Administrator

Administrator

  አንጋፋው ብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት፤ ከጀርመኑ ሙልባወር ኩባንያ ጋር በመተባበር የስማርት ካርድ ህትመት ሊጀምር መሆኑን አስታወቀ፡፡
ማተሚያ ቤቱ ከዚህ ቀደም ሚስጥራዊ ህትመቶችን በወረቀትና በቀለም ቴክኖሎጂ ያከናውን እንደነበር የጠቆሙት የድርጅቱ ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ተካ አባዲ፤ በዓለማቀፍ ደረጃ በአብዛኛው ሚስጥራዊ ህትመቶች ወደ ዲጂታል ቴክኖሎጂ እየተሸጋገሩ በመሆኑ፣ ማተሚያ ድርጅቱ ራሱን ለማዘመን ቴክኖሎጂውን ወደ ሀገር ውስጥ በማስገባት፣ የስማርት ካርድ ምርቶችን ለመጀመር ማቀዱን አስታውቀዋል፡፡
በዚህ ቴክኖሎጂ በመታገዝ በከፍተኛ የውጪ ምንዛሬ በውጪ ሀገራት በስማርት ካርድ ቴክኖሎጂ የሚታተሙ የባንክ ገንዘብ ማውጫ ካርዶች፣ ሲም ካርዶች፣ የመታወቂያ ካርድ፣ ፓስፖርት የመሳሰሉትን በሀገር ቤት ለማተም ያስችላል ተብሏል፡፡
የማተሚያ ቤቱ አመታዊ ትርፍ ከነበረበት 8 ሚ. ወደ 1.5 ቢሊዮን ብር ማደጉንና ትርፋማ መሆኑን ያወሱት ስራ አስኪያጁ፤ ቴክኖሎጂውን በስራ ላይ ለማዋል የገንዘብ አቅም ችግር የለብንም ብለዋል፡፡ ቴክኖሎጂውን ለመተግበር ከ125 እስከ 150 ሚሊዮን ብር እንደሚያስፈልግ በመጠቆም፡፡ አገልግሎቱም ከ6-8 ወር ባለው ጊዜ ውስጥ እንደሚጀመር አቶ ተካ ተናግረዋል፡፡

እሳትና ውሃ ቀርቦላታል፤ እጇን ወዳሻት መስደድ የእሷ ምርጫ ነው- ዶናልድ ትራምፕ

       ባለፈው ማክሰኞ ባልተጠበቀ ሁኔታ ባለስቲክ ሚሳኤል ወደ ጃፓን በማስወንጨፍ አለምን በድንጋጤ ክው ያደረገቺው ሰሜን ኮርያ፣ “ይህ እኮ በፓሲፊክ አካባቢ የማደርገው ወታደራዊ ዘመቻ ጅማሬ ነው፤ ገና ብዙ ሚሳኤሎችን ወደ አካባቢው አስወነጭፋለሁ” ስትል በይፋ ተናግራለች፡፡
የሰሜን ኮርያው ፕሬዚዳንት ኪም ጆንግ ኡን፤ ሚሳኤሉን ያስወነጨፍነው አሜሪካና ደቡብ ኮርያ እያደረጉት ለሚገኘው ወታደራዊ ልምምድ ምላሽ ለመስጠት ነው፣ የአገሬ ጦር በፓሲፊክ አካባቢ የሚያካሂደውና የአሜሪካ ግዛት የሆነቺውን ጉኣም ለማጥቃት ያለመው ቀጣይ ወታደራዊ ዘመቻ ጅማሬ ነው ሲሉ በይፋ ማስታወቃቸውን ኬሲኤንኤ የተባለው የአገሪቱ መንግስት መገናኛ ብዙሃን ዘግቧል፡፡
“ያስወነጨፍነው ሚሳኤል አሪፍ መነቃቂያ ነው፤ ከፍተኛ እርካታ ተሰምቶኛል” ሲሉ በይፋ የተናገሩት ፕሬዚዳንቱ፤ በቀጣይም ተመሳሳይ በርከት ያሉ ሚሳኤሎችን ወደ አካባቢው እንዲያስወነጭፍ ለአገሪቱ የጦር ሃይል ትዕዛዝ ማስተላለፋቸውንም ዘገባው አመልክቷል፡፡
ሰሜን ኮርያ ከሚሳኤል ሙከራዋ እንድትታቀብ በተባበሩት መንግስታት ድርጅትና በአገራት መንግስታት ተደጋጋሚ ጫና ቢደረግባትም ባለፉት ወራት በተጠናከረ ሁኔታ የሚሳኤል ሙከራ ስታደርግ መቆየቷን ያስታወሰው ዘገባው፤ የማክሰኞው የሚሳኤል ማስወንጨፍ ድርጊት ግን ብዙዎችን ያስደነገጠ ነው ብሏል፡፡
ከፒንግያንግ አቅራቢያ ከሚገኝ ጣቢያ ወደ ጃፓን አቅጣጫ የተወነጨፈው ይህ ሚሳኤል፤ 2ሺህ 700 ኪሎ ሜትሮች ያህል በመጓዝ በሰሜናዊ ጃፓን በሚገኘው ሆካይዶ ደሴት ላይ ቢያርፍም በነዋሪዎች ላይ ምንም አይነት ጉዳት አለማድረሱን ያስታወሰው ዘገባው፣ ድርጊቱ የጃፓንን መንግስት በከፍተኛ ሁኔታ ማስደንገጡንና ይህን ተከትሎ፣ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር በሰጡት መግለጫ፤ ድርጊቱ ያልተጠበቀ፣ አጅግ አደገኛና አውዳሚ ስጋት ነው ሲሉ ሰሜን ኮርያን መኮነናቸውን አመልክቷል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፤ የሰሜን ኮርያ ድርጊት ለጃፓንና ለአካባቢው አገራት ብቻ ሳይሆን ለሁሉም የተመድ አባል አገራት ከፍተኛ ስጋት ነው በሚል ድርጊቱን በይፋ ያወገዘው ሲሆን ሩስያና ቻይና ግን በአካባቢው ውጥረት እንዲነግስ ያደረገው የአሜሪካ ወታደራዊ ልምምድ ነው ሲሉ አሜሪካን ኮንነዋል፡፡
የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በበኩላቸው፤ ድርጊቱ ሰሜን ኮርያ ለጎረቤት አገራት ያላትን ጥላቻ ያሳየችበት ነው፣ ከአሁን በኋላ እሳትና ውሃ ቀርቦላታል፤ እጇን ወዳሻት መስደድ የእሷ ምርጫ ነው ሲሉ ተናግረዋል፡፡

 ጌም ኦፍ ትሮንስ በተመልካቾች ብዛት ክብረ ወሰን አስመዝግቧል

       የሃሪ ፖተር ተከታታይ መጽሃፍት ደራሲ የሆነቺው እንግሊዛዊቷ ጄኬ ሮውሊንግ፣ የ2017 የአለማችን ከፍተኛ ተከፋይ ደራሲ መሆኗን የዘገበው ኢኮኖሚክ ታይምስ፣ ደራሲዋ ከሰኔ ወር 2016 አንስቶ በነበሩት 12 ወራት ከመጽሃፍቷ ሽያጭ በድምሩ 95 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቷን አስታውቋል፡፡
የመጀመሪያውን የሃሪ ፖተር መጽሃፍ ለንባብ ያበቃችበትን 20ኛ አመት ክብረ በዓል በቅርቡ ያከበረቺው ደራሲዋ፣ መጽሃፍቶቿ ከፍተኛ ተወዳጅነትን በማግኘት በገፍ መቸብቸባቸውን ቢቀጥሉም፣ የአለማችን ቁጥር አንድ ከፍተኛ ተከፋይ ደራሲ ስትሆን ግን ይህ ከአስር ዓመታት በኋላ የመጀመሪያ ጊዜዋ መሆኑን አመልክቷል፡፡
ጄምስ ፓተርሰን በ87 ሚሊዮን ዶላር ሁለተኛ፣ ጄፍ ኬኒ በ21 ሚሊዮን ዶላር፣ ዳን ብራውን በ20 ሚሊዮን ዶላር፣ ስቴፈን ኪንግ በ15 ሚሊዮን ዶላር አመታዊ የህትመትና የኤሌክትሮኒክስ መጽሃፍት ሽያጭ ገቢ፣ በቅደም ተከተላቸው እስከ አምስተኛ ያለውን ደረጃ የያዙ የአለማችን ድንቅ ደራሲያን መሆናቸውንም ዘገባው ገልጧል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ ተወዳጅ ሆኖ የዘለቀውና ሰባተኛው ሲዝን ላይ የደረሰው ጌም ኦፍ ትሮንስ ተከታታይ ፊልም ከሰሞኑ በታሪኩ ከፍተኛውን የተመልካች ቁጥር ማግኘቱ ተዘግቧል፡፡ የጌም ኦፍ ትሮንስ የሲዝን ሰባት ማጠናቀቂያ በ12.1 ሚሊዮን ተመልካቾች በቀጥታ፣ በ16.5 ሚሊዮን ተመልካቾች ደግሞ ከቀጥታ ስርጭት በኋላ መታየቱን የዘገበው ፎርብስ መጽሄት፤ከዚህ ቀደም በቀጥታ የተከታተሉት ተመልካቾች ከፍተኛው ቁጥር 10.1 ሚሊዮን እንደነበር አስታውሷል፡፡


   የዕውቁ የታሪክ ተመራማሪና የስነ-ፅሁፍ ባለሙያ ፕሬፌሰር ፍቅሬ ቶሎሳ፣ “ስውሩና ያልተነገረው የአይሁዳውያንና ኢትዮጵያውያን ታሪክ” የተሰኘ መፅሀፍ፣ ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡
መፅሀፉ በዋናነት፣ የሁለቱ አገራት ህዝቦች ከ4 ሺ ዓመታት በላይ ስላላቸው ትስስር፤ ስለ ዮዲት ጉዲት ያልተነገሩና ለኢትዮጵያ ስላደረገቻቸው መልካም ተግባራት፤ ስለ አፋር ህዝብና በስሙ ስለተሰየመው አፍሪቃና በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ትንታኔ ይሰጣል፤ ተብሏል፡፡
ፕሮፌሰር ፍቅሬ ከዚህ ቀደም ይህንን መፅሀፍ “The hidden and untold history of the Jewish people and Ethiopian” በሚል ርዕስ በእንግሊዝኛ ፅፈው አቅርበውት እንደነበር ተገልጿል። መፅሀፉ በ238 ገፅ ተቀንብቦ፣ በ101 ብር ከ20 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል። ፕሮፌሰር ፍቅሬ በቅርቡ ለንባብ ካበቁት፣‹‹የኦሮሞና የአማራ እውነተኛ የዘር ምንጭ” ከተሰኘው አነጋጋሪ መፅሀፋቸው በተጨማሪ፣ በእንግሊዝኛ፣ በጀርመንኛና በአማርኛ በርካታ ግጥሞችን፣ ተውኔቶችንና ከ60 በላይ አጫጭር መጣጥፎችን ለንባብ ማብቃታቸው ይታወሳል፡፡


  እናት የማስታወቂያ ድርጅት፣ ከጀርመን የባህል ማዕከልና ከብሄራዊ ቤተ-መጻሕፍትና ቤተ- መዛግብት ኤጀንሲ ጋር በመተባበር፤ ነገ ከቀኑ 8፡ 00 ጀምሮ፣ በሩስያዊው ጸሐፊ አንቷን ቼኮብ ተጽፎ በተርጓሚ ትዕግስት ኅሩይ “ቅብጥብጧ” በሚል ርዕስ ወደ አማርኛ በተመለሰው መጽሐፍ ላይ፤ በመወዘክር አዳራሽ ውይይት ያካሂዳል፡፡ በዕለቱ፣ ለውይይቱ የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት አቶ ዓለማየሁ አሊ እንደሆኑ የገለፀው እናት የማስታወቂያ ድርጅት፣ ፍላጎት ያለው በውይይቱ ላይ እንዲሳተፍ ጋብዟል፡፡

Saturday, 02 September 2017 12:28

አዳራሹ ባዶ አይደለም!

 የ“እኔ” ስለምንላቸው ተመልካቾች መጻፍ ከፈለግሁ ቆየሁ፡፡ “እኔ” የሌለሁበት ቦታ ማግኘት አስቸጋሪ ነው፡፡ “እኔ” ስል ግን እያንዳንዳችንን ማለቴ ነው፡፡ በእያንዳንዳችን ኅሊና ውስጥ ‹ጉዳይ› የምናደርጋቸው ሃሳቦች ብቻ ሳይሆኑ ሰዎች አሉ፡፡
የእያንዳንዳችን ኅሊና ደግሞ አዳራሽ ነው፤ አዳራሹ መድረክ አለው፤ አትሮኖሱ የተዘረጋውና መጽሐፉ የተገለጠው ለአንድ ሰው ነው፡፡ አንድ ሰው ደግሞ መድረክ ላይ የሚቆመው ዲስኩር ሊያስደምጥ፤ ወይም ትርኢት ሊያሳይ ወይም ሊያሰማ ነው፡፡ ንግግርም ሆነ ትዕይንት ደግሞ ራስን ለማስደሰት ተብሎ ብቻ የሚደረግ አይደለም፡፡ ታዳሚ ይፈልጋል። ታዳሚውን ማስደመም ወይም ማበሳጨት ደግሞ መድረክ ላይ የወጣው ሰው ሚና ነው፡፡
እንደዚህ ዓይነት ነገር ወደ ጭንቅላቴ ሰርጎ መግባት ከጀመረ ዘጠኝ ዓመታት አልፎታል፡፡ ሰውን ሰው ያደረገው ሰው ነው፡፡ ስለ ሰው የማያስብ ሰው የለም፡፡ በዕለቱ እንተውናለን፤ ሲተወንም እናያለን፡፡ የቴአትር ጥበባት ተማሪ ሳለሁ፣ ስለ አዘጋጃጀት ጥበብ ያስተማረን መምሕር ተሻለ አሰፋ ‹Private audience› የሚለውን ቃል ያነሳሳልን ነበር፡፡ “ፕራይቬት ኦዲየንስ” ማለት፣ አንድ ተዋናይ ወክሎት የሚጫወተውን ገፀ ባሕርይ በጥልቀት አጢኖ፣ ገጸ ባህርዩ ማንን አስቦ ነው፣ እያንዳንዱን ቃል የሚናገረው? ማንን አስቦ ነው፣ ድርጊቱን እየተገበረ፣ ሕይወቱን እየኖረ ያለው? ለሚሉ ጥያቄዎች ተዋናዩ ምላሽ እንዲሰጥ የሚያደርግ ፅንሰ-ሀሳብ ነው፡፡
ለምሳሌ ከሼክስፒር ተውኔቶች ውስጥ ኦቴሎን እንውሰድ፡፡ ኦቴሎ የእናቱ ነገር አይሆንለትም፡፡ የእናቱን ስጦታ፣ ያቺን መሀረብ፣ እንደ ማተብ ክር ይሞትላታል። የእናቱ ምስል እየተመላለሰበት ያንፀዋል፤ ያፅናናዋል። እናቱ ናት በውስጡ ያለችው፡፡ በኢያጎ ውስጥ ግን ጎልቶና ደምቆ የሚታየው ኦቴሎ ነው፡፡ ብዙዎቻችሁ እንደምታውቁት፣ የኢያጎ መንፈስ የሚናወፀው ኦቴሎ ከፍ ብሎ ሲታይ ነው፡፡ የአንድ ጥቁር ሰው ጄኔራል መሆንና በበላይ ሹማምንት ተወዳጅ መሆን ኢያጎን ረብሾታል፡፡ የሚገባኝ ቦታ በሌላ ሰው ተይዟል ብሎ ያምናል፡፡ ስለዚህ ኦቴሎ ከክብሩ ዝቅ እንዲል፣ ዝቅ ባለም ጊዜ ያልተገባ ነገር በራሱና አብረውት በሚኖሩት ታማኞቹ ላይ እንዲፈፅም ኢያጎ ነገር መጎንጎን ይጀምራል፡፡
ዴዝዴሞና ከቃስዮ ጋር የተለየ ግንኙነት እንዳላት አስመስሎ፣ ኦቴሎ ለዴዝዴሞና የሰጣት ተወዳጁን መሀረብ ሚስቱ ሰርቃ እንድታመጣለትና ቃስዮ እጅ እንዲገባ አድርጎ፣ ቅናት አረሙን በትዳሩ ላይ ይዘራበታል፡፡ ከላይ በጠቀስነው “ኦቴሎ” ቴያትር ውስጥ፣ የኦቴሎ “ፕራይቬት ኦዲየንስ” ማለት፣ እያንዳንዱ ገፀባህርይ በሕይወቱ ውስጥ ሰፊ ስፍራ የሚሰጠውን  ተመልካች የሚመለከት ይሆናል፡፡ ሰፊ ስፍራ የሚሰጠው ደግሞ ለሚወዱት ብቻ አይደለም፤ ለሚጠሉትም ጭምር እንጂ!
በእያንዳንዱ ድርጊቶች መሃል ይሄ ስሜት አለ። የተማርንም ያልተማርንም ያው ነን፤ ብቻችንን አይደለንም፤ ይዘናቸው ወይም በማይታይ አንቀልባ አዝለናቸው የምንዞራቸው ሰዎች አሉን፡፡ ያለ እነዚህ ሰዎች አንድ ስንዝር ፈቅ ማለት ይከብደናል፡፡ እነዚህ ሰዎች ወዳጆቻችን፣ ወይም ወላጆቻችን፣ ወይም የመሰረትነው የቤተሰብ አባላት ይሆኑ ይሆናል፡፡
ይህንን የተማርኩ ዕለት፣ “ፕራይቬት ኦዲየንስ” የሚባለውን ነገር፣ ‹ለገፀባህርይ አሳሽነት ብቻ› ሳይሆን ወደ የዕለት ተዕለት ሕይወት ማውረድ ፈለግሁ፡፡ አብረውኝ የሚማሩ ተማሪዎችን አሰብኩና፣ ራሴንም ጨመርኩና፣ እነዚህ ተማሪዎች በየኅሊናቸው ይዘዋቸው የሚዞሩ፤ ወደ  ዕድገት ተራራ ባቀኑ፣ ወይም ወደ ውድቀት ሸለቆ በወረዱ ቁጥር፣ ቶሎ ወደ ጭንቅላታቸው ብቅ የሚለው “ተመልካች” ማን ይሆን? ብዬ አሰብኩ፡፡ በየኅሊናቸው አዳራሽ እንዴት ያሉ ሰዎች ወንበሮቻቸውን ይዘው ተቀምጠዋል ብዬ የማይመለከተኝን አሰሳ አካሄድኩ፡፡ እነዚህ ተማሪዎች፣ እንደ ማንኛውም ሰው ሞራላቸው ተሰብሮ ቢወድቅ “እኔን!” ብለው የሚደነግጡላቸው ሰዎች አሏቸው፡፡ በተቃራኒውም፣ “ይበላቸው!” ብለው ክፉውን ሁሉ የሚመኙላቸው ሰዎችም አሏቸው፡፡ ግና ተማሪዎቹ ማንን ደስ ለማሰኘት ወይም ማንን በንዴት ባህር ለማስዋኘት ብለው ነው፣ እየኖሩና እየተማሩ ያሉት? በእልልታና በእሪታቸው ጊዜ ቶሎ ወደ አእምሮአቸው ብቅ የሚለው አንዴት ያለ ሰው ነው? ሕይወት እንድትተውነው ባዘጋጀችላቸው ተውኔት ለመሳተፍ መድረክ ላይ ሲወጡ፣ ከእልፍ አእላፍ ተመልካቾች መሀል፣ ማንን ወይም እነማንን አስበው ነው፣ ትወናቸውን የሚያካሂዱት? ብዬ ራሴን ጠየቅኩ፡፡
አንድ ተማሪ ነበረ፡፡ እድሜው ገፋ ብሏል፡፡ የድርሰትም ሆነ የዝግጅት ዝንባሌ የለውም፡፡ የትወና ተሰጥኦም እንዳልታደለ ያውቃል፡፡ ግን ይማራል፤ ቴአትር ይማራል፤ ቴአትረኛ ለመሆንም ሆነ ለመባል ሳያጓጓውና የመንፈስ ግለት በውስጡ ሳይኖር ይማራል፤ የሚማረው ግን ንቃ የተወችውን ሴት፣ የት እንደደረሰ ለማሳየት ነው፤ አዎን፤ ንቃ የተወችውን ሴት ለማስቆጨት፣ “አመለጥኩሽ!” ለማለት!!
ይህቺን ሴት ይወዳት ነበር፡፡ ገጠር ገብቶ፣ የአንደኛ ደረጃ ተማሪዎችን በሚያስተምርበት ጊዜ፣ ይህቺ ሴት ብዙ መደናበሮችን አስረስታው ነበረ። ደስታውና ፈገግታው ሞቅ፣ ፈካ እያለ እንዲሄድ አድርጋው ነበረ፡፡ ቆይቶ ግን አንድ ነገር ተፈጠረ። አንድ ቀን ጠረኖቻቸውን ተጠጋግበው ሲያበቁ፣ “ላገባሽ ወስኛለሁ!” አላት፤ ይህንን ስትሰማ ደነገጠች፤ መጀመሪያ አይደነግጡ አደነጋገጥ ደነገጠች፤ ቀጥሎ ሣቋ መጣ፤ ከትከት ብላ ሣቀች፤ ሣቀችበት፤ አሁን ድንጋጤዋን ተረከባት፡፡ በተራው ደነገጠ፡፡ “ሰርፕራይዝ አደርጋታለሁ!” ብሎ አስቦ በተናገረው ነገር፣ “ሰርፕራይዝ” ያደረገውን ምላሽ ሰጠችው፡፡ “ድፍረትህ! እኔ እኮ እዚህ ምንም መዝናናት በሌለበት ገጠር፣ ብቻ ከመሆን ይሻላል ብዬ የፍቅር ጥያቄህን ተቀበልኩህ እንጂ እኔና አንተ እኮ አንመጣጠንም! አንኳኋንም!” አለችው፡፡ ግራ ገብቶት፣ “ለምን?” አለ፡፡ መልስ ለመስጠት ደቂቃ አልፈጀባትም፣ “አንኳኋንም!! እኔ’ኮ ዲፕሎማ አለኝ!! አንተ ደግሞ ገና የቲ.ቲ.አይ. ምሩቅ ነህ! እንዴት ቁልቁል ወርጄ ካንተ ጋር ትዳር ልመስርት?!” አለችው፤ ጥያቄውን በማቅረቡም ታዘበችው፡፡
ምንጭ፡- (ሰሞኑን ለንባብ ከበቃው የደራሲ እንዳለጌታ ከበደ፣ ”ያልተቀበልናቸው”
የወጎች መድበል የተቀነጨበ፤ ነሐሴ 2009 ዓ.ም)

  በረጅም ልብወለድ- አዳም ረታ (“የስንብት ቀለማት”)
በሥነ ግጥም- አበረ አያሌው (“ፍርድና እርድ”)
 በልጆች መፅሐፍ - አስረስ በቀለ (“የቤዛ ቡችላ”)
ኢስትዌስት ኢንተርቴይንመትና ኤቨንት ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ለመጀመሪያ ጊዜ ያዘጋጁት “ሆሄ” የሥነ ፅሑፍ ሽልማት፣ባለፈው ሰኞ ምሽት በብሔራዊ ትያትር ባካሄደው ሥነሥርዓት በየዘርፉ ተወዳድረው ያሸነፉትን  ሸልሟል፡፡ ዋናዎቹ የውድድር ዘርፎች ረጅም ልብወለድ፣ሥነግጥምና የልጆች መጻሃፍት ሲሆኑ ከሐምሌ 2008 እስከ ሐምሌ 2009 ዓ.ም ተፅፈው ለንባብ የበቁ መፅሐፍት በውድድሩ መካተታቸው  ታውቋል፡፡ ለእያንዳንዱ ዘርፍ ሶስት ሶስት ዳኞች ተመድበው ምርጫና ምዘናው መካሄዱም ተጠቁሟል፡፡ 80 በመቶ በዳኞች ምዘና ፣20 በመቶ ደግሞ በአንባቢያን ምርጫ መሰረት፣  አሸናፊዎቹ እንደተለዩ ተነግሯል፡፡
በረጅም ልቦለድ ዘርፍ ለውድድር ከቀረቡት ሥራዎች መካከል የዶ/ር ዓለማየሁ ዋሴ “ዝጎራ”፣ የአዳም ተረታ “የስንብት ቀለማት”፣ የሰብለ ወንጌል ፀጋ “መፅሀፉ”፣ የያለው አክሊሉ “ወሰብሳቤ” እና የብርሀኑ አለባቸው “የሱፍ አበባ” ለመጨረሻው ዙር ያለፉ ሲሆን  የደራሲ አዳም ረታ “የስንብት ቀለማት፣ አሸናፊ ሆኗል፡፡ ደራሲው በሃገር ውስጥ ስለሌለም፣ተወካዩ፣ ከደራሲ ሳህለ ስላሴ ብርሀነ ማሪያም እጅ ሽልማቱን ተቀብሏል፡፡
በግጥም መፅሀፍ ዘርፍ ለውድድር ከቀረቡት ሥራዎች ውስጥ የኤፍሬም ስዩም “ኑ ግድግዳ እናፍርስ”፣ የትዕግስት ማሞ “የጎደሉ ገፆች”፣ የአበረ አያሌው “ፍርድና እርድ”፣ የዶክተር በድሉ “ተስፋ ክትባት” እና የበላይ በቀለ ወያ “እንቅልፍና ሴት” የግጥም መፅሀፍት ለመጨረሻው ዙር ያለፉ ሲሆን  የአበረ አያሌው “ፍርድና እርድ” አሸናፊ ሆኖ ከገጣሚ፣ ባለቅኔና ፀሀፌ ተውኔት አያልነህ ሙላቱ እጅ ሽልማቱን  ወስዷል፡፡
በልጆች መፅሐፍ ዘርፍ ከቀረቡት ሶስት መፅሐፎች መካከል የኮሜዲያን አሥረስ በቀለ “የቤዛ ቡችላ” የተሰኘ መፅሐፍ አሸናፊ ሆኗል፡፡ ለመጨረሻው ዙር ካለፉት ሶስት የልጆች መፅሐፍት ሁለቱ የአሥረስ በቀለ ናቸው፡፡ ኮሚዲያን አሥረስ በቀለ ሽልማቱን ከተቀበለ በኋላ ባደረገው አጭር ንግግር፤ “እኔ ሁሌም ተስፋ ሳልቆርጥ ስለምሰራ ለዚህ በቅቻለሁ፤ ዛሬ ሆሄ የሽልማት ድርጅት ከሥነ-ፅሁፍ ጋር በይፋ ድሮኛል” ሲል ደስታውን ገልጧል፡፡ ኮሜዲያኑ አስከትሎም፤ “ዛሬ አበባ ተስፋዬ በህይወት ኖረው፣ ይህንን ክብር ቢያዩልኝ  ምን ያህል በታደልኩ” ሲል በቁጭት ስሜት ተናግሯል፡፡  
የ”ሆሄ” ሌሎች ተሸላሚዎች  
የላቀ አስተዋፅኦ ያበረከተ የሚዲያ ተቋም -
ሸገር ኤፍኤም 102.1 ሬዲዮ
በረጅም ዘመን የትምህርት ማስፋፋት የላቀ ባለውለታ- አቶ ማሞ ከበደ ሽንቁጥ
ለአይነ ስውራን መፅሀፍትን ተደራሽ በማድረግ የላቀ አስተዋፅኦ ያበረከተ- “አዲስ ህይወት ለአይነ ስውራን ማዕከል”
በረጅም ዘመን ጋዜጠኝነትና ስነ-ፅሁፍን በትረካ ለህዝብ በማድረስ - ጋዜጠኛ ደጀኔ ጥላሁን
በረጅም ዘመን የኃያሲነትና ስነ-ፅሁፍ ሥራ የላቀ አስተዋፅኦ በማበርከት- ኃያሲና ደራሲ አስፋው ዳምጤ
በህይወት ዘመን የስነ-ፅሁፍ ሽልማት- አለቃ አካለወልድ ክፍሌ (“መፅሀፈ ሰዋሰው ወግዕዝ”)

   ብክለትን ለመቀነስ የወጣው ህግ 176 ፋብሪካዎችን ያዘጋል፣ 60 ሺህ ሰራተኞችን ያፈናቅላል

        የኬንያ መንግስት፤ የፕላስቲክ ከረጢት ወይም ፌስታል ባመረተ ወይም በተጠቀመ ላይ እስከ 4 አመት እስር እና 40 ሺህ ዶላር የገንዘብ ቅጣት የሚጥልና በአለማችን በመስኩ እጅግ ጥብቅ የተባለ ህግ አውጥቷል፡፡
በኬንያ ከሰኞ ጀምሮ የፕላስቲክ ከረጢት ይዞ የተገኘ የአገሪቱ ዜጋ፣ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውሎ ተገቢው ቅጣት እንደሚጣልበት የጠቆመው ዘገባው፤ የፕላስቲክ ከረጢቶችን የሚያመርቱ ፋብሪካዎችም ቁጥጥር እንደሚደረግባቸው አመልክቷል፡፡
የፕላስቲክ ምርቶች በአካባቢ ብክለት ረገድ የሚፈጥሩትን ተጽዕኖ ለመቀነስ ታስቦ የወጣው ይህ እጅግ ጥብቅ ህግ፤ ከቀጣዩ ሰኞ ጀምሮ በስራ ላይ እንደሚውል የዘገበው ዘ ጋርዲያን፣ በአገሪቱ የፕላስቲክ ከረጢቶች በየቦታው እየተጣሉ ከፍተኛ ብክለት እየፈጠሩ እንዳሉም አመልክቷል፡፡
የፕላስቲክ ከረጢቶች ለመበስበስ እስከ 1000 አመታት የሚደርስ ጊዜ እንደሚፈጁ የገለጸው ዘገባው፤ እንስሳትም ያገለገሉ የፕላስቲክ ከረጢቶችን በመመገብ ለጤና ችግር እንደሚጋለጡና በመዲናዋ ናይሮቢ በሚገኙ የከብት ማረጃ ቄራዎች ከአንድ ከብት ሆድ ዕቃ ውስጥ እስከ 20 የሚደርሱ ያገለገሉ የፕላስቲክ ከረጢቶች እንደሚገኙ ጠቁሟል፡፡
የፕላስቲክ ከረጢት ምርቶችን ወደ ውጭ አገራት በመላክ፣ከአካባቢው አገራት በቀዳሚነት የምትሰለፈው ኬንያ፣ የአካባቢ ብክለትን ለመቀነስ በሚል ያወጣቺው ይህ ህግ፣ በአገሪቱ የሚገኙ 176 ፋብሪካዎችን የሚያስዘጋና ከ60 ሺህ በላይ ዜጎችን ከስራ የሚያፈናቅል ነው በሚል የአገሪቱ የአምራች ኩባንያዎች ማህበር  ክፉኛ ተችቶታል፡፡
ቻይና፣ ፈረንሳይ፣ ሩዋንዳና ጣሊያንን ጨምሮ የተለያዩ 40 የአለማችን አገራት፣ የፕላስቲክ ከረጢቶችን ምርት በከፊል ወይም ሙሉ ለሙሉ የሚከልክሉ ተመሳሳይ ህጎችን አውጥተው በስራ ላይ ማዋላቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

     ሀብታሙ አለባቸው፣ ዛሬም ብዕሩንና ብራናውን አጣምሮ፣ የኢትዮጵያን ፖለቲካ ለመቃኘት ሞክሯል።  ቅኝት በመቃኘት ይታዘዛል። ጥሩ ቃኚ፣ ጥሩ ዜማን እንደሚያወጣ እሙን ነው፡፡ ሀብታሙ በቅኝቱ ጥሩ ዜማን አውጥቶ ይሆን የሚለው እንደ አድማጮቹ የሚወሰን ነው፡፡ በበኩሌ ያልተደፈረውን የቤተ መንግስት ጓዳ፣ ያልተደፈረውን የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነትና ያልተለመደውን የኢህአፓ ዘመን ድብብቆሽ ባለፉት ስራዎቹ ለመቃኘት መሞከሩን ወድጄለታለሁ፡፡
ዛሬ በወፍ በረር ለመቃኘት የፈለግሁት “ታላቁ ተቃርኖ” የተሰኘውን ስራውን ነው፡፡ በእርግጥ ይህንን መጽሐፍ ለማሔስም ሆነ ጥናታዊ ዳሰሳ ለማድረግ አቅሉም አቅሙም ኖሮኝ አይደለም፡፡ ሆኖም እንደ አንባቢና በአገር ጉዳይ ላይ ለመሳተፍ/ለመጠየቅ/ እንዲሁም የግል አስተያየትን መስጠት የተፈጥሮ መብትና/ግዴታ ከመሆኑ አንጻር፣ ስለ መጽሐፉ ጥቅል ሐሳብ የተሰማኝን ለማስቀመጥ  ነው፡፡
በበኩሌ የምስማማበት ጉዳይ (ከሌሎች ጋር አለመስማማት እንዳለ ሆኖ) የኢትዮጵያን ፖለቲካዊና ታሪካዊ ችግር ከአንድ ነጠላ መንግስት እና “ሬዥም” ጋር ማያያዙ የውድቀታችን መነሻ ነጥብ ነው፡፡ በዚህም አግባብ ዳግማዊ ምኒልክ ኢትዮጵያ፣ ታሪክ ማጠንጠኛ “የትክተት ነጥብ” ሆነው ሲወሰዱ፤ ልንወጣው ወደማንችልበትና ሸክማችንን የሚያበዙ ጋሬጣዎችን ይሰበስባሉ። ሌላኛው አስከፊ ችግር ጋሬጣዎች መብዛታቸው ብቻ ሳይሆን ጋሬጣውን የምናስወግድበት እሾኩ ላይ ይሆናል፡፡
ሀብታሙ አለባቸው፣ የዚህ ምሳሌ ማሳያ ሆኖ የሚቀርብ ይመስለኛል፡፡ በመጽሐፉ ሽፋን፣ የመሃል ኢትዮጵያንና የሰሜን ጫፍ ድንበርን እንደ መነሻ በማድረግ፣ “ታላቁ ተቃርኖ”ን በማመልከት፤ “አጼ ምኒልክ ሠርተውት ያለፉት ነገር በትክክል ምንድን ነው?” ሲል የአጼ ሚኒልክን ምስል አስቀምጦ፣ይጠይቃል፡፡ በእርሱ አተያይና ጥልቅ ምርምር፣ የኢትዮጵያ መሰረታዊ ችግር የተገለጸው ወይም የተጠቀለለው በአጼ ሚኒሊክ ዘመነ መንግስትና ከዚህ ወዲህ ነው ማለት ነው፡፡
ይህን መሰል የምሁራን ቅኝት (ቅዠት ላለማለት)፤ ከ1960ዎቹ የምዕራባዊያንና የምስራቁ ዓለም የፖለቲካ ርዕዮተ ዓለም ውዥንብር በፈጠራቸው አስተሳሰቦች (የያ ትውልድ አባላት) ኢትዮጵያን ቀርጸው (የፈጠሯት እስኪመስል ድረስ) የዘመናችንን ትኩሳትና የወደፊት እጣ ፈንታችን በየመቶ አመት ታሪክ ብሂል ውስጥ ይቀብረናል። ይህ በራሱ የታላቁ ተቃርኖ አንኳር መነሻ ነው፡፡ (በኢትዮጵያ የመቶ አመት ታሪክ የክርክር ሐሳብ፤ እነ ዮሐንስ አድማሱን፣ እሸቱ ጮሌን፤ ፈቃደ አዘዘንና ፕ/ር መስፍን ወልደማርያምን ተችተው የተነሱበትን ዘመን ያስታውሷል)
የፖለቲካ ድንበርና የአገርን ማስተዳደር ቅርጽ፣ መልኩን ቀይሮ፣ የምዕራባዊያን ጣልቃ ገብነት በተስፋፋበት ዘመን ላይ ቆመን፤ መፍትሄም ይሁን የጥናታችንን ዛቢያ በዚህ ማዕቀፍ ውስጥ ብቻ ሆነን ስናንዣብብ “የታላቁ ተቃርኖ” መነሻም መድረሻም እንደሚሆን አስባለሁ፡፡ “የኤርትራ” ችግር እና “የደቡብ ቅራኔ” በምኒልክ መጀመሩን እንደ ፖለቲካዊ ትንታኔ አድርጎ መነሳት፣ የሃብታሙ አለባቸውና የመሰሎቹ የፖለቲካ ልሂቃን ውድቀት መሆኑ የዚህ ጽሑፍ ጭብጥ (የግል እይታዬ) ነው፡፡
የዳዕማት ሥልጣኔ አንድምታው ምንድን ነው? የአሁኑ ትውልድ ምን ያህል ያውቀዋል? የአክሱምን ሥልጣኔ ማን አቆመው?  ማን መራው? ማን ማን ገበረ? የትኛው ሕዝብ በየትኛው ህዝብ ትስስሩን ፈጠረ? በምን መንገድ ከየት ወደየት? ሕዝብ በምን ተለያየ? በምን ተሳሰረ? የዛጉዌ ሥልጣኔ ከየት የት ይደርስ ነበር? የውጭው ዓለም በወቅቱ በምን መልኩ ይረዱት ነበር? በዚህ ወቅት የደቡቡ ይዞታ በምን መልኩ ይተሳሰር ይተዳደር ነበር?
የመካከለኛው ዘመን የይኩኖ አምላክ መንግሥት፤ ከደቡቡ ጋር የነበረው ትስስር? የሸዋ ነገሥታትና ቀሪው ማሕበረሰብ የነበራቸው ገጽ፤ አጼ ዘርዓ ያዕቆብ ሶማሌ ድንበር ድረስ ሄደው የገነቡት ልማት፣ ጥፋት፣ የትዳርም ይሁን የማስገበር/የመገበር ታሪካችን፣ የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ እስከ ቀይ ባሕርና ህንድ ውቅያኖስ ወይም የአፍሪካ ቀንድ ጫፍ መታየት፤ የልብነ ድንግል ንጉሳዊ ስም አጠራር በራሱ የሚሰጠው ትርጓሜ፤ የምስራቁ ዘመቻ ወደ ሰሜን ያመጣው ለውጥ፤ ለምላሹም የተሰጠው አጸፋ (አሉታዊም አዎንታዊም የአገር ግንባታ ሂደት...)
የእነ ሰርጸድንግል ታሪክ፤ የጎንደር ነገሥታት ከደቡቡ በተለይም ከኦሮሞው ሕዝብ ጋር የነበራቸው ትስስር፤ የየጁ መሳፍንት በጎንደር ዘመን የነበራቸው ሚና፣ ኦሮምኛ በጎንደር የነበረው ቦታ፤ ባሕረነጋሽ/ኤርትራ የነበረችበት ሁኔታ (ይዞታ)፤ የአጼ ቴዎድሮስ አነሳስ፣ ዘመኑ የጠየቀው መስፋፋት ምክንያት፤ ለምን አጼ ቴዎድሮስ? በዘመኑ የነበረው የግዛት አወሳሰን እንዴት ይገለጽ ነበር? ነው ወይስ “አቢሲኒያ”ን ቀርጸን ማነብነብ ይቀልለናል? …
(እዚህ ላይ ትልቅ የሚዘነጋ ሐሳብ ይታየኛል፤ ይሄውም የአጼ ቴዎድሮስ ዜና መዋዕል ከታቢና ምጡቅ ግለሰብ አለቃ ዘነብ፣ የኦሮምኛን ቋንቋ ማጥናታቸው፤ ብሎም መጽሐፍ ቅዱስን በኦሮምኛ ለመተርጎም ማሰባቸው፤ አስበውም መተግበራቸው በምን መልኩ የሚታይ ነው?)
በአጼ ዮሐንስ ዘመን መባቻ ላይ የተደረገው የባዕዳን ወረራና ተጽዕኖ፤ ሃይማኖታዊ ርዕዮተ ዓለም ለምን?  የባሕረ ነጋሽስ ይዞታ፤ የሂወት ውል፤ የምዕራባዊያን ቅኝ ግዛት ዘመቻ፤ የፖለቲካ አስተሳሰብ ዘመቻ፤ የመንግሥታት ትብብር ሐሳብ፤ የዘመናዊነት ትርጓሜ፤ … ወዘተ እንዲህ እንዲህ እያልን ጥናታዊ ምርምር፤ የታሪክ ጥናት የሚጠይቀውን መነጽር እየተጠቀምን፣ “ታላቁ ተቃርኖ” በሚል ሐሳብ እያላወስን፤ የኢትዮጵያን ችግር ነቅሰን እናውጣ ቢባል፣ አዕምሮዬንም ሆነ ስሜቴን የሚገዛ ጭብጥ የማገኝ ይመስለኛል፡፡
ዋናው ሀብታሙ አለባቸውን የምሞግትበት ነጥብም ይሄው ነው፤ ከእነዚህ ጭብጦች ውስጥ ነበር የአጼ ምኒልክን ቦታ ፈልቅቀን በማውጣት፣ ወዳለንበት ደረጃ ደርሰን፣ ተቃርኖንም ይሁን የግጭት መንስኤዎችን አልያም ስኬቶችን ልንገልጽ የምንገደደው፡፡ ከአንድ ትልቅ ሰፌድ ውስጥ አንዱን ሰንደዶ አውጥቶ፣ የሰፌዱን ሕልውና አድርጎ መውሰድ፣ በሰፌዱና በሌሎች ሰንደዶዎች ላይ የሚሰራ ደባ ሆኖ መታሰቡ አይቀሬ ነው! ኤርትራ ከምኒልክ በፊት የኢትዮጵያ ግዛት የሆነችበትና ያልሆነችበት ጊዜ በታሪክ ተፈትሾ ሲጠና፤ የደቡቡን ይዞታና ትስስር ቅድመ ታሪክ ጥናት ሳናደርግ፤ ምኒልክን መነሻም መድረሻም ማድረጉ ትልቅ የታሪክ ሸፍጥ ሆኖ ይታየኛል፡፡ ምኒልክ ሳይፈጠሩ ኤርትራ የነበረችና ለበርካታ ነገስታት የድልም የውድቀትም የስኬትም የክሽፈትም ማጠንጠኛ ሆና የዘለቀች በመሆኗ፤ “ኤርትራ” “ኤርትራ” የምንለው የምዕራባዊያኑ እርኩስ መንፈስ ወርሶን ለመግባቢያነት የምንጠቀምበት የቦታ ስም ብቻ ሳይሆን ለውድቀታችን የተበተብነው የቄሳሩ መንፈስ አዚም /አዙሪት/  ነው፡፡ ደቡቡንም በመቶ አመት ውስጥ የተፈጠረ መልክዓ ምድራዊ ይዞታ እስኪመስል ድረስ፤  ስለ ሺሕ አመታት የኢትዮጵያ ታሪክ ሂደት እያወራን ቦታና የሕብረተሰብን ፍልሰት ሳናጤን፤ የጥንቱን ስያሜ በዘመነኛ “ሰካራም” ስያሜ እየሰጠን፤ በአሁኑ ትርጉምና ዘመን አመጣሽ መቀመርያ መመዘን፤ የውድቀታችን መነሻና የታላቁ ታቃርኖ ክስተት መደምደሚያው/መፈጸሚያው/ ነው፡፡
ሀብታሙ አለባቸው፣ በመጽሐፉ በርካታ የአገር ውስጥ እና የባዕዳንን ስም እየጠቀሰ፤ የሐሳብ ክርክሩን ለማጠናከር ሲሞክር እናስተውላለን። የምሑራኑን ሐሳብም እየጠቀሰ፣ ለ“ታላቁ ተቃርኖ” መፍትሄ ‹‹ፋይዳ የሌለው›› እና ‹‹ያለው›› እያለ ሲገልጽ እናስተውላለን፤ በተለይም ከአገር ውስጥ ገብረሕይወት ባይከዳኝንና ፕ/ር መስፍን ወልደማርያምን በተደጋጋሚ ሲገልጽ ማስተዋላችን አልቀረም፡፡
በበኩሌ ፕ/ር መስፍን ወልደማርያምን ስለ ኢትዮጵያ ታሪክ ባሕልና ፖለቲካ ትንታኔ አረዳድ በአንድ እና በሁለት መጽሐፎቻቸው ዙሪያ ብቻ በማተኮር፣ አጠቃላይ ሐሳባቸውን መተቸቱም ሆነ መፍትሄ የለውም ብሎ መነሳቱ  ጸሐፊውን ያስገመግመዋል ባይ ነኝ፡፡ “አዳፍኔ” ይህንን አላስቀመጠም ብሎ ወደ ፍረጃ መሄድ ጸሐፊው የተልዕኮ ማስፈጸሚያ አንደበት መያዙን ያሳብቅበታል፡፡ (አንባቢ ሆይ፤ በሀብታሙ አለባቸው መጽሐፍ ውስጥ ከበርካታ ምሁራን ሐሳቦች ከመጡ መደምደሚያዎች አንጻር፤ “መስፍን ወልደማርያም በዘመናቸው ያልጠቀሱት ሐሳብ (መፍትኄ) ይሄ ነው” ብሎ የሚያሳየኝ ሰው ካለ፣ ለመቀጣት ዝግጁ ነኝ! - ፕሮፌሰሩ ከጻፏቸው መጽሐፍት ውስጥ እንደ ዋቢ የጠቀሳቸው ከሶስት አለመብለጡን ያጤኗል!)
መጽሐፉ የበርካታ ምሁራንን ሐሳቦች በቁንጽልም ቢሆን መያዙ ምሁራኑ ተሰባስበው እንዲመካከሩበትና እንዲወያዩበት፣ የኢትዮጵያን ትልቁን ቁልፍ ችግር ለመያዝም ሆነ የተዘጋብንን ደንቃራ አስተሳሰብ ለመክፈት፤ ብሎም ቁልፉን ለእያንዳንዱ ዜጋ ሰጥቶ ወደ ብርሃናማው “የታሪክ አቅጣጫ” እንድንዘልቅ ለማድረግ ያግዛል ብዬ አስባለሁ፡፡ ሆኖም ጸሐፊው፣ ለመማርም ይሁን ለመታረም ዝግጁነቱን ሲያሳይና በአካለ መንፈስ ሲገኝ ብቻ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡
መጽሐፉን በተደጋጋሚ እየተመለስኩ ለማንበብ ሞክሬያለሁ፡፡ ምርምራዊ ሂደትን ለመከተል የታሰበ ከመሆኑ አንጻር አሁንም ልዩ ትኩረትና አንጽንዖት ተሰጥቶት ሊታይ የሚገባው ነው፡፡ እንደ መቋጫ ሁለት ነጥብ ብቻ ላንሳ፡፡ አንደኛ፤ የኔ የአስተሳሰብ አድማስ ልኬት በእጅጉ የተወሰነ መሆኑን ወይንም በሌላኛው ጎን የጸሐፊው ሐሳብ በኢትዮጵያ ታሪክና ፖለቲካ ዙሪያ አዲስ አስተሳሰብን ይዞ ስለመጣ ለመረዳት አዳግቶኛል፡፡ በበኩሌ ጸሐፊው (ለእኔ) ይህንን የፈጠረበት ምክንያት  ምንድን ነው ብዬ ሳስብ አንዳንድ ነጥቦችን ማስቀመጥ ይኖርብኛል። በተቻለኝ መጠን በማሳጠር በሦስት ነጥቦች ብቻ ላጠቃልል፡፡
የኢትዮጵያን ችግር ከአጼ ምኒልክ ጋር አቆራኝቶ በመነሳቱና የመፍትኄ ሐሳቡንም እዚያው ዙሪያ በማድረጉ፣
በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የባዕዳን ተልዕኮና ጫና ራሱን የቻለ ሰፊ ቦታ ያለው ቢሆንም ጸሐፊው ጥናቱን በዚያ ላይም ባለማድረጉ፣
አሁንም በምሁራን እይታ ይቀርቡ የነበሩ ቃላትንን ለምሳሌ፤ ብሔር፣ አገር፣ ሐገረ መንግስት፣ ስልጣኔ፣ ባሕል፣ መንግስት ሬዥም…. ወዘተ መሰል ቃላትን አጠቃቀማቸውን ከእነ ልዩነታቸው ለማስረዳት ቢሞክርም በተለያዩ ገጾች ላይ ግን ራሱ ሲዳክርባቸው መመልከታችን አልቀረም።
ሶስቱን ነጥቦች በመያዝ ሌላ አንድ ረዥም ትንተና የሚያስፈልገው ጽሑፍ ማሰናዳት ይቻላል፡፡
ለማጠቃለል ግን፣”ታላቁ ተቃርኖ” በባዕዳን አስተሳሰብ የተቃኘ የምሁር እይታ መሆኑን መካድ አልችልም፡፡ የገብረህይወት ባይከዳኝ ሐሳቦች ላይ አተኩሮ ሚዛኑን እሱ ላይ መድፋቱን ሲገልጽ እናየዋለን፡፡ የሌሎች ባዕዳን አስተሳሰቦች/ጥናታዊ እይታ/ ከውስጣዊ ታሪካችን ጋር እያነጻጸሩ ለመግባቢያነት መቀመጡ፣ በተደጋጋሚ ውስጤን ኮርኩሮታል፡፡ የበርካታ ምሑራንን ሐሳቦች፣ ጥናታዊ ስራዎችና የምርምር ውጤቶችን ጠልቆ ገብቶ ዋኝቶ በመውጣት - የ”አዕምሯዊ ጅምናስቲክ” ጽሁፍ  እንዳይሆን ጸሎቴን አድርሼ፤ በመጽሐፉ ዙሪያ የወጡ አስተያየቶችን ለማንበብም ሆነ ለመሳተፍ ዝግጁነቴን ጀምሬያለሁ፡፡ መጽሐፉ አሁንም በተደጋጋሚ ሊመረመርና ሊታይ የሚገባው መሆኑን ግን የሚክድ አንደበት የለኝም፡፡

 የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በተነሳ ማግስት በኦሮሚያ የተለያዩ አካባቢዎች የንግድ ሥራና የትራንስፖርት አገልግሎት ማቆም አድማ ባለፈው ሳምንት ተደርጓል፡፡ እነዚህ አድማዎች ምን አንደምታ አላቸው? በኢኮኖሚ ላይ የሚያሳድሩት ተጽዕኖ ምን ያህል ነው? በቱሪዝም ዘርፉና በኢንቨስትመንት ላይስ? በመንግስት ላይ የሚያሳርፈው ፖለቲካዊ ጫና ምንድን ነው? አድማዎቹ ተባብሰው ወዳልተፈለገ አቅጣጫ እንዳይሻገሩ መፍትሄው ምንድን ነው ? የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ
አለማየሁ አንበሴ፤ ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ በርሄን፣አቶ ሞሼ ሰሙንና አቶ ክቡር ገናን በጉዳዩ ዙሪያ አወያይቷቸዋል፡፡ ሁሉም ሃሳባቸውን፣ አስተያየታቸውን፣ ስጋታቸውንና የመፍትሄ ሃሳቦቻቸውን ሰንዝረዋል፡፡ ለፖለቲካዊ ችግሮች መፍትሄው ፖለቲካዊ ውይይት ብቻ ነው፡፡

                    “በማንኛውም የሀገሪቱ ጉዳይ ህዝብን ማሳተፍ ያስፈልጋል”
                          ዶ/ር ቆስጠንጢኖስ በርሄ (የኢኮኖሚ ባለሙያ)

      የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ በተነሳ ማግስት የንግድና ትራንስፖርት አገልግሎት ማቆም አድማ ባለፈው ሳምንት በኦሮሚያ የተለያዩ ከተሞች ተደርጓል፡፡ በእንዲህ ያሉ አድማዎች ማነው ተጎጂው?
እንዲህ ያለ አድማ ሁሉንም ነው የሚጎዳው፤ ሸማቹን፣ ነጋዴውን፣ መንግሥትን ይጎዳል። በአጠቃላይ እንደ ሀገር ደግሞ መረጋጋቱን ስለሚያበላሽ፣ ኢንቨስተሮች በሀገሪቱ ላይ የሚኖራቸውን መተማመን ይቀንሳል፡፡ ብዙ ኢንቨስተሮች እንደ ቢቢሲ ላሉት፣ የውጪ ሚዲያ በሚሰጡት ቃለ ምልልስ፣ በተለይ የቻይና ኢንቨስተሮች፣ ኢትዮጵያን የመረጡበት አንዱ መመዘኛ፣ አገሪቱ የተረጋጋች፣ ሰራተኛውም ሰላማዊ በመሆኑ እንደሆነ ሲናገሩ ይደመጣሉ፡፡ እንደነዚህ አይነቱ ረብሻዎችና አድማዎች የሚያሳዩት፣ በአንድ መልኩ፣ ህዝቡ በህገ መንግስቱ ላይ የሰፈረውን  የመናገር መብቱን መጠቀሙ ነው፡፡ ጉዳዩ ወደ መጥፎ ሁኔታ ሲሸጋገር ደግሞ መንግስት ህግ የማስከበር ኃላፊነት አለበት፡፡ በዚህ አጋጣሚም የተለያየ አላማ ያላቸው ወገኖች፣ የህዝቡን ቅሬታ ለራሳቸው አላማ ሊጠቀሙበት ይችላሉ፡፡ ይህ እንዳይሆን መንግስት፣ ህዝቡን በየጊዜው ቀርቦ ማነጋገር አለበት፡፡ በተለይ በወረዳ ደረጃ ያሉ ኃላፊዎች፣ ለህዝቡ ቀጥተኛ መፍትሄ መስጠት አለባቸው፡፡
ለምሳሌ በኦሮሚያ ለተደረገው አድማ በምክንያትነት ከቀረቡት ጉዳዮች አንዱ የግብር ጉዳይ ነው---
በየትኛውም አገር ነጋዴ በተቻለ አቅም ታክስ ባይከፍል ይመርጣል፡፡ የአሜሪካን ፕሬዚዳንት ትራምፕ እንኳ ታክስ አይከፍሉም ተብለው ሲብጠለጠሉ የሰጡት ምላሽ፤ “እኔ ብልህ ስለሆንኩ ነው ታክስ የማልከፍለው” የሚል ነበር፡፡ አብዛኛው ነጋዴ ታክስ መክፈል አይፈልግም፡፡ ያገኘውን ቆጥቦ ንግዱን ማስፋፋትና ኑሮውን ማሻሻል ነው የሚመርጠው፡፡ መንግስት ደግሞ መሰረተ ልማት ለማሟላት፣ ሀገር ለመገንባት ገንዘብ ያስፈልገዋል። ስለዚህ በግብር ዙሪያ ያሉ አለመግባባቶችንና ችግሮችን በውይይትና  በሰለጠነ መንገድ መፍታት ያስፈልጋል፡፡
መንግስት የግብር ሰብሳቢ ሰራተኞችን ሁኔታም መፈተሽ ይኖርበታል፡፡ የአቅም ጉዳይ መታየት አለበት፡፡ ሌላው የንግድ መደብሮችን እያሸጉ ጉቦ የሚጠይቁ እንዳሉም ይሰማል፡፡ እነዚህ ነገሮች ላይ ትኩረት ሰጥቶ መከታተል ያስፈልጋል፡፡ የህዝብን ብሶት የሚቀሰቅሱት እንዲህ ያሉ ህገ ወጥ አሰራሮች ናቸው፡፡ በስፋት አድማ የሚያደርጉ ነጋዴዎች፣ ትልልቆቹ ወይም ለማህበረሰቡ በእጅጉ የቀረቡ አይደሉም፡፡ በየመንደሩ ያሉ ከህብረተሰቡ ጋር የቅርብ ግንኙነት ያላቸው አነስተኛ ነጋዴዎች ናቸው። የእነዚህ ነጋዴዎች ተፅዕኖ ቀላል አይደለም።
አድማው በመንግስት ላይ ምን ዓይነት ተጽዕኖ ያሳርፋል?
እርግጥ ነው ለጊዜው በመንግስት ላይ ምንም አይነት ቀጥተኛ ተፅዕኖ ላይኖረው ይችላል፤ ምክንያቱም የጸጥታ ኃይሉን ልኮ ህግ ሊያስከብር ይችላል፡፡ ነገር ግን አድማና ረብሻ ባለበት ቦታ ቱሪስት ሊመጣ አይችልም፡፡ ለምሳሌ ከዚህ ቀደም ከቱሪዝም በየዓመቱ ይገኝ የነበረው በቢሊዮን ብር የሚገመት ገቢ፣ አማራ ክልል ወይም ትግራይ ውስጥ ረብሻና አለመረጋጋት ከተከሰተ፣ ቱሪስት ወደ አካባቢው አይመጣም፤ ገቢውም አይገኝም። በዚህ በቀጥታ ተጎጂ የሚሆኑት የጎጃም የጎንደር ወይም የትግራይ ነዋሪዎች ናቸው፡፡ ህዝቡ ሲጎዳ ደግሞ መንግስት ላይ ነው ጫናው የሚያርፈው፤ ስለዚህ በአጠቃላይ ጉዳቱ በአገር ደረጃ ነው የሚሆነው፡፡ ሀገሪቱ ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ በምትፈልግበት፣ ግድቦች በሚገነቡበት፣ የባቡርና ሌሎች ሰፋፊ ፕሮጀክቶችን በዘረጋችበት አሁኑ ወቅት ከቱሪዝም የሚገኝ ገቢን ማጣት አገሪቱን ክፉኛ ይጎዳታል፡፡
በየዓመቱ በመቶ ሺህ የሚቆጠር ወጣት ከዩኒቨርሲቲ እየተመረቀ ነው፡፡ በሚሊዮን የሚቆጠር ወጣትም ከኮሌጅና የሙያ ተቋማት እየተመረቀ ነው የሚገኘው፡፡ እነዚህ ምሩቃን ሥራ እስካላገኙ ድረስ ይሄን አድማ በመጠቀም ጉዳዩን ወደ ሌላ ነገር የማሸጋገር ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል፡፡ ባለፈው ዓመት እንደተመለከትነው፡- ፋብሪካ ማቃጠል፣ እርሻዎች ማውደም፣ መኪና መሰባበር ወዘተ --- የመሳሰለ አደገኛ ውጤት ሊኖረው ስለሚችል፣ የመንግስት ኃላፊዎች ለጉዳዩ ትኩረት ሊሰጡት ይገባል፡፡ እርግጥ የህግ አስከባሪዎች በምንም ሁኔታ  እንዲህ አይነት ነገር እንዲኖር አይፈቅዱም። ነገር ግን እንዲህ ያሉ አድማዎችና ተቃውሞዎች እየተጠናከሩ በሄዱ ቁጥር ህዝብ በገዥው ፓርቲ ላይ ያለው እምነት እየመነመነ ሊሄድ ይችላል፡፡ ሀገሪቱ ያላት አንፃራዊ ሰላምና መረጋጋት በተለይ በዓለም አቀፍ ሚዲያዎች መጥፎ ገፅታ እየያዘ ከመጣ፣ ኢንቨስተሮች እዚህ ሀገር መጥተው ኢንቨስት እንዳያደርጉ እንቅፋት ይሆናል፡፡ እንዲህ ያሉ አድማዎች በተራዘሙ ቁጥር ደግሞ የሰው የስራ ተነሳሽነት ስሜት እየቀዘቀዘ፣ ወደ ረብሻ የሚገፋፋበት ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል። ይሄ አይነቱን ክስተት በተለያዩ የአፍሪካ ሀገራት ተመልክተነዋል፡፡
መፍትሄው ታዲያ ምንድን ነው?
በዚህ ጉዳይ የሲቪክ ማህበረሰቡና ሚዲያዎች ትልቅ ሚና እንዲጫወቱ ማድረግ ያስፈልጋል። በተለይ የምርመራ ስራ የሚሰሩ ሚዲያዎች መጠናከር አለባቸው፡፡ በሀገራችን በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ የህዝብ ስብስቦች አሉ፡፡ የህዝብ ስብስቦች ስንል እድሮችን፣ ማህበሮችን ያካትታል። እነዚህ ቁልፍ አካላት ናቸው፡፡  እነዚህን የሲቪክ ማህበራት ማጠናከር ያስፈልጋል፡፡ በሌላው ዓለም መንግስት የማያውቀውን ነገር አጉልቶ በማውጣት እርምት እንዲደረግ በመጠቆም ረገድ ሚዲያው ያለው ሚና ቀላል አይደለም፡፡ በሀገራችን ግን በሲቪክ ማህበራትም ሆነ በሚዲያ በኩል እስከ ዛሬ ያለው እንቅስቃሴ ደካማ ነው፡፡ በተለይ ሙስናን ለመዋጋት ሚዲያና የሲቪክ ማህበራት ወሳኝ ናቸው፡፡ አንድ ሰው ያለአግባብ ሀብት ሲያካብት ቀድሞ ሊያውቁ የሚችሉት በየአካባቢው ያሉ የህዝብ ማህበራት ናቸው፡፡ ስለዚህ ከእነዚህ ጋር ተቀራርቦ መስራት መጀመር አለበት፡፡ አንድ ወረዳ ላይ መንገድ በአግባቡ ላለመሰራቱ ዋናው ምስክሮች የሚሆኑት በወረዳው ያሉ ማህበራት ናቸው፡፡፡
ሌላው የዲሞክራሲ መንሰራፋት ጉዳይ ነው፡፡ ዲሞክራሲ ስንል የፖለቲካ ባህልን መቀየር ማለት ነው፡፡ እኛ ገና የፖለቲካ ባህላችን እየዳበረ ያለ ሀገር ነን፡፡ ባለፉት 10 ዓመታት በተለይ ከ97 በኋላ ብዙ ነገሮች ተለውጠዋል፡፡ ልማታዊ መንግስት ሲባል፣ መንግስት ብቻ አይደለም መስራት ያለበት። ህዝቡ ቀጥተኛ ተሳታፊ መሆን አለበት፡፡ ህዝቡን ለማሳተፍ ደግሞ የሲቪክ ማህበራት ወሳኝ ናቸው። በማንኛውም ጉዳይ የህዝብ ተሳትፎ ሲጠናከር ነው፣ ይህቺን ሀገር ወደፊት ሊያራምዳት የሚችለው። መንግስት ወደ ህዝቡ የበለጠ ቀርቦ፣ በአገሩ ጉዳይ በያገባኛል ስሜት እንዲሳተፍ ማበረታታትና መገፋፋት አለበት፡፡

------------------

                            “ህገ መንግስትን ሁልጊዜ መንከባከብ ያስፈልጋል”
                               አቶ ክቡር ገና

      በኦሮሚያ የተደረገው የንግድ ሥራና የትራንስፖርት አገልግሎት ማቆም አድማ አንደምታው ምንድን ነው?
 ሁሌም እንዲህ አይነት የስራ ማቆም አድማ ሲደረግ የማይበላሽ ነገር የለም፡፡ በተለይ ትራንስፖርት የሀገሪቱ የንግድ አንቀሳቃሽ ዋና ሞተር ነው፡፡ በየአካባቢው ያለው የንግድ ስራ ማቆም በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡ የህዝቡንም ኑሮ እንደሚያናጋ ግልፅ ነው፡፡
እነዚህ አድማዎች ከግብር ትመናው ጋር ብቻ የተገናኙ ናቸው ወይስ ሌላም ሰበብ አላቸው?
በመሰረቱ ግልፅ ሆኖ የሚታየው የፖለቲካም ችግር እንዳለ ነው፡፡ የፖለቲካ ችግርን ደግሞ በጊዜ መፍታት ያስፈልጋል፡፡ አንዳንዱ የፖለቲካ ችግሮችን በፖለቲካዊ ውይይቶች ለመፍታት ይሞክራል። አንዳንዱ ደግሞ በኃይል ለመፍታት ይሞክራል። ይሄ እንደየ ሀገራቱ ተጨባጭ ሁኔታ ይለያያል፡፡ እንደ‘ኔ ግን ፖለቲካዊ ችግሮችን በኃይል ለመፍታት ከመሞከር ይልቅ በንግግርና በውይይት መፍታት የተሻለ ዘላቂ ውጤት ያመጣል ብዬ አምናለሁ፡፡  
እንዲህ ያሉ አድማዎች መንግስት ላይ ምን ዓይነት ተጽዕኖ ያሳርፋሉ?
እንዲህ ያሉ አድማዎች የሚደረጉት መልዕክት ለማስተላለፍ ነው፡፡ መልዕክት ለማስተላለፍ ሌሎች አማራጮች ሳይኖሩ ሲቀር ህዝብ እንዲህ ያሉ መንገዶችን ለመጠቀም ይገደዳል፡፡ እነዚህ ችግሮች የመጡበትን ዋና ምክንያት ለይቶ ቀጥተኛ መልስ ካልተሰጠ ጉዳቱ ይጨምራል፡፡ አድማ የሚያደርጉ አካላትም እኮ ደልቷቸው አይደለም ሱቃቸውን የዘጉት፤ ሱቅ ሲዘጉ መቸገራቸው አይቀርም፡፡ ስለዚህ እነዚህ ችግሮች በቀላሉ የሚታዩ አይደሉም። መሰረታዊ የሆኑ ለረጅም ጊዜ ሲንከባለሉ የመጡ ናቸው፡፡ አሁንም ችግሩ አንድ ሳምንት ጠፍቶ ተመልሶ የሚመጣ አይነት ከሆነ፣ መሰረታዊ ችግሩ አልተፈታም ማለት ነው፡፡
በዚህ ሂደት አንዱ ከአንዱ የበለጠ ይጎዳል ማለት አይቻልም፡፡ ሁሉም ተያይዞ ነው የሚጎዳው። ተፅዕኖው በመንግስት ላይም ቀላል አይሆንም። ፈረንጅ ሀገር የሚደረጉ አድማዎች አሉ፡፡ ግን የእነሱ ምላሽ የሚያገኝበት የራሱ ጥበብ አለው፡፡ በኛ ሀገር እንዲህ ያለው አድማ መፍትሄ ሳይሰጠው የሚደጋገም ከሆነ  ጉዳቱ ቀላል አይሆንም፡፡ አድማው በየጊዜው ያዝ ለቀቅ እያለ የሚሄድ ከሆነ፣ ኢትዮጵያ በኢንቨስትመንት ተፈላጊነት ላይ ያላት ቦታ እየቀነሰ ሊመጣ ይችላል፡፡
የእነዚህ አድማዎችና ውጥረቶች መደጋገም ምን ያህል አሳሳቢ ነው?
ከብዙ ሰዎች ጋር ስወያይ፣ ጉዳዩ አሳሳቢ እንደሆነ ነው በመጨነቅ የሚናገሩት፡፡ በኔ አስተያየት፤ ከመንግስት በኩል ግን የችግሩ አሳሳቢነት ጎልቶ የወጣ አይመስልም፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መነሳቱ ጥሩ ነው፡፡ ነገር ግን በድጋሚ አስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከመጣ፣ እንደገና ኃይልን መምረጥ ነው የሚሆነው። እንዲህ ያለውን ችግር ለመፍታት የሚመረጠው ኃይል ነው ወይስ ውይይት? ይሄ ጠርቶ መቀመጥ አለበት፡፡ ሌላ አዲስ መፍትሄም መፈለግ ያሻል፡፡  
ለምሳሌ ምን ዓይነት መፍትሄ?
እኔ እንደሚገባኝ ጥያቄዎች ግልፅ አይደሉም። እንደየ አካባቢው ብዙ አይነት ናቸወ፡፡ የመሬት ጉዳይ የሙስና፣ የሃብት ፍትሃዊ ክፍፍል የመሳሰሉ ጉዳዮች ይነሳሉ፡፡ በየቦታው የሚነሱ ጉዳዮች ምን እንደሆኑ ተጠንተው መቅረብ አለባቸው፡፡ ሀገር ማስተዳደር እንዲህ ቀላል አይደለም፡፡ ህገ መንግስት ስላለ ብቻ ሀገር አለ ማለት አይደለም፡፡ የህዝብ ጥያቄ ተፈታ ማለት አይደለም፡፡
ህገ መንግስትን ሁልጊዜ መንከባከብ ያስፈልጋል። ጥያቄዎች በህገ መንግስት እንኳ የማይመለሱ ከሆነ፣ ሀገርን ለማዳን ሲባል ከተቃዋሚ ኃይሎች ጋር በጥያቄዎቻቸው ላይ መነጋገር ያስፈልጋል፡፡ ከባዱን ነገር ተጋፍጦ መፍትሄ መሻት ያስፈልጋል፡፡ ዋና ዋና ጥያቄዎችን ለይቶ፣ ከህዝብ ጋር ቁጭ ብሎ በመወያየት መመለስ ወሳኝ ነው፡፡ ይሄ ሊደረግ ይገባዋል ባይ ነኝ፡፡     

--------------------
                                      “በሀገሩ ጉዳይ የተገለለ ሰው መኖር የለበትም”  
                                         አቶ ሞሼ ሰሙ

      ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መነሳት በኋላ የተደረገው የንግድና የትራንስፖርት አገልግሎት ማቆም አድማ ተቃውሞው ማገርሸቱን ከማሳየት ባሻገር ምን?
ከአስቸኴይ ጊዜ አዋጁ በፊት የነበሩ እንቅስቃሴዎች  ወይም  አድማዎችና አሁን  የሚታዩት  ባህሪያቸው የተለያየ ነው፡፡ የመጀመሪያው ኢትዮጵያ ውስጥ የተፈጠረውን መሰረታዊ ኢኮኖሚያዊ ችግር ማዕከል አድርጎ የዲሞክራሲ፣ የሰብአዊ መብት፣ የሙስና፣ የመሬት አጠቃቀም፣ ፍትሃዊ የሀብት ክፍፍል ጥያቄዎች ላይ ያነጣጠረ ነበር፡፡ ኢህአዴግ ስልጣን ከያዘ ጀምሮ ባሉት ከ20 በላይ አመታት ውስጥ ተወልደው፣ በትምህርት ሂደት አልፈው ለአቅመ ስራ የደረሱ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ወጣቶች አሉ፡፡ እነዚህ ወጣቶች ራሳቸውን የሚችሉበት ስራ አለማግኘታቸው አንዱ ችግር ነበር፡፡ በዚህ ሳቢያ የተነሳው ተቃውሞ መንግሥት በወሰደው የማመቅ እርምጃ ሁነኛ ምላሽ ሳያገኝ በእንጥልጥል ነበር የቀረው፡፡ ይህ ችግር ባለበት ሁኔታ ደግሞ የነጋዴውን ሰርቶ የመኖር አቅም የሚፈታተን አሉታዊ የግብር ትመና መጣሉ የተዳፈነውን ተቃውሞ ቀስቅሶታል፡፡ ይሄ አጀንዳ ማቀጣጠያ ነው እንጂ ዋናው መንስኤ ለዘመናት የተከማቹ አስቀድሜ የገለፅኳቸው ችግሮች ድምር ነው፡፡ እነዚህ ችግሮች ታይቶ በማይታወቅ ደረጃ ለብዙ የህይወት መጥፋት ምክንያት ሆነዋል፡፡ ኢንዱስትሪና ፋብሪካዎችን እስከ ማቃጠል አድርሷል፡፡ ይሄ በኢትዮጵያ ታሪክ ውስጥ የተለመደ አይደለም፡፡ ምናልባት በፊት አውቶቡሶች ይሰበሩ ይሆናል እንጂ ህዝቡ መጠቀሚያው በሆኑ መሰረተ ልማቶች ላይ ጉዳት ሲያደርስ ታይቶ አይታወቅም፡፡ ይሄ የቁጣው ደረጃ ምን ያህል እንደሆነ ነው የሚያሳየው፡፡
የእነዚህ አድማዎች ኢኮኖሚያዊ አንደምታዎች እንዴት ይገለጻል? በኢንቨስትመንት ላይ የሚያሳድረው ተጽዕኖስ?
ከኢንቨስትመንት ጋር በተያያዘ የሚያሳድረው ተፅዕኖ አለ፡፡ የውጭ ሀገር ኢንቨስተሮች ባለመረጋጋት መሃል ባለች ሀገር ኢንቨስት ለማድረግ ፍላጎቱ አይኖራቸውም፡፡ ሰላም በሌለበት ሀገር ውስጥ ንብረቱን ይዞ መጥቶ ኢንቨስት ለማድረግ የሚፈለግ አይኖርም፡፡ ሰላም፣ መረጋጋት፣ በቂ የኃይል አቅርቦት፣ የሰው ኃይል--- እነዚህን ፈትሾ ነው ኢንቨስተር የሚመጣው፡፡ አድማና አለመረጋጋት መኖሩን ሲያውቅ ግን ሃሳቡን ይሰርዛል፡፡ ኢንቨስተሮች ከዚህ ሽሽት ወደዚህ ሀገር ባመምጣታቸው ሊገኝ የሚችልን የውጪ ምንዛሬ ያሳጣል፣ የስራ እድል አይኖርም፡፡ ገበያውም በአቅርቦት ችግር መመታቱ አይቀርም፡፡ በተለይ የትራንስፖርት መቋረጥ በዚህ ላይ ቀጥተኛ ተፅዕኖ አለው፡፡ በሌላ በኩል፤ የሀገር ቤት ባለሀብትም በኢኮኖሚው ላይ የሚኖረውን አስተዋፅኦ መገደቡ አይቀርም፡፡ ገንዘቡን በአገሩ ላይ ኢንቨስት ከማድረግ ይልቅ በውጭ ምንዛሬ እየለወጠ ወደ ውጪ ማሸሽ፣ ገንዘቡ ወደ ሀገሪቱ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ እንዳይገባ አፍኖ መያዝ፣ የራሱን የንግድ እንቅስቃሴ ማቀዝቀዝ፣ ፋብሪካ መዝጋትና የመሳሰሉት ውስጥ ይገባል፡፡ ይሄን የሚያደርገው ሀብቱ እንዳይባክን በመስጋት ነው፡፡ ይሄ ደግሞ በፊናው በኢኮኖሚ ውስጥ መንቀሳቀስ የሚገባውን ገንዘብ ይገድባል፣ ሀገሪቱ ከውጪ ገበያ ገቢ እንዳታገኝ ያደርጋል የንግድ ተቋማትና ፋብሪካዎች በቆሙ ቁጥር ለኪሳራ መዳረጋቸው አይቀርም፡፡ በዚህ ደግሞ መንግስት ከግብር የሚያገኘውን ገቢ ያጣል፡፡
ሌላው ደግሞ ማህበረሰቡ በቁጣ ተነሳስቶ የሚያደርሰውን ውድመት ተከትሎ፣ መንግስት ንብረቱን ለባለቤቶቹ የመተካት ግዴታ አለበት፡፡ እንደ አጋጣሚ ሆኖ ሀገሪቱ ለኩባንያዎች አለማቀፍ የኢንሹራንስ ሽፋን የላትም፡፡ ይህ አለመኖሩ ደግሞ መንግስት ለወደመ ንብረት ከበጀቱ ላይ ቀንሶ ለተጎጂዎች እንዲከፍል ነው የሚያስገድደው፡፡ ሌላው በዚህ ሂደት ውስጥ እንዲህ ያሉ ውጥረቶች ያለ መፍትሄ በተራዘሙ ቁጥር በማህበረሰቡ ውስጥ ግንኙነቱ ይላላል፣ አንድነቱ አደጋ ላይ ይወድቃል፣ ሰዎች ተስፋ በመቁረጥ ስደትን አማራጭ ሊያደርጉ ይችላሉ፡፡ ችግሮቹ  በጊዜ እልባት ካላገኙ በሰው ልብ ውስጥ ተቀብረው የሚፈነዱበትን የተመቻቸ ሁኔታና ጊዜም ሊጠብቁ ይችላሉ፡፡
በዚህ ግርግር መሃል ደግሞ በአቋራጭ ለመክበር የሚፈልጉ ሰዎች ገበያ ላይ ያሉ እቃዎችን ይደብቃሉ፣ በገበያው ላይ እጥረት ለመፍጠር ይሯሯጣሉ፡፡ ይሄ ደግሞ በህብረተሰቡ ላይ የገበያ እጥረት ይፈጥራል፤ የዋጋ ንረትም ያስከትላል፡፡ ከዚህ ሲያልፍ ደግሞ የቱሪዝም ገቢያችን ይቀዛቀዛል፡፡ ጎብኚዎች ቅድሚያ ለህይወታቸው ደህንነትና ሰላም ይፈልጋሉ፡፡ ቱሪስቶች ባለመምጣታቸው ደግሞ በዘርፉ ሰንሰለት ውስጥ ያሉ ሆቴሎች፣ አስጎብኚዎች፣ የትራንስፖርት አገልግሎት ሰጪዎች ይጎዳሉ፡፡
አገሪቱ ለውጭ ኢንቨስተሮች  አለማቀፍ ኢንሹራንስ መግባት ያስፈልጋታል ማለት ነው?
ኩባንያዎች ላይ ጉዳት የሚደርሰው በተቃውሞ በሚፈጠር ቀውስ ብቻ አይደለም፡፡ በየጊዜው የክልል ድንበር ግጭቶች፣ የብሔር ግጭቶች የመሳሰሉ ይፈጠራሉ፡፡ በዚህ መሃል ንብረት ሊወድም ይችላል፤ የውጭ ሀገራት ሰዎች ንብረት ሲወድም በሀገር ውስጥ ኢንሹራንስ ለመሸፈን ከባድ ነው፡፡ ስለዚህ የውጭ ሀገር ኢንሹራንስ መኖሩ እንደ ኢትዮጵያ ላለ ሀገር በጣም ጠቃሚ ነው፡፡ እነዚህ ኢንቨስተሮች አደጋ በንብረታቸው ላይ ቢደርስ፣አለማቀፍ አስተማማኝ ኢንሹራንስ እንደተገባላቸው ሲያውቁ ይረጋጋሉ፡፡ እንደ አንድ ሁነኛ ዋስትና ነው የሚቆጥሩት፡፡ ይህ ባልሆነበት ለእነዚህ ሰዎች ለንብረታቸው መተኪያ ስትከፍል ዞሮ ዞሮ የህብረተሰቡ ኪስ ነው የሚጎዳው። ለመሰረተ ልማት ይውል የነበረውና ከሰው የተሰበሰበው ግብር ነው ተመልሶ ለነዚህ ሰዎች የካሳ ክፍያ የሚውለው። ከዚህ ውጭ  መንግስት ያለ አግባብ ተጨማሪ ገንዘብ ካላተመ በስተቀር ከየትም አይመጣም፡፡
በእንዲህ ያሉ አድማዎች የመጀመሪያ ተጎጂ የሚሆነው ማን ነው? መንግሥት ላይ የሚፈጥረው ጫናስ ምን ያህል ነው?
ሁለት የማህበረሰብ ክፍሎች በጣም ተጎጂ ይሆናሉ፡፡ አንደኛ ለእለት ጉርሳቸው በየእለቱ የሚያገኙትን ገቢ የሚያጡ ዜጎች አሉ፡፡ በሸክም ስራ፣ በጥበቃ፣ በጫኝ አውራጅነት የሚሰሩ፣ የእለት ገቢ ላይ ብቻ ተመስርተው የሚኖሩ አሉ፡፡ እንቅስቃሴዎች ሲቆሙ እነዚህ ሰዎች የመጀመሪያዎቹ ተጎጂዎች ይሆናሉ፡፡ ሁለተኛ በአጠቃላይ ማህበረሰቡ ተጎጂ ይሆናል፡፡ አብዛኛው ሰው ኑሮው ከእጅ ወደ አፍ ነው፡፡ በአቅርቦቱ መቋረጥ የእለት ጉርሱን የሚያጣው የማህበረሰብ ክፍል ቀላል አይደለም፡፡ ሶስተኛ ተጎጂ የሚሆነው ሀገር ነው፡፡ መንግስት ተገቢውን ግብር የማግኘት እድሉን ስለሚያጣ ስራ መስራት አይችልም፡፡ እንቅስቃሴ የሌለበት ኢኮኖሚ ደግሞ የሚያስከትለው ተፅዕኖ ቀላል አይሆንም፡፡ ከፍተኛ አለመረጋጋትም ያስከትላል፡፡
የእነዚህ አድማዎች ፖለቲካዊ አንድምታስ ምንድን ነው?
እነዚህን አድማዎች በመጀመሪያ ያመጣው ህብረተሰቡ በመንግሥት ላይ ያለው መተማመን መሸርሸሩ ነው፡፡ መንግስት ለጥያቄ ምላሽ ይሰጣል ብሎ የሚያምን ማህበረሰብ፣ ለህዝባዊ እምቢተኝነት ወይም ለአድማ አይነሳሳም፡፡ መንግስት ቦታ እያጣ መምጣቱን ማሳያው ይኸው ህዝባዊ እምቢተኝነት ነው፡፡ አንድ ማህበረሰብ በራሱና በቤተሰቡ ላይ ጉዳት ሊያስከትል የሚችል እንቅስቃሴ ሲያደርግ ተስፋ የመቁረጥ ምልክት መሆኑ  ግልፅ ነው፡፡ የስራ እድል የፈጠረለት ተቋም ላይ እርምጃ ሲወስድ ተስፋ የመቁረጥ ምልክት ነው፡፡ አሁን ከግብር ጋር በተያያዘ የመጣው እምቢተኝነት፣ የመጀመሪያው እምቢተኝነት ተቀጥላ ነው፡፡ ስለዚህ በቀጣይ አመት ምን እንደሚፈጠር ለመገመትም አስቸጋሪ ነው፡፡ ለምሳሌ የተጣለው ግብር ከ40 በመቶ በላይ ስህተት ነበር ብለዋል፤ ጠ/ሚኒስትሩ፡፡ 40 በመቶ ስህተት ካለ፣ ለእርማትም የሚመች አይደለም ማለት ነው፡፡ ስለዚህ ወዲያው ነው መቆም የነበረበት፡፡ እንደገና እንደ አዲስ ነው ጉዳዩ መታየት ያለበት፡፡ በዚህ ምክንያት ለተፈጠረው ምስቅልቅል፣ ቁጣ እና አለመረጋጋት ኃላፊነትስ የሚወስደው ማን ነው? መንግስት ትመናው 40 በመቶ  ስህተት አለው ብሎ ካመነ፣ለተፈጠረው ችግር ኃላፊነት መውሰድ አለበት፡፡
እነዚህ አድማዎች በመንግስት ለይስ የሚኖራቸው ተፅዕኖ ምን ያህል ነው?
ህዝቡ መጀመሪያ የሚያደርገው እነዚህ በደሎችና እሮሮዎችን ማሰማት ነው፡፡ ለእነዚህ ምላሽ ሲያጣ ደግሞ ተደራጅቶ በአንድ ላይ ወጥቶ መንግሥት ላይ ግፊት ይፈጥራል፡፡ ጉዳዩ ወደ ዲሞክራሲ፣ ፍትሃዊ የሀብት ክፍፍል፣ የህግ የበላይነት ጥያቄዎች ሊያመራ ይችላል፡፡ ይሄን ደግሞ ህዝብ በራሱ እንዲከውነው እየተገደደ ነው ያለው፡፡ ምክንያቱም ሊወክሉት የሚችሉ ኃይሎች፣ አጀንዳውን ተቀብለው ማስተናገድ ላይ ውስንነት አለባቸው፡፡ ይሄ እንግዲህ ችግሩ ምን ያህል መልኩንና ቅርፁን እየለወጠ እንደመጣ ያሳያል፡፡ ህዝብ እዚህ ደረጃ ላይ ሲደርስ ደግሞ ሁኔታው አስቸጋሪ ነው የሚሆነው፡፡ የዲሞክራሲ፣ የህግ የበላይነት፣ ፍትሃዊ የሀብት ክፍፍል ጥያቄዎች በፊት በተቃዋሚ ፓርቲዎች ወይም በፕሬሶች ነበር የሚነሱት፡፡ እነሱ በየጊዜው እየተመናመኑ ከጨዋታ ውጪ ሲሆኑ፣ ህዝቡ ትግሉን ራሱ ለመውሰድ ተገደደ፡፡ ይሄ ፖለቲካዊ አንድምታው ቀላል አይደለም፡፡ ልክ እንደ አፄው ሥርአት ጊዜ ፋታ … ትንሽ ፋታ በማለት ብቻ የሚቆም አይደለም፡፡ ችግሮች በፋታ የሚፈቱ አይመስልም፡፡
ለዚህ ሁሉ ችግር መፍትሄው ምንድን ነው?
አጭሩ መፍትሄ ትክክለኛውን የህዝብ ስሜትና ጥያቄ አውቆ፣ ለዚያ የሚመጥን መልስ መስጠት ብቻ ነው፡፡ የህዝቡን ጥያቄ ሁሉ የውጭ ኃይሎች ሴራና የፀረ ሰላም ኃይሎች ነው ብሎ ችላ ማለት ዋጋ ያስከፍላል፡፡ መቼም ህዝብ አይሳሳትም። በዚህ ደረጃ በውጪ ኃይሎች የተሳሳተ ህዝብ አለ ከተባለም፣ ለስህተቱ ተጠያቂ የሚሆነው መንግስት ነው፡፡ ምክንያቱም መንግስት ለህዝቡ ተስፋ የሚሰጥ ስራ አልሰራም ማለት ነው፡፡ ሌላው መፍትሄ ከህዝቡ ጋር መወያየት ነው፡፡ ጊዜ ለሁሉም ነገር ወሳኝ ነው፡፡
በጊዜ መልስ መስጠትና ማረሚያ መውሰድ ከፀፀት ያድናል፡፡ ይሄ ጉዳይ ለሥርአቱ ብቻ ሳይሆን ለሀገሪቱም አደጋ ነው፡፡ ስለዚህ በሀገሩ ጉዳይ የተገለለ ሰው መኖር የለበትም፤ በሀገሩ ጉዳይ ማንም ሰው የመገለል ስሜት እንዲሰማው መደረግ የለበትም፡፡