Administrator

Administrator


            በ14 ዓመቱ ታዳጊ ላይ የብልት መሰለብና የአካል ጉዳት ያደረሰበት ተጠርጣሪ አልተገኘም

          ታዳጊው ለከፍተኛ ህክምና ወደ ጳውሎስ ሆስፒታል ይመጣል
                 በቤኒሻንጉል ጉሙዝ ክልል መተከል ዞን፣ ድባጤ ወረዳ፣ ዝግህ ቀበሌ፣ ልዩ ስሙ በካር ወንዝ በተባለ ቦታ ከብት በመጠበቅ ላይ የነበረው የ14 ዓመት ታዳጊ አበጠር ወርቁን ብልት በመስለብ ጥቃት ያደረሰበት ተጠርጣሪ እየተፈለገ ነው። የድባጤ ወረዳ ፖሊስ ጽ/ቤት አዛዥ ዋና ኢንስፔክተር ንጋቱ ኢተፋ፤ ጉዳዩ ገና በምርመራ ላይ መሆኑንና ሰባት ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውን ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡
ባለፈው ሰኞ ግንቦት 6 ቀን 2010 ዓ.ም በግምት ከቀኑ ከ7፡00 እስከ 8፡00 ባለው ጊዜ ውስጥ በካር በተሰኘው አካባቢ ታዳጊው ከብት ሲጠብቅ በነበረበት ወቅት አንድ ጫት በመቃም ላይ የነበረ ሰው አጠገቡ ሆኖ ለረዥም ሰዓት ሲያጫውተው እንደቆየና በድንገት ማጅራቱን ከመታው በኋላ ወድቆ ራሱን መሳቱን እንደነገራቸው የታዳጊው አጎት አቶ አያሌው አበረ ገልፀዋል፡፡ በአካባቢው ልማድ መሰረት የሰፈሩ ከብቶች የሚጠበቁት በተራ እንደሆነ የጠቆሙት የተጎጂው አጎት፤ በዕለቱም የከብት ጥበቃ ተራው የታዳጊው አባት እንደነበረና አበጠርም የአካባቢውን ከብቶች በመጠበቅ ላይ እንዳለ ጥቃቱ እንደደረሰበት ተናግረዋል፡፡
የፓዌ ሆስፒታል ሜዲካል ዳይሬክተር ዶ/ር ግርማ በየነ በታዳጊው ላይ ስለደረሰው የጉዳት መጠን ጠይቀናቸው ሲመልሱ፤ ህፃኑ ወደ ሆስፒታሉ ሲመጣ ብልቱ ተቆርጦ ፊቱ በከፍተኛ ሁኔታ ተጎድቶና የመንጋጋ ስብራት ደርሶበት እንደነበር አስታውሰው፤ ለሶስት ቀናት በሆስፒታሉ ህክምና ቢደረግለትም በሆስፒታሉ ያለው ራጅ ብቻ በመሆኑና በሲቲ ስካን የጭንቅላቱ ሁኔታ መታዬት ስለነበረበት ወደ አንጎሉ ደም እንዳይፈስ በመስጋት ባህርዳር ወደሚገኘው ፈለገ ህይወት ሆስፒታል ሪፈር ተፅፎለት ለተሻለ ህክምና እንደሄደ ነግረውናል፡፡ የጉዳቱን መጠን በተመለከተም “ብልት ተቆርጦ ሲሄድ አንድ አካልን ማጣት ከባድ ጉዳት ነው፤ ፊቱም ላይ የደረሰው አደጋ ቀላል አይደለም” ያሉት ሜዲካል ዳይሬክተሩ፤ ሲቲ ስካን ተነስቶና ሙሉ ምርመራ ተደርጎ የሚገኘው ውጤት ነው በህክምና ሙያ በዋናነት የጉዳቱን መጠን የሚገልፀው ብለዋል፡፡ ታዳጊው በአሁኑ ሰዓት በባህር ዳር ፈለገ ህይወት ሆስፒታል ማህበራዊ አገልግሎት ዘርፍ በኩል አስፈላጊው ምርመራና ህክምና እየተደረገለት መሆኑን የልጁን ጉዳይ በቅርበት እየተከታተሉ የሚገኙት በባህር ዳር ዩኒርቨሲቲ ረ/ፕሮፌሰር ዶ/ር ደሳለኝ ጫኔ ከፈለገ ህይወት ሆስፒታል ገልፀውልናል፡፡
የ14 ዓመቱ አበጠር ወርቁ ለእናቱ የመጀመሪያ ለአባቱ ሶስተኛ ልጅ እንደሆነ የገለፁት አጎቱ አቶ አያሌው አበረ፤ ምንም የማያውቅ ልጅ እንዲህ አይነት አሰቃቂ ጥቃት ሲደርስበት የወረዳው ፖሊስ የተወሰኑ ሰዎችን እያሰረ ከመፍታት ውጭ የተጠናከረ ምርመራ እያደረገና ትኩረት እየሰጠ አለመሆኑ እንዳሳዘናቸው ገልፀው ጉዳዩ በመንግስት ደረጃ ትኩረት አግኝቶ ህፃኑ ፍትህ እንዲያገኝና አጥፊዎች ለፍርድ እንዲቀርቡ እንጠይቃለን ብለዋል፡፡
በፈለገ ህይወት ሆስፒታል ለልጁ ህክምናና ክትትል እያደረጉ የሚገኙት በባህርዳር ዩኒቨርሲቲ የመጨረሻ አመት የቀዶ ህክምና ተማሪ ዶ/ር ሲሳይ ሙሉቀን በበኩላቸው፤ ህፃኑ የብልት መቆረጥ የጭንቅላትና የአይን ጉዳት እንዲሁም የጥርስ መውለቅና ተደራራቢ ጉዳቶች የደረሰበትና በስለት ፊቱ የተቆረጠ በመሆኑ የጉዳቱ መጠን ከፍተኛ መሆኑን ገልፀው፣ በአፉና በአንገቱ አካባቢ ኢንፌክሽን የተፈጠረ በመሆኑ የአንቲ ባዮቲክ ህክምና እየተደረገለት ነው ብለዋል፡፡ ዶ/ር ሲሳይ አክለውም፤ ልጁ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየነቃ መሄዱን፣ በአተነፋፈሱ በኩል ትንሽ ችግር ስለገጠመው በኦክስጅን ታግዞ እየተነፈሰ መሆኑን ጠቁመው፤ ብልቱ ላይ ካቲተር ተገጥሞለት ህክምናው ቀጥሏል ብለዋል፡፡
ባለሀብቱ አቶ በላይነህ ክንዴ የታዳጊውን ሙሉ ወጪ ሸፍነው ለማሳከም ቃል የገቡ ሲሆን የጤና ጥበቃ ሚኒስትሩ ዶ/ር አሚር አማን ህፃኑ ጳውሎስ ሆስፒታል መጥቶ እንዲታከምና ወጪውን ሚኒስቴሩ እንደሚሸፍን መግለፃቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡

 ባለፈው እትም ትዳርን ከመፍረስ ለማዳን ከሚረዱን ምክንያቶች አንዱን አስነብበናችሁዋል፡፡ የስነልብና ባለሙያዎች ትዳርን እንደአጀማመሩ ለማቆየት የሚረዱ በርካታ ጠቃሚ ነገሮችን የሚያማክሩ ሲሆን ለዚህ እትምም ለንባብ የተወሰኑትን መራርጠናል፡፡
አንድ መረጃ እንደሚጠቁመው በአሜሪካ 40-50% የሚሆኑ ትዳሮች የመፍረስ እድል ሲያጋ ጥማቸው በኢትዮጵያ ደግሞ በ30 አመት ውስጥ 45% ያህል ትዳር የመፍረስ እድል ያጋጥ መዋል የሚለው መረጃ የተገኘው ከ American Psychological Association ነው፡፡ ከሰሀራ በታች ባሉ 20/የአፍሪካ ሀገራት በ20/አመት ጊዜ ውስጥ ያለው ሁኔታ ሲታይ ትዳር ከመፍረስ ቆጠብ ያለ ነው ቢባልም ነገር ግን በትክክለኛው ጥናት ተደግፎአል ለማለት አይቻልም እንደ መረጃው እማኝነት፡፡
እንደአለምአቀፉ መረጃ ከሆነ ፍቺ የሚፈጸምባቸው የተለያዩ ምክንያቶች አሉ፡፡ ከእነርሱም ውስጥ፡-
በትዳር ላይ መማገጥ፤
በገንዘብ አለመተማመን ወይንም አንዱ ለአንዱ በቂ ገንዘብ አለመስጠት፤
እርስ በእርስ ለመግባባት ችግር፤
ነጋ ጠባ በየእለቱና በየጊዜው መጨቃጨቅ፤
የሰውነት ቅጥ ያጣ ክብደት መኖር፤
አንዱ አንዱን የመናቅ፤ አስተዳዳሪ…ውሳኔ ሰጪ እኔ ነኝ የሚል ስሜት፤ እኩልነት ማጣት፤
እርስ በእርስ የመቀራረብ ችግር፤
ከሚገባው በላይ ነገሮችን የመጠበቅ፤
ካለእድሜ ጋብቻ፤
ልጅ አለመውለድ፤…ወዘተ
ከላይ የተጠቀሱት ነገሮች ትዳር ጤናማ እንዳይሆን ሊያደርጉ ከሚችሉ መካከል ሲሆኑ መፍት ሔውን ለመፈለግ አስቀድሞ ግንዛቤው ቢፈጠር መልካም ነው ይላሉ ጥናት አቅራቢዎቹ፡፡
ባለፈው እትም ለትዳር መፍረስ ምክንያት ሊሆኑ የሚችሉ አንዳንድ የተፈጠሩ ችግሮችን በሚ መለከት በምን መንገድ ማስወገድና ፍቅር እንደገና ማለት እንደሚቻል Mort-Fertel የተባሉት የስነልቡና ባለሙያ የጻፉትን አስነብበናችሁዋል፡፡ በዚህ እትም ደግሞ ትዳርን እንደጠበቀ ለማቆየትና ምናልባት ቢበተን ሊያስከትል የሚችለውን የጤና፤ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ችግር አስቀድሞ ለመከላከል እንዲቻል ሌላው መንገድ መነጋገርና መነካካት ነው ይላሉ፡፡
መነጋገር እና መነካካት(Talk and Touch)
ባለሙያው እንደሚሉት አስቀድሞ በአንድ ነገር ግልጽ መሆን ያስፈልጋል፡፡ ኑሮ ማለት በድርጊት እንዲሁም በንግግር አንዱ አንዱን በመነካካት የተደገፈ ነው፡፡ ለምሳሌም በ24 ሰአት ውስጥ ባልና ሚስቶች ምን ያህል መነጋገር እንዲሁም አንዳቸው አንዳቸውን በፍቅር መዳሰስ ይባቸዋል? ሁኔታውስ ምን ይመስላል? ለሚለው ሁልጊዜ ፊት ለፊት ተቀምጦ መነጋገር ወይንም ስራ በመፍታት አንዱ አንዱን መዳሰስ ይገባል ማለት አይደለም፡፡ ለዚህ ስርአት ወይም ህግ የለውም፡፡ እኔ እናገር ቁጭ ብላችሁ አድምጡኝ የሚያሰኝም አይደለም፡፡ ምናል ባትም በስልክ የድምጽ መልእክት ሊሆን ይችላል፡፡ አንተ/ቺ ስትናገር/ሪ የትዳር ጉዋደኛ ማዳመጥ ይችላል፡፡    
መንካት የተባለውም በንግግር ፈንታ በመንካት ተተካ እንጂ ከላይ ከተጠቀሰው ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ይህ ከሚወዱት ሰው ጋር ፍቅርን በመተቃቀፍ፤ ጸጉርን በማሻሸት ፤በመሳሳም በመሳሰሉት  የሚጋሩበት አይነት ነው፡፡ ይህ ምናልባትም በወሲብ ግንኙነት ጊዜ የሚደረገውን ሳይሆን በማናቸውም ጊዜ ፍቅርን ለመግለጽ የሚደረግ ነው፡፡
መነጋገር ሲባል በቀጥታ በእለት ተእለት ሕይወት ውስጥ ስለሚያጋጥም ነገር መሆን ይችላል፡፡ ለምሳሌም…. ልጆቹን ከትምህርት ቤት አምጣ/ጪ…. የመብራት ወይንም የውሀ ክፍያ ክፈይ/ል… የመሳሰሉት ሊሆኑ ይችላሉ፡፡ ለምሳሌም… ይህን ሕልም አየሁ …እኔ ይህንን ነገር እፈራዋለሁ/እወደዋለሁ…. ቀልድ ማውራት… በእለቱ ስላጋጠመ ነገር …የመሳሰሉት ሊሆኑ ይችላሉ፡፡
መነካካት ሲባልም …አንዱ አንዱ ትከሻ ላይ ደገፍ በማለት…ጸጉርን በመዳሰስ…ፊትን በመዳበስ …ሰውነትን መዳበስ  ….ማቀፍ …ሊሆን ይችላል፡፡
አንዳንድ ጊዜ ተጋቢዎች በመካከላቸው የማይግባቡባቸው ነገሮች ካሉና አንደኛው ሌላውን በሚነካካበት ወይንም አስቂኝ በሆነ መልክ በሚያነጋግርበት ጊዜ ሌላኛው ወገን (ባል ወይንም ሚስት) ሊናደዱና ምላሹ የሚያስቆጣ ሊሆን ይችላል፡፡ Mort-Fertel የሚከተለውን የትዳር ልምድ ለንባብ ብለዋል፡፡
‹‹…አንድ ቀን እኔና ባለቤቴ በጋራ ቁጭ ባልንበት ለማናገርም ይሁን ለመንካት ስሞክር ተናደ ደችብኝ። እኔ ልዳብሳት ስሞክር እስዋ ሌላ ርእስ ታመጣና ወሬ ትጀምራለች፡፡ እኔ ምነው? የሚል ጥያቄ አነሳሁላት፡፡ የእስዋም መልስ የሚከተለው ነበር፡፡››
‹‹…እኔ በጣም ከባድ የሆነ በትዳር ሕይወታችን ያልተመቸኝ ነገር አለ፡፡ አንተ በቀላሉ ምንም እንዳልተፈጠረ በማስመሰል በመቀለድ በመነካካት ልታሳልፈው ትፈልጋለህ። ይህ ደግሞ ጭራሹንም ቀልድ ነው፡፡ አለችኝ፡፡ እኔም ጉዳዩ ምንድነው….እስቲ አስረጂኝ አልኩአት፡፡ እስዋም ከአሁን ቀደም የተነጋገርንባቸውን ቀላል ነገር ግን ማስተካከያ የሚፈልጉ ነገሮች እንደገና ነገረ ችኝ፡፡ አካሄድዋም እኔን እያታለልክ ነገሩን ችላ ብለኸዋል የሚል ነበር፡፡ እኔ ደግሞ የሚስተ ካከለውን ነገር በጋራ ተመካክረን እናደርገዋለን እንጂ የእኔ ብቻ ኃላፊነት አይደለም፡፡ ቢሆንም ደግሞ ፍቅራችንን ሊያደበዝዝ …አንዳችን በአንዳችን እንድንናደድ የሚያስችል መሆን የለበትም አልኩአት፡፡ በእውነቱ ባለቤቴ ይህንን አስተሳሰብ ከጭንቅላትዋ ለማስወገድ ጊዜ ፈጅቶባት ነበር። ስናገር አትስቅም፡፡ ስነካካት እጄን ትገፈትረዋለች፡፡ ስለዚህ ቢቸግረኝ የወሰድኩት እርምጃ የሚከተለው ነበር፡፡
‹‹…የምወድሽ ባለቤቴ …ምንም ሳትዘጊኝ በአስፈላጊው ጊዜ ሁሉ የምታነጋግሪኝ እና የማነጋግርሽ ከሆነ የምታቅፊኝ የምትነኪኝ ወይም ሳቅፍሽ ስነካሽ በአጸፋ ምላሽ የምትሰጪኝ ከሆነ በትዳርሽ ላይ አስገራሚ እና ጥሩ ለውጥ ታያለሽ፡፡ ይህ ካልሆነና እኔ ጥፋት ካለብኝ በፈለግሽው መንገድ እቀጣለሁ አልኩአት፡፡ ባለቤቴም ተስማምታ ፍቅር እንደገና ብለን ኑሮአችንን ቀጠልን፡፡››
አንድ ትንሽ እርምጃ ትልቅ ለውጥ ታመጣለች፡፡ ያሉት Mort-Fertel የሚከተለውን ምክር ሰጥተዋል፡፡  
ጥዋት ከመኝታህ ስትነሳ ከትዳር ጉዋደኛ ጋር አንድ ቁምነገር መጋራት እንዲሁም ቀልድ ቢጤ ጣል አድርጎ ተሳስሞ መለያየት ቀኑን ብሩህ ያደርገዋል ይላሉ የስነልቡና ባለሙያው፡፡ በእኩለ ቀንም ካለህበት/ሽበት በመሆን አዋዋልን መጠየቅ ስለቀጣዩ ጊዜ ፕሮግራም መነጋገር ያስፈል ጋል፡፡ ሁልጊዜ ቀልድ ይወራል ማለት ሳይሆን ቁምነገርም ማካፈል …ይሆናል ወይንም አይሆንም መባባልም ያስፈልጋል፡፡ የትዳር ጉዋደኛን እጅ በመያዝ ጉንጭን በመነካካት ትከሻን በመዳበስ በመደገፍ በመሳም በመሳሰሉት ሁኔታዎች ትዳር ሁልጊዜ እንዲታደስ ማድረግ ይቻ ላል፡፡ ምናልባትም ተገቢውን ትኩረት አላገኘሁም የሚል ስሜት ካለ በሆድ ይዞ ከማብሰልሰል ይልቅ በግልጽ በመነጋገር ትዳርን ከሚያጠቁር ነገር መከላከልና ማጽዳት ያስፈልጋል፡፡
Mort-Fertel  የትዳር ጉዋደኛሞች ሊያደርጉዋቸው የሚገቡ ወደ 50/የሚጠጉ ቁም ነገሮችን በዝርዝር አስቀምጠዋል፡፡ በጣም በጥቂቱ እናስነብባችሁ፡፡
በትዳር ጉዋደኛ ውሳኔ እምነት መኖሩን መግለጽ፤
የትዳር ጉዋደኛን ድንገት ከቢሮ ወይንም ከቤት በመሄድ መጎብኘትና ሳም ሳም በማድረግ መለየት፤
እለቱ ለትዳር ጉዋደኛ እንዴት እንደነበረ በኃላፊነት ስሜት መጠየቅ፤
የትዳር ጉዋደኛን በመለያየት ወይንም በመገናኘት ጊዜ እንዲሁም ከመተኛት በፊት መሳም፤
ባልተጠበቀ ጊዜ የትዳር ጉዋደኛን በመፈለግ ምንጊዜም እንደምታስባት/ቢው ማሳየት፤
የትዳር ጉዋደኛን ትከሻ ወይንም አንገት Massage ማድረግ ወይንም ማሸት፤
ከእራት በፊት ዳንስ ለማድረግ መገባበዝ፤
ችግርን ማዋየት እና ለሚሰጠው ምላሽ በፍቅር መንገድ ማመስገን፤
በመኝታ ጊዜ ባለትዳሮች እጃቸውን አንዳቸው ለአንዳቸው ሰጥተው ወይንም ተያይዘው ቢሆን እና የመሳሰሉትን መፈጸም የትዳር ጉዋደኛሞች ፍቅራቸው እንዲጸና ትዳርም እንዳይበተን ይረዳል፡፡  

• 736 ተጨዋቾች ይሳተፋሉ 1120 በመጀመርያ እጩ የቡድን ስብስብ በፊፋ ተመዝግበዋል፡፡
• 32 ቡድኖች በ10.43 ቢሊዮን ዩሮ የሚተመን የተጨዋቾች ስብስብ የሚገነቡ ይሆናሉ
• በዝውውር ገበያ የዋጋ ተመን ሊዮኔል ሜሲ ከአርጀንቲና 180 ሚሊዮን ዩሮ፤ ኪላን ማብፔ ከፈረንሳይ 120
ሚሊዮን ዩሮ ፤ ክርስትያኖ ሮናልዶ ከፖርቱጋል 120 ሚሊዮን ዩሮ
• ውድና ምርጥ 11 ተጨዋቾች ቡድን ከ900 ሚሊዮን ዩሮ በላይ ያወጣሉ
• በተጨዋቾች ስብስብ ውዱ ቡድን ፈረንሳይ በ999.50 ሚሊዮን ዩሮ


    በ21ኛው የዓለም ዋንጫ ላይ የሚሳተፉት 32 ብሄራዊ ቡድኖች እያንዳንዳቸው 35 ተጨዋቾች ያሉባቸውን የመጀመርያ እጩ የቡድን ስብስባቸውን ሰሞኑን ለፊፋ አስታውቀዋል፡፡ ብሄራዊ ቡድኖቹ በዓለም ዋንጫ የሚያሰልፏቸውን 23 ተጨዋቾች ያሉባቸውን የመጨረሻ የተጨዋቾች ስብስብ ውድድሩ ከመጀመሩ ከ10 ቀናት ቀደም ብሎ ማሳወቅ ይኖርባቸዋል፡፡ በትራንስፈር ማርከት ድረገፅ መሰረት በዓለም ዋንጫ በሚሳተፉ 32 ብሄራዊ ቡድኖች በመጨረሻ የተጨዋቾች ስብስብ የሚመዘገቡ 736 ተጨዋቾች በዝውውር ገበያው አጠቃላይ የዋጋ ተመናቸው እስከ 10.43 ቢሊዮን ዩሮ ነው፡፡ በዓለም ዋንጫው ሻምፒዮናነቷን ለማስጠበቅ በምትገባው ጀርመን ወሳኝ ይሆናል የተባለው ቶኒ ክሮስ፤ በአጥቂ መስመር ድንቅ ብቃቱን በማሳየት ለእንግሊዝ ብዙ ያገባል ተብሎ የሚጠበቀው ሃሪ ኬን፤ በቅርቡ ከገጠመው ጉዳት ካገገመ ብራዚልን በአምበልነት በመምራት ለ6ኛው የዓለም ዋንጫ ድል ያበቃታል ተብሎ የተወሳለት ኔይማር፤ በዓለም ዋንጫ ድል ስኬታማ በመሆን አርጀንቲናን ይክሳል የሚባለው ሊዮኔል ሜሲ፤ ከ2017 እኤአ ጀምሮ የዓለም ኮከብ ተጨዋች ሆኖ የሚገኘው ክርስትያኖ ሮናልዶ፤ ሊውስ ስዋሬዝ ከኡራጋይና በእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ እና በአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ከፍተኛ አግቢነት የተሳካለት መሃመድ ሳላህ በኮከብ ተጨዋችነት እና በኮከብ ግብ አግቢነት እንደሚፎካከሩ እየተገመተ ነው፡፡ ሊሮስ ሳኔ ከጀርመን፤ ግራኔት ዣካ ከስዊዘርላንድ፤ ኬሌቺ ኢሄናንቾ ከናይጄርያ ፤ ማቲያ ቬሲኖ ከኡራጋይ፤ ማከስ ራሽፈርድ ከእንግሊዝ እንዲሁም ሮበርቶ ፈርሚሆ ከብራዚል በወጣት ኮከብ ተጨዋችነት የሚጠበቁ ሆነዋል፡፡ በየብሄራዊ ቡድኖቻቸው ባለመመረጣቸው፤ በጉዳት ምክንያት፤ በጡረታ በመሰናበታቸው እና ብሄራዊ ቡድኖቻቸው ባለመሳተፋቸው ደግሞ ዓለም ዋንጫው የሚያመልጣቸው ምርጥ ተጨዋቾች ጥቂት አይደሉም፡፡  ካሪም ቤንዜማና ሎረን ኮሰልኒ ከፈረንሳይ፤ አሌክስ ኦክስሌይ ቼምበርለይን፤ ጃክ ዊልሸርና ጆ ሃርት ከእንግሊዝ፤ ዳኒ አልቬስ ከብራዚል፤ማርዮ ጎትዜ ከጀርመን በመጀመርያው ተጨዋቾች ስብስብ  በብሄራዊ ቡድኖቻቸው ካልተጠሩት መካከል ይገኙበታል፡፡ ዝላታን ኢብራሞቪች ከስዊድን ዣቪ አርናንዴዝ ከስፔን በጡረታ ዓለም ዋንጫውን ከማይሳተፉ ተጨዋቾች የሚጠቀሱ ሲሆን እነ ሮሲ ከጣሊያን፤_እነ ሩበን ከሆላንድ ብሄራዊ ቡድኖቻቸው ለዓለም ዋንጫ ባለማለፋቸው ታላቁ የስፖርት መድረክ ያመለጣቸው ናቸው፡፡
ከፍተኛ የዋጋ ግምት ያላቸው ተጨዋቾች
ከ21ኛው የዓለም ዋንጫ ጋር በተያያዘ በዝውውር ገበያ ከፍተኛ የዋጋ ግምት ያላቸው ተጨዋቾች ከ1 እስከ10 ባለው ደረጃ በቅደም ተከተል ሲቀመጡ እንደሚከተለው ነው፡፡ ሊዮኔል ሜሲ ከአርጀንቲና 180 ሚሊዮን ዩሮ፤ ኪላን ማብፔ ከፈረንሳይ 120 ሚሊዮን ዩሮ ፤ ክርስትያኖ ሮናልዶ ከፖርቱጋል 120 ሚሊዮን ዩሮ ፤ ኬቨን ዴብርዋኒ ከቤልጅዬም 100 ሚሊዮን ዩሮ ፤ ኤዲን ሃዛርድ ከቤልጅዬም 100 ሚሊዮን ዩሮ ፤ አንቶኒዮ ግሬዝማን ከፈረንሳይ 100 ሚሊዮን ዩሮ ፤ ፊሊፕ ኩቲንሆ ከብራዚል 90 ሚሊዮን ዩሮ  ፤ ፖል ፖግባ ከፈረንሳይ 90 ሚሊዮን ዩሮ ፤ ሉዊስ ስዋሬዝ ከኡራጋይ 85 ሚሊዮን ዩሮ እንዲሁም ሮሜሉ ሉካኩ ከቤልጅዬም በ85 ሚሊዮን ዩሮ ነው፡፡
በ80 ሚሊዮን ዩሮ የዋጋ ተመናቸው ዴል አሊ ከእንግሊዝ፤ ሮበርት ሎውንዶውስኪ ከፖላንድ፤ቶኒ ክሮስ ከጀርመን፤ ኡስማን ዴምቤሌ ከፈረንሳይ፤ መሃመድ ሳላህ ከግብፅ እንዲሁም ራሂም ስተርሊንግ ከእንግሊዝ ይጠቀሳሉ፡፡ በ75 ሚሊዮን ዩሮ የዋጋ ተመናቸው ደግሞ ሊሮይ ሳኔ ከጀርመን፤ ሰርጂዮ አግዌሮ ከአርጀንቲና እንዲሁም ኢስኮ ከስፔን  ሲሆኑ በ70 ሚሊዮን ዩሮ የዋጋ ተመን ደግሞ ሳል ኑጎዌዝ ከስፔን፤ ኮኬ ከስፔን ፤ ገብሬል ጂሰስ ከብራዚል፤ ክሪስትያን ኤርክሰን ከስዊዘርላንድ እንዲሁም ጎንዛሎ ሄግዌን ከአርጀንቲና ይገኙበታል፡፡
ከዚህ በታች የቀረበው ደግሞ በዓለም ዋንጫ ከሚሰለፉ 736 ተጨዋቾች  መካከል በክለብ ደረጃ በሚያገኙት ሳምንታዊ ደሞዝ ከ1 እስከ 10ኛ የሚኖራቸው ደረጃ ነው፡፡
ኔይማር (ብራዚል) 509.26 ሺ ዩሮ በሳምንት
ክርስትያኖ ሮናልዶ (ፖርቱጋል) 421.6ሺ ዩሮ  
ሊዮኔል ሜሲ (አርጀንቲና)421.6ሺ ዩሮ  
ሜሱት ኦዚል (ጀርመን) 403.75 ሺ ዩሮ  
ኪላይን ሚባፔ (ፈረንሳይ) 357ሺ  ዩሮ  
ሊውስ ስዋሬዝ (ኡራጋይ) 331.5 ሺ ዩሮ  
ፖል ፖግባ (ፈረንሳይ)  331.5 ሺ ዩሮ  
ሰርጅዮ አግዌሮ (አርጀንቲና) 254.15 ሺ ዩሮ  
ቶኑ ክሮስ (ጀርመን) 229.5 ሺ ዩሮ  
ሰርጂዮ ራሞስ (ስፔን ) 229.5 ሺ ዩሮ  
ባለ ከፍተኛ ዋጋና  ምርጥ 11
የ21ኛው ዓለም ዋንጫ ባለ ከፍተኛ ዋጋና  ምርጥ 11 ተጨዋቾች ቡድን ከ900 ሚሊዮን ዩሮ በላይ እንደሚያወጣ በድረገፁ ያሰፈረው www.transfermarkt.co.uk ነው፡፡ ትራንስፈርማርከት  የዓለም እግር ኳስ የተጨዋቾች ዝውውር ገበያ ታሪክ፤ተመንና የዋጋ ውጣውረድ በማስላት የሚሰራ ታዋቂ ድረገፅ ነው፡፡ የዓለም ዋንጫ ባለ ከፍተኛ ዋጋና ምርጥ 11 ተጨዋቾች  ድረገፁ የመረጠው በ21ኛው የዓለም ዋንጫ ላይ የሚሳተፉት 32 ብሄራዊ ቡድኖች ከሚያሰልፏቸው 736 ተጨዋቾች ነው፡፡ ይህ ቡድን አሰላለፉ 4-3-3 ወይምን 4-3-2-1 እንደሚሆን ድረገፁ ቢያመለክትም ዋና አሰልጣኙ ማን እንደሆነ ግን አልጠቆመም፡፡  
ከዚህ በታች ከ900 ሚሊዮን ዩሮ በላይ የሚያወጣው ቡድን አባላት የቀረበ ሲሆን በመቀጠል ደግሞ የዓለም ዋንጫውን ከፍተኛ የዝውውር ገበያ የዋጋ ተመን  በሚሊዮን ዩሮ ያስመዘገቡ  ተጨዋቾችን ያገኛሉ፡፡
ግብ ጠባቂ
ዴቪድ ዴ ጊያ (ስፔን)    50,00 Mill. €
ተከላካዮች
ማርኩዊኖስ (ብራዚል) 55,00 Mill. €
ራፋኤል ቫርኔ (ፈረንሳይ)     40,00 Mill. €
ማርሴሎ  (ብራዚል)    40,00 Mill. €
ዳንኤል ካርቫሃል (ስፔን)    45,00 Mill. €
አማካዮች
ፖል ፖግባ (ፈረንሳይ)90,00 Mill. €
ቶኒ ክሮስ (ጀርመን) 80,00 Mill. €
ኬቨን ዴብርዋኒ (ቤልጅዬም) 110,00 Mill. €
አጥቂዎች
ክርስትያኖ ሮናልዶ (ፖርቱጋል) 120,00 Mill. €
ሊዮኔል ሜሲ (አርጀንቲና) 180,00 Mill. €
አንቶኒዮ ግሪዝማን (ፈረንሳይ) 100,00 Mill. €

ጥንት ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ዐረብ ፍርድ ቤት ይቀርባል፡፡ የከሰሱት ሶስት ሴቶች ናቸው፡፡ ያለአግባብ ፈቶናል፣ በድሎናል፣ ብለው ነው አቤቱታ ያቀረቡት፡፡
ዐረቡ ቀርቦ እያንዳንዳቸውን፤ “ለምን እንዳባረርካቸው አስረዳ?” ተባለ፡፡
ዐረቡም፤
“የመጀመሪያዋ ሚስቴ ጠዋት ማታ ጭቅጭቅ አበዛችብኝ!” አለ፡፡
“ምን ብላ ጨቀጨቀችህ?” አሉ ዳኛው፡፡
“ነገ ትፈታኛለህ፤ አላምንህም ትላለች፡፡ ሲሰለቸኝ እንደውም ‹ዛሬ ነው የምፈታሽ› ብዬ አስወጣኋት!”
“መልካም፡፡ ሁለተኛዋንስ?”
“ሁለተኛዋ ደግሞ የትላንትናዋን ሚስትህን እንዴት ፈታሃት? እያለች ነጋ - ጠባ ትነተርከኛለች፡፡ ‹አንቺ ስለትላንት ምን አገባሽ? የዛሬን በሰላም ኑሪ› ብላት አሻፈረኝ አለች፤ አባረርኳት!”
“ሶስተኛዋስ?”
“እሷ ደግሞ ‹ለነገ አታስብም› ትለኛለች፡፡ ‹የዛሬን መደሰት ብቻ ነው ፍላጎትህ፡፡ ነገም እኮ መኖር አለብን› ትላለች፡፡ ‹ዝም ብለሽ የዛሬን ተደሰች› ብላት እምቢ አለች - አባረርኳት!”
ዳኛው የሚስቶቹንም ቃል ከሰሙ በኋላ፣ “ፍርድ ቤቱ ሁኔታውን ካየና ግራ ቀኙን አመሳክሮ ከመረመረ በኋላና በተለይም ለማንኛዋም ባለቤትህ ምንም ንብረት አለማካፈልህን በማመንህ፣ አሁን ለሁሉም ካሳ ክፈል ብትባል ስለሚከብድህ፤ ሶስቱንም አግብተሃቸው እንድትኖር ተወስኗል!”
ዐረቡም፤
“ክቡር ፍርድ ቤቱ ትላንትን፣ ዛሬና ነገን አግብተህ ኑር ነው የሚለኝ?”
“አዎን፡፡ ውሳኔው እንደዚያ ነው፡፡”
“ባይስማሙልኝስ?”
“እሱን ስንደርስ እናየዋለን!”
“ነገም አላችሁ ማለት ነው?”
“ፍርድ ቤቱን አትዳፈር! የታዘዝከውን ፈፅም” አሉ ዳኛው በቁጣ፡፡
*   *   *
ፍትህና የፍትህ አካላት ነገር ሁሌም እንዳሳሰበን አለ፡፡ የተከማቹ ፋይሎች ጉዳይ፣ የቀጠሮዎች መራዘም ልማድ፤ እንደጤናማ ሂደት መቆጠር ከጀመረ ዘመናት አልፈዋል፡፡ “የፍርድ ቤት ሙግት አለብኝ” ይሉ የነበሩት አያት ቅድመ - አያቶቻችን ህይወት ዛሬ ይታያል ማለት ጊዜና ሁኔታን ያላገናዘበ ትዝብት ሆኖ ይሰማናል - anachronistic እንዲሉ፡፡ ያም ሆኖ ወደ ትላንት ተመልሰን እየኖርን ነው ባንልም፣ የትላንት ድባብ ስር እንድንጠለል የሆንን ይመስላል፡፡ የጥንት ፍርድ ቤቶች ዋና ሥራ የመሬት ሙግት እንደነበር ይታወቃል፡፡ ዳኞች ‹በጓሮ በር ሙክት ያስጎትታሉ›፤ ጉቦና እጅ መንሻ ምስሳቸው ነው ይባላል፡፡
“ተወኝ ዳኛ አዳኜ፣ የበግ መግዣም የለኝ እጅ እጄን የሚያዩ ብዙ ልጆች አሉኝ” ተብሎ የተገጠመው ቢቸግር ነው፡፡ ዛሬ ስሙ ሙስና የተባለው ጉቦ፤ የቤት ስሙ “ቢዝነስ”፣ “ኮሚሽን”፣ “የሥራ ማንቀሳቀሻ - ጉዳይ ማስፈፀሚያ” መሆኑ አይገርምም፡፡ “ጠበቃ ማንን ያዝክ?” እገሌን። “በጣም ጥሩ ሰው ይዘሃል፡፡ እሱ ዳኞቹን አሳምሮ ያውቃል!” ሙስና ፈርጁ ብዙ ነው፡፡ የፖሊስ ጣቢያ እስረኛ ስልኩ ተወስዶበት፤ በፖሊሱ ሞባይል ወደዘመዶቹ ለመደወል ብዙ ብር የሚከፈልበት አገር ፍትሕ እንዴት እንደሚገኝ ግራ ይገባል፡፡ ይህ ማለት ግን ሀቀኛና ጠንካራ አካላት የሉም ማለት አይደለም -ይዋጣሉ ነው ችግሩ! የሚገርመው በየመስሪያ ቤቱ ሲዘርፍ የከረመው ሁሉ አንደኛ የፍትህ ተቆርቋሪ ሆኖ መገኘቱ ነው፡፡ ዙሪያ - ገባው፣ ከልሂቅ እስከ ደቂቅ “ሌባ! ሌባ!” እያለ እየጮኸ ሳር - ቅጠሉን የሚግጥ ነው! ከቤተ - ሰባዊ የኮንትሮባንድ ንግድ ጀምሮ እስከ ኩባንያዊ ሽቀላ ድረስ አገሩን ያምሳል፡፡ ዛሬ ለበላይ አካል የሚያስፈልገው ጥያቄ የት ቦታ ሙስና አለ? ሳይሆን፤ የት ቦታ ሙስና የለም? የሚለው ነው፡፡ የመፍትሄው ቁልፍ ጥያቄ፤ የበላይ አካልን እገሌ ከእገሌ ሳይሉ መፈተሽ ነው፡፡ ሀቀኛ ጥናት ማካሄድ ነው። በሽርክና የተገባባቸው ንግዶችን፣ የኮንስትራክሽን እንቅስቃሴዎችን፣ በልማት ስም የሚሰሩ ደባዎችን ደፍሮ ማጣራትና ማጥራት ነው! አንድ ፀሐፊ እንደጠየቀው፤ “ይሄ የበላይ አካል ማለት የብዕር ስም ነው እንዴ?” ተብሎ መጠየቅ አለበት፡፡ የበላይ አካል ምስጢር መሆን የለበትም፡፡ በተማሪው ለመተማመን፣ አስተማሪውን መመርመር ነው፡፡ የፍትህ የበላይ አካላት፣ የኢኮኖሚ የበላይ አካላት፣ የፖለቲካ የበላይ አካላት፣ የትምህርት የበላይ አካላት … ሁሉም የበላይ ጠባቂ አላቸው፡፡ ሥረ - ነገራችን እንግሊዞች እንደሚያቀርቡት ጥያቄ “Who guards the guards?” ዓይነት ነው፡፡ “ጠባቂዎቹን ማን ይጠብቃቸዋል?” እንበልና ላዕላይ ጠባቂውንም በጥበብ እንመርምር፡፡

ሁሴን አዳል መሐመድ (ዶ/ር)

    ብሔር ወይስ ብሔረሰብ?
የቀበሌ፤ ወረዳ፤ ዞን ወዘተ ሕዝብ፤ ሕዝብ ነው፤
የብሔረሰብ ሕዝብ፤ ሕዝብ ነው፡፡
የብሔር ሕዝብ፤ ሕዝብ ነው፤
የኢትዮጵያ ሕዝብ፤ ሕዝብ ነው፡፡
ሕዝብ = አገር
አገር = ሕዝብ
ብሔር/ብሔረሰብ ሕዝቦች እያሉ በደፈናው ማነብነብና መጻፍ በአገራችን የተለመደ ነገር ሆኗል፡፡ የማህበረሰባዊ ጽንሰ ሓሳብ መግለጫዎች የሆኑት ሁለቱ ቃላት፤የአገራችን ፖለቲካ ንድፈ-ሓሳብ ማጠንጠኛ እንዲሆኑ በመደረጉ የማንም ባለ ወቅት ፖለቲከኛ ሰው፤ የፖለቲካ አፍ መፍቻ ይሁኑ እንጂ ከአገራችን ሕዝብ ተጨባጭ ሁኔታ አንጻር በእነዚህ ሁለት ቃላት መኻል ያለው አንድነትና ልዩነት በትክክል የሚታወቅ አይመስልም፡፡ ይህ ሆኖ እያለ ግልጽ ካልሆነ ጽንሰ-ሓሳብ ላይ ተነስቶ ቃላቱን የሕገ መንግሥት አንቀጽ አድርጎ እስከ መሄድ የተደረሰው በድፍረት መሆኑ በእጅጉ ያስገርማል፡፡
ብሔር/ብሔረሰብ፤ የማርክሲስት/ሌኒኒስት የማህበረሰብ ዕድገት ታሪክ፣ ቁስ አካልነት፣ ፍልስፍና ጽንሰ-ሐሳብ ሲሆን አንዱ ወይም ሌላው የሚገለጸው ከህብረተሰብ ታሪክ ወቅት ጋር ባለው ተዛምዶ፣ በአንድ የተወሰነ የታሪክ ወቅት የሚኖር ማህበረሰብ በማለት እንጂ በግል ስሜት አይደለም፡፡ ብሔረሰብን በዝቅተኛ የኢኮኖሚ ደረጃ ማለትም በፊውዳላዊ ወይም ቅድመ ካፒታሊዝም የኢኮኖሚ ደረጃ ውስጥ የሚገኝ ማህበረሰብ እንደሆነ ሲገልጹ፤ ብሔር ደግሞ ከፊውዳሊዝም መክሰም በኋላ ከካፒታሊዝም ማደግ ጋር ተያይዞ የተዋሃደና በከፍተኛ የዕድገት ደረጃ ላይ ያለ፣ የጋራ ኢኮኖሚ ሕይወት ያለው ማህበረሰብ እንደሆነ ይገልጻሉ፡፡ ከዚህ ጽንሰ-ሐሳብ አኳያ አሁን በአንድ ክፍለ ዘመን እየኖሩ ካሉት የኢትዮጵያ ብሔረሰቦች ሕዝቦች የትኛው፣ በየትኛው የታሪክ ወቅት እየኖረ ነው? ኢትዮጵያ አሁን በስንት የታሪክ ወቅት ውስጥ ትገኛለች? ብሔሩ የየትኛው አስተዳደር ክልል ሕዝብ ነው? ብሔረሰቡስ? ደቡብ፤ ኦሮሞ፤ አማራ፤ ትግራይ፤ ሱማሌ፤ አፋር፤… ብሔር ወይም ብሔረሰብ ለመሆን አሟልተው የተገኙት መስፈርት ምንድን ነው? የትኛው በፊውዳሊዝም ስልተ-ምርት ይገኛል? ወደ ካፒታሊስት ስልተ-ምርት እየገሰገሰ ያለ ወይም የሚያደርገውን ሽግግር ያጠናቀቀው የትኛው ነው? እያንዳንዱ መልስ የሚያሻው ጥያቄ ነው፡፡ ስለ ፌደራሊዝምና ዲሞክራሲያዊ ብሔረተኝነት የሚኖረን ዕውቀት፣ ከማነብነብ እልፍ እንዲል ከፈለግን፣በሁለቱ ላይ የጠራ ግንዛቤ መያዝ ያስፈልገናል፡፡
በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ (ቀ.ኃ.ሥ.ዩ) ታጋይ ተማሪዎች የተራገበው፣ በአገራችን ተጨባጭ ሁኔታ ላይ ያልተመሰረተው የማርክሲስት/ሌኒኒስት፣ የብሔር/ብሔረሰብ ጽንሰ-ሓሳብ፣ የሜዳ ትግል ስልት የመረጡትን ወጣቶች፣ በአገራችን ታሪካዊ ጠላቶችና ባልነቃ ብሶተኛ ሕዝብ ድጋፍ፣ ለሁለት አስርተ ዓመታት ጫካ ውስጥ አክርሞ፤ በጦር ሜዳ ያልተሰውቱን ታጋዮች፣ ለቤተ መንግሥት ከማብቃቱ በስተቀር በጽንሰ-ሓሳቡ ላይ የጠራ ግንዛቤ ባለመያዙ፣ ለችግሩ መቋጫ የሚሆን መፍትሔ እስከ አሁን አልተገኘም፡፡ አገራችን ሌላ ዙር ትርምስ የሚጠብቃት ይመስላል፡፡ በደርግ ላይ ድል መቀዳጀት፣ አጼ ምኒልክ ቤተመንግሥት ካስገባ በኋላ፣ ቀ.ኃ.ሥ.ዩ ተጠንስሶ፣ ጫካ ውስጥ ተደፍድፎ፣ የፈላውን ያልጠራ ጽንሰ-ሓሳብ የመንግሥት/ገዥ ፓርቲ የፖለቲካ ሰነድ በማድረግ፣ ማንኛውንም ሓሳብ ሳያቅማሙ የሚቀበሉ ዜጎችን ከየብሔረሰቡ ተወላጆች አስጠግቶ በመጋት፣ በእነርሱ መንኩራኩርነት ለማስፋፋት የተደረገው የትግል እንቅስቃሴ፤ ሕዝባችንን ለእንግልት፤ አገራችንን ለውርደት አጋልጧል፡፡
በቅጡ ካልተረዱት ጽንሰ-ሓሳብ በመነሳት የጠባብ ብሔረተኝነት ትግል አስፈላጊነትን በእንጭጭ አእምሯቸው በመቀበል፣ ለአገራችን ታሪካዊ ጠላቶችና የገዥ መደብ ዝንባሌ ለነበራቸው ቡድኖች ፍላጎት ማሳኪያ በረሐ ገብተው፣ የተደናበረው ትግል ትሩፋት ተቋዳሽ ሆነው ከቆዩ በኋላ፣ ዘግይተውም ቢሆን ሁኔታዎችን በሰከነ አእምሮ ማገናዘብ የቻሉ፣ ራሳቸውን ወደ ዳር ያገለሉ፣ አንዳንድ የቀድሞ ወጣቶች/የአሁኖቹ አዛውንቶች፣ ላሳለፉት የዜሮ ድምር የበረሐ ትግል ፍጻሜ፣ በየተራ እየተጸጸቱ ንስሐ በሚገቡበት በአሁኑ ጊዜ፣ “ጉድ ሳይሰማ አይታደርም” እንዲሉ፣ የአገራችንን የመከራ ዘመን ለማራዘም መጥበብ በማይችል ብሔረሰብ ስም ጭምር የጠባብ ብሔረተኝነት ትግል ጥንስስ የሚጠነስሱ፣ የማህበረሰብ ክፍሎች ብቅ ብቅ ማለታቸው አስደንጋጭ ነው፡፡
እዮሃ! እዮሃ!
የጎመኑ ዘመን ውጣ፤ የጮማው ግባ እንዲሉ፤
የብሔረሰብ ፓርቲ ዘመን ይሻር፤
የርዕዮተ ዓለም ፓርቲ ዘመን ይንገሥ፡፡
--እንደ ማለት፣ የጠባብ ብሔረተኝነት ገመድ በመጓተት፣ አገራችን ከአንዱ የዘመን አሮንቃ ወጥታ በሌላ የዘመን አሮንቃ! ውስጥ እንድትርመጠመጥ ይተጋሉ፡፡ በወዳጅና ጠላትነት ሁልጊዜ በደም ስንፈላለግ እንድንኖር ይሻሉ፡፡ ቀጥሎ የቷን “ብሔር”፣ “ህብረተሰባዊ ዕረፍት ለማሳጣት” ነው፡፡ እሺ ቀጥሎስ? ወደ ቀድሞ ገናናነታችን የሚመልሱን ሠረገላዎች፣ የብሔረሰብ ፓርቲዎች ይሆኑ እንዴ? በርካታ ብሔረሰቦች ሕዝቦች በሚኖሩባት ውድ አገራችን፣ የሚፈጠር የፖለቲካ አስተሳሰብ ቅኝት፣ ሁሉንም የአገሪቱን ዜጎች ሊያሳትፍ ከሚችል የጋራ ርዕዮተ ዓለም አውድ ይልቅ በብሔረሰቦች ልዩነቶች ላይ እንዲመሰረት የሚደረግበት ምክንያት ምንድን ነው? እርግጥ ነው፤ የፖለቲካ አስተሳሰብ ቅኝትን በርዕዮተ ዓለም አውድ ላይ እንዲያተኩር ማድረግ የፖለቲከኛን የአስተሳሰብ ከፍታና በሰፊ የፖለቲካ ስነ ምህዳር ውስጥ በነጻ መወዳደርን ይጠይቃል፡፡ ይህ አቅም በሌለበት፤ ዘወትር በኪራይ ሰብሳቢነት ለመኖር በጠባብ ብሔረተኝነት የፖለቲካ አንቀልባ መታዘል፣ አዋጭ የፖለቲካ አማራጭ ይሆናል፡፡   
ኤሎሄ ኤሎሄ፤
ለማ ሰበቅታኒ፡፡
ከእንግዲህ ወዲያ የብሔረሰብ ፓርቲ ስህተት፣ ያለፈ ታሪካችን አካል ሆኖ መቅረት እንጂ መቀጠል የለበትም። ምንም እንኳ ለጠባቦች የኪራይ መሰብሰቢያ፣ጊዜያዊ የንግድ ፈቃድ ወረቀት ሆኖ ቢያገለግልም ያለፈው ስህተት ያስከተለው ዕዳ፣ የብሔረሰቡ ሕዝብ ዕዳ ብቻ ከመሆን አልፎ ለሌሎች ብሔረሰብ ሕዝቦች በአጠቃላይ ለመላው የኢትዮጵያ ሕዝብ የተረፈ የጋራ ዕዳ ነው፡፡ እርግጥ የአማራ ብሔረሰብ ሕዝብ በይበልጥ ስለመጎዳቱ አስረጂዎች በግልጽ እየቀረቡ ይገኛል፡፡
የብሔረሰብ ፓርቲ፤ ዘመን ተሻጋሪ፣ መልካም ውርስ አይደለም፡፡ ጠባቦችን ላለፈው ስህተታቸው ንስሐ ለማስገባት ግፊት ማድረግ እንጂ ፈለጉን በመከተል አዳዲስ የብሔረሰቦች ፓርቲዎችን መፍጠር ለምንወዳት አገራችን፤ ኢትዮጵያ አንድነት መቀጠል አይረባንም፡፡ አገራችን ተነጣጥለው የቆሙ ብሔረሰቦች ሕዝቦች የሏትም፡፡ ለምሳሌ በአማራ ሕዝብ ስም ጠባብ የብሔረሰብ ፓርቲ አቋቁሜ እታገላለሁ የሚል ቡድን ቢነሳ፣ ሁኔታው ከማስደንገጥ አልፎ ያስፈራል፡፡ ይህ የማይቀር የሚሆነው ሌሎች ከጠባብነት ሐዲድ መውጣት ተስኗቸው፣ ያንኑ የጠባብነት ገመድ ነክሰው ባሉበት እየረገጡ ከቀጠሉ ብቻ እና ብቻ መሆን ይኖርበታል፡፡ ያኔ! ለአማራ ሕዝብ መጥበብ የሕልውና ጥያቄ ስለሚሆንበት የጠባብ ቡድን ዓላማን መሸከም የግድ ይላል፡፡ በኢትዮጵያዊነቱ የሚኮራ፤ ለኢትዮጵያ አንድነት ዘብ የሚቆም ትምክተኛ ሕዝብ በመባል በጠባብ ቡድን ኃይሎች ሲጠራ የኖረ ታላቅ ሕዝብ፤ እሱነቱን እንደ ባዶ ስልቻ አቅልሎ ወደ እዚህ ዝቅተኛ ደረጃ መድረስ ግድ ከሆነበት የጠባብነት ትግሉን ፈር ለማስያዝ፣ በመጀመሪያ የአማራ ሕዝብን አገር ወሰን ዳርቻ ማስመር፤ ብሎም ከዳር ድንበሩ ውጭ ስለሚኖረው የአማራ ሕዝብ ዕጣ ፈንታ ሁነኛ አቅጣጫ ማስቀመጥ ግድ ይለዋል፡፡
“የእኛ ቡድን ብሔር መሬት ያን ሁሉ ያጠቃልላል”፤ “ጨቋኟ የአማራ ብሔር፣ ህብረተሰባዊ ዕረፍት አታገኝም” እያለ ሲወተውት የነበረ ጠባብ ቡድን፤ በምስጢር የነደፈው የአስተዳደር ክልሎች አወቃቀር ለአገራችን እንደ ማይበጅ አንዳንድ ነባር የቡድኑ አባላት በጸጸት ስሜት ምስክርነት እየሰጡ ነው፡፡ የኤርትራ ከእናት አገሯ መገንጠል፤ አገራችን የባህር በር ማጣት፣ ኢሕአዴግ የፈጸመው ታሪክ ይቅር የማይለው ጥፋት/ንዝህላልነት መሆኑን ሳያወላውሉ በማውገዝ፣ ላለፈ ክረምት ቤት ከሚሠሩ ነባር ታጋዮች ጎን ለጎን፣ ልቦና የማይገዙ ደቀ-መዝሙሮች መኖራቸው ያስገርማል፡፡
ፌደራሊዝምና ዴሞክራሲያዊ ብሔረተኝነት፤ “የአገራችን ሕልውናና የአብሮነት መሰረቶች” ናቸው የሚለውን ጥርት ያለ ሐቅ የሚክድ ዜጋ ያለ ይመስል፣. ዘወትር ንግግር በማሳመር፣ እምቧ ከረዩ የሚሉ አንዳንድ የመንግሥት/የገዥ ፓርቲው ባለስልጣናት አሉ፡፡ ችግሩ ፍትሐዊ በሆነ መንገድ አለመተግበሩ ስለመሆኑ መናገር ድክመት መስሎ ይታያቸዋል፡፡ ዴሞክራሲያዊ ብሔረተኝነት ያለ መከባበርና መዋደድ አይመጣም፡፡ በፌዴራሊዝምና ዴሞክራሲያዊ ብሔረተኝነት ዙሪያ በአገራችን የነበረው ያለፈ ዘመን መልካም ገጽታ፤ በአሁኑ የአስከፊ ዘመን መስታወት ውስጥ በግልጽ እየታየ ለመሆኑ ከዚህ በላይ ማስረጃ የለም፡፡ እስካሁን ድረስ በአገራችን የሰፈነውን የአተገባበር ጉድለት መንስዔ፤ ዓላማና ግብ እንደዚሁም ፋይዳ የሚያውቁት ምስጢረኞቹ ብቻ ነበሩ፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን የምስጢሩ እሽግ ፖስታ ተከፍቶ በመነበቡ ምክንያት ምስጢሩ ለአብዛኛው ዜጎች ግልጽ ሊሆን በመቻሉ፣ ሕዝቡ በዕውቀት ላይ ለተመሰረተ ትግል ተነሳስቷል፡፡
ባለፉት 27 ዓመታት አገራችን ክፉኛ አዘቅት ውስጥ የወደቀችበት ችግር መንስኤው የፌደራሊዝም ቅርጸ-መንግሥት መዘርጋቱ ሳይሆን የፌደራሊዝም ስርዓቱን ያዋቀርንበት መርህ-አልባ የአወቃቀር ንድፍ ነው፡፡ ጥቂት መገለጫዎችን እስቲ እንይ፡
አንዳንዴ ቋንቋን ወሳኝ መስፈርት በማድረግ ማህበረሰቦች የምንነት ጥያቄ ይዘው እንዲቀርቡ በማድረግ ለቀረበ የምንነት ጥያቄ አስቸኳይ ምላሽ ይሰጣል፤ አዲስ የአስተዳደር ክልል ወዲያውኑ ይፈጠራል ወይም ማህበረሰቦች ወደ አንዱ ክልል ይካተታሉ፤
ቋንቋውን ባይችልም ተካትቶ ሲያበቃ፣ ቋንቋ እንዲማር የሚወሰንበትም አለ፤
ቋንቋው ጭራሽ በመጥፋቱ የተነሳ በሚናገሩት ቋንቋ ብቻ ከሌላው ምንነታቸውን መለየት የሚያስቸግሩትን የማህበረሰብ ክፍሎች፤ በመንግሥት ድጋፍ፤ የምንነት መጠሪያ ስም አውጥተው ከነባር የማህበረሰብ ዘውግ እንዲለያዩ ይደረጋል፤  
የምንነት ጥያቄ ማቅረብ የሚያስጠይቅበት እና የምንነት ጥያቄ እንዲቀርብ ግፊት የሚደረግበት ክልል ጎን ለጎን አለ፡፡
“ከልጅ ልጅ ቢለዩ በሞት ይለዩ” የሚሉ ማህበረሰቦች ደግሞ ጆሮ ዳባ ልበስ ይባላሉ፡፡
በማይመስለን ክልል ተቀርቅረናልና፣ መልሱን፣ የሚሉ ማህበረሰቦች ደግሞ መከራ ይከፍላሉ። ማህበረሰቦቹ ይመስለናል የሚሉት ክልላዊ አስተዳደር፤ አንዴ አሳልፎ ለሌላው ስለሰጣቸው ፊት ይነሳቸዋል፤ የወሰዳቸው ክልል ደግሞ መብታቸውን በመጠየቅ፣ ክፉኛ አሳጡኝ በሚል “ካፈርኩ አይመልሰኝ” ድርቅና ነገሮችን ሁሉ ያጠብቅባቸዋል፡፡ መብትን መጠየቅም ስለሚያስጠይቅ ማህበረሰቦቹ በ”እከክልኝ፣ ልከክልህ”ተደጋግፎት ይሰቃያሉ፡፡
ማህበረሰቦቹ በሰሚ ዕጦት፣ ከሁለት የወጣ ጎመን ሆነው በመንከራተት፣ከመጠውለግ ወደ መድረቅ ተጠግተዋል፡፡ የወልቃይት፤ የራያ ሕዝቦች ችግር ይኸው ነው፡፡
ብሔረሰባዊ ምንነት ተፈጥሯዊ የሆነና ማንኛውም ሰው ከተገኘበት ብሔረሰብ ጋር አብሮ የሚወለድ ወይም በማህበራዊ መስተጋብር በሚፈጠር አጋጣሚ ወይም በምርጫ የሌላውን ብሔረሰብ ምንነት በመያዝ ሊገኝ እንደሚችል ተቀባይነት ያገኘ መርህ ነው፡፡ ከዚህ መርህ አንጻር የአንድ ብሔረሰብ ቋንቋ ተናጋሪ መሆን ብቻውን ለብሔረሰባዊ ምንነት አያበቃም፡፡ ቋንቋ ብቻውን ብሔረሰባዊና አገራዊ ምንነትን ገላጭ ዋና መስፈርት ተደርጎ ሊወሰድ አይችልም፡፡ በሚናገሩት ቋንቋ ብቻ ማህበረሰቦችን፣ የዚህ ብሔረሰብ አባላት ናቸው ማለት ቋንቋ የሚጋሩ የሁለት ጎረቤት አገሮች ማህበረሰቦችን፣ የአንድ አገር ዜጎች ናቸው ማለት ያለመቻል ያህል ነው፡፡
ለሚቀርቡ የምንነት ጥያቄዎች በርካታ መስፈርቶችን ተጠቅሞ፤ ከሁሉም በላይ ደግሞ የማህበረሰቡን ታሪካዊ ዳራ አጥንቶ፤ በማህበረሰቡ ፍላጎት ላይ ተመስርቶ፤ በጥንቃቄ ተመልክቶ፣ በወቅቱ መልስ የማይሰጥ ከሆነ፣ እንዲሁም አድሏዊ አሰራር ካለ፤ የቃልና የተግባር አንድነት እጥረት አጋጥሟል፤ ተቀባይነት አግኝቷል የሚባለው መርህ ተጥሷል ማለት ነው፡፡ ለምንነት ጥያቄ መልስ በሚጠብቅ ማህበረሰብና ጉዳዩ በሚመለከተው ውሳኔ ሰጭ አካል መኻል፣ የጥቅም ግጭት የወለደው ቅራኔ ይታያል፡፡ እቅጩን ለመናገር ደጋግሞ መነገር ያለበት ጉዳይ በአገራችን የደረሰው ህብረተሰባዊ ችግር መንስዔው ለድብቅ የቡድን ፍላጎት ማሳኪያ ሲባል፣ በፌደራሊዝም ስም፣ ሕዝቡን በቋንቋ ግድግድ አጥር አካልሎ በማናቆር የተፈጠረው የመልካም አስተዳደር ችግር ነው፡፡ ሕዝቡ የሚያነሳቸው ኢ-ፍትሐዊ የሐብት ክፍፍል፤ ሙስናና ሌሎች ጥያቄዎች፣ በተዋረድ የሚገኙ የዋናው ችግር መገለጫዎች ናቸው፡፡
በብዝህነት ላይ ሲያተኩር ለሕዝቦች አንድነት ዝቅተኛ ትኩረት የሰጠው በብሔረሰብ ምንነት መስፈርት ላይ የተመሰረተው አዲሱ የአስተዳደር ክልሎች አወቃቀር፣ ወደ ፊት የሚያስከትለውን ችግር ባለማጤን ማህበረሰቦችን ያለ ይሁንታቸው ለዘመናት አብሮ በመኖር በጋራ ከመሰረቱት የማህበረሰብ ዘውግ በማፈናቀል ለያይቷቸዋል፡፡ የአካባቢ አስተዳደር አወቃቀሩ በአካላዮቹ ራዕይ መሰረት፤ በቋንቋ ልዩነት ላይ የተገነባ በመሆኑ ዜጎችን በአገራቸው የሚኖሩ ባይተዋሮች አድርጓቸዋል፡፡ ይህ ሆኖ እያለ አዲሱ የአስተዳደር ክልሎች አወቃቀር ተበታትነው የቆዩ የብሔረሰብ ሕዝቦችን አንድ ላይ በማሰባሰብ በብሔረሰቦች ሕዝቦች መካከል ጠንካራ ግንኙነት ለመፍጠር ያስቻለን ህብረተሰባዊ ዕድገት ነው በማለት ይቀለዳል! “ዓሳን ከባሕር አውጥቶ ማንሳፈፍ፣ ለጭልፊት ርሕራሄ ይመስላታል” እንዲሉ አበው! ዳሩ ግን ምንም ያህል ጠቃሚ ይሁንም አይሁንም፤ አዲሱ የአካባቢ አስተደደር ክልል አወቃቀር የተከናወነው ከሕዝብ ውሳኔ ውጭ ነበር፡፡ የባለራዕዮችን ውሳኔ ዝም ብሎ እንዲቀበል ነው የተደረገው፡፡ ሕዝቡ ከክልል ስያሜ አሰጣጥ ጀምሮ አልመከረበትም፡፡ ክልሎች በመነሻው ላይ በቁጥር ተሰየሙ፤ ቀጥሎ ስም ሲወጣ እያንዳንዱ ስም እንዴት እንደወጣ ሕዝቡ አያውቅም። በመጨረሻም ያስከተለው ውጤት ታየ፡፡ አብዛኛው ዜጋ የስነልቦና ጉዳቱን ተሸክሞ፣ ከዚህ የተሻለ ቀን በተስፋ እየጠበቀ ነው፡፡   (ይቀጥላል)


    በህክምና ባለሙያው ቸርነት ገብረ ክርስቶስ የተፃፈው በህክምና ላይ የሚያጠነጥን “ዲባቶ” የተሰኘ መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡
መፅሐፉ በዋናነት በህክምናው አለም ያሉ የአካሚና የታካሚ እውነቶችን በስነ ፅሑፍ ለዛ እያዋዛ እውቀትና ግንዛቤ የሚያስጨብጥ ነው ተብሏል፡፡ በ371 ገፆች የተቀነበበው መፅሐፉ በ160 ብር እና በ20 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡  

 በኢትዮጵያ ለመጀመሪያ ጊዜ በአገር አቀፍ ደረጃ የመገናኛ ብዙኃን ሽልማት ሊካሄድ መሆኑን የሽልማት አዘጋጁ ዋይጂኤስ መልቲ ሚዲያ አስታወቀ፡፡ የሽልማት ሥነ ሥርዓቱ በብሮድካስት ባለስልጣን እውቅና እንዳገኘ የገለፁት የድርጅቱ ኃላፊዎች፤  የሽልማት ሥነ ሥርዓቱ ነሐሴ 26 ቀን 2010 ዓ.ም በብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ እንደሚካሄድ ጠቁመዋል፡፡
በዕለቱም በህትመት፣ በብሮድካስትና በድረ ገፅ መገናኛ ብዙኃን ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያደረጉና የተመረጡ ጋዜጠኞች እንደሚሸለሙ ተገልጿል፡፡ ተሸላሚዎች የሚመረጡት በዘርፉ የካበተ ልምድና ብቃት ባላቸው የመገናኛ ብዙኃን ባለሙያዎች ዳኝነት እንደሆነም ለማወቅ ተችሏል፡፡ የሽልማቱ አዘጋጅ ዋይጂኤስ መልቲ ሚዲያ ከአሁን በፊት የተለያዩ የኪነ ጥበብ መድረኮችን በማዘጋጀት የሚታወቅ ሲሆን በአሁኑ ወቅት በብስራት ኤፍ ኤም ሬዲዮ ላይ “ማራኪ” የተሰኘ ፕሮግራም የሚያቀርብ ድርጅትም ነው፡፡

የእውቁ ፖለቲከኛና መሐንዲስ ኢ/ር ዘለቀ ረዲ፣ “የ21ኛው ክ/ዘመን መሳፍንትና ኢትዮጵያን እንደ ሀገር የማስቀጠል ፈተና” የተሰኘው መፅሐፍ የፊታችን ሰኞ ከቀኑ 11፡00 ጀምሮ በዋቢ ሸበሌ ሆቴል ይመረቃል፡፡
በምርቃት ስነ ስርዓቱ ላይ የመፅሐፉ  ዳሰሳ (review)፣ እንዲሁም ከመፅሐፉ የተመረጡ ክፍሎች የሚቀርቡ ሲሆን ውይይትም ይደረጋል ተብሏል፡፡

• የብሔር ፖለቲካ ባለበት፣ ሊበራል አስተሳሰብ በድንገት ቢመጣ ጥሩ አይሆንም
  • ከኤርትራ ጋር መደራደር ስለተፈለገ ብቻ መደራደር ይቻላል ወይ?
  • የጠ/ሚኒስትሩ የጎረቤት አገራት ጉብኝት አንደምታው ብዙ ነው

    ታዋቂው የፖለቲካ ሣይንስ ምሁር ፕ/ር መድህኔ ታደሰ በዶ/ር አብይ ሰሞንኛ እንቅስቃሴዎች ፣ በኤርትራ እና ኢትዮጵያ ግንኙነት፣ በቀይ ባህር ጉዳይ... ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ ጋር ተከታዩን ቆይታ አድርገዋል፡፡
      ፕ/ር መድህኔ ታደሰ (የፖለቲካ ተንታኝ)


    የጠ/ሚኒስትሩን የሥራ እንቅስቃሴ እንዴት አገኙት? በተለይ በክልሎች እየተዘዋወሩ፣ ከህዝብ ጋር የሚያደርጓቸው ንግግሮችና ውይይቶች? ----
የጠቅላይ ሚኒስትሩ እንቅስቃሴ በአጠቃላይ ከፖለቲካዊ ማዕቀፍ አንፃር ነው መታየት ያለበት። የእሳቸው ቅቡልነት ከኢህአዴግ ውጪ ባሉትም ያመዘነበት፣ የህዝብን ስሜት የያዙበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ በየአካባቢውና በየክልሉ ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር መወያየታቸው፣ ቅቡልነታቸውንና ተፈላጊነታቸውን የሚያሳድጉበት አንድ መንገድ ነው። በሌላ በኩል ከነበረው የጨለምተኝነትና የስጋት ስሜት፣ ህዝቡንና ሀገሪቱን ተስፋ ወደሚፈነጥቅበት ምዕራፍ ለማሸጋገር የተጠቀሙበት አካሄድ ነው ተብሎ ሊወሰድ ይችላል፡፡ መንግስት ከአሁን በኋላ ህዝቡን እያዳመጠ፣ የተለያዩ ፖለቲካዊ ማሻሻያዎች፣ የፖሊሲ ማሻሻያዎች ወዘተ-- ማድረግ አለበት፡፡ ለዚህ ደግሞ ከህዝቡ ጋር እንዲህ ባለው መንገድ ቀጥታ ተገኝቶ መወያየት ጠቃሚ ነው፡፡ ከህዝቡ የሚያገኙት ግብአት፣ ፖሊሲያቸውን ለመቀመር ያስችላቸዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ በድርጅታቸው የተሟላ ድጋፍ ባያገኙም በመጪው ነሐሴ ጉባኤ ማካሄዱ አይቀርም። እስከዚያው ድረስ ከህዝቡ ጋር ተነጋግረው፣ የድርጅታቸውን የወደፊት አቅጣጫና ትክክለኛ ማንነት በሚያስረግጥ መልኩ ስራዎች ለመስራት ከተፈለገ፣ እንደዚህ አይነት እንቅስቃሴዎች ማድረግ ተገቢ ነው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ብዙ ነገር እያደረጉ ነው፡፡ አሁን ባለው ተጨባጭ ሁኔታ ከዚህ በላይ  ማድረግ የሚችሉ አይመስለኝም፡፡
ጠ/ሚኒስትሩና የሚመሩት ድርጅታቸው ኢህአዴግ ምንና ምን ናቸው ?
ግንባሩ በድርጅት የማንነት ቀውስ ውስጥ ነው ያለው፡፡ የእሳቸው ወደ ስልጣን አመጣጥ አንደኛው ምክንያት፣ የፖለቲካ ውጤት ብቻ ሳይሆን አንድ የተቀየረ ነገር እንዳለ አመላካች ነው፡፡ ኢህአዴግ ድሮ የሚመራበትና ራሱን አጥሮ የሚያስርበት ዲሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት፣ የተዳከመበት ደረጃ የደረሰ ይመስለኛል፡፡ እሳቸው የተለየ፣ ወደ ሊበራል የሚያደላ፣ ለዘብ ያለ የፖለቲካ መስመር የመያዝ አዝማሚያ ነው የሚታይባቸው፡፡ ሊበራል አመለካከት ሲባል እንግዲህ ኒዮሊበራል ነው ወይስ--? የሚለውን ማየት ያስፈልጋል፡፡ በሂደት መውጣቱ አይቀርም፡፡ በፓርቲው ውስጥ የሚደረገውን ውስጠ ትግል፣ከህዝብ ተፈላጊነትና ቅቡልነት አንፃር ለማካሄድ የፈለጉ ይመስለኛል፡፡  አጠቃላይ እንቅስቃሴያቸው፤ፖለቲካዊ ነው ማለት ይቻላል፡፡ እንቅስቃሴያቸው በኢህአዴግ ውስጥ ያለውን የኃይል ሚዛን ጭምር ታሳቢ ያደረገ ነው የሚመስለው፡፡ የመጡበት መንገድ ሲታይ፣ የሚሄዱበትም መንገድ፣ የፖለቲካ ውድድርና ፉክክር የሚታይበት ስለሆነ፣ ለዚያ ውድድርና ፉክክር፣ የተወሰነ እምቅ አቅም ለማግኘት ያሰቡ ይመስላል፡፡
ጠ/ሚኒስትሩ፤ የሀገሪቱን የፖለቲካ ችግሮች መፍታት ከፈለጉ፣ በቅድሚያ ከፖለቲካ ኃይሎች ጋር ድርድር ማድረግ አለባቸው የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ እርስዎ  ምን ይላሉ?
ምን ይዘው ነው በቅድሚያ ከፓርቲዎች ጋር ይደራደሩ የሚባለው? ለመደራደር ፍኖተ ቀመር ያስፈልጋቸዋል፡፡ እኚህ ሰው ወደ ስልጣኑ የመጡት በፓርቲው የውስጥ ዲሲፕሊንና አሰራር ተደግፈው አይደለም፡፡ በአለመስማማት መሃል ነው የመጡት። የተለያዩ የኃይል እና የስልጣን ማዕከላት፣ የተለያዩ የተቃዋሚ ኃይሎች---ባሉበት ሀገር፣ በመጀመሪያ ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች ጋር ተነጋግረው፣ የህዝቡን ፍላጎት እንዲታይ አድርገው፣ ፓርቲያቸውን ማስተካከልና መለወጥ አለባቸው፡፡ ይሄን መልክ ሳያስይዙ፣ በምን መልክ? በምን ሰነድ? በምን ፍኖተ ካርታ? ነው ሊደራደሩ የሚችሉት? በሌላ በኩል ጠ/ሚኒስትሩ ይዘውት የመጡት አስተሳሰብ አለ። ሙሉ ለሙሉ ከኢህአዴግ ባይለይ እንኳ በተወሰነ አቅጣጫው ሊለይ ይችላል፡፡ ኢህአዴግ ውስጥ ባለው የሃሳብ የበላይነት ተፈትሾ ነው ተግባር ላይ የሚውለው። እሳቸው አዲስ አቅጣጫቸውን መሬት ባላወረዱበት ሁኔታ እንዴት አድርገው ነው ከተቃዋሚዎች ጋር የሚደራደሩት? ተቃዋሚዎችስ ምን ያህል ለድርድር ተዘጋጅተዋል? የሚለው አጠያያቂ ነው፡፡ ይሄ አሁን የሚያደርጉት እንቅስቃሴ፣ ሃሳባቸውን ለህዝቡም ለፓርቲያቸውም ይፋ እያደረጉ፣በሀሳባቸው ዙሪያ ኃይል የሚያሰባስቡበት ነው የሚሆነው፡፡  
ለወደፊት ስትራቴጂ ቀርፆ ለመደራደርና የፖሊሲ ለውጥ ለማምጣት ይሄ አካሄዳቸው ጠቃሚ ነው። ወደ ሊበራል አቅጣጫ ለመሄድም ብዙ ጥናት የሚጠይቅ ነገር አለ፡፡ ዝም ብለው ቸኩለው ከገቡበት ለራሳቸውም ለፓርቲያቸውም ለሃገርም አይበጅም። የብሔር ፖለቲካ ባለበት ሃገር፤ ሊበራል አስተሳሰብ በድንገት ቢመጣ ጥሩ አይሆንም፡፡ በሂደት ነው ነገሮች መታየት ያለባቸው፡፡ ለምሳሌ አንዳንዱ፣ ለምን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ አልተነሳም ይላል፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ለፖለቲካ ውድድር በሚያመች መልኩ መቀመር አለበት፤ በተለይ የፀጥታና የደህንነት መዋቅሩ፡፡ እሳቸው የሚያመቻቸውን የአካባቢያዊና አጠቃላይ ሀገራዊ የደህንነት ሁኔታ መፍጠር አለባቸው፡፡ ይሄ ደሞ ጊዜ ይፈልጋል፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ይነሳ የሚለው ጥያቄ፤ አሁን ያለውን ሽኩቻና ችግር በጥልቀት ካለመረዳት የሚመነጭ ይመስለኛል፡፡
በጎረቤት አገራት ያደረጓቸው ጉብኝቶች---እንዴት ይገመገማሉ?
እነዚህ ጉብኝቶች በሶስት አቅጣጫ ነው መተንተን ያለባቸው፡፡ አንዱ የተለመደው የጉርብትና እና የዝምድና አቅጣጫ ነው፡፡ ይሄ ኢኮኖሚውንም፣ ፀጥታውም ይነካል፡፡ አላማውም እነዚህን ነገሮች ማጠናከር ነው፡፡ ሁለተኛው አካባቢያዊ አንድምታው ነው፡፡ አካባቢያዊ አንድምታው ሲባል የኤርትራ የደቡብ ሱዳን፣ የሶማሊያና የቀይ ባህር አካባቢ ሁኔታ ማለት ነው፡፡ ሶስተኛው የውስጥ የፖለቲካ አንደምታ ነው። ወደ ሱዳን ሲኬድ፣ ወደ ኬንያ ሲኬድ፣ ወደ ጅቡቲ ሲኬድ ብዙ የሚያገናኙን ነገሮች አሉ፡፡ ለምሳሌ፡- ወደ ጅቡቲ ሲኬድ፣ የአፋርና የኢሳ ጉዳይ አለ፡፡ በሶማሌና በኦሮሚያ ያለውን አንዳንድ ያልተገባ ሁኔታ ማንም የሚያውቀው ነው፡፡ ይሄ ከጅቡቲ ሱማሌዎች ጋር በምን ይገናኛል? የአፋር ጉዳይም አለ፡፡ ስለዚህ በሦስተኛ ደረጃ መታየት ያለበት፤ የኢትዮጵያን የፖለቲካ ሁኔታ፣ በውስጥ በራሳቸው ስልጣን የማጠናከር ጉዳይ ነው፡፡ ይሄን ካላደረጉ የአካባቢ ህልው አደጋ ላይ ይወድቃል ማለት ነው፡፡ ለምሳሌ አቶ መለስ ከመሞታቸው በፊት በፃፉት ደብዳቤ፤ “ከኦብነግ ኃይል ጋር አስታርቁን” ብለው ኬንያን ጠይቀው ነበር፡፡ እዚያ ኬንያ ውስጥ በኦጋዴን ጉዳይ ከፍተኛ ተሰሚነት ያላቸው ሰዎች አሉ። እሱ ላይም ለመነጋገር ጉብኝታቸው አስፈላጊ ሊሆን ይችላል፡፡ እነዚህ ነገሮች ስላሉት ለየት ሊል ይችላል። በኤርትራ በኩል ደግሞ የመታረቁ ነገር ከአሜሪካኖቹ ግፊት የመጣ ሊሆን ይችላል፡፡ ከኤርትራ ጋር ለመታረቅ ኢትዮጵያ ብቻዋን ዘው ብላ መግባት አለባት? ወይስ ከወዳጆቿ ጅቡቲና ሱዳን ጋር ማቀናበር አለባት? ይሄ አንዱ ወሳኝ ሁኔታ ነው፡፡
በሌላ በኩል፤ የግድቡ ጉዳይ አለ፡፡ ይሄም ታሳቢ መደረግ አለበት፡፡ ለምሳሌ ሱዳንና ኢትዮጵያ፤ ከፍተኛ የሆነ ወታደራዊ ስምምነት አላቸው፡፡ ይሄን ጉዳይ ተነጋግረው፣ የሃገሪቱን ሉአላዊነት ከማስከበር አንፃር መልክ ማስያዝ አለባቸው፡፡ ሌላው የደቡብ ሱዳን ጉዳይ ነው፡፡ ከሱዳንና ከኬንያ ጋር አንድ አቋም መያዝ ሊያስፈልጋቸው ይችላል፤ለዚህም መነጋገር አለባቸው። ጉብኝታቸው አካባቢያዊ፣ ሁለትዮሻዊ እና የውስጥ ፖለቲካ አንድምታ አለው፡፡
ሃገሮች የተጠናከረ ኢኮኖሚያዊ ትስስር ካላቸው፣ በፀጥታና በፖለቲካ ጉዳይ ለከባድ ችግር አይጋለጡም። ከዚህ አንፃር በተለየ ሁኔታ በኢኮኖሚ መተሳሰር ያስፈልጋል፡፡ ለምሳሌ ወደብ የኤሌክትሪክ ኃይል አቅርቦት፣ የውሃ አቅርቦት፣ የባቡር መስመር ዝርጋታ የመሳሰሉ ይገኙበታል፡፡  እነዚህ በሀገራቱ መካከል የጋራ ጥቅም ላይ የተመሰረተ ኢኮኖሚያዊ ትስስር ለመፍጠር አጋዥ ናቸው፡፡ የጋራ ጥቅም ካለ ፖለቲካው አይጎዳም። እርስ በእርስ መጠባበቁ ይኖራል፡፡
በውጭ የሚያደርጉት ጉዞ ከዚህ አንፃር ሲታይ፣ በውስጥ ያለውን ሰላምና መረጋጋት ለማምጣት የሚደረገው ጥረት አካል ሆኖ ነው መታየት ያለበት። ለመጀመሪያ ጊዜ በህዝብ ጫና ጠቅላይ ሚኒስትር የሆነ የኦሮሞ ተወላጅ፣ በኬንያ ኦሮሞዎች ላይ ተፅዕኖ የለውም ማለት ይከብዳል፡፡  ከዚህ አንፃር ከኦነግ ጋር ወደ ሰላም ድርድር ሊገባ ይችል ይሆናል፡፡ ስለዚህ የውጭ ሃገሩ ጉብኝታቸው አንድምታው ብዙ ነው፡፡
በኤርትራ እና በኢትዮጵያ መንግስታት መካከል ሰላም መፍጠር ይቻላል ብለው ያስባሉ?
ፍላጎቱ በኢትዮጵያውያንም፣ በኤርትራውያንም፣ በውጭ መንግስታትም አለ፤ በአካባቢው መንግስታትም እንዲሁ፡፡ አሁን የሚያስፈልገው ሁለቱ ሀገራት የሚደራደሩበትን መነሻ ሐሳብ ማዘገጀትና ማጠናቀር ብቻ ነው፡፡ ምክንያቱም የኤርትራ መንግስት አቋም ልክ ጦርነቱ እንደተጀመረበት ወቅት ነው ያለው። የሁለቱ ሃገራት ሁኔታ ያኔ በጦርነቱ ጊዜ እንደነበረው ነው፡፡  
የፀቡ መነሻ የሆነ መሬት ለኤርትራ ተወሰነ፤ የኤርትራ መንግስት ደግሞ ያንን መሬት ለድርድር እንደ ቅድመ ሁኔታ፣ይዞት ቀጠለ፡፡ የኤርትራ መንግስት አንገብጋቢ የሆነበት የባድመ መሬት ቢሰጠው እንኳ በበጎ አይን ይደራደራል ተብሎ አይጠበቅም። ምክንያቱም መነሻው ባድመ አይደለም፡፡ ሁለተኛ የሰላም ዋስትና ባድመ አይደለም፡፡ የኤርትራ መንግስት ባህሪ፤ ለኢትዮጵያ በጎ አመለካከት ያለው መሆኑን በምን ልናረጋግጥ እንችላለን? ይሄን ማረጋገጫ ማንም ሊሰጥ አይችልም፡፡ ኤርትራን ወደ ሰላም እናምጣ የሚሉ የአሜሪካ ፖለቲከኞችም ይሄን ሊያረጋግጡ አልቻሉም፡፡ ስለዚህ ከኤርትራ ጋር ድርድር ማድረጉ ለምን ውጤት ነው?
የኤርትራ ፖለቲካል - ኢኮኖሚ መርህ እስካልተቀየረ ድረስ የሰላም ሂደቱ በቀላሉ የሚከናወንና የሚፈፀም አይደለም፡፡ ከኤርትራ ጋር መደራደር ስለተፈለገ ብቻ መደራደር ይቻላል ወይ? ይሄም ሌላው ጥያቄ ነው፡፡ ሌላው በአካባቢው የቻይና መምጣት፣ ከየመን ሁኔታ ጋር፣ ከአሜሪካ የቀይ ባህር የጦር ኃይል ጋር፣ ቀይ ባህር ደግሞ ለኤርትራም ሆነ ለኛ ስትራቴጂካዊ ቦታ ነው ከሚል መነሻ ነው ውጤት መምጣት ያለበት። የሚፈለገው ምንድን ነው? የሁለቱ ሀገራት ሰላም መሆን ነው? ወይስ ቀይ ባህር ላይ ያላቸውን ጥቅም ከማስከበር አኳያ ነው? የሚለው ግልፅ አልወጣም። ይሄ ግልፅ ባልወጣበት ሁኔታ፣ የመሬት ልውውጥ ጉዳይ ብቻ ከሆነ ዋጋ የለውም። የሰላም ሂደቱ መጀመር ያለበት ቀጠናውን ባገናዘበ መልኩ ነው፡፡ ባድመ የሰላማዊ ግንኙነቱ መነሻ ነው መሆን ያለበት፡፡ አሁን ግን ባድመን ለብቻዋ ነጥሎ የመውሰድ ሁኔታ ነው፣ በኤርትራ በኩል ያለው፡፡ ያ ከሆነ ምንም ውጤት የለውም፡፡
ዶ/ር አብይ፤ የቀንዱ አካባቢ ጎረቤት ሃገራትን መጎብኘታቸው፣ የኢትዮጵያን ተፅዕኖና ሚና በማስጠበቅ ረገድ  ከዶ/ር አብይ በቀጠናው ጉዳይ ምን ይጠበቃል?
ቀጠናው ላይ የኢትዮጵያ ሚናን ለማጠናከር ወሳኙ የውስጥ ሰላምን ማጠናከር ነው፡፡ በመጀመሪያ እሳቸው የሀገሪቱን የውስጥ ሰላም ማጠናከር አለባቸው፡፡ የውስጡን ሁኔታ እንዳይጎዳም የጎረቤት ሃገራትን ግንኙነት ማጠናከሩም ጠቃሚ ነው፡፡ አሁን እንደሚያደርጉት ማለት ነው፡፡ በወሳኝ መልኩ ኢትዮጵያ በአካባቢው የሰላም እና የማረጋጋት ሚናዋን ልታጠናክር የምትችለው ግን የኢትዮጵያ የፖለቲካ ሂደት ሰላማዊ፣ ዲሞክራሲያዊ እና በንግግር ላይ የተመሰረተ ሲቪላዊ የፖለቲካ ሂደት ሲፈጠር ነው፡፡ የውስጧ ሰላም የተረጋገጠ ሃገር፤ የአካባቢው የኃይል ሚዛን ወደሷ ያደላል፡፡ አሁን የህዝብ ቁጥር የበላይነት አላት፤ ወታደራዊ የበላይነት አላት፣ ጥንታዊ የመንግስት አወቃቀርና ስርአት ያላት ሃገር ነች፣ ኢኮኖሚዋ እያደገ የመጣ ሃገር ነች፤ መሃል ላይ ነው ያለችው፡፡ ከዚህ አንፃር መሬት ላይ ያላት ኃይል ጠቃሚ ነው፡፡ ነገር ግን ይሄን ኃይሏን ተጠቅማ በቀይ ባህር አካባቢ ያላትን ሚናዋን እንዳትወጣ፣ አስሮ የያዛት የውስጥ የፖለቲካ ቀውስ ነው፡፡
 ዶ/ር አብይ፤ ይሄን የውስጥ ቀውስ በመፍታት፣ ሰላማዊ የስልጣን ሽግግር በማምጣት፣ ዲሞክራሲያዊ ተቋሞች በማጠናከር --- የሃገር ውስጥ የፖለቲካ ሂደቱን ማስተካከል ለኢትዮጵያ አካባቢያዊ የበላይነት ወሳኝ መሆኑን የተረዱ ይመስላል፡፡ ከዚህ አንፃር እዚህ ላይ ማተኮራቸው አይቀርም፡፡ እስከዚው ድረስ የውጪ ኃይሎች የሚያበላሹት ነገር ይኖራል፡፡ ለምሳሌ የዩናይትድ አረብ ኤምሬትስ እና የእነ ኳታር በሶማሊያ ጉዳይ የሚያደርጉት ነገር አለ፡፡ ይሄን ከኬንያ፣ ከኢጋድ ጋርም ተነጋግሮ ወደ አፍሪካ ህብረት በአጀንዳነት ማምጣት ያስፈልጋል፡፡ የቀይ ባህር ጉይ ለቀንዱ ሃገራት በሙሉ የደህንነት ጉዳይ ነው፡፡ የወደብ እና የኮንቴነር ጉዳይ አይደለም ቀይ ባህር የደህንነት ቀጠና ነው፡፡ ለኢትዮጵያ ቀይ ባህር የደህንነት ቀጣና ነው። ይሄ የደህንነት ጉዳይ ኢጋድን የአፍሪካ ህብረትን ይመለከታል፡፡ ስለዚህ ከእነዚህ ሃገሮች ጋር መነጋገር ይሄን አጀንዳ ወደ ላይ ከፍ የማድረግ ሙከራዎች ዶ/ር አብይ እያደረጉ ያለ ነው የሚመስለኝ በጉብኝታቸው። ማድረግ ያለባቸውም ይሄንኑ ነው፡፡ ዋናው ግን የኢትዮጵያን የውስጥ የፖለቲካ ሃዲድ ማስተካል ለኢትዮጵያ ቀጠናዊ የበላይነት ወሳኝ ነው፡፡ ተፅዕኖ ፈጣሪነቱም የሚመጣው ከዚህ በመነጨ ነው፡፡  

ለመሆኑ ስንቶች ይሆኑ በትዳር አለመታመን የተነሳ ወደ አልሆነ አቅጣጫ እየተጉዋዙ በስነተ ዋልዶ ጤና ችግር የታወኩ? ይህንን ጥያቄ ለመመለስ እራሱን የቻለ ጥናት ቢያስፈ ልገውም በየአቅራቢያችን ግን የታዘብናቸው ብዙ ክስተቶች አሉ፡፡ በቤታቸው ውስጥ ሆነው ልጆቻቸውን ከማሳ ደግ እና ባልን ከመርዳት ውጭ ደጁን የማያውቁ በኤችአይቪ ምክንያት ለህልፈት የተ ዳረጉ ብዙዎች ናቸው። ቤተሰባቸውን ለማስተዳደር ሲሉ ጧት ማታ ከመማሰን እና ከሚስቶቻ ቸው ውጭ ሌላ ሴት የማያውቁ ብዙ ወንዶች በግብረስጋ ግንኙነት ምክንያት በሚተላለፉ በሽታ ዎች ኤችአይቪን ጨምሮ የተጠቁ ብዙዎች ናቸው።  ምናልባትም ልቅ የግብረስጋ ግንኙ ነት መፈጸም ከአመል ወይንም ከባህርይ ጋር ብቻ የሚያያዝ አለመሆኑን እና ይልቁንም በትዳር መካከል ከሚኖር አለመግባባት ወይንም ታማኝነት ማጣት በመሳሰሉት የሚከሰት መሆኑን ብዙ ጥናቶች ያስረዳሉ፡፡ መረጃ ዎች በትክክል ይህን ያህል ቁጥር ብለው ባይገልጹም በስፋት በአለም ላይ ሪፖርት የተደረገው ግን በዚህና በመሳሰሉት ምክንያቶች 60% የሚሆኑ ወንዶችና 40% የሚሆኑ ሴቶች በትዳር ዘመናቸው ከትዳር ውጭ ከሌላ ፍቅረኛ ጋር እንደሚገናኙ (Live-  about) የተሰኘ ድረገጽ ያስነ ብባል፡፡
Mort – Ertel የተባሉ የስነ ልቡና ባለሙያ ደግሞ ትዳር ለከፋ የጤንነት፤ የኢኮኖሚና ማህበራዊ ችግር ተጋልጦ ተጋቢዎችን ብቻ ሳይሆን ዙሪያውን ያሉ ቤተሰቦችን ከዚያም በላይ በህብረተ ሰብና በአገርም ላይ ችግር ከማስከተሉ በፊት ተጋቢዎች ሊያጤኑዋቸው የሚገባቸው ነገሮች አሉ ይላሉ፡፡  
የመጀመሪያው ችግርን ወደጎን መተው ነው፡፡
አንድን ትዳር ከመፍረስ ለማዳን ችግርን እንዴት መፍታት እንዳለባቸው ባለትዳሮች አስቀድ መው ሊያውቁ ይገባል። አንዳቸው ከአንዳቸው በምን አይነት መንገድ መግባባት ወይም መገናኘት እንዳለባቸው በስርአተ ጾታው ረገድም ያለውን ልዩነት ዘልቆ መመልከት ይገባል ይላሉ ባለሙያው። ይህንን ርእሰ ጉዳይ በሌላ ሙያ የተካኑ ባለሙያዎች ወይም ከሕክምና አንጻር በመመልከት ችግሩን ለመፍታት ቢሞከር እንኩዋን ትዳርን ማዳንና እንደነበረ ለመጠበቅ መፍትሔው የሚገኘው በራሳቸው በባለጉዳዮቹ እጅ መሆኑ ልብ ሊባል ይገባል ይላሉ የስነልቡና ባለሙያው። Mort – Ertel የቀረበላቸው የትዳር አጋሮች የህይወት ልምድ አላቸው፡፡ ታሪኩ እንደሚከተለው ነው፡፡  
‹‹….እኔና ሚስቴ ትዳራችንን የመሰረትነው አንዳችን ለአንዳችን በፍቅር ወድቀን ነው፡፡ ለፍቅራ ችን እጅግ ጥልቅ ስሜት ነበረን፡፡ በየምሽቱ ስናወራ፤ አንዳችን ለአንዳችን ያልተጠበቀ ወይንም አስደናቂ ስጦታዎችን ስንቀባበል ፤አንዳችን አንዳችንን ስናቀማጥል፤ ብቻ ባጠቃላይ አንዳችን ከአንዳችን ውጭ ምንም የምናስበው ነገር ሳይኖር በደስታ እየኖርን ነበር፡፡ እኛ በጣም የምና ስቀናና ለሌሎች ምሳሌ የምንሆን ፍቅረኞች እና ባለትዳሮች ነበርን፡፡   
ነበርን የሚለው ቃል አለምክንያት አልመጣም፡፡ የሁዋላ ሁዋላ ግን ይህንን እ…ፍ…ፍ..ያለ እንደእሳት የሚንቦገቦግ ፍቅር የሚያጠፋ ነገር ተከሰተ፡፡ ይህ ደግሞ የብዙዎችን ትዳር የሚፈ ትን መሆኑ ግልጽ ነው፡፡ አንድ ልጅ ተወልዶ ገና በሳምንት እድሜው ሞተ፡፡ ከዚያም መንትያ ሴት ልጆች ወልደን እነርሱም ገና በጨቅላነት እድሜያቸው አለፉ፡፡ ከዚህ በሁዋላ ሚስቴ በእ ኔም ባይሆን እንኩዋን በጠቅላላው በተፈጠረው ነገር በጣም እየተደበረች መጣች። ይህ ደግሞ በትክክል የሚጠበቅ ነገር ሲሆን እየዋለ እያደረ ግን በእኔና በእስዋ መካከል ችግር መፍጠሩ አልቀረም፡፡ እኔም እራሴን በስራ በጣም መጥመድ እና ጊዜ እንዳይኖረኝ መጣር ጀመርኩ፡፡ ሁለታችንም በየፊናችን መሮጥ እንጂ እንደድሮው መገናኘታችንን አፍ ለአፍ ገጥሞ ማውራታ ችንን እየተውነው መጣን፡፡ እንዲ ያውም ሳንተያይ ውለን ማታ አልጋ ላይ ብቻ አንዳችን አን ዳችንን መኖራችንን የምናረጋግጥበት አጋጣሚ በዛ፡፡ ሶስት ልጆቻችንን ካጣን በሁዋላ ሁሉም ነገር የተለየ ሆነ፡፡ ምሽቱን በሙሉ ሳቅ ጨዋታ ቀርቶ ኃላፊነትን በሚጠይቁ ጉዳዮች ጥቂት ንግግር ብቻ ተተካ፡፡ ማቆላመጥ ቀርቶ በሚያናድድ መልክ መጠራራት ጀመርን፡፡ ባጠቃላይም ግንኙነታችን ጸጥታ የመላበትና ብዙም የማያገናኘን እየሆነ መጣ፡፡
በእርግጥ ሁለታችንም ሁኔታዎች አስገድደውን እንጂ ይህ እንዲሆን አልፈለግንም፡፡ ስለዚህ ትዳ ራችንን ወደነበረበት ጤናማ ሕይወት ለመመለስ ሁለታችንም አንደምንፈልግ ተግባብተናል፡፡ ግን ወደፍቅር የሚወስደውን ጉዞ በሚመለከት አንዴ እኔ ስጀምረው እስዋ ትተወዋለች፡፡ እስዋ ስትጀምረው ደግሞ እኔ ችላ እላለሁ፡፡ በዚህ መልክ እንደቆየን አንድ እርምጃ ለመውሰድ ቁር ጠኝነቱን አሳየን፡፡  
መፍትሄው ምን ሆነ?
እማኞቹ እንደሚሉት በምን መንገድ ችግሮቻችንን መፍታት እንዳለብን የቻልነውን ያህል አነበብን፡፡ የግጭት ማስወገጃ ዘዴዎችን ጥቅም ላይ ለማዋል ጥረት አደረግን ይላሉ፡፡ ለምሳሌም፡-
...ውዴ…ምን ነበር ያልሽኝ…አልሰማሁሽም…እስቲ አድምጪኝ ልድገምልሽ…አንቺ ያልሽውን ተረድቼ እንደሆነ አድምጪኝ እና አረጋግጪልኝ፡፡
…የኔ ፍቅር …ተረድተኸኛል? ይሄ ነገር እኮ እንደዚህ ቢሆን ጥሩ ነበር፡፡ አይመስልህም?
…ጨመር አርገሽ ብዪ እንጂ…ትንሽ እኮ ነው የበላሽው…፤
…ይርድሀል…ይህን እስቲ ደርብበት…፤
የመሳሰሉትን የማግባቢያ እና አንዱ ለአንዱ የሚሰ ጠውን ክብርና መተሳሰብ የሚያሳዩ ድርጊቶችንና አባባሎችን ተጠቀምን፡፡ እንዲሁም ወደተለያዩ መዝናኛዎች በመሄድ ችግሮቹን ለመፍታት ሙከራ አደረግን፡፡ ነገር ግን ያነበብ ናቸው መጽ ሐፎች፤ የሄድንባቸው የምክር አገልግሎቶች ሁሉ የሚነግሩን ችግርን አለማንሳትን ሳይሆን እያነሱ መፍትሔ መፈለግ የሚል ስለሆነ ለእኛ ምንም ጥቅም አልሰጠንም። እንዲያውም ይበልጥ ያጣላን ጀመር፡፡ ድካማችን ምንም ለውጥ አላመ ጣም፡፡ የምንነጋገራቸውና የምናደርጋቸው ድርጊቶች የይምሰል ሆኑብን፡፡ ስለዚህም ሁለታችንም ከልባችን በግልጽ ለምን ለውጥ ማምጣት እንዳልተቻለ ተነጋገርን፡፡ በስተ መጨረሻም የራሳችንን ዘዴ ቀየስን፡፡ ጊዜ ወስደን ተወያየን፡፡ አንዳችን አንዳችንን አሳመንን፡፡ በቃ፡፡ እባካችሁ …ተጋቢዎች …ትዳራችሁ ችግር ገጥሞት ከሆነ …ይህንን ሞክሩ፡፡ ››ይላሉ የራሳቸውን ምስክርነት የሰጡት ባለትዳሮች፡፡
መፍትሔ ሆኖናል ያሉት የሚከተለውን ነበር፡፡ ‹‹ገጥሞን የነበረውን ችግር ምንነት ሁለታችንም ለየራሳችን በመረዳት ወደጎን አስቀመጥነው፡፡ በእነዚህ ችግሮች ዙሪያ በድጋሚ መነታረክም አልፈለግንም፡፡ ይልቁንም… ግንኙነታችን በተለየ ሁኔታ እንዲቀጥል ያለንን አቅም በሙሉ ተጠቀምን። አስቀድሞ የተፈጠረውን ችግር እያነሱ ከመታገል ወይንም አንቺ ነሽ …አንተ ነህ …እያሉ ከመነታረክ ምንም ይልቅ ምንም እንዳልተፈጠረ አድርጎ ለምን በአዲስ መልክ ኑሮአችንን አንቀጥልም ተባባልንና ተግባባን፡፡ ምክንያቱም በውስጣችን ያለውን ፍቅራ ችንን ሊያደበዝዝ የሚችል ምንም መሰረታዊ የሆነ ጉዳት አንዳችን በአንዳችን ላይ አልፈጸም ንም፡፡ ስለዚህ  አንዳንድ ለየት ያሉ መንገዶችን ተጠቀምን፡፡ ትዳራችን በአዲስ መልክ እንደገና እንዲቀጥል ለማድረግ አዳዲስ ልማዶችን ባህሪዎችን በማምጣት አንቺ ትብሽ አንተ ትብስ በመ ባባል በሚያስገርም ሁኔታ አንዳችን በአንዳችን እቅፍ ውስጥ እንደገና ወደቅን፡፡ ፍቅር እንደገና ብለን አዲሱን የትዳር ሕይወት መንገድ ተያያዝነው፡፡ ተፈጥሮ የነበረው ችግር ከእኛ ፍላጎት ውጭ እና ከአቅማችን በላይ በሆነ ምክንያት መሆኑን አምነን አንዳችን ለአንዳችን ቀና የሆነ አስተሳሰብ እንዲኖረን የቻልነውን ያህል ሞከርን። ተሳካልንም፡፡›› ብለዋል፡፡
የስነልቡና ባለሙያው Mort – Ertel የእነዚህን ተጋቢዎች ምስክርነት ይጋሩታል፡፡ ብታምኑም ባታምኑም ይላሉ ባለሙያው...ይህ ለብዙዎች ችግር ለገጠማቸው ትዳሮች እንደ በጎ ምሳሌ የሚቆጠር ነው፡፡ ሁልጊዜም ማድረግ የሚሻለው ከተፈጠሩት ችግሮች እርቆ በተቃራኒው ግን በጎ የሆነ ግንኙነትን ለመፍጠር በተፈጠረው ወይንም ባሉበት ሁኔታ ላይ በግልጽ ተነጋግሮ አቅምን ለበጎ ነገር ማዋል ነው ፡፡ይህ ከሆነ ችግሮች ይሳሳሉ፤ ትዳር ከመፍረስ ይርፋል፤ የሌሎች በትዳር መሐል የሚከሰቱ ጣልቃ ገብነቶችም ይገታሉ ብለዋል የስነልቡና ባለሙያው፡፡   ይቀጥላል፡-