Administrator

Administrator

ለምዝገባ 500 ዶላር? የተሸላሚዎች ዝርዝር ውስጥ አልተካተቱም?


ባለፈው ህዳር 9 ቀን 2016 ዓ.ም በአሜሪካ ካሊፎርኒያ፣ትልቁ የአፍሪካ የፊልም ሽልማት “ናፍካ” ሥነ-ስርዓት ተካሂዷል፡፡ በየዓመቱ የሚካሄደው ይኼው የሽልማት ሥነስርዓት፣ ለመጀመሪያ ጊዜ በወኪሉ “ቆንጆ ፕሮሞሽን”በኩል ኢትዮጵያውያን አርቲስቶች እንዲወዳደሩ በሰጠውእድል ተዋንያን፣ ዳይሬክተሮች፣ የሜካፕ አርቲስቶች፣ሲኒማቶግራፈሮችና አንድ የበጎ አድራጎት መስራች በድምሩ
9 ሰዎች በእጩነት ወደ አሜሪካ ተጉዘው ነበር፡፡በተለይም ዝነኞቹ ተዋንያን ግሩም ኤርሚያስና ሩታመንግስተ አብ፤“ምርጥ የህዝብ ምርጫ ተዋንያን” በሚለውዘርፍ አሸናፊ መሆናቸው ተገልፆ፣በአገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን ተዘግቦ ነበር፡፡ የሽልማቱ ቦታ ላይ ሲደርሱ ግን
ብዙ ችግር እንደገጠማቸው፣ የናፍካው የኢትዮጵያ ተወካይ ሀሰተኛ እንደሆነና በሽልማት ቦታው ላይ ግራ ተጋብተው
እንደነበር፣ ሲወራ ሰንብቷል፡፡ከሽልማት ሥነ ስርዓቱ መካሄድ በኋላ አንድ ወር ከ10 ቀን ያህል በአሜሪካ ቆይቶ የተመለሰው አርቲስት ግሩም
ኤርሚያስ፤ በሽልማቱ ዙሪያ ያለውን እውነታ እንዲገልጽ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛዋ ናፍቆት ዮሴፍ እንደሚከተለው አነጋግራዋለች፡


ለናፍካ ሽልማት ወደ አሜሪካ ያደረጋችሁት ጉዞ ምን ይመስል ነበር?
እንግዲህ ለሽልማት ወደ ካሊፎርኒያ የሄድነው ሐሙስ ዕለት ማታ ነው፡፡ ለ21 ሰዓት በረራ አድርገናል፡፡ አርብ ጠዋት ደረስን፤ ቅዳሜ ሽልማቱ ነበር፡፡ አመሻሽ ላይ ነው ሽልማቱ የተካሄደው፡፡ እኛ ካረፍንበት ራቅ ያለ ቦታ ላይ ነው፡፡ በትራፊክ መጨናነቅና በራሳችንም ምክንያት ወደ አዳራሹ ዘግየት ብለን ብንደርስም፣ ሽልማታችንን ግን ተቀብለናል፡፡
ከዚህ ስለ ሽልማቱ ብዙ ተወርቶ ብትሄዱም፣ እዚያ ከደረሳችሁ በኋላ ችግር እንደገጠማችሁና የእናንተ ስም በተሸላሚዎች ዝርዝር ውስጥ እንዳልተካተተ፣ በተለያዩ የአገር ውስጥ ሚዲያዎች ተወርቷል፡፡ ወሬው ከየት የመጣ ነው?
በዚህ መልኩ የተፈጠረ ችግር የለም፡፡ መድረክ አካባቢ ትንሽ ማስተባበር የጎደላቸው ነገሮች ነበሩ። ለምሳሌ ተሸላሚዎች ስማቸው መድረክ ላይ ተጠርቶ ሽልማቱ ሳይቀርብ፣ ከመድረክ ጀርባ የወሰዱ አሉ፡፡ በሌላ በኩል፤ መድረክ መሪዎቹ “ከ1-5 የወጡ ፊልሞች እነዚህ ናቸው፤ አንደኛ የወጣው ደግሞ ይሄ ነው” ማለት ሲገባቸው፣ ቀድሞ ስክሪን ላይ ይለቀቅ ነበር፡፡ ይሄ አጓጊነቱን ይቀንሰዋል። እና የሽልማት ሂደቱ ላይ በአዘጋጆቹ ችግር ትንሽ የተዘበራረቁ ነገሮች ነበሩ እንጂ እኔና ሩታ ላይ ብቻ ተለይቶ የደረሰ ነገር አልነበረም፡፡ ከዝግጅቱ በኋላ እንዲህ የተዘበራረቀበትን ምክንያት ለማወቅ ሙከራ ስናደርግ፣ ከዚህ በፊት የተካሄዱትን አምስት የናፍካ ሽልማቶች ራሱ ሸላሚው ድርጅት ያዘጋጃቸው ሲሆኑ ጥሩ ሂደት እንደነበራቸው ሰምተናል፡፡ የዘንድሮው ለሌላ ኤጀንት በመሰጠቱ፣ ኤጀንቱ እንደ ጀማሪነቱ ትንሽ ክፍተት እንደተፈጠረበት ነው የተገለፀልን፡፡
ሁለታችሁ ሽልማቱን እንዳላገኛችሁ----በተለይም ሩታ ታጨች በተባለችበት ዘርፍ አንዲት ናይጀሪያዊት ሽልማቱን ይዛ ፎቶ መነሳቷ---እየተወራ ያለው ከምን መነሻ ነው?
እኔ ይሄ ነገር በምን መነሻ እንደተወራ፣ ወሬውን ማን እንዳዛመተውም አላውቅም፡፡ እኛ የሄድነው መዘጋጀቱ እውን በሆነ የሽልማት ስነ-ስርዓት ላይ ለመገኘት ነው፡፡ ሽልማታችንን አግኝተን ተመልሰናል። ይሄ “በሬ ወለደ” አይነት ወሬ በጣም ገርሞኛል፡፡ ሙያችንን እናሳድጋለን ብለን በምንጥርበት ጊዜ፣ እንዲህ አይነት ወፍ ዘራሽ ወሬዎች መናፈሳቸው እጅግ አሳፋሪ ነው፡፡
በናፍካ የኢትዮጵያ ተወካይ ነው የተባለውና የ“ቆንጆ ፕሮሞሽን” ስራ አስኪያጅ አቶ ማይክ በናፍካ እንዳልተወከለ፣ በአሜሪካ የታክሲ ሹፌር እንደሆነና ከኪነ-ጥበብ ጋር ግንኙነት እንደሌለውም ተወርቷል፡፡ ለምዝገባ እያንዳንዳችሁ 500 ዶላር ከፍላችኋል የተባለውስ--- ሰምተኸዋል?
የመጀመሪያው ነገር የናፍካ ተወካይ የታክሲ ሹፌር ከሆነም ነውር አይደለም፡፡ ሹፍርናም የተከበረ ሙያ ነው፡፡ ዋናው ነገር ይህንን እድል ለአገራችን ማምጣቱና የያዘው ራዕይ ትልቅ መሆኑ ነው፡፡ አንድ ሰው ታክሲ እየነዳ ወይም ሌላ ስራ እየሰራ፣ ጎን ለጎን ሌላ ተጨማሪ ስራ ቢሰራ ችግሩ ምንድን ነው፡፡ አየሽ ወሬው ሰውንና የሰውን ሙያ ከመናቅ ይጀምራል፤ ይሄ በጣም ያሳፍራል፡፡ እንደኔ እንደኔ ማይክ ሁሉቃ ወደ ኢትዮጵያ ይዞት የመጣው እድል፣ ለአርቲስቱና ለአገር ይጠቅማል አይጠቅምም የሚለው ነው መታየት ያለበት እንጂ ሌላው ነገር አይደለም፡፡ እንዲህ አይነት ጥሩ ዕድሎች ሲመጡ፣ ለማበላሸትና የሚሰራን ሰው ሞራል ለመንካት የሚደረግ ሩጫ ያሳዝናል፡፡ ዌብ ሳይቱን ናፍካ ብሎ ገብቶ ማየት ይቻላል፤ ሁሉም ነገር በግልፅ ይገኛል፡፡
ሩታን በተመለከተ ስሟ በስነ ስርዓቱ ተጠርቶ፣ መድረክ ላይ ወጥታ ንግግር አድርጋ፣ ሽልማቷን ተቀብላለች፡፡ እኔም እንደዛው፤ ሽልማቴ በቤቴ ይገኛል፡፡ በመጀመሪያ ሚዲያዎች ይህን ወሬ ተቀብለው  ዜና ሲሰሩ፣  እኛን የጉዳዩን ባለቤቶች ለምን አልጠየቁንም? ልክ አሁን አንቺ እንደምትጠይቂን፣ ለምን አልተጠየቅንም፡፡ እኛ በቦታው የነበርነውን የጉዳዩን ባለቤቶች መጠየቅ ነበረባቸው፡፡ ከሆነ አካል ወሬ ሰሙ፤ ዋና ባለቤቶቹን ሳይጠይቁ፣ የአንድ ወገን ሃሰተኛ ወሬ ይዘው ወጡ። ይሄ ነው ሁላችንንም ወደ ኋላ እየጎተተን ያለው፡፡ ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ በዝግጅቱ በኩል አንዳንድ ክፍተቶች ነበሩ፤ ለምሳሌ ሰው ስሙ እየተጠራ መድረክ ላይ ሲወጣ፣ ገና አዋርዱ ወደ መድረክ አልመጣም፡፡ ብዙ ተሸላሚ ማለት ይቻላል … ሽልማቱን ከመድረክ ጀርባ ነው የወሰደው፡፡ ይሄ የእኔም ሆነ የሩታ ወይም የሌሎች ተሸላሚዎች ችግር ሳይሆን የአዘጋጁ ነው፡፡ እዚያም የሽልማት ቦታ ላይ የተፈጠረው አንዳንድ ክፍተት እንደዚህ ነው የሆነው፤ አዘጋጆቹ ናቸው ሊጠየቁ የሚገባው፡፡
ተወካዩን በተመለከተ የናፍካ አርማና ማህተም ባለው ደብዳቤ፤ ‹‹On behalf of Nafca›› ተብሎ ስሙ ተጠቅሶ፣ ውክልና የተሰጠበትን ደብዳቤ አይቼ ነው ወደ ጉዳዩ የገባሁት፡፡ እኔ ህፃን ልጅ አይደለሁም፤ በምንም መልኩ ልታለል አልችልም። ወይም ደግሞ ዋንጫ የመሸለም ሱስ የለብኝም። እንዴት የኢትዮጵያን ህዝብ አታልላለሁ፤ ሰው ድምፅ ሰጥቶናል፤ እንዲህ አይነት ወሬ ማውራት የደገፈንን ሰው መናቅ ነው፡፡ እያንዳንዱ ነገር በዶክመንት የተደገፈ፣ በተፈለገው ጊዜ ሊታይ የሚችል ነገር ነው የተካሄደው፡፡ እንደተባለው በአየር ላይ የተናፈሰ ወሬ፣ ወይም በክፍያ የተከናወነ አይደለም። ናፍካም ትልቅ የአፍሪካ የፊልም ሽልማት ነው፤ ለ6ኛ ጊዜ የተካሄደ። እኔም ሩታም ይዘን የመጣነው ኩራታችንን፣ የሚገባንን ሽልማት ነው፤ ይሄ ደረቴን ነፍቼ በኩራት የምናገረው ነው። አንድ ጥቁር አሜሪካዊ የሆነውን ልንገርሽ፡፡ ለሽልማት ስሙ ተጠራ፤ነገር ግን ሽልማቱ የለም፤ ለምን ብሎ ሲጠይቅ፤ ”የአንተን ሽልማት ኢ-ሜይል እናደርግልሃለን” አሉት፡፡ የእኔን ሽልማት ይዞ ነው ፎቶ የተነሳው፤ ይሄ የናፍካ ስህተት ነው። በእንዲህ አይነት ስነ-ስርዓቶች ላይ ትልልቅ ስህተቶች ይፈጠራሉ፡፡ ለምሳሌ በዓለም የቁንጅና ውድድር ላይ አንደኛ ለወጣችው ሽልማቱ መሰጠት ሲገባው፣ ሁለተኛ ለወጣችው ተሰጥቷል፡፡ ይሄ ያጋጥማል፤ ስህተት እየተሰራ ይቀጥል ለማለት ግን አይደለም፡፡
የሽልማቱ ሥነ ስርዓት ከተካሄደ በኋላ፣ ከ1ወር በላይ ቆይታችሁ ነው ወደ አገራችሁ የተመለሳችሁት። እግረ መንገዳችሁን ያከናወናችሁት ነገር ነበር?
ከሄድንበት ፕሮግራም መጠናቀቅ በኋላም እዚያው ሎስ አንጀለስ ስለነበርን መጀመሪያ ያደረግነው ‹‹ዩኒቨርሳል ስቱዲዮ›› የተሰኘውን ትልቅ የፊልም ኩባንያ መጎብኘት ነው፡፡ በጣም አስደናቂ ስቱዲዮ ነው፡፡ አሜሪካ በጣም ከተደነቅኩባቸውና ከተገረምኩባቸው ነገሮች አንዱና ዋነኛው “ዩኒቨርሳል ስቱዲዮ” ነው፡፡ ይህ ስቱዲዮ አንድ የፊልም ባለሙያ ማየት የሚገባው ወሳኝ ቦታ ነው፡፡ ብዙ ልምዶችን ቀስመናል፡፡ ከዚህ በኋላ ያደረግነው በበጎ አድራጎት ዘርፍ የመሰረት በጎ አድራጎት ድርጅት መስራችና ዳይሬክተር እጩ ነበረች፡፡ በእርግጥ በዚህ ዘርፍ አንዲት ጣሊያናዊት ካቶሊክ በጎ አድራጊ ሴት ናቸው የተሸለሙት፡፡ እናም የተለያዩ ግዛቶች እየተዘዋወርን፣መሰረት ለምትረዳቸው ህፃናትና እናቶች፣ የገቢ ማሰባሰቢያ ስራዎችን ሰርተናል፡፡
በሌላ በኩል፤ብዙዎቻችን የየራሳችን ህልም አለን፡፡ ወደ ህልማችን ለመጠጋት ብዙ ጥረናል። ከተለያዩ የአፍሪካ ፊልም ሰሪዎች ጋር በብዙ ስራዎች ዙሪያ ተነጋግረናል፡፡ በተለይ አንድ የጋና ትልቅ የፊልም ባለሙያ፣ ሆሜስ ማክቪል ይባላል። “One Night in Vegas” እና “Paparazi” በተሰኙ ፊልሞቹ ይታወቃል፡፡ ከዚህ ባለሙያ ጋር በጣም ተወያይተናል፡፡ በቀጣይ ስለምንሰራውም እየተነጋገርን እንገኛለን፡፡ ዲሲም ሄደን አቶ ታምራት የተባሉ፣ ላለፉት 42 ዓመታት በዲሲ የኖሩ ሰውን አነጋግረናል፡፡ ብቻ ብዙ ነገሮችን ከውነናል፡፡ መቼም ዋናው ህልማችን የናፍካን ሽልማት ወስዶ ለመመለስ ብቻ አይደለም፡፡ ወደ ህልማችን የሚያስጠጋንን ነገር እግረ መንገዳችንን ፈፅመን መጥተናል፡፡
በቆይታህ ካገኘኸው ልምድ የፊልሙን ኢንዱስትሪ ለማሳደግ ምን አስበሀል?
እኔ እንግዲህ ሁሌም ተማሪ ነኝ ብዬ ነው የማስበው፡፡ እኔ እንደ ችግር የማየው፣ ራሳችንን ለሌላው ዓለም አላሳየንም፤ ኤክስፖዠር ያስፈልገናል። እነዚህን ነገሮች ለማድረግ በግሌ እጥራለሁ፡፡ ነገር ግን እድሎች ሲመጡ እንዲህ አይነት ያልተፈጠረ ነገር እያወሩ ሙያውን ከማቀጨጭ፣ በቅን ልቦና ማሰብ፣ መቻቻልና መተራረም የተሻለ ነው፡፡ እድሎችን ባበላሸን ቁጥር፣ ሙያችንን ወደ ዓለም ገበያ ለማቅረብ እንቸገራለን፡፡ በተረፈ አገራችን ላይ ጥሩ ተሰጥኦ ያላቸው ተዋንያን፣ ደራሲያን፣ ዳይሬክተሮች አሉ፡፡ ከመላው ዓለም ጋር መፎካከር የሚችሉ ባለሙያዎች አሉን፡፡ ሌላው የሚጎድለን እርስ በእርስ በሙያችን መደጋገፍና አብሮ የመስራት ነገር ነው፡፡ የናይጄሪያና የጋና ፊልም ሰሪዎች፣ የዓለምን ገበያ የተቀላቀሉት አብሮ የመስራት ባህል ስላላቸው ነው፡፡   



Saturday, 14 January 2017 16:04

የቴክኖሎጂ ጥግ

የፍቅር ጥግ
· ማፍቀር እንጂ በፍቅር መውደቅ የለብንም፤
ምክንያቱም የሚወድቅ ነገር ሁሉ ይሰበራል፡፡
ቴይለር ስዊፍት
· አንድ ላይ መሆን የቱንም ያህል ፈታኝ ቢሆን
ግዴለኝም፤ ከመለያየት የሚብስ ነገር የለም፡፡
ጆሴፊን አንጄሊኒ
· ራሳችሁን ለመሆን ለማይፈቅድላችሁ
ግንኙነት እጅ አትስጡ፡፡
ኦፕራ ዊንፍሬይ
· ከራሱ ጋር በፍቅር የሚወድቅ፣ ማንም
ተፎካካሪ የለውም
ቤንጃሚን ፍራንክሊን
· እናንተ እብደት ትሉታላችሁ፤ እኔ ግን ፍቅር
እለዋለሁ፡፡
ዶን ቢያስ
· ፍቅር አብሮን የተፈጠረ ሲሆን ፍርሃት እዚህ
የተማርነው ነው፡፡
ማርያኔ ዊሊያምሰን
· ፍቅር ባለቤትነትን አይጠይቅም፤ ነፃነትን
ያጎናፅፋል እንጂ፡፡
ራቢንድራናዝ ታጎ
· ፍቅር፤ ፍቅርን የሚያመነጭ ኃይል ነው፡፡
ኤሪክ ፎርም
· ሰዎችን ልትወዳቸው እንጂ ልታድናቸው
አትችልም፡፡
አናይስ ኒን
· ሁለት ነፍሶች ግን አንድ ሃሳብ፤ ሁለት ልቦች
ግን እንደ አንድ የሚመቱ፡፡
ፍሬድሪክ ሃልም
· የማይቻለውን የሚቻል የሚያደርገው ፍቅር
ነው፡፡
የህንዶች አባባል
· ፍቅር፤ በትዳር የሚድን ጊዜያዊ እብደት
ነው።
አምብሮሴ ቢርስ

አለማችን በሲጋራ ሳቢያ በአመት 1 ትሪሊዮን ዶላር ታጣለች
- በ2030 በየአመቱ የሚሞቱ አጫሾች ቁጥር 8 ሚሊዮን ይደርሳል

የሩስያ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር እ.ኤ.አ ከ2015 በኋላ ለተወለዱ ሁሉም የአገሪቱ ዜጎች ሲጋራ እንዳይሸጥ የሚከለክል እጅግ ጥብቅ
ህግ በማውጣት ተግባራዊ ለማድረግ ማቀዱን የእንግሊዙ ዘ ታይምስ ዘገበ፡፡ ቀጣዩን የሩስያ ትውልድን ከሲጋራ ነጻ እንደሚያደርግ ቢታሰብም የአፈጻጸሙ ጉዳይ አጠያያቂ ነው የተባለው የሚኒስቴሩ ዕቅድ፣ እንደታሰበው ተግባራዊ የሚደረግ ከሆነ፣ ሩስያ ከአለማችን አገራት እጅግ ጥብቅ የጸረ-ትምባሆ ህግ ያወጣች የመጀመሪያ አገር ትሆናለች ያለው ዘገባው፤ አገሪቱ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በትምባሆ ዙሪያ ጉልህ እርምጃዎችን መውሰድ መጀመሯን ጠቁሟል፡፡ ዕቅዱ ጤናማ ዜጋ ለመፍጠር ቢያስችልም፣ በሌላ በኩል ግን ከጥራት በታች የሆነ የትምባሆ ምርት በጥቁር ገበያ ህገወጥ መንገድ እየተሸጠ የዜጎችን ጤና የከፋ አደጋ ላይ እንዲጥል ምክንያት ሊሆን ይችላል የሚል ስጋት መፍጠሩን እንዲሁም ለሁሉም ዜጎች ሲጋራ አትሽጡ የሚለው ህግ በተጠቃሚዎችና በትምባሆ አምራች ኩባንያዎች ዘንድ ቁጣን ሊቀሰቅስ እንደሚችል መነገሩንም ዘገባው
አመልክቷል፡፡ የሩስያ መንግስት ባለፉት አመታት የሲጋራ አጫሾችን ቁጥር ለመቀነስ በሚል በወሰዳቸው የተለያዩ እርምጃዎች ከፍተኛ ውጤት
ማስመዝገቡን ያስታወሰው ዘገባው፣ ባለፈው የፈረንጆች አመት 2016 ብቻ የአገሪቱ አጫሾች ቁጥር በ10 በመቶ መቀነሱንም አክሎ ገልጧል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ የአለማችን ኢኮኖሚ በሲጋራ ሳቢያ በየአመቱ 1 ትሪሊዮን ዶላር ገደማ ኪሳራ እንደሚገጥመውና በሲጋራ ማጨስ
ሳቢያ በየአመቱ ለህልፈተ ህይወት የሚዳረጉ ሰዎች ቁጥር በመጪዎቹ 13 አመታት፣ 8 ሚሊዮን ያህል ይደርሳል ተብሎ እንደሚገመት
የአለም የጤና ድርጅት ሰሞኑን ባወጣው መረጃ ማስታወቁን ዘገባው አስረድቷል፡፡ ድርጅቱ ባለፈው ማክሰኞ ያወጣውን የጥናት ውጤት
ጠቅሶ ሮይተርስ እንደዘገበው፣ እስካሁን ባለው መረጃ በአለማቀፍ ደረጃ በሲጋራ ሳቢያ 6 ሚሊዮን ያህል ሰዎች በየአመቱ የሚሞቱ
ሲሆን፣ ይህ ቁጥር እስከ 2030 ድረስ 8 ሚሊዮን ይደርሳል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ በሲጋራ ለህልፈተ ህይወት ከሚዳረጉት
ሰዎች መካከል ከ80 በመቶ በላይ የሚሆኑት በመካከለኛና በዝቅተኛ ገቢ አገራት የሚገኙ እንደሆኑም ዘገባው ጠቁሟል፡፡

የፊሊፒንሱ ፕሬዚዳንት ሮድሪጎ ዱቴሬ፤ ከአደንዛዥ ዕጽ ህገወጥ ንግድ ጋር ንክኪ ያላቸው የአገሪቱ ከንቲባዎችና ባለስልጣናት ከህገወጥ ተግባራቸው እንዲታቀቡ አልያ ግን ያለአንዳች ማመንታት በግድያ እንደሚያስወግዷቸው ባለፈው ሰኞ ማስጠንቀቃቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡ ፕሬዚዳንቱ በአደንዛዥ ዕጾች ንግድ ውስጥ ተሳትፈዋል የተባሉ 10 ሺህ የሚደርሱ የአገሪቱ ከንቲባዎች፣ አገረ ገዢዎች፣ የፖሊስ መኮንኖችና ሌሎች የመንግስት ባለስልጣናትን ስሞች የያዘ ዝርዝር ሰነድ ማሰናዳታቸውንና እርምጃ ለመውሰድ መዘጋጀታቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡ በዚህ ዝርዝር ውስጥ ስማቸው የተጠቀሰ ከንቲባዎች፣ ዛሬ ነገ ሳይሉ በአፋጣኝ ስራቸውን በገዛ ፈቃዳቸው እንዲለቁና ከህገወጥ ስራቸው እንዲታቀቡ ያሳሰቡት ፕሬዚዳንቱ፤ ይህን በማያደርጉት ላይ ፈጣን የግድያ እርምጃ እንደሚወስዱ ዝተዋል፡፡ ፕሬዚዳንቱ ከዚህ ቀደምም በከንቲባነት ሲሰሩ፣ከአደንዛዥ ዕጾች ህገወጥ ንግድ ጋር ንክኪ አላቸው ያሏቸውን የመንግስት ባለስልጣናት መግደላቸውን ማመናቸው የተዘገበ ሲሆን፣ ፕሬዚዳንቱ ከጉዳዩ ጋር ንክኪ አላቸው ባሏቸው ዜጎች ላይ እርምጃ እንዲወሰድ ማዘዛቸውን ተከትሎ፣ በስድስት ወራት ጊዜ ውስጥ ከ5 ሺህ 900 በላይ ሰዎች መገደላቸውን ሲኤንኤን በቅርቡ ባወጣው ዘገባ አስረድቷል፡፡

ድንገት በእሳት በሚጋየው ጋላክሲ ኖት 7 ምርቱ ሳቢያ በታሪኩ የከፋ በተባለው ቀውስ እየተናጠ አመቱን የሸኘው ግዙፉ ሳምሰንግ ኤሌክትሮኒክስ፤ በዚህ አስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ሆኖም በመጨረሻው የሩብ አመት ትርፉ ካለፈው አመት በ50 በመቶ እድገት ማሳየቱን አስታውቋል፡፡ ኩባንያው ባለፈው ሳምንት ይፋ ባደረገው መረጃ፣ የ2016 የመጨረሻው ሩብ አመት ትርፉ ባለፈው አመት ተመሳሳይ ጊዜ ካስመዘገበው ትርፍ የ50 በመቶ ያህል ጭማሪ በማሳየት፣ 7.8 ቢሊዮን ዶላር መድረሱን እንዳስታወቀ አሶሼትድ ፕሬስ ዘግቧል፡፡ ሳምሰንግ በአመቱ ያስመዘገበው ገቢ ካለፈው አመት የ10 በመቶ ጭማሪ ማሳየቱንና ይህም ባለፉት ሶስት አመታት ካገኘው ገቢ ከፍተኛው መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፤ ትርፋማነቱ ማደጉን ይፋ ማድረጉን ተከትሎም የአክሲዮን ድርሻው በ1.9 በመቶ ማደጉን አስታውቋል፡፡ ኩባንያው ከገባበት ቀውስ ለመውጣት ከፍተኛ ጥረት እያደረገ እንደሚገኝ ያመለከተው ዘገባው፤ የተለያዩ ምርቶቹን በስፋት ወደ ገበያ ለማቅረብ በማቀድ በአስር ቢሊዮኖች ዶላር መድቦ፣ የማስፋፊያ ስራዎችን እያከናወነ እንደሚገኝም ገልጧል፡፡

የኡጋንዳው ፕሬዚዳንት ዮሪ ሙሴቬኒ፣ የአገሪቱ ልዩ የጦር ሃይል ሃላፊ ሆኖ ሲሰራ የቆየውን የመጀመሪያ ልጃቸውን ሜጀር ጄኔራል ሙሆዚ
ኬነሩግባን የፕሬዚዳንቱ ልዩ አማካሪ አድርገው መሾማቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡ ፕሬዚዳንት ሙሴቬኒ ደህንነታቸውን ለማስጠበቅ የተቋቋመውን ልዩ ሃይል ሲመራ የቆየውን የበኸር ልጃቸውን የ42 አመቱን ጄኔራል ሙሆዚ ኬነሩግባን በአማካሪነት መሾማቸው በአገሪቱ ቀጣይ ፖለቲካ ላይ ትልቅ ትርጉም እንዳለው የጠቆመው ዘገባው፤ ስልጣናቸውን ለማራዘም የያዙት እቅድ አካል ነው መባሉን ገልጧል፡፡
ባለፈው ማክሰኞ በአገሪቱ የጦር ሃይል መኮንኖች ሹም ሽር ያደረጉት ሙሴቬኒ፤ በአጭር ጊዜ ውስጥ ከፍተኛ የስልጣን ዕድገት ያገኘውን ልጃቸውን በወሳኙ የአማካሪነት ቦታ ላይ መሾማቸው፣ ልጅዬው የሆነ ጊዜ ላይ የአባቱን ስልጣን ተረክቦ የአገሪቱ መሪ መሆኑ አይቀርም የሚለውን የቆየ ጥርጣሬ አባብሶታል ተብሏል፡፡የፕሬዚዳንቱ ልጅ ሜጀር ጄኔራል ሙሆዚ ኬነሩግባ፣ በጦር ሃይሉ ውስጥ ያለው ስልጣን
በአጭር ጊዜ ውስጥ ከፍ እያለ መምጣቱን የጠቆመው ዘገባው፤ ባለፈው አመት ከብርጋዴር ጄኔራልነት ወደ ሜጀር ጄኔራልነት ማደጉንም አስታውሷል፡፡ እ.ኤ.አ በ1986 ለመጀመሪያ ጊዜ ስልጣን ላይ የወጡትና ለአምስት ተከታታይ የስልጣን ዘመናት አገሪቱን በመምራት ላይ የሚገኙት የ72 አመቱ ሙሴቬኒ፤ ስልጣን ከእጃቸው እንዳይወጣ በማሰብ ዘመዶቻቸውን በወሳኝ ቦታዎች ላይ እንደሚሾሙ
የጠቆመው ዘገባው፣ ወንድማቸው ሳሊም ሳልህ የፕሬዚዳንቱ አማካሪ፣ ሚስታቸው ጃኔት ሙሴቬኒ ደግሞ የትምህርት ሚኒስትር ሆነው በመስራት ላይ እንደሚገኙ ገልጧል፡፡

የሆሊውድ አክተሩ - ፊደል ካስትሮ
የኩባው ኮሙኒስት መሪ ፊደል ካስትሮና የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ሮናልድ ሬጋን አንድ የሚያመሳስላቸው ነገር አለ ከተባለ፣ የፊልም ባለሙያ የነበሩ መሆናቸው ነው፡፡ ሁለቱም በሆሊውድ ፊልሞች ላይ ተውነዋል - የየአገሮቻቸው መሪ ከመሆናቸው በፊት፡፡ በርግጥ የሬጋንን መሪ ተዋናይነት፣ የአዘቦት ቀን ተመልካች ያልሆኑ የድሮ ፊልም አድናቂዎች ሳይቀሩ አሳምረው ያውቁታል። የካስትሮ ግን የተረሳ የሆሊውድ ታሪክ ሆኗል፡፡ ለምን? ፊደል ካስትሮ እ.ኤ.አ በ1946 በተሰሩ ሁለት ፊልሞች ውስጥ ነው የተሳተፉት፡፡ አንደኛው “Holiday in Mexico” የሚል ሲሆን ሁለተኛው “Easy To Wed” ይሰኛል፡፡ ካስትሮ በሁለቱም ፊልሞች ላይ በአጃቢነት ነበር የተሳተፉት፡፡ በአንደኛው ፊልም ላይ አንድ መስመር ንግግር የነበራቸው ቢሆንም ከተቀረፁ በኋላ ዳይሬክተሩ ቆርጦ ካስትሮ ብግን ብለው ነበር አሉ፡፡ “አሜሪካ የምወዳት አገር ነበረች … አሁን ግን” … ብለው በንዴት ወደ አገራቸው ተመልሰዋል፡፡  
የመፅሃፍ ቀበኛው ፕሬዚዳንት
የአሜሪካ 26ኛው ፕሬዚዳንት ቴዎዶር ሩዝቬልት፤ በመፅሃፍ አንባቢነታቸው ዝነኛ ነበሩ፡፡ መፅሐፍ “የሰጠ ይድከም” የሚባልላቸው ዓይነት ሰው ናቸው፡፡ በህይወት ዘመናቸው በ10ሺዎች የሚቆጠሩ መፃህፍት እንዳነበቡ የሚነገርላቸው ሩዝቬልት፤ በአማካይ በቀን አንድ መፅሀፍ ያነቡ ነበር ተብሏል፡፡ በል በል ያላቸው ዕለት ደግሞ ከቁርስ በፊት አንድ መፅሀፍ፣ እስከ እራት ደግሞ ሁለት መፅሀፍት እምሽክ ያደርጉ ነበር፡፡ በፕሬዚዳትነት ዘመናቸውም ከንባብ ያላቀቃቸው አልተገኘም፡፡ የሥራ ጉዞ በባቡር ሲያደርጉ እንኳን ረዥም ሰዓት በንባብ ተመስጠው ነበር የሚያሳልፉት፡፡
የአገር መሪ ምን ዓይነት መፃህፍትን ማንበብ እንዳለበት ተጠይቀው ሲመልሱ፡- ሥነ ግጥምና ረዥም ልብ ወለዶችን እንዲሁም አጭር ልብ ወለዶችን ጠቅሰዋል። እኒህ ብቻ ግን አይደሉም፡፡ የሂብሩ ነቢያትንና የግሪክ ፀሐፌ ተውኔቶችን የማያደንቅ ከሆነ በራሱ ማዘን አለበት ብለዋል፡፡ በታሪክና በመንግስት እንዲሁም በሳይንስና በፍልስፍና ዙሪያ የተፃፉ መፃህፍትንም ማንበብ እንዳለበት ይመክራሉ - አንብበው የማይጠግቡት ሩዝቤልት፡፡
ተዋናይቷ ሂትለርን ለመግደል ትመኝ ነበር
ትውልደ - ስዊድን አሜሪካዊቷ የፊልም ተዋናይት ግሬታ ጋርቦ፤ ሁለተኛው የዓለም ጦርነት ካበቃ ከአስርት ዓመታት በኋላ፣ ለቅርብ ጓደኞቿ አንድ ምስጢርና ምኞቷን አካፍላቸው ነበር፡፡ እንዲህ ስትል፤ “ሚ/ር ሂትለር በጣም ነበር የሚፈልገኝ፡፡ ሁልጊዜ ይፅፍልኛል፤ ወደ ጀርመን እንድመጣም ይጋብዘኝ ነበር፡፡ ጦርነቱ በወቅቱ ባይጀመር ኖሮ፣ እሄድለትና ከቦርሳዬ ውስጥ ሽጉጤን አውጥቼ እደፋው ነበር፤ ምክንያቱም እኔ ብቻ ነኝ ሳልፈተሽ ልገባ የምችል ብቸኛ ሰው፡፡”
በነገራችን ላይ በአሜሪካ በ1920ዎቹና 30ዎቹ ዓመታት ዝነኛ ተዋናይት የነበረችው ግሬታ ጋርቦ፤ በምርጥ ተዋናይትነት ሦስት ጊዜ ለኦስካር ታጭታ ነበር፡፡  
ለ20 ሚ. ዶላር ጀርባውን የሰጠ ኮሜዲያን
እንግሊዛዊው ኮሜዲያን ራስል ብራንድ፣ ከድምፃዊት ሚስቱ ካቲ ፔሪ ጋር የመሰረተውን ትዳር ከ14 ወራት በኋላ እ.ኤ.አ በ2012 በፍቺ ሲደመድም፣ ከ44 ሚ. ዶላር ሀብቷ ላይ ግማሹን የመውሰድ ህጋዊ መብት ነበረው - 20 ሚ. ዶላር ገደማ፡፡ ራስል ግን ከሚስቱ ገንዘብ ላይ ድምቡሎ መውሰድ እንደማይፈልግና በተቻለ መጠን መለያየታቸው ሰላም የሰፈነበት ይሆን ዘንድ እንደሚሻ መናገሩን TMZ.com በወቅቱ ዘግቦታል፡፡ በሴት አውልነቱ በእጅጉ የሚታወቀው ራስል፤ ፍቺው ከመጠናቀቁ በፊት እንኳን ከአንድ ከሁለት ሴቶች ጋር ግንኙነት ጀምሮ ነበር ተብሏል፡፡  የፖላንድ ተወላጇ ፈረንሳዊት ሳይንቲስት ሜሪ ኩሪ፤ የዘመኗ ዝነኛ የፊዚክስና ኬሚስትሪ ተመራማሪ ነበረች፡፡ ከባለቤቷ ከፒሬ ጋር እ.ኤ.አ በ1903 ዓ.ም በፊዚክስ የኖቤል ሽልማት ያሸነፈችው ኩሪ፤ በ1911 ዓ.ም ሁለተኛውን የኖቤል ሽልማት በኬሚስትሪ ተሸልማለች። ኩሪ ራዲየም የተሰኘውን የኬሚካል ንጥረ ነገር ያገኘች ዝነኛ ሳይንቲስት ናት፡፡ ሆኖም ከወንዶች የሙያ አቻዎቿ ተቃውሞና ተፅዕኖ ይደርስባት እንደነበር መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡ ከዚሁ ሁሉ ስኬትና ሽልማት በኋላ ስመ ጥር የሆነው የፈረንሳይ አካዳሚ አባል እንድትሆን አልተፈቀደላትም ነበር፡፡ በሌላ ምክንያት አልነበረም -  ሴት በመሆኗ ብቻ!  

ባለፈው ቅዳሜ ማለዳ...
ምዕራብ አፍሪካዊቷ ጋና፣ ለሳምንታት ደፋ ቀና ያለቺበትን የአዲሱ መሪዋ በዓለ ሲመት በድምቀት አከበረች፡፡ አዲሱ የጋና ፕሬዚዳንት ናና አኩፎ አዶ፣ ከመዲናዋ አክራ ለሚወዱት ህዝባቸው በስሜት የታጀበና ልብ የሚነካ ንግግር አደረጉ፡፡ ህዝባቸውም የታላቁን ናና አኩፎ አዶን አነቃቂ ንግግር በጥሞና እያዳመጠ፣ ባለ ራዕይ መሪነታቸውንና አንደበተ ርቱዕነታቸውን ሲያደንቅ ዋለ፡፡
የዋሁ የጋና ህዝብ የአዲሱን መሪውን የንግግር ችሎታ እያደነቀ ባለበት ቅጽበት ግን፣ ጉድ መጎልጎል የሚወደው የፌስቡክ ሰራዊት፣ አዲሱን መሪውን ትዝብት ላይ የሚጥል ዘመቻ ከፈተ፡፡
“ፕሬዚዳንቱ በበዓለ ሲመታቸው ላይ ባደረጉት ንግግር፣ ከሁለት የቀድሞ የአሜሪካ ፕሬዚዳንቶች ንግግር፣ የተመነተፏቸውን አንቀጾች ተጠቅመዋል” የሚለው ያልተረጋገጠ ውንጀላና ሃሜት፣ቅዳሜን ሙሉ በፌስቡክ ሲሰራጭ ዋለ፡፡
በነጋታው...
ነገርዬው ካልተረጋገጠ ውንጀላና ሃሜትነት፣ በማስረጃ ወደተደገፈ አነጋጋሪ ዜናነት ተቀየረ፡፡ የናና አኩፎ አዶ ንግግር፣ የበርካታ የዓለማችን መገናኛ ብዙሃን ትኩስ ዜና ብቻ ሳይሆን የአዲሱ የጋና መንግስት የሃፍረትና የይቅርታ አጀንዳ ሆነ፡፡
ቢቢሲ እንደዘገበው፣ የጋናው ፕሬዚዳንት በበዓለ ሲመታቸው ላይ ባደረጉት ንግግር፣ የቢል ክሊንተንን እና የጆርጅ ደብሊው ቡሽን ንግግሮች መንትፈው፣ የራሳቸው በማስመሰል ማቅረባቸው ተረጋግጧል፡፡ የአዲሱ ፕሬዚዳንት ጽህፈት ቤትም፣ አዲሱ ፕሬዚዳንት የተባለውን ነገር መፈጸማቸውን በማመን፣ እሁድ ማለዳ የይቅርታ መግለጫ አውጥቷል፡፡
የጋናው ፕሬዚዳንት በዕለቱ ባደረጉት ንግግር፣ የቀድሞው የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ቢል ክሊንተን ከ20 አመታት በፊት በበዓለ ሲመታቸው ላይ ካደረጉት ንግግር የወሰዱትን አንድ ማራኪ አንቀጽ የራሳቸው አስመስለው አቅርበዋል፡፡ ይሄም ብቻ አይደለም። ጆርጅ ደብሊው ቡሽ በ2001 ካደረጉት ንግግር፣ የወሰዱትን ሌላ ማራኪ አንቀጽም፣ ምንጩን ሳይጠቅሱ አነብንበዋል፡፡
ከሌላ ሰው የመነተፉትን ልብ አማላይና ማራኪ አንቀጽ የራሳቸው አስመስለው በማቅረብ፣ የጋናው ፕሬዚዳንት የመጀመሪያው የአገር መሪና ገናና ፖለቲከኛ አይደሉም የሚለው ቢቢሲ፤ ወደ ኋላ መለስ ብሎ ተጨማሪ ክስተቶችን ያስታውሳል፡፡
የትራምፕ ሚስት
የተመራጩ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት የዶናልድ ትራምፕ ባለቤት፣ ሚላንያ ትራምፕ በሃምሌ ወር ላይ ባደረጉት ንግግር፣ ቀዳማዊት እመቤት ሚሼል ኦባማ በ2008 ካደረጉት ንግግር የመነተፏቸውን አንቀጾች የራሳቸው አስመስለው አቅርበዋል፣ በሚል የትችት ናዳ ሲወርድባቸው መሰንበቱን የቢቢሲ ዘገባ አስታውሷል፡፡
የማዳጋስካር መሪ
የማዳጋስካር ፕሬዚዳንት በበኩላቸው፤በጥር ወር 2014 በተካሄደው በዓለ ሲመታቸው ላይ ባደረጉት ንግግር፣ ተመሳሳይ ምንተፋ መፈጸማቸው ተነግሯል፡፡ ፕሬዚዳንቱ በወቅቱ ባደረጉት ንግግር ውስጥ፣ የፈረንሳዩ ፕሬዚዳንት ከአስር አመታት በፊት ካደረጉት ንግግር የተወሰደና አንዳች እንኳን ለውጥ ያልተደረገበት አንቀጽ ተገኝቷል፡፡
የፕሬዚዳንቱ ተወካይ ግን፣ እንደ ጋናው አቻቸው ይቅርታ አልጠየቁም፡፡
“ከሌሎች ሰዎች ንግግር የተመረጠ አንቀጽ ወስዶ መጠቀም ምን ነውር አለው?!...” ብለው ድርቅ አሉ እንጂ፡፡
የናይጀሪያው መሪ
የናይጀሪያው ፕሬዚዳንት ሙሃመድ ቡሃሪ፤ በመስከረም ባደረጉት ንግግር፣ ባራክ ኦባማ በ2008 ካደረጉት ንግግር የወሰዱትን አንቀጽ ተጠቅመዋል፡፡
የአየርላንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር
የአየርላንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ኤንዳ ኬኒ፤ ምንተፋ ግን ለየት ያለ ነው፡፡
እሳቸው በ2011 ደብሊን ውስጥ ባራክ ኦባማን ለህዝብ ሲያስተዋውቁ ባደረጉት ንግግር የተጠቀሙትን አንድ አንቀጽ የመነተፉት፣ ከራሳቸው ከባራክ ኦባማ መሆኑ ተነግሯል፡፡
ኦባማ ራሳቸው
ከንግግሮቻቸው በርካታ አንቀጾችን በሌሎች ሰዎች የተመነተፉት ኦባማ ራሳቸውም፣ ከሌሎች ሰዎች ተመሳሳይ ምንተፋ መፈጸማቸውን የቢቢሲ ዘገባ ያስረዳል፡፡
ዘገባው እንዳለው፣ ኦባማ በ2008 ባደረጉት ንግግር፣ የቀድሞው የማሳቹሴትስ ገዢ ዴቫል ፓትሪክ፤ ከአስር አመታት በፊት ካደረጉት ንግግር የወሰዱትን አንቀጽ የራሳቸው አስመስለው አቅርበዋል፡፡
ኦባማ ይህን በማድረጋቸው ለቀረበባቸው ወቀሳ ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ “ይህን አንቀጽ በንግግሬ ውስጥ እንድጠቀም ምክር የሰጡኝ ራሳቸው ዴቫል ፓትሪክ ናቸው፤ ይሄም ሆኖ አንቀጹ የእሳቸው መሆኑን አለመጥቀሴና እውቅና አለመስጠቴ ስህተት መሆኑን አምናለሁ” በማለት፡፡
የቀድሞው የካናዳ ጠቅላይ ሚኒስትር
የቀድሞው የካናዳ ጠቅላይ ሚኒስትር ስቴፈን ሃርፐርም በ2003 ባደረጉት ንግግር ተመሳሳይ ድርጊት ፈጽመዋል፡፡
ሰውዬው በወቅቱ ባደረጉት ንግግር ውስጥ የተጠቀሙት አንድ አንቀጽ፣ የያኔው የአውስትራሊያ ጠቅላይ ሚኒስትር ጆን ሃዋርድ፤ ከቀናት በፊት ካደረጉት ንግግር የተመነተፈ እንደሆነ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡ ይህ የአንቀጽ ምንተፋ፣ እንደ ዋዛ ታልፎ አልቀረም፡፡ ድርጊቱ ከተፈጸመ ከአምስት አመታት በኋላ፣ ሌላ መዘዝ ይዞ መጥቷል፡፡ በወቅቱ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ንግግሩን የጻፈላቸው ሰው፣ ያንን አንቀጽ ከሌላ ሰው መመንተፉ በመረጋገጡና ድርጊቱ ስቴፈን ሃርፐርንና ፓርቲያቸውን ሃሜትና ስላቅ ላይ በመጣሉ፣ ስራውን እንዲለቅ ተደርጓል፡፡












Saturday, 14 January 2017 15:40

የዘላለም ጥግ

(ታላላቅ ሰዎች በመሞቻቸው ሰዓት)

“ይቅርታ አድርግልኝ ጌታዬ፤ ሆን ብዬ
ያደረግሁት አይደለም”
ንግስት ሜሪ አንቶይኔቴ
(የሰቃይዋን እግር በስህተት ረግጣ የተናገረችው)
· “እኖራለሁ!”
የሮማ ንጉስ
(በራሱ ወታደሮች ከመገደሉ በፊት)
· “ህመም ይሰማኛል፡፡ ሀኪሞቹን ጥሯቸው”
ማኦ ዜዶንግ
(የቻይና ኮሙኒስት ፓርቲ መሪ)
· “የተጎዳ ሰው አለ?”
ሮበርት ኤፍ.ኬኔዲ (የአሜሪካ ፕሬዚዳንት)
(በጥይት ከተመቱ በኋላ ኮማ ውስጥ ከመግባታቸው
ጥቂት ሰኮንዶች በፊት ሚስታቸውን የጠየቁት)
· “አትጨነቅ፤ ዘና በል!”
ራጂቭ ጋንዲ (የህንድ ጠ/ሚኒስትር)
(በአጥፍቶ ጠፊ ከመገደላቸው ጥቂት ደቂዎች
በፊት ለፀጥታ ሰራተኛቸው ያሉት)
· “ኢየሱስ፤ እወድሀለሁ! ኢየሱስ፤ እወድሃለሁ!”
ማዘር ቴሬሳ
(ህንዳዊ መነኩሲት፣ በጎ አድራጊ)
· “በደንብ አውቅሻለሁ እንጂ! ፍቅሬ ነሽ፡፡
እወድሻለሁ”
ጆን ዋይኔ
(ለሚስቱ የተናገረው)
· “ኦህ ዋው! ኦህ ዋው! ኦህ ዋው!”
ስቲቭ ጆብስ
(የአፕል ኮምፒዩተር መሥራች)
· “እማማ፤ እቃዎቼን እሸክፍና ከዚህ ቤት
እወጣለሁ፡፡ አባባ ጠልቶኛል፤ ስለዚህ
ተመልሼ አልመጣም”
ማርቪን ጌይ
(በአባቱ ከመገደሉ ከጥቂት ደቂቃዎች በፊት ያለው)
· “የፍሎሪዳ ውሃዬን”
(የምትፈልገው ነገር ካለ ተጠይቃ የመለሰችው)
ሉሲሌ ቦል
· “ለምን ታለቅሳላችሁ? ለዝንተ ዓለም የምኖር
መስሏችሁ ነበር?”
ሉዊስ 14ኛ
(የፈረንሳይ ንጉስ)
· “መሞቴ ነው ወይስ ልደቴ ነው?”
ናንሲ አስቶር
(ስትነቃ በቤተሰቦቿ መከበቧን አይታ የተናገረችው)
· “ኦህ … አታልቅሱ - ጥሩ ልጆች ሁኑ፤ እናም
ሁላችንም በገነት እንገናኛለን፡፡”
አንድሪው ጃክሰን
(የአሜሪካ 7ኛው ፕሬዚዳንት)

የኢትዮጵያ የሃይማኖት ተቋማት ጉባኤ፤”የሰላም እና የእርቅ ሀገራዊ የምክክር መድረክ”፤ በአፍሪካ የኢኮኖሚ ኮሚሽን አዳራሽ፣ ባለፈው ማክሰኞና ረቡዕ
ተካሂዷል፡፡ በዚህ መድረክ ላይ የተለያዩ የሃይማኖት መሪዎች፣ባለፈው ዓመት የተቀሰቀሰውን ህዝባዊ ተቃውሞ ተከትሎ፣የተከሰተውን የዜጎች ህልፈትና
የንብረት ውድመት እንዲሁም በህዝቦች መካከል የተፈጠረውን መቃቃር በማስታወስ፣አገራዊ አንድነቱንም ሆነ ህዝባዊ ትስስሩን ወደቀድሞው ቦታው
ለመመለስ እርቀ ሰላም ማውረድ ወሳኝ መሆኑን በስፋት አንጸባርቀዋል፡፡
የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፣በምክክር መድረኩ ላይ ተገኝቶ የሃይማኖት መሪዎቹን የእርቀ ሰላም ሃሳብና ጥሪ እንደሚከተለው አጠናቅሮታል፡፡
ለፖለቲካዊ ችግሮች መፍትሄው ፖለቲካዊ ውይይት ነው፡፡

“ጠባሳው እንዲድን የእርቀ ሰላም ስራዎች
መስራት ይገባል”

ፓትርያርክ አባ ማትያስ (የኢ/ኦ/ተ/ቤ/ክ ፓትርያርክ)

ጌታችን በትምህርቱ፤”አስታራቂ ሰዎችን ብፁአን ናቸው” ብሎ ከማወደሱም በላይ “የእግዚአብሔር ልጆች ይግባቡ” በማለት የመጨረሻውን አምላካዊ ክብር እንደሚሰጣቸው አረጋግጦአል፡፡ ከዚህ አኳያ የዕርቀ ሰላም ተግባር ምን ያህል ታላቅ እንደሆነ መገንዘቡ የሚከብድ አይሆንም፡፡ በዓለም ዙሪያ ሁሉ እንደሚታየው፣ ጥንትም ሆነ ዛሬ፣ በአማንያንም ሆነ በኢ-አማንያን፣ የችግሮች ሁሉ መቋጫና አስተማማኝ መፍትሄ፣ እርቀ ሰላም ብቻ እንደሆነ ጥያቄ የለውም፡፡ ከአምላካዊ መርህ በመነሳት ስለ እርቀ ሰላም አስፈላጊነት ስናሰላስል፣ ነገሩ ግልፅ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ እግዚአብሔር ሁሉን ማድረግ የሚችልና ምንም የሚሳነው የሌለ ኃያል አምላክ ሲሆን ደካማ ከሆነው ፍጡር ጋር መታረቅ ለምን መረጠ? ብንል፣ እግዚአብሔር ባህርዩ ዕርቀ ሰላምን የሚወድ፣ ጥላቻን የሚጠላ በመሆኑ ብቻ እንደሆነ ቅዱስ መፅሐፍ ይነግረናል፡፡
ምንጊዜም ከሃይማኖት ቅኝት ርቆ የማያውቀው የሀገራችን ብሂለ አበው፤ “እርቅ ደም ያደርቅ” እያለ ከእግዚአብሔር ቃል ጋር በመተባበር፣ የዕርቀ ሰላም ሰዎች እንድንሆን ያስተምረናል፡፡ ባለፈው የክረምት ወራት በአንዳንድ የሃገራችን አካባቢዎች ያለአስፈላጊ አለመግባባቶች ተከስተው፣ በንፁሃን ወገኖች ላይ የህይወትና የንብረት ጉዳት ከማድረሳቸውም ሌላ በህዝቦች መካከል የመቃቃር ጠባሳ ፈጥረው አልፈዋል፡፡ ይሁንና ይህ መጥፎ ጠባሳ ብዙ እድሜ ሊሰጠው ስለማይገባ፣ ጠባሳው ሙሉ በሙሉ ድኖ፣ በፊት እንደነበረው ጤናማ እንዲሆን፣ተከታታይነት ያላቸው የዕርቀ ሰላም ስራዎች መስራት ይገባናል፡፡
መንግስት ባስቀመጠው ህጋዊ አሰራር ነገሩ ለጊዜው ሰከን ያለ ቢመስልም አበው፤ ‹‹መተው ነገሬን ከተተው›› እንደሚሉት፣ ሁሉም ቅሬታውን በመተው፣ ወደ ፍፁም መግባባት ይደርስ ዘንድ ባለድርሻ ወገኖች ነገሩን በሰከነ መንፈስ ተወያይተውበት፤ እንዲህ ያለ የሃገርን አንድነት የሚፈታተን ጎጂ ድርጊት እንዳይደገም፣የእርማት ስራ ሰርተውበት፣ በሃገራዊና ወንድማዊ መንፈስ ተማምነው፣ በዕርቀ ሰላም ማህተም የሚያትሙበት፣ ለወደፊትም መሰል ችግር ተነስቶ ዜጎች እንዳይጎዱ የሚያስችል አመለካከትና አስተሳሰብ የሚያሳድጉበት የዕርቀ ሰላም ስራ መሰራት አለበት፡፡ ይኸም ተልዕኮ በዋናነት የሃይማኖት አባቶች ኃላፊነትና ግዴታ መሆኑ ስለሚታወቅ፣ እኛ የሃይማኖት መሪዎች፣ ህዝቡን አስተምረን አሳምነንና አስታርቀን፣ ወደ ቀድሞው ሁናቴ ለመመለስ የአንበሳውን ድርሻ ወስደን፣ በሠፊው ለመስራት መትጋት ይኖርብናል፡፡
እኛ ኢትዮጵያውያን፤ ትናንትም ዛሬም ነገም አንድ ነን፡፡ መቼም ቢሆን አንለያይም፡፡ ይህንንም የምናረጋግጠው፣ በህዝቦቻችን መካከል ብቅ ማለት የጀመሩትን ብዥታዎች፣ ስሜታዊ እንቅስቃሴዎች በዕርቀ ሰላም እንዲስተካከሉና፣ በይቅርታ መንፈስ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ፋይላቸው እንዲዘጋ በማድረግ ነው፡፡

===========================================

“የሰላም ዋጋ የሚታወቀው ሰላም የጠፋ ጊዜ ነው”

ሼህ ሙሃመድ አሚን ጀማል ኡመር (የኢ/እስ/ጉ/ጠ/ም/ቤት ፕሬዚዳንት)

    እርቅና ሰላም፤ ጥልቅ ትርጉም ያላቸው፣ በሁሉም ሃይማኖቶች የሚፈለጉና የሚወደዱ ሀሳቦች ናቸው፡፡ የምክክር መድረኩም በእርቅና በሰላም ላይ በማተኮር መዘጋጀቱ፣ በሀገራችን ዘላቂ ሰላም እንዲረጋገጥ፣ የሀይማኖት ተቋማት የድርሻችንን ለማበርከት እድል ይሰጠናል፡፡ በተለይም ከሀገራችን ወቅታዊ የሰላም ሁኔታ አንፃር ሲታይ፣መድረኩ ወቅታዊና የጎላ ጠቀሜታ እንደሚኖረው ጠቅላይ ምክር ቤታችን ይገነዘባል፡፡
ከጥቂት ወራት በፊት በሀገራችን አንዳንድ አካባቢዎች የታየው አለመረጋጋትና የተፈጠረው ግጭት፣ይህንንም ተከትሎ የደረሰው የህይወትና የንብረት ውድመት ሲታይ፣ ሰላም በምንም የማይተመን ዋጋ እንዳለው ያስገነዝበናል፡፡ የሰላም ዋጋ የሚታወቀው ሰላም የጠፋ ጊዜ ነው፣ የሚለውን አባባል በተግባር አይተናል፡፡ ሁላችንም እንደምናውቀው፣ በሀገራችን ባሳለፍናቸው ሁለት አስርት አመታት፣ አንፃራዊ ሰላም በመኖሩ በርካታ ለውጦችን ተመልክተናል፡፡ መልካምና ተስፋ ሰጭ የእድገትና የልማት ጅማሮዎች ታይተዋል፡፡ ይህም አንዱ የሀገራችን ተጨባጭ እውነታ ነው፡፡ በአንፃሩ ከእድገታችንና ከለውጣችን ጋር አብሮ መጓዝ ያልቻለ የኋላቀርነት አመለካከት፣ ድህነት፣ ብልሹ አስተዳደርና አመራር፣ ሙስና እና መሰል ሁኔታዎች በተቃራኒው የእኛ መገለጫዎች ናቸው፡፡
ይህ አይነቱ የተደበላለቀ ሁኔታም፣ አንዱ በሌላው ላይ የበላይነት ለመያዝ በሚደረግ ፍትግያ፣ በሀገራችን በአንፃራዊነት ሰፍኖ የነበረው ሰላማዊ ሁኔታ፣ በአንዳንድ አካባቢዎች ለመታወክና ለግጭት መፈጠር ምክንያት ሆኗል፡፡ በውጤቱም ሁሉንም ወገን ያሳዘነ ክስተት ተፈጥሮ አልፏል፡፡ ይህ አይነቱ ሁኔታ ዳግም እንዳያገረሽና እንዳይከሰት፣ በየደረጃው ያለን የሀይማኖት መሪዎች፣ ምዕመናንን የማስተማር ኃላፊነታችንን ልንወጣ ይገባል፡፡
በሰዎች ማህበራዊ ግንኙነት ውስጥ የሀሳብ ልዩነትና የሀሳብ ግጭት መኖሩ የሚጠበቅና ተፈጥሯዊ ነው፡፡ ይሁንና ዋናው ጉዳያችን መሆን ያለበት፣ ልዩነቱና ግጭቱ ለምን ተፈጠረ የሚለው ሳይሆን፣ ግጭቱ እንዴት እንደሚፈታ ማወቁ ላይ ነው፡፡ ከዚህ አንፃር የሀሳብ ልዩነቶች ላይ ተመስርቶ የሚፈጠር ግጭትና አለመግባባት፣ በሰከነ መንገድ በውይይት፣ በጥበብና በብልሃት መፈታት አለበት፡፡ ይህ ግጭትን በሰላማዊና በሰለጠነ መንገድ የመፍታት፣ የይቅርታና የእርቅ መንገድም በሀይማኖቶች የሚደገፍ ቅዱስ ስራ ነው፡፡ በመካከላችን እርቅና ሰላም እንዲሰፍንም፣ ፍትህ እንዳይጓደል መጠበቅና ፍትሃዊ መሆን ይገባል፡፡ ሁሉም ሃይማኖቶች ፍትህን በመጠበቅ፣ ግጭትንና ጥላቻን በይቅርታ ልብ ማከም እንደሚገባ ያስተምራሉ፡፡ እስልምናም ከዚህ አስተሳሰብ ጋር በእጅጉ ይስማማል፡፡ በብዙ የቁርአን አንቀፆችም ፍትህን፣ ይቅርታን፣ እርቅንና ሰላምን የተመለከቱ ግልፅ መመሪያዎች ሰፍረዋል፡፡

==================================

‹‹ልዩነቶችን በመነጋገር መፍታት የስልጣኔ ም ልክት ነው››

ካርዲናል ብርሃነየሱስ ሱራፌል (የኢ/ካ/ቤ/ክ ሊቀጳጳስ)

በሃገራችን በተለያዩ የታሪክ ምዕራፎች ውስጥ መጠነ ሰፊ የሆኑ የውጭና የውስጥ ግጭቶችን ያስተናገድን ህዝቦች ብንሆንም የውጭውን ግጭቶች፣ ሃገራዊ ፍቅርን መሰረት ባደረገ፣ ጥበብ በተሞላበት ስልት በመከላከል፣ በአለም መድረኮች እስከ ዛሬ ስማችንን የሚያስጠራ ታሪክ ተመዝግቦ ይገኛል፡፡ በሌላ በኩል በሃገር ውስጥ የሚነሱ ሃይማኖታዊም ሆነ ፖለቲካዊ ግጭቶች በተለያዩ ደረጃና ሁኔታዎች መፍትሄ እየተበጀላቸው ካለንበት ዘመን ላይ ደርሰናል፡፡ የሃገራችን ህዝቦች ዘመናት ተሻግሮ እስከ ዛሬ ድረስ ህያው የሆነ ዘላቂ ሰላም ይገኝ ዘንድ የእርቅ ሂደቶች፣ ግጭቶችን የመፍታት ጥበብና ክህሎቶች ጠብቀው በማቆየት አስተላልፈውልናል፡፡ ይህ ጥልቅ የሆነ ሀይማኖትን መሠረት አድርጎ፣ ህዝቦችንና የሃገራችንን ሀብቶች ማክበር፣ የእለት ተእለት ኑሮአችን መርሆ ማድረግ ያለብን መልካም እሴት ነው፡፡
በሃገራችን ካለፈው አመት ጀምሮ የሰላም መደፍረስ አጋጥሞ እንደነበር ይታወሳል፡፡ ሰላም ያልሰፈነበት ህብረተሰብ፤ ስለ ሁለንተናዊ የሰው ልጅ ብልፅግና፣ ግብረ-ገብነትና መልካም አስተሳሰብ በፅናት የመቆም አቅሙ ይዳከማል። ተያያዥ ውጤቱም ምድራዊና ሰማያዊ ድህነት ይሆናል፡፡
በሃገራችን ህዝቦቿ ምንም አይነት ልዩነት ሳይገድባቸው በጋራ ለሰው ልጆች ክብር፣ ለፍትህ፣ ለእውነት፣ ለነፃነትና ለፍቅር የቆሙ እንዲሆኑ አደራ እንላለን፡፡ በሃገራችን በተከሰተው ሁከትና ጠብ ሰለባ ሆነው ላለፉት ወገኖቻችን ከልብ እናዝናለን፡፡ የጠፋውም የአገር ሃብት የሚያስቆጭና የሚያሳዝን ነው። ለዚሁ ጥፋት ምክንያት የሆኑ ተግባራት ሁሉ ሊወገዙና ሊታረሙ ይገባል፡፡ ለወደፊት ተመሳሳይ ፈተናዎች ቢያጋጥሙን እንኳን ሰላማዊ በሆነ መንገድ፣ በውይይት የመፍታት ልምድ እንድናዳብር ከወዲሁ መሰራት እንዳለበት በታላቅ አፅንኦት አደራ እንላለን፡፡
ልዩነቶችን በሠላማዊ መንገድ በመነጋገር መፍታትም የስልጣኔ ምልክት ነው፡፡ ይህን የሚቃወም ወይም የሚያግድ አካልም መኖር የለበትም፡፡ ልዩነቶች በሰላማዊ መንገድ የማስተናገድ ልምድ እንዲኖረን፣ በት/ቤቶች የግብረገብና ስነምግባር ትምህርት ከመዋዕለ ህፃናት ጀምሮ መሰጠት እንዳለበት እምነታችን ነው፡፡

=================================

‹‹ሰላም የሁላችንንም ስምምነት ትፈልጋለች››

ፓስተር ፃድቁ አብዶ (የኢት/ወ/አ/ክ/ህ/ፕሬዚዳንት)

የሰላም ሕልውና በተለያዩ ምክንያቶች አደጋ ውስጥ ሊወድቅ ይችላል፡፡ በእግዚአብሔር አምሳል በተፈጠሩ ሰዎች መካከል የሚደረግ አድልዎ፣ ወገንተኝነትና ብሔርተኝነት፣ የመልካም አስተዳደር እጦት እንዲሁም የተለያዩ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ መድልዎች የሰላምን እስትንፋስ በአጭሩ ሊቀጩት ይችላሉ፡፡ እንዲህ ዓይነቱ አደጋ በትውልድ ላይ እንዳይወድቅ፣ የአገር መሠረት ከሆነው ቤተሰብ ጀምሮ ሰላምን በማስፈን፣ እውነቶች ላይ መነጋገርና ወደ ማኅበረሰብ ማዝለቅ ከእያንዳንዳችን ይጠበቃል፡፡
እርስ በርስ መከባበርን፣ መደማመጥንና ለሌላው የሚጠቅመውን ማሰብን፤ ይህንንም መልካም እሴት ኅብረተሰቡ በሃይማኖታዊ ግንኙነት፣ በማኅበራዊ ተራክቦውና በፖለቲካ አስተሳሰቡ ተግባራዊ እንዲያደርገው ማስተማርና ደጋግሞ ማስገንዘብ በብርቱ ይጠበቃል፡፡ በተለይ በአሁኑ ወቅት፣ የዓለማችን ሰላም በተለያዩ ምክንያቶች በመደፍረሱ፣ የሰው ልጆች ሕይወት ከመቼውም ጊዜ ይልቅ ስጋት ላይ ወድቋል፡፡ ተፈጥሮ በምታስከትለው ቀውስና የሰው ልጆች በሚፈጥሩት ፀረ ሰላም ድርጊቶች፣ ሕዝቦች ሰላማቸውንና ነፃነታቸውን ተነጥቀው፣ ተንከራታችና ምውት ሆነው መመለከት ሲበዛ ኀዘን ላይ ይጥላል፤ ልብንም ይሰብራል፡፡
መቼም ጦርነትን ለመቀስቀስ ብዙ ልፋት አያስፈልግም፡፡ ጥቂት አሉታዊ ቃል መሰንዘር ይበቃል፡፡ ሰላምን ለማስፈን ግን እንደዚያ አይደለም፤ ብዙ ውይይት፣ ብዙ ትጋትና ብዙ መሥዋዕትነትን የሚጠይቅ ሂደት ነው፡፡ ከዚህም የተነሳ፣ ሰላም በአንድ ወገን መልካም ፈቃድ ብቻ የምትገነባ ሳይሆን የሁላችንንም ስምምነት የምትፈልግ ናት፡፡ ስለሆነም ማናችንም አስቀድመን በሰላም አስፈላጊነት ልናምን፣ አስከትሎም እውነተኛ በሆነ የአመለካከትና የሕይወት ለውጥ እምነታችንን ልንተረጉም ያስፈልጋል፡፡
ሰላም በሰው ልጅ ሕይወት ውስጥ መሠረታዊ ጉዳይ በመሆኑ፣ ክርስቶስ ኢየሱስ ወደ ምድር የመምጣቱ ብሥራት በተነገረ ጊዜ፣ ከመላዕክቱ የምሥጋና ቃል ጋር የተላለፈውና፣ ‹‹ክብር ለእግዚአብሔር በአርያም ይሁን፣ ሰላምም በምድር ለሰውም በጎ ፈቃድ›› የተሰኘው መልዕክት፣ በዓለማችን ላይ የሰላም አስፈላጊነት የቱን ያህል ዋጋ እንዳለው ያመላክተናል፡፡ ስለሆነም የሰላም መልዕክተኞች ተብለን የምንጠራ የሃይማኖት አባቶች፣ በዚህ ዐቢይና ዋነኛ ጉዳይ ላይ አብዝተን እንድንሠራ የሰላም አለቃ ከሆነው ከእግዚአብሔር የተሰጠን ሃላፊነት በመሆኑ፣ ለሰላም መስፈን እንቅፋት የሆነውን ጉድፍ ነቅሰን በማውጣት፣ በሕዝባችን መካከል ፍፁም ሰላም የሚሰፍንበትን ጎዳና ልንተልም፣ ሰላምና እድገት በምድራችን ይሠፍን ዘንድም በተግባርና በጸሎት ሃላፊነታችንን ልንወጣ፣ አብዝተን ሰላምን እንደምንሻ ሁሉ የመጠበቅንም ትጋት አጥብቀን ልንፈልግ የእያንዳንዳችን ሃላፊነት መሆኑን ልንገነዘብ ያስፈልጋል፡፡

=================================

“ዘላቂ ሰላም የሚኖረው ሁሉም ለሰላም ሲሰራ ነው”
ፓስተር ተመስገን ቡልቲ (በሰባተኛው ቀን አድቬንቲስት
ቤ/ክ የኢትዮጵያ ዩኒየን ሚሽን ፕሬዚዳንት)

ፈጣሪ አምላካችን የሰላም አምላክ ነው፡፡ እንደዚሁም የፍትህ አምላክ ነው፡፡ ሰላምና ፍትህ ለአንድ ሀገር እድገትና ልማት ወሳኝ መሆናቸው አያጠያይቅም፡፡ በቅርቡ በሀገራችን ተከስቶ የነበረው የሰላም መደፍረስ አስከትሎት የነበረው አለመረጋጋት፣ የሰላም ዋጋ ምን ያህል ውድ እንደሆነ እንደገና እንድናስታውስ አድርጎናል፡፡ ሰላም ለሁሉም አስፈላጊና ጠቃሚ ቢሆንም ዘላቂ ሰላም ሊኖር የሚችለው፣ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በአንድነት ለሰላም ሲሰሩ ብቻ ነው። ሰላም አንድ አካል ብቻ በተናጠል ሊያስጠብቀው የሚችለው እሴት አይደለም። ይልቁንም ሁሉም አካላት የሚጠበቅባቸውን ድርሻ በትጋት፣ በቅንነትና ሌላውን በመረዳት ሲያበረክቱ ዘላቂ ሰላም ይሰፍናል። ስለዚህ የሀገራችንን ሰላም ዘላቂ በሆነ መልኩ ለማስፈን፣ መንግስትም ሆነ ሌሎች የፖለቲካ ፓርቲዎች እንደዚሁም መላው የሀገራችን ህዝቦች፣ በፍቅርና በመቻቻል፣ ይቅር ተባብለው፣ ወደ ሰላም መድረክ ለመምጣት ዝግጁ መሆናቸው ወሳኝ ነው፡፡
ሰላም የሚወርደው “እኔ ያልኩት ብቻ ይሁን” በማለት እንዳልሆነ፣ ያለፈው ታሪካችን በግልፅ ያሳያል። መቻቻል፣ ተጨማሪ ምዕራፍ መሄድ፣ የመሸነፍ ሳይሆን የበሳልነት፣ የአመራር ብቃት ምልክቶች ናቸው፡፡ ስለዚህ ከመንግስትም ሆነ ከሌሎች የፖለቲካ ፓርቲዎች እንደዚሁም ከመላው የሀገራችን ህዝቦች፣ ይሄ ከመቼውም ጊዜ ይልቅ በአሁኑ ወቅት ይጠበቃል። የአመለካከት ልዩነቶች እንደተጠበቁ ሆነው፣ የጋራ ሀገራችንን ለማሳደግና ለማልማት፣ ሁሉን አቀፍ የሆነ ዲሞክራሲን ለማስፈን፣ በመቀራረብ፣ በልበ ሰፊነትና በይቅርታ መንፈስ፣ ሁሉም ወገኖች ለእርቅና ለሰላም እንዲሰሩ ጥሪ እናቀርባለን፡፡    

===============================


‹‹የችግሮቻችን መፍቻ ያለው በእኛው እጅ ነው››
ቄስ ዋቅስዮም ኢዶሣ (ዶ/ር) (የኢ/ወ/ቤ/ክርስቲያን መካነኢየሱስ ፕሬዚዳንት)


የሰው ልጅ ለዕለት ተእለት ኑሮውና ተግባሩ፣ ለእድገቱና ለደህንነቱ አስተማማኝ ሠላም መኖሩ እጅግ አስፈላጊ እንደሆነ ይታወቃል፡፡ ለግለሰብ፣ ለቤተሰብ፣ ለማህበረሰብ፣ በአጠቃላይ ለህብረተሰብ እንዲሁም ለሃገር እድገትና ብልፅግና ሰላም የሁሉም ነገር መሠረት ነው፡፡ በምንኖርባት ምድር ላይ ለሰላምና ስለ ሰላም ሲባል ትልቅ ዋጋ የሚከፈለው፣ የሰላም መደፍረስ ወይም እጦት የሚፈጥረው ቁስል ጥሎ የሚያልፈው የማይሽር ጠባሳን ለማስቀረት ነው፡፡
ባለፉት ጥቂት ወራት ህዝባችን ለመንግስት ሲያቀርብ ከነበረው የመልካም አስተዳደር ችግር ጋር ተያይዞ በሃገራችን የተለያዩ ቦታዎች የተከሰተው ግጭትና ሁከት ያስከተለው የሰው ልጅ ህይወት ማለፍና የንብረት ጥፋት፣ ምን ያህል የዜጎችን ልብ እንዳሳዘነና እንዳቆሰለ እንዲሁም ምን ያህል የሃገርን ሰላም እንዳወከ በቅርብ የምናስታውሰው ነው፡፡ ሃገራችን ኢትዮጵያ በብዙ አባቶችና እናቶች ያልተቋረጠ ትግልና መስዋዕትነት፣ ሰላሟ ተጠብቆ፣ ከዚህ የደረሰች አኩሪ የሰላም እሴት ያላት ሃገር ነች፡፡ ከእነዚያ አባቶችና እናቶች ጥንካሬና እግዚአብሄርም ከሰጣቸው ስኬት የተነሳ የተረከብናትን ይህቺን ሃገር፣ ለመጭው ትውልድ የማስረከብ ኃላፊነት የተጣለው አሁን ባለን ኢትዮጵያውያን ሁሉ ላይ እንደሆነ ግልፅ ነው፡፡ ይህንን ብርቱ ኃላፊነት ለመወጣት ዛሬም ተቀራርቦ መመካከርና ለጋራ ችግሮቻችን የጋራ መፍትሄ ማፈላለጉ ጊዜ የምንሰጠው ጉዳይ አይደለም፡፡ ሃገሪቱ የእኛ፣ እኛም የእኛ ስለሆንን፣ የራሳችንን ችግር ለመፍታት ከእኛ የተሻለ የምንጠብቀው ሌላ አካል የለም፡፡ የችግሮቻችን መፍቻ ያለው በእኛው በኢትዮጵያውያን እጅ ነው። በተለይም የሃይማኖት መሪዎችም ሆነ ተቋማት ግንባር ቀደም ተግባር ለእርቅና ለሰላም ግንባታ መስራት መሆን ይኖርበታል፡፡
በሁለት ወይም ከዚያ በላይ በሆኑ ግለሰቦች፣ ቤተሰቦች፣ ህዝብና መንግስት መካከል የሃሳብ ልዩነቶች መከሰታቸው የማይቀር ሃቅ ነው። እነዚህን ልዩነቶች የምናስተናግድበትም ሆነ የምንይዝበት መንገድ ግን ሊጠቅመን ወይም ሊጎዳን ይችላል፡፡ ስለዚህ የሃሳብ ልዩነቶችን ይዘን፣ በረጋ መንፈስና በማስተዋል መፍትሄ ካበጀንላቸው፣ ለአብሮነታችን፣ ለሰላማችንና ለእድገታችን መፋጠን ያላቸው ጠቀሜታ ከፍተኛ እንደሚሆን መገመት አያዳግትም።
ለዚህም ስራ ውጤታማነት የሁላችን የሆነችውን የሃገራችንን ሰላም፣ የህዝቦቿን አንድነት ለመጠበቅ፣ አባቶቻችን የተጠቀሙባቸውን የሽምግልና ዘዴዎች መዳሰስና መከተሉ ጠቃሚ ይመስለኛል፡፡ ያለፉ መልካም ምሳሌነት ያላቸው ልምዶቻችን፣ ወደፊት ለምንሰራቸው ስራዎች ኃይል ሆነውን አዲስ ታሪክን ለመስራት የሚቀሰቅሱን መሆን አለባቸው። ስለዚህ አኩሪ ታሪክን ከቀደምት ኢትዮጵያውያን እንደተረከብን ሁሉ፣ የእኛም ልጆች የሚኮሩበትና የሚጠቅሱት መልካም ታሪክ ለመስራት ጊዜው አሁን እንደሆነ አልጠራጠርም፡፡ እኛ በመልካም ነገር ስንነሳ፣ ፍቅር የተሞላው አምላካችን እግዚአብሔር፣ እንደሚረዳንና ስራችንን እንደሚባርክ እርግጠኛ ነኝ።