Administrator

Administrator

 “ሃገር ለዋጭ ሐሳቦች ከምሁራኑ ሊፈልቁ ይገባል”

    ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተስፋፋ የመጣውን ጎሠኝነትና ብሔርተኝነት ከሃገራዊ ማንነት ጋር ማስታረቅ የሚቻልበትን የመፍትሄ ሐሳብ እንዲያፈላልጉ ጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አሕመድ ለምሁራን ጥሪ አቀረቡ፡፡ የአገሪቱ ፖለቲካዊ ችግሮች የተወሳሰቡ በመሆናቸው ችግሮቹን አገናዝቦ መውጫ መንገድ የሚያሳይ ምሁር ያስፈልገናል፤ ብለዋል፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ባለፈው ሳምንት የባሕር ዳር ቆይታቸው፤ በዐውደ ጥናት ላይ የነበሩ የባህር ዳር ዩኒቨርሲቲ መምህራንን ያነጋገሩ ሲሆን፤ ምሁራኑ ለሀገሪቱ ፖለቲካዊ ችግሮች መፍትሄ የሚሆኑ የምርምር ሥራዎችን እንዲያቀርቡ ጠይቀዋል፡፡ አገር ለዋጭ ሐሳቦች ከምሁራኑ ይፈልጋሉ ሲሉም ተናግረዋል፡፡
ምሁራኑ በሀገሪቱ እየተስፋፋ ስለመጣው የብሔርተኝነት ጉዳይ ጥናት እንዲያደርጉ ያሳሰቡት ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ “መንግሥት ከምሁራኑ ጋር እስካልተመካከረ ድረስ ከገባንበት ችግር ልንወጣ አንችልም፤” ብለዋል፡፡ የብሔር ማንነትና ኢትዮጵያዊ ማንነት የሚታረቁባቸው የመፍትሔ ሐሳቦች ከምሁራኑ እንዲፈልቅም ጠይቀዋል፡፡

 ከሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ ጋር አለኝ ያሉት ግንኙነት ትኩረት ስቧል
   ሥራ አስኪያጁ፣ ለሠራተኛ ቅጥር 100ሺሕ ብር ጉቦ መቀበላቸው ታወቀ

     በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የደብረ ምጥማቅ ሰዓሊተ ምሕረት ቅድስት ማርያም ካቴድራል፣ ከሀብት ምዝበራና ብክነት እንዲሁም ከሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን ጥሰት ጋራ በተያያዘ ማኅበረ ምእመናኑ በአስተዳደር ሓላፊዎች ላይ ያቀረቡትን አቤቱታ ለማጣራትና ወራት ያስቆጠረውን አስተዳደራዊ ችግር ለመፍታት፣ ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት መምሪያ ተልኬያለሁ ያሉ ግለሰብን ፖሊስ አስሮ እየመረመረ ነው፡፡
በካቴድራሉ የተፈጠረው ችግር ከአቅሙ በላይ እንደኾነ በመግለጽ ለመፍትሔው ትብብር እንዲደረግለት፣ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ለብሔራዊ መረጃና ደኅንነት መምሪያ የፖሊቲካ ጉዳዮች ጽ/ቤት የጻፈውን ደብዳቤ በመያዝና በሕገ ወጥ መታወቂያ ተጠቅመው ራሳቸውን የመሥሪያ ቤቱ ባልደረባ በማስመሰል፣ የማጣራት ሒደቱን አስቀጥላለሁ በማለት የተንቀሳቀሱ ሲኾን፤ አኳኋናቸው በተጠራጠሩ የአጥቢያው ማኅበረ ምእመናን ዐቢይ ኮሚቴ አባላት ጥቆማ በፖሊስ ቁጥጥር ሥር ውለዋል፡፡
ኃይለ ኢየሱስ ተፈራ የተባሉት እኚሁ ግለሰብ፣ መጋቢት 19 ቀን 2010 ዓ.ም. ወደ ካቴድራሉ አምርተው ከአጥቢያው ማኅበረ ምእመናን ዐቢይ ኮሚቴ ጋራ በተገናኙበት ወቅት፣ ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት መምጣታቸውን ገልጸው እንደተዋወቋቸው የጠቀሱ ምንጮች፤ የካቴድራሉን አስተዳደራዊ ችግር የማጣራት ሒደት በእርሳቸው አማካይነት እንዲቀጥል የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ፍላጎት እንደኾነና ለዚህም ደብዳቤ እንደደረሳቸው ለኮሚቴው ማስታወቃቸውን ተናግረዋል፡፡
በዕለቱ በተደረገው ስብሰባ፣ ቀደም ሲል የተጀመረው የማጣራት ሒደት የተስተጓጎለበትን ምክንያት ኮሚቴው ያስረዳ ሲኾን፣ በምክክርና በሰላማዊ መንገድ በአስቸኳይ እንዲፈታ ፍላጎት እንዳለው ገልጿል፡፡ ለዚህም፣ አቤቱታ የቀረበባቸውና በሕዝብ የታገዱት የአስተዳደር ሓላፊዎች በአካል ተገኝተው ከማስመርመር የዘለለ ተግባር ማከናወን እንደማይችሉ እንዲሁም ሀገረ ስብከቱ በአዲስ መልክ ከሚመድባቸው አጣሪዎችና ‘ደኅንነት ነኝ’ ካሉት ግለሰብ በተጨማሪ፥ ከጠቅላይ ቤተ ክህነት፣ ከአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን፣ ከቦሌ ክፍለ ከተማ አስተዳደር ጽ/ቤትና ፖሊስ መምሪያ፣ ከቦሌ ክፍለ ከተማ የወረዳ 07 አስተዳደር ጽ/ቤትና ስድስት የአጥቢያው ምእመናን ተወካዮች እንደሚሳተፉ የጋራ ስምምነት ተደርሶ እንደነበር ተጠቁሟል፡፡
በበነጋው መጋቢት 20 ቀን 2010 ዓ.ም.፣ የካቴድራሉ የአስተዳደር ሓላፊዎች ፈጽመውታል የተባለውን የሀብት ምዝበራና ብክነት እንዲሁም የሥርዐተ ቤተ ክርስቲያን ጥሰት የሚገልጹና ምእመናን በየመግቢያ በሮች ላይ የሰቀሏቸውን ባነሮች እንዲያነሡ ማድረግን በተመለከተ ግለሰቡ ባስያዙት አጀንዳ፣ ከዐቢይ ኮሚቴው ጋራ ተወያይተዋል፡፡ ባነሮቹ ተፈላጊውን መልእክት በማስተላለፋቸው በሚመለከተው መንግሥታዊ መሥሪያ ቤት እንዲነሡ መታዘዙን ግለሰቡ በቅድመ ኹኔታ መልክ ቢገልጹም፤ ባነሮቹ እንደተሰቀሉ እንዲቆዩ የተደረገው፣ ሀገረ ስብከቱ ማጣራት እንደሚጀምር ቃል ከገባ በኋላ ጥር 18 ቀን በፍ/ቤት የሁከት ይወገድልኝ ክሥ በመመሥረቱ እንደኾነ በኮሚቴው አባላት ተነግሯቸዋል፡፡ ከአንድ ሺሕ በላይ የካቴድራሉ ምእመናን የሀገረ ስብከቱን አካሔድ በመቃወም፣ የካቲት 2 ቀን ለቋሚ ሲኖዶስ አቤቱታ አቅርበው አምስት አባላት ያሉት አጣሪ ልኡክ ቢመደብም ሒደቱ በአስቸኳይ ተፈጻሚ ባለመኾኑ ወርዶ የተቀመጠው ባነር ተመልሶ መሰቀሉን አስረድተዋቸዋል፡፡
በዚሁ ዕለት በግለሰቡ ላይ የተመለከቱት ኹኔታ ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት መ/ቤት መምጣታቸውን እንዲጠራጠሩ እንዳደረጋቸው የተናገሩት የኮሚቴው ምንጮች፤ ካቴድራሉ ለሚገኝበት የቦሌ ክ/ከተማ አስተዳደር የጸጥታ አካል ስለጉዳዩ በመጠቆም፣“ደኅንነት ነኝ” የሚሉት አቶ ኃይለ ኢየሱስ ተፈራ በክትትል ውስጥ እንዲገቡ ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡ መጋቢት 21 ቀን፣ ግለሰቡ ባስያዙት ቀጠሮ መሠረት፣ የሀገረ ስብከቱ ሥራ አስኪያጅ መ/ር ጎይትኦም ያይኑና ሁለት የአስተዳደር ጉባኤ አባላት ከዐቢይ ኮሚቴው ጋራ በጽ/ቤቱ ተገናኝተው ስለማጣራት ሒደቱ አፈጻጸም በተነጋገሩበትም ወቅት ክትትሉ ቀጥሎ እንደነበር ጠቁመዋል፡፡ የማጣራት ሒደቱን ለመጀመር ስምምነት በተደረሰበትና ግለሰቡ በካቴድራሉ ቅጽር በተገኙበት መጋቢት 25 ቀን፣ አስቀድሞ መረጃው ደርሷቸው ሲከታተሏቸው በቆዩ የፖሊስና የጸጥታ አካላት ያለምንም ውዝግብ በቁጥጥር ሥር እንዲውሉ መደረጋቸው ታውቋል፡፡
ግለሰቡ በቁጥጥር ሥር ሲውሉ፣ ከብሔራዊ መረጃና ደኅንነት መ/ቤት ተልከው ስለመምጣታቸው የሚያረጋግጥ ትክክለኛ ማስረጃ ማቅረብ እንዳልቻሉና ደርሶኛል ካሉት የሀገረ ስብከቱ ደብዳቤ ጋር በተያያዘ ሥራ አስኪያጁን መ/ር ጎይትኦም ያይኑን የተመለከተም ምርመራ እየተካሔደባቸው መኾኑን ለማወቅ ተችሏል።
በአ/አበባ ሀ/ስብከት ሥራ አስኪያጅ መ/ር ጎይትኦም ያይኑ ቲተርና ፊርማ ወጪ በተደረገውና ለብሔራዊ መረጃና ደኅንነት መምሪያ የፖሊቲካ ጉዳዮች ጽ/ቤት በተጻፈው የትብብር መጠየቂያ ደብዳቤ፣ ግለሰቡ በካቴድራሉ ተገኝተው ስለጉዳዩ አጭር ሪፖርት እንዲያቀርቡ የሚያዝ ምሪት ተሰጥቶበታል። የመሥሪያ ቤቱን ትብብር በደብዳቤ መጠየቃቸውን ለቦሌ ክፍለ ከተማ ፖሊስ መምሪያ በጽሑፍ በሰጡት ምላሽ ያረጋገጡት ሥራ አስኪያጁ በበኩላቸው፤ የካቴድራሉን ሰላም ለመመለስ ከመጣር ውጪ፣ ግለሰቡን እንደማያውቋቸው፣ ደብዳቤውንና በአባሪነት የተያያዘውን 35 ገጽ ሰነድም ለግለሰቡ እንዳልሰጧቸው ገልጸዋል፡፡
ሀገረ ስብከቱን በበላይነት የሚመሩት ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ፤ ባለፈው ሳምንት ኃሙስ ከቀትር በኋላ፣ የካቴድራሉን ወቅታዊ ኹኔታ በተመለከተ በጽ/ቤታቸው ተቀብለው ላነጋገሯቸው የማኅበረ ምእመናኑ ዐቢይ ኮሚቴ አባላት፣ ሥራ አስኪያጁ እና “ደኅንነት ነኝ” ባዩ ግለሰብ አላቸው ስለሚባለው ግንኙነት ማንሣታቸው ተጠቅሷል፡፡“የሁለቱን ግንኙነት ነጥብ በነጥብ ዘርዝረን ለቅዱስነታቸው አስረድተናቸዋል፤” ብለዋል የኮሚቴው አባላት፡፡ ፓትርያርኩም፤ “ደኅንነት ነኝ የሚለው ግለሰብ አሳስቶት ነው ወይስ አምኖበት?” በማለት እንደጠየቋቸውና “ኾን ብለው ተማክረው እንዳደረጉትና ኹሉንም ነገር መ/ር ጎይትኦም እንደሚያውቅ፤ ጉዳዩም በሕግ እንደተያዘና እኛም ፍትሕ እንደምንሻ ገልጸንላቸዋል፤” ብለዋል፡፡
ሀገረ ስብከቱ የመሠረተባቸውን ክሥ፣ የመጀመሪያ ደረጃ ፍ/ቤት ውድቅ ቢያደርገውም፣ የጠየቀው ይግባኝ እንዲቋረጥ ትእዛዝ እንዲሰጡላቸውና ቋሚ ሲኖዶሱ የመደባቸው ልኡካን ማጣራቱን እንዲጀምሩ በአጽንኦት ያመለከቱት የዐቢይ ኮሚቴው አባላት፤ ሒደቱ በመዘግየቱ ከላይ ለተጠቀሱት ዐይነት ትንኮሳዎች እየዳረጋቸው መኾኑን ለፓትርያርኩ አስረድተዋል፡፡ የካቴድራሉ አስተዳደር ሓላፊዎች በሕዝቡ ተቃውሞ ከተባረሩበት ታኅሣሥ 20 ቀን 2010 ዓ.ም. ጀምሮ ሰላሙ ተጠብቆ ዓመታዊና ወርኃዊ በዓላት መከበራቸውን፤ የውስጥ አገልግሎቱና ስብከተ ወንጌሉም ያለአንዳች እንከን እየተከናወነ እንደኾነም ነግረዋቸዋል፡፡ በሦስት ክብረ በዓላት በሙዳየ ምጽዋት የተሰበሰበው ገንዘብ፣ የሀገረ ስብከቱና የክፍለ ከተማ ቤተ ክህነቱ ተወካዮች በተገኙበት የተቆጠረበትን ቃለ ጉባኤና የባንክ ሰነዱን አሳይተዋቸዋል፡፡
“የአስተዳደር ሓላፊዎቹ እያሉ በሁለት የባንክ ሒሳቦች የነበረውን የገንዘብ መጠንና ከእነርሱ በኋላ 1ነጥብ2 ሚሊዮን ብር የሁለት ወራት የካህናት ውዝፍ ደመወዝ ተከፍሎም ከ7 ሚሊዮን ብር በላይ ተቀማጭ እንደሚገኝ በመጥቀስ ቤተ ክርስቲያናችንን እየጠበቅን እንዳለ አስረድተናቸዋል፤”ብለዋል የኮሚቴው አባላት፡፡
ኮሚቴው ባቀረበው የሥራ ክንውን መደሰታቸውን የገለጹት ፓትርያርኩ፣ “ቢሮዎቹን ባታሽጉ ኖሮ አትንከራተቱም ነበር፤ እግዚአብሔር በሚያውቀው እንዲጣራ እፈልጋለሁ፤ ለዚህም ወዲያው መርቼበት ነበር፤” ማለታቸውን የዐቢይ ኮሚቴው ምንጮች ተናግረዋል፡፡ በሀገረ ስብከቱ የተመሠረተውን ክሥ በተመለከተም፣ ጉዳዩ በፍ/ቤት በመያዙ ውሳኔውን እየጠበቁ እንደኾነ ያስታወቁት አቡነ ማትያስ፤ “ለቤተ ክርስቲያን ሲባል ነው የተከሰሣችሁት፤ የፍ/ቤቱ ጉዳይ አይቆምም፤” እንዳሏቸው ተገልጿል፡፡ ከውሳኔው በፊት ተተኪ አስተዳዳሪ መመደብ የማይመልሱት ችግር ውስጥ እንደሚከታቸው ፓትርያርኩ ቢጠቁሙም፣ “ስላለው ነገር ልመካከርበትና እነግራችኋለሁ፤” በማለት የዐቢይ ኮሚቴውን አባላት በቡራኬ እንዳሰናበቷቸው ምንጮቹ አክለው ተናግረዋል፡፡
ደኅንነት ነኝ ባዩን ግለሰብ በቁጥጥር ሥር አውሎ በተለይ በደብዳቤው በተሰጠው ምሪት ላይ ያተኮረ የቴክኒክ ምርምራ እያካሔደ ያለው የቦሌ ክፍለ ከተማ ፖሊስ፤ ተጠርጣሪውን ሁለት ጊዜ ፍ/ቤት አቅርቦ ተጨማሪ የምርመራ ጊዜ ቀጠሮ እንደጠየቀባቸውና ለሦስተኛ ጊዜም የፊታችን ሚያዝያ 25 ቀን ፍ/ቤት እንደሚቀርቡ ታውቋል፡፡ በተያያዘ ዜና፣ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት የደብረ ገሊላ ቅዱስ ዐማኑኤል ካቴድራል የትሩፋት(ነፃ) አገልጋይ የኾኑ ዲያቆን፣ ወደ ቢሮ ሥራ ለመመደብ በሚል ለሥራ አስኪያጁ መ/ር ጎይትኦም ያይኑ 100ሺሕ ብር ጉቦ መስጠታቸውን፣ ከግለሰቡ የተገኘው ማስረጃ አጋለጠ፡፡ ፈቀደ ተስፍዬ የተባሉት አገልጋዩ፣ በአንድ የግል ባንክ በተከፈተ የሥራ አስኪያጁ የቁጠባ ሒሳብ፣ ባለፈው ዓመት ሐምሌ 4 ቀን 2009 ዓ.ም. ገንዘቡን እንዳስገቡ፣የገቢ ማዘዣ ሰነዱ(Cash Deposit Voucher) ያረጋግጣል፡፡
በአካውንቲንግ ሞያ በብድርና ቁጠባ ተቋም እንደሠሩና በካቴድራሉ ከ15 ዓመታት ያላነሰ በደጀ ጠኚነት በዲቁና እንዳገለገሉ የሚናገሩት ግለሰቡ፤ ምደባ የጠየቁበት የቢሮ ሥራ፣ ሒሳብ ሹምነት እንደኾነ ተጠቁሟል፡፡ ኾኖም እጅ መንሻ የሰጡበትና በአንድ ከፍተኛ የካቴድራሉ ሓላፊ አማካይነት ለማስፈጸም የሞከሩትን ምደባ በመካከላቸው በተፈጠረ አለመግባባት ምክንያት ባለማግኘታቸው፣ ገንዘባቸውን ባለፈው ማክሰኞ በሓላፊው አማካይነት ማስመለሳቸው ታውቋል፡፡
በአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት የሠራተኞች ቅጥር የሚፈጸመው ጥያቄው በአድባራት ሲቀርብ፣ በሀገረ ስብከቱ እንደኾነና አሠራሩም የቅጥር ኮሚቴ በማዋቀርና ማስታወቂያ በማውጣት በውድድር እንደሚፈጸም፣ ባለፈው መጋቢት አጋማሽ ከአዲስ አድማስ ጋራ ቃለ ምልልስ ያደረጉት ሥራ አስኪያጁ መ/ር ጎይትኦም ያይኑ መግለጻቸው ይታወሳል፡፡ ከአሠራሩ ውጭ የሠራተኛ ቅጥር “አልፎ አልፎ የሚፈጸመው” በአድባራቱ እንደኾነና ከአቤቱታ አቅራቢዎች ጋር አለመግባባት የሚፈጠርበት አንድ መንሥኤ እንደኾነም መናገራቸው አይዘነጋም፡፡
ሥራ አስኪያጁ ይህን ይበሉ እንጅ፣ ከደብረ ገሊላ ቅዱስ ዐማኑኤል ካቴድራል ነፃ አገልጋይ ቅጥር ጋር በተያያዘ አስተያየት የሰጡ ምንጮች፤ “ከአጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት እስከ ሀገረ ስብከቱ ሹማምንት ድረስ በተለይ ለጽ/ቤት ሓላፊዎች ቅጥርና ዝውውር የተዘረጋውን የሙስና ሰንሰለትና የሚያካብቱትን ሕገ ወጥ ሀብት የሚያረጋግጥ ነው፤” ብለዋል፡፡ የማስረጃ ሰነዱ ለብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርኩ መድረሱን ያመለከቱት ምንጮቹ፤ በሰነዱ ትክክለኛነትና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ላይ ማጣራቱ እንደተጠናቀቀ አስተዳደራዊና ሕጋዊ ርምጃ ይወሰዳል ተብሎ ይጠበቃል፤ ብለዋል፡፡


             “የበላይ ባለስልጣናት በፈፀሙት ወንጀል እኛ ዋጋ እየከፈልን ነው”
            
      ባለፈው ሐምሌ ወር በተካሄደው የፀረ ሙስና ዘመቻና በተለያዩ ጊዜያት በልዩ ልዩ የሙስና ወንጀሎች ተከሰው ጉዳያቸው በፍ/ቤት እየታየ የሚገኘው 152 ተከሳሾች፤ ፍትህ ይሰጠን የሚል አቤቱታቸውን ለጠቅላይ ሚኒስትሩ አቀረቡ፡፡
ጉዳያቸው በፍ/ቤት ቀጠሮ ላይ የሚገኘው እነዚህ የሙስና ወንጀል ተከሳሾች፤ ለጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ እንዲቀርብላቸው የላኩት የ152 እስረኞችን ፊርማ ያካተተ የአቤቱታ፤ ደብዳቤ ሲሆን ለጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዲደርስ በፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ለፍትህ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ተመርቶላቸዋል፡፡
ተከሳሾቹ፤ በዚህ አቤቱታቸው ላይ እንደገለፁት፤ የሙስና ወንጀል ሳንፈፅም ለፖለቲካ ፍጆታ ሲባል የታሰርን ሰዎች በመሆናችን ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሌሎች ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሆን ፍትህ እንድናገኝ ሊያደርጉን ይገባል ብለዋል፡፡ “ትልልቆቹና ዋንኞቹ አሳዎች በሰሩት ሙስና እኛ ዋጋ ከፋይ ልንሆን አይገባም” ያሉት እነዚሁ ተከሳሾች፤ “አብዛኛዎችን የራሳችን የሆነ ምንም ነገር የሌለን በኪራይ ቤት የምንኖርና በወንጀል ሥራ ውስጥ ተሳትፎ ያላደረግን ሰዎች ነን” ብለዋል፡፡ አቤቱታ አቅራቢዎቹ ዘመቻው የፖለቲካ መሆኑን ጠቁመው፤ ያለበቂ ማስረጃ ክስ ቀርቦባቸው ያለአግባብ እየተሰቃዩ መሆኑን በአቤቱታቸው ላይ ገልፀዋል፡፡ ፍርድ ቤቶች ያለ ተፅዕኖ በነፃነት ፍትህ እየሰጡን አይደለም ያሉት አቤቱታ አቅራቢዎቹ “ያለ ስራችን እጅግ አሳፋሪና ሞራላችንን የሚነካ ሙሰኞች የሚል ስም ተሰጥቶን በእስር እየተሰቃየን እንገኛለን፡፡ ስለዚህም ፍ/ቤቱ ነፃ ሆኖ የሚገባንን ፍትህ ይሰጠን ዘንድ እንጠይቃለን” ብለዋል፡፡
እነዚሁ አቤቱታ አቅራቢዎች በአቤቱታቸው ላይ እንደገለፁት፤ “አቃቤ ህግ ያለፍርድ ቤት ትዕዛዝ አወጣሁ በሚላቸውና ትክክለኛውን የፍትህ ሂደት ባልጠበቁ የተለያዩ ማስረጃዎች ማቅረብ ሰበብ የማይገባንን ዋጋ እየከፈልን በመሆኑ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር በመሆኑን ለአቤቱታችን አፋጣኝ ምላሽ ይሰጡን ዘንድ እንጠይቃለን” ሲሉ ተማፅነዋል፡፡


             “ለመለወጥ የተዘጋጀ አዲስ አመራር ነው የገጠመኝ”

    የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከፍተኛ ኮሚሽነር ዛይድ አል ሁሴን፤ በኢትዮጵያ በነበራቸው የሦስት ቀናት ጉብኝት ከእስር ከተፈቱ ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞችና ሲቪል ማህበራት አመራሮች እንዲሁም አባ ገዳዎች ጋር በአገሪቱ የሰብአዊ መብት አያያዝ ላይ መነጋገራቸው ታውቋል፡፡
ከፍተኛ ኮሚሽነሩ ከእስር ከተፈቱ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች፣ጋዜጠኞች፣ጦማሪያን፣የዋልድባ መነኮሳትና ከሙስሊሙ መፍትሄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት ጋር  ባደረጉት ውይይት፣ በእስር ቤቶች ውስጥ ስለሚፈጸሙ የመብት ጥሰቶች ተነግሯቸዋል፡፡ በውይይቱ ላይ ተሳታፊ የነበረው  ጋዜጠኛ እና የሰብአዊ መብት ተሟጋቹ እስክንድር ነጋ፤በኢትዮጵያ ውስጥ የሚፈፀሙ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች አሰቃቂ እንደሆኑ ኮሚሽነሩ መረዳታቸውን  ጠቁሟል፡፡ ኮሚሽነሩ በሀገሪቱ ስለሚፈጸሙ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች ብቻ ሳይሆን  በቀጣይ እንዴት ጥሰቶቹን ማስቀረት ይቻላል በሚለውም ላይ ከተሳታፊዎች ጋር እንደመከሩ ለማወቅ ተችሏል፡፡
በሀገሪቱ የሚፈፀሙ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች ከምንጫቸው ሊደርቁ የሚችሉት ጠ/ሚኒስትር ስለተቀየረ ወይም አዲስ ካቢኔ ስለተቋቋመ አሊያም ማዕከላዊ ስለተዘጋ ሳይሆን በአጠቃላይ ዲሞክራሲያዊ ስርአት ሲረጋገጥ መሆኑን  መግባባት ላይ መደረሱን የውይይቱ ተሳታፊዎች ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡
“በተቃውሞ ላይ በመሳተፋቸውና መንግስት ላይ ከሰነዘሩት ትችት ጋር በተያያዘ ታስረው የነበሩ ጦማርያንን ጨምሮ በርካታ ቁጥር ያላቸው ተቃዋሚ ፖለቲከኞችና ሌሎችም ከእስር መለቀቃቸውን እንደሚያደንቁ የገለጹት ዛይድ አል ሁሴን፤በዚህ ጉብኝታቸውም ከጥቂቶቹ ጋር በግል ለመነጋገር ዕድል ማግኘታቸውንም ጠቁመዋል፡፡  
በኦሮሚያ ከክልሉ ባለሥልጣናትና አባ ገዳዎች ጋር ተገናኝተው መነጋገራቸውን የገለጹት ከፍተኛ ኮሚሽነሩ፤ከክልሉ ባለሥልጣናትና አባ ገዳዎች ጋር የተደረገውን ይህን የመጀመሪያ ግንኙነት መንግስት በማመቻቸቱ ምስጋና አቅርበዋል፡፡ አባ ገዳዎች በክልሉ ያልተመጣጠነ ሃይል በመጠቀም በዜጎች ላይ ግድያ የፈጸሙ ወገኖች ተጣርተው፣ ለህግ እንዲቀርቡና የሁሉም ኢትዮጵያውያን ሰብአዊ መብቶች እንዲከበር መጠየቃቸውንም የጠቀሱት ኮሚሽነሩ፤በክልሉ ለረዥም ዘመን የዘለቀውን የሰብአዊ መብት ችግሮች ከአዲሱ አመራር ጋር በመሥራት እንፈታዋለን ብለው ተስፋ እንደሚያደርጉ  ገልጸውልኛል ብለዋል፡፡ ከጠ/ሚኒስትር ዐቢይ ጋር በአገሪቱ የሰብአዊ መብት አያያዝ ጉዳይ ላይ ያደረጉት ውይይትም ውጤታማና ተስፋ ሰጪ ነው ብለዋል- ኮሚሽነር ዛይድ አል ሁሴን፡፡
የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ቢሮም፣ በኦሮሚያና አማራ ክልሎች  የተፈጸሙ የሰብአዊ መብት ጥሰቶችን መመርመር እንደሚፈልግ ያስታወቁት ከፍተኛ ኮሚሽነሩ፤ይህም የሰብአዊ መብት አያያዝን የተሻለ ለመገምገም፣መንግስት የዲሞክራሲ ምህዳሩን ለማስፋትና  ለሰብአዊ መብት ጥሰቶች ተጠያቂነትን ለማስፈን በሚያደርጋቸው ጥረቶች ለማገዝ የሚያስችል ይሆናል፡፡” ብለዋል፡፡
በተመሳሳይ ኮሚሽነሩ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ዶ/ር ወርቅነህ ገበየሁ፣ ከኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን ኮሚሽነር ዶ/ር አዲሱ ገብረ እግዚአብሄር እንዲሁም ከጠ/ሚኒስትር ዶ/ር አብይ አህመድ ጋር በሀገሪቱ የሰብአዊ መብቶች ይዞታ ላይ የመከሩ ሲሆን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የሰብአዊ መብት ኮሚሽን የምስራቅ እና ደቡብ አፍሪካ 17 አገሮችን የሚሸፍን ፅ/ቤቱን በአዲስ አበባ ለመክፈት ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር  ስምምነት ተፈርሟል፡፡
የተመድ የሰብአዊ መብት ኮሚሽን ከፍተኛ ኮሚሽነሩ ዛይድ አል ሁሴን፣ የኢትዮጵያ ጉብኝታቸውን አጠናቅቀው  ለውጭ መገናኛ ብዙኃን በሰጡት መግለጫ፤”በኢትዮጵያ ለመለወጥ የተዘጋጀ አዲስ አመራር ነው የገጠመኝ” ብለዋል፡፡

 ደራሲ ከበደ ሚካኤል ከፃፏቸው አስገራሚ ተረቶች መካከል የሚከተለው ተረት ደጋግሞ ቢነገር እንኳ የማይሰለችና ትምህርታዊ ተምሳሌት ነው፡፡
አንድ ፈረሰኛ ወደ አንድ ከፍተኛ ተራራ ይጓዝ ነበር፡፡ ወደ ተራራው ወገብ ላይ ሲደርስ አንድ ምስኪንና አንድ እግሩ ሽባ የሆነ ሰው እንዳቅሙ ቋጥኙን እየቧጠጠ ለመውጣት ሲፍጨረጨር ያገኛል፡፡
ፈረሰኛው፤
ወዳጄ፤ ይህን የሚያህል ተራራ እንዲህ ተንፏቀህ የሚገፋ አይደለም፡፡ ስለዚህ እንደምንም ፈረሴ ላይ ላውጣህና አፈናጥጬ ዳገቱ ጫፍ ላይ ላድርስህ?
ሰውዬው፤
እግዚአብሔር የባረከህ ሰው ነህ! ግን ሥጋቴ እንዳላጣብብህ ነው፡፡ ለማፈናጠጥ ይበቃል ብለህ ነውን?
ፈረሰኛው፤
እንደምንም ተጣበን እንወጣዋለን እንጂ በዚህ ሁኔታ በፍፁም ጥዬህ ብሄድ ግፍ ይሆንብኛል፡፡ ሰው እንኳ ባይኖር ተራራውም ይታዘበኛል፡፡ ስለዚህ ና ውጣ ግዴለህም፡፡
ሰውዬው፤
ፈጣሪ ምስክሬ ነው፤ ለእኔ የተላክ ውድ አዳኝ መልዐክ ነህ፡፡ አምላክ ውለታህን ይክፈልህ!
ፈረሰኛው ተሸክሞ ፈረሱ ላይ አስቀመጠውና ተራራውን ተያያዙት፡፡ ጥቂት እንደሄዱ ግን፤
ሰውዬው
ወዳጄ፤ ቅድም እንደፈራሁት በጣም ተጣበናል፡፡ ብወርድልህ ይሻላል፡፡
ፈረሰኛው፤
እንደሱማ አይሆንም፡፡ ባይሆን የተወሰነውን ዳገት እኔ በእግሬ ልሞክረው፤ አንተ ፈረሱን ያዝ አለውና ፈረሱን ሰጥቶት ወረደ፡፡ ሰውየው እየጋለበ ዳገቱን እየወጣ እየራቀ ሄደ፡፡
ፈረሰኛው በእግሩ ዳገቱን ተያያዘው፡፡ ሆኖም ባለፈረሱ እየራቀ ሄደ፡፡ ፈረሰኛው ሥጋት እየገባው በተቻለው ፍጥነት ሊከተለውና ሊጠጋው ቢሞክርም ሰውዬው ፈረሱን ይብስ አፈጠነው፡፡
ፈረሰኛው መጣራት ጀመረ፡፡ ወይ የሚለው ግን አጣ፡፡ ሰውዬው ፈረሱን ይዞ ሊጠፋ መሆኑ ለፈረሰኛው ገባው፡፡
“አንተ ሰው፤ ግዴለም ፈረሱን ይዘኸው ትሄዳለህ፡፡ ግን አንድ ነገር ቆም ብለህ ስማኝ እባክህ፡፡ እንደማልደርስብህ ታውቃለህ፡፡ ጆሮህን ብቻ አውሰኝ?” ሲል ለመነው፡፡
ሰውዬው ርቀቱን በደንብ ካረጋገጠ በኋላ፤
“እሺ ምንድነው ልትነግረኝ የፈለከው?”
ፈረሰኛውም፤
“ወዳጄ፤ መቼም አንድ ቦታ ወርደህ ከሰው መቀላቀልህ አይቀርም፡፡ አደራህን ይሄን አሁን እኔን የሰራኸኝን ነገር ለማንም ሰው እንዳትነግር፡፡ አለበለዚያ ደግ የሚሰራ ሰው ይጠፋል!”
*   *   *
የሚያጪበጭቡልን፣ የሚያሞግሱን፣ የሚያወድሱን ሁሉ ደግ ላይሆኑ እንደሚችሉ አንርሳ! ሰዎች ለችግራቸው የደረሰላቸውን ሰው እንኳ ውለታውን መመለስ ቀርቶ ጭራሹን ተንኮል ሊሰሩበት፣ ግፍ ሊውሉበት ይችላሉ፡፡ ደግ የሚሰራ እንዳይጠፋ የሰራነውን ክፉ ነገር ለሰዎች ባንነግር መልካም ነው፡፡ አገራችን ኢትዮጵያ የብዙ ችግር ባለቤት ናት፡፡ የብዙ ፀጋም ባለቤት ናት፡፡ ከእነ ችግሮቹ ሀገሩን አሳቢ ብዙ ንቁ ዜጋ፣ ብዙ ልባም ሰው፣ ብዙ የተማረ፣ አስተዋይና አገር ሊለውጥ የሚችል አዋቂ አላት፡፡ እንዲህ ዓይነቱን ሰው በዲዮጋን ፋኖስም ቢሆን ፈልጎ ማግኘት ተገቢ ነው፡፡ ሰዓሊ ገ/ክርስቶስ ደስታ ብራውኒንግን ጠቅሶ እንደፃፈው፤
“… ደግሞም፤ ማወቅ ማለት፤
ከውጪ ያለውን ሄዶ ከመፈለግ
ከውስጥ የበራውን እንዲወጣ ማድረግ”
… ወቅታዊነት ያለው ጥበብ ነው፡፡
ሀገራችን የብዙ ካህናት፣ የአያሌ ጠቢባን፣ የበርካታ አበው ፈላስፎች አገር ሆና ሳለ፤ የትምህርት ሥርዓቷ እየተዳከመ፣ ምሁር ማፍራቷ እየተመናመነ መምጣቱ ቢያንስ ሊያስቆጨን የሚገባና አንገብጋቢ ጉዳይ መሆኑን መረዳት ይጠበቅብናል፡፡ የትምህርት ድክመት የሀገርን ድክመት የሚጠቁም ከባድ የመከራ ደወል ነው፡፡ ባለሙያ የምናፈራው ከዚህ የዕውቀት ማሳ ነው፡፡ “ኩሉ አመክሩ ወዝሰናየ እፅንዑ” (ሁሉንም ሞክሩ የተሻለውን አፅኑ) የሚለው የጥንቱ ዲግሪ ላይ የተፃፈው መልዕክት፤ ተምረን በየአቅጣጫው ጥረት ማድረግና አገርን የማሳደግ አደራ እንዳለብን ጠቋሚ ጥቅስ ነበር፡፡፡ አሁንም በነበር መቅረት ያለበት ሀሳብ አለመሆኑን ማስተዋል ይጠበቅብናል! መንገዱ መኖሩን እያየን አላየንም ማለት ሐጢያት ነው፡፡ መማር እየቻልን አለመማርም ሐጢያት ነው፡፡ ለሐጢያታችን ሥርየት የምናበጀው ዕውቀት ሲኖር ነው፡፡ አገር የምትድነው በአዋቂዎቿ የተከፈተ ዐይን ነው፡፡
“ይቺን ጨቅላ መጥሐፍ የምታነቡ ሁሉ
አደራ ስለኔ ማርያም ማርያም በሉ፡፡
ከሃያ ስድስቱ ወንዶች ፊደላት
አርግዣለሁና መዝገበ - ቃላት
ከሆዴ ያለውን የትምህርት ሽል
ያለጭንቅ እንድወልድ እንድገላገል!
ስንት እልፍ አበው ናቸው አርግዘው የሞቱ
ቀኝ እጃቸው አጥሮ ፊደል በማጣቱ
ለትምክህት አይደለም ይህን መናገሬ
ለማስቀናጠ እንጂ ሰነፉን ገበሬ!
ሐዋርያው ሲናገር ወደ ምዕመናኑ
ለምትበልጥ ፀጋ ይላል ቅኑ አስቀኑ”
በተባለባት አገር የትምህርት ደሀ ልትሆን አይገባም፡፡ መልሰን ራሳችንን ለመፍጠር መፍረምረም አለብን። ብልሃቱንና መላውን ካበጀን የማንወጣው ዳገት አይኖርም፡፡ እጅ ለእጅ ከተያያዝን፣ አዕምሮ ለአዕምሮ ከተናበብን፤ መሻሻል ግዴታችን ይሆናል፡፡
ሁሉንም አዳርሰን ስናበቃ እያንዳንዱን በተናጠልና በጥበብ ካቀድን፣ ለሀገር ቅጥ ቅጥ ማበጀት አያቅተንም። መልካም እንሰራለን ያልነው ሁሉ ላይሳካ ቢችልም፤ ለዛም መዘጋጀት አንድ መልካም ነገር ነው፡፡ ሁሉንም ሰው እናረካለን ብለን አናስብ፡፡ ፈረንጆቹ፤ “To satisfy all is to satisfy none” የሚሉት ወደው አይደለም - ዕውነትም “ሁሉንም ለማርካት መሞከር ማንንም አለማርካት ነው!”

Sunday, 29 April 2018 00:00

አፍታ ለማለፊያዎቻችን

       የሥነ-ጥበብን ውስጥ ውስጡን ለመመርመርና ለማድነቅ ይቅርና ላይ ላዩንም ለመነካካት ቸልታ ከሚያሳይ ማኅበረሰብ የፈለቁት የሃገራችን ሠዓልያንና የሥነ-ጥበብ ማኅበረሰቡ፣ለሠፊው የኢትዮጵያ ሕዝብ “ባርጤዛ” ሆነው ቆይተዋል። ሆኖም ሠዓሊውና የሥነ-ጥበብ ማኅበረሰቡ ይህ ተቃርኖ መኖሩን ፈጽሞ የማያውቅ እስኪመስል ለሙያው ባለው ልባዊ ፍቅርና ጽናት፣ ድንበሮቹን እየገፋ፣ ጭላንጭል ለውጦችን የሚያይበት ጊዜ እየመጣ ይመስላል፡፡ እዚህ ላይ በተለይ መንግስት ለሥነ-ጥበብ ያለው ጥልቅ ዝንጋዔ መቼ ሊሻሻል እንደሚችል ግምትም ሆነ መላምት ለማስቀመጥ አዳጋች ነው፡፡ እንዲህ ድንግዝግዝ ባለ ሁኔታ ስለ ሥነ-ጥበብ ማሰብና ማለም ደግሞ የጥበብ ልግስና ነውና ደስ ያሰኛል፡፡ ከላይ የጠቀስኩት ተቃርኖን የሚቃረን መልክ ባለው ገጽ ደግሞ የሃገር ባለ ውለታ የሆኑ አያሌ ሠዓልያን የሚገኙባት ሃገር ውስጥ መኖራችን የሚያስገርም ነው፡፡ ይህ ተለቅ ሲል ደግሞ እነዚህ የሃገር ባለ ውለታ የሆኑ ሠዓልያንን ያፈራ ታላቅና አንጋፋ ት/ቤትን እናገኛለን፡፡ ይህ ት/ቤት እንደ ተቋም በመንግስት ቢተዳደርም፣ ሕልውናው የተመሰረተውና የጸናው ግን ለሙያው ፍቅርና ቦታ ባላቸው ታላላቅ ሠዓልያን መስዋዕትነት ነው። ይሄ ደግሞ ማንኛውንም ኢትዮጵያዊ እንደ ዜጋ የሚያኮራ፣ መንፈስና ነብስን የሚያጠግብ እንዲሁም የሕሊና ምቾት የሚሰጥ ነው፡፡ የዚህ አጭር ጽሁፍ ዓላማ በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አለ የሥነ-ጥበብና ዲዛይን ት/ቤት ውስጥ ለረዥም ዘመናት ያስተማሩትንና በቅርቡ ያረፉትን ቀራጺ ታደሰ በላይነህን በጣም በጥቂቱ ለማውሳት ነው፡፡
ቀራጺ ታደሰ በላይነህ ባጋጠማቸው ሕመም ለሶስት ወራት ህክምና ሲከታተሉ የነበሩ ሲሆን መጋቢት 29 ቀን 2010 ዓ.ም እስኪያርፉ ድረስ በት/ቤቱ ለሃምሳ ዓመታት በመምህርነት አገልግለዋል። እነዚህ ሃምሳ አመታት የማስተማር ብቻ ሳይሆን ሃገራችን የሥነ-ጥበብ ሙያተኞችን እንድታገኝ የማስቻል ኃላፊነትንም የሚጨምር ነበር፡፡ ለአስተዋጽኦዋቸው የሚመጥን ብሔራዊ እውቅና ባይቸራቸውም ባለፈው ሃሙስ በት/ቤቱ የመታሰቢያ ዝግጅት ተሰናድቶ የተዘከሩ ሲሆን ያስተምሩበት የነበረው አንዱ ስቱዲዮም በስማቸው ተሰይሟል፡፡
በቀድሞ ስያሜው የአዲስ አበባ ሥነ-ጥበብ ት/ቤት በመባል የሚታወቀው ይህ ተቋም የተመሰረተው ከስድሳ ዓመት በፊት ሲሆን ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ በልደታቸው ቀን ሐምሌ 16 ቀን 1950 ዓ.ም ነበር መርቀው የከፈቱት፡፡ የትምህርት ቤቱ መስራች አሁን በስማቸው የሚጠራው ሠዓሊ አለ ፈለገሰላም ሕሩይ ሲሆኑ ትምህርት ቤቱ ተማሪዎችን ማስመረቅ ብቻ ሳይሆን ከተመረቁም በኋላ ወደ ውጪ ሃገራት በመላክ፣ ተምረው ሲመለሱም በትምህርት ቤቱ በመምህርነት እንዲቀጥሉ እድል መክፈት ችሏል፡፡ በዚህ እድል ተጠቃሚ ሆነው ወደ ቀድሞ ሶቭየት ሕብረት በማቅናት ትምህርታቸውን በLeningrad Repin Academy of Art ኪነ-ቅርጽ ያጠኑትና ወደ ሃገር ተመልሰውም በትምህርት ቤቱ ማስተማር ከጀመሩት ቀደምት መምህራን አንደኛው ታደሰ በላይነህ ናቸው፡፡
ጋሽ ታደሰ በላይነህ ከመምህርነታቸው ባሻገር በሙያቸው የተለያዩ ግልጋሎቶችን አበርክተዋል። በአዲስ አበባና በተለያዩ ክፍለ ሃገራት በሚገኙ አብያተ ክርስቲያናት ቅርጾችን የሰሩ ሲሆን በጎላ ሚካኤልና በየካ ሚካኤል የሰሯቸው ተጠቃሾች ናቸው፡፡ በዩጎዝላቪያ FORMA VIVA በተሰኘው የዓለም ቅርጻ-ቅርጽ አዋቂዎች ድርጅት ባደረጉት ተሳትፎና በቆይታቸው በሰሩት ስራም የዲፕሎማ ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡
በአለ የሥነ-ጥበብና ዲዛይን ት/ቤት ከ1983 እስከ 1989 የኃላፊነት ቆይታቸውም፤ ትምህርት ቤቱን በዳይሬክተርነት የመሩ ሲሆን ተቋማዊ የኔነት እንደነበራቸውም በመታሰቢያቸው ላይ በሰፊው ተወስቷል፡፡ ለትምህርት ቤቱ ተማሪዎችና መምህራን የመማሪያና የመስሪያ ስቱዲዮዎችን በማስገንባት ት/ቤቱ ወደ ከፍተኛ የትምህርት ተቋምነት እንዲሸጋገር የተጀመረውን ትግል አጠናክረው በመቀጠል አዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲን እንዲቀላቀል ከፍተኛውን ድርሻ እንደተወጡ ተባባሪ ፕሮፌሰር በቀለ መኮንን ገልጸዋል፡፡  
በሌላ በኩልም ጋሽ ታደሰ በላይነህ፤ የእንጦጦ ቴክኒክና ሙያ ኮሌጅ ሲቋቋም፣ ምስረታውን በማገዝና አስፈላጊውን ሙያዊ ድጋፋቸውን በመቸራቸው የሚወሱ ታላቅ የሃገር ባለውለታ ናቸው፡፡ ጋሽ ታደሰ በላይነህ ካጠኗቸውና በአደባባይ ላይ ሊቀመጡ ከሚገቡ ቅርጾች መካከል የአጼ ቴዎድሮስ ኪነ-ቅርጽ እንደሚገኝበት የጠቆሙት ረዳት ፕሮፌሰር አበባው አያሌው፤ በከተማችን ስለሚገኙና በውጭ  ዜጎች ስለተሰሩት ኪነ-ቅርጾች መሰረት ያለውና የተብራራ እውቀት እንደነበራቸውም  አውስተዋል፡፡
ይህች አፍታ እንደ ቀራጺና መምህር ጋሽ ታደሰ በላይነህ ያሉ ባለውለታዎቻችንን ለመዘከር እጅግ ቁንጽል ብትሆንም ጊዜና እርጋታው ተገኝቶ የሥነ-ጥበብ ታሪካችንን ለማጥናትና ለመሰነድ፤ የሥነ-ጥበብ ፍቅርና አክብሮት የሚኖረው ትውልድ ለመፍጠር የሚያስችሉ ጥረቶች በመንግስትና ሌሎች አጋዥ የማኅበረሰብ ክፍሎች እስኪጎለብቱ፣ማለፊያ የሆኑ ሥነ-ጥበባዊ ማንነቶችን ማውሳቱ ተገቢ ነው፡፡

Sunday, 29 April 2018 00:00

ድማሚት (1+1=3)

 የአንዳንድ መጽሐፍ አርዕስቶች ለየት ማለት ቀልብ ይስባል፡፡ ይኼ አንዱ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡ የሽፋኑ አርእስት በአሀዝም በፊደልም ‹‹አንድ ሲደመር አንድ እኩል ይሆናል ሶስት›› ነው የሚለው፡፡ ONE PLUS ONE EQUALS THREE. ጸሐፊው DAVE TROTT ስለ መጽሐፉ ፋይዳ በመግቢያ ገጹ ላይ ያሰፈረው አጭር ማስታወሻም...
which is the point of this book.
under the old system 1+1=2
 under the new system 1+1=3
በነባሩ ስሌት ውጤቱ ሁለት የነበረው፤ በአዲሱ አተያይ/ቀመር ሦስት ሲሆን እንደ ማለት፡፡
 1. HERD THINKING - መንገኝነት
ከጥቂት ዓመታት በፊት አፍሪቃ (ኮንጎ) ውስጥ ለማረፍ ያኮበኮበ አይሮፕላን በድንገት ተከሰከሰ፡፡ አንድ ተሳፋሪ ብቻ ተርፎ ወደ ሆስፒታል ሲወሰድ፣ ሌሎቹ ሀያ ተሳፋሪዎችና ሁለቱ አብራሪዎች ህይወታቸው አለፈ፡፡ አይሮፕላኑ ዘመናዊና በቴክኒክ አቋሙ የተሟላ፣አብራሪዎቹ በቂ ልምድና ብቃት ያላቸው፣ የአየር ንብረት ሁኔታው ለበረራ በጣም አመቺ ስለነበር የአደጋውን መንስኤ ለማወቅ በጣም አስቸገረ። በመጨረሻም ተርፎ ሆስፒታል የገባውን ሰው መጠየቅ ግድ ሆነ፡፡
ሰውየው ሲመሰክርም፤ ከተሳፋሪዎቹ መካከል አንዱ በድብቅ ትንሽዬ አዞ ይዞ ገብቶ ነበር፡፡አይሮፕላኑ ለማረፍ ሲያዘቀዝቅ አዞው ከነበረበት ቦርሳ ወጣ፡፡ ተሳፋሪዎቹ ሲያዩት በፍርሀት እየተንደረደሩ ወደ አብራሪዎቹ አቅጣጫ መነባበር ያዙ፡፡ ካፒቴኑ ባሉበት እንዲቆዩ ትእዛዝ ቢሰጥም ሰሚ አጣ፡፡ አይሮፕላኑ አፍንጫውን ቁልቁል ወደ መሬት ባደረገበት በዚያ ቅጽበት፤ ተሳፋሪዎቹ ሁሉ ባንድ ላይ ተሰባስበው ወደፊት ስለመጡ ሚዛኑን ስቶ ክፉኛ ባፍጢሙ ተከሰከሰ፡፡
ሚጢጢው አዞ በማንም ላይ አደጋ ለማድረስ የማይችል ገና ለአቅመ አዞነት ያልደረሰ መሆኑን ለማስተዋል ፋታ የወሰደ አልነበረም፡፡ የችግሩ ዋንኛ መንስኤም ይኸው ነበር - ከተሳፋሪዎቹ መካከል አንዳቸውም በተለየ መንገድ ማሰብ አለመቻላቸው፡፡ አንዱ ያደረገውን ኮርጆ ሌላውም ስለቀጠለበት ለከፋ አደጋ ተጋለጡ፡፡
በአለም ላይ ለሚከሰቱ የመከራና ሰቃይ፣ ጦርነት፣ ሽብር፣ ጅምላ ጭፍጨፋ . . .ወዘተ መነሻ ፍርሀት የሚፈጥራቸው አጉል ውሳኔዎች ናቸው፡፡ መላው ዜጋ ብቻውን እንደተተወ፣ባይተዋርነት፣ የመገለል ስሜት ሲያድርበት፤ከሌላ እንደሱ በፍርሀት ቆፈን ውስጥ ካለ ዜጋ ጋር መሆንን ምርጫው ያደርጋል፡፡ ፍርሀት አመክንዮን፡እንዴትና ለምን ብሎ መጠየቅን፣ምክንያታዊነትንና ማመዛዘንን ሁሉ ነጥቆ በስሜታዊነት ይነዳል፡፡ ለዚህም ነው ጥርስን ነከስ ሀሞትን ዋጥ ማድረግን የሚጠይቀው ውሳኔ በቁርጥ ቀን ላይ ግድ ይላል መባሉ፡፡ ከመንጋው መካከል ነጠል ብሎ በግል በራስ መወስን ለመቻል፡፡
ባለቅኔው  እንዲል...
ከሰው መንጋ እንገንጠል
ላንዳፍታ እንኳ እንገለል
በእፎይታ ጥላ እንጠለል... እንዲል ባለቅኔው
2. MOTIVATION - ማፋፋም
ቢል ሻንክሊ የሊቨርፑል ቡድንን ተጫዋቾች በከፍተኛ የአሸናፊነት መንፈስ ቅስቀሳ በማድረግ ከሁለተኛ ዲቪዚዮን አውጥቶ ወደ አንደኛ ዲቪዚዮን ወሰደው፡፡ አሁንም እያነሳሳ የዲቪዚዮኑ አሸናፊ አደረጋቸው፡፡ በእንግሊዝ ውስጥ ምርጥ ቡድን እንዲሆኑ አራገባቸው - ሆኑ፡፡ ቀጥሎም በአውሮጳ ዙሪያ ግጥሚያ በማድረግ ድል እንዲቀዳጁ አቀጣጠላቸው - ድል በድል ሆኑ፡፡ በ1965 የጀርመን አሸናፊ ከነበረው EC Cologne ቡድን ጋር ተጋጠሙ፡፡ ኮሎኝ ውስጥ አሸነፉ፡፡በመልስ ጨዋታውም ራሳቸው ሜዳ ላይ እንዲሁ፡፡ እናም በመጨረሻው ወሳኝ ግጥሚያ ከሁለቱም ሜዳ ውጪ ሮተርዳም ውስጥ ፍልሚያ የሚሰኝ ግጥሚያ አድርገው፣ በተጨማሪ ሰአት አሸነፉ እና ስማቸው ገነነ፡፡ ቡድኑም ወደ ኢንግላንድ ተመለሰ፡፡ ከሦስት ቀናት በኋላ ከቼልሲጋ ግጥሚያ ይጠብቃቸዋል፡፡
ተጫዋቾቹ መልበሻ ክፍል ውስጥ በድካም ዛል ብለው እንደተቀመጡ ሻንክሊ ገብቶ ፊት ለፊታቸው ቆሞ ትክ ብሎ አያቸው፡፡ እውነትም ድካም ይነበብባቸዋል፡፡ እናም እንዲህ አላቸው፡- ‹‹ልጆች መናገር ያልነበረብኝ ቢሆንም መደበቅ ደሞ አልችልምና ልንገራችሁ...›› አለና ወደ ኪሱ ገብቶ በደማቅ ወረቀት ላይ የታተመ ጽሑፍ አውጥቶ እያሳያቸው፣ ‹‹ይኼ ቼልሲዎች ስለ ናንነተ አሳትመው ያሰራጩት ነው፡፡ እናም ባለፈው ጨዋታችሁ ትንቅንቅ ስታደርጉ አቅማችሁን ሁሉ ስላሟጠጣችሁ ዛሬ በዝረራ እንደሚያሸንፏችሁ ጉራ ነፍተው የጻፉት ነው፡፡ እና እንዴት ነው እንዳሉትም ደክማችኋል እንዴ!››
በተጫዋቾቹ መሀል መጀመሪያ ቅሬታ ከዚያም የመጠቃት መንፈስ፣ ከዚያም እንደ ግስላ እመር አመር እያሉ በእልህ ይጎፈሉ ጀመር፡፡ ጨዋታውን እንደለመዱት በድል ካጠናቀቁት በኋላ፤ ሻንክሊ ወደ ቼልሲ አሰልጣኝ ሄዶ ሰላምታ ሲሰጠው አሰልጣኙ ቶሚ ዶቼቲ በጣም ተገርሞ፤ ‹‹ከዚያ የሮተርዳም ግጥሚያ በኋላ ልጆችህ በምን ተአምር እንዲህ አይነት ብቃት ይዘው ሊገኙ ቻሉ!›› ሲል ጠየቀው። ሻንክሊ ‹‹ይህን ስላስነበብኳቸው ነው›› ብሎ ያቺን ደማቅ ወረቀት አውጥቶ ሰጠው፡፡ ቶሚ ወረቀቱን አይቶ ‹‹ይኼ የምን እንቶ ፈንቶ ነው!›› ብሎ ጮኸ፡፡ ወረቀቷ በሌላ በማንም እጅ ያልነበረችና ልጆቹን አቀባብሎ ለመተኮስ ራሱ ሻንክሊ ያዘጋጃት አንዲት ኮፒ ብቻ ነበረችና፡፡ አለ አይደል በቃ ትንሽ ለመቆስቆስ፡፡
3. MIND BLOWING - እፎይታ
 በ1866 አሜሪካ የnitroglycerineን ፍንዳታ ጥቅም ላይ በማዋል ተራራና ቋጥኞችን ነድሎ የውስጥ ለውስጥ መንገዶች ለመስራትና መላ አህጉሩን ለማገናኘት ቋምጠው ነበር። ጉዳዩ ቢሳካ ለነዳጅ ፍለጋና ማእድን ቁፋሮ የሚባክነውን በመቶ የሚቆጠሩ ሰራተኞችን ጉልበትም ቆጣቢ ነው ተብሎ ነበር፡፡ ችግሩ nitroglycerine ፈሳሽ ስለነበር እርሱን ለማጓጓዝ በተደረጉ ሙከራዎች የብዙዎች ህይወት ተቀጠፈ። በመርከብና የተለያዩ ስፍራዎች ካለቁት ሰዎች በተጨማሪ ድንገተኛ ፍንዳታው ከተከሰተበት ግማሽ ማይል ርቀው ባሉ መኖሪያ ቤቶች 3ኛ ፎቅ ደርሶ መስኮት በመገነጣጠል የአንድ ሰው ክንድ እስከመጉመድና በመንገድ ላይ ተፈነጣጥረው የተገኙ የሰው ጀርባ አጥንት ዜናዎች መነጋገሪያ ሆኑ፡፡
ከሁለት አመት በፊት በ1864  በዚሁ የፍንዳታ ጦስ ታናሽ ወንድሙን ያጣ ሰው ነበረ - አልፍሬድ ኖቤል፡፡ ኖቤል ሳይንቲስት እና ጦርነት የማይወድ (Scientist and Pacifist) ሰው ነበረ፡፡ እናም nitroglycerineን በቀላሉ ለመያዝና ለማጓጓዝ የሚያስችል ፈጠራ ፈጠረ፡፡የፈጠራውንም ስም Dynamite (ድማሚት) ብሎ ሰየመው፡፡ ጥሩ ማሸጊያም ስለሰራለት የሚፈለገው ቦታ ደርሶ እስኪፈነዳ ድረስ ምንም ጉዳት እንዳያመጣ በማድረጉ የብዙዎችን ህይወት ታደገ። በዚያም እጅግ ብዙ ገቢ ለማግኘት ቻለ፡፡ እንደ አንድ ጦርነትን እንደሚጸየፍ Pacifist ሰውም የተሻለች ዓለም በመፍጠር ረገድ አቅሙ የፈቀደውን እገዛ ማድረጉ ተሰማው፡፡ ታላቅ ወንድሙ ታምሞ እስኪሞት ድረስ፡፡
አንድ የፈረንሳይ ጋዜጣ ዜናውን አወጫብሮ የወንድሙን ሞት ራሱ አልፍሬድ ኖቤል እንደሞተ አድርጎ ዘገበው፡፡ አርእስተ ዜናው እንዲህ ነበር የሚለው፡- ...‹‹ነጋዴው ኖቤል ሞተ››
ኖቤል ክው ብሎ ደነገጠ፡፡
ጋዜጣው ሀተታውን ሲቀጥልም፡- ‹‹የሰው ልጆችን ከመቼውም ጊዜ በበለጠ በፍጥነት እንዲሞቱ መንገድ የቀየሰ ሰው›› ይላል፡፡ ኖቤል ማመን አቃተው፡፡
እርሱ ስለ ራሱ የሚያስበው የነበረው እውነት፤ ድማሚትን በመፍጠሩ የሌሎችን ሕይወት የታደገ ግብረ ሰናይ ሰው መሆኑን ነበር፡፡ በዓለም ገሀድ እውነት ዓይን ሲታይ ግን ዳይናማይትን መፍጠር በጭራቅ እንዲመሰል አድርጎት ኖሯል ለካንስ!
ስለዬህም ኖቤል በጋዜጣ ላይ ከተገለፀበት መልኩ በተለየ በሌላ መልካም ስም ይታወስ ዘንድ በጽኑ ፈለገ፡፡ እናም የኖቤል ሽልማት የተሰኘውን የሽልማት ድርጅት አቋቋመ፡፡
በየዓመቱ በሳይንስ፣ ኬሚስትሪ፣ ህክምና፣ ሥነ ጽሑፍና ልዩ የዓለም የሰላም ኖቤል ሽልማት ተሸላሚ በሚል ዘርፍ ሽልማቱ መሰጠት ተጀመረ፡፡ ይኸውም ሽልማት ዛሬ በዓለም ላይ ያሉ ሳይንቲስቶች፣ የሀገር መሪዎችና ልዕለ ሰብእናዎች ሁሉ የሚጓጉለት ሽልማት ለመሆን በቃ፡፡
እናም ኖቤል የሚለው ስም አሁን እርሱ በፈለገው መንገድ የሚታወስ ለመሆን በቃ፡፡ የሞት ነጋዴው በሚለው አጉል መጠሪያ ሳይሆን በዓለም ላይ ካሉ ሽልማቶች ሁሉ ላቅ ባለውና የግብረ ሰናይነት መገለጫ በሆነው ስሙ- የኖቤል ሽልማት፡፡ እፎይ፡፡

 የታዋቂው ማህበራዊ ድረገጽ ፌስቡክ የመጀመሪያው ሩብ አመት አጠቃላይ ገቢ ካለፈው አመት ተመሳሳይ ጊዜ በግማሽ ያህል መጨመሩን የዘገበው አልጀዚራ፤ ፌስቡክ ባለፉት ሶስት ወራት ብቻ 11.96 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቱን ገልጧል።
ተቀማጭነቱን በካሊፎርኒያ ያደረገው ፌስቡክ ምንም እንኳን በመረጃ ቅሌት ቀውስ ውስጥ ቢሆንም ገቢውና የተጠቃሚዎቹ ቁጥር መጨመሩንና የተጠቃሚዎቹ ቁጥር ባለፉት ሶስት ወራት በ13 በመቶ በማደግ፣ 2.2 ቢሊዮን መድረሱን ባለፈው ረቡዕ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
በተመሳሳይ ዜናም የደቡብ ኮርያው ሳምሰንግ ኤሌክትሮኒክስ ለተከታታይ አራት ሩብ አመታት ክብረወሰን ያስመዘገበበትን ትርፍ ማግኘቱ የተዘገበ ሲሆን ባለፉት ሶስት ወራት ብቻ 10.8 ቢሊዮን ዶላር ትርፍ እንዳገኘ ተነግሯል፡፡
ሳምሰንግ በሚሞሪ ቺፕስና በጋላክሲ ኤስ 9 ስማርት ፎን ምርቶቹ ላይ ያለው የገበያ ፍላጎት ማደጉ ከፍተኛውን ትርፍ እንዲያገኝ አስችሎታል መባሉን የዘገበው ቴክ ግሎባል፤ 73 በመቶ የሚሆነውን ትርፍ ያገኘው ከሚሞሪ ቺፕስ ሽያጭ መሆኑንም አመልክቷል፡፡

የሳኡዲ አረቢያ መንግስት ባለፉት 4 ወራት ጊዜ ውስጥ ብቻ 48 ሰዎችን አንገታቸውን በመቅላት መግደሉን አለማቀፉ የሰብዓዊ መብቶች ተሟጋች ተቋም ሂውማን ራይትስ ዎች ማስታወቁን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
ሳኡዲ አረቢያ አንገት በመቅላት ብዙ ሰዎችን በመግደል በቀዳሚነት ከሚጠቀሱ የአለማችን አገራት አንዷ ናት ያለው ተቋሙ፤ በአገሪቱ መንግስት በ2018 የፈረንጆች አመት የመጀመሪያዎቹ አራት ወራት፣ አንገታቸው ተቀልቶ ከተገደሉ ሰዎች መካከል አብዛኞቹ የከፋ ወንጀል ያልፈጸሙ መሆናቸው እርምጃውን ኢ-ፍትሃዊ  ያደርገዋል ብሏል፡፡
በአገሪቱ ባለፈው አመት ብቻ 150 ያህል ሰዎች ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ አንገታቸውን ተቀልተው መገደላቸውንና እ.ኤ.አ ከ2014 መጀመሪያ አንስቶ ባለው ጊዜ ውስጥ በ600 ያህል ሰዎች ላይ የአንገት መቀላት ፍርድ ተፈጻሚ መሆኑን ያስታወሰው ተቋሙ፤ ከ30 በመቶ በላይ የሚሆኑትም ቅጣቱ የተጣለባቸው ከአደንዛዥ ዕጾች ዝውውር ጋር በተያያዘ ተከስሰው መሆኑን አመልክቷል፡፡
የሳኡዲው ልኡል ሞሃመድ ቢን ሳልማን በቅርቡ ከታይም መጽሄት ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፤ አገሪቱ ከነፍስ ማጥፋት ወንጀል በስተቀር በሌሎች ክሶች የሚሰጡ የሞት ፍርዶችን ወደ እድሜ ልክ እስራት ዝቅ የማድረግ ሃሳብ እንዳለ መናገራቸውን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡

 በሰሜን ኮርያ እጅግ ግዙፉ እንደሆነ የሚነገርለትና ላለፉት 12  አመታት በአገልግሎት ላይ የቆየው የኒውክሌር ሙከራ ጣቢያ፤ አብዛኛው ክፍል በተደጋጋሚ ፍንዳታዎች በደረሰበት ጉዳት ሳቢያ መደርመሱና አገልግሎት የማይሰጥበት ደረጃ ላይ መድረሱ ተዘግቧል፡፡
ከአቅሙ በላይ በሆነ መልኩ ተደጋጋሚና በርካታ የኒውክሌር ሙከራ ፍንዳታዎችን ያስተናገደው ግዙፉ የሰሜን ኮርያ የሙከራ ጣቢያ፣ በከፋ ሁኔታ የተጎዳ ሲሆን ምናልባትም ቀጣይ ሙከራዎች ከተደረጉበት የኒውክሌር ጨረሮችን ሊያሾልክና አደጋ ሊያደርስ እንደሚችል አረጋግጠናል ሲሉ ቻይናውያን ተመራማሪዎች ባለፈው ረቡዕ ይፋ ባደረጉት የጥናት ሪፖርት ማስታወቃቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ፑንጌሪ በተባለው የአገሪቱ ሰሜን ምስራቃዊ ተራራማ ስፍራ ላይ የሚገኘው ግዙፉ የኒውክሌር ሙከራ ጣቢያ፣ ፕሬዚዳንት ኪም ጁንግ ኡን እ.ኤ.አ ከ2006 ወዲህ ያደረጓቸውን ስድስት የኒውክሌር ሙከራዎች በሙሉ ማስተናገዱን ያስታወሰው ዘገባው፤ የቻይና ሳይንስና ቴክኖሎጂ ዩኒቨርሲቲ ተመራማሪዎችም ጣቢያው በመደርመሱ ሳቢያ ከአሁን በኋላ አገልግሎት ላይሰጥ እንደሚችል አረጋግጠናል ማለታቸውን አመልክቷል፡፡
የኒውክሌር ሙከራ ጣቢያው በሃይለኛ ፍንዳታዎችና በተደጋጋሚ የመሬት መንቀጥቀጦች በመመታቱ ክፉኛ መጎዳቱን የዩኒቨርሲቲው ተመራማሪዎች በጥናት ማረጋገጣቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ይህንን ግዙፍ የኒውክሌር ሙከራ ጣቢያ እንደሚዘጉ፣ የኒውክሌር ጦር መሳሪያዎችንና የባላስቲክ ሚሳኤል ሙከራዎችን እንደሚያስቆሙ ከሰሞኑ ማስታወቃቸውንም አስታውሷል፡፡