Administrator

Administrator

 በሳምንቱ መጀመሪያ በተካሄደው የአሜሪካን ሚዩዚክ አዋርድ፣ አራት ሽልማቶችን ያገኘቺው ታዋቂዋ አሜሪካዊ ድምጻዊት ቴለር ስዊፍት፣ ያገኘቻቸውን ሽልማቶች 23 በማድረስ፣ በሴቶች ዘርፍ አዲስ ክብረወሰን ማስመዝገቧ ተዘግቧል፡፡ባለፈው ማክሰኞ በተካሄደው አመታዊው አሜሪካን ሚዩዚክ አዋርድ ስነስርዓት ላይ የአመቱ ምርጥ አርቲስትን ጨምሮ በአራት ዘርፎች የዋንጫ ተሸላሚ በመሆን ያገኘቻቸውን ሽልማቶች 23 ያደረሰቺው ቴለር ስዊፍት፤ በዊትኒ ሆስተን ተይዞ የነበረውን ክብረወሰን መስበሯን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡ድምጻዊቷ በሎሳንጀለስ የማይክሮሶፍት ቴአትር በተካሄደው የሽልማት ስነስርዓት ላይ ባደረገቺው ንግግር፤ በመጪው ህዳር መጀመሪያ ላይ በሚካሄደው የአሜሪካ የሚድተርም ምርጫ ላይ ዲሞክራቶችን ወክለው ድምጻቸውን እንዲሰጡ ለደጋፊዎቿ ጥሪ አቅርባለች፡፡

   ዱባይ ከቱሪስቶች 29.7 ቢ. ዶላር በማግኘት ቀዳሚ ከተማ ናት


    ለሁለት ተከታታይ አመታት በብዛት በመጎብኘት ከአለማችን ከተሞች ቀዳሚነቱን ይዛ የቀጠለቺው የታይላንድ ርዕሰ መዲና ባንኮክ፣ ዘንድሮም በ20.5 ሚሊዮን አለማቀፍ ቱሪስቶች በመጎብኘት፣ የአንደኛነት ስፍራዋን ማስጠበቋ ተነግሯል፡፡
ማስተርካርድ የተባለው ተቋም ሰሞኑን ያወጣውን የአለማችን የአመቱ ምርጥ የቱሪስት መዳረሻ ከተሞች ሪፖርትን ጠቅሶ ፎርብስ እንደዘገበው፣ ባንኮክ ባለፈው የፈረንጆች አመት 2017 ብቻ በ20.5 ሚሊዮን አለማቀፍ ቱሪስቶች የተጎበኘች ሲሆን ይህ የጎብኝዎቿ ቁጥር በተገባደደው የፈረንጆች አመት 2018 መጨረሻ በ9.06 በመቶ  እድገት ያሳያል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
በመላው አለም የሚገኙ 162 ከተሞችን የአመቱ አለማቀፍ የንግድና የቱሪዝም ጎብኝዎች ፍሰት መሰረት አድርጎ ተቋሙ ባወጣው ሪፖርት፣ ከባንኮክ ቀጥሎ ያለውን የሁለተኛነት ደረጃ የያዘቺው የእንግሊዟ ርዕሰ መዲና ለንደን ስትሆን ከተማዋ በአመቱ በ19.83 ሚሊዮን ሰዎች ተጎብኝታለች፡፡
የፈረንሳይ መዲና ፓሪስ በ17.44 ሚሊዮን አለማቀፍ ጎብኝዎች የሶስተኛነት ደረጃን ስትይዝ፣ ዱባይ በ15.79 ሚሊዮን ጎብኝዎች በአራተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጣለች። ሲንጋፖር በ13.91 ሚሊዮን፣ ኒው ዮርክ በ13.13 ሚሊዮን፣ ኳላላምፑር በ12.58 ሚሊዮን፣ ቶኪዮ በ11.93 ሚሊዮን፣ ኢስታምቡል በ10.7 ሚሊዮን፣ ሴኡል በ9.54 ሚሊዮን ሰዎች በመጎብኘት እንደ ቅደም ተከተላቸው ከአምስተኛ እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ መያዛቸውን ዘገባው አስታውቋል፡፡
በፈረንጆች አመት 2017 ከአለማቀፍ ቱሪስቶች ብዙ ገቢ በማግኘት ከአለማችን ከተሞች ቀዳሚነቱን የያዘቺው ዱባይ መሆኗን የጠቆመው ዘገባው፣ ከተማዋ በአመቱ በድምሩ 29.7 ቢሊዮን ዶላር ማግኘቷን አመልክቷል፡፡ ከአለማቀፍ ቱሪስቶች ብዙ ገቢ በማግኘት ሁለተኛ ደረጃን የያዘቺው የሳኡዲ አረቢያዋ መካ በአመቱ በድምሩ 18.45 ቢሊዮን ዶላር ያገኘች ሲሆን  ለንደን 17.45 ቢሊዮን ዶላር፣ ሲንጋፖር 17.02 ቢሊዮን ዶላር፣ ባንኮክ በ16.36 ቢሊዮን ዶላር በቅደም ተከተላቸው እስከ አምስተኛ ያለውን ደረጃ መያዛቸውንም ዘገባው ገልጧል፡፡

 የ2019 የፈረንጆች አመት የታይም የአለማችን ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝር ይፋ የተደረገ ሲሆን፣ የእንግሊዙ ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ እንደ አምናው ሁሉ ዘንድሮም የአንደኛነት ደረጃን መያዙ ተዘግቧል፡፡
ሌላው የእንግሊዙ ታዋቂ ዩኒቨርሲቲ ካምብሪጅ የአምና ክብሩን በማስጠበቅ የሁለተኛ ደረጃን ሲይዝ፣ የአሜሪካው ስታንፎርድ አምና በነበረበት ሶስተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል፡፡ በአመቱ የአለማችን ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝር ውስጥ ከአራተኛ እስከ ሰባተኛ ያለውን ደረጃ የያዙት የአሜሪካዎቹ ማሳቹሴትስ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ፣ ካሊፎርኒያ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ፣ ሃርቫርድ፣ ፕሪንሲቶንና የል ሲሆኑ፣ ኢምፔሪያል ኮሌጅ ለንደን ስምንተኛ፣ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ቺካጎ አስረኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠዋል፡፡
በአመቱ የአለማችን ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝሩ ውስጥ በርካታ ዩኒቨርሲቲዎችን በማስመዝገብ ቀዳሚነቱን የያዘቺው አሜሪካ ስትሆን፣ በዝርዝሩ ውስጥ 172 የአገሪቱ ዩኒቨርሲቲዎች መካተታቸው ተነግሯል፡፡ ጃፓን 103 ዩኒቨርሲቲዎቿን በዝርዝሩ ውስጥ በማካተት የሁለተኛነት ደረጃን ስትይዝ፣ ቻይና በበኩሏ 72 ዩኒቨርሲቲዎቿን በዝርዝሩ አካትታ ሶስተኛነቱን ይዛለች፡፡

 ባለቤታቸው ጠ/ሚ ናጂብ ራዛቅ የተመሰረቱባቸው ክሶች 25 ደርሰዋል

   
   በስልጣን ዘመናቸው ፈጽመዋቸዋል በተባሉ የገንዘብ ማጭበርበርና በስልጣን የመባለግ ወንጀሎች 25 ክሶች የተመሰረቱባቸው የቀድሞው የማሌዢያ ጠቅላይ ሚኒስትር ናጂብ ራዛቅ ባለቤት ቀዳማዊት እመቤት ሮሳማህ ማንሶር፣ 17 የታክስና ገንዘብ ማጭበርበር ክሶች ተመስርቶባቸዋል፡፡
የቅንጦት ኑሮን በመውደድና በሚሊዮን ዶላሮችን እያወጡ በውድ ጌጣጌጥ በማሸብረቅ የሚታወቁት የቀድሞዋ ቀዳማዊት እመቤት ሮሳማህ ማንሶር፣ ረቡዕ በአገሪቱ የጸረ ሙስና ተቋም ሃላፊዎች በቁጥጥር ስር መዋላቸውንና ከትናንት በስቲያ በኳላላምፑር ፍርድ ቤት መቅረባቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የ66 አመቷ ሮሳማህ ማንሶር ፍርድ ቤት ቀርበው በሰጡት ምላሽ፣የተከሰሱባቸውን ሁሉንም የወንጀል ድርጊቶች አለመፈጸማቸውን ገልጸው፣ ክሶቹን መቃወማቸውንና የዋስ መብታቸው እንዲከበርላቸው መጠየቃቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ ፍርድ ቤቱም በግማሽ ሚሊዮን ዶላር  ዋስትና ከእስር እንዲለቀቁ መፍቀዱን አመልክቷል፡፡
በብዙ ሚሊዮን ዶላሮች የሙስና ቅሌት 21 የወንጀል ክሶች ተመስርቶባቸው የነበሩት የቀድሞው የማሌዢያ ጠቅላይ ሚኒስትር ናጂብ ራዛቅ፤ ባለፈው ሳምንት 556 ሚሊዮን ዶላር የህዝብ ገንዘብ ያለ አግባብ ወደ ግል ካዝናቸው ከማስገባታቸውና በስልጣን ከመባለጋቸው ጋር በተያያዘ፣ አራት አዳዲስ ክሶች እንደተመሰረቱባቸው  ተዘግቧል፡፡  


የመጀመሪያው ባለ 10ጂቢ ራም ሞባይል እየመጣ ነው

   የሞባይል ቴክኖሎጂ እየተራቀቀ መምጣቱን ተከትሎ፣ ፎቶ ለመነሳት ወደ ፎቶ ቤት መሄድ ታሪክ እየሆነ መጥቷል፤ ህጻን አዋቂው ሞባይሉን ወደ ራሱ ደግኖ፣ በሰኮንዶች እድሜ ውስጥ ጥርት ኩልል ያለ የራሱን ፎቶ ማንሳት ጀምሯል፡፡
ጥራት ያላቸው ካሜራዎች በተገጠሙላቸው ሞባይሎች ተጠቅመው፣ ራሳቸውን ፎቶ በማንሳት ወይም ሰልፊ ሱስ የተጠመዱ ሰዎችን ማየት የተለመደ አለማቀፋዊ ክስተት እንደሆነ የዘገበው ቢቢሲ፤ ችግሩ ግን የራሳቸውን  አስገራሚ ፎቶ ለማንሳት ከመጓጓት የተነሳ ለአደጋና ለሞት የሚጋለጡ የሰልፊ ሱሰኞች እየበዙ መምጣታቸውን አመልክቷል፡፡
በጉዳዩ ዙሪያ የተሰራን አንድ አለማቀፍ ጥናት ዋቢ አድርጎ ቢቢሲ ከትናንት በስቲያ እንደዘገበው፣ ባለፉት ስድስት አመታት ብቻ በአለማችን 259 ሰዎች በአደገኛ ሁኔታ ራሳቸውን ፎቶ ለማንሳት ሲሞክሩ ለሞት መዳረጋቸው የተረጋገጠ ሲሆን በዚህ ሰበብ መሞታቸው ሳይታወቅ የቀሩ እጅግ በርካቶች እንደሚኖሩም ይገመታል፡፡
በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ በሰልፊ ምክንያት ለሞት ከተዳረጉት መካከል 72.5 በመቶው ወንዶች እንደሆኑ የጠቆመው ዘገባው፤ አብዛኞቹ ከተራራና ከሰማይ ጠቀስ ህንጻዎች ጫፍ፣ ባህር ውስጥና በፍጥነት በሚበርሩ ተሽከርካሪዎች ላይ ሆነው፣ እንዲሁም ከአደገኛ እንስሳት ጋር ፎቶ ለመነሳት ሲሞክሩ ለሞት የተዳረጉ መሆናቸውን  አመልክቷል፡፡ በአደገኛ ሁኔታ ሰልፊ ለመነሳት ከሚደረግ ሙከራ ጋር በተያያዘ የሚከሰቱ የሞት አደጋዎች ከሚበዙባቸው የአለማችን አገራት መካከል ህንድ፣ ሩስያ፣ አሜሪካና ፓኪስታን እንደሚጠቀሱ የጠቆመው ዘገባው፣ በመሰል ሁኔታ የሚሞቱ ሰዎች ቁጥርም ከአመት ወደ አመት በከፍተኛ ሁኔታ ማደጉንም ገልጧል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ፣ ቴና የተባለው የቻይና ታዋቂ የሞባይል ስልኮች አምራች ኩባንያ፣ ኦፖ ፋይንድ ኤክስ የተሰኘውንና በአለማችን የመጀመሪያውን ባለ 10ጂቢ ራም የሞባይል ስልክ አምርቶ ለገበያ ለማቅረብ እየተዘጋጀ መሆኑን ዘ ቨርጅ የቴክኖሎጂ ድረገጽ ዘግቧል፡፡ በአለማችን የሞባይል ስልኮች ኢንዱስትሪ ውስጥ እስካሁን ድረስ ከፍተኛ ራም ወይም ውስጣዊ የመረጃ መያዝ አቅም ተብሎ ሲጠቀስ የነበረው 8 ጊጋ ባይት ራም እንደነበረ ያስታወሰው ዘገባው፤ ኦፖ ፋይድ ኤክስ የተባለው አዲሱ ሞባይል ግን ባለ ሁለት ዲጂት ጊጋ ባይት የመረጃ መያዝ አቅም ተጎናጽፎ በመምጣት በታሪክ የመጀመሪያው ሞባይል ይሆናል መባሉን ገልጧል፡፡
አዲሱ ሞባይል ከአንዳንድ መካከለኛ ዋጋ የሚያወጡ ላፕቶፖች የበለጠ መረጃ የመያዝ አቅምና ፍጥነት እንዳለውም ተነግሯል፡፡ ኦፖ ፋይድ ኤክስ ከዚህ በተጨማሪም ለአስራ አምስት ደቂቃዎች ያህል ብቻ ቻርጅ ተደርጎ ግማሽ ያህል ባትሪው የሚሞላ መሆኑና ካሜራዎቹም ከፍተኛ ጥራት ያላቸውን ምስሎችና ቪዲዮዎች የመቅረጽ ብቃት ያላቸው መሆናቸው ሞባይሉን በገበያ ዘንድ ተመራጭ ያደርገዋል ተብሎ እንደሚጠበቅ የጠቆመው ዘገባው፣ ያም ሆኖ ግን ስልኩ ተመርቶ በገበያ ላይ የሚውልበትን ትክክለኛ ወቅት በተመለከተ በይፋ የተባለ ነገር አለመኖሩን ገልጧል፡፡

 በስዊዘርላንዳዊው ሳይንቲስት አልፍሬድ ኖቤል መታሰቢያነት በተለያዩ ዘርፎች በየአመቱ ሽልማት የሚሰጠውና መቀመጫውን በስዊዘርላንድ ያደረገው የኖቤል የሽልማት ተቋም፣ የ2018  የኖቤል ተሸላሚዎችን ዝርዝር በሳምንቱ መጀመሪያ ይፋ ማድረግ ጀምሯል፡፡
ተቋሙ ባለፈው ሰኞ የአመቱን የኖቤል የህክምና ዘርፍ ተሸላሚዎች ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ በካንሰር ህክምና ዘርፍ የላቀ ፈጠራ ያበረከቱት ጄምስ ፒ አሊሰንና ታሳኩ ሆንጆ የተባሉ የዘርፉ ዝነኛ ሳይንቲስቶች ሽልማቱን እንደተጋሩት ታውቋል፡፡
ማክሰኞ ዕለት ይፋ የተደረገው የፊዚክስ ዘርፍ የኖቤል ተሸላሚዎች መረጃ ደግሞ፣ በመስኩ አዲስና ፈር-ቀዳጅ የፈጠራ ውጤት ያበረከቱት አሜሪካዊቷ አርተር አሽኪን፣ ፈረንሳዊው ጄራርድ ሞሩ እና ካናዳዊቷ ዶና ስቲክላንድ በጋራ አሸናፊ መሆናቸውን አመልክቷል፡፡
ካናዳዊቷ ዶና ስቲክላንድ፣ የኖቤል የፊዚክስ ሽልማትን ከ55 አመታት በኋላ ያገኙ የመጀመሪያዋ ሴት ሳይንቲስት ሲሆኑ፣ ሌላኛው የዘርፉ ተሸላሚ የ96 አመቱ አሜሪካዊ አርተር አሽኪን ደግሞ በኖቤል ሽልማት ታሪክ እጅግ ካረጁ በኋላ የተሸለሙ የመጀመሪያው የእድሜ ባለጸጋ ናቸው ተብሏል፡፡
 ተቋሙ ባለፈው ረቡዕ ከስቶክሆልም ይፋ ባደረገው መረጃ፣ አሜሪካዊቷ ፕሮፌሰር ፍራንሲስ ኤች አርኖልድ፣ ከሌላኛው የአገሯ ልጅ ጆርጅ ፒ ስሚዝና እንግሊዛዊው ግሪጎሪ ፒ ዊንተር፣ በጋራ በኬሚስትሪ ዘርፍ የአመቱ የኖቤል ተሸላሚ መሆናቸውን አስታውቋል፡፡
በካሊፎርኒያ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ የኬሚካል ምህንድስና መምህር የሆኑት ፕሮፌሰር ፍራንሲስ ኤች አርኖልድ፣ በኖቤል ሽልማት ያለፉት 117 አመታት ታሪክ፣ በኬሚስትሪ ዘርፍ ተሸላሚ የሆኑ አምስተኛዋ ሴት መሆናቸው ተነግሯል፡፡
ብዙዎች በጉጉት ሲጠብቁት በነበረውና ትናንት ይፋ የተደረገው የዘንድሮው የኖቤል የሰላም ሽልማት ዘርፍ ውጤት ደግሞ፣  ጾታዊ ጥቃትን እንደ ጦር መሳሪያ መጠቀምን ለማሰቀረት ውጤታማ ስራ ያከናወኑት ኮንጓዊው ዴኒስ ሙክዌጌ እና በአሸባሪው ቡድን አይሲስ ለወሲብ ባርነት ተዳርጋ የነበረቺው ኢራቃዊቷ ናዲያ ሙራድ ተሸላሚ መሆናቸውን አረጋግጧል፡፡
የዘንድሮው የኖቤል የኢኮኖሚ ዘርፍ ተሸላሚዎች ከነገ በስቲያ ይፋ እንደሚደረጉ የሚጠበቅ ሲሆን፣ የኖቤል የሽልማት ተቋም ዘንድሮ በስነጽሁፍ ዘርፍ እንደማይሸልም አስታውቋል፡፡
የኖቤል የሽልማት ተቋም ከተመሰረተበት እ.ኤ.አ ከ1901 አንስቶ 585 ሽልማቶችን ለ896 ግለሰቦችና 27 ተቋማት የሰጠ ሲሆን፣ በተለያዩ ዘርፎች እስካሁን 49 ሴቶች መሸለማቸው ተነግሯል፡፡ በለጋ እድሜ የኖቤል ሽልማትን በመሸለም ቀዳሚነቱን ይዛ የምትገኘው በ2014 ላይ በ17 አመት ዕድሜዋ፣የኖቤል የሰላም ሽልማትን ያገኘቺው ማላላ ዩሱፋዚ ናት፡፡

 በ”ጉዞ ሚዲያና ማስታወቂያ” በየወሩ የሚዘጋጀው “ብራና ጃዝ” የኪነ ጥበብ ምሽት የፊታችን ረቡዕ ከምሽቱ 12 ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ ቴአትር ይካሄዳል፡፡ በዚህ የመጀመሪያ ምሽት፣ ኢትዮጵያዊ አንድነትን የሚያፀኑ ልዩ ልዩ ጥበባዊ ክዋኔዎች እንደሚቀርቡ የተገለጸ ሲሆን አንጋፋው ገጣሚ ነቢይ መኮንን፣ አስቴር በዳኔ፣ ሰለሞን ሳህለና ትዕግሥት ማሞ በመሶብ ባህላዊ ባንድ ታጅበው ግጥሞቻቸውን ያነባሉ ተብሏል፡፡
በተጨማሪም ጋዜጠኛና አክቲቪስት እስክንድር ነጋና የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፍልስፍና መምህሩ  ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ ዲስኩር የሚያቀርቡ ሲሆን በአንጋፋው አርቲስት ተስፋዬ ገ/ሃና አጭር ተውኔት፣ በወጣቷ ፀሐፊ ፅጌረዳ ጎንፋ ደግሞ  ወግ እንደሚቀርብ አዘጋጆቹ አስታውቀዋል፡፡   


አዲስ አበባ፤ አዲስ አስተዳደር ካገኘች ሁለት ወር አስቆጠረች፡፡ በፌደራል ደረጃ እየተካሄደ ከሚገኙት ለውጦች አንፃር በከተማችን አዲስ ለውጦችን ብንጠብቅ አይፈረድብንም፡፡ ለዛሬ ብዕሬን ያነሳሁት፣ አዲሱ አስተዳደር በሁለት ወራት ጊዜ ውስጥ ያከናወናቸውን ተግባራት ለመገምገም ሳይሆን የኛን የከተማዋን ዜጐች ምኞት፣ተስፋና ሥጋት በመግለጽ፣ አዲሱ አስተዳደሩ ትኩረት ሊያተኩርባቸው ይገባል የምላቸውን አንዳንድ ሃሳቦች ለመሰንዘር ነው፡፡
1ኛ) አገልግሎት አሰጣጥን ማዘመንና ቀልጣፋ ማድረግ፤
አገልግሎት ሲባል በጣም በርካታ ጉዳዮች እንደ ጤና፣ ትምህርት፣ ትራንስፖርት፣ ግብር አሰባሰብ ያሉትን እጅግ ሰፊና ውስብስብ ጉዳዮች የሚያካትት ነው፤ በየራሳቸዉ ርዕስ ሆነው፣ ብዙ ሊፃፍባቸው የሚችሉም ናቸው፡፡ የዛሬው ትኩረቴ በተመረጡ የማዘጋጃ ቤት አገልግሎቶች ላይ ነው፡፡ ከአካባቢ ውበትና ፅዳት ስንነሳ፣ አዲስ አበባን የፌደራል መንግስት መቀመጫ፣ የኢትዮጵያ ተምሳሌት ፣የአፍሪካ መዲና ወዘተ…እያልን  እናሞካሻታለን፡፡ እውነታው  ግን አዲስ አበባ በማንኛውም መመዘኛ፣ ሊጠቀሱ ከሚችሉ የአፍሪካ ከተሞች ባነሰ ደረጃ ላይ መገኘቷ ነው። ለስብሰባ ወይም እግር ጥሎት አዲስ አበባ የተገኘን የውጪ ዜጋ - አውሮፓዊ ወይም አሜሪካዊ፣ አይደለም አፍሪካዊ፣ አንድ ተጨማሪ ቀን ለማቆየት የሚያበቃ ሰው ሰራሽ ሆነ ተፈጥሮአዊ መስህብ አላደራጀችም፡፡ አዲስ አበባ አሁንም ድረስ ሰዎችና እንስሳት አብረው የሚኖሩባት ትልቅ መንደር ነች የሚሏት አሉ፡፡ እውነት ነዉ፣  በአዲስ አበባ አውራ ጎዳናዎችና አደባባዮች የቀንድ ከብቶች፣ አህዮች፣ በጎችና ባለቤት አልባ ውሾች ሲተረማመሱ መመልከት በጣም የተለመደ ነዉ፡፡ ይህ ሁኔታ የከተማዋን የገፅታ ግንባታ  ጥላሸት የሚቀባ ብቻ ሳይሆን የትራፊክ ፍሰቱን በእጅጉ የሚያስተጓጉል፣ የከተማዋን የፅዳት ሁኔታ የሚያበላሽ እንዲሁም መንገዶችንና ያሉትን ጥቂት አረንጓዴ ቦታዎች የሚያጎሳቁሉ መሆኑን መረዳት አዳጋች አይደለም።
እውን ይህን ይህን ሁኔታ መለወጥ የማይቻል ሆኖ ነው ወይስ በተለመደው ቸልተኝነታችን ተላምደው ነዉ? ዛሬ ዛሬ የገጠሩ ሕዝባችን እንኳን ቤት ሲሰራ የሰዎችንና የእንስሳቱን ለይቶ ነው፡፡ እነዚህ ነገሮች አያስፈልጉንም  እያልኩ አይደለም፤ ወይም በከብት እርባታና ንግድ ኑሯቸዉን የሚገፉ ዜጎች መኖራቸው ተዘንግቶኝም አይደለም፡፡ እያልኩ ያለሁት ለምን በተሻለ መንገድ አናካሂደውም ነዉ? አዲሱ የከተማው አስተዳደር  ይህንን ሁኔታ ለመለወጥ ተግቶ መስራት ይኖርበታል  ብዬ አስባለሁ፡፡  አዲስ አበባ የዘመናዊነት መስታወት እንጂ የእንስሳት መራኮቻ መሆኗ ማብቃት አለበት፡፡
የማዘጋጃ ቤት አገልግሎትን ከማዘመንና ቀልጣፋ ከማድረግ ጋር ተያይዞ መጠቀስ የሚገባቸው ሌሎች በርካታ ጉዳዮችም አሉ። በተለይ የስራ ቅልጥፍናን ከመፍጠርና ተጠያቂነትን ከማስፈን አኳያ፣ ልዩ ትኩረት ሊሰጠው የሚገባው፣ ለአገልግሎቶች ዝቅተኛውን ደረጃ መወሰንና ተግባራዊ የማድረግ ጉዳይ ነው። ለምሳሌ የህዝብ ማመላለሻ አገልግሎቶች ላይ የተሰማሩ ሁሉ ሊያሟሏቸዉ የሚገቡ መሰረታዊ ደረጃዎች ተለይተው ሊነገሯቸው ይገባል፡፡ ብዙዎች የትራንስፖርት አገልግሎት መስጠት ላይ የተሰማሩ ተሽከርካሪዎች፤ ንፅህናቸው በእጅጉ የተጓደለ፣ የተጎሳቆሉና ጥገና ስለማይደረግላቸው፣ በሚያወጡት ጭስ፣ የከተማዋን የአየር ብክለት በማባባስ ላይ ናቸው። አብዛኛዎቹ የከተማዋ ህንፃዎች፤ አካል ጉዳቶችን ታሳቢ አለማድረጋቸው ብቻ ሳይሆን የአደጋ ጊዜ መውጫ የሌላቸው ናቸው።
የህንፃው ተጠቃሚዎች እንኳ መኪኖቻቸውን የሚያቆሙበት ቦታ ስለማያዘጋጁም፣ መንገዶች ሁሉ ወደ መኪና ማቆሚያነት እየተቀየሩ ናቸዉ። የከተማ  መንገዶች  አሰራርና አስተዳደርም እንደዚሁ የተዘበራረቀና ለተጠቃሚዎች የማይመች ናቸው። እኛ ደሃ አገር ነን፤ እየሰራን እያፈረስን ልንቀጥል አንችልም፡፡ ሐብታችንን መቆጠብና በጥንቃቄ  መጠቀም አለብን፤ ይህ ደግሞ በዘመቻ ሳይሆን አቅዶ መስራትን የግድ ይላል፡፡ ከተማዋ የአጭር የመካከለኛና የረጅም ጊዜ ዕቅድ ሊኖራት ይገባል፡፡
የውሃ አቅርቦት ሌላዉ የአገልግሎት አይነት ነው:: በአለም ዙሪያ ያሉ በርካታ ከተሞች ለመጠጥና ለሌላ ስራ (ለፋብሪካ፣ ለማጠቢያ፣ ለአትክልት) የሚውለውን ውሃ ለይተው ያቀርባሉ:: ይህም ብቻ ሣይሆን የአንድን ግለሰብ (ቤተሰብ) ዝቅተኛውንና ከፍተኛውን የፍጆታ መጠን ይወስናሉ፡፡ ይህን የሚያደርጉት የውሃ ሃብትን በአግባቡ አለመጠቀምና ስርጭቱንም ፍትሃዊ ለማድረግ ነው፡፡ አዲስ አበባ ውስጥ እንደምናውቀው፣ 24 ሰዓት ያልተቋረጠ ውሃ የሚያገኙ አካባቢዎች አሉ፤ በተቃራኒው  አንድ ወርና ከዚያም በላይ ለሆነ ጊዜ፣ እጅግ መሰረታዊ የሆነው የውሃ አቅርቦት የሚነፈጋቸው አካባቢዎችም  አሉ፡፡ ይህ በአጭር ጊዜ ባይሆን በመካከለኛ ጊዜ እንዲሻሻል መስተዳደሩ ተግቶ ሊሰራ ይገባዋል፤ በሌላ በሌላው ብንለያይ በውሃማ ሊሆን አይገባም፡፡
2ኛ) የአካባቢ ፅዳትና ውበትን ማሻሻል፤
የአዲስ አበባ የጽዳት ጉድለት ብዙ ተነግሮለታል። ለችግሩ መባባስ መስተዳደሩም ነዋሪውም አስተዋፅኦ አደርገዋል፡፡ ከተማና ከተሜነት የራሳቸው የሆነ መለያ ባህሪያት አሏቸው። እንደ ድፍረት እንዳይቆጠርብን እንጂ፣ አንዳንድ የአዲስ አበባ ነዋሪ ከተሜነት ይጎድለዋል፡፡ አዲስ አበባ እኮ ሥልጡን ነን ባዮች (ዘመናዊ መኪና የሚያሽከረክሩት ሳይቀር)፣ የበሉትን የሙዝና ብርቱካን ልጣጭ እንዲሁም  የተገለገሉበትን ዕቃ በየጎዳናው የሚጥሉ፤ ዘመናዊ  መኖሪያ ቤት ውስጥ እየኖሩ የራሳቸውን ቆሻሻ ከግቢያቸው አስወጥተው መንገድ ላይ የሚደፉ፣ ይባስ  ብሎም በየመንገዱና አጥር ስር  የሚፀዳዱ ሰዎች--የሞሉባት ከተማ ነች፡፡ ታዲያ እኛ  አዲስ አበቤዎች፣ ከተሜነት አይጎድለንም ትላላችሁ? በዓመት በዓል ሰሞን የሚታየውን በየመንገዱ የተዝረከረከ የእርድ ተረፈ ምርት ለተመለከተ፣ ለከተማው መቆሸሽና መጎሳቆል ዋናው ተጠያቂ፣ ነዋሪው መሆኑን አይጠራጠርም፡፡ እንዲያም ሆኖ የከተማው አስተዳደር፣ ተግባሩን በትክክል እየተወጣ ነው ማለት አይደለም፡፡ የህዝብ መጸዳጃ ቦታዎች፣ ሕዝብ በሚበዛባቸውና አማካይ በሆኑ ቦታዎች፣ በበቂ መጠን መገኘት ሲኖርባቸው፣ በፍለጋ እንኳን የማይገኙ ናቸው። ጥቂቶቹም አገልግሎት ከሚሰጡበት የሚዘጉበት ጊዜ ይበልጣል፡፡ የትራፊክ ፍሰት በሚበዛባቸው አካባቢዎች፣ ቀላልና ደረቅ ቆሻሻ የሚጠራቀሙባቸው ቅርጫቶች (በአንዳንድ ድርጅቶች ተነሳሽነት የተቀመጡት ቅርጫቶች፣ በወሮበሎችና ራስ ወዳዶች እየተነቀሉ መወሰዳቸው ወይም አገልግሎት እንዳይሰጡ መደረጋቸው እንደተጠበቀ ሆኖ)፣ በአግባቡ ተደራጅተው አይገኙም፡፡
የሕንፃና የመንገድ ግንባታ፣ አስገዳጅ ደረጃዎች እንዳሉ ሲነገር እንሰማለን፡፡ ግን ምን ያህል ተፈፃሚ ሆነዋል? ያልተተገበረ ደንብና መመሪያ ሳይኖር  አይቀርም፡፡ ከቶ ስለ ምን የምንናገረውን ፈፅመን ለመገኘት እንቸገራለን?  መጀመር እንጂ መጨረስ ዳገት እንደሆነብን ሊቀር  ነው ማለት ነው?  መስተዳደሩ፣ እነዚህን ሕፀፆች ከማስወገድ ባለፈ፣ የከተሜነት ባህልና እሴቶች እንዲስፋፉ ከመገናኛ ብዙሃንና መንግስታዊ ካልሆኑ ድርጅቶች ጋር በመቀናጀት፣ የተጠናከረ የትምህርት ፕሮግራም ቀርፆ ሊተገብር ይገባዋል። በቀጣይ ግን አስገዳጅ ደንብና መመሪያዎችን ማውጣትና ተግባራዊ ማድረግ አለበት፡፡ አካባቢን የማስዋብና አረንጓዴ የማድረግ ስራ ሌላው ሊታሰብበት የሚገባ ጉዳይ ነዉ፡፡ አሁን ያለው የከተማ መስፋፋት ምጣኔ፣ በዚህ ከቀጠለ ከተማዋ ሩቅ በማይባል ጊዜ፣ ለከፋ የአየር ብክለት እንደምትጋለጥና የሙቀት መጠኑም በእጅጉ እንደሚጨምር አንዳንድ ጥናቶች ይጠቁማሉ፡፡ በአንዳንድ ክፍለ ከተሞች፣ እዚህም እዚያም የተወሰኑ ጥረቶች ቢደገረጉም ያልተደራጁ፣ ደረጃቸውን ያልጠበቁና ቀጣይነት የሌላቸው ናቸዉ። በነገራችን ላይ እንደ  አንድ ግብር ከፋይና ሃላፊነት እንደሚሰማው ዜጋ፣ በጣም ከሚያስቆጩኝ ነገሮች አንዱ፣ ምን እየሰሩ እንደሆነ እንኳ በውል የማይታወቁ የመንግስት ተቋማትን ለማስቀጠል የሚወጣው ገንዘብ ነው፡፡ የዚህ ዓይነት የመንግስት ተቋማት፣ በርካታ ሲሆኑ የደንብ ማስከበር አገልግሎትና የውበትና መናፈሻ ኤጀንሲ በምሳሌነት  ሊጠቀሱ ይችላሉ። የባህልና ቱሪዝም ቢሮ እንዲሁም የአካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣንን፣ ከዚሁ ጎራ ልትመድቧቸዉ ትችላላችሁ። እባካችሁ፤ በየወሩ ስለምትሰበስቡት ደሞዛችሁ ስትሉ ሥራችሁን በአግባቡ ስሩ፡፡
3ኛ) በመሰረተ ልማት አቅራቢ ተቋማት መካከል ቅንጅታዊ አሰራርን ማረጋገጥ፤
ለአዲስ አበባ መንገዶች መጎሳቆል፣ ለከተማዋ ውበት ማጣትና ለነዋሪዎች መጉላላት ዋነኛ ተጠያቂ ማን ነዉ? ብትሉኝ፣ ከሶስቱ ድርጅቶች ማለትም፡- ከመብራት ኃይል፣ ቴሌኮሚኒኬሽንና ውሃና ፍሳሽ አልወርድም። እርግጥ ነው የእነዚህ ድርጅቶች አገልግሎት በእጅጉ ያስፈልገናል፡፡ ያለ እነርሱ ከተማንና ዘመናዊ አኗኗርን መመኘት አይታሰብም፡፡ ግን አንዱ የገነባውን ሌላው እያፈረሰ የሚቀጥለው እስከ መቼ ነው? ስለ ምን እነዚህ ድርጅቶች አቅደውና ተቀናጅተው መስራት አቃታቸው? እውነት ይህን ያህል ሀብታም ነን ማለት ነዉ? ለጥገና ወይም ለማስፋፋት መንገድ መቁረጥ ግድ ሊሆን ይችላል፤ ግን የፈረሰውን ወደነበረበት መመለስ ለምን አይቻልም? ተጠያቂነትን ማረጋገጥ ያለበትስ ማነው? ይህ መስተዳደር ለዚህ ችግር ዘላቂ መፍትሄ መፈለግ አለበት ብዬ አምናለሁ፤ እየሰሩ ማፍረስ መቆም አለበት፡፡ ከዚህ ጋር በተገናኘ መታየት ያለበት የመንገዶች አገልግሎት ጉዳይ ነዉ። ለእግረኛ ወይም ለመኪና የተዘጋጁ መንገዶች ከታሰቡላቸው አላማ ዉጪ ለጎዳና ላይ ንግድ፣ ለግንባታ እቃዎች ማከማቻ፣ ለካፌ፣ ለወርክሾፕ አገልግሎት ሲውሉ ማየት የተለመደ ነወ፡፡ ይህን ጉዳይ ማንሳት አንዳንዶች እንደሚያስቡት ምቀኝነት አይደለም፡፡ ሰዎች ሰርተው ኑሮአቸውን ማሻሻላቸው፣ አለፍ ሲልም በግብር መልክ ለአገር አስተዋጽኦ ማድረጋቸዉ የሚበረታታ ጉዳይ ሆኖ፤ ሲሰሩም ሆነ ሲያተርፉ የሌሎችን ምቾትና ደህንነት በመጋፋት፣ የከተማውን ገፅታ በማበላሸት፤ ሱቅ ከፍተው፣ ሰራተኛ ቀጥረው፣ ቤት ተከራይተው በሚሰሩት ኪሣራ መሆን የለበትም፡፡ ደንብ አስከባሪው  ተቋም ሊሠራ የሚገባው ትልቅ ተግባር ይህ ነበር። አዲሱ ከንቲባ እየሰሩ ያልሆኑ ተቋማትን መፈተሽ ሳይኖርባቸዉ አይቀርም፤ ተጠያቂነት የሚባል ነገር የለማ - በሁለቱም ወገን።
4ኛ) ከተማዋን ከማናቸውም የድምጽ ብክለት በህግ መከላከል፤
ኢትዮጵያ የእምነት አገር ነች፤ በየምክንያቱ ወደ እምነት ተቋማት የሚተመውን ሕዝብ ብዛት ለተመለከተ፣”በእውነት ኢትዮጵያዊያን ሃይማኖተኞች ናቸው” ያሰኛል፡፡ የፈጣሪ መንፈስ የቀረበዉ ሆኖ ከመገኘት የላቀ ነገር የለምና፣ ይህ በጣም ጥሩ ነገር ነዉ። ስንቶቻችን የእምነቶቹን ትዕዛዝ በአግባቡ እየፈፀምን ነው? ስንቶቻችንስ የምንለውን ሆነን ተገኝተናል?--- ለጊዜው  ጥያቄዎቹ ይቆየንና ወደ ርዕሰ ጉዳያችን እንመለስ፡፡
ከተማችንን የሚያሳስበው ሌላው ዋና ጉዳይ የድምፅ ብክለት ነዉ፡፡ ሁሉም ቤተ-እምነቶች ማለት ይቻላል፣ ፉክክር በሚመስል ሁኔታ፣ ከተማዋን በድምፅ ማጉሊያ ሲቀውጧት ይዉላሉ፣ ያድራሉ፡፡ የዉጪ ዜጎች ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ፣ እንደ ማሳሰቢያ የሚነገራቸው (ወይም ከተመለሱ በኋላ፣ እንደ አሉታዊ ትውስታ የሚነሱት) ከትራፊክ አደጋና ከልመና መስፋፋት ቀጥሎ ከቤተ- እምነቶች የሚወጣው አዋኪ ድምፅ ነው፡፡ የዚህ መጣጥፍ አዘጋጅ  አማኝ ነው፤ ግን እውነቱን ለመናገር ይህ ገደብ ያለፈ ከእምነት ተቋማት የሚነሳ የድምፅ ብክለት መቆም አለበት ከሚሉት ወገን ነው፡፡
የድምፅ ብክለት ጉዳይ ከተነሣ፣ በአስፈሪ ሁኔታ እየተስፋፋ ያለዉ ደግሞ ከጭፈራ (መሽታ) ቤቶችና ከጋራዦች የሚወጣው ድምፅ ነዉ። ዓላማው ቢለያይም ሁሉም የራሱን ፍላጎት ለማራመድ በትጋት እየሰራ ነዉ፡፡ በዚህ መሃል እየተጎዳ ያለዉ የከተማው ነዋሪና የከተማዉ ገፅታ በመሆናቸው መስተዳድሩ ከተቋማቱ ጋር ሊመክርበት ይገባል፡፡ እንደ  አንድ ዘመናዊ  ከተማ፤  አስገዳጅ የድምፅ ብክለት ደረጃ ወጥቶ፣ ሁሉም ህብረተሰብ እንዲያዉቀው ብቻ ሳይሆን የማስፈጸሚያ ስርዓት ሊዘረጋ ያስፈልጋል፡፡ በአጠቃላይ አዲሱ መስተዳደር፤ ድክመቶችንና ዉስንነቶችን መሸፋፈኑን ትቶ፣ ሥኬቶችን ብቻ በማጋነን ከመኩራራት ወጥቶ፣ ከህዝቡ ጋር በመተባበር፣ ለዘላቂና ሁለንተናዊ ለዉጥ ተግቶ መስራት ይጠበቅበታል፡፡ በመንግስት ላይ ጣት መቀሰር ቀላል ነዉ፡፡ እኛ የከተማ ነዋሪዎችም በያገባኛልና በኃላፊነት መንፈስ፣በግልና በጋራ የሚጠበቅብንን ሃላፊነት መወጣት ይኖርብናል። ይህ እንዲሆን መንግስት (መስተዳደሩ) ነዋሪዎች፣ በተናጠልና በተደራጀ መልክ የሚደርጉትን ተሳትፎ ለማሳለጥ የሚያስችል፣ የፖሊሲና የህግ ማዕቀፍ ሊቀርፅ ይገባል፡፡ በዚህም ሳያበቃ፣ መሰረታዊ በሆኑ ከተማ አቀፍ ጉዳዮች፣ ከነዋሪዎቹ ጋር የጋራ መግባባት ለመፍጠር መስራት አለበት። በመሰረታዊ ጉዳዮች ላይ የጋራ መግባባት ሲኖር፣ ለጋራ ዓላማ መሥራት ይከተላል፡፡
ከአዘጋጁ፡-   (ጸሃፊውን በኢ-ሜይል አድራሻው፡- This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it. ማግኘት ይቻላል፡፡)




ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንድ ከባድ የአገር ወረራ ሊካሄድ መሆኑ ይሰማና፣ ሰው ስጋት በስጋት ይሆናል፡፡ ዙሪያ ገባው ህዝብ መነጋገሪያው ይሄ ጉዳይ ይሆናል፡፡
ከሽማግሌዎቹ አንዱ፤
“በሰሜን በኩል እንሂድና ወደ ታች ወደ ምሥራቅ እንውረድ”
ሁለተኛው፤
“የለም የለም፤ ከምዕራብ ወደ ደቡብ ብንከባቸው ነው የሚያዋጣን”
ሶስተኛው፤
“ኧረ ኧረረ እረረ … ያማ በጭራሽ አይታሰብም፤ መሆን ያለበት ከደቡብ እንነሳና--- ዳር ዳሩን፣ አጥር ላጥር ተጉዘን ወደ ማህል መግባት ነው፡፡ ዋናው ያካሄድ ዘዴ ማበጀት ነው፡፡”
አራተኛው፤
“ሰሜንንም፣ ደቡብንም ምሥራቅንም፣ ምዕራብንም አካለላችሁ፡፡ ጠላት ግን የት ጋ እንደሆነ እንኳ አላነሳችሁም” አሉ፡፡
ሁሉም ግራ ተጋቡና ዝም አሉ፡፡
አንደኛው፤
“ችግራችን ይሄው ነው፡፡ ጦርነቱ የት ጋ እንደሆነ እንኳን ሳናውቅ ዘመቻ እንጀምራለን! ሳንደራጅ መሳሪያ እንወለውላለን፤ ሳናስብ እናውቃለን፡፡ ሳናውቅ ማሰብ እናቆማለን። ማሰብን እንገድፋለን፡፡ ያንን ብናውቅ፣ አገርን እየበደልን መሆኑን ተገንዝበን በጭራሽ አይፀፅተንም፡፡”
ሁለተኛው፤
“አሁን ወራሪ እየመጣብን ነው፡፡ ምን እናድርግ ብንባባል አይሻልም?”
ሦስተኛው፤
“ወራሪያችንማ ነገ ራሱ ነው፡፡ ቀኑ ነው፡፡”
በዚሁ ስብሰባው ተጠናቀቀና ወደ ምርጫ ሄዱ፡፡ የሰዎች ስሞች ተጠቁሞ፣ አንድ የጎበዝ አለቃና አስራ ሶስት ጎበዛዝት ተመረጡ፡፡
ጦርነቱ ተጀመረ፡፡ ተፋፋመ፡፡ ከግራም ከቀኝም ብዙ ሰው ወደቀ፡፡ በቀጠሉት ቀናትም ጦርነቶች ተካሄዱና በጠላት አሸናፊነት ተጠናቀቀ፡፡ የጎበዝ አለቃውም ወደ ቀዬው ተመለሰ።
የመንደሩ ሰው የጦርነቱን ውጤት ለማወቅ ልቡ ተንጠልጥሎ ነበርና፤
“የጦርነቱ መጨረሻ ምን ሆነ?” ሲል ጠየቀው፡፡
የጎበዝ አለቃውም፤
“አይ፤ እንደፈራነው አይደለም፡፡ እኔ በሰላም ተመልሻለሁ” አለ፡፡
*   *   *
ጉዟችን ዛሬም ረጂም ነው፡፡ አውሎ ነፋሱ ረግቦ፣ አቧራው መሬት ሲወርድ፣ መጠያየቅ መጀመሩ አይቀሬ ነው፡፡
“ቀጣይ ጉዟችን ወዴት ነው?”
“የራሳችን ጥያቄ አለን ወይስ መሪዎች እንደ መሩን መነዳት ነው?”
“ስለ ፖለቲካው ብዙ አወራን፡፡ የኢኮኖሚው የታመቀ መገለጫ ነውና ፖለቲካ፤ ኢኮኖሚው ምን ይዋጠው ሳንል ወዴት እንደርሳለን?”
“ሁሉን ነገር መንግሥት ላይ ላክከን አንችለውም፡፡ የተቃዋሚዎች ድርሻ ምንድን ነው? የሲቪል ተቋማትስ? የህዝብስ? የየአንዳንዱ ዜጋስ? ሁሉም የየድርሻውን እንዴት ይውሰድ?”
ሌሎችም ጥያቄዎች አሉ፡፡ እንጠይቃቸው፡፡ እንጠያየቅባቸው፡፡ እንጠየቅባቸው። ሁሉንም ነገር “ዓለም አላፊ ነው፡፡ መልክ ረጋፊ ነው፤ ፎቶግራፍ ቀሪ ነው” ብለን አንዘልቀውም፡፡ ከልብ እናስብ፡፡ እራሳችንን የምንወደውን ያህል አገራችንን እንውደድ፡፡ ድህነትን ለመዋጋት ወደ ጦርነቱ እንግባ!
ብዙ ግብረ-ገብነት፤ ከመሰላቸትና ውሎ አድሮም ከመናናቅ አያልፍም፡፡ መሪ ከተናቀና ተመሪ ከናጠጠ፣ ተከታይ አደጋ አይቀሬ ነው፡፡ ለማንም የማይበጅ ሥርዓተ - አልበኝነትን አውርሶን የሚሄድ፣ አልሮ ሂያጅ ግርግር ብቻ ነው የሚተርፈን፡፡ አመፅም አይደለም። ሥር ነቀል አብዮትም አይደለም፡፡ ሌላው ቀርቶ ክለሳም (ሪቪዥኒዝምም) አይደለም፡፡ እዚህ ውስጥ ስለ ሪፎርም ማሰብ፣ ስለ ሊብራሊዝም ማሰብ ዘበት ይሆናል፡፡ “ባለቤቱን ካልናቁ አጥሩን አይነቀንቁ” የሚለው ተረት ፣ ቤት የሚመታው እዚህ ጋ ነው፡፡ ይሄን መቼም እናስብ። “ትንሽ ሥጋ እንደ መርፌ ትወጋ”ንም ልብ እንበል!
ለአገርና ለህዝብ ወደሚበጀው  በሰላም ያሸጋግረን!!

“ከዜግነት ጋር የተያያዘው ህግ እንቅፋት ሆኖብናል”
በመንግስት ጥሪ ተደርጎላቸው ከውጭ አገራት ወደ ሃገር ቤት የተመለሱ በርካታ የፖለቲካ ድርጅቶች እስካሁን በኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ ተመዝግበው ህጋዊነትን ያላገኙ ሲሆን የፖለቲካ
ድርጅቶቹ እንዲመዘገቡ ምርጫ ቦርድ ጥሪ አቅርቧል፡፡ የኢትዮጵያ ምርጫ ቦርድ የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክተር አቶ ተስፋለም አባይ ለአዲስ አድማስ በሰጡት ማብራሪያ፤ ቦርዱ ቀደም ሲል ለፖለቲካ ድርጅቶቹ ጥሪ በማድረግ፣ በአመዘጋገብ ስርአቱና ሂደቱ ላይ ገለፃ መስጠቱንና እንዲመዘገቡም ማስታወቁን ጠቁመው፤ እስካሁን ከ“አፋር ህዝብ ፓርቲ” በስተቀር ወደ ጽ/ቤቱ ቀርቦ አቅርቢ እውቅና ለማግኘት
ያመለከተ ፓርቲ የለም ብለዋል፡፡ የሀገሪቱ ህግ፤ “ማንኛውም የፖለቲካ ድርጅት በሃገር ውስጥ ህጋዊ ሆኖ ነው መንቀሳቀስ አለበት” ይላል ያሉት አቶ ተስፋለም፤ ድርጅቶቹ ወደ
ምዝገባ ስርአቱ እንዲገቡ ቦርዱ የተለያዩ ጥረቶችን እያደረገ መሆኑን ገልፀዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት ምርጫ ቦርድ በህጋዊነት የመዘገባቸው 22 ሀገር አቀፍና 40 ክልላዊ፣ በድምሩ 62 ፓርቲዎች መሆናቸውንም ዳይሬክተሩ ጠቁመው፡፡ ቦርዱም በሀገሪቱ የፖለቲካ ፓርቲነት የሚያውቃቸው እነዚህኑ ድርጅቶች ብቻ ነው ብለዋል - አቶ ተስፋለም፡፡ ወደ ሀገር ቤት የተመለሱ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ ወደ ቦርዱ ቀርበው ህጋዊ የሚያደርጋቸውን ምዝገባ እንዲያከናውኑም ቦርዱ ጥሪ አቅርቧል፡፡ ወደ ሀገር ውስጥ ከተመለሱት የፖለቲካ ድርጅቶች መካከል የኦሮሞ ነፃነት አንድነት ግንባር እና የትግራይ ዲሞክራሲያዊ ትብብር፤ ከዜግነት ጋር የተያያዙ የህግ ድንጋጌዎች ምዝገባ እንዳያደርጉ እንቅፋት እንደሆነባቸው አስታውቀዋል፡፡
የትግራይ ዲሞክራሲያዊ ትብብር አመራር አቶ ግደይ ዘርአፅዮን “ከዜግነት ጋር በተያያዘ ያለው ህገ ደንብ ላይ ማብራሪያ እየጠየቅን ነው፤ ህጉ ተስተካክሎ ምዝገባውን እናከናውናለን
ብለን ተስፋ እናደርጋለን” ብለዋል፡፡ የኦሮሞ ነፃነት አንድነት ግንባር አመራር አቶ አሚን ጁንደም በተመሳሳይ፤ ይህ ህግ እና ተያያዥ ጉዳዮች ምዝገባውን እንዳያደርጉ እንቅፋት እንደሆነባቸው ለአዲስ አድማስ
አስታውቀዋል፡፡ አንድ የፖለቲካ ድርጅት በኢትዮጵያውያን ተቋቁሞ ኢትዮጵያዊ ዜግነት ባላቸው አመራሮች ብቻ እንደሚመራ በህግ ተደንግጓል፡፡
የጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ጥሪን ተከትሎ የትጥቅ ትግል ሲያደርጉ የነበሩ የፖለቲካ ድርጅቶችን ጨምሮ ከ15 በላይ የሚሆኑ ፓርቲዎች ወደ ሀገር ቤት መመለሳቸው ይታወቃል፡፡