Administrator

Administrator

በጦርነትና የግጭት ቀጠናዎች ውስጥ አደገኛና አስቸጋሪ ህይወት እየገፉ የሚገኙ የአለማችን ህጻናት ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ በማደግ ከ357 ሚሊዮን በላይ መድረሱን ሴቭ ዘ ችልድረን ከትናንት በስቲያ ባወጣው ዓለማቀፍ ሪፖርት ማስታወቁ ተዘግቧል፡፡
በጦርነትና በግጭት ቀጠናዎች ውስጥ ከሚገኙት የአለማችን ህጻናት፣ ግማሽ ያህሉ ወይም 165 ሚሊዮን የሚደርሱት ከፍተኛ ግጭት በሚከሰቱባቸው አካባቢዎች ውስጥ እንደሚኖሩ የጠቆመው ሪፖርቱ፤ የመካከለኛው ምስራቅ አገራት ህጻናት ለዚህ ችግር በመጋለጥ ረገድ ቀዳሚነቱን እንደሚይዙና አፍሪካውያን ህጻናት እንደሚከተሉ በመግለጽ፣ በመካከለኛው ምስራቅ አገራት ከሚኖሩ አምስት ህጻናት፣ ሁለቱ ግጭት ወይም ጦርነት በሚከናወንበት አካባቢ በ50 ኪሎ ሜትሮች ርቀት ውስጥ እንደሚኖሩ አመልክቷል፡፡
በርካታ ህጻናት በጦርነትና በግጭት ቀጠናዎች ውስጥ እንደሚገኙባቸውና ለህጻናት እጅግ አደገኛ ናቸው ተብለው በሪፖርቱ ከተጠቀሱት የአለማችን አገራት መካከል ሶሪያ ቀዳሚነቱን ስትይዝ፣ አፍጋኒስታንና ሶማሊያ በተከታታይነት ተቀምጠዋል፡፡
በህጻናት ላይ የሚፈጸሙ ግድያዎችና የማቁሰል ጥቃቶች ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተበራከቱ እንደመጡ የዘገበው ዘ ኢንዴፔንደንት፤ የተባበሩት መንግስታት በማስረጃ አስደግፎ የሚመዘግባቸው መሰል ጥቃቶች ቁጥር ባለፉት ሰባት አመታት ውስጥ በ3 እጥፍ ማደጉንም አስታውሷል፡፡
በግጭቶችና በጦርነቶች ሳቢያ ከመኖሪያ አካባቢያቸው እየተፈናቀሉ ለተለያዩ ስቃዮችና እንግልቶች የሚዳረጉ የአለማችን ህጻናት ቁጥር እያሻቀበ እንደሚገኝ የጠቆመው ዘገባው፤ ከ65 ሚሊዮን በላይ የዓለማችን ህጻናት ምንም አይነት ቋሚ የመኖሪያ ቤት እንደሌላቸው አመልክቷል፡፡

   የአገሪቱ መሪ፤ ሚኒስትሮች ከባልደረቦቻቸው ጋር ፍቅር እንዳይጀምሩ አስጠንቅቀዋል

   ከሰሞኑ ይፋ ከተደረገባቸው የወሲብ ቅሌት መረጃ ጋር በተያያዘ፣ አገራዊ የመነጋገሪያ አጀንዳ የሆኑት የአውስትራሊያ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ባርናቢ ጆይስ፤ የፓርቲ መሪነትና የሚኒስትርነት ስልጣናቸውን ይለቃሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ የተዘገበ ሲሆን የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ማልኮም ተርንቡልም፤ ሚኒስትሮች ተመሳሳይ ድርጊት ፈጽመው ከተገኙ ከፍተኛ ቅጣት እንደሚጠብቃቸው ማስጠንቀቃቸው ተዘግቧል፡፡
የአገሪቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ባርናቢ ጆይስ፣ በቅርቡ የ24 አመት ትዳራቸውን በማፍረስ፣ የስራ ባልደረባቸው ከሆነች አንዲት ሴት ጋር በፈጠሩት የድብቅ የፍቅር ግንኙነት፣ ሴትየዋን ማስረገዛቸውን የሚያጋልጥ የወሲብ ቅሌት መረጃ ከሰሞኑ ይፋ መደረጉንና ጉዳዩ ትልቅ አገራዊ አጀንዳ መሆኑን የዘገበው ዘ ቴሌግራፍ፤ ይህን ተከትሎም የአገሪቱ ፓርላማ ከትናንት በስቲያ ባደረገው ስብሰባ፣ ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ ተከስተዋል ያላቸውን ሌሎች ተጨማሪ የሙስና ድርጊቶችን በመመርመር፣ ሚኒስትሩ ከስነምግባር ውጭ የሆነና ክብርን የሚያጎድፍ ጸያፍ ተግባር በመፈጸማቸው፣ በፈቃዳቸው ስራቸውን እንዲለቅቁ ወይም እንዲባረሩ የሚጠይቀውን የውሳኔ ሃሳብ በአብላጫ ድምጽ ማጽደቁን አመልክቷል፡፡
“በምክትል ሚኒስትሩ ድርጊት እጅግ አዝኛለሁ፤ ይሄም ሆኖ ግን ከአሁን በኋላ ባለትዳርም ሆነ ወንደላጤ ማንኛውም ሚኒስትር፣ የስራ ባልደረባው ከሆነች ሴት ጋር በፍጹም የፍቅር ግንኙነት መመስረትም ሆነ አንሶላ መጋፈፍ አይችልም” ሲሉ በይፋ ያስጠነቀቁት የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ማልኮም ተርንቡል፤ ድርጊቱ በቀጣይም እንደ አንድ ከባድ የስልጣን ብልግና ወይም የሙስና ወንጀል ተወስዶ እንደሚያስቀጣም አስታውቀዋል፡፡
ምንም እንኳን በአገሪቱ የሚኒስትሮች ስነምግባር ደንብ ውስጥ ከስራ ባልደረባቸው ጋር የፍቅር ግንኙነት በሚጀምሩም ሆነ በሚያማግጡ ሚኒስትሮች ዙሪያ የሚያትት ምንም አይነት አንቀጽ ባይኖርም፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ግን ከአሁን በኋላ መሰል ድርጊት የፈጸመ ሚኒስትር፤ ከፍተኛ ቅጣት እንደሚጠብቀው በማስጠንቀቅ፣ ድርጊቱን በግልጽ የሚያወግዙና ተገቢ ቅጣት የሚጥሉ ህጎችና መመሪያዎች በቀጣይ ወጥተው፣ ተግባራዊ እንደሚደረጉም ተናግረዋል፡፡
24 አመታትን በትዳር አብረዋት ከዘለቋት ባለቤታቸው፣ አራት ሴት ልጆችን ያፈሩት የ50 አመቱ የአገሪቱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር፤ የስራ ባልደረባቸው ከሆነች ሌላ ሴት ጋር በድብቅ እፍ ክንፍ ማለታቸውና ማስረገዛቸው ባለፈው ሳምንት ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ ጉዳዩ የአገሪቱን ፖለቲካ ፓርቲዎችም ጨምሮ በርካታ ዜጎችን እያነጋገረ እንደሚገኝም ዘገባው አስታውሷል፡፡  

 ለወራት በጉጉት ሲጠበቅ የነበረውና ብዙ ሲወራለት የቆየው አዲሱ የሳምሰንግ ስማርት ፎን ምርት ጋላክሲ ኤስ9 በመጪው ሳምንት በባርሴሎና በሚካሄደው አለማቀፍ የሞባይል ትርዒት ላይ በይፋ ተመርቆ በገበያ ላይ ይውላል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
አዲሱ ጋላክሲ ኤስ9 የመሸጫ ዋጋው 739 ፓውንድ ያህል እንደሚሆን የዘገበው ቴክራዳር ድረገጽ፣ ሞባይሉ 6 ጊጋ ባይት ራም እንዳለውና 64 ጊጋ ባይት መረጃ መያዝ እንደሚችል እንዲሁም ባለ 12 ሜጋፒክስል ሁለት ካሜራዎች እንደተገጠሙለት አመልክቷል፡፡
ውሃንና ቆሻሻን የመከላከል አቅሙ እጅግ ከፍተኛ እንደሆነ የተነገረለት ኤስ9 ያለ ገመድ ቻርጅ መደረግ የሚችል እንደሆነም ዘገባው አስረድቷል፡፡
ኩባንያው ሞባይሉ በይፋ በተመረቀ በቀናት እድሜ ውስጥ ከደንበኞች የግዢ ትዕዛዝ መቀበል እንደሚጀምርና በቀጣዩ ወር አጋማሽ ላይ ምረቱን ለገዢዎች የማድረስ ስራ ይጀምራል ተብሎ እንደሚጠበቅም ዘገባው አመልክቷል፡፡

  በአፍጋኒስታን ባለፈው የፈረንጆች አመት 2017 በተካሄዱ ብጥብጦች፣ ከ10 ሺህ በላይ በሚሆኑ የአገሪቱ ንጹሃን ዜጎች ላይ የግድያ ወይም የመቁሰል አደጋ መድረሱን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከትናንት በስቲያ ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
በአፍጋኒስታን በአመቱ 3 ሺህ 438 ንጹሃን ዜጎች መገደላቸውን የጠቆመው ተመድ፤7 ሺህ 15 ያህል የሚሆኑትም ለመቁሰል አደጋ መዳረጋቸውን ያመለከተ ሲሆን በዜጎች ላይ ከተፈጸሙት ግድያዎች ወይም የማቁሰል ድርጊቶች መካከል ከስድሳ በመቶ በላይ የሚሆኑት የተፈጸሙት በጸረ-መንግስት ሃይሎች በተደረጉ የቦንብ ጥቃቶች መሆኑንም አመልክቷል፡፡ በአመቱ በአፍጋኒስታን ንጹሃን ዜጎች ላይ ከተፈጸሙት ጥቃቶች መካከል ታሊባን 42 በመቶ፣ አይሲስ 10 በመቶ ድርሻ እንደነበራቸው ያስታወሰው መግለጫው፤ በአሜሪካ የአየር ድብደባዎች ለሞትና ለመቁሰል አደጋ የሚጋለጡ ዜጎች ቁጥርም እያደገ ነው ብሏል፡፡
በ2017 የፈረንጆች አመት አፍጋኒስታናውያን ህጻናትና ሴቶች በከፍተኛ ሁኔታ የጥቃት ሰለባ መሆናቸውን የጠቆመው መግለጫው፤በአመቱ 359 ሴቶች መገደላቸውንና 865 ሴቶች ደግሞ መቁሰላቸውን፤ 861 ህጻናት መገደላቸውንና 2 ሺህ 318 መቁሰላቸውን አስታውቋል፡፡

የደን ሽፋንን በተፋጠነ የዛፍ ተከላ በማሳደግ፣ የአየር ብክለትን ለመዋጋት ቆርጦ የተነሳው የቻይና መንግስት፤ ከስራ ገበታቸው ተሰናብተው የነበሩ 60 ሺህ ወታደሮችን መልሶ በመቅጠር በችግኝ ተከላ ስራ ላይ ሊያሰማራ ማቀዱን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
ከዚህ በፊት በመደበኛ ውትድርና ሙያ ላይ ያገለግሉ የነበሩና ከስራ ገበታቸው የተሰናበቱት እነዚህ ወታደሮች፤ የቻይና መንግስት በአገሪቱ የተለያዩ ግዛቶች ሊያከናውናቸው ባቀዳቸው ሰፋፊ የደን ልማት ፕሮጀክቶች ውስጥ በችግን ተከላ ስራ ላይ እንደሚሰማሩ የጠቆመው ዘገባው፤በተለይም የኢንዱስትሪ ጭሶችን በብዛት በማውጣት ከፍተኛ የአየር ብክለትን በሚያስከትሉ አካባቢዎች ብዛት ያላቸው ዛፎችን ለመትከል መታቀዱን አመልክቷል።
ቻይና በዘንድሮው የፈረንጆች አመት ብቻ 84 ስኩየር ኪሎ ሜትር በሚሸፍን ቦታ ላይ በርካታ ዛፎችን የመትከል እቅድ ይዛ በስፋት እየተንቀሳቀሰች እንደምትገኝ የጠቆመው ዘገባው፤ በደን ይሸፈናል ተብሎ የታቀደው ቦታ ስፋት ከአየርላንድ አጠቃላይ የቆዳ ስፋት ጋር ተመጣጣኝ መሆኑን አስረድቷል።
 አገሪቱ የደን ሽፋኗን አሁን ከሚገኝበት 21 በመቶ፣ በመጪዎቹ ሁለት አመታት ጊዜ ውስጥ ወደ 23 በመቶ ከፍ ለማድረግ ማቀዷንና የደን ሽፋኑ እ.ኤ.አ እስከ 2035 ድረስ 26 በመቶ ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅም አመልክቷል፡፡

  በጀርመኑ የቴክኒክ ተራድኦ ድርጅት (ጂአይዜድ) እና ሲኤንኤፍኤ በተሰኙ ዓለም አቀፍ ተቋማት እገዛ በአርሲ ዞን ሁሩታና ሳጉሬ ወረዳዎች፣ከ60 ሺ ዩሮ በላይ በሆነ ወጪ፣ ዘመናዊ የግብርና ግብአቶች ማስፋፊያ ማዕከላት ተገነቡ፡፡
ሰሞኑን የተመረቁት እነዚህ የግብርና ማዕከላት፣ ዘመናዊና ጥራት ያላቸው የሰብል ዘሮችን፣ የአረም መከላከያ መድሐኒቶችና የእንስሳት ህክምና ምርቶችን በሰለጠኑ ሠራተኞችና በተመጣጣኝ ዋጋ፣ ለአርሶ አደሮች ያቀርባሉ ተብሏል፡፡
ማዕከላቱን የተራድኦ ድርጅቶችና የአካባቢው ሥራ ፈጣሪ ወጣቶች በእኩል መዋጮ ያስገነቧቸው ሲሆን ከአገልግሎት ሽያጭ የሚሰበሰበው ገቢም ለወጣቶቹ እንደሚሆን ተነግሯል፡፡ አንድ ማዕከል ለ25 ሺህ ያህል አርሶ አደሮች እንደሚያገለግል የተጠቆመ ሲሆን ማዕከላቱ ግብአቶችን ከማቅረብ ጐን ለጐን፣ለአርሶ አደሮች የምክርና ስልጠና አገልግሎት እንደሚሰጡ በምረቃ ሥነ-ሥርዓቱ ላይ ተገልጧል፡፡    

 የ“ፊታውራሪ” የሙዚቃ ክሊፕ የሽፋን ፎቶ በ400 ሺህ ብር ተሽጧል

    በቅርቡ በገበያ ላይ የዋለው “እስኪ ልየው” የተሰኘው የድምጻዊት ሄለን በርሄ የሙዚቃ አልበም ባለፈው ሳምንት አርብ ምሽት በማማስ ኪችን በተከናወነ ልዩ ፕሮግራም የተመረቀ ሲሆን፣ በእለቱ በይፋ ተመርቆ ለእይታ የበቃውና በአልበሙ ውስጥ ከተካተቱት 14 ሙዚቃዎች አንዱ የሆነው የ“ፊታውራሪ” የሙዚቃ ክሊፕ ፎቶ ግራፍ ለጨረታ ቀርቦ በ400 ሺህ ብር ተሽጧል፡፡
ኡቡንቱ አርት ማኔጅመንት እና ንጉስ ኢንተርቴንመንት በጋራ ያዘጋጁትና የካቲት 2 ቀን 2010 ዓ.ም ምሽት ወሎ ሰፈር በሚገኘው ማማስ ኪችን በተከናወነው የአልበሙ የምረቃ ፕሮግራም ላይ በርካታ የኪነጥበብ ባለሙያዎች፣ ታዋቂ ግለሰቦች፣ የድምጻዊቷ አድናቂዎችና ተጋባዥ እንግዶች የታደሙ ሲሆን፣ ድምጻዊቷ አዳዲስና ቆየት ያሉ ተወዳጅ ሙዚቃዎቿን በአስገራሚ ብቃት በማቀንቀን ታዳሚውን ስታዝናና አምሽታለች፡፡
ድምጻዊት ሄለን በርሄ፣ በአዲሱ አልበም ውስጥ የተካተተውን የኔ ቆንጆ የተሰኘ ተወዳጅ ዜማ ያበረከቱላትን ታዋቂውን የዜማ ደራሲና የማንዶሊን ተጫዋች አቶ አየለ ማሞን ጨምሮ ለአልበሙም ሆነ ለሙዚቃ ክሊፑ ስኬታማነት አስተዋጽኦ ያበረከቱ ባለሙያዎችን በተደጋጋሚ ስታመሰግን አምሽታለች፡፡
ምነው ሸዋ ኢንተርቴንመንት ፕሮዲዩስ ያደረገውና 350 ሺህ ብር ያህል ወጪ እንደተደረገበት የተነገረለት እንዲሁም ከ50 በላይ ተዋንያን የተሳተፉበት “ፊታውራሪ” የሙዚቃ ክሊፕ በምሽቱ ለመጀመሪያ ጊዜ በይፋ ለእይታ በበቃበት ቅጽበት፣ በዩቲዩብ ድረገጽ የተለቀቀ ሲሆን፣ የፕሮግራሙ ታዳሚያን አድናቆታቸውን በሚገርም ሁኔታ ሲገልጹ ተስተውለዋል፤ በዩቲዩብም ብዙ ተመልካቾች እያዩት እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ።
የ“ፊታውራሪ” የሙዚቃ ክሊፕ የሽፋን ፎቶ ግራፍ በምሽቱ ለጨረታ የቀረበ ሲሆን፣ የድምጻዊቷ አድናቂዎችና በዝግጅቱ ላይ የታደሙ የሙዚቃ አፍቃሪያን ፎቶግራፉን በእጃቸው ለማስገባት ረጅም ፉክክር ካደረጉ በኋላ፣ በስተመጨረሻም 400 ሺህ ብር ያቀረቡት የማማስ ኪችን ባለቤት ጨረታውን አሸንፈዋል፡፡
በአልበሙ የምረቃ ስነስርዓት ላይ ጸደኒያ ገብረ ማርቆስ፣ ጌትሽ ማሞ፣ ዳግማዊት ጸሃዬና አስገኘው አሽኮ (ዴንዳሾ)ን ጨምሮ ሌሎች ተጋባዥ ድምጻውያን የሙዚቃ ስራዎቻቸውን ለታዳሚያን አቅርበዋል፡፡

 “የኢትዮጵያ የባህል ሙዚቃ ሕያው መሆን አለበት”

     የክራርና የዋሽንት መምህርና የኦርኬስትራ ኢትዮጵያ መስራች የነበሩት አርቲስት መላኩ ገላው በሰማንያ ዓመት ዕድሜያቸው አሜሪካ ውስጥ አርሊንግተን - ቨርጂንያ በሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው አርፈዋል።
አርቲስት መላኩ ገላው በጣልያን የወረራ ዘመን መጋቢት 12 ቀን 1929ዓ.ም ከአባታቸው ከአቶ ገላው ተክሌና ከእናታቸው ከእማሆይ ትኩነሽ ተሰማ በላስታ ላሊበላ ተወለዱ፡፡ ከልጅነታቸው ጀምሮ የተፀነሰው የሙዚቃ መሳሪያ የመጫወት ፍቅር ከልጅነት ባለፈ በ1956 ዓ.ም የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዩኒቨርሲቲና የኦርኬስትራ ኢትዮጵያን በመቀላቀል በክራርና በዋሽንት ተጫዋችነት፣ ከዚያም ከ1959 ዓ.ም ጀምሮ በያሬድ የሙዚቃ ትምህርት ቤት በሁለቱም ባሕላዊ የሙዚቃ መሣሪያዎች በመምህርነት ከ28 ዓመታት በላይ አገልግለዋል።
በተለይ በኦርኬስትራ ኢትዮጵያ ከተስፋዬ ለማ፤ ከአሜሪካዊው መሲንቆ ተጫዋች ቻርለስ ሳተን እና ከአርቲስት ጌታ መሳይ አበበ ጋር በመሆን የባህል አምባሰደርነታቸውን በዓለም ለማስመስከር ችለዋል፡፡ በያሬድ ሙዚቃ ት/ቤትም የባህል የሙዚቃ መሳሪያ መጫወት በማይበረታታበት ጊዜ የራሳቸውን የማስተማር ልምድ በመጠቀም ትምህርቱን መስጠት እንደጀመሩና መሰረት እንደጣሉ ተማሪዎቻቸው ይመሰክራሉ፡፡ ታላላቅ የሚባሉ የሙዚቃ ባለሙያዎችን እንደ ጥላሁን ገሠሠ፤ ብዙነሽ በቀለ፤ ሂሩት በቀለንና ሌሎች አንጋፋ ድምፃውያንን በዋሽንትና በክራር በማጀብ የሙያ ድርሻቸውን የተወጡ ባለሙያ ነበሩ፡፡ ለአርቲስት ጌታ መሳይ አበበም “የሽምብራው ጥርጥር” የሚለውን የሙዚቃ ድርሰት በመስጠትም ይታወቃሉ፡፡ የእጅጋየሁ ሽባባውን የአገው ባህላዊ ሙዚቃንም በልዩ መልክ በማጀብ የዋሽንት ችሎታቸውንም አስመስክረዋል፡፡
ኑሯቸውን በአሜሪካ ካደረጉበት ጊዜ አንስቶ በግላቸው በርካቶችን ክራር በማስተማር የቆዩ ሲሆን በአቶ ተስፋዬ ለማ በተቋቋመው ሙዚየም ውስጥ የባህል ሙዚቃ መሳሪያዎችን በማስተዋወቅ ከፍተኛ አስተዋጽዖ ከማበርከታቸውም በተጨማሪ ከቀድሞ የሙዚቃ አጋሮቻቸው ከተስፋዬ ለማ፤ ቻርለስ ሳተን እና ጌታ መሳይ አበበ ጋር በመሆን “ዞሮ ገጠም” የሚል ሙዚቃን በመስራት ለባህል ሙዚቃ ህዳሴ የበኩላቸውን ተወጥተዋል፡፡
እ.ኤ.አ በ2015 ለባህል የሙዚቃ መሳሪያ ዕድገት ላበረከቱት ከፍተኛ አስተዋጽዖ የፊደል ዕድሜ ዘመን ተሸላሚ ክብርን አግኝተዋል፡፡ “የኢትዮጵያ የባህል ሙዚቃ ሕያው መሆን አለበት” የሚለውን ጽኑ አቋማቸውን ህይወታቸው እስካለፈችበት ጊዜ ድረስ ሌሎችን በማስተማርና በተለይም ሙያውን ለልጆቻቸው በማውረስ ታላቅ ታሪክ የሰሩ የባህል ሙዚቃ አምባሳደር ሆነው አልፈዋል፡፡
አርቲስት መላኩ ገላው ባለትዳርና የ7 ልጆች አባት ሲሆኑ 12 የልጅ ልጆችም አይተዋል፡፡ ባደረባቸው ህመም በህክምና ሲረዱ ቆይተው ባለፈው ቅዳሜ የካቲት 3 ቀን 2010 ዓ.ም በአርሊንግተን ቨርጂኒያ ቤታቸው በ80 ዓመት ዕድሜያቸው ሕይወታቸው አልፏል፡፡ አስክሬናቸውም በመጪው እሁድ ከአሜሪካ ወደ ኢትዮጵያ የሚሸኝ ሲሆን ቀብራቸውም የፊታችን ሰኞ የካቲት 12 ቀን 2010ዓ.ም በፈረንሳይ ደብረ ፀሀይ ቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተክርስቲያን ከቀኑ በ9ሰዓት እንደሚፈጸም ከቤተሰቦቻቸው የተገኘ መረጃ ያስረዳል፡፡

  “አዝማሪና ውሃ ሙላት” በተሰኘው የደራሲ ከበደ ሚካኤል ግጥም ውስጥ የምናቃቸው ዝነኛ መስመሮች ለዛሬ የመረጥናቸው ናቸው፡፡

        አዝማሪና ውሃ ሙላት
        አንድ ቀን አንድ ሰው ሲሄድ በመንገድ
        የወንዝ ውሃ ሞልቶ
                ደፍርሶ ሲወርድ
        እዚያው እወንዙ ዳር
                እያለ ጐርደድ
        አንድ አዝማሪ አገኘ
                ሲዘፍን አምርሮ
        በሚያሳዝን ዜማ
            ድምፁን አሳምሮ፡፡
        “ምነው አቶ አዝማሪ
        ምን ትሠራለህ?”
        ብሎ ቢጠይቀው፤
        “ምን ሁን ትላለህ፣
        አላሻግር ብሎኝ
        የውሃ ሙላት
        እያሞጋገስኩት
        በግጥም ብዛት
        ሆዱን አራርቶልኝ ቢያሻግረኝ ብዬ”
        “አሁን ገና ሞኝ ሆንክ ምነዋ ሰውዬ
        ነገሩስ ባልከፋ
        ውሃውን ማወደስ
        ግን እንደዚህ ፈጥኖ
        በችኮላ ሲፈስ
        ምን ይሰማኝ ብለህ
        ትደክማለህ ከቶ
        ድምፁን እያሽካካ መገስገሱን ትቶ
        እስኪ ተመልከተው ይህ አወራረድ
        ያልሰማው ሲመጣ የሰማው ሲሄድ”

        ተግሳጽም ለፀባይ ካልሆነው አራሚ
        መናገር ከንቱ ነው ካልተገኘ ሰሚ!
*   *   *
በተደጋጋሚ ሀገራችን ባለፈችበት የለውጥ ሂደት ውስጥ የተገነዘብነው ዋና ነገር ገዢው “ያቀድኩትን ልተግብርበት እረፉ”፤ ሲል፤ ተገዢው “ኧረ ይሄ ነገር አልተሟላልኝም እያለ ሲያማርር፤ በመሀል ውዱ ጊዜ ማለፉ ነው፡፡ የጠፋው ጊዜ ከሰነበትን በኋላ ተመልሶ መፀፀቻችን ይሆናል፡፡ የተወሳሰበው ችግር መፍትሄ ማግኘት ቀርቶ የባሰ የተወሳሰበ ሆኖ ይገኛል፡፡ የባሰ ምስቅልቅሉ ይወጣል፡፡ መፍትሄ መስጠት ያለባቸው አካላት የውስጥም የውጪም ግፊትና ውጥረት ስላለባቸው፤ ሌሎች ችግሮችን ማስተናገድ አልሆነላቸውም። ቢወተወቱ አያዳምጡም፡፡ “አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት አይነቃም” የሚለው ተረት የበለጠ ይገልፀዋል፡፡ ለማደግም ሆነ ለውጥ ለማምጣት የሚያስችለው መደማመጥ ነው። ሁሉንም ነገር ዐይኔን ግንባር ያድርገው ብለን አንችለውም፡፡ ካለመደማመጥ በተጨማሪ የሚደረገውንም ሆነ የተደረገውን አላውቅም፤ ማለትና መስማትም ማየትም እምቢ ካልን፣ ጉዟችን የዕውር የድንብር ይሆናል፡፡
ጊዜ እየረፈደ ከመጣ በኋላ ሁኔታውን ለመቀልበስ ብንሞክር ፍሬ-አልባ ሙከራ ይሆናል። ዛሬም ዐይናችንን ከፍተን ቆም ብለን እናስብ፡፡ ውጥረት ውስጥ ከመግባታችን በፊት የውጥረቱን መፈጠሪያ ቧንቧዎች እንዝጋ፡፡ አሁንም ደግመን ደጋግመን እናዳምጥ። ሀገራችን ከእንግዲህ ተጨማሪ ችግር የምትሸከምበት ጫንቃ የላትም፡፡ ካልተጠነቀቅን ሀገርም እንደ ሰው ተሰባሪ ናት፡፡ የ1966ን አብዮት አንርሳ፡፡ ገዢዎች መግዛት ሲያቅታቸው፣ ተገዢዎች አንገዛም ሲሉ፣ ሀገር ለአብዮት የበሰለ ሁኔታ ላይ እንደደረሰች አንዘንጋ፡፡ ሲመሽ ጉሮሮ ለጉሮሮ ከመተናነቅ፣ ፊት ለፊት ተገናኝቶ መነጋገር ነው፤ ወደ መፍትሄው የሚያስጠጋን። እስከ መቼ “ዴሞክራሲያችን ለጋ ስለሆነ ነው” እያልን ምክንያት እንሰማለን? እስከ መቼ “የመልካም አስተዳደር ችግር ነው” እያልን እንዘልቀዋለን? እስከ መቼስ “የፍትህ ሰጪ አካላት የአፈፃፀም ችግር አለ” እያልን እንጓዛለን? የድህነት ችግርስ እስከመቼ ነው ቁልፍ ነው እየተባለ የምንቀጥለው? ከሃያ በላይ ዓመታት ተጉዘን፣ ምንም ለውጥ አለማምጣታችን፣ የሚያሳፍረን ጊዜ አይመጣምን? ዛሬም መብራት ይጠፋል፡፡ ዛሬም ውሃ ይጠፋል፡፡ ዛሬም ኔትዎርክ ይቸግራል፡፡ ዛሬም ኑሮ አዘቅት ውስጥ እየከተተን ነው፡፡ እነዚህ የብሶትና የምሬት ምንጮች እስከ መቼ እንደተጫኑብን ይኖራሉ? እናስብ! ምንጣፉ ከእግራችን ስር ተስቦ እስኪወሰድ አንጠብቅ! “ጉልቻ ቢለዋወጥ ወጥ አያጣፍጥም” ከአርባ ዓመት በኋላ መድገም አሳፋሪ ይሆናል፡፡ “ፋታ ስጡኝ”  ለማለትም ጊዜ የለም! የነካነው ሁሉ ወርቅ ይሆናል ብለን እንደ ሚዳስ አስማት (Midas Touch) የምናስብበት ጊዜ አልፏል፡፡
“እስቲ ተመልከተው ይህ አወራረድ
ያልሰማው ሲመጣ የሰማው ሲሄድ”
የሚለውን ዛሬም ማስተዋል ይበጃል፡፡ መልካም ጊዜ ይመጣ ዘንድ ሁላችንም እንመኛለን!   

የአገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ አለመሻሻል
የአገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ መሻሻል ከማሳየት ይልቅ የበለጠ እየተበላሸ መጥቷል፡፡ የዚህ ምክንያት ደግሞ ለረጅም ጊዜ ችግሮች ተገቢውንና ቀጣይነት ያለው መልስ ያለማግኘታቸው ያመጣው ድምር ውጤት ነው፡፡ ማህበረሰቡ በተለያየ መንገድ ፖለቲካዊ ጥያቄዎች ነበሩት፡፡ ኢኮኖሚያዊ ጥያቄዎችም አሉት፡፡ ለነዚህ ጥያቄዎች ደግሞ አፋጣኝ መልስ ያለማግኘት፣ ትኩረት ማጣት፣ በቂ ክትትል አለመኖር አንዳንድ ጊዜ ደግሞ የሚነሱ ጥያቄዎች እርባና ቢስ እንደሆኑ ተደርጐ መቆጠሩ ማህበረሰቡ መጨረሻ ላይ በራሱ መንገድ መፍትሄ እንዲፈልግ ነው ያስገደደው፡፡ የመድብለ ፓርቲ ፖለቲካ መገለጫው፣ ማህበረሰቡ በዚህ መልኩ የራሱን ጥያቄ አንግቦ ጐዳና ወጥቶ፣ መንግሥትን በቀጥታ መታገል ሳይገባው፣ በወኪሎቹ በኩል የሚታገልበትና ጥያቄዎቹን የሚያቀርብበት መንገድ ነው፡፡ ይሄ አሁን በኢትዮጵያ እንዳይኖር ተደርጓል፡፡ በዚህ ምክንያት ተቃውሞ መሪ የለውም፡፡ የተደራጀ ጥያቄ የለውም፡፡ እንዲህ በሚሆንበት ጊዜ ደግሞ ምላሽ ለመስጠትም ሆነ ለመቆጣጠር የተወሳሰበና አስቸጋሪ ነው የሚሆነው፡፡ እያየን ያለነውም ይሄንን ነው፡፡
በሌላ በኩል መንግሥት ለችግሮቹ ምላሽ ለመስጠት እየሞከረ ያለው ጊዜያዊ መፍትሄዎችን ብቻ በማስቀመጥ ነው፡፡ አግባብ ያለው መልስ እየሰጠ አይደለም፡፡ ስር ነቀል ለውጥ አካሂዶ ጥያቄዎቹን በዘላቂነት የመመለስ ስራ አይደለም እየተከናወነ ያለው፡፡ ዝም ብሎ እግር በእግር እየተከታተለ ነው፣ ትንንሽ መልሶችን  ለመስጠት እየሞከረ ያለው፡፡ ይሄ ህዝቡን አያረካም፡፡ ማህበረሰቡ ደግሞ አሁን ተጨባጭና ቀጥተኛ ምላሽ ነው የፈለገው፡፡ በአሁኑ ወቅት ህዝቡ ዛሬውኑ መልሱን አምጣ ነው እያለ ያለው፡፡ ከዚህ በፊት ማህበረሰቡ ላሉት የፖለቲካ ጥያቄዎች ትእግስት ነበረው፤ ምክንያቱም ሀሳብን በነፃነት መግለፅ የመደራጀት፣ ሰላማዊ ሰልፍ የመውጣት፣ የፕሬስ ነፃነት ጉዳይ ለአብዛኛው ህዝብ የልሂቃኑ ጥያቄ መስሎ ነበር የሚታየው፡፡ በዚህ ምክንያት ማህበረሰቡ ህይወቱን እስከ መሰዋት ሊሄድ አይችልም ነበር፡፡ አሁን ግን ነገሮች ተቀይረዋል። ሲከማቹ የቆዩት ችግሮችና ጥያቄዎች፣ አግባብ ያለው አፈታት ባለማግኘታቸው፣ ማህበረሰቡ ታግሶ ታግሶ፣ የራሱን አማራጭ ሊወስድ ችሏል፡፡ የተጠራቀሙ ጭቆናዎችና ፍረጃዎች ናቸው ለዚህ ያበቁት፡፡

ብሄር ተኮር ጥቃቶች   
ከብሄር ጉዳይ ጋር ተያይዞ የሚነሱት ውዝግቦች ለረጅም ጊዜያት ህብረተሰቡ ውስጥ ሲብላሉ የነበሩ ናቸው፡፡ አሁን ከመብላላት አልፈው ዋነኛ ችግር ሆነዋል፡፡ እውነቱን ለመናገር በዚች አገር፣ አንዱ ብሄር አንዱን እንዲያጠቃው የሚፈቅድ ማህበረሰብ ፈፅሞ የለም፡፡ በሌላ በኩል፣ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘበት ጊዜ ጀምሮ ይሄ የብሄር ጉዳይ ያልተነሳበትና ያለመግባባት መንስኤ ያልሆነበት ጊዜ የለም፡፡ በወቅቱ አግባብ ያለው ውይይት ተደርጐ መልስ ቢሰጠው ኖሮ፣ ዛሬ ተመልሶ አይከሰትም  ነበር፡፡ ሰዎች ከቦታ ቦታ ተንቀሳቅሰው የመኖር መብታቸው፣ አስቀድሞ መተግበር ነበረበት፡፡ በወቅቱ እነዚህ ነገሮች ባለመታከማቸው ዛሬ ላይ ፈጠው ወጥተዋል፡፡ ከዚህ ችግር  ለመውጣት አሁንም ውይይት ያስፈልጋል፡፡ ሁነኛ የግጭት አፈታት ስልት መነደፍ አለበት፡፡ እርግጥ ነው ከህዝባችን ታሪክ ስንነሳ፣ የብሄር ግጭት ተፈጥሮ አያውቅም፡፡ ግጭቶች ሲኖሩም፣ ከድንበርና ከግጦሽ መሬት የባለቤትነት ጥያቄ አያልፍም፡፡ አሁን ግን ትንሽ ነገሮች የተቀየሩ ይመስላል፡፡
 ባለፉት 27 ዓመታትም አንዱ አንዱን ሲጨቁን፣ ሲበድል፣ ሲበዘብዝ እንደነበር ነው ሲተረክ የተኖረው። አንዱ አንዱን በጥርጣሬና በጥላቻ እንዲያይ ተደርጐ ነው፣ የማህበረሰቡ ቀደምት ግንኙነቶች ሲተረኩ የኖሩት፡፡ ታዲያ ከዚህ ተረክ ምን በጐ ፍሬ ነው የሚጠበቀው፡፡ ማህበረሰቡ “እገሌ ሀብትህን ሲበዘብዝ ነበር” ሲባል ነው የኖረው። በዚህ የተነሳ  አንዱ በሌላው የአገሪቱ ክፍል ሰርቶ ሲኖር፣ እንደ ሀብት በዝባዥ ነው የሚታየው። ንብረቴን ዘረፉኝ ነው፤ ብሶቱ፡፡ እንግዲህ ካለፉት ዓመታት ተረኮች ያተረፍነው ይሄንን ነው፡፡ ችግሩ የበለጠ አድማሱን ሳያሰፋና የአገሪቱን ህልውና ሳይፈታተን በጊዜ እልባት ማግኘት አለበት፡፡

የፖለቲከኞች መፈታትና ፋይዳው
እነዚህ ሰዎች ሀሳባቸውን በነፃነት በመግለፃቸውና በፖለቲካ አመለካከታቸው ምክንያት እስር ቤት የገቡ ናቸው፡፡ የእነዚህ ሰዎች መፈታት በእርግጥም ህዝቡ የበለጠ ትግሉን አጠናክሮ እንዲቀጥል ይረዳዋል፡፡ መንግሥት እነዚህን ሰዎች በመፍታቱ ብቻ ለህዝቡ ጥያቄ በቂ መልስ ሰጥቻለሁ ብሎ ካሰበ በእጅጉ ተሳስቷል፡፡ ምክንያቱም የእስረኞች መፈታት ጉዳይ ከህዝቡ ጥያቄዎች አንዱ እንጂ ዋነኛ ግብና ዓላማ አይደለም፡፡ እርግጥ ነው ማህበረሰቡ እንዲፈቱ ታግሎላቸዋል፡፡ ስለዚህ መፈታታቸው እንደ አንድ ድል ነው የሚቆጠረው፤ ግን የጥያቄዎች ሁሉ መልስ አይሆንም፡፡

የህግ የበላይነትና ሰብአዊ መብት
የህግ የበላይነትን ማስከበር የመንግስት ዋነኛ ሃላፊነት ነው፡፡ ጥያቄው የህግ የበላይነትን ማስከበር ሲባል በምን መንገድ የሚለው ነው፡፡ የህግ የበላይነትን በሌላ የህግ ጥሰትና ጥፋት ለማስከበር ጥረት የሚደረግ ከሆነ ውጤት አያመጣም፡፡ መንግሥት ደግሞ የህግ የበላይነትን ለማስከበር ሲጥር፣ የማህበረሰቡን የህግ ንቃተ ህሊና ማገናዘብ አለበት፡፡ መፍትሄው የህይወት ማጥፋት ሳይሆን አጥፊዎችን በህግ ጥላ ስር ማዋል ነው፡፡ የህግ የበላይነትን ለማስከበር የሚወሰደው እርምጃ የበለጠ ጥፋት የሚያስከትል ከሆነ ቆም ብሎ ማሰብ ያስፈልጋል፡፡ መንግሥት ችግሮችን የመፍታት አቅም ከሌለው፣ ከሚችሉ ሰዎች ጋር ህብረት ፈጥሮ መፍታት ነው የሚበጀው፡፡ እስካሁን ይሄን ማድረግ አልቻለም፡፡ ከዚህ በኋላም ይሄን ለማድረግ ጊዜ አለው፡፡ ወደ ህብረተሰቡ ቀርቦ በመነጋገር፣ ተከታታይ የመትሄ ሀሳቦችን ማመንጨትና ተግባር ላይ ማዋል ያስፈልጋል፡፡