Administrator

Administrator

      የገጣሚ ዮሐንስ ሞላ ሁለተኛ ስራ የሆነው “የብርሃን ሰበዞች” የግጥም ስብስብ መጽሐፍ ከነገ
በስቲያ በብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ ከምሽቱ 11፡00 ሰዓት ጀምሮ ይመረቃል፡፡በማህበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ ውስጠ ወይራ የሆኑ ከሰባ በላይ ግጥሞችን ያካተተው መጽሐፉ፤ በ110 ገፆች የተቀነበበ ሲሆን ለአገር ውስጥ በ46 ብር፣ ለውጭ አገራት በ18 ዶላር ለገበያ ቀርቧል፡፡ በምረቃ ሥነሥርዓቱ ላይ ከመጽሐፉ የተመረጡ ግጥሞች የሚነበቡ ሲሆን ወጣትና አንጋፋ ገጣሚያንም ግጥሞቻቸውን ለታዳሚው እንደሚያቀርቡ ተገልጿል፡፡ የግጥም መድበሉን ሊትማን መጽሐፍት መደብር ያከፋፍለዋል ተብሏል፡፡
ዮሐንስ ሞ ላ ከ ዚህ ቀ ደም በ 2005 ዓ .ም “የብርሃን ልክፍት” የተሰኘ የግጥም መጽሐፍ ለአንባቢ ማድረሱ የሚታወስ ሲሆን “ጠይም በረንዳ” በተሰኘው የራሱ ጦማር ላይ የተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮችን በመፃፍ ይታወቃል፡፡ ገጣሚውበተጨማሪም የዘፈን ግጥሞችን የሚጽፍ ሲሆን ቀደም ሲ ል በ ግጥም የ ተሳተፈበት የ ፀደንያ ገ / ማርቆስ ዘፈን፤ ሁለት የአገር ውስጥ፣ አንድ አህጉር አቀፍ ሽልማቶችን አሸንፏል፡፡

Saturday, 14 May 2016 13:44

የዘላለም ጥግ

ስለ አመራር)
• ድርጊትህ ሌሎችን የበለጠ እንዲያልሙ፣
የበለጠ እንዲማሩ፣ የበለጠ እንዲሰሩና
የበለጠ እንዲሆኑ ካነቃቃ አንተ መሪ ነህ፡፡
ጆን ኩይንሲ አዳምስ
• መሪ ማለት መንገዱን የሚያውቅ፣ በመንገዱ
የሚጓዝና መንገዱን የሚያሳይ ሰው ነው፡፡
ጆን ሲ.ማክስዌል
• በበግ የሚመራ የአንበሶች ሠራዊት
አያስፈራኝም፤ እኔን የሚያስፈራኝ በአንበሳ
የሚመራ የበጐች ሠራዊት ነው፡፡
ታላቁ እስክንድር
• ብርሃኑን ልታሳያቸው ካልቻልክ፣ ሙቀቱ
እንዲሰማቸው አድርግ፡፡
ሮናልድ ሬገን
• ስህተት ፈላጊ ሳይሆን መፍትሔ (መድሃኒት)
ፈላጊ ሁን፡፡
ሔነሪ ፎርድ
• ሰዎች በመሪና በአለቃ መካከል ያለውን
ልዩነት ይጠይቃሉ፡፡ መሪ ይመራል፤ አለቃ
ይነዳል፡፡
ቴዮዶር ሩዝቬልት
• እሴቶችህ ግልጽ ሲሆኑልህ ውሳኔዎችን
መወሰን ይቀልሃል፡፡
ሮይ ኢ ዲዝኒ
• ራዕይ ከሌለ ተስፋ የለም፡፡
ጆርጅ ዋሺንግተን ካርቨር
• መሪነት፤ ራዕይን ወደ እውነታ የመተርጐም
አቅም ነው፡፡
ዋረን ቤኒስ
• ለውጤት በቅጡ ከተጨነቅህ፣
በእርግጠኝነት ታሳካዋለህ፡፡
ዊሊያም ጄምስ
• ማሰብህ እንደሆነ አይቀርም፤ ስለዚህ ለምን
በትልቁ አታስብም?
ዶናልድ ትረምፕ
• ተነሳሽነት ከሌላቸው፣ መሪዎች በአመራር
ቦታ ላይ የተቀመጡ ተራ ሠራተኞች ናቸው።
ቦ ቤኔት
• የዛሬ አንባቢ፣ የነገ መሪ ይሆናል፡፡
ማርጋሬት ፉለር
• ኦርኬስትራን መምራት የሚሻ ሰው፣
ጀርባውን ለጀማው መስጠት አለበት፡፡
ማክስ ሉቻዶ

“ገዴ” እና “ቢሰጠኝ” በተሰኙ ቀደምት አልበሞቿ ተቀባይነትን ያገኘችው ዝነኛዋ ድምፃዊት ፀደንያ ገ/ማርቆስ፤ “የፍቅር ግርማ” የተሰኘ ሶስተኛ አዲስ አልበሟ ለአድማጭ ቀረበ፡፡ አልበሙ 11 ዘፈኖችን ያካተተ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ አንዱ የተፈራ ደምሴ ግጥም የሆነው “ካምፕፋየር” የተሰኘ የእንግሊዝኛ ሙዚቃ እንደሆነ ድምፃዊቷ ለአዲስ አድማስ ገልፃለች፡፡ የአምስቱን ዘፈኖቿን ግጥም አንጋፋው ገጣሚ ይልማ ገ/አብ፣ አንዱን ገጣሚና ፀሐፌ ተውኔት ጌትነት እንየው፣ ሶስቱን ፋሲል ከበደ የተሰኘ አዲስ ገጣሚ፣አንዱን ደግሞ #ህመሜ” የተሰኘው ነጠላ ዜማዋ ገጣሚ አብዲ ራዋ የሰሩላት ሲሆን ዜማውን በአብዛኛው ራሷ ድምፃዊቷ እንደሰራችና አንዱን ሄኖክ መሀሪ እንደሰራላት ተናግራለች፡፡
“ካምፕፋየር” የተሰኘውን የእንግሊዝኛ ሙዚቃ ቅንብር ኬሊ አለን የሰራላት ሲሆን  የሌሎቹን ቅንብር አቤል ጳውሎስ መስራቱንና አሳትሞ ያከፋፈለው ኤራ ኮሙዩኒኬሽንና ኤቨንት እንደሆነ ድምጻዊቷ ጠቁማለች፡፡  
 ጸደንያ በዘንድሮ ዓመት ብቻ የ“አፍሪካ ሚዩዚክ አዋርድ” (አፍሪማ)፣ የ“ለዛ አድማጮች” እና ለ“ሀሪየት” ፊልም በሰራችው የማጀቢያ ሙዚቃ የ#ጉማ አዋርድ” ሶስት ሽልማቶችን አሸናፊ ለመሆን የበቃች ሲሆን በአገራችን ብቸኛዋ የ“ኮራ አዋርድ” ተሸላሚ እንደሆነችም ይታወቃል፡፡


“ገዴ” እና “ቢሰጠኝ” በተሰኙ ቀደምት አልበሞቿ ተቀባይነትን ያገኘችው ዝነኛዋ ድምፃዊት ፀደንያ ገ/ማርቆስ፤ “የፍቅር ግርማ” የተሰኘ ሶስተኛ አዲስ አልበሟ ለአድማጭ ቀረበ፡፡ አልበሙ 11 ዘፈኖችን ያካተተ ሲሆን ከእነዚህ ውስጥ አንዱ የተፈራ ደምሴ ግጥም የሆነው “ካምፕፋየር” የተሰኘ የእንግሊዝኛ ሙዚቃ እንደሆነ ድምፃዊቷ ለአዲስ አድማስ ገልፃለች፡፡ የአምስቱን ዘፈኖቿን ግጥም አንጋፋው ገጣሚ ይልማ ገ/አብ፣ አንዱን ገጣሚና ፀሐፌ ተውኔት ጌትነት እንየው፣ ሶስቱን ፋሲል ከበደ የተሰኘ አዲስ ገጣሚ፣አንዱን ደግሞ #ህመሜ” የተሰኘው ነጠላ ዜማዋ ገጣሚ አብዲ ራዋ የሰሩላት ሲሆን ዜማውን በአብዛኛው ራሷ ድምፃዊቷ እንደሰራችና አንዱን ሄኖክ መሀሪ እንደሰራላት ተናግራለች፡፡
“ካምፕፋየር” የተሰኘውን የእንግሊዝኛ ሙዚቃ ቅንብር ኬሊ አለን የሰራላት ሲሆን  የሌሎቹን ቅንብር አቤል ጳውሎስ መስራቱንና አሳትሞ ያከፋፈለው ኤራ ኮሙዩኒኬሽንና ኤቨንት እንደሆነ ድምጻዊቷ ጠቁማለች፡፡  
 ጸደንያ በዘንድሮ ዓመት ብቻ የ“አፍሪካ ሚዩዚክ አዋርድ” (አፍሪማ)፣ የ“ለዛ አድማጮች” እና ለ“ሀሪየት” ፊልም በሰራችው የማጀቢያ ሙዚቃ የ#ጉማ አዋርድ” ሶስት ሽልማቶችን አሸናፊ ለመሆን የበቃች ሲሆን በአገራችን ብቸኛዋ የ“ኮራ አዋርድ” ተሸላሚ እንደሆነችም ይታወቃል፡፡


ከ10 ብር እስከ 34 ሺ ብር የተገዙ መጻህፍት ይገኛሉ
በቅርቡ “The Book Cafe” ይከፈታል ተብሏል
ካፌው ሲከፈት በዓመት 3 መጻህፍትን በነጻ ያሳትማል

     በተለምዶ 22 ተብሎ በሚጠራው አካባቢ ልዑል ሲኒማ የሚገኝበት “አናት ህንፃ” ፊት ለፊት አንድ ባርና ሬስቶራንት ያገኛሉ፡፡ ከስሙ ጀምሮ ከለመድናቸው ባርና ሬስቶራንቶች በእጅጉ ይለያል። እግርዎ አንዴ ወደ ውስጥ ከዘለቀ ወደ የትኛውም ክፍል ሲገቡ (መፀዳጃ ቤትና በረንዳውን ጨምሮ) በሚያዩት ነገር ግራ ሊጋቡ አሊያም ሊደመሙና ሊደነቁ ይችላሉ፡፡ ባሩም ሬስቶራንቱም፣ መፀዳጃ ቤቱም፣ በረንዳውም የሚያመሳስላቸው በመጻሕፍት የተከበቡ መሆናቸው ነው፡፡ በዓለም ላይ አሉ የተባሉ ዝነኛ መፅሐፍት እዚህ ይገኛሉ፡፡ ምን መፅሐፍት ብቻ ---- በአገሪቱ ያሉ የህትመት ውጤቶችም አይቀሩም፡፡ ደንበኞች መፅሄትና ጋዜጦችን ከትኩስ ቡና ጋር ያወራርዳሉ፡፡ ንባብ ክፍያ የለውም፡፡  
መፅሐፍቱ አይነታቸው ብዙ ነው፡፡ የርዕዮተ ዓለም ቢሉ፣ የፍልስፍና አሊያም ግለ ታሪኮች፣ የ60ዎቹ ፖለቲካ መጻህፍት፣ የአማርኛ ልብወለዶች፣ የጥናትና ምርምር ሥራዎች --- ብቻ የሚነበብ ሞልቷል፡፡ ይህ በከተማችን ምናልባትም በአራችን ለየት ያለ የመዝናኛም የማንበቢያም ቦታ #ዘ ቡክ” ባርና ሬስቶራንት ይባላል፡፡ ለስጋም ለነፍስም የሚሆን ምግብ የሚገኝበት ሥፍራ በሉት፡፡ እንዲያው ለነገሩ ባለቤቶቹን ምን አሳስቧቸው ይሆን ለደንበኞቻቸው መረጃና ዕውቀት እንዲህ ጭንቅ ጥብብ ያሉት፡፡ ለነገሩ ሌላም ዕቅድ አላቸው፡፡ በቅርቡ “ዘ ቡክ ካፌ” የተባለ ቡና ብቻ እየተጠጣ የሚነበብበት ካፌ እንደሚከፍቱ ለአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ለናፍቆት ዮሴፍ ነግረዋታል፡፡ ይህ ካፌ ሲከፈት ኢትዮጵያ ውስጥ በገንዘብ ማጣት መፅሐፍ ማሳተም ያቃተው ፀሐፊ (ደራሲ) አይኖርም፤ይላሉ የባርና ሬስቶራንቱ ባለቤት አቶ ሀብቶም ገ/ሊባኖስ፡፡ እንዴት? የመጀመሪያ ድግሪያቸውን በማኔጅመንት፣ሁለተኛ ድግሪያቸውን በሂዩማን ሪሶርስ እንዳገኙ ከሚናገሩት አቶ ሀብቶም ገ/ሊባኖስ ጋር ሪፖርተራችን ያደረገችውን አስደማሚ ቃለምልልስ እንዲህ አጠናቅረነዋል፡-  
 “ሰለብሪቲ” የተሰኘውን ባርና ሬስቶራንት እንዴት እንደከፈቱ ቢያጫውቱኝ?
አዎ፤“ሰለብሪቲ” የተከፈተው የኢትዮጵያ አርቲስቶች የሚገናኙበትና ሰብሰብ ብለው የሚጨዋወቱበት ሥፍራ እንዲሆን ታስቦ ነው። ውጤታማ ሆነና ጥሩ ነገር አየን፤ከዚያ ደግሞ “ዘ ቡክ”ን ከፈትን፡፡
“ዘ ቡክ” ባርና ሬስቶራንትን ለመክፈት እንዴት አሰቡ፤ምክንያቱም በአገራችን የተለመደ አይደለም----
እንደሚታወቀው በተለይ የኢትዮጵያ ፀሐፊያንና ደራሲያን በየቦታው ነው ያሉት፤መፅሐፋቸውም ዲስፕሌይ የለውም፡፡ ምናልባት በዓመት አንድ ጊዜ የሚዘጋጅ አውደ ርዕይ ጠብቀው ነው መፅሃፋቸውን የሚያሳዩት፤ስለዚህ አንድ ዲስፕሌይ ማግኘት አለባቸው በሚል ነው የ “ዘ ቡክ”ን ሀሳብ ያመጣነው። ለወንድሞቼ ሳማክራቸው በጣም ደስተኞች ነበሩ። ወንድሞቼ አንድ ሀሳብ ስታቀርቢላቸው፣እንዴት እንደሚያዳብሩት ብታይ ይገርምሻል፡፡ ጎበዞች ናቸው፡፡ አሁን “ዘ ቡክ” ለዚህ በቃ ማለት ነው፡፡
“ዘ ቡክ” የተከፈተው መቼ ነው? ምን ያህል መፅሐፍትን ይዞ ጀመረ? አሁንስ ምን ያህል መፅሐፍት በውስጡ ይገኛሉ?
የተከፈተው ከሶስት ወር በፊት ነው፤ሲከፈት መኖሪያ ቤታችን ውስጥ የነበሩ አንድ ሺህ ሀምሳ (1050) መፅሀፍት አምጥተን ነው የደረደርነው። አሁን ከሁለት ሺህ በላይ አለም ላይ አሉ የተባሉ መፅሐፍትን ይዘናል፡፡ ይህን አላማችንን ያዩ ምሁራን፣ እዚህ ሻይ ቡና ለማለት የሚመጡ ደንበኞች በስጦታ እየሰጡን ቁጥራቸው ከፍ እያለልን ይገኛል። መፅሀፍት እቤትሽ አንብበሽ ስታስቀምጫቸው ጌጥ ብቻ ነው የሚሆኑት፤እንዲህ ዓይነት ቦታ ስታመጫቸው ግን በርካታ ሰው ያያቸዋል፤ብዙ ሰው ቡና ፉት እያለ አንዳንድ ቁም ነገሮችን ጨብጦበት ይወጣል፡፡ የማንበብ ልማድ ይዳብራል፤በርካታ ጠቀሜታ አለው፡፡
 በእርግጥ እናቴ መፅሐፍቱን ከቤታችን ይዤ ስወጣ፣ ቤቱ ጭር አለብኝ ብላ ቅሬታ ተሰምቷት ነበር፡፡ ወይ ተኩልኝ አለበለዚያ መኖሪያዬን እዚህ አድርጉልኝ እስከማለት ደርሳለች፤እስከ 8ኛ ክፍል ተምራለች፤ጥሩ የማንበብ ልምድም አዳብራለች፡፡
ተዘዋውሬ እንዳየሁት ብዙ አይነት መፅሐፍት አሉ፡፡ እንደው በዋጋ ደረጃ ውድ የሚባለው የትኛው መፅሐፍ ነው? እኔ መንገድ ላይ አግኝቼ የገዛሁትን የአቤ ጉበኛ መፅሐፍም እዚህ አይቸዋለሁ ----
በነገራችን ላይ መፅሐፍን በዋጋ መተመን ያስቸግራል፡፡ አንድ መፅሀፍ ይነስም ይብዛም የራሱ የሆነ ፋይዳ ይኖረዋል፡፡ ዋጋው መብዛቱና ማነሱ የመፅሀፉን ይዘት አይወክልም፡፡ የሆነ ሆኖ የአቤ ጉበኛ መፅሐፍ የተፃፈው በእንግሊዝኛ ቢሆን ከ60ዎቹ የፖለቲካ መፅሀፍት ግንባር ቀደም ይሆን ነበር፡፡ በአማርኛ ቋንቋ በመገደቡ ዛሬ መንገድ ላይ አስር ብርና ከዚያ በታች ቢሸጥ አይገርመኝም፡፡ እኛ እዚህ ሼልፍ ውስጥ ስናስቀምጠው ሰው እቤቱ ጥሎት ከነበረ አስታውሶ እንደገና ሌላ ሰው እንዲጠቀምበት ያደርጋል፡፡ አሁን እኛ ጋ የፕሮፌሰር ጆሴፍ ስቲግሊትዝ ከመጀመሪያው እስከ መጨረሻው “Globalization and Its Discontents” እስከሚለው ድረስ አለን፡፡ ይህ ሰው የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ሌክቸረር፣ የዓለም ባንክ ከፍተኛ ኢኮኖሚስት ሆኖ ያገለገለ ነው፡፡ በተለይ የመጨረሻው መፅሐፉ ከኢኮኖሚ አንፃር ኢትዮጵያንና መለስ ዜናዊን አስመልክቶ የሰጠው ትንታኔ በጣም የሚገርም ነው፡፡ የዚህ ምሁር “Free Fail” የተሰኘ መፅሀፍ አለ፤በአንድ ሺህ ሰባት መቶ ዶላር ከለንደን ነው ያስመጣነው፡፡ እዚህ እኛ ባርና ሬስቶራንት ውስጥ ይገኛል፡፡ ትልቁም ዋጋ እስካሁን ይሄ ነው፡፡ በዋጋ ደረጃ ቅድም እንዳልሽው ባለ 10 ብርና ባለ 1700 ዶላር አለ ለማለት ነው፡፡ ይዘታቸው ሲመዘን ግን የ10 ብሩ ከ1700 ዶላሩ የሚተናነስ አይደለም፤ የጊዜና የመገኘት ሁኔታው ልዩነት እንጂ፡፡
በዚህ ባርና ሬስቶራንት ውስጥ የሚገኙ መፅሐፍትን ደንበኞች በምን መልኩ ነው መጠቀም የሚችሉት?
ደንበኞች እዚህ ቡና እየጠጡ የትኛውንም መፅሀፍ፣ ጋዜጣም ሆነ መፅሄት አንብቦ የመመለስ መብት አላቸው፡፡ በሌላ በኩል እዚህ የታሪክ፣ የርዕዮት ዓለም፣ የልቦለድ፣ የጥናት ውጤቶች ወዘተ-- ምንም የሌለ የለም፡፡ አንድ ሰው መጥቶ ይህን መፅሐፍ ለጥናትና ምርምር እፈልገዋለሁ፤በማጣቀሻነት እጠቀመዋለሁ፤ ለአገሪቱ ይበጃል፤የሚል ከመጣ ደግሞ ደግመን የማናገኘው የመጨረሻ ውድ መፅሐፍ እንኳን ቢሆን በውሰት እንሰጣለን፡፡ እዚህ ዲስፕሌይ የሆነው ለጌጥ ሳይሆን ለዚህ ዓይነት ፋይዳ ነው፡፡ የራሴ ኮርነር እንዲኖረኝ ፍቀዱልኝ የሚል ደራሲም ካለ ኮርነር ይሰጠዋል፡፡ በረንዳ ላይ የአዳም ረታ ኮርነር እንዳለ ተመልክተሻል፡፡ ቤቱን እኛ እንክፈተው እንጂ የህዝብ መማሪያ እንዲሆን ነው የምንፈልገው፡፡
አንድ ግለሰብ መፅሐፍ መዋስ ቢፈልግ፣ በምን ዋስትና መዋስ ይችላል?
እንግዲህ እኛ መፅሐፍ አውሱኝ ለሚለው ሁሉ አናውስም፡፡ ለምናውሳቸው ደግሞ መታወቂያ አንጠይቅም፡፡ ደንበኞቻችንን እናውቃለን፤ እንመዝናቸዋለን እናውሳለን፡፡ እስካሁን ወስዶ ያስቀረብን የለም፤ ሲያቆዩ እንኳን ደውለው ፊልድ ወጥቼ ነው፣ እንዲህ ሆኜ ነው ብለው ያሳውቃሉ፡፡
ባርና ሬስቶራንቱን ሲያስጎበኙኝ በቅርቡ ለሚከፈት ቤተ-መፃህፍት የተዘጋጀ ቦታ አሳይተውኛል፡፡ መቼ ነው የሚከፈተው? ያኔ በሬስቶራንቱ ውስጥ ያሉት መጻህፍት ተሰብስበው ቤተ-መፃህፍት ይገባሉ ማለት ነው?
እነዚህ የ “ዘ ቡክ” ባርና ሬስቶራንት ናቸው፤አይነኩም፡፡ ቤተ-መጻህፍቱ በሌሎች በግዢም በስጦታም በሚሰበሰቡ መፅሐፍት ነው የሚሞላው፡፡ የ“ዘ ቡክ ካፌ” ስራ ከላይብረሪው ነው የሚጀምረው፡፡ በረንዳ ላይ አንዱ ዲስፕሌይ በየሶስት ወሩ በአዳዲስ መፅሀፍት ይቀየራሉ፡፡ ሌሎቹ ቋሚ ናቸው፡፡
 ቤቱ ምግብና መጠጥ ይሸጣል፡፡ ንባብና መጠጥ አብረው ይሄዳሉ ብለው ያስባሉ?
ጥሩ ጥያቄ ነው፤ስለተነሳ አመሰግናለሁ፡፡ አብዛኛው ሰው ቡና እየጠጣ ነው የሚያነበው። እኛ  ዋና አላማችን ሰው እየጠጣ ባያነብ እንኳን መፅሐፍቱን አይቷቸው፣ ነገ ቤቱ ሲሄድ ስራ እንዲሰራባቸው እንዲያነባቸው ማስታወሻ መስጠት ነው፡፡ በነገራችን ላይ ቢራም ዋይንም እየተጎነጩ በተመስጦ የሚያነቡ አሉ፡፡
ቤቱም ብዙ ጫጫታና የሚጮህ ሙዚቃ የለበትም፡፡ እዚህም የሚመጡ ደንበኞች በአብዛኛው ከቤቱ ድባብ ጋር አብረው የሚሄዱ ናቸው፡፡ ለምሳሌ ፀሐፊዎች፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎች፣ ምሁራን ---ወዘተ፡፡ መቀመጫውም ድጋፍ ያለው ምቹ ሶፋ ነው፡፡ ብዙዎቹ አንድ ሁለት እያሉ በጥልቀት የሚወያዩ ምሁራን ናቸው፡፡ ቤቱ ሰዎች እንዲሰክሩ የሚጋብዝ ድባብ የለውም፡፡ ሰው ቡና ወይ ሻይ ብቻ እየጠጣ፣ ቀን ብቻ እየተገናኘ መወያየት፣ ማንበብ ሊሰለቸው ይችላል፡፡ ይሄ እንደ አማራጭ ከስራ በኋላ ሰዎች ተሰባስበው ፍሬ ያለው ነገር የሚወያዩበት ነው፡፡
ባር ሁሌ መስከሪያና የፀብ መነሻ መሆኑ ቀርቶ ሰዎች እያረፉ የሚዝናኑበት፣እውቀት የሚገበዩበት የማይሆነው ለምንድን ነው ከሚል እሳቤ ነው ይህን ሁሉ የምንደክመው፤ግን ደስተኞች ነን፤ዓላማችንም ግቡን የሳተ ሆኖ አላገኘነውም፡፡ አንዳንዴ ሰዎቹ እየተጎነጩ የሚያነሷቸው ሀሳቦች የሚገርሙ ናቸው። እዚህ ተዋውቀው ጓደኛ የሆኑ፣ መፅሐፍ እስከ መዋዋስ የደረሱ ሰዎችን ስመለከት ደስታ ይሰማኛል፡፡
 ከዚሁ ከመፅሐፍት ጋር ግንኙነት ያለው አዲስ ስራ እንዳሰባችሁም ሰምቻለሁ፡፡ እስቲ ስለሱ ያጫውቱኝ?
እንደ እግዚአብሔር ፈቃድ በቀጣዮቹ ስድስት ወራት ውስጥ “The Book Cafe” የተሰኘና ቡና እየተጠጣ ብቻ የሚነበብበት ካፌ ለመክፈት ዝግጅት ጨርሰናል፡፡ ይህ ካፌ ሲከፈት ኢትዮጵያ ውስጥ በገንዘብ ማጣት መፅሐፍ ማሳተም ያቃተው ፀሐፊ (ደራሲ) አይኖርም፡፡
ያብራሩልኝ ---- እንዴት ማለት?
በዓመት ሶስት መፅሐፍትን በነፃ ለማሳተም እቅድ ይዘናል፡፡ ካፌው የኢትዮጵያን ቡና ያስተዋውቃል፤ ኢትዮጵያ ውስጥ የተፃፉ መፅሐፍት ማሰባሰብ ላይ ይተጋል፣ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ ለህትመት በቅተው የነበሩ በማንኛውም ጉዳይ ላይ የሚያተኩሩ መፅሐፍት ተለቅመው፣ ታድነው ወደ ካፌው ይገባሉ፡፡ ይሄ ማለት የግል የሆነ ልክ የወመዘክር አይነት ቤት ነው የሚሆነው፡፡ ይሄን በወንድሞቼ በኩል አሳካለሁ፡፡ እኔ ኖርኩም አልኖርኩም እነሱ ያሳኩታል፡፡
ሥራችሁ ከመጻህፍት ከአርቲስቶችና ከኪነጥበብ ጋር ጥብቅ ቁርኝት ያለው ይመስላል፡፡ ከዚህ ቀደም በስራቸው ውጤታማ የሆኑ አርቲስቶችን እንደሸለማችሁና ነገም በዚሁ ሬስቶራንት የትግርኛ ዘፈን ግጥም ደራሲውን ዳዊት ሰለሞንን እንደምትሸልሙ ሰምቻለሁ ----
አዎ ኪነ ጥበቡም አንዱ እሴታችን ነው፡፡ ከዚህ በፊት የሸለምናቸው አሉ፡፡ አሁን የትግርኛ ዘፈን የጀርባ አጥንት የሆነውን ዳዊትን እሁድ ምሽት እንሸልማለን፤ሽልማቱ ሰርፕራይዝ ስለሆነ ዝርዝር ነገር አልናገርም፤ በሰዓቱ ተገኝተሽ መመልከት ትችያለሽ፡፡     



   አንዳንድ ተረት ካልተደጋገመ የሚሰማ የለም፡፡ ይሄንንም በድጋሚ አቅርበነዋል፡፡ ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ትልቅ ዝሆን አንድ ትልቅ ገደል ውስጥ ወድቆ ይሞታል፡፡ ሌሊቱን የተራቡ ጅቦች ወደ ገደሉ አፋፍ መጥተው፣ ዞር ዞር ሲሉ ዝሆን እጅግ አዘቅት በሆነው ገደል ውስጥ ገብቶ መሞቱን አዩ፡፡
ከፊሎቹ ጅቦች፤
“እንዴት ግዙፍና የሰባ ዝሆን ነው?”
ኧረ እንግባና የተራበ አንጀታችንን እናርስ!” አሉ፡፡
አንዳንድ ብልህ ጅቦች ግን፤
“ኧረ ጐበዝ! እጅግ ሩቅ ወደሆነው ወደዚህ ጉድጓድ ገብተን፤ ኋላ ሆዳችን ሲሞላ ተመልሰን ወደ ገደሉ አፋፍ መውጣት የማይሞከር ነገር ነው” አሉ፡፡
ብዙዎቹ ጅቦች፤
“እቺን ዳገት ብላችሁ ታወራላችሁ? ተደጋግፈን ፉት እንላታለን፡፡ ይልቅ በረሃብ ሳንሞት ቶሎ እንወስን”
ጥቂቶቹ ጅቦች፤
“ኧረ ይሄ ገደል የዋዛ አደለም ጐበዝ! አንዴ ከገባን መመለሻም የለን”
ብዙዎቹ ጅቦችም፤
“የምትጨቃጨቁን ከሆነ፤ ያለው መፍትሔ ድምጽ እንስጥና አብላጫውን ድምጽ ያገኘው አሸናፊ ይሁን!”
ይሄው ዋናው የውሳኔ ሃሳብ ሆነና
“ድምፅ ይሰጥ” ተባለ፡፡
ድምጽ ተሰጠ፡፡
“ወደ ገደሉ ገብተን የሞተውን ዝሆን እንብላና ረሃባችንን እንመክት!” ያሉት አሸነፉ፡፡
ጅቦቹ ሁሉ ተንደርድረው፣ ተግተልትለው፣ ወደ ገደሉ ገቡ፡፡
ያን ድልብ ዝሆን ተያያዙት፡፡
ጠገቡ፡፡ ለጥ ብለው ተኙ፡፡ ነጋ፡፡
የተረፈውን ተቀራመቱ፡፡ ቀናት እየገፉ ሲሄዱ የዝሆኑ ስጋ ተመናመነና አለቀ፡፡
ቀና ብለው የገደሉን ጫፍ አዩት፡፡
በጭራሽ የሚሞከር ነገር አይደለም፡፡
“ኧረ እንዴት ነው ይሄን ገደል የምንወጣው?”  አለ አንዱ ጅብ፡፡
ብዙዎቹ ጅቦች፤
“እስቲ ማታውን አድረን እናስብበትና ጠዋት መላ እንመታለን” አሉ፡፡
ነገም መጥቶ አፈጠጠ፡፡ ዘዴ ግን ከቶ አልተገኘም፤ የዝሆኑ አይደለም ስጋው አጥንቱም አልቋል፡፡ ስለዚህ በራሳቸው በጅቦቹም መንደር ረሃብ ገባ፡፡ ረሀብ መጣ፡፡
አንድ ሌሊት ሁሉም ጅቦች ለጥ ብለው ባሉበት፤ አንድ ሁለት ጅቦች ነቁ፡፡
ምክር ጀመሩ፡፡ አንደኛው ጐኑ ላለው፤
“መቼም በረሃብ ከምንሞት እንቅልፍ የወሰደውን አንዱን ጅብ ብንበላ እሰየው ነው፡፡ ምን ይመስልሃል?”
ሁለተኛው፤
“ጐንህ ያለውን ቀስቅሰውና ሃሳቡን አካፍለው” አለው፡፡ ያም እንዳለው አደረገ፡፡
ደሞ ያኛውም ጐኑ ላለው ቀጠለ፡፡ የመጨረሻው፣ ዳር ላይ ያለው፣ እንዳንቀላፋ ተበላ!
ይሄ ሂደት ቀጠለ፡፡ በሚቀጥለው ሌሊት ዳር ላይ ያንቀላፋ ተበላ! እንዲህ እንዲህ እያለ ያ ሁሉ ጅብ ተራ በተራ ተበላ! በመጨረሻ ሁለት ብቻ ቀሩ፡፡ አንዱን በጣም ያንቀላፋ ጅብ፣ ሌት አንደኛው ቅርጭጭ አረገው!
አንድ ብቻውን የቀረውን፤ እንደፈረደበት ረሀብ ራሱ በላው!!
***
እርስ በርስ የመበላላት ባህል የተለመደ ነገር ሆኗል፡፡ ከታሪክ እስከ ዛሬ፡፡ ወይ በፖለቲካ ሽኩቻ፣ ወይ በኢኮኖሚ ድቀት አሳቻ፣ ወይ በባህል ልምሻ ዛቻ፣ ወይ በሶሻል ቀውስ ውድቀት አቻ፤ …አገር መበላላትን መቀበል ከጀመረችና ካመነች ቆይታለች፡፡ አያሌ የፖለቲካ ድርጅቶችን አይታለች፡፡
አስገራሚው ነገራችን፤ ትላንት የተበላውን ዛሬ በቦታው የተቀመጠው ጠንቅቆ ለማስተዋል አለመቻሉ! “የማስጠንቀቂያውን ደወል” እንኳን ሳያይ፣ ያለፈውን መራገምና ራሱን መልዐክ ማድረግ፣ ነው ፈሊጡ፡፡ አልፎም ተፈጥሮዬ ነው እስከማለት ደርሶ ወንበሩን ሙጥኝ ማለቱ፡፡ ቀጥሎም በራሱ ጊዜ “አወዳደቄን አሳምርልኝ!” ሳይል የቀደመው ባለስልጣን በወደቀበት መንገድ መንኮታኮቱ ነው፡፡ ስለ ምን አንዱ ካንዱ አይማርም? አካሄዱንስ ስለ ምን አይለውጥም? ኢ-ፍትሐዊነትን፣ ኢ-ዲሞክራሲያዊነትን፣ ሙስናን እንቋቋማለን ተብሎ በተነገረ ማስትግ፣ እዚያው ጥፋት ውስጥ ተዘፍቆ መገኘት እጅግ አሳዛኝ ብቻ ሳይሆን እጅግ አናዳጅም ነው፡፡ በተለይ ስለመልካም አስተዳደር መበላሸት በሰፊው እየተወራ፣ እዚያው ብልሹነት ማጥ ውስጥ በፊት ለፊት ተውጠው የሚታዩ የበላይ ኃላፊዎች ለሀገርም ለህዝብም ጠንቅ መሆናቸው አያጠያይቅም፡፡ መነሳትም አለባቸው፡፡ ህዝብ በኃላፊነት በሰጣቸው ቦታ ላይ ነውና ምዝበራውን ያካሄዱት፣ በከፍተኛ ደረጃ ነው መጠየቅ ያለባቸው፡፡
“በልቼ ልሙት” የማለት ፈሊጥ፤ ተጠናውቶናል፡፡ የሸጥኩትን፣ የሸቀልኩትን በተለያየ ስም ያስቀመጥኩትን፣ ንብረትና ገንዘብ ብታሰርም እየበላሁ እኖራለሁ የሚለው አስተሳሰብ በሰፊው የተንሰራፋ ይመስላል፡፡ ገንዘብን በሺዎች መቁጠር ከቀረ ሰንብቷል፡፡ ምዝበራውን ለመከላከል የተወሰነ ክልል ባለስልጣናት ላይ ብቻ ማተኮር ሳይሆን ሁሉንም ክልሎች መፈተሽ ተገቢ ነው፡፡ ይሄ ደግሞ ዕቅድና አፈፃፀምን ማስታረቅን የግድ ይላል፡፡ ይህ መደረግ ያለበት ነው!
ባሳለፍነው ሳምንት የነፃ ፕሬስ ቀንን አክብረናል፡፡ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት በዓሉ ሲከበር ትኩረት ይደረግባቸው ያላቸውን የፕሬስ ነፃነት መርሆዎች መከበርንና የሚዲያ ተቋማት ምን ያህል ነፃ ናቸው የሚሉ ጥያቄዎችን፣ ማውጠንጠን እጅግ ተገቢ ነው፡፡ አብሮም የዲሞክራሲያዊና ሰብዓዊ መብቶችን ወቅታዊ ድባብ መፈተሸ ዋና ነገር ነው፡፡ ፈትሾ መቀመጥና የግምገማ ነጥቦችን መደርደር ብቻ ሳይሆን ሁነኛ የእርምት እርምጃ መውሰድ ወሳኝ ነው፡፡ አለበለዚያ ውሃ ቢወቅጡት እንቦጭ ነው የሚሆነው! ተገምግመው እርምጃ ያልተወሰደባቸው ሰዎች አያሌ ናቸው፡፡ አንድም “እሱን ነክተን ማ ይተርፋል” በሚል፤ አንድም “እጅግ ከፍ ያለ ቦታ” በመሆኑ ይዘለላልና ነው፡፡ የመጀመሪያው የሰንሰለት (Network) ጉዳይ ሲሆን፤ ሁለተኛው አንቱ የተባሉ ሰዎች ተጠያቂ ያለመሆናቸው ጉዳይ ነው፡፡ የህግ የበላይነት፣ ከህግ በላይ ያሉ ሰዎች እንደሌሉ የሚያረጋግጥ መርህ ነውና በተግባር መታየት አለበት፡፡ አለበለዚያ ህዝብ፤ “የሰቡት ዋጋቸው ውድ ነው፤ የጉፋያዎቹን ንገሩን” ሲል መኖሩ ነው፡፡

    መነሻውን ከምስራቃዊው የአገሪቴ ክፍል ባደረገውና በቀጣይነት መላውን የአገሪቱን አካባቢዎች ያዳርሳል በተባለው የጎርፍና ሌሎች ቅፅበታዊ የተፈጥሮ አደጋዎች ከ1.5 ሚሊዮን በላይ ኢትዮጵያውያን ተጋላጭ ናቸው ተባለ። በተከሰተው የተፈጥሮ አደጋ እስካን ከ100 በላይ ዜጎች ህይወታቸው አልፏል፡፡
የአማራ ክልል፣ ደቡብ ክልል፣ ኦሮሚያ፣ አፋርና ትግራይ ክልሎች ለአደጋው በከፍተኛ ሁኔታ ተጋላጭ መሆናቸውን ለአዲስ አድማስ የገለፁት የብሔራዊ አደጋ መከላከል ብሔራዊ ኮሚሽን ኮሚሽነር አቶ ምትኩ ካሣ፤ ለአደጋ ተጋላጭ በሆኑ አካባቢዎች ላይ የሚኖሩ ዜጎችን በዘላቂነት ሰላማዊ ወደሆኑ አካባቢዎች ለማዛወር እንቅስቃሴ መጀመሩን ጠቅሰው በአሁኑ ወቅት የጎርፍና የመሬት ናዳ አደጋዎች በደረሱባቸው አካባቢዎች ያሉ ዜጎችን በፕላስቲክ መጠለያ ውስጥ ለማስፈር ርብርብ እየተደረገ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
አደጋው በተከሰተባቸው አካባቢዎች ለሚኖሩ ዜጎች የምግብና ጊዜያዊ የመጠለያ እርዳታዎች እየተደረጉ እንደሆነ የተናገሩት ኮሚሽነሩ፤ ዝናቡ ባለማቋረጡ ምክንያት የእርዳታ አሰጣጡ ላይ ችግር መፈጠሩንና ጎርፍ የተረጂዎችን ምግብና አልባሳት ጠራርጎ እንደወሰደው ጠቁመው ተጎጂዎቹ በሚደረግላቸው እርዳታ መጠቀም እንዳይችሉ አድርጓቸዋል ብለዋል፡፡
የአማራ ክልል ደሴ፣ ወልዲያ፣ ሸዋሮቢት ጣና ዙሪያ፣ በኦሮሚያ ክልል በተለይም ከአዋሽ ተፋሰስ ጋር ያሉ እንደ ዝዋይና መቂ ያሉት አካባቢዎች፣ ከደቡብ ክልል ጎሞጎፋ ዞን፣ ወላይታ ሃዲያ፣ ስልጤ፣ ሲዳማ ዞን፣ ሐዋሳ ዙሪያ፣ ከትግራይ ክልል አላማጣና አካባቢው እንዲሁም ከአፋር ክልል አሚባራ፣ ዱቢቲ፣ አዳይቱና ሚሎ ለአደጋ ተጋላጭ ናቸው ተብለው ከተጠቀሱት አካባቢዎች ውስጥ የሚገኙ ናቸው፡፡
ሰሞኑን በደቡብ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች ላይ በተከሰተው የጎርፍና የመሬት ናዳ እስካሁን 39 የሚሆኑ ሰዎች መሞታቸው የተረጋገጠ ሲሆን በናዳው የተቀበሩ ሰዎችን የማፈላለግ ሂደቱ እንደቀጠለ ታውቋል፡፡ በሥፍራው ከሚገኙ ምንጮች ባገኘነው መረጃ መሰረት፤ በወላይታ ዞን ኪንዶዳ ዲዬ ወረዳ ውስጥ በሚገኙ አራት ቀበሌዎች ሰሞኑን እየጣለ በሚገኘው ከባድ ዝናብና በዚሁ ሳቢያ በተከሰተ የመሬት ናዳ ምክንያት የሰዎች ህይወት የጠፋ ሲሆን ወላይታን ከዳውሮ ዞን የሚያገናኘው መንገድ በጎርፍ ተሰብሯል፡፡ የወላይታ ዞንን ከሲዳሞ ዞን ጋር የሚያገናኘው ትልቅ ድልድይም በብላቴ ወንዝ ተወስዷል፡፡ በአደጋው ከ135 በላይ ቤቶች በጎርፍ በመወሰዳቸው ምክንያት 1385 አባወራዎች ከቀዬአቸው ተፈናቅለዋል፡፡
ኮይሻ ዋሙራ፣ ሞጊሳ፣ ዋሙራ ቦረከሼ ፋታታና ጎጨ በተባሉት ቀበሌዎች ላይ በደረሰው በዚሁ የጎርፍና የመሬት ናዳ አደጋ፤ በናዳው የተቀበሩ ሰዎችን ህይወት ለማትረፍ የአካባቢው ህብረተሰብና የነፍስ አድን ሰራተኞች ቢጣጣሩም መንገዶቹ በጎፍርና በመሬት ናዳው በመዘጋታቸው የነብስ አድን ስራውን አስቸጋሪ እንዳደረገውና ይህም በናዳውና በጎርፍ አደጋው ህይወታቸውን የሚያጡ ሰዎችን ቁጥር ከፍ ሊያደርገው እንደሚችል ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ በአካባቢው ዝናቡ አሁንም ያለማቋረጥ እየዘነበ ሲሆን መሬቱ የንቅናቄና ለየት ያለ ድምፅ የሚያሰማ በመሆኑ አካባቢው በስጋት ውስጥ እንደሚገኝም ከስፍራው ያገኘናቸው ምንጮች ገልፀውልናል፡፡
የደቡብ ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ደሴ ዳልኬ፤ አደጋው የደረሰባቸው ቀበሌዎች በመዘዋወር ተጎጂዎችን ያነጋገሩ ሲሆን በጊዜያዊነት መጠለያ ስለሚያገኙበት ሁኔታና በዘላቂነት ከአካባቢው ርቀው የሚሰፍሩበትን ሁኔታ ለማመቻቸት መንግስት ከፍተኛ ጥረት እንደሚያደርግ ቃል መግባታቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡
በተመሳሳይ ሁኔታ በምስራቃዊው የአገሪቱ ክፍል ከፍተኛ የጎርፍ አደጋ ሥጋት እያንዣበበ ሲሆን ሰሞኑን በጣለው ከፍተኛ ዝናብ ሳቢያ በተከሰተው ጎርፍ፤ ድሬደዋን ከአዲስ አበባ የሚያገናኘው አስፋልት መንገድ መሰንጠቁን ከአካባቢው ያገኘነው መረጃ ያመላክታል፡፡ ኬላ (ገነት መናፈሻ) እየተባለ በሚጠራው አካባቢ ላይ በጎርፍ የተሰነጠቀው አስፋልት መንገድ ለተሽከርካሪዎች ከፍተኛ ችግር እየፈጠረ ሲሆን በ1998 ዓ.ም ከተማዋ ላይ ደርሶ ከነበረው የጎርፍ አደጋ በኋላ የተሰራው የጎርፍ መከላከያም መፍረሱ ታውቋል፡፡ በምሽት ከድሬደዋ የሚመጡና ወደ ድሬደዋ የሚገቡ መኪኖች ልዩ የመብራት ታፔላ አድርገው እንዲንቀሳቀሱ መመሪያ የወጣ ሲሆን መኪኖቹም በዚሁ መንገድ በመንቀሳቀስ ላይ መሆናቸው ለማወቅ ተችሏል፡፡
የድሬደዋ ከተማ ከንቲባ አቶ ኢብራሂም ኡስማን፤ ስፍራው ድረስ በመሄድ ሁኔታውን የተመለከቱ ሲሆን አካባቢው በከፍተኛ ሁኔታ በጎርፍ አደጋ ስጋት ውስጥ መውደቁን ምንጮች አመልክተዋል፡፡
የመንግስት ኮሚኒኬሽን ፅ/ቤት ሚኒስትር አቶ ጌታቸው ረዳ ከትናንት በስቲያ በወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ ድርቅ በተከሰተባቸው አካባቢዎች ላይ ደራሽ የጎርፍ አደጋ እንደሚከሰት አስቀድሞ መተንበዩን ጠቁመው፤ ዝናቡ ቀጣይነት ያለው በመሆኑ ለአደጋዎች መዘጋጀት እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡
እስከ አሁን ድረስ ባለው መረጃ፤ ከአንድ መቶ በላይ ሰዎች በጎርፍ አደጋ ህይወታቸውን ማጣታቸውን ሚኒስትሩ አቶ ጌታቸው ረዳ ተናግረዋል፡፡



      የአሜሪካ የተራድኦ ድርጅት ዩኤስኤአይዲ፣ በኢትዮጵያ በተከሰተው ድርቅ ተጎጂ ለሆኑ ዜጎች 128 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ ተጨማሪ የሰብአዊ እርዳታ ለመስጠት መወሰኑን ከትናንት በስቲያ አስታወቀ፡፡
በዩኤስኤአይዲ የዲሞክራሲ፣ የግጭትና የሰብዓዊ ጉዳዮች ቢሮ ረዳት አስተዳዳሪ ቶማስ ኤህ ስታል፣ ተጨማሪ የሰብዓዊ ድጋፍ እርዳታው ምግብ፣ ንጹህ የመጠጥ ውሃ፣ የስነምግብ አገልግሎቶችና ተንቀሳቃሽ የጤና ቡድኖችን የሚያጠቃልል መሆኑንና ለአርሶ አደሮችም የተለያዩ የእህል ዘሮች እንደሚከፋፈሉ ተናግረዋል፡፡
ተጨማሪ እርዳታው አሜሪካ ድርቁ አስከፊ ሰብዓዊ ቀውስ እንዳያስከትል ለመከላከል ስታደርገው የቆየቺውን ጥረት አጠናክራ ለመቀጠል ያላትን ቁርጠኝነት ያሳያል ያሉት ስታል፣ አሜሪካ ከጥቅምት ወር 2014 አንስቶ፣ ለኢትዮጵያ 705 ሚሊዮን ዶላር የሚደርስ የሰብዓዊ ድጋፍ ማድረጓንም አስታውሰዋል፡፡

       በደቡብ አፍሪካ ምስራቃዊ ኬፕታውን በሚገኘው ሴንት ፍራንሲስ ቤይ የተባለ አካባቢ በንግድ ስራ ላይ ተሰማርቶ የሚኖር አንድ ኢትዮጵያዊ ባለፈው ሳምንት በዘራፊዎች መገደሉንና ይህን ተከትሎ በአካባቢው የሚገኙ የውጭ አገራት ዜጎች መደብሮች በአገሬው በመዘረፍ ላይ እንደሚገኙ ተዘገበ፡፡
ኢዮብ ማዴሞ የተባለው ኢትዮጵያዊ የ27 አመት ወጣት ከ9 ቀናት በፊት ክዋኖምዛሞ በተባለው አካባቢ በሚገኘው መደብሩ ውስጥ እያለ በአንድ ዘራፊ መገደሉን ያስታወሰው ዘገባው፣ ወጣቱን በመግደል የተጠረጠረው ዘራፊ የሌላን ኢትዮጵያዊ መደብር ዘርፎ ካመለጠ በኋላ፣ ባለፈው እሁድ ኢትዮጵያውያን ናቸው በተባሉ የአካባቢው ነዋሪዎች በደረሰበት ድብደባ ህይወቱ ማለፉን ገልጧል፡፡
ይህም በአካባቢው በሚገኙ ደቡብ አፍሪካውያን ላይ ቁጣ መቀስቀሱንና የተደራጁ ዘራፊዎች ሲ ቪስታ በተባለው አካባቢ የሚገኙ የውጭ አገራት ዜጎችን መደብሮች መዝረፍ መጀመራቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ የአካባቢው የፖሊስ ቃል አቀባይም ስምንት ያህል የውጭ አገራት መደብሮች መዘረፋቸውን እንዳረጋገጡ ገልጧል፡፡
ፖሊስ ዝርፊያውን ለማስቆም በአካባቢው መሰማራቱን የጠቆመው ዘገባው፣ በዘረፋው ላይ ተሰማርተዋል በሚል የተጠረጠሩ ሶስት ደቡብ አፍሪካውያንም በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለው ከትናንት በስቲያ በሁማንስ ድሮፕ ፍርድ ቤት መቅረባቸውን አስታውቋል፡፡
በሌላ ዜና ደግሞ የሉዋንግዋ ፍርድ ቤት በህገ ወጥ መንገድ ድንበር ጥሰው ወደ ዛምቢያ ገብተዋል በሚል በተከሰሱ 41 ኢትዮጵያውያን ስደተኞች ላይ ከትናንት በስቲያ በዋለው ችሎት የጥፋተኝነት ውሳኔ ማስተላለፉን ሉሳካ ታይምስ የተባለው የአገሪቱ ድረገጽ ዘግቧል፡፡ በቀረበባቸው ክስ ጥፋተኛ ሆነው የተገኙት ኢትዮጵያውያኑ ስደተኞች፤ የገንዘብ ወይም የሶስት ወራት እስር እንደሚጠብቃቸው የገለጸው ዘገባው፣ ስደተኞች ዕድሜያቸው ከ30 አመት በታች መሆኑን አስታውቋል፡፡ ኢትዮጵያውያኑ ስደተኞች ሉዋንግዋ ተብሎ በሚጠራው የድንበር አካባቢ አቋርጠው ወደ ዚምባቡዌ ሊያመሩ ሲሉ በዛምቢያ ፖሊስና የደህንነት አካላት በቁጥጥር ስር መዋላቸውም ተነግሯል፡፡
ባለፈው ወርም በተመሳሳይ ሁኔታ ይህን ድንበር ለማቋረጥ የሞከሩ 16 ኢትዮጵያውያን ስደተኞች በአገሪቱ የደህንነት ሃይሎች በቁጥጥር ስር እንደዋሉም ዘገባው አስታውሷል፡፡

          በኦሮሚያ ክልል ቦረና ዞን ቡሌ ሆራ ወረዳ ገርባ ከተማ፣ ከሑዳዴ ጾም እና የፋሲካ እርድ ጋር በተያያዘ ከበዓሉ ቀን ጀምሮ ሁከት ተፈጥሮ እንደነበር የተገለጸ ሲኾን፤ በቡድን ተደራጅታችሁ ሁከት ፈጥራችኋል በሚል የታሰሩ ከኻያ ያላነሱ ሰዎችም ፍ/ቤት ቀርበው በነፃ እና በዋስ ተለቀዋል፡፡
በጾም ወቅት የከተማዋ ሉካንዳ ቤቶች እንዳይዘጉ ሲከላከሉ ነበር በተባሉ ግለሰቦች ስጋት ተፈጥሮ መቆየቱን የተናገሩ የከተማዋ ነዋሪዎች፤ በበዓሉ ዕለት በተከፈተ አንድ ሉካንዳ ቤት ደግሞ ሕገ ወጥ እርድ ተካሒዷል በሚል ሁከቱ መቀስቀሱን ጠቁመዋል፡፡
በሁከቱ በሉካንዳው ላይ ጉዳት የደረሰ ሲኾን ባለቤቱን ጨምሮ የከብቱን ቆዳ ገዝቷል የተባለ ነዋሪና ሥጋም ለመሸመት ሞክሯል የተባለ ሌላ ሰው በማዘጋጃ ቤቱ ታስረው መዋላቸው ተገልጧል፡፡
በበዓሉ ማግሥት፣ የሉካንዳው ባለቤት ይቅርታ ጠይቆ የከብቱ ሥጋ ከተወገደ በኋላ ሉካንዳው ሥራውን ቀጥሎ የዋለ ሲኾን፤ ከቀትር በኋላም የከተማው አስተዳደር ሓላፊዎች፣ የሃይማኖት አባቶች እና የሀገር ሽማግሌዎች በተገኙበት በጉዳዩ የምክክር ስብሰባ ተካሒዶ እንደነበር ተጠቅሷል፡፡
ስብሰባው ምሽቱን መጠናቀቁን ተከትሎ ግን፣ ማንነታቸው ያልታወቁ ግለሰቦች የወረዳውን ሊቀ ካህናት እና በከተማው የሚገኘውን የገርባ ደብረ ሰላም ቅድስት ሥላሴ ቤተ ክርስቲያን የሰበካ ጉባኤ አባላት በድንጋይ እሩምታ ሲያሳድዱ፣ መኖርያ ቤቶቻቸውንም እየለዩ በመደብደብ ጉዳት አድርሰዋል፤ ተብሏል፡፡ የከተማዋ ፖሊስ ኹኔታውን ለመቆጣጠር ጥረት እያደረገ በነበረበትም ወቅት፣ ግለሰቦቹ የቤተ ክርስቲያኑን ክልል በመክበባቸውና ደወልም በመሰማቱ ለሁከቱ መባባስ ምክንያት መሆኑ ተገልጿል፡፡
በቀጣዩ ቀን በወረዳው ባለሥልጣናት በተጠራውና የሁከቱን መንሥኤ በመለየት ላይ ያተኮረ ነበር በተባለው ስብሰባ፤ ፖሊስ በቡድን ተደራጅተው ሁከት ፈጥረዋል ያላቸውን ተጨማሪ ሰዎች ማሰሩን ምንጮች ተናግረዋል፡፡ ከበዓሉ ማግሥት ጀምሮ በወረዳዋ ፖሊስ ጣቢያ የታሰሩ ከኻያ የማያንሱ ግለሰቦች ማክሰኞ እና ኃሙስ በቡሌ ሆራ ፍ/ቤት የቀረቡ ሲኾን፤ ፖሊስ እና ዐቃቤ ሕግ በቂ ማስረጃ አላገኘሁባቸውም በማለታቸው በነፃ እና በዋስ መለቀቃቸው ታውቋል፡፡
ሁከቱ የዓመት በዓሉን የሉካንዳ ንግድ መነሻ ያደረገ ይኾናል ብለው እንደሚገምቱ የተናገሩ አንድ የሃይማኖት አባት፤ “ጉዳዩ የሃይማኖት ግጭትም አይደለም፤ የብሔረሰብ ግጭትም አይደለም፤ ችግሩ የተወሰኑ ሰዎች ስሜትና አጀንዳ ነው፤” ብለዋል፡፡
“ሕዝቡ አብሮ የኖረ ነው፤ ነገም አብሮ የሚኖር ነው፤” ያሉት እኚሁ አባት፤ በግለሰብ ደረጃ ያሉ ጠብ አጫሪዎችና በሕዝቡ ወይም በሃይማኖት ተቋማት ሽፋን በመጠቀም የብጥብጥ ሙከራ የሚያደርጉ በየመሥሪያ ቤቱም ኾነ በየሃይማኖት ተቋማት ሊኖሩ እንደሚችሉ ጠቁመው፤ የታሰሩ ሰዎች እንዲፈቱ ከመጠየቅ ጀምሮ የከተማችንን ችግር እኛው በራሳችን ተነጋግረን መፍታት አለብን፤ የሚሉ የተለያዩ የሃይማኖት አባቶችና የሀገር ሽማግሌዎች ግን፣ የማረጋጋት ዓላማ ያላቸውን ስብሰባዎች እንደቀጠሉ መኾናቸውን ተናግረዋል፤ መንሥኤውንና ተጠያቂውን አካል በትክክል ለይቶ መፍትሔ ለመስጠት የሚደረገው ጥረት ባለመቋጨቱም እንዲህ ነው የሚል መረጃ ለመስጠት እንደሚያስቸግር አስታውቀዋል፡፡
የከተማዋን ፖሊስ እና የአስተዳደር ሓላፊዎች በስልክ ለማነጋገር ተደጋጋሚ ጥረት ብናደርግም ጥሪው ስለማይመልስ አስተያየታቸውን ለማካተት አልቻልንም፡፡