርቱ፡፡ እኔ የተላኩበት አላማም ያንን ትምህርት ተምሬ ስመለስ የባህር ሀይሉን ማርቺንግ ባንድ እንድመራ ነበር፡፡ አጋጣሚ ሆኖ ሶስት አመት አካባቢ እንደተማርኩ ኢትዮጵያ ከህወሃት ጋር ከፍተኛ ጦርነት ውስጥ ገባች፤ ጭንቅ ሆነ፡፡ ያን ጊዜ ለትምህርት ወደ ራሺያ የተላኩ ሁሉ ወደ ኢትዮጵያ ይመለሱ ሲባል ግራ ገባን፤ ምክንያቱም ሁሉም ነገር ዝብርቅርቁ ወጥቷል፤ የምናውቀውና የምንወደው ባህር ሀይልም ሰላም አይደለም፤ ብዙ ጓደኞቼም ሞተዋል፡፡ እኔ እንዴት ነው የምመለሰው፤ ጓደኞቼ የሉ ባህር ሀይሉ የለ ብዬ ቀረሁ፡፡
ከዚያስ ራሽያ ቆዩ ወይስ ?
ከራሽያ ወደ ስዊድን ሄድኩኝ፡፡ ስዊድን ሄጄ ህይወትን እንደገና ከዜሮ ጀመርኩኝ፡፡ ይህ እንግዲህ በፈረንጅ በ1990 ዓ.ም ወይም በእኛ 1980 ዓ.ም መሆኑ ነው፡፡
እስኪ በስዊድን እንደገና ህይወትን እንዴት ከዜሮ እንደጀመሩት ያጫውቱኝ?
እኔ ህልሜ የነበረው እዚሁ አገሬ ተመልሼ በተማርኩት ሙያ መስራትና እውቀቴን ማካፈል ነበር። ነገር ግን አዲስ ህይወት በስዊድን ጀመርኩ፡፡ የሚገርምሽ ራሽያና ስዊድን ፍፁም የተለያዩ ዓለማት ናቸው፡፡ በፖለቲካም፣ በባህልም በኑሮም ሆነ በሁሉም ነገር የሰፋ ልዩነት ነው ያላቸው፡፡ ከለመድሽው አካባቢ ሄደሽ ሌላ አዲስ ዓለም ውስጥ ስትገቢ ደግሞ ብዙ የቤት ስራ ይጠብቅሻል፡፡ ኑሮውን፣ አየሩን፣ ባህሉን ለመልመድ ማለቴ ነው፡፡ በአጠቃላይ ግን ስደት በጣም ከባድና አስቸጋሪ ነገር ነው፡፡ ቋንቋውን መማር በራሱ ከባድ ነው፡፡ እኔ ስዊድን ስገባ ቶሎ ብዬ የሀበሻ ማህበረሰብ ውስጥ ነው የተቀላቀልኩት፡፡
የባህል ቀውሱን ፈርተው ነው ቶሎ ሀበሻን የተቀላቀሉት?
አዎ! ራስን የሚመስል አግኝቶ አገር ለመላመድ፣ ሀበሻ ኮሚዩኒቲ ውስጥ መግባቴ ጥሩ ነው፡፡ ህይወትን ለማስቀጠል የሚሰሩትን ሥራዎች በሙሉ ከባርቴንደርነት ጀምሮ ያሉትን ሁሉ ሰርቻለሁ። ከዚያ የሙዚቃ ትምህርት ለመቀጠል ሞከርኩና ትምህርቱ በሙሉ የማውቀው ሆነብኝ፤ ምክንያቱም እኔ ሩሲያ ውስጥ ትልቅ የሙዚቃ ዩኒቨርስቲ ውስጥ ነበርኩኝ፡፡ ነገር ግን በ1996 እ.ኤ.አ አንድ ትምህርት አገኘሁ፤ ‹‹ካልቸር አድምኒስትሬሽን›› የሚባል። ይህ ትምህርት ተሰጥቶኝ ነው ይህ ሁሉ እድል የተከፈተው፡፡ ምክንያቱም እኔ ሁሌም ስዊድንም ከገባሁ በኋላ ወደ ሀገሬ ተመልሼ የመስራት ህልም ነው የነበረኝ። ይህን ለማድረግና ወደ ሀገር ተመልሶ እውቀት ለማካፈል ማወቅም ያስፈልጋል፡፡ የሰለጠነውን አለም እውቀት አንቺ ቀድመሽ ጠንቅቀሽ ካላወቅሽው ለሌላ ማካፈል አትችይም፡፡ ስለዚህ የመጀመሪያ ትኩረቴ የስዊድንን ሲስተም ማጥናት ነበር፡፡ የስዊድን የባህል ዘርፍ እንዴት ነው የተመሰረተው? ከላይ ጀምሮ ምን ይመስላል? ማን ምንድን ነው የሚሰራው? መንግስት ምን አይነት ፖሊሲ ነው ያለው? የመንግስት ፖሊሲ ዋና ሚናው ምንድን ነው? ተቋማት አሉ ወይ? ካሉ ምን ይሰራሉ? ት/ቤቶች አሉ ወይ? የሚዲያ ሚናስ ምን ይመስላል? የሚለውን በሙሉ ለአንድ ዓመት አጠናሁና እ.ኤ.አ በ1997 ዓ.ም “ሰላም ኢትዮጵያ”ን ለመሞከር አቋቋምኩት፡፡
እኔ ስዊድን በሄድኩበት ጊዜ አጠቃላይ የስዊድን ህዝብ ብዛት 9 ሚሊዮን ብቻ ነበር፡፡ ከዚህ ውስጥ 2 ሚሊዮኑ የውጪ ሀገር ዜጎች ናቸው፡፡ የውጭ ሀገር ዜጎችም ይሁኑ ራሳቸው ስዊዲኖቹ ዓለም አቀፍ ነገር ይወዳሉ፡፡ ነገር ግን ያንን ዓለም አቀፍ ነገር ፕሮፌሽናል በሆነ መልኩ ሰርቶ የሚያቀርብ የለም፡፡ እኛ ያደረግነው ምንድነው? የታወቁ ሎካል ቦታዎች ላይ ፕሮፌሽናል ኢቨንት ማዘጋጀት ነው፡፡ ጥሩ ሀሳብና ፈጠራ ካለሽ የፋይናንስም ሆነ ሌሎች ድጋፎች ይደረጉልሻል። እኔን ለየት የሚያደርገኝ ምን መሰለሽ? ከመጀመሪያው ጀምሮ በትክክል ለመስራት ነው ያቀድኩት፡፡ እናም በተጠና መንገድ ፕሮጀክቴን አቀረብኩ፤ በፈጣን ሁኔታ ተቀባይነት አገኘ፡፡
በዚያው አገር ሲስተም ነው “ሰላም ኢትዮጵያ” የተቋቋመው?
ሁሉ ነገሩ በስዊድን ደንብና ሲስተም ነው የተቋቋመው፡፡ ከዚያ ወዲያው ፈንድ ማግኘት ጀመርን። ከዚያም የአፍሪካ፣ ላቲን አሜሪካና የካሪቢያንን ሀገራት ሙዚቃና ባህል ለስዊድን ማስተዋወቅ ዋና ሥራችን ሆነ፡፡ ትልልቅ የሚባሉ ቦታዎች ላይ ኢቨንቶችን ማዘጋጀት ጀመርን። ሌላው ቀርቶ እዚያው ስዊድን ውስጥ ስዊድኖችም ሆኑ ሌሎች የውጪ ሀገር ሙዚቃዎችን የሚጫወቱ አርቲስቶችን ሁሉ መደገፍ ጀመርን፡፡ ይህን ተከትሎ ሚዲያውም ሁሉም አወቀን። የእኛ ኢቨንት በጉጉት የሚጠበቅ ሆነ፡፡ ከዚያ በኋላ መንግስትም ትኩረት ሰጥቶን መስራት ጀመርን፡፡ ጎበዝ ጎበዝ ሰራተኞችን ቀጥረን ትልልቅ ስራዎችን መስራታችንን ቀጠልን ማለት ነው፡፡ ከዚያ በኋላ ከየትኛውም ዓለም ትልልቅና ስመጥር አርቲስቶችን እያስመጣን ማሰራት ቀጠልን፤ ከአፍሪካም ከኢትዮጵያም ጭምር፡፡ አሁን የእኛ ሀገር ትልልቅ አርቲስቶች እነ ቴዎድሮስ ካሳሁን (ቴዲ አፍሮ)፣ አስቴር አወቀ፣ ሙላቱ አስታጥቄና ሌሎቹም በእኛ ስር ነው ስዊድን እየመጡ የሚሰሩት፡፡ የሚሰሩትም በትልልቅ መድረኮች ላይ ነው፡፡ አብሮን ያልሰራ ታዋቂ አርቲስት የለም፡- እነ አልፋ ብሉንዲ፣ እዩ ስዱር፣ አንጀሊ ኪዶ… ስንቱን ልጥቀስልሽ። ትልቁ ሥራችን ይሄ ነው፤ የዓለምን ሙዚቃ ለስዊድን ማስተዋወቅ፡፡ የስዊድን መንግስትም ድርጅታችንን አምኖ ድጋፍ እያደረገልን እዚህ ደርሰናል፡፡
‹‹ሰላም ኢትዮጵያ›› ስዊድን ቢመሰረትም ስራው ዓለም አቀፍ እንደሆነ ነግረውኛል፡፡ ግን ኢትዮጵያ በተቋማችሁ አማካኝነት በስዊድን ምን ያህል ታወቀች? በአጠቃላይ ለኢትዮጵያ ሙዚቃ ያደረጋችሁት አስተዋፅኦ እንዴት ይገለጻል?
ይህን ጥያቄ ለተጠቃሚዎቹ ብታቀርቢ የበለጠ መረጃ ታገኚ ነበር፡፡ የሆነ ሆኖ የመጀመሪያው ነገር እኛ ይህን ስራ ለመስራት ይህን ትልቅ መድረክ ማግኘታችን እድለኞች ነን፡፡ ይህ ማንም የማያገኘው ዕድል ነው፡፡ እውነቴን ነው፤ በስዊድን ሀገር በጣም ትልልቅ ሥራ ከሚሰሩ በጣም ጥቂት የውጭ ሀገር ዜጎች አንዱ ነኝ፡፡ ይሄ ትልቅ እድል ነው። የእናቴም ፀሎት ይመስለኛል፡፡ እና በዚህ ሥራዬ ኢትዮጵያዊ እንደመሆኔ ለየት ያለ ስሜትም አለኝ፡፡ ለእኔ የኢትዮጵያን ሙዚቃ በዚያ ትልልቅ መድረክ ማቅረብ ትልቅ ነገር ነው። ከዚህ ቀደም ተደርጎም አይታወቅም። ሌሎቹም የምር በእኛ ይቀናሉ፡፡ የኢትዮጵያን ሙዚቃ በከፍተኛ ደረጃ በትልልቅ መድረክ አስተዋውቀናል፤ ለአርቲስቶችም እድል ሰጥተናል። እነ ዓለማየሁ እሸቴን፣ እነ ጋሽ ማህሙድ አህመድን ከወጣቶቹም ጭምር 20 ሺህ እና ከዚያ በላይ ታዳሚ ባለው መድረክ ላይ ነው የምናሰራቸው፡፡ የምናዘጋጅበትም ቦታም እዚያው ስቶክሆልም ውስጥ የኖቤል ሽልማት የሚሰጥበት ‹‹ኮንሰርት ሀውስ›› የሚባል ትልቅ መድረክ ላይ ነው፡፡
እንደዚህ አይነት መድረኮች የዚያ ሀገርም ሆነ የውጪው ዜጋ ለኢትዮጵያ ሙዚቃ ያለውን ፍቅር የምናይበት መስታወት ነው፡፡ በተለይ ሀበሻው ደስታውን፣ ኩራቱን፣ አክብሮቱንና ፍቅሩን እየገለፀ ሲያመሰግነኝ፣ ከዚህ በላይ ደስታና እርካታ የለም፡፡ እውነት ለመናገር በዚህ ጉዳይ ከእኛ ይልቅ ሌሎች ቢናገሩ ጥሩ ነበር፡፡ ነገር ግን እኛ በተቻለን መጠን በሙዚቃችን ኢትዮጵያ ያላትን ነገር እያስተዋወቅን ነው፡፡ እውነቱን ልንገርሽ፤ ሀገርሽን ለማገዝ የግድ ፖለቲከኛ መሆንና የፖለቲካ ንግግር ማድረግ የለብሽም፡፡ እኛ በሙዚቃችን ከፖለቲካና ከዲፕሎማሲ ስራ በላይ የሆነ ሥራ እየሰራን ስለመሆኑ በልበ ሙሉነት መናገር እንችላለን፡፡ በዚህ ሥራዬ እንደ ኢትዮጵያዊነቴ ብሎም እንደ አፍሪካዊነቴ እኮራለሁ።
ሌላው የስዊድን መንግስት በህክምና በግብርናና በመሳሰሉት ነገሮች ሌሎች አገሮችን ይረዳል፡፡ እኔም ከ20 ዓመት በፊት ከስዊድን መንግስት ጋር በመነጋገር የባህል ዘርፉን ለምን አናግዝም በሚል የተለያዩ ጥናቶችን መስራት ጀመርኩ፡፡ በእርግጥ የዛን ጊዜ ህልሜ የነበረው አሁን እዚህ የገነባነውን አይነት ፕሮፌሽናል መድረክ መገንባት ነበር፡፡ ምን ማለት ነው? በውጪ ሀገር ያለው ልምድ ወደ ኢትዮጵያ እንዲመጣ፣ ሙዚቃው እንዲያድግና ሙያተኛው በሙያ እንዲጎለብት ማድረግ ነበር፡፡ ምክንያቱም ያን ጊዜ ኢትዮጵያ ውስጥ ፕሮፌሽናል ስቱዲዮ ያለው አበጋዝ ብቻ ነበር፡፡ ሌሎቹ ለመቅረፅ ስቱዲዮ ፍለጋ አሜሪካ ድረስ ይሄዱ ነበር፡፡ እኛ አሁን ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ስቱዲዮ እዚህ ገንብተናል (አሁን እኔና አንቺ የምንነጋገርበት ስቱዲዮ ማለት ነው)። ከዚያ ፕሮዲዩሰሮች እንዲሰለጥኑ እያደረግን ነው። አሰልጣኞችንም ከውጪ እያስመጣን እስካሁን አስራ ምናምን ፕሮዲዩሰሮችን አሰልጥነናል። አሁን ከተማ ውስጥ እነ ይትባረክና ኪሩቤል የተባሉ ልጆችን አብቅተን ሁሉን ነገር ይሰራሉ፡፡ ስቱዲዮ ፍለጋ ውጪ ሀገር መሄድም አያስፈልግም፡፡ ይህ እንግዲህ ከ20 ዓመት በፊት የነበረ ህልም ነው፤አሁን እውን አድርገነዋል። ለኢትዮጵያም ትልቅ አበርክቶ ነው ብዬ አምናለሁ። በውጪ ያለውን እዚህ ለመተግበር አክሰስ ስለሌለ እንጂ እውቀት ጠፍቶ አይደለም። እውነት ለመናገር እኛ ያንን ለማድረግ ሞክረናል፡፡
ወደ ጥናቱ ስመለስልሽ የባህል ሴክተሩ ከላይ እስከ ታች በሚገባ ካልተደረጀ በዘርፉ ለውጥ አይመጣም፡፡ አሁንም ትልቁ ተግዳሮታችን ይሄው ነው፡፡ መንግስት ጠንካራ ፖሊሲ ኖሮት ካልሰራ፣ የተለያዩ ተቋማት ካልተገነቡ፣ የተጠናከሩ የሙያ ማህበራት ከሌሉን፣ የኮሜርሽያል ዘርፉ ጠንካራ ካልሆነና በባህሉ ላይ መንግስት ኢንቨስት ካላደረገ አስቸጋሪ ነው፤ ማደግ አንችልም። በሁሉም ዘርፍ ደግሞ የተማሩና የሰለጠኑ ሰዎች ያስፈልጉናል፡፡ ለምሳሌ በእኛ በሙዚቃ ዘርፍ ብንመለከት በሙዚቃ ስቱዲዮ፣ በፊልም፣ በፕሮዲዩሰርነት፣ በሙዚቀኛነት በትዕይንት ዘርፍ ሁሉም ትምህርት ይጠይቃል፡፡ እኛም ይህን ለማገዝ “ሰላም ኢትዮጵያ”ን አቋቋምን። ይህ በፈረንጆች 2005 ዓ.ም አካባቢ ነው፡፡ እናም በዚያን ጊዜ የተለያዩ የሙዚቃ ማህበራትን ለመርዳት፣ ኮርሶችን ለመስጠትና የመሳሰሉትን ለማድረግ ሞክረናል። አሁን ላይ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚገርም ደረጃ ላይ ነን፤ ትልልቅ ሥራዎችን እየሰራን ነው፡፡ ግን ያን ጊዜም ይሄ ሁሉ ህልም ይታየኝ ነበር፡፡ ይህን ኢትዮጵያ ውስጥ ብናደርገው፣ ይህን ብናከናውን፣ ይሄኛው እዚያ እንዲለመድ ብናደርግ እል ነበር። ያው ለሁሉም ጊዜ አለውና ሁሉም በጊዜው ነው የሚሆነው፡፡ ያኔ የሪኮርድ ሌቭሉ እኛም ጋር ቢመጣ እል ነበር። ድሮ ምስጢር የሚመስለን ነገር አሁን ምንም ምስጢር አይደለም፡፡ እዚያው ስለምኖር አየዋለሁ። እኛ የጎደለን የእውቀት ሽግግሩ ብቻ ነበር። እኔ አሁን የምለው ከላይ ያሉት ሀላፊዎች ወርደው ፕሮዲዩስ ያድርጉ አይደለም፡፡ ነገር ግን ለዘርፉ አመቺ የሆኑ ፖሊሲዎችንና ስትራቴጂዎችን ያዘጋጁ። ይህን ካደረጉ ሌላውን ባለሙያው ደስ ብሎት ይሰራዋል፡፡
ስለዚህ “ሰላም ኢትዮጵያ” በውጪው ዓለም የሚሰራበትን የቴክኖሎጂ ደረጃ አሟልቶ ዘመናዊ የሙዚቃ ስቱዲዮ ገንብቷል። ቃለ ምልልሱንም እያደረግን ያለነው በዚሁ ዘመናዊ ስቱዲዮ ውስጥ ነው፡፡ አሁን ተቋማችሁ እንደ ስልጠና ማዕከልም እንደ ሙዚቃ አምራች ኩባንያም ሆኖ እያገለገለ ነው ማለት ይቻላል?
ትክክል ነው፤ እንደ ስልጠና ተቋምም እያገለገለ ነው፡፡ በተጨማሪም፣ ‹‹ሙዚቃዊ›› በተሰኘው የሙዚቃ ፕሮዲዩስ ማድረጊያ ተቋማችን የተለያዩ የሀገራችንን ባለሙያዎች ትልልቅ ስራዎች ፕሮዲዩስ እያደረግን እንገኛለን፡፡
‹‹ሙዚቃዊ›› በተሰኘው ተቋማችሁ አኒስ ጋቢ የተሰኘ ወጣት የኦሮሚኛ ሙዚቃ ተጫዋችን አንድ ነጠላ ዜማ ቪዲዮ እዚሁ ፕሮዲዩስ አድርጋችሁ ስታስመርቁ ጋብዛችሁኝ ተገኝቼ ነበር። በቅርቡም የአንጋፋው ሙዚቀኛ ዳዊት ይፍሩን በመሳሪያ የተቀነባበሩና ከ45 ዓመት በፊት የተሰሩ ሥራዎችን በሸክላ አሳትማችሁ ከሳምንታት በፊት በጊዮን ሆቴል አፍሪካ ጃዝ መንደር ስታስመርቁም ተመልክቻለሁ፡፡ ከሁለቱ ሌላ ፕሮዲዩስ ያደረጋችሁት ሌላ አልበም ወይም ነጠላ ዜማ አለ?
እስካሁን ፕሮዲዩስ ያደረግናቸውና የወጡ ስራዎች አሉ፡፡ ለምሳሌ ባልከው አለሙ የተባለ ጎበዝ ድምፃዊ ሥራን ሰርተናል፡፡ ‹‹ኢትዮ ከለር›› የተሰኘ አልበምም ፕሮዲዩስ አድርገናል፡፡ ስንታየሁ የተባለች አርቲስት ስራም በእኛው ስቱዲዮ ፕሮዲዩስ ተደርጓል፡፡ ከዚያ በኋላ ነው የአኒስ ጋቢን ስራ ፕሮዲዩስ ያደረግነው፡፡ እንዳልሽው በቅርቡ የዳዊት ይፍሩን አልበም ፕሮዲዩስ አድርገን በሸክላ አሳትመናል፡፡
የሸክላው ሙዚቃ ከሚያዚያ 30 ጀምሮ ለገበያ ቀርቧል። የኦንላይን አልበሙን ጊዮን ካስመረቅንበት ጊዜ ጀምሮ በሁሉም የሙዚቃ መገበያያ ፕላት ፎርሞች ለገበያ ቀርቧል፡፡ የዳዊት ይፍሩ ትንሽ ለየት ያለ ነው፣ በደንብ መግለፅ እፈልጋለሁ። ከዚያ ውጪ ግን በጣም ብዙ ስራቸውን ጨርሰው የሚጠባበቁ አሉ፡፡
ወረፋ ነው የሚጠባበቁት?
ወረፋ ብቻ ሳይሆን ገና ብዙ ሥራ የሚጠይቁ አልበሞች አሉ። ለእሱ በደንብ እየተዘጋጀን ነው፡፡ ለምሳሌ የእውቁ የጃዝ ሙዚቃ ተጫዋች ጆርጋ መስፍን ሥራ ቀጣዩ ፕሮጀክታችን ይሆናል፡፡ ሌሎችም ወጣቶች የሂፕ ሆፕ ሙዚቃ ተጫዋቾች ‹‹አዝማች›› የሚባል ባንድ አለ፣ ‹‹ጎንደር ፋሲለደስ›› የሚባሉ የጎንደር ሙዚቃ ቡድኖችም እንዲሁ አሉ፡፡ በጣም ብዙ ስራ ለመስራት ዝግጅት ላይ ነን፤ነገር ግን እዚህ አገር አንድ ትልቅ ችግር አለ፡፡
ምንድን ነው ችግሩ?
በቦታው ስለነበርሽ የዳዊት ይፍሩን አልበም ስናስመርቅ የተናገርኩትን ሰምተሽኝ ይሆናል። ችግሩ የቅጅ መብት አለመከበር ነው። እዚህ አገር የቅጂ መብት አለመከበር፣ ለሙዚቃ ኢንዱስትሪው ትልቅ እንቅፋት ሆኗል፡፡ ይህ መሰረታዊ ችግር ካልተፈታ አሁንም በስራው ላይ ትልቅ ችግር ይፈጥርብናል። ሌላው ዓለም ይህንን መብት አስከብሮ ባለሙያ ከስራው ተጠቃሚ የሚሆንበትን ሥርዓት አስተካክሏል፡፡ በዚህም አገር የቅጅ መብትን ለማስከበር የተቋቋሙ ድርጅቶች አሉ፡፡ ነገር ግን ተጠናክረው መስራትና ይህን ችግር መቅረፍ አለባቸው፡፡ ይህ እስካልተቀረፈ ድረስ እዚህ ዘርፍ ላይ ኢንቨስት ማድረግ በጣም ይከብዳል፡፡
የሮያሊቲ ክፍያ እንዲኖር፣ ባለሙያው ከልፋቱ እንዲጠቀምና ሙያውም በራሱ በአግባቡ እንዲከበር ነፍሱን ይማርና ስመ ጥሩው የሙዚቃ ባለሙያ ኤሊያስ መልካ ከጓደኞቹ ጋር እስትንፋሱ እስከቆመበት ጊዜ ድረስ ሲታገል እንደነበር ይታወቃል……
እውነት ነው፤በጣም ደክሞ ነበር። እስካሁን ግን በተግባር የታየ ውጤት የለም፡፡ እኛ ከዚህ በፊት ይሄ ነገር እውን እንዲሆን በተለያየ መንገድ ድጋፍ አድርገናል። ለምሳሌ ስልጠና ለመስጠት ሰዎች ከውጭ እያስመጣን፣ ከዚህም ወደ ውጪ እየሄዱ እውቀት እንዲያገኙ ስናደርግ ነበር፡፡ ነገር ግን ጉዳዩ ትልቅ ትብብርና ስራ የሚፈልግ እንጂ በሰላም ኢትዮጵያ ጥረት ብቻ የሚፈታ አይደለም፡፡
ወይም አርቲስቶቹ ሁሌ ስላለቀሱና ስለተቆጩበት ብቻ የሚቀረፍ አይደለም፡፡ ይሄ በመንግስትም ትልቅ ትኩረትን የሚሻ ነው፡፡ ይህን መብት ለማስከበር የተደራጁትን ድርጅቶች በገንዘብም፣ አመቺ ፖሊሲና ስትራቴጂ በማውጣትም ማገዝን ይጠይቃል፡፡ እነዚህ ድርጅቶች በአቅማቸው ትልቅ ትግል ላይ እንዳሉ አውቃለሁ፡፡ እንደኔ እሳቤ ይሄ ነገር የሚሆነው በመንግስትም፣ በህብረተሰቡም ሆነ በሚዲያው ትልቅ ትኩረት ሲሰጠው ነው፡፡ እኔ በተለያዩ ሀገራት ስዘዋወርና የሙዚቃ ኢንዱስትሪያቸው እንዴት እንዳደገ ስመለከት፣ ሁሉም የቅጅ መብት የሚስከብሩላቸውን ጠንካራ ተቋማትና ኮሌክቲቭ ሶሳይቲ የሚባሉትን አቋቁመዋል፡፡ ሁሉም ህግና ሥነስርዓት ሲይዝ ኢኮኖሚውም ያድጋል፡፡ ያለበለዚያ ግን ችግሩ ቀጥላል፡፡
ለምሳሌ የዳዊት ይፍሩን እንውሰድ፡፡ ቅድም የዳዊት ይፍሩ የተለየ ነው በደንብ መግለፅ እፈልጋለሁ ብዬሽ ነበር፡፡ የዳዊት ይፍሩን ሸክላም ጭምር ነው ያዘጋጀነው፡፡ ሸክላ ስናዘጋጅ ከ45 ዓመት በፊት የሰሩትን ካሴት ያውም በደንብ የማይሰማ ካሴት ነው የሰጡን፡፡
እኛ እሱን ወደ ስዊድን ወስደን ድምፁን አጥርተን፣ ወደ ሸክላ ቀይረን፣ ስራቸውን በኢንተርናሽናል የቅጅ መብት ባለቤትነት አስመዝግበን ነው የተቀረፀው። ማነው ያቀናበረው? ማን ነው ያጀበው? የሚለውን ሁሉ ፅፈን ለዘላለም ታሪክ ሆኖ እንዲቀጥል ነው ያደረግነው፡፡ ይሄ እንደ ልምድና እንደ ባህል እንዲቀጥል ነው የምንፈልገው። መጋቢት 30 ነው የተለቀቀው፡፡ በዓለም አቀፍ ገበያ ውስጥ ነው የተለቀቀው። ለውጪዎች ቅድሚያ እንዲያዝዙ ተደርጓል፡፡ ሸክላው በእጅሽ ላይ ታሪክ ሆኖ የሚቀመጥም ነው፡፡ ቀድማችሁ እዘዙ ብለን ማስታወቂያ ስንለቅ ከጃፓን፣ ከእንግሊዝ ከየትና ከየት ትእዛዝ እየመጣ ነው፡፡ ምን አይነት ሙዚቃ ነው እየተባለ፡፡ ይሄ የሚያሳየው ብዙ የሙዚቃ ሀብታችን አለም ሳያውቀው ተቀብሮ ቀርቷል የሚለውን ጉዳይ ነው፡፡ በሌላ በኩል አሁንም እጃችን ላይ ያልተጠቀምንበት ትልቅ ሀብት መኖሩንም አመላካች ነው፡፡
ቅድመ ትዕዛዙ ምናልባት የዓለም አቀፍ ማህበረሰብ ያለውን ፍላጎት ማሳያ ይሆናል ብዬ አስባለሁና እስኪ ስለ ፍላጎቱ በደንብ ያብራሩልኝ?
በጣም የሚገርምሽ እኛ ስዊድንና በዚያ አካባቢ ያለ ትልቅ ኔትወርክ ስላለን አለም አቀፉ ማህበረሰብ ምን እንደሚፈልግ እናውቃለን፡፡ የሸክላው ጉዳይ በጣም እየተፈለገ ነው፡፡ ይሄ የዲጂታል ሁኔታ እንዳለ ሆኖ የሸክላው ህትመት እየተፈለገ ነው፡፡
ከዚህ በተጨማሪ የድሮ ሙዚቃ ጥራት ያለው ነው፤ ቅንብሩ ድምፁ ሁሉ ምንም ሳትነካኪው በራሱ እዚያ ሲያዳምጡት ዋው ነው የሚሉት! ስዊድን ያሉ ሰራተኞቻችን ሲያዳምጡ በጣም ነው የሚደነቁት። ምን አይነት ሙዚቃ ነው እያሉ ማመን ያቅታቸዋል፡፡ አሁን የዳዊት ይፍሩን በዚህ አይነት አሳተምን፡፡ ስራው ሁለት ሶስት ወር ፈጅቷል። ፈረንሳይ አገር ነው የታተመው፡፡ በሁለት ሶስት ሳምንት ውስጥ ከመላው ዓለም የማይመጣ መልዕክት የለም፤ በተለይ ከጃፓን ከጀርመን፣ ከእንግሊዝ፣ ሌላው ቀርቶ ከአሜሪካ ሁሉ ይመጣል። ይሄ እንግዲህ በሁለት ሳምንት ውስጥ ነው፡፡ ይሄ ግን የሚያመላክተው ትልቅ ነገር አለ፡፡ ያልተጠቀምንበት አንድ ትልቅ ሀብት አለን፡፡ እንደ ሙዚቃዊም ይህን ዘርፍ መረዳት እንችላለን፡፡ በአጠቃላይ የሙዚቃ ዘርፍ አለም አቀፍ እንዲሆን እዚህ ያለው መሰረታዊ ነገር መስተካከል አለበት፡፡ ሌላው እኛ ሸክላውን ለውጪ ገበያ ብለን ነው ያዘጋጀነው፡፡ ነገር ግን ባልጠበቅነው መንገድ አገር ውስጥም ከፍተኛ ፍላጎት አለ፡፡ የት ነው የምንገዛው እያሉ ኢሜል እያደረጉ ነው፡፡ በተለይ ወጣቱ የተማረው ክፍል ፍላጎት እያሳየ ነው፡፡ ስለዚህ አገራችን ውስጥ ያለን ሀብት እንደ ቡናችን ለአለም አቀፍ ገበያ ኤክስፖርት መደረግ የሚችል ነው፡፡
ዋናው ነገር መንግስት በዚህ ጉዳይ አረዳዱ ቢስተካከልና ቢገባው ትልቅ ሀብት እጃችን ላይ አለ፤ ልንመነዝረው እንችላለን፡፡ እኔ በዚህ ጉዳይ መለፍለፍ ከጀመርኩ 20 ዓመት ሆኖኛል፡፡ ግን ሰሚ ጠፋ፡፡
ለምሳሌ የጋሽ ሙላቱ ‹‹ኢትዮ ጃዝ›› በውጪው ዓለም እንደ ቡናችን ነው የሚታወቀው፡፡ ስለ ሙዚቃ ስታወሪ ‹‹ኢትዮ ጃዝ›› ይሉሻል፡፡ ከስዊድን ጓደኞቼ ጋር ስናወራ ቡናና ኢትዮ-ጃዝን ነው የሚጠሩት፡፡
ያንን አቅም አልተረዳነውም፡፡ መንግስት ሙያተኛውን አጠናክሮ ቢደግፍ የውጪው ዓለም የደረሰበት ደረጃ ላይ መድረስ ይችላሉ፡፡ እኛም የተለያዩ ጥናቶችን ሰርተን ሰጥተናቸዋል።
‹‹የባላገሩ ምርጥ›› ምርጥ 10 ተወዳዳሪዎች በዕለተ ፋሲካ ይታወቃሉ ተባለ
በባላገሩ ቴሌቪዥን የሚተላለፈው ‹‹የባላገሩ ምርጥ›› ተወዳዳሪዎች ወደ ምርጥ 10 የሚያልፉበት ውድድር ነገ በዕለተ ፋሲካ እንደሚካሄድና ከቀኑ 8 ሰዓት ጀምሮ በቀጥታ ስርጭት ለተመልካች እንደሚቀርብ ተገለፀ፡፡
በውድድሩ ከአንደኛ እስከ አስረኛ የሚወጡ አሸናፊዎች ከ3 ሚሊዮን ብር እስከ 100 ሺ ብር ይሸለማሉ ተብሏል፡፡
የባላገሩ ቴሌቪዥንና ‹‹የባላገሩ ምርጥ›› ባለቤትና አዘጋጅ አርቲስት አብርሃም ወልዴ፣ ከአጋሩ ‹‹ያሆ ኢንተርቴይመንት›› እና ከስፖንሰሩ ጊፍት ሪል እስቴት ሃላፊዎች ጋር በመሆን ባለፈው ረቡዕ በቦናንዛ ሆቴል ውድድሩን አስመልክቶ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥቷል፡፡ በአሁኑ ወቅት 27 ተወዳዳሪዎች ካምፕ ውስጥ ገብተው እየሰለጠኑ መሆኑን የገለፀው አርቲስት አብርሃም ወልዴ፤ ከእነዚህ ውስጥ 15ቱ ስራቸውን አቅርበው ምርጥ አስሩ የሚለዩበት ውድድር ነው በነገው እለት በቀጥታ ሥርጭት የሚከናወነው ብሏል፡፡
የባላገሩ ምርጥ ውድድር መጠናቀቅ ከነበረበት ጊዜ መዘግየቱን የጠቆመው አርቲስት አብርሃም፤ የዘገየበት ምክንያትም የኮቪድ-19 ወረርሽኝና የአገሪቱ አጠቃላይ አለመረጋጋት መሆኑን ገልጿል፡፡
በዘንድሮው የውድድር ዘመን ባላገሩ ምርጥ አሻሽሎ የመጣው ነገር የአሸናፊዎች የገንዘብ ሽልማት መጠን እንደሆነ የገለፀው አርቲስት አብርሃም፤ በውድድሩ አንደኛ ለሚወጣ 3 ሚሊዮን ብር፣ ሁለተኛ ለሚወጣ 2 ሚሊዮን ብር፣ ሦስተኛ ለሚወጣ ደግሞ 1 ሚሊዮን ብር ሽልማት መዘጋጀቱን አስታውቋል፡፡ በተጨማሪም፤ ከአራተኛ እስከ አስረኛ ለሚወጡ ለእያንዳንዳቸው 100 ሺ ብር ሽልማት እንደሚበረከትም አርቲስቱ ተናግሯል።
የገንዘብ ሽልማት አሰጣጡን በተመለከተ በተሰጠው ማብራሪያ፤ አንደኛ ለሚወጣው ከተመደበው የ3 ሚሊዮን ብር ሽልማት፣ ለአሸናፊው በእጁ 1 ሚሊዮን ብር የሚሰጠው ሲሆን፤ 2 ሚሊዮን ብሩ ለሚፈራረመው የአልበም ኮንትራት አጠቃላይ ወጪ ይውላል ተብሏል፡፡ ሁለተኛ ለሚወጣው አሸናፊ ከተመደበው የ2 ሚሊዮን ብር ሽልማት፣ 500 ሺ ብር በእጁ የሚሰጠው ሲሆን፣ 1.5 ሚሊዮን ብሩ ለአልበሙ መስሪያ እንደሚውል ታውቋል፡፡ ሶስተኛ የሚወጣውና 1 ሚሊዮን ብር የሚሸለመው ደግሞ 250 ሺ ብር በእጁ ሲሰጠው፣ ቀሪው 750 ሺ ብር ሦስትና አራት ነጠላ ዜማዎች ይሰራበታል ተብሏል፡፡በውድድሩ ከ1ኛ -10ኛ የሚወጡት አሸናፊዎች በአንድ ላይ የሚሰሩት አንድ የጋራ አልበም እንደሚኖራቸውም በመግለጫው ላይ ተጠቁሟል።ለአሸናፊዎች ሽልማት በአጠቃላይ 8 ሚሊዮን ብር የተመደበ ሲሆን አንደኛ ለሚወጣው አሸናፊ የተመደበውን 3 ሚሊዮን ብር ጊፍት ሪል እስቴት ስፖንሰር ማድረጉ ተገልጿል፡፡ ሁለተኛና ሦስተኛ ለሚወጡ አሸናፊዎች ስፖንሰሮች ይፈለጋሉ ያለው አርቲስት አብርሃም ወልዴ፤ ይህንንም ኩባንያዎችና ተቋማት ስፖንሰር እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርቧል፡፡ በነገው ዕለት ከሚለዩት ምርጥ 10 ተወዳዳሪዎች ውስጥ ወደ መጨረሻው ዙር የሚያልፉት ስድስቱ እንደሚሆኑ የተገለፀ ሲሆን፤ አሸናፊዎች ከሁለት ወር በኋላ በደማቅ ሥነ ስርዓት ይሸለማሉ ተብሏል፡፡
“እድል”፣ “እጣ” እና “ፈንታ”… - በኢትዮጵያ ፖለቲካ ውስጥ
“መወለድ”፣ እንደ ፀሐይ፣ እንደ ዝናብ ነው። የብቃት ወይም የድክመት ውጤት አይደለም። ፀሐይ የሚወጣው፣ ዝናብ የሚወርደው፣… ለሁሉም ሰው ነው። መወለድም እንደዚያው። እገሌ፣ በራሱ ጥበብና ምርጫ አልተወለደም። እከሊት፣ በትጋቷና በበጎነቷ አልተወለደችም። በሞኝነትና በስንፍና ሳቢያ፣ “መወለድህ ተሰርዟል”፤ “መወለድሽ ቀርቷል” ብሎ ነገር የለም። ጥበብና ሞኝነት፣ ትጋትና ስንፍና፣ መልካምነትና ክፋት፣ የእኔነት ክብርና የግል ኃላፊነት፣… ከልደት በኋላ የሚመጡ የማንነት ገፅታዎች ናቸው።
በሌላ አነጋገር፣ የእገሌ ብሔር የእገሊት ብሔረሰብ ተወላጅነት አያሳፍርም፤ አያኮራም። ሃሳብን፣ ተግባርንና ማንነትን አያመለክትም። ለዳኝነት አይቀርብም - ለአድናቆትና ለሽልማት ይቅርና፣ ለወቀሳና ለክስ የሚሆን ነገር የለውም። እና፣ በሌለ ነገር ነው፣… ሰዎች በዘር እየተቧደኑ በጎራ እየተሰዳደቡ የሚወነጃጀሉት፤ ሰዎችን ለጥቃትና ለሞት፣ አገርን ለውድመትና ለትርምስ የሚዳርጓት። በሌለ ነገር መነዳትም ነው፣ ጭፍንነት ማለት። “ቅዠት” የሚለው ስያሜም ትክክለኛ ነው።
የጥንት ታሪክ አይለወጥም። ወደ ኋላ ተመልሰን ማበላሸትም ሆነ ማሻሻል አንችልም። በብዙ ዘመናት በእልፍ አእላፍ ሰዎች አማካኝነት እየተሸበላሸም ሆነ እየተሻሻለ የመጣ ነባር ባህል፣ ወደ ፊት ማሻሻል ይቻል እንደሆነ እንጂ፣ ወደ ኋላ ተመልሰን ልንቀይረው አንችልም። የድሮ ታሪክና ነባር ባህል፣ ለወደፊት ተግባር መማሪያና መነሻ ይሆናል እንጂ፣ መበሻሸቂያና መወነጃጀያ ሰበብ መሆን አልነበረበትም።
የድሮ ዘመን ሰዎች፣ የጥንታዊው ታሪክና ባህል ተዋናዮች፣… በአንዳች ተዓምር አፅማቸው ስጋ ለብሶ ቢነሳ እንኳ፣… አሁን የምናየው ያህል ጭቅጭቅና ንትርክ አይፈጥሩም ነበር። ባልነበርንበት ዘመንና ባልዋልንበት ቦታ፣ በባዶ መፎከርና የክስ እሮሮ ማንጋጋት ምንድነው? የጊዜ መንኮራኩር ሰርተው ወደ ጥንቱ ዘመን ተመልሰዋል እንዳንል፣ የዚያን ያህል እውቀትና ጥበብ ቢኖራቸው እንዲህ በከንቱ የጥላቻ መዓት ለመዝራት የሕይወት ዘመናቸውን የሚያባክኑበት የስድብና የውንጀላ ጊዜ ባልተረፋቸው ነበር።
ይልቅስ፣… በድሮ ታሪክና ባህል ሰበብ፣… ዛሬ ውንጀላና ጥላቻ የሚያራግቡት፣… የጥንት ዘመን ጉዳይ ስለቆረቆራቸው አይደለም። በዚያ ሰበብ ዛሬ በዘመናችን፣ ከድሮ የባሰ ጥፋትና ግፍ የመፈፀም ፍላጎትና ዝግጅት ነው ማለት ይቻላል።
+++++++++++++++++++++++++++
“እድል፣ እጣና ፈንታ”፣… በተለያየ ትርጉም የሚያምታቱና ለጭፍን አስተሳሰብ ተጋለጡ ቃላት መሆናቸው አያጠራጥርም። ነገር ግን፣ በምሳሌያዊ ዘይቤ ቁምነገረኛ ፍሬ ሃሳቦችን ለመጨበጥ መነሻ ቢሆኑልንስ? እስቲ ከኢትዮጵያ ፖለቲካ ጋር እያዛመድን እንያቸው።
እድል ማለት፣… ለክፉም ለደጉም፣ በጊዜውና በቦታው፣ ከናንተ ቁጥጥር ውጭ የሆነ ነገር ማለት ነው? ብትፈልጉም ባትፈልጉም፣ ወደዳችሁም ጠላችሁም፣ የሚለወጥ ነገር አይደለም ማለት ነው።
ወላጆቹን የሚመርጥ ሰው የለም። የመሬት ስበትን፣ በዲሞክራሲያዊ ምርጫ፣ በፓርላማ አዋጅ የመሻር ወይም የማፅደቅ፣ የስበት ኃይሉን የመቀነስ ወይም የመጨመር ስልጣን የለም።
ወደ ኋላ ተመልሶ ታሪክን ማስቀረትና መፍጠር፣ ማሻሻልና ማበላሸት የሚችልም የለም። ስለማይቻልም ነው፣ ለማስመሰል መከራቸውን የሚያዩት።
ካንተ ወይም ካንቺ ምርጫ ውጭ የሆኑ ነገሮች ብዙ ናቸው። የቢሊዮን ሰዎች የእለት ተእለት ውሳኔና ተግባር፣ ካንተ ጥረት ወይም ካንቺ ምርጫ ውጭ ነው። ንፁሐንን የሚያጠቁ፣ በጭካኔ ነፍስ የሚያጠፉ ወንጀለኞች አሉ። አንተ ወይም አንቺ እጃችሁ የለበትም። ወንጀልን ለመከላከልና አጥፊዎችን ለመቅጣት፣ ሕግና ሥርዓትን በትክክል ለማስፋፋት የምትችሉትን ያህል ጥራችኋል ወይ የሚል ጥያቄ ግን፣ በቀጥታ ይመለከታችኋል። የወንጀለኞች ተግባር ውስጥ ግን፣ ቅንጣት ድርሻ አልነበራችሁም።
ነፃነትንና መብትን የሚያከብር ባህል፣ በዚህ የተቃኘ ሕግና ስርዓት የተስፋፋበት ዘመን ላይ ብትወለዱ፣ “መታደል” ነው። ግን የሚያኮራ አይደለም - የናንተ ውጤት አይደለምና። ወንጀለኞችና ነውጠኛ ሽፍቶች፣ ወይም አምባገነን አሰራርና ሕግ የማይገዛቸው ባለስልጣናት የበዙበት ዘመንና አገር ውስጥ መወለድም፣… የናንተ ልማትና ስኬት፣ ወይም ጥፋትና ውድቀት አይደለም። የአጋጣሚ፣ የእድል ጉዳይ ነው ልንለው እንችላለን።
ይልቅስ፣ “ከትናንቱ ባህልና ስርዓት ለመማር፣ ጥሩ ጥሩውን ለመጠበቅና ለማፅናት፣ የወደፊቱን ደግሞ ለማሻሻል ምን አይነት ድርሻ ይኖርሃል? ምን ያህል ድርሻ ይኖርሻል?” የሚለው ነው ዋናው ጥያቄ። ይሄ ነው ያንተና ያንቺ ፈንታ።
የጥበበኞች ድንቅ የእውቀት ግኝትና የፈጠራ ውጤትስ? በአካል ባታውቋቸውም፣ በምርምራቸውና በቤተሙከራቸው ውስጥ ድርሻ ባይኖራችሁም፣… ከአዋቂዎቹ መማር፣ ከሙያተኞቹ ልምድ መቅመስ፣ የቴክኖሎጂያቸውና የምርታቸው ተጠቃሚ ገበያተኛ መሆን ትችላላች። በእርግጥም፣ የጥበበኞች ፍሬ ለብዙ ሰዎች በረከት ይሆናል። መታደል ነው። እውቀትና ቴክኖሎጂ በተበራከተበት አገርና ዘመን መወለድ፣ የሚያኮራ ወይም የሚያሳፍር አይደለም። “አጋጣሚ” ወይም “እድል” ብንለውስ?
አንተስ ምን ሰራህ? አንቺስ ምን ፈጠርሽ? ይሄ የየግል ኃላፊነትና ፈንታ ነው - በግል ምርጫና በግል ጥረት የሚወሰን።
የሌሎች ሰዎች የዛሬ ተግባር ብቻ ሳይሆን፣ የዛሬ ተፈጥሯዊ ክስተቶችም ከእያንዳንዱ ሰው ምርጫ ውጭ ናቸው። የጥንት ታሪኮችና የቀድሞ ተፈጥሯዊ ክስተቶችም እንዲሁ።
በዘመናት የታነፀ ባሕል እንዲሁም የተፈጥሮ ዑደትና ሕግስ?
የመሬት ስበት፣… የሚያኮራም የሚያሳፍርም አይደለም ብለናል። የስንፍና ወይም የጉብዕዝና፣ የበጎነት ወይም የክፋት ውጤት አይደለም። ለሁሉም የሚታደል ነው። ፀሐይ የምትወጣው ዝናብ የሚጥለው፣ ለጥበበኛም ለሞኝም ነው። ለአጥፊም ለአልሚም ያው ናቸው - ፀሐይና ዝናብ።
በዝናብና በፀሐይ ማምረት፣ እንዲሁም መጠለያ መስራት ግን ለሁሉም የሚታደል ጉዳይ አይደለም። መስራትና አለመስራት የሚያኮራ የሚያሳፍር ነው። የመሬት ስበት ተፈጥሯዊ ገፅታዎችን ተምሮ ከዚያም ተመራምሮ ማወቅ፣ በዚያው ልክ ያኮራል። በእርግጥ፣ ጥበበኛ አስተማሪ የማግኘት እና ያለማግኘት ጉዳይ፣ የእድል ጉዳይ ሊሆን ይችላል። ከኒውተን በፊት፣… የስበት ትምህርት ብዙም አልነበረም።
ከ300 ዓመት በፊት የነበሩ ሰዎች፣ የስበት ቀመሮችን የሚያስረዳ መፅሀፍና የሚያስተምር አዋቂ አለማግኘታቸው አያሳፍርም። እኛ ከኒውተን በኋላ መወለዳችንም አያኮራም። በምርጫችንና በጥረታችን የተገኘ ውጤት አይደለም።
ይልቅ እንደየ ዝንባሌያችን በተገቢው መማር አለመማራችን ነው - ከኮራንበትም ካፈርንበትም። በእርግጥ ለመማር መምረጥና ከልብ መትጋት፣ የእያንዳንዱ ሰው ድርሻ ቢሆንም፣ እንደ ልብ ጎበዝ አስተማሪ ይገኛል ማለት አይደለም። በጥንቃቄ የተዘጋጀ የመማሪያ መጽሃፍ፣ እጅ በመሰንዘር ብቻ ከመዳፋችን ማስገባት እንችላለን ማለትም አይደለም። እድሉ ግን ተፈጥሯል። ጎበዝ አስተማሪዎችና ጥሩ መፃህፍት በሌላ ዘመን አልነበሩም። ዛሬ ግን ጥቂት ቢሆኑ እንኳ አሉ።
ከጣርን እናገኛቸዋለን። መፅሐፍና አስተማሪ ፍለጋ ስንጀምር፣ “እጣው ውስጥ እንደ መግባት” ቁጠሩት። ዛሬውኑ በቅርባችን ባናገኛቸው እንኳ፣ ዞር ዞር ብለን ካየን ወዲያውኑ ባይሳካልን እንኳ፤ ውለን አድረን በፍለጋ እናገኛቸዋለን። እጣው ውስጥ ከገባንበት፣ ቀን ቆጥሮ ግራ ቀኝ ዞሮ ይደርሰናል። ወይም እንደርስበታለን።
እቁብ እንደ መግባት ነው። በሚቀጥለው ሳምንት እጣው ባይደርሳችሁ እንኳ፣ መምጣቱ አይቀርም - የተበላ እቁብ ካልሆነ በቀር ማለቴ ነው።
በእርግጥ፣… እድሉ ካለ፣ እጣውም ከደረሰ፣… ጥሩ መፅሐፍ ለማግኘት ወይም እቁብ ለመግባት ስለወሰንክ ብቻ፣ ስኬታማ ባለሀብት፣ አዋቂና ጥበበኛ ሆንክ ማለት አይደለም። እያንዳንዱ ሰው፣ ፍሬያማ ለመሆን ከፈለገ፣ ከእድልና ከእጣ ባሻገር፣ በየፊናው የየራሱን ድርሻ ማከናወን አለበት። የተማረውን ማጥናትና ገቢ መፍጠር፣… የእድልና የእጣ ጉዳይ አይደለም። እነዚህን የግል ኃላፊነቶች የአቅሙን ያህል መወጣት፣ የእያንዳንዱ ሰው ፈንታ ነው።
ይሄኔ፣ እድል፣ እጣ እና ፈንታ ተሟልተዋል ማለት ይቻላል።
ዓለማትና ከዋክብት ተገጣጠሙ ያስብላል።
ሁሉም በዓይነታቸው ተሟልተው፣ በየልካቸው ስክትክት ሲሉ፣… መስመር ሲይዙ፣ አላማ ተሳካ፣ ኑሮ ሰመረ ያሰኛል።
ጥንታዊ ትረካዎች፣ የሰውን ህይወት ከጨረቃ (ከወር) ዑደት ጋር ያመሳስሉታል።
ጨረቃ፣ የወሩ መግቢያ ላይ ትንሸ ሆና ትወለዳች። እያደገች የወሩ መንፈቅ ላይ ሙሉ ትሆናለች። ወደ ወሩ መገባደጃ እያነሰች ትከስማች። የመወለድ፣ የማደግና የማርጀት ዑደት መሆኑ ነው። ዑደቱ እየተመላለሰ ይሸከረከራል - ሁሉም ሰው ላይ።
አንዳንድ ሰባኪዎች፣ ይህን ምሳሌ የህይወትን ወረትነት ለመግለፅ ይጠቀሙበታል። በዘይቤ ለማስረዳትም፣ “ፎርቹን” የተሰኘችውን አምላክ ይጠቅሳሉ። “ቨርቱ” ከሚል ቃል የተዛመደው የአምላኪቱ ስያሜ፣ መዘወር ወይም ማሾር እንደማለት ነው። በምስል ለመግለፅም፣ መዘውር አስይዘው ይስሏታል። ሐውልት ይሰሩላታል።
አንዳንዴ፣ መዘውሩን ታፈጥነዋለች፡፡ የኑሮ መከራዎችን እየደራረበች ያለ እድሜው ታጎሳቁለዋለች፡፡ ወደ እርጅና ትጠመዝዘዋለች። ሲያሰኛትም፣ በተደላደለ ኑሮና በድንቅ ስኬት፣ የሰዎችን ሕይወት ታድሳለች - የያዘችውን መዘውር በመጠቀም። ትርጉሙ፣ የሰው ሕይወት፣ ከሰዎች ቁጥጥር ውጭ ነው ለማለት ሊሆን ይችላል - በጭፍን አስተሳሰብ። የሰውን ሕይወት የሚያሻሽሉ ወይም የሚያበላሹ አጋጣሚዎች ሊፈጠሩ ይችላሉ የሚል መልዕክትም ሊኖረው ይችላል።
በመዘውር፣ ወይም በዑደት ላይ ተጨማሪ እንቅስቃሴ በመጨመር የሰውን ሕይወት የሚገልጹ ሌሎች ጥንታዊ ትረካዎችም አሉ።
የህይወት ዑደት በሁሉም ሰው ላይ ተመሳሳይ እንደሆነ ቢያምኑም፣ ህይወት ማለት ዑደት ብቻ… መሽከርከር ብቻ አይደለም። እየተሸከረከረ ይጓዛል። እየሾረ ይጠቀለላል፤ ይመዘዛል።
ሕይወት፣ እንደ መንኮራኩር እየተሸከረከረ፣ ረዥም ርቀት ይጓዛል፤ ወይም አንድ ቅያስ ሳይሻገር በአጭር ይቋጫል።
ሕይወት እንደ እንዝርት እየሾረ በቀጭን ወይም በወፍራሙ፣ በረዥሙ ወይም በአጭሩ፣ የተለያየ ዓይነት ፈትል ይወጣዋል።
ይህን የሚገልፅ ይመስላል የሶስቱ ወይዛዝርት ትረካ። እህትማማች ናቸው ይባላል። የሰውን እድል፣ እጣና ፈንታ ያዘጋጃሉ፤ ይመዘግባሉ፤ ይዘጋሉ።
የሰው ህይወት እንደ እንዝርት ሆነና፤ አንዷ ታሾረዋለች፤ ፈታይ ናት። “ኮለቶ” ይሏታል።
ሁለተኛዋ የየዘመኑን ፈትል ትመትራለች። በማስመሪያ በመለኪያ ዘንግ ርዝመቱንና እጥረቱን ትመዘግባች። “ለከሲስ” ይሏታል።
ሦስተኛዋ መቋጫውን ትቆርጣለች - አጥሮፓስ ናት።የሕይወት ዑደት፣ ከውልደት እስከ ሞት፣ የዓመታትና የወራት፣ የየእለቱ ውሎና አዳር ተመሳሳይ ተፈጥሯዊ ዑደትና ተደጋጋሚ ዙረት ቢሆንም፤… ይህ ብቻ አይደለም።
የሕይወት መኪና ይጓዛል፤ እንዝርቱ ይፈትላል። ከጉዞው ርቀት ጋር ከፍታውና ዝቅታው፣ ከፈትሉ ርዝመት ጋር ንጣቱና ጥቁረቱ በሁሉም ሰው ህይወት ላይ ተመሳሳይ አይደለም። እንዝርቱ ይሾራል፤ የጋሪው እግር ይሽከረከራል። ነገር ግን ምንም አዲስ ነገር የለም የሚያስብል አይደለም።
የሕይወት ዑደት ከጨረቃ የየወሩ ሂደት ጋር መመሳሰሉ እውነት ቢሆንም፤ ወረት ብቻ ግን አይደለም። ቀንና ሌሊት፤ ነቅቶ መነሳት፤ ተኝቶ ማረፍ፤ ነባር እውቀትና አዲስ ነገር ማየት፤ … እንደጨረቃ ዑደት ከወር ወር ያው ነው። አይለወጥም።
ነገር ግን፣ መሽቶ ሲነጋ ተኝተን ስንነቃ በየቀኑ እንደ ህፃን አንሆንም። በየቀኑ አእምሮ በላጲስ እየተፋቀ ሀሁ ብለን ከባዶ አንጀምርም። እያፈረሱ መገንባት አይደለም። በየቀኑ ሽቅብ እያንከባለሉ ከኮረብታው ጫፍ አናቱ ላይ ለመድረስ መውተርተር፤ ተመልሰው ቁልቁል እየተንሸራተቱ መውረድ፣ የደከሙበት ስራም ቁልቁል እየተንከባለለ ወደ ትናንትናው መመለስ አይደለም-ሕይወት።
በእለታዊውም ሆነ በዓመታዊው ዑደት የተሰራውን ቁም ነገር ከንቱ እንዳይሆን መጠበቅ፣… የትናንቱን እየተንከባከቡና እያደሱ፤ ተጨማሪና የተሻለ ቁምነገር ማከናወን… በዚህ መንገድ ሲገለፅ፣ የሰው ህይወት የዑደትና የሂደት፣ የነባርና የአዲስ፣ የአላማና የውጤት ገጽታዎችን አዋህደን እንድናይ ይረዳናል።
ተፈጥሯዊ እውነታን፤ ተመልሰን የማንቀይራቸው የዘመናት ታሪኮችንና የትናንት ተግባራትን፣ በረዥም ጊዜ የተዋቀሩ ልማዶችንና ዝንባሌዎችን፣… ከዛሬ የስራ እቅድና ድርጊት፣ ከዛሬ ክስተቶችና ከአዲስ መረጃዎች፣… ከሕይወት ዘመን አላማና ምኞት፣ ዘመን ከማይገድበው የስነ ምግባር መርህና ከሩቅ ራዕይ ጋር ማዋሀድ፣ ትልቁ የህይወትና የጥበብ ምስጢር ነው።
ተፈጥሯዊውን እውነታና ዑደት በአወንታ መቀበል እንጂ ሌላ አማራጭ የለም። በዚያ ላይ ጥፋትም ልማትም አይደለም። በዚያ ላይ የክፋት ወይም የመልካምነት ውጤት አይደለም።
አያስቀጣም፤ አያሸልምም። አያኮራ፤ አያሳፍርም። በሰው ምርጫና ተግባር አማካኝነት የመጣ አይደለም- ተፈጥሯዊ እውነታ።
መወለድም የምርጫ ጉዳይ አይደለም።
የጥንት ታሪክና በረዥም ዘመን የተፈጠረ ባህል፤ የእልፍ አእላፍ ሰዎች ውጤት ነው- አውቀውም ተሳስተውም፣ በድክመትም በብቃትም፣ ተፀፅተው በተሻሻሉ እጥፊዎችም፤ ፅናታቸው እየላላ በተበላሹ አልሚዎችም፤ በብዙ አይነት ሰዎች፤ የተገነባ፤ የተሸረሸረ፣ የተጠገነ፣ የተጎሳቆለ፣ እየተሻሻለ፣ እየተበላሸ… ብዙ እያየ የመጣ ነው- ነባር ባህል፤ የጥንት ታሪክ።
ወደኋላ ተመልሰን ልናሻሽለው ወይም ልናበላሸው ግን አንችልም። ልንማረርበት ግን እንችላለን። የወደፊት ታሪክንና ባህልን የማሳመር እድል አለ። ከጥንቱ ታሪክ በመማርና ነባሩን ባህል በመጠቀም የወደፊት ሕይወትን ማሻሻልና ማነፅ ነው የዘመናችን ሕያዋን ፈንታ።
የጥንቱን ታሪክ ዛሬ ማዕረግ ሰጥተን ልንሸልመው ፍርድ ቤት ልናቀርበው አንችልም። በነባሩ ባህል ማፈርና መኩራት፤ አይገባም። ወደኋላ ተመልሶ ነባሩን ባህል መቀየር የሚችልም የለም። ያማ፣ የጥንቱ ዘመን ሰዎች ፈንታ ነው። ወደኋላ ተመልሶ በራሱ ምርጫ ለመወለድ እንደመሞከር ነው።
የሰው ክብሩና ውርደቱ፣ ማንቱና ኃላፊነቱ፣… በሆነ ዘመን በሆነ ባሕልና አገር ውስጥ መወለዱ አይደለም። ያማ የሌሎች ሰዎች ስራ ነው። ከተወለደ በኋላ ነባሩን ባህል ተጠቅሞ በሕይወት ዘመኑ ምን ፋይዳ ሰራ? ምን አይነት ብቃትና ስብዕናን ተቀዳጀ? የሚሉ ጥያቄዎች ናቸው የእያንዳንዱ ሰው ፈንታና ድርሻ። ማፈርና መኩራ መምጣት ያለበት ከግል ኋላፊነትና ፈንታ ጋር ነው።
የሚሄድ ዝሆን ስር ነቅሎ ሲበላ የሚኖር ዝሆን ቀንበጡን ይበላል
አጼ በካፋ አንድ በጣም የሚወዱት ለማዳ በግ እንደነበራቸው ይነገራል። በጉ ቀላዋጭ ስለነበር እንዳይቸገር ተብሎ አዋጅ ወጣለት። አዋጁም በደረሰበት ያሻውን እንዲበላ የሚያዝ ሲሆን፤ ያ ካልተደረገለት ግን ማንም ቢሆን ቅጣት እንደሚጠብቀው ይገልጻል። ሰው ግን ተማረረ። በጉ ማን አለብኝ ብሎ የተሰጣ ስጥ፣ ለወፍጮ የቀረበ እህል አልተርፈው አለ። እንዲህ እያደረገ አገሬውን አስለቀሰ። አንድ ቀን አንድ ደብተራ ቤት እግር ጥሎት ገባና የመጨረሻው ሆነ። ደብተራ ሆዬ በሩን ጥርቅም አድርጎ ዘግቶ ቀላዋጩን የንጉስ በግ አርዶ ቅርጥፍ አድርጎ በላው። አፄ በሁኔታው በሽቀው የእኔን በግ የሰረቀው ሰው የገባበት ገብታችሁ ያዙት አሉ። ያ ደብተራ ግን አርዶ መብላቱ አልበቃ ብሎት የበጉን ቆዳ በብራና መልክ ፍቆ እዚያ ብራና ላይ “የንጉሱን በግ አርጄ ጣፍጦኝ የበላሁት እኔ እራሴ ነኝ!” ብሎ ጽፎ የብራና ቁራጮችን በድብቅ ሄዶ በአደባባይ ሰቀላቸው። ነገሩ ንጉሱ ጆሮ ደረሰ። እጅግ አድርገው ተበሳጩ! መደፈራቸው የባሰ አንጀታቸውን አቃጠለው! “አሁን ብልሃት መዘየድ አለብኝ። ይሄ ሌባ የዋዛ አይደለም ማለት ነው።” ብለው አንድ መላ መቱ። “የተመዘነ ወርቅ አምጡና ከአደባባዩ እስከ አውራ ጎዳናዎቹ ድረስ በሚስጥር በስሱ በትኑት። ከዚያም እናንተ ከአካባቢው ራቅ ብላችሁ በአይነቁራኛ ጠብቁ። የለመደች ጦጣ ሁልጊዜ ሽምጠጣ ነውና ልማደኛ ሌባ ሲመጣ እጅ ከፍንጅ ያዙት።” ደብተራ ሆዬ የተጠመደ ወጥመድ እንዳለ ስለገባው አዲስ ጫማ አሰፋፍቶ ሶሉን ሰም ቀባውና ወርቁን እያጣበቀ በመንገዱ ሁለት ሶስቴ ከተመላለሰ በኋላ መጭ አለ። በሰሙ ብዙ ወርቅ እያጣበቀ አንስቷል። ይህንን ቤቱ ወስዶ እያራገፈ ወርቁን አከማቸ።
ማታ “በሉ ወርቁን መዝኑት” አሉ አፄ። ቢመዘን ተሟጦ ተሰርቋል። መጉደሉን ሲሰሙ አፄ እጅግ በገኑ። ጠባቂዎቹ አንድም ሰው ጎንበስ ብሎ እንዳላነሳ አስረዱ።
ንጉሱ ግራ ገባቸውና ጠንቋዮች አስጠሩ፤ ሌባው የት እንደሚኖርና አሁን የት እንዳለ ጠየቋቸው። “እገሌ አፈር ላይ ጠይቁ” አሏቸው ጠንቋዮቹ። ደብተራው ግን ሲጨንቃቸው ምን እንደሚያደርጉ ቀድሞውኑ ጠርጥሮ ኖሮ አፈር እየለዋወጠ አልገኝ አለ። ንጉሱ ይብሱን ብሽቅ አሉና ሌላ ዘዴ ቀመሩ። ግብር አግብተው ደብተራ፣ አለቆችና ተማሪዎች አንድም እንዳይቀሩ አዘዙ። “በሰከሩ ጊዜ አንዱ ምስጢሩን መተንፈሱ ስለማይቀር፤ ያኔ ሲተኛ ጠብቆና ከጆሮው ትንሽ ቀንጥቦ ጠዋት ጆሮው የተቀነጠበውን ሰው ፈልጎ መያዝ ነው። አለቀ።” እውነትም ደብተራ ሆዬ በመጠጥ ላይ ንጉሱን እንዴት ጉድ እንደሰራቸው ለጓደኛው ሲያጫውት ተሰማ። ሰክሮ ሲተኛ ጆሮውን ተቀነጠበ። ከስካሩ ሲነቃም እንደተታለለ ገባው። ስለዚህ የተጋደሙትን ተማሪዎችና ደብተራዎች እያንዳንዳቸውን ጆሮአቸውን እንደተኙ ቀነጠባቸው። የደብተራውን ጆሮ የቀነጠበው ባለሟል ሽልማቱን ለመቀበል ወደ ንጉሱ ሄዶ የሆነውን ተናገረ። ንጉሱ ሌቱ አልነጋ ብሏቸው እንደጓጉ አደሩ። ጠዋት ግን ተማሪው ሁሉ ጆሮውን መቆረጡን ሲያዩ አንጀታቸው እርር አለ። ወሬውን ያመጣውን ባለሟል ጠርተው “የዚህን ሁሉ ሰው ጆሮ ቁረጥልኝ ብየሃለሁ ወይ!” ብለው ተቆጡት። “ኧረ እኔ የአንድ ተማሪ ለምለም ጆሮ ብቻ ነው የቆረጥኩት።” ሲል መለሰ። ንጉሱም “አሁንማ አጅሬ ስለነቃብህ አገሩን ሁሉ ጆሮውን መደመደው።” በብልሃቱ ተደነቁ። እንዲህ ያለውን ብልህና ጎበዝ ሰው ከመቅጣት መሾም መሸለም ይበልጣል! ለመንግስት ይጠቅማል ብለው፤ ሲያበቁ አዋጅ አሳወጁ። “በጌን የበላህ ደብተራ ምህረት ተደርጎልሃል! እንደውም ሸልሜ እሾምሃለሁ እኔ ነኝ በል!” የሚል ትዕዛዝ ሰጡ። ይሄኔ ደብተራ ሆዬ እየተጀነነ ብቅ አለ። ከመጀመሪያ እስከ መጨረሻው ምን እንዳደረገ ለንጉሱ በዝርዝር አስረዳ! ንጉሱም አሳማኝ ቃሉን ተቀብለው ሹመት ሰጡት!
***
ንጉስ ያለበት ሃላፊነት እጅግ ትልቅ ነው። ንጉስ የመሪ፣ የሃላፊ፣ የሚንስትር፣ የአለቃ ምሳሌ ነው። ሁሉም ለበጌ ታዘዙ፣ በጌን መግቡ፣ በጌን አኑሩ ባለ ቁጥር ህዝብ እየተሽቆጠቆጠ ካስተናገደ በጉም ማን-አለብኝን ይቀጥላል፤ ባለበጉም የህገወጥና የአዛዥ ናዛዥነት ባህሪውን እያስታመመ በእልክና በንዴት ወደባሰ ጥፋት እንዲያመራ ይሆናል። እንዲህ ባለው ስርዓት ውስጥ ለአንድ ወቅት ያህል “ታላቅየው ሲመቸው ታናሽየው ሳይድህ በእግሩ ይሄዳል” እንደተባለው ሊሆን ይችላል። ውሎ አድሮ ግን በጉን ጨክኖ የሚበላ፣ በልቶም አድራጎቱ ትክክል መሆኑን በጽሁፍ የሚያኖር ብልህ ዜጋ በተፈጠረ ጊዜ፣ ባለበግ ከፉከራና ከያዙኝ- ልቀቁኝ ያለፈ አቅም አይኖረውም። አባትና ልጅ አውራሽና ወራሽ ናቸው። አውራሽ እሚያወርሰውን ሃብትና ንብረት በንፉግነት ያከማቸ፣ በሙስና፣ በኢ-ፍትሃዊ ምዝበራ፣ በማናለብኝና “የአገር ባለውለታ እኔ ብቻ ነኝ” በሚል አንድም በካሳ አንድም በሳንሳ የዘረፈ ከሆነና፤ ወራሽም “በአባቴ ንብረት ምን አገባችሁ፤ ባለጊዜ ነኝና ባፈሰው-ብዘራው ምን ጥልቅ አደረጋችሁ፤” የሚል ከሆነ፤ ሀገር ሁለት ጊዜ ትበደላለች ማለት ነው። አበው አንድ አባባል አላቸው፡-
“የንፉግ አባትን ገንዘብ አባካኝ ሲዘራው
አባቱ ከራሱ በቀር ወዳጅ አልነበረውም።
ልጁ ግን ከራሱ በቀር ጠላት የለውም።”
ከራሱ በቀር ወዳጅ የሌለውና ከራሱ በቀር ጠላት የሌለው መሆን የሁለት ጥፉዎች ማለትም የባለበግና የበግ፣ የሐዋርያና የደቀ-መዝሙር፣ የሚንስትርና የምክትል ሚንስትር፣ የፖለቲካ አዛዥና በኩር ካድሬ፣ የበላይ በላይና የበላይ ተከታይ ታሪካዊ ገጽታ ነው። በታሪክ በተደጋጋሚ እንደታየው ወዳጅ ለማፍራትም ሆነ ጠላት የመቀነስ ጊዜው ሳይመሽ በፊት መሆን ይገባዋል። ምክንያቱን ሸክስፒር በኦቴሎ አንደበት እንደገለጸው፤
“ነበርን ማለት ግን ከንቱ ነው፣ ተውነው መጀነን በቅቶን
ጉራ መንዛት መዘባነን፣ የሚያዛልቅ ዘዴ ባይሆን!” የሚባልበትን ሰዓት ማፋጠን ይሆናል።
በርካታ ወገናዊነት የተጠናወታቸው ድርጊቶች፣ ንፉግነት የተጫናቸው “የዲሞክራሲያዊ ተሳትፎ” ጥሪዎች፣ እንዲሁም የመድረኬን አትንኩ ዛቻና ማስፈራሪያዎች፤ ቀን የጣለ ለታ፣ “የተያዘ ዓሳ በገዛ አንገቱ ይንጠለጠላል።” እንዲል መጽሐፍ በታሪካዊ ማስረጃነት የሚቀርቡና የሚጠቀሱ ዛሬ ባለሙሉ ስልጣን ሆነው በጉልበተኝነት የፈረዷቸው ፍርዶች ናቸው። የህብረተሰብ ሂደት አይመለሴ- አይሻሬ ነው። (Irreversible and Irrevocable እንደማለት) ከቶውንም “ፉርሽ ባትሉኝ!” የማይባልበት ነው! ያለበቂ ጥናት የሄድንበት መንገድ የጠለፍነው ውሃ፣ የገደብነው ግድብ፣ ዛሬ የምናቁረው ውሃ፣ ያወጅነው ያልተተገበረ አዋጅ፣ የይድረስ ይድረስ ውጤት-ተኮርነት፣ በቀን ሶስቴ ከመብላት በቀን ሶስቴ ፊታችንን ወደመታጠብ የተሸጋገርንበት ኢኮኖሚያዊ ምጸት፣ በሯጮቻችን ፍጥነት የመሰልነው ፈጣን እድገት ወዘተ ሁሉ የታሪክ መተዛዘቢያዎች የሚሆኑት ያለስክነት ለመጓዛችንና የተገቢው ሰው በተገቢው ቦታ መርህ በወገናዊነት በመታጠሩ ነው።
በታሪክ በተደጋጋሚ እንደታየው ህብረተሰብን በመሪነት ወደፊት ያራምዳል የተባለ የፖለቲካ ድርጅት ወይም ፓርቲ በቀሰቀሰው አውሎ ነፋስና ጎርፍ ራሱ እየታፈነ፣ እራሱ እየተጠለፈ፣ የገዛ ህዝቡ እንቅስቃሴ ሲያጥለቀልቀው ግንባር ቀደም (Vanguard) የተባለው ጭራ-ተጓዥ (Tailist movement) እየሆነ አገር ያለመሪ ስትዋልል፣ የቀናው ባለጊዜ ደግሞ በተራው ወንበሩን ሲረከብ፤ ሲረካከብ፤ ብዙ ዘመን አሳልፈናል። ከዘመነ መሳፍንት እስከ ዘመነ ሊቃነ-መናብርትና ዘመነ ፕሬዝዳንት፤ ድኸን፣ ተንፏቅቀን እዚህ ደርሰናል። ባለበጉና በጉ እከክልኝ ልከክልህ ሲባባሉ፣ ህዝቡም አንዴም በምሬት፣ አንዴም በቁጭት የበግ መጫወቻ ሆኜ ቀረሁ ሲል፣
“አርኮም ይሄድና ሊሬውም ያልቅና
ያስተዛዝበናል ይሄ ቀን ያልፍና!” እያለ ሲዝት ወይም ደግሞ ወረት አላፊ ነውና ልስማማ ልደራደር በሚል፤
“በትንሽ መለኪያ ይጠጣል አረቄ
በርታ አገሩ ገባ ከባልሽ ታረቂ” ብሎ እየሸነቆጠ፣ መጨረሻ ሲመረውም
“አስረው ደበደቡት ያን የዝሆን ጥጃ
ዛሬን ደስ አላቸው የነገውን እንጃ!” ሲል፤ አሊያም ደግሞ ተስፋውን ጭምር እየተራበ በአይነ-ስውሩ ለማኝ ቃና፤ “ያውና እዚያ ማዶ ብርሃን ያድላሉ
አሁን እኔ ብሄድ አለቀ ይላሉ” እያለ ጉዞ-ብሶቱንና ጉዞ-ፍትሃቱን ያካሂዳል።
የጠፋው ጥፋት ካላሳዘነንና ካልጸጸተን፣ ነገም እንድገመው አንድገመው ዋስትና ካልሰጠን፣ “ሆ!” ብለን አቅደን “ሆ!” ብለን ሳንተገብረው ዕድሜያችንን ለስብሰባ አድባር ገብረን የምንከርም ከሆነና ጥቂት ጥቂት የተግባር ብልጭታ የሚያሳየውን የህብረተሰብ ክፍል ከቁጥርም የማንጽፈው ከሆነ፤
“የሚሄድ ዝሆን ስር ነቅሎ ሲበላ
የሚኖር ዝሆን ቀንበጡን ይበላል” ከማለት የተሻለ ቋንቋ ለጊዜው አናገኝም!
መልካም የትንሳኤ በዓል!!
የመልካ ጀብዱ ኢንዱስትሪያል ፓርክ ሊገነባ መሆኑ ተገለፀ
የመጀመሪያው ዙር የሲሚንቶ ፋብሪካ ግንባታ ስምምነት ተፈጽሟል
በድሬዳዋ ከተማ የኖራ፣ የሲሚንቶና የብረት ፋብሪካዎችን ያካተተ የመልካ ጀብዱ ኢንዱስትሪያል ፓርክ በ540 ሚሊዮን ዶላር ወጪ ሊገነባ መሆኑ ተገለጸ።
ግንባታውን የሚያከናውነው የቻይናው ሲኖማ ኢንተርናሽናል ኢንጂነሪንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ ነው። በ106 ሄክታር መሬት ላይ የሚገነባውን የመልካ ጀብዱ ኢንዱስትሪያል ፓርክ የመጀመሪያ ምዕራፍ ግንባታ ለማስጀመር ናሽናል ዌስት ኢንተርናሽናል ሆልዲንግ ከሲኖማ ኢንተርናሽናል ኢንጂነሪንግ ሊሚትድ ጋር ባለፈው ማክሰኞ ሚያዝያ 3 ቀን 2015 ዓ.ም በስካይላይት ሆቴል ስምምነት ተፈራርመዋል።
ናሽናል ዌስት ሆልዲንግ፤ አገር በቀሉ ኢስት አፍሪካ ሆልዲንግና የቻይናው ዌስት ኢንተርናሽናል ሆልዲንግ በጋራ ጥምረት የሚሰሩበት ግዙፍ ኩባንያ ሲሆን በሰሜን ሸዋ ዞን በለሚ ከተማ በርካታ ፋብሪካዎችን የያዘውን እና በ600 ሚሊዮን የአሜሪካ ዶላር የሚገነባውን የለሚ ኢንዱስትሪያል ፓርክ ግንባታ በታቀደለት ጊዜ እየገነባ እንደሚገኝም ይታወቃል።
የናሽናል ዌስት ሆልዲንግ ኩባንያ ዋና ሥራ አስፈጻሚ ብዙአየሁ ታደለ (ዶ/ር) እንደገለጹት፤ አጠቃላይ ግንባታው 540 ሚሊዮን ዶላር የሚፈጅ ሲሆን፤ የመጀመሪያ ምዕራፍ የሲሚንቶ ፋብሪካ ግንባታ 243 ሚሊዮን ዶላር ወጪ ይደረግበታል ተብሏል።
የኢንዱስትሪ ፓርኩ ግንባታ ሲጠናቀቅ በዓመት 700 ሺህ ቶን የማምረት አቅም ያለው የብረት ፋብሪካ፣ በቀን 1ሺህ ቶን የማምረት አቅም ያለው የኖራ ፋብሪካ፣ በዓመት 3 ሚ.ቶን የማምረት አቅም ያለው የሲሚንቶ ፋብሪካና ለተገጣጣሚ ቤቶች የሚውል ኮንክሪት ማምረቻ ፋብሪካዎችን የሚያካትት ሲሆን፤ ለ5ሺ ያህል ዜጎችም የሥራ ዕድል ይፈጥራል ተብሏል።የመልካ ጀብዱ ኢንዱስትሪያል ፓርክ ግንባታው ተጠናቅቆ በሙሉ አቅሙ ማምረት ሲጀምር በዓመት ከመቶ ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ ማስገኘት የሚችል ግዙፍ ፕሮጀክት መሆኑም ተገልጿል።
መልካ ጀብዱ ለዚህ ፕሮጀክት ግንባታ የተመረጠበትን ዋና ምክንያት ሃላፊዎቹ ሲያስረዱም፤ በዚህ የኢንዱስትሪያል ፓርክ ውስጥ በሚገነቡ ፋብሪካዎች የሚመረቱትን ምርቶች ለአጎራባች አገራት ገበያ ለማቅረብ ታቅዶ የተነደፈ እንደመሆኑ መልካ ጀብዱ ለታቀደው የኤክስፖርት ገበያ ለጅቡቲና በርበራ ወደብ ቅርብ መሆኑ፣ አካባቢው ላይ ያለው የጥሬ ዕቃ ክምችት ጥራትና ብዛት እንዲሁም ከወደብ ጋር የሚገናኝ የባቡር መስመር መኖሩ ተመራጭ አድርጎታል ብለዋል።
ከሶሻል ሚዲያ በጨረፍታ
እስቲ ስለ ሞት እናውጋ
አቈልቊዬ ፡ ባይ ፡ መሬቱን ፡
ቈስሎ ፡ አገኘሁት ፡ እግሬን ፡
ምን ፡ አሳዘነኝ ፡ ለእግሬ ፡ ቊስል ፡
ስሄድ ፡ እኖር ፡ ይመስል፡፡
(ከብላቴን ጌታ ማኅተመ ሥላሴ ወልደ መስቀል
ሞት በስሙ ኗሪ ነው፡፡ ሶምሶን ሹሩባው ላይ ሀይል እንዳለው ሁሉ ሞትም ሀይሉ ስሙ ላይ ነው፡፡ ደህና ስም አጥፊ አጥቶ ይህ ሁሉ ዘመን ፋነነብን እንጂ፡፡ አንዳንድ ዘመን አለ ሞት ስሙ የሚገንበት፡፡ ሞት ስሙ ሲገን ለሞት የብልፅግና ወቅት ነው፡፡ ይሄንንም የኛን ዘመን የሞት የልምላሜ ዘመን ነው እላለሁ፡፡ ከተፈጥሮ ግብሩ በዘለለ በሰዎችና በተፈጥሮ ክስተቶች እየታገዘ ስሙን በየሜዳው የፃፈበት ለሰው የመከራ፣ ለሞት የተድላ ወቅት ነው፡፡ ሞትን መረሳት እንደሚገድለው እናምናለን፡፡ ምክንያቱም በስሙ ያለ ነዋ፡፡ ካልተጠራ ይሞታል፡፡
የዚህ ፅሑፍ አላማ፣ ሞት ቅጥራችንን እየዞረው ከሚኖር ከዚህ ዘመን ሰው ጋር፣ እንደው ሞታችን እርግጥ ቢሆን እንኳ፣ ሞትን እንዴት ባለ መንገድ ነው ማስተናገድ ያለብን የሚለው ላይ ለመምከር ነው፡፡ መቼም ከላይ የገባንባት መተከዣ መዲና ሳትገልጠን አትቀርም የሚል እምነት አለን፡፡አንድ እየተባለለት ነው አጥርም የሚወድቅ፣ እናም፣ እስኪ ሞትን ለመጣል ባንችል ለመነቅነቅ አንዳንድ ጉዳዮችን እንይ፡፡
ፈራና አሁንስ፣ ፈራን አቦ! ፈረንጆቹ አስቦኩን፡፡ እንዴት ያሉ ውለታ ቢሶች ሆነዋል አንተ፣ A living dog is better than a dead lion. ከሞትክ አትረባም ማለታቸው ነው አይደል? ቁርጣችንን ንገሩን እንጂ ጎበዝ! ይሄ በአንበሳ የሰማነው ጉዳይ ሰውም ላይ ይሰራ ይሆን? ከሞተው ሰውስ ድመቱ ትሻላለች፣ ቢያንስ ከአዋኪ አይጥ ታሳርፋለች ማለት ይሆን? ጉርብትናውስ? ፍቅሩስ? ፅዋውስ በአንድ ሽክና አፍ ገጥመን የጠጣነው? ሞት ሲመጣ ሁሉ ገለባ ነው ማለት ነው? በቃ በቃ ሁሉ እንዲሁ ባክኖ ቀሪ ነው? ይህ ማለት አንበሶቹ የታሪክ ጀግኖቻችን ውኃ በላቸው ማለት ነው? ወይስ ለነሱ ሲሆን የትርጉም ማሻሻያ እናደርጋለን? ኸረ ፈራን ጎበዝ! ኸረ የዚህን የሞት ነገር አንድ በለን ክንዴዋ!
አንድ!
ሞት የእግዜር እንግዳ ነው፡፡ ሰው ደግሞ በስነ ፍጥረት ባህሪው እንግድነት ስላለበት በእንግዳ የሚጨክን አንጀት የለውም፡፡ (እንስሳት ምድር ላይ በመንፈላሰስ በአምስት ቀን ይቀድሙን የለም ወይ፣ ያ ማለትስ የእንስሳት ሀገር ሰው ነን ማለት አይደለም ወይ፣ ነው እንጂ ጎበዝ እየተማመንን)
አያ ሞት እንግዳ ነው ብለናል፡፡ በር ይቆምና ‹‹ የመሸበት የእግዜር እንግዳ ›› ይላል፡፡ አቤት ድምፁ እንዴት ያስፈራል፡፡ ፍርሃት ደግሞ ሞት የሚገባበት ቀዳዳ ነው፡፡ ሰው ይሄን ሲሰማ፣ አንድም በፍርሃት ሁለትም በብድር መላሽነት በር ይከፍታል፡፡ ሞት ይገባል፡፡ ሲገባ ያኔ የሞት እንግድነት ያበቃል፡፡ ምክንያቱም ዐይን ያወጣ ባለጌ ነዋ፡፡ ሰዎች ሆይ ሞትን ከደጅ መልሱት፡፡ በራፋችሁ ቆሞ ሲለምን እንዲህ በሉት፣
‹‹… ቦታውን ሁሉ ሕይወት ሞልቶታል፣ ለሞት የሚሆን ስርፋ የለም ››
ፃድቁ ላዖ ሱም ረቡዕ በሚፀለይ ውዳሴው ይህንኑ ነው ያለው (መቼም ስሙ ሲነሳበት እንዴት ብሽቅ እንደሚል፣ አያ ሞት)
‹‹… He who knows how to live can walk abroad
Without fear of rhinoceroses or tiger.
He will not be wounded in battle.
For in him rhinoceroses can find no place to thrust their horn,
Tigers no place to use their claws,
And weapons no place to pierce.
Why is this so?
ምክንያቱም፣ He has no place for death to enter. ››
ከበር የመለስነው ሞት፣ በር ገንጥዬ እገባለሁ ካለስ አንልም? ካለማ አንድም ዘራፍ ብሎ መነሳት አንድም ከነመኖሩ መርሳት፡፡ ዘራፉ ይቆየንና ከነመኖሩ መርሳት ይቻላል ወይ? የሚለውን እንይ፡፡ the denial of death ስልታዊ ማፈግፈግ ነው፡፡ ልክ ጲላጦስ እጁን ታጥቦ ኢየሱስን እንዳስገደለው ያለ፡፡ ለሞት ጀርባ መስጠት፡፡ እኔ ጋ አይደለም የመጣው አልያም እኔ የለሁበትም ብሎ ማለት፡፡
የሞትን ሕልውና አለማወቅ እና ሞትን መካድ ሁለት የተለያዩ ነገሮች ናቸው፡፡ እስኪ በተናጠል ለማየት እንሞክር፡፡ አንደኛ፣ ሞት ብሎ ነገር መኖሩን ጭርሹን አለማወቅን አስመልክቶ ፍሩውድ ያለውን እናንሳ፣ ፍሩውድ ያለው ይህን ነው፡፡
‹‹… እንዲያውም ልንገርህ፣ The conscious ጭርሹኑ does not know death or time, in man’s physiochemical, inner organic recesses he feels immortal. ››
ይህ ማለት፣ ደጅ ቆሞ ‹‹ ቤቶች ›› ሲል፡፡
‹‹ ማን ነው? ›› (ማለት፣ ተነስተህ ከመክፈትህ በፊት፡፡)
‹‹ እኔ ነኝ ›› (ስሙን አይናገርም? ሌባ)
‹‹ አንተ ማን ነህ? ስም የለህም? ›› (ጎበዝ! ደግ አደረግህ)
‹‹ ሞት ነኝ ››
‹‹ ሞት ምንድን ነው? አውሬ ነው? ሰው ነው? ካለዛሬም ስምህን ሰምቼው አላውቅ›› ብሎ ማለትን ይመስላል፡፡
ሞትን መካድ ላይ እንምጣ፣ ለዚህ ማሳያ ተመሳሳይ ምሳሌ እንጠቀም፡፡
ሞት ደጅ ይቆምና በር እየቀጠቀጠ ‹‹ቤቶች›› ሲል፡፡
‹‹እዚህ አይደለም የተንኳኳው፣ ጎረቤት ካለ ቤት ነው›› ብሎ በማሰብ ምንም እንደሌለበት ሰው ፊትን ወደ ግድግዳ መልሶ ለጥ ማለት፡፡ ሞትን የምንክደው መኖሩን ካወቅን በኋላ ነው፡፡ እዚህ ጋር ነው ከፍሩውድ ጋር ልዩነት የሚፈጠረው፡፡
ሞት ባዳ ነው፡፡ ሞት ከሰው ወገን ስላልሆነ፣ ለሰው አይራራም፡፡ ብላቴን ጌታ ማህተመ ስላሴ ወልደ መስቀልስ ምን አሉ የሞትን ነገር ታዝበው ‹‹… የሰው እንግዳ ሲመጣ፣ ግባ ይሉታል ብላ ጠጣ፣ ያንት መላክተኛ የመጣለት፤ ይዋል ይደር የለበት ›› ሞት ክፉ እንግዳ ስለሆነ ውለታውን በክፋት ነው የሚመልሰው፡፡ እርሱ ከፍቶ ባይሆን እንኳ፣ ውጤቱ ለእኛ ስለሚከፋ እጁ እስኪገነጠል ቢያንኳኳ እንኳ፣ የኛ በር እንዳልተንኳኳ ማመን እስከሚቻለን ድረስ መፅናትን መለማመድ፡፡ እውነት ማን ይሙት! የትኛዋ ልጃገረድ ናት የምጥ ስቃይን ከወላድ የምትጋራ? ስሜቱን፡፡ ምጥ እንዲያም ብታውቅ እንጂ ሕመሙ አይሰማትም፡፡ ሞትስ እንደ ውልደት አይደለም ወይ? ሕመሙን ሆነ ደስታውን እስካልቀመስነው መች ይሰማናል፡፡ አይሰማንም፡፡ ሰውም እንዲሁ ነው፤ ስለ ሞት ያለው ግምት፡፡ ከጎረቤቱ ጥል ባይሆን እንኳ ሞትን በማሻገር፣ አንዱ ቀሪና ቀባሪ እርሱ እንደሆነ ይሰማዋል፡፡
ጋሽ ቤከርም ይህንኑ ነው ያሉት፣
‹‹… at heart one doesn’t feel that he will die, he only feels sorry for the man next to him. ››
ሌላው ጥያቄ፣ እንዴት ነው ሞት ላይ ዘራፍ የሚሉት? እና፣ ዘራፍ ያሉት ጠላት በዘራፍ አልበረግግ ቢልና ይልቁን ዘሎ ቢያንቅ ምን ያደርጋሉ? የሚለው ነው፡፡
ነገሩን ሁለት ቦታ ከፍለን ለማየት እንሞክር፡፡
ታግሎ ማሸነፍና፣ ታግሎ መሸነፍ፡፡ ታግሎ መሸነፍን፣ በታሪክም በዓይናችን ብሌንም ዐይተን በተማርነው መሰረት የሁላችን ሊባል ቁጥሮች ለጎደለን ለ99ኞቹ ትተን ፣ ታግሎ ማሸነፍን ለአንዱ እንሰጣልን፡፡
ዘጠኝ ሞት መጣ ሲሉት፣ አንዱን ግባ በሉት አላ፡፡
አንዱ ማን ነው?
እዚህ ጋ ጋሽ ቤከርን በድጋሚ ወደ’ዚህ ለመጥራት እንገደዳለን (ለማይረባ ነገር አመላለስንዎት አይደል ጋሼ… ይቅርታ)
‹‹ The hero was the man who could go into the spirit world, the world of dead, and return alive. ››
ሆድህ ገብቼ ደም ሳይነካኝ እወጣለሁ እንደማለት ያለ ነው ነገሩ፡፡ ይሄ ከሞት ግብግብ እግረ መንገዱን ሽልማት የሚገኝበት ነው፡፡ ሽልማቱ ደግሞ ጀግንነት ነው፡፡ ሞት ያልተፈራበት ዘመን አለ ቢሉ፣ ሰው አልነበረም ያኔ ብለን ለመጠየቅ እንደፍራለን፡፡ ስፓርታ ልጆቿን ለክብር ሞት መውለዷስ? ብትሉ፣ ሰው ሕይወቱን በትፍስህት ለሞት አያጫትም፣ ቢሳካለት እንኳ ሞትን ተሻግሮ ማየት አልቻለም፤ እንላለን፡፡ ሁሉም ሕይወት ሞት ፊት ኢምንት ነው፡፡ ያንን ማወቅ ለፈለገ ለእገሌ እሞታለሁ ያለ ጀግና አንገት ላይ ሰይፍ ያስደግፍ፡፡ ያኔ ጉራውና ትምክህቱ ለነፍሱ ቦታ ትለቃለች፣ ነፍስ ደግሞ ፈሪ ናት፡፡ ነፍስ የታሰረችበት ግድግዳ ነው ስጋ ማለት፡፡ ነፍስ ስጋን መሽጋ የምትኖር የሌላ ዓለም ዜጋ ናት፡፡ ድንገት የዜግነት ማጣሪያ ሲደረግ ትበረግጋለች፣ በስጋው እንጂ በነፍሱ ጀግና የሰው ዘር የለም፡፡ እንዲያው ልቡ ጀግኖለት እንደ ስፓርታውያኑ ወጠጤዎች ሞትን በድፍረት ቢጋፈጥ እንኳ ተመልሶ ገድሉን ለማፃፍ የሚሆን እድል አላገኘም፡፡ ካርል ዩንግ ይሄን የጀግንነት ጉዳይ ስነልቦናዊ ፍካሬ ይሰጠዋል፡፡ ነገር ግን ጉዳዩ ሰው የራሱን ሞት ከማሸነፍ በዘለለ በሌሎች (የሞት አገልጋይ ተደርገው በተመሰሉ monsters and force of evil) ላይ በመዝመትና እነሱን በማሸነፍ ጭምር ነው ይለናል፡፡ ባለቤቱን ካልናቁ አጥሩን አይነቀንቁ አይደል ተረቱስ፣ እሱን ባይሆን መልዕክተኞቹን በመጠፍጠፍ የሰው ልጅ ንቀቱን አሳይቷል፡፡ ይሄን እምነት ለማሳየት በየጫካው እየዞሩ፣… እነማ አትሉም?
‹‹ እነ ሄርኩለስ፣ እነ ዳዊት፣ እነ ጊዮርጊስ፣ ጊለጋሜሽ፣ ሲጉርድ፣ ዘንዶና አንበሳ በጥፊና በቴስታ ሲዘርሩ፣… ክርስቶስ መጣና ታዲያ፣…
… አያይ እንደዚያ አይደለም፣… አንዱና ትልቁ (ጉልቤው) ሌላውን (ደካማውን) እየበላና እየገደለ መኖር ሥርዓተ ተፈጥሮ ነው፡፡ ማሸነፍ ያለብን ሞትን ነው፡፡ don’t kill the messenger፣… የቱ ሞኝ ነው ኮምፒውተሩን ቫይረስ ሲያጠቃው፣ ቫይረሱን ፀረ- ቫይረስ በማስረጨት ፈንታ አውጥቶ የሚወረውር? የቷስ ቂል ናት ስንት ፈዋሽ ፀበል (ቡሩክ ካህን) ባለበት ሀገር ቤቴ ሰይጣን ገባ ብላ ቤቷን ጥላ ብርር የምትል? ይሄ ሞኝነት ነው፡፡ ሞት ግድግዳ ነው፡፡ ግድግዳውን ማፍረስና መተላለፊያ ማበጀት ነው ያለብን፣ እኔ ያንን ነው ያደረግሁት፡፡ ››
ያለውን አደረገ፡፡ ይሄን ጀግንነት ያለተቀናቃኝ በምልዓት የተቆጣጠረው ኢየሱስ ብቻ ነው፡፡ ኢየሱስ የሰው ልጆች ጀግና ነው፡፡ ኢየሱስ ሞት ላይ ተረማምዶ ከማለፍ በላይ የጀግንነቱን ዜና በራሱ ጆሮ ለመስማት ችሏል፡፡ ከኢየሱስ ትንሳዔ ወዲህ ሞት እምብዛም ያልተፈራበት ዘመን ሆነ፡፡ ሰዎች እየሞቱ እያየ እንኳ ከሞት ባሻገር ስላለው ሕይወት ማወቁ ሰውን አፅናናው፡፡
ሞት ምን አለ ይሄን ጊዜ?
‹‹ ተበላሁ! ››
ሞት ይሄን ማለቱ በሀገር ተሰማ፡፡ ሀገሬው ሞት ይሄን ማለቱን ሲሰማ የድል ድግስ ደገሰ፡፡ (ኸረ ዘፈን ያወጡም አሉ አሉ፣… ሞትዬ ሞትነት፣ ሞት’ለም ሞቱካ፣… አሃሃሃ፣… እንዲህ ያለው ፈሪ፣ ልፍስፍስ ነህ ለካ፣… ሆሆይ ናና…) በየድግሱ ሞት ላይ ተቅራራ፡፡ የኢየሱስ ትንሳዔ ለሰዎች፣ ሞት ማለት ከገቡበት የማይወጡበት እንዳልሆነ መልመጃ ሆነ፡፡ ይሄን ጊዜ ጋሽ ቤከር ሰልፍ አሳብሮ ገባና እንዲህ አላ፣
‹‹ when we see a man bravely facing his own extinction we rehearse the greatest victory we can imagine. ››
ሰው በየመቅደሱ፣ በየእድሩ፣ በየዛፉ ጥላ፣ በየጨብሲ ቤቱ፣ ጠረጴዛ በጡጫ እየመታ ጥርሱን እያፋፋቀ ተማማለ፡፡ አንዱ ጎበዝ ብድግ ይልና መሃላውን ይመራል ሌላው እየተከተለ እሱ ያለውን ይላል፡፡
‹‹ ከእንግዲህ በኋላ፣… ሞት ሆይ እግር ብላ፣… If I am like my all powerful father, I will not die. ››
ኦስትሪያዊው ዶክተር ዊልካልም ሪችም ይሄን መሃላ Character armor ብሎ ጠራው፡፡
እንበልና (በእንበልና ገብተው የእውነትን ቦታ ያገኙ ስንቶች እንዳሉ መረጃው ቢኖረንም) ቅድመ ክርስቶስ የነበረው የሰው ልጅ ሞትን ሲፈራው የነበረው፣ ሞት የሙከራ ዕድል ስለማይሰጥ ነው እንበል፡፡
በምሳሌ እንየው፡- ከ’ለታት በአንዱ ቀን፣… እንዲያው አንዱ ጥጋብ ልቡን ንፍት ያደረገው ወጠጤ፣ በሰላም ኑሮውን እየኖረ ካለበት ድንገት ብድግ ብሎ የሞትን ነገር ቢያጣጥል፣ አጣጥሎም ባይቀርና ካልገጠምኩት ሞቼ ልገኝ ቢል፡፡
‹‹ የታባቱንስና ደግሞ! አሁንስ ለማንም ጠቋራ (መቼም ፈረንጅ ይመስላል እንደማትሉኝ) መንቦቅቦቅ ሰለቸኝ ››
ብሎ ቢገጥመውና ሞት በአንድ ቃሪያ ጥፊ ጥሎት ያንን የመሰለ መኳንንት ሙትት ብሎ ቢቀር፡፡ እሱኮ ሀሳቡ የነበረው፣ ሞት ቢያሸንፈው ከንግዲህ ኋላ አንገቱን ሰብሮ ሊኖር፣ እንደሁ አድባር ቀንታው ሞትን ቢያሸንፈው ጊዮርጊስ እንደረገጠው ድራጎን ያለ ምስል፣ ሞትን ከእግሩ ስር ረግጦ የሚያሳይ ሀውልት አደባባይ አቁሞ ለመኖር ነበር፡፡ ሞት ግን አሰራሩ እንደዚያ አይደለም፣ ከተጣሉት ለእርቅና ለሽምግልና የሚሆን ጊዜ አይሰጥም፡፡ እንዲያው ዝግት ያለ ነገር ነው፡፡ ይህ እንዴት ማለት ነው? ለነገ የሚሆን እቅድ ይዘህ ከአልጋ ትወጣና ነገን ብትጠብቅ ብትጠብቅ ሳይመጣ ቢቀር፣ ይሄም በቀላል እንግልጣርኛ
‹‹ any schoolboy can do experiments in the physics laboratory to test various scientific hypothesis. But man, because he has only one life to live, cannot conduct experiments to test whether to follow his passion [compassion] or not. ››
ኩንዴራ ከላይ ያለንን ሰምተን ‹‹ ልክ ብለሃል ›› ብለን ብዙም ሳንርቅ ሌላ አጣብቂኝ ውስጥ እንገባለን፡፡ አጣብቂኙ የመጣው ከታሪክ ነው፡፡
ቅድመ ክርስቶስ ያለው የሰው ልጅ ሞት የመጨረሻ አለመሆኑ ጠፍቶት ነው? የሚል፡፡ ‹‹እህሳ?›› ስንል፡፡ ነገሩ ወዲህ ነው ብሎ ይጀምራል አጣብቂኙ፣
‹‹ ዛሬ አይምሰላችሁ፣ ጥንት የሄለናውያንን ፍልስፍና የሚያራምዱ የዜኖ ደቀመዛሙርት የሆኑት ስቶይክሶች፣ ቡድሂስቶች፣ ሂንዱሂስቶች ሁሉ ሳይቀር ሞት ለሰው ልጅ የመጨረሻው እንዳልሆነና Infinite (የሰው ልጅ የቁጥር እውቀቱ አገልግሎት እስከሚያጣበት) ጊዜ ተደጋግሞ ተወላጅ እንደሆነ ያምናሉ፡፡ ››
የአጣብቂኙን ነገር ችላ ለማለት ‹‹ የድሮ ሰው ምኑ ይታመናል ›› ብለን ልናጣጥል ስንጀምር፣ የድሮ ሰዎች አምላክ ከድህረ ክርስቶስ ሰዎች ነብይ አስነሳብና፡፡ እንደ ኒቼ ባሉ ባለ ጎፈሬ ሙስታሾች ስል ምላስ ሊያስገርፈን፡፡ ኒቼ ተነሳ ያንን ዞማ ፅዕሙን እያስተኛ፣
‹‹ የድሮ ሰው ምናምን እያልክ ነገር ከምታጣጥል ካሽ አውጣና መፅሐፌን ግዛኝ፣ እዛ ላይ ስለ Eternal recurrence የፃፍኩትን ታገኛለህ፣…››
ታዲያ እንዲህ ከሆነ ነገሩ የዛን ዘመን ሰው ሞትን ለምን ፈራ? ተብሎ ሲጠየቅ፣ እኛም መላምትን ለፈጠረ አምላክ ገለተ ጢሎሲ! እያልን መመልመት እንጀምራለን፡፡
መላምት 1፡- በዚህኛው ዓለም ያስኮረፉት ሞት (የድሮው ሞት ደግሞ ተበቃይ ነው) በሌላኛው ሕይወት ሲያገኛቸው መከራቸውን እንዳያበዛው በመስጋት፡፡ ማን ያውቃል ሞትም የTalien principle ተከታይ እንደሆነ? የናቀውን በንቀት፣ የተሳፈጠውን በስፍጠት የሚመልስ እንደሆን? ሞት ሲሳፈጥ ደግሞ አሟሟት በማክበድ ነው ሲባል ሰምተናል፣ ሲያደርግ ባናይም፡፡
መላምት 2፡- ድግግሙ ቅልሽልሽ ስላለው፡፡ አልያም ምን የመሰለው ከበርቴ አሳማ ሆኜ ብመለስስ ከሚል ከንቱ ስጋት?
ደግሞ ሞትን መፍሪያ ምክንያት ጠፍቶ ነው? እንዲያው ስታደክሙን እንጂ፡፡
ከዚህ ሁሉ በኋላ ታዲያ ሰው ምን በጀው? ብለን ከአፋችን ሳንጨርስ አጋፋሪሻ በቅሎአቸውን እየኮለኮሉ ከተፍ፡፡ በግራ ይሁን በቀኝ እጃቸው መፈክር ይዘዋል፡፡
‹‹ ሞትን ሽሹት! ›› የሚል የተፃፈበት፡፡
ጨዋታን ጨዋታ አይደል የሚያነሳው፣ ለመሆኑ አጋፋሪ ሞትን ሲሸሹ ነው ሲያባርሩ የሰነበቱት? ብሎ መጠየቅ አይከፋም፡፡ ምክንያቱም ሞት ሁሉ ሀገሩ ነዋ፡፡ ይልቅ አጋፋሪ በፍርሃትም ይሁን በግብታዊነት ሞትን በንቃት ይከታተሉት ነበር፡፡ ንቃታቸው ሞትን ከጉያቸው አልለየውም፡፡ ባሰቡት ቁጥር ሞት ቅርባቸው እንዲገኝ ሆነ፡፡ ለመሸሽ ባሉት ልክ እየቀረቡት በአንፃሩ ሞት ያለቀጠሮ እንዳያስቱት ብሎ ሲሸሽ እንደኖረ አድርገንም ማሰብ ይገባል፡፡ ይባስ ብለን፣ አጋፋሪ ሞትን ሳይሆን ሙታንን ነበር ሲሸሹ የነበሩት ብንልስ? ለምን አንልም ለምለም አንደበት እስካለን፡፡
እናም በስተመጨረሻ፣… ጋሽ ኩንዴራ The stupidity of people comes from having an answer for everything ብሎ እፍኝ ስላሳከለን መልስ ኪሳችን ቢኖርም ታላቅ የመታዘዝ ባሕል እድሜው እንዲረዝም ሲባል ጠይቀን እንወጣለን፡፡
1. ከሚከተሉት ምርጫዎች መካከል እንደው ይሄ ለኔ ይበጀኛል ያላችሁት ላይ አክብቡ?
ሀ. ቤቴን በሕይወት ሞልቼ ለሞት የሚሆን ቦታ ማሳጣት
ለ. ሞትን ታግዬ ማሸነፍ
ሐ. ከነመኖሩ ርስት አድርጌው መኖር
መ. እንደ አጋፋሪ መሸሽ
ሠ. መልሱ እዚህ የለም
ረ. እዚህ ከሌለ የት ነው?
(በስተመጨረሻም፣ በእኚህ ከላይ በጥቂቱም ቢሆን በጠቀስናቸው ግለሰቦች (በላዖ ዙ፣ በኤርነስት ቤከር፣ በፍሩውድና በአጋፋሪ) ሕይወት ውስጥ ስለተፈከረው ሞት ለመጨዋወት የያዝነውን የመንደርደሪያ ሀሳብ ዳግም የምንመለስበት ስለሚሆን፣ አትጥፉ ለማለት ነው፡፡)
የምስጋና ተዓምራዊ ሃይል!!
ለማሰብ እጅግ አስከፊ ከነበረ ሁኔታ ውስጥ በምስጋና ኃይል፣ ህይወታቸውን ሙሉ በሙሉ የለወጡ በሺዎች የሚቆጠሩ ሰዎችን አውቃለሁ። ፈጽሞ ተስፋ የሌለው የሚመስል የጤና ጉዳይ፣ ተአምር የሚያሰኝ ውጤት አምጥቷል።
ሥራቸውን ማከናወን ያቃታቸው ኩላሊቶች እንደገና ሲያንሰራሩ፤ የታመሙ ልቦች ሲፈወሱ፤ የታወሩ አይኖች ሲበሩ አይቻለሁ። የተበጠሱ የግንኙነት ክሮች ተቀጥለው ወደ ሰመረ ግንኙነት መቀየራቸውን አውቃለሁ- በምሥጋና ተዓምራዊ ሃይል!!
አለቀለት የተባለ ጋብቻ ሲታደስ፤ የተራራቁ የቤተሰብ አባለት እንደገና ሲገናኙ፣ የወላጆችና የልጆች ግንኙነት እንደ አዲስ ሲገነባና መምህራን ተማሪዎቻቸውን ሲለውጡ ሁሉ አውቃለሁ።
በምስጋና አማካኝነት፣ ቤሳ ቤስቲን ያልነበራቸው ድሆች ባለጠጋ ሲሆኑ፣ የከሰረ ንግዳቸውን እንዲንሰራራ ሲያደርጉ፤ እድሜ ልካቸውን ከገንዘብ ጋር ግብግብ ገጥመው ሲንጠራወዙ የነበሩ፣ የተትረፈረፈ ሀብት ሲፈጥሩ አይቻለሁ።
አንዳንዶቹም እንዲያውም፣በአንድ ሳምንት ጊዜ ውስጥ፣ ከጎዳና ተዳዳሪነት ወጥተው ባለሥራና ባለመኖሪያ ቤት ሆነዋል። በድብርት ውስጥ የነበሩ ሰዎች አስደሳችና የተሳካ ህይወት መቀዳጀታቸውን አውቃለሁ። በጭንቀትና በተለያዩ የአዕምሮ ህመሞች ሲሰቃዩ የነበሩ ሰዎች፣ በምስጋና አማካኝነት ፍጹም የአዕምሮ ጤናቸው ተመልሶላቸዋል።
ሁሉም የዓለም አዳኞች፣ ምስጋናን ተጠቅመውበታል። ምክንያቱም ምስጋና እጅግ ላቅ ካሉት የፍቅር መገለጫዎች አንዱ መሆኑን ያውቃሉና። ምስጋናቸውን ባለማጓደል ሲያደርሱ፣ ህጉን በትክክል ጠብቀው እየኖሩ መሆናቸውንም ያውቃሉ።
ኢየሱስ ክርስቶስ እያንዳንዱን ተአምራት ከመፈጸሙ በፊት፣ “አመሰግናለሁ” ይል የነበረው ለምን ይመስላችኋልሃል?
የሰዎች ውለታ በተሰማችሁ ቁጥር ፍቅርን እየሰጣችሁ ነው። የሰጣችሁት ደግሞ ተመልሶ ይሰጣችኋል። ሰዎችን ስታመሰግኑ ይሁን ለመኪናችሁ፣ ለአዲሱ ቤታችሁ፣ ለዕረፍት ጊዜያችሁ ወይም ለምትጠልቅ ጀንበር (Sun Set) አሊያም ለተበረከተላችሁ ስጦታ ወይም ደግሞ ለገጠማችሁ አስደሳች ክስተት ምስጋና ስታቀርቡ፣ ለእነዚህ ነገሮች ፍቅር እየሰጣችሁ በመሆኑ በአጸፋው የበለጠ ደስታን፣ የበለጠ ጤንነትን፣ የበለጠ ገንዘብን፣ የበለጠ አስደሳች ሁኔታዎችን፣ የበለጠ አስደናቂ ግንኙነቶችንና የበለጠ ምቹ አጋጣሚዎችን ታገኛላችሁ።
(ተአምራዊ ኃይል - The Power)