Administrator

Administrator

ሰሜን ኮርያ ጃፓንንና ዋና ዋና የአሜሪካ ወታደራዊ ካምፖችን የማጥቃት ብቃት ያለውን አዲስ የመካከለኛ ርቀት ተወንጫፊ ባለስቲክ ሚሳኤል በገፍ ለማምረት ዝግጅቷን ማጠናቀቋን የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ኪም ጆንግ ኡን ባለፈው ማክሰኞ አስታወቁ፡፡
ፕሬዚዳንቱ ፑክጉሶንግ 2 የተባለውን ባለስቲክ ሚሳኤል በብዛት ለማምረትና በአገሪቱ ስትራቴጂካዊ የጦር ሰፈሮች በማስፈር፣ ለተልዕኮ ዝግጁ እንዲደረጉ ትዕዛዝ እንደሰጡ ማስታወቃቸውን የዘገበው ዘ ኢንዲፔንደንት፣ ፕሬዚዳንት ኡንም አዲሱ ባለስቲክ ሚሳኤል ብቃቱ በሙከራ መረጋገጡንና ውጤታማ መሆኑን በመጥቀስ፣ ኢላማውን አነጣጥሮ ያለ አንዳች ስህተት መምታት የሚችለው የዚህ ሚሳኤል ባለቤት በመሆናችን ኩራት ይሰማናል ማለታቸውንም ዘገባው ገልጧል፡፡
የኒውክሌርና የሚሳኤል ፕሮግራሟን እንድታቋርጥ ቻይና እና አሜሪካን ጨምሮ ከተቀረው አለም በተደጋጋሚ እየቀረበላት ያለውን ጥሪ ላለመስማት የወሰነቺው ሰሜን ኮርያ፤ ከአሜሪካ የሚቃጣብኝን ወረራ ለመመከት በበቂ ሁኔታ መታጠቅ ግድ ይለኛልና አልሰማችሁም ብላለች፡፡
ሰሜን ኮርያ በዚህ አንድ ሳምንት ብቻ ሁለት የሚሳኤል ሙከራዎችን ማድረጓን ያስታወሰው ዘገባው፤ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤትም አገሪቱ የተጣለባትን ማዕቀብ በመጣስ እያደረገቺው ያለውን እንቅስቃሴ በተመለከተ ሰሞኑን ተሰብስቦ ውሳኔ ላይ ይደርሳል ተብሎ እንደሚጠበቅም አክሎ ገልጧል፡፡

  88 የባንክ አካውንቶችና የ14 ኩባንያዎች ሃብቶች እንዳይንቀሳቀሱ በፍ/ ቤት ታግደዋል

       በምርጫ ቢሸነፉም ስልጣኔን አልለቅም ብለው ሲያንገራግሩ ከቆዩ በኋላ በደረሰባቸው ከፍተኛ ጫና ባለፈው ጥር ወር አገር ጥለው የተሰደዱት የቀድሞው የጋምቢያ ፕሬዚዳንት ያያ ጃሜህ፤ ከመንግስት ካዘና ከ50 ሚሊዮን ዶላር በላይ ዘርፈዋል መባሉን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ያያ ጃሜህ ባለፉት አስር አመታት ብቻ ከ50 ሚሊዮን ዶላር በላይ የህዝብ ገንዘብ ዘርፈው ከአገር ማስወጣታቸውን የአገሪቱ የፍትህ ሚኒስቴር ባለፈው ሰኞ ማስታወቁን የጠቆመው ዘገባው፤ በአገር ውስጥ ያሉ የጃሜህ ሃብቶችና ንብረቶች በሙሉ እንዳይንቀሳቀሱ በፍርድ ቤት መታገዳቸውንም ገልጧል፡፡ ከቀድሞው ፕሬዚዳንት ጋር ንክኪ አላቸው የተባሉ 14 ኩባንያዎች እና በስማቸው ወይም በወዳጆቻቸው ስም የተከፈቱ 88 የባንክ አካውንቶችም እንዳይንቀሳቀሱ በፍርድ ቤት መታገዳቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በርካታ መኪኖችን ጨምሮ በፕሬዚዳንቱ ስም የተመዘገቡ በርካታ ንብረቶችም መታገዳቸውን አብራርቷል፡፡
ጃሜህ ከመንግስት ካዝና የዘረፉት ገንዘብ 11 ሚሊዮን ዶላር ያህል ይሆናል ተብሎ ሲገመት የቆየ ቢሆንም፣ የአገሪቱ ፍርድ ቤት ባደረገው ምርመራ ገንዘቡ ከ50 ሚሊዮን ዶላር በላይ እንደሚደርስ ማረጋገጡን እንዳስታወቀ ቢቢሲ በዘገባው አስረድቷል፡፡
ምዕራብ አፍሪካዊቷን አገር ለ22 አመታት የመሩትና ባለፈው ታህሳስ በተካሄደው ምርጫ በተቀናቃኛቸው አዳማ ባሮው መሸነፋቸውን ተከትሎ ስልጣን አልለቅም በማለታቸው የጎረቤት አገራት ባሳደሩባቸው ከፍተኛ ጫና ወደ ኢኳቶሪያል ጊኒ የተሰደዱት ያያ ጃሜህ፣ በርካታ ውድ መኪኖችንና ሌሎች ንብረቶቻቸውን ይዘው እንደሄዱ ዘገባው አስታውሷል፡፡

 የእርስ በእርስ ግጭት እየተስፋፋ በመጣባት ማይንማር በየቀኑ እድሜያቸው ከ5 አመት በታች የሆኑ 150 ያህል ህጻናት ለህልፈተ ህይወት በመዳረግ ላይ እንደሚገኙ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ባለፈው ማክሰኞ ማስታወቁን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
በአገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች እየተስፋፋ በመጣው የእርስ በእርስ ግጭት፣ በድህነት እና በበሽታ ለህልፈተ ህይወት የሚዳረጉ ህጻናት ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ ነው ያለው በተባበሩት መንግስታት ድርጅት የህጻናት መርጃ ድርጅት፣ በተለይም ግጭት ባለባቸው አካባቢዎች የጤና አገልግሎት በመቋረጡ በርካታ ህጻናት በኒሞኒያና በሌሎች በሽታዎች እየተሰቃዩ፣ ምንም አይነት የህክምና እርዳታ ሳያገኙ ለህልፈተ ህይወት እንደሚዳረጉም አስታውቋል፡፡
በመላ አገሪቱ 2.2 ሚሊዮን ያህል ህጻናት የሰብአዊ ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸው የጠቆመው ድርጅቱ፣ የአገሪቱ መንግስት እየተስፋፋ የመጣው ብጥብጥና የእርስ በእርስ ግጭት ሰለባ ለሆኑት ለእነዚሁ ህጻናት አስቸኳይ የሰብአዊ ድጋፍ ማድረግና በህጻናቱ ላይ የሚፈጸሙ የመብቶች ጥሰቶችን ለማስቆም አፋጣኝ እርምጃ እንዲወስድም ጠይቋል፡፡
ከግማሽ በላይ የሚሆኑ የአገሪቱ ህጻናት ከድህነት ወለል በታች የሆነ አስከፊ ኑሮ እንደሚመሩ የጠቆመው ዘገባው፣ 30 በመቶ ያህሉ የማይንማር ህጻናት የከፋ የምግብ እጥረት ተጠቂ እንደሆኑም አመልክቷል፡፡

  የህንድ ህዝብ 1.32 ቢሊዮን ሲደርስ፣ የቻይና ግን 1.29 ቢሊዮን ቢደርስ ነው ተብሏል

     የቻይና የህዝብ ቁጥር ሆን ተብሎ በመጋነን በ90 ሚሊዮን ያህል እንዲጨምር መደረጉንና 1.32 ቢሊዮን ህዝብ ያላት ህንድ በቻይና ተይዞ የነበረውን የዓለማችን የህዝብ ብዛት ደረጃ መረከብ እንደምትችል በጥናት ማረጋገጣቸውን አንድ ታዋቂ  የስነ ህዝብ ተመራማሪ ማስታወቃቸውን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
በአሜሪካው የዊስከንሰን ማዲሰን ዩኒቨርሲቲ የስነ ህዝብ ተመራማሪ የሆኑትና በህንድ እና በቻይና የህዝብ ብዛት ዙሪያ ጥናት ሲሰሩ የቆዩት ዪ ፉክሲያን፣ የቻይና ባለሙያዎች በህዝብ ቆጠራ ወቅት ሆን ብለው የህዝቡን ቁጥር እንዳጋነኑት በመጠቆም የአገሪቱ ህዝብ ቁጥር በ90 ሚሊዮን እንዲጨምር ማድረጋቸውን ገልጸዋል፡፡
የቻይና የህዝብ ቁጥር የአገሪቱ መንግስት እንደሚለው 1.38 ቢሊዮን ሳይሆን፣ ከዚያ ያነሰ ነው፤ የህዝብ ቁጥሩ እስካለፈው የፈረንጆች አመት 2016 መጨረሻ ቢበዛ 1.29 ቢሊዮን ያህል ቢደርስ ነው፤ በመሆኑም ህንድ በህዝብ ብዛት ከቻይና በመቅደም በአንደኛነት እንድትቀመጥ ያደርጋታል ብለዋል - ተመራማሪው፡፡
ተመራማሪው ይህን ቢሉም በርካታ ህንዳውያንና ቻይናውያን የስነህዝብ ባለሙያዎች ግን የተመራማሪውን ድምዳሜ በበቂ መረጃዎች ላይ ያልተመሰረተና ስሜታዊነት የሚንጸባረቅበት፣ ሙያዊ ያልሆነ አደገኛ ነገር ነው በማለት በስፋት እያጣጣሉት እንደሚገኙም ዘገባው ገልጧል፡፡

   በዩኒቨርሲቲው የ81 አመታት ታሪክ በዚህ መልኩ የተመረቀ የመጀመሪያው ተማሪ ነው
     በታዋቂው ሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ የዘንድሮ የእንግሊዘኛ ቋንቋ ተመራቂ የሆነውና ለመመረቂያ ጽሁፍ የራፕ ሙዚቃ አልበም ሰርቶ ያቀረበው የሃያ አመቱ ወጣት ኦባሲ ሻው፣ በትምህርት ክፍሉ ተቀባይነት በማግኘት በማዕረግ መመረቁን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
በዩኒቨርሲቲው የ81 አመታት ታሪክ የሙዚቃ አልበምን በመመረቂያ ጽሁፍነት አቅርቦ በማዕረግ በመመረቅ የመጀመሪያው ተማሪ የሆነው ኦባሲ ሻው፣ በራፕ ስልት የተቀነቀኑ 11 ሙዚቃዎቹን ያካተተበትንና “ሊሚናል ማይንድስ” የሚል ስያሜ የሰጠውን አልበሙን ለመመረቂያ ጽሁፍነት እንዲያቀርብ ሃሳብ የሰጡት እናቱ እንደሆኑ ተናግሯል፡፡
ወጣቱ የራፕ የሙዚቃ አልበም በመመረቂያ ጽሁፍነት የማቅረብ ሃሳቡ በዩኒቨርሲቲው ተቀባይነት ያገኛል ብሎ በፍጹም ባይገምትም፣ የእናቱን ሃሳብ ተከትሎ የመመረቂያ ፕሮጀክት ፕሮፖዛሉን ለትምህርት ክፍሉ ሃላፊዎች ሲያቀርብ ያገኘው በጎ ምላሽ ግን በሃሳቡ እንዲገፋበት እንዳበረታታው ይናገራል፡፡
“ኤ” ውጤት ያስገኘለትንና በማዕረግ ያስመረቀውን ይህንን የራፕ ሙዚቃ አልበሙን ሰርቶ ለማጠናቀቅ አንድ አመት ያህል እንደወሰደበት የጠቆመው ዘገባው፣ ወጣቱ በአልበሙ ባካተታቸው ሙዚቃዎቹ የጥቁሮችን ህይወት፣ የቀለም ልዩነትንና ሌሎች ርዕሰ ጉዳዮችን መዳሰሱንም አክሎ ገልጧል፡፡

  ከእለታት አንድ ቀን አንድ ዛፍ ቆራጭ ከወንዝ ዳር ዛፍ እየቆረጠ ሳለ፣ መጥረቢያው ከእጁ ወጥቶ፣ ግንዱ ላይ ነጥሮ ወንዙ ውስጥ ወደቀበት፡፡ በወንዙ ዳር ቆሞ፣
“አዬ ጉድ! የእንጀራ ገመዴ ተበጠሰ!” እያለ ሲያለቅስ፤ የውሃው አማልክት መልክተኛ ሜርኩሪ ብቅ አለና፤
“ምን ሆነህ ታለቅሳለህ? ለምን አዘንክ?” አለው፡፡
“የሥራ መጥረቢያዬ ወንዝ ውስጥ ገባብኝ” አለው፡፡
ሜርኩሪ ወደ ውሃው በዋና ጠለቀና አንድ የወርቅ መጥረቢያ ይዞ ወጣ፡፡ ከዚያም፤ይሄ መጥረቢያ ያንተ
ነውን?” ሲል ጠየቀው፡፡
ዛፍ ቆራጩም፤
“የለም ይሄ የእኔ መጥረቢያ አይደለም” አለና መለሰ፡፡
ሜርኩሪ ለሁለተኛ ጊዜ በዋና ወደ ወንዙ ጠለቀና አንድ ሌላ ከብር የተሰራ መጥረቢያ ይዞ ብቅ አለ፡፡
“ይሄስ ያንተ ነውን?” አለና ጠየቀው፡፡
“እረ የለም፤ ይሄ የእኔ አይደለም” አለ ዛፍ ቆራጩ፡፡
ሜርኩሪ ለሦስተኛ ጊዜ ወደ ውሃው ጠልቆ ሌላ ተራ መጥረቢያ አወጣ
“ይሄስ?” አለው
ዛፍ ቆራጩ፤“በትክክል ይሄኛው የእኔ መጥረቢያ ነው!” አለ በከፍተኛ ሐሴት ተውጦ፡፡ “እጅግ አድርጌ
አመሰግናለሁ!” አለ፡፡
ሜርኩሪም በጣም ረክቶ፤
“ስለ ታማኝነትህ እነዚህን ሁለት መጥረቢያዎች - ከወርቅ የተሰራውንና ከብር የተሰራውን፤ ሸልሜሃለሁ!”
ብሎ ሰጠው፡፡
ዛፍ ቆራጩ ወደ ሰፈሩ ሲደርስ፤
“ዛሬ ትልቅ ፌሽታ ነው ያጋጠመኝ!” ብሎ የሆነውን ሁሉ ለባልንጀሮቹ ነገራቸው፡፡
ከዛፍ ቆራጮቹ አንዱ ቅናት ይይዘዋል፡፡ ስለዚህ ወደ ወንዙ ሄዶ፣እሱም እድሉን ለመሞከር ይወስናል፡፡
ቀናተኛው ዛፍ ቆራጭ፤ አንድ ከወንዙ ዳር ያለ ዛፍ መቁረጥ ይጀምራል፡፡ ከዚያም አውቆ ወደ ውሃው
መጥረቢያውን ይወረውረውና፤
“ወይኔ መጥረቢያዬ! ወይኔ የሥራ መሣሪያዬ!” እያለ ይጮሃል፡፡
ይሄኔ ሜርኩሪ ብቅ አለ፡፡
“ምን ሆነህ ነው የምትጮኸው?”
“መጥረቢያዬ በሥራ ላይ ሳለሁ ውሃ ውስጥ ወደቀብኝ” አለ፡፡
ሜርኩሪ ወደ ውሃ ውስጥ ጠለቀና አንድ የወርቅ መጥረቢያ ይዞ ብቅ አለ፤ ከዚያም
“የጠፋብህ መጥረቢያ…” ብሎ ሊጠይቀው ሲጀምር፤
ዛፍ ቆራጩ በስግብግብነት፤
“አዎን፡፡ የኔ የራሴ መጥረቢያ ነው! የገዛ ራሴ መጥረቢያ ነው!!” አለና ሁለት እጆቹን ዘረጋ፡፡
ሜርኩሪ የማይታመን ሰው በመሆኑ በጣም በመከፋት፤
“አንተ ታማኝ አይደለህም! ስለዚህም እንኳንስ፤ የወርቅ መጥረቢያ፣ ውሃ ውስጥ የጣልከውን የራስህን
ተራ መጥረቢያም፣ አታገኝም!” አለው፡፡
*   *   *
ታማኝነት የህይወታችን መሰረት መሆን አለበት፡፡ ለሥራ ታማኝ መሆን አለብን፡፡ ለእውቀት ታማኝ
መሆን አለብን፡፡ ለፖለቲካ ታማኝ መሆን አለብን፡፡ ለኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴያችን ታማኝ መሆን አለብን፡፡
ከሁሉ በላይ ደግሞ ለሀገራችንና ለህዝባችን ታማኝ መሆን አለብን፡፡ በሌሎች ላይ ልናደርገው ያሰብነውን ወይም ያደረግነውን በራሳችን ላይ ሲሆን የምንሸሽ፣ አሊያም መመሪያ የምናወጣበት ከሆነ፣ ታማኝነት የጐደለው ድርጊት ነው፡፡ “ሲያቃጥል በማንኪያ፣ ሲበርድ በእጅ” የምንል ከሆነ ታማኝነት የጐደለው ድርጊት ነው፡፡ “እኔ ከሞትኩ ሰርዶ አይብቀል” የምንል ከሆነ፣ ታማኝነት የጐደለው ድርጊት ነው፡፡
ጐር ቫይዳል ምቀኝነትን ሲገልፅ፤ “ጓደኛዬ ሲሳካለት፣ አንድ ነገር ከውስጤ ይሞታል/ይቀንሳል”
እንዳለው፤ ጓደኛችን የተሻለ አገኘ ብለን ዐይናችን የሚቀላ ከሆነ፣ ታማኝነት የጐደለው መንፈስ ነው። “ጐረቤታችን ጫጩት ሲያረባ ስናይ፣ እኛ ሸለምጥማጥ ማርባት የምንጀምር” ከሆነ፣ ፍፁም ታማኝነት የጐደለው የምቀኝነት ድርጊት ነው፡፡ ለእድገት የበቃ ባልደረባችን በደስታ ሲጥለቀለቅ ስናይ፣ እንባ የሚተናነቀን ከሆነ ፈርዶብናል ማለት ነው፡፡ የ”ተያይዘን እንለቅ” ፍልስፍና የትም አያደርሰንም - እርግማን ነው፡፡ በሌሎች ደስታ ውስጥ የእኛን ደስታ ለማየት መቻል አለብን፡፡ ደስታችንን ለሌሎች እናጋራ፡፡ ራስ ወዳድነትን እንታገል!
“ደስታን ከራሱ ጋር፣ አጥብቆ ያሰረ
ክንፍ - ያላትን ህይወት፣ ትንፋሽ አሳጠረ፡፡
ደስታ እየከነፈች፣ የሳማት ሰው ግና
የዘለዓለም ፀሀይ ይሞቀዋል ገና”፤ እንዳለው ነው ዊልያም ብሌክ፡፡
ደስታችን የአገር ይሁን እንደ ማለት ነው፡፡ ደስታ የእኔና የእኔ ብቻ ይሁን ብሎ የሙጥኝ አለማለት ነው። ከአገር ካዝና የወጣ ደስታ፤ የአገር ነውና ለህዝብ እናዳርሰው፡፡ ለራሳችን ሸሽገን አንቀራመተው ማለት ነው። የጋራ ቤታችንን እናስብ፡፡ በፓርቲ አጥር አንታጠር፡፡ ደፋር - መሀይም ብቻ ሳይሆን፣ ጭምት - ምሁር የሚኖርባትም አገር እናልም! ዕቡይ - ምሁር ብቻ ሳይሆን ያልተማረ - ጨዋ ህዝብ ያላት አገር እናስብ። ከፓርቲም ውጪ በቤተሰብ፣ በቢሮ፣ በተቋም፣ በንግድ ድርጅት ውስጥ የሚኖር ነፃ ዜጋ አለ ብለን፣ ከሳጥን ውጪ እንመልከት! ቢያንስ ባስበው ያስበኛል ብሎ ግንዛቤ መውሰድ ያባት ነው፡፡ “የእኔ ወንበር እስካልተነካች ድረስ” የሚል እሳቤ፤ ኃላፊነትን ዘንግቶ አጥር ማጠር፣ ረጅም ጊዜ መኖርን ከዘለዓለማዊነት ጋር ማምታታት ነው (Mistaking Longevity for immortality እንደ ማለት ነው)፡፡ በዚህም እሳቤ ምክንያት ነው መተካካትን ከብወዛ ጋራ አንድ አድርገን (Mistaking Replacement for Reshuffling እንደ ማለት) የምናየው፡፡ ወደድንም ጠላንም ቢያንስ ማንም ሰው ሊተካ የሚችል ነው፤ የማይተካ የለም (No one is indispensable) የሚለውን ሁለንተናዊ መርህ ያለ ራስ ወዳድነት፤ ያለ ምቀኝነት እንቀበል፡፡
ከአጠቃላይ ነባራዊ እውነታው፤ የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር፤ አናመልጥም፡፡ እውነታውን ተቀብሎ መፍትሄውን መሻት ከአላስፈላጊና ከማናመልጥበት ሽሽት ይገላግለናል፡፡ አገርም ለቅቀን እንሽሽ ብንል አይሆንም፡፡ ከራስ የህሊና ቁስል ማምለጥ አይቻልምና፡፡ የጊዜ ጉዳይ ነው እንጂ የናዚም ወታደር ይያዛል፤ ተብሏል፡፡ በመሸሽ፣ በመሸሸግና ሌላ አገር በድሎት ከመኖር ጋር ራስን ማስተሳሰር ቢያንስ የዋህነት ነው። እንኳን በባሌ በቦሌም ምቾት ቅርብ አደለም፡፡ ምቾትና ነፃነትን በሌላ ምድር ማግኘት ቀላል አይደለም፡፡ በሰሜንኛ፤“ጠላ አገኛለሁ ብለህ ውሃ ረግጠህ አትሂድ”ይባላል፡፡ በወላይትኛ ደግሞ፤“በውሃ የሚያቦኩበት አገር መጥፎ ነው ብላ፤ በምራቅ የሚያቦኩበት አገር ደረሰች”ማለት ነው፡፡ በማህል አገርኛ፤“ከድጡ ወደ ማጡ” ብለው ያጠቃልሉት ይሆናል፡፡ ብቻ ከዚህ ይሰውረን!!

• ፓርቲ በመንግስት ተቋማት ውስጥ ጣልቃ መግባቱ መገታት አለበት
• ተቃዋሚዎች በፓርላማ አለመኖራቸው ለስርአቱ ስጋት ነው ተባለ

የፌደራል ስርአቱ በህገ መንግስቱ መሰረት በአግባቡ እየተተገበረ አለመሆኑ፣ የሀገሪቱን አንድነት ስጋት ላይ እንደጣለ ሰሞኑን የቀረቡት ጥናቶች ያመለከቱ ሲሆን በፓርላማው የተቃዋሚ ድምፅ አለመኖሩም ለፌደራል ስርአቱ ስጋት ነው ተብሏል፡፡
በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ አዘጋጅነት ከትናንት በስቲያ በተከናወነ የአንድ ቀን አውደ ጥናት ላይ በዩኒቨርሲቲው ምሁራን “በፌደራል ስርአቱ ላይ” የቀረቡ ጥናቶችን መነሻ በማድረግ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተሳተፉበት ሰፊ ውይይት ተደርጓል፡፡ በመድረኩ ላይ ጥናታዊ ፅሁፍ ካቀረቡት ምሁራን መካከል ፕ/ር አሰፋ ፍሰሀ፤ባለፉት 26 ዓመታት የተገነባው የፌደራል ስርአት የተለያየ ማንነት ያላቸውን ህዝቦች በራስ የመተዳደር መብት በማጎናፀፍና እርስ በእርስ በማቀራረብ በኩል ውጤታማ መሆኑን ጠቁመው፤በዚህ መሃል ግን የዜጎች መብት በተለያዩ ግለሰቦች መጣሱ ለፌደራል ስርአቱ አደገኛ ነው ብለዋል፡፡
ዜጎች ከሀገራዊ እሳቤ ይልቅ ክልላዊና መንደራዌ እሳቤ ላይ ማተኮራቸው አሳሳቢ መሆኑን የጠቆሙት ምሁሩ፤ ይህን አመለካከት ለመቀየር በርካታ የፖለቲካ ስራዎች መሰራት እንዳለባቸው ተናግረዋል፡፡ የፌደራሊዝም ስርአቱ ዋነኛ አላማ፤ ጎሰኝነትንና ክልላዊነትን ማስፈን እንዳልሆነ ባልተገነዘቡ ሰዎች፣ ባልተገባ መንገድ እየተተረጎመ መሆኑንም አስረድተዋል -ምሁሩ፡፡  
በፌደራሊዝም ስርአት ግንባታ ውስጥ ዋነኛ ምሰሶ የሆነው ህገ መንግስቱ በሚገባ በተግባር ላይ ካልዋለ ቅሬታና ግጭት እንደሚያስነሳ በጥናታቸው ያመለከቱት ሌላው የፅሁፍ አቅራቢ ፕ/ር ካሣሁን በሪሁን፤ ህገ መንግስቱ መሬት ላይ ሲተረጎም በአግባቡ አለመሆኑ የፌደራሊዝም ስርአቱ ተግዳሮት ነው ብለዋል፡፡ የመንግስትና የፓርቲ ጉዳይ መደበላለቅም የወቅቱ የፌደራሊዝም ስርአቱ እንቅፋቶች መሆናቸውን የጠቆሙት ጥናት አቅራቢዎቹ፤ ፓርቲ በመንግስት ተቋማት ውስጥ ጣልቃ መግባቱ መገታት አለበት ብለዋል፡፡  
“በቤኒሻንጉል፣ ኦሮሚያና ሌሎች ክልሎች፣የሌላ ብሄር ተወላጆች በየጊዜው መፈናቀላቸው ብሄርና ቋንቋን መሠረት ያደረገው ፌደራሊዝም ውጤት ነው” የሚል አስተያየት ከመድረኩ የተሰነዘረ ሲሆን ጥናት አቅራቢዎች፤ ”የመንግስት አስፈፃሚ አካላት ችግር የፈጠረው ነው” ብለዋል፡፡ ፌደራሊዝሙ ለምን በመልከዓ ምድራዊ አቀማመጥና በህዝብ ፈቃደኝነት ላይ የተመሰረተ አይሆንም የሚል ጥያቄም ከተሣታፊዎች የተሰነዘረ ሲሆን ከመድረኩ በተሠጠው ምላሽ፤ ከዚህ በኋላ አሁን ያለውን የፌደራል ስርአት ቅርፅና ይዘት አጠናክሮ ከማስቀጠል ውጪ ወደ ኋላ መመለስ አደጋ እንዳለው ተጠቁሟል፡፡ “ችግሮቹን ነቅሶ አውጥቶ፣ እያረሙና እያስተካከሉ መጓዝ እንጂ ከዚህ በኋላ እንደገና መመለስ የሚፈጥረው ቀውስ ከባድ ይሆናል”
“የማንነት፣ የወረዳና ዞን እንሁን” ጥያቄዎች በሰፊው እየቀረቡና ለግጭትም መንስኤ እየሆኑ መምጣታቸው ፌዴራሊዝሙን አደጋ ላይ እንደጣለው የተጠቆመ ሲሆን መፍትሄው ፖለቲካዊ መግባባት መፍጠርና የዜጎች ድምፅ የሚሰማበትን አማራጭ ማስፋፋት ነው ተብሏል፡፡
የዘንድሮ 26ኛው የግንቦት 20 በዓል፤ ‹‹የህዝቦች እኩልነት፣ ፍትሃዊነትና ተጠቃሚነት ያረጋገጠ ፌደራላዊ ስርአት እየገነባች ያለች ሃገር›› በሚል መሪ ቃል እየተከበረ ሲሆን በዓሉ በዋናነት በክልሎችና በውጪ በሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ዳያስፖራዎች በድምቀት እንደሚከበርም ለማወቅ ተችሏል፡፡  

የፍርድ ቤት የእግድ ትእዛዝ በመጣስ፣ በአዲስ አበባ የካ ክፍለ ከተማ፣ ልዩ ስሙ የካ አባዶ እየተባለ በሚጠራው አካባቢ የምትገኘውን የቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን ያፈረሱ፣ የወረዳ 12 አስተዳደር ዋና ሥራ አስፈጻሚና የደንብ ማስከበር ጽ/ቤት ሓላፊ፣ በ15 ቀን ቀላል እስራት እንዲቀጡ የከተማው ይግባኝ ሰሚ ፍ/ቤት ወሰነ፤ ቤተ ክርስቲያኒቱ እንድትፈርስ የሥር ፍ/ቤት የሰጠው ውሳኔ ግን፣ “ይግባኝ አያስቀርብም” ብሏል፡፡
በይግባኝ ባይ፥ የደብረ ልዕልና ቅድስት አርሴማ ቤተ ክርስቲያን አስተዳደር እና በመልስ ሰጪ፥ የየካ ክፍለ ከተማ ወረዳ 12 ደንብ ማስከበር አገልግሎት ጽ/ቤት መካከል ያለውን የይግባኝ ቅሬታ ሲመረምር መቆየቱን ከትላንት በስቲያው ውሳኔው ያስታወቀው ፍ/ቤቱ፤ መልስ ሰጪዎቹ፥ የወረዳው ዋና ሥራ አስፈጻሚ አቶ ደመላሽ ጎሳ እና የደንብ ማስከበር ጽ/ቤቱ ሓላፊ አቶ ዳዊት ሙሉጌታ፤ የፍ/ቤትን የእግድ ትእዛዝ እያዩ፣ ክርክር የቀረበባትን ቤተ ክርስቲያን ማፍረሳቸው፣ የፍርድ ቤትን ሥራ ማወክ በመኾኑ ጥፋተኛ ኾነው እንደተገኙ ገልጿል፡፡
በይግባኝ ባይ በኩል የቀረቡ አራት ምስክሮች፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ አስተዳዳሪ ሊቀ ካህናት በየነ አሰፋ፥ “የፍ/ቤት የእግድ ትእዛዝ አለ፤ በሕግ አምላክ አታፍርሱ” እያሉ ለተጠቀሱት ሁለት ሓላፊዎች እንዳሳዩዋቸው፤ እነርሱ ግን ለማቆም ፈቃደኛ እንዳልነበሩና በግብረ ኃይል ቤተ ክርስቲያኒቱን እንዳስፈረሱ፣ በበቂ ሁኔታ ማስረዳታቸውን ፍ/ቤቱ በውሳኔው ጠቅሷል፡፡ በመልስ ሰጪዎች የቀረቡ ሁለት ምስክሮች፣ አፍራሽ ግብረ ኃይል ሆነው የማፍረስ ተግባር ያከናወኑና ምስክርነታቸው እርስ በርሱ የሚጋጭ ሆኖ በመገኘቱ፣ “ገለልተኛና ተኣማኒነት ያለው ኾኖ አላገኘነውም፤” ብሏል፡፡
ዋና ሥራ አስፈጻሚው፣ “የጣስነው ሕግ የለም፤ የወሰድነው ርምጃም ተቋሙን ወክለን ነው፤” በሚል የቅጣት ማቅለያ ያቀረቡ ቢኾንም፣ ፍ/ቤቱ፥ “ጥፋተኞችንም ኾነ ሌሎች ግለሰቦችን ያስተምራል፤” በሚል አቶ ደመላሽ ጎሳ እና አቶ ዳዊት ሙሉጌታ፣ ውሳኔው ከተሰጠበት ቀን ጀምሮ በ15 ቀን ቀላል እስራት እንዲቀጡ ወስኗል፤
በሌላ በኩል፣ የሥር ፍ/ቤት፣ የቤተ ክርስቲያኒቱ ይዞታና ግንባታ ሕገ ወጥ ነው፤ በሚል መጋቢት 13 ቀን 2009 ዓ.ም.፣ የሰጠው ውሳኔ፣ የሚነቀፍበት ምክንያት እንዳላገኘበት የይግባኝ ሰሚው ፍ/ቤቱ ጠቅሶ፤ “መልስ ሰጪን መጥራት ሳያስፈልግ፣ ይግባኙ አያስቀርብም” በማለት መዝገቡን መዝጋቱን በተጨማሪ ትእዛዙ አስታውቋል፡፡ የደብሩ አስተዳደር፣  ለሰበር ሰሚ ይግባኝ እንደሚጠይቅ ተጠቁሟል፡፡

የ2017 ቶታል የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ  የምድብ ፉክክር 25ኛ ዙር ወዘተ ቢሮ ቅዱስ ጊዮርጊስ በአዲስ አበባ ስታድየም የቱኒዚያውን ኤስፔራንስ የፊታችን ማክሰኞ ያስተናግዳል፡፡ ባለፈው ሳምንት የቀጠለው በምድብ  ማጣርያ የመጀመርያ ጨዋታ ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሜዳው ውጭ ከደቡብ አፍሪካው ሜመሎዲ ሰንዳውንስ ጋር ተገናኝቶ 0ለ0 አቻ ሲለያይ፤ በምድብ 3  ሌላ የቱኒዚያው ኤስፔራንስ ዴቱኒስ በሜዳው የዲ.ሪ ኮንጎውን ኤኤስ ቪታ አስተናግዶ 3ለ1 አሸንፏል፡፡
ይህ በእንደህ እያለ ባለፈው ሐሙስ ቅዱስ ጊዮርጊስ የ2009 የኢትዮጵያ ፕሪሚየርሊግ ሻምፒዮናነት ክብሩን ያረጋገጠ ሲሆን ኤስፔራንስም በተመሳሳይ ቀን የቱኒዚያ ሊግ 1 አሸናፊነቱን አግኝቷል፡፡ ስለሆነም የፊታችን ማክሰኞ በአዲስ አበባ ስታድየም የሚደረገው የሁለቱ ክለቦች ፍልሚያ የሻምፒዮኖች ትንቅንቅ ይሆናል፡፡
ቅዱስ ጊዮርጊስ ባለፈው ሰሞን ለምድቡ የመጀመርያ ጨዋታ ወደ ደቡብ አፍሪካዋ ከተማ ፕሪቶርያ ያቀናው 18 ተጨዋቾችን በመያዝ ወሳኙን የአጥቂ መስመር ተሰላፊ ሳላዲን ሰኢድ በዚህ ጨዋታ ላይ 1 ቅጣት አለማሰለፉ የግብ እድሎችን እንዳይፈጥር አድርጎታል። ይሁንና ኡጋንዳዊው ግብ ጠባቂ ሮበርት አዶንካራ፤ እንዲሁም የተከላካይ መስመር ተሰላፊዎቹ ደጉ ደበበ እና አስቻለው ታመነ ወሳኝ ሚና ሊጫወቱ የቻሉበት ፍልሚያ ነበር። በፕሪቶርያ በሚገኘው የሜመሎዲ ሰንዳውንስ ስታድዬም በሺዎች የሚቆጠሩ በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ቅዱስ ጊዮርጊስ በህብረት በመደገፍ የፈጠሩትን ድምቀት ሚዲያዎች አድንቀውታል፡፡
የቅዱስ ጊዮርጊሱ አሰልጣኝ ማርቲን ኖይ ከሜመሎዲ ሰንዳውንስ ጋር ከመጫወታቸው በፊት ለካፍ ድረገፅ በሰጡት አስተያየት የምድብ ፉክክሩ ላይ የሚገኙት ሁሉም ክለቦች የአፍሪካ ምርጦች እንደሆነ በመግለፅ ምንም አይነት ጨዋታ ቀላል አይደለም ብለው ነበር፡፡ ክለባቸው ከአምናው ሻምፒዮን ጋር  አቻ ሊወጣ የቻለው በሱፕር ስፖርት ስርጭት ስለሜመሎዲ ሰንዳውንስ ብዙ በማወቃችንና ልዩ ክትትል አድርገን በመዘጋጀታችን ነው ብለዋል፡፡‹‹ ሆላንዳዊ ነኝ፡፡ የጨዋታ ትንተና በዚያ አገር አሰልጣኝነት የተለመደ ነው፡፡ በተለያዩ የግንኙነት መረቦች መረጃዎች እንሰበስባለን፡፡ ያንን በመንተራስ ታክቲክ እነድፋለሁ›› በማለትም ለካፍ ኦንላይን አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ በአፍሪካ እግር ኳስ በአሰልጣኝነት ሲሰሩ 17 ዓመታን ያስቆጠሩት ማርቲ ኖይ በ2012 እኤአ ላይ በኬፕታውኑ ክለብ ሳንቶስ የሰሩበትም ልምድ ስላላቸው በርግጥም ስለደቡብ አፍሪካ ክለቦች እንግዳ አይደሉም፡፡
ከቅዱስ ጊዮርጊስ ጋር በተደረገው ጨዋታ በሜመሎዲ ሰንዳውንስ በኩልም ከፍተኛ ግምት የተሰጠው ተጨዋች ኡጋንዳዊው ግብ ጠባቂ ዴኒስ ኦንያንጎ ነበር፡፡ በደቡብ አፍሪካ ሊግ የወሩ ኮከብ ሆኖ ጨዋታውን የተሰለፈው የ31 ዓመቱ ዴኒስ ኦንያንጎ በ2005 እና በ2006 እኤአ ላይ ለቅዱስ ጊዮርጊስ ክለብ መጫወቱ የሁለቱን ክለቦች ግንኙነት ልዩ አድርጎታል፡፡ የኡጋንዳ ብሄራዊ ቡድን ግብ ጠባቂ ሆኖ የሚያገለግለው ዴኒስ ኦንያንጎ በ2016 እኤአ ላይ አገሩን ከ38 ዓመታት በኋላ ለአፍሪካ ዋንጫ ያበቃ፤ ከክለቡ ሜመሎዲ ሰንዳውንስ ጋር በ2016 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግና የአፍሪካ ክለቦች ሱፕር ካፕ እንዲሁም የደቡብ አፍሪካ ሊግ ሻምፒዮን በመሆን 3 ዋንጫዎችን የሰበሰበ ነው፡፡ በተጨማሪም በ2016 በአፍሪካ ውስጥ የሚጫወት አፍሪካዊ ኮከብ ተጨዋች ሆኖ በካፍ ሽልማት ያገኘ ነው፡፡ ዴኒስ ኦንያንጎ ከጨዋታው በፊት ለሱፕር ስፖርት በሰጠው አስተያየት ‹‹የቀድሞ ክለቤን የምገጥምበት አጋጣሚ በመፈጠሩ ደስ ብሎኛል፡፡ ስሜታዊ አይደለሁም፤ በፕሮፌሽናልነት የማገለግለው ክለቤን ነው ብሎ ነበር፡፡ የሜመሎዲ ሰንዳውንስ ዋና አሰልጣኝ ደግሞ የደቡብ አፍሪካ ብሄራዊ ቡድንን ሲያሰለጥኑ የነበሩት ፒትሶ ሞስማኔ ናቸው፡፡ በ2016 በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን ምርጥ አሰልጣኝ ሆነው ለሽልማት የበቁት ፒትሶ ‹‹ የምንገኘው በሞት ምድብ ነው፡፡ ዘንድሮ የሻምፒዮንስ ሊግ የምድብ ፉክክር የሽልማት ገንዘቡ በማደጉ እና የቴሌቭዥን ስርጭቱ በመስፋቱ ጠንካራ ነው፡፡ የምንገኘው በሞት ምድብ ነው። ሲሉ ይናገራሉ፡፡
ሞሲማኔ ክለባቸው በሜዳው ነጥብ መጣሉ አላስደሰታቸውም፡፡ ክለባቸው ባለፈው የውድድር ዘመን የአህጉሪቱ ሻምፒዮን ለመሆን ሲበቃ በመላው አፍሪካ በመዘዋወር ያደረጋቸው ጨዋታዎች በተጨዋቾቹ ላይ መዳከም መፍጠሩን ምክንያት አድርገውም ጠቅሰዋል። በዘንድሮ የደቡብ አፍሪካ ፕሪሚዬር ሊግ ክለቡ የነበረበት የጨዋታዎች መደራረረብ ተፅዕኖ መፍጠሩንም ያማርራሉ፡፡ ሜመሎዲ ስንዳውንስ የአምና ሻምፒዮናነቱን ለማስጠበቅ ሊከብደው ይቻላል ያሉት አሰልጣኙ በ2ኛ ዙር ጨዋታ፡፡ ወደ ኪንሻሳ በመጓዝ ለምናስመዘግበው ውጤት ከተጨዋቾቼ ቁርጠኝነት እጠብቃለሁ ብለዋል፡፡ ኤኤስቪታ ክለብ በአርቴፊሻል ሜዳ ጨዋታውን በማስተናገድ ብልጫ ሊወስድ ስለሚችል ተጫዋቾቻቸው አዕምሯቸውን ማዘጋጀት እንዳለባቸውም ጥሪ አቅርበዋል፡፡
ከምድቡ የመጀመርያ ጨዋታዎች በኋላ ኤስፔራስን ዴ ቱኒስ በ3 ነጥብ እና በ2 የግብ ክፍያ መሪነቱን ሲይዝ ሜመሎዲ እና ጊዮርጊስ በእኩል 1 ነጥብ ያለምንም ግብ ተከታታይ ደረጃ ላይ ተቀምጠው ኤኤስ ቪታ ያለምንም ነጥብ በመጨረሻ ደረጃ ላይ ነው፡፡
የምድብ ፉክክሩ ሁለተኛ ዙር ጨዋታዎች በሚቀጥለው ሳምንት ሲደረጉ ማክሰኞ ላይ ቅዱስ ጊዮርጊስ በሜዳው የቱኒዚያውን ኤስፔራንስ ዴ ቱኒዝ ሲገጥም፤ የዲ.ሪ ኮንጎው ኤኤስ ቪታ  የአምናውን የሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊ  ሜሞሎዲ ሰንዳውንስ በኪንሻሳ ከተማ ያስተናግዳል፡፡

 3 ማራቶኒስቶች፤ 20 ሳይንቲስቶች፤ 30 አሯሯጮች ተሳትፈዋል

      የአሜሪካው የስፖርት ትጥቅ አምራች ኩባንያ ናይኪ Breaking2 በሚል ስያሜ በነደፈው ማራቶንን ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት  ልዩ ፕሮጀክት የመጀመርያውን ሙከራ ከሁለት ሳምንት በፊት አድርጓል፡፡ በሙከራ ውድድሩ ኬንያዊው ኤሊውድ ኪፕቾጌ ለታቀደው ሰዓት በጣም በመቃረብ ሲሳካለት፤ ኤርትራዊው ዘረሰናይ ታደሰ እና ኢትዮጵያዊው ሌሊሳ ዴሲሳ ግን አልተሳካላቸውም ነበር።
ናይኪ ከ2014 እኤአ ጀምሮ በፕሮጀክቱ ላይ በተለያዩ አቅጣጫዎች ሲሰራ ቢቆይም ስለመጀመርያው የሙከራ ውድድር ለመላው ዓለም  በይፋ በማስታወቅ የሰራው ከ6 ወራት ወዲህ ነበር፡፡
በናይኪ ማራቶንን ከ2 ሰዓት በታች የመግባት Breaking2 ፕሮጀክት  ላይ 3 የዓለማችን ምርጥ ማራቶኒስቶች ተሳትፈዋል፡፡ በማራቶን የኦሎምፒክ ሻምፒዮን የሆነውና የ32 ዓመቱ ኬንያዊ አትሌት  ኤሊውድ ኪፕቾጌ፤ በማራቶን በዓለም ሻምፒዮና የነሐስ ሜዳልያ ያገኘው፣ የቦስተን ማራቶንን ለሁለት ጊዜያት ያሸነፈው የ27 ዓመቱ ኢትዮጵያዊ አትሌት ሌሊሳ ዴሲሳ እና የዓለም የግማሽ ማራቶን ክብረወሰን ባለቤት የሆነው የ35 ዓመቱ ኤርትራዊ አትሌት ዘረሰናይ ታደሰ ናቸው፡፡ ሶስቱ የማራቶን አትሌቶች በናይኪ ፕሮጀክት ስር በመታቀፍ ለመጀመርያው የሙከራ ውድድር ዝግጅት ሲያደርጉ ነበር፡፡ ለፕሮጀክቱ በሰጡት ትኩረትም በትልልቅ የማራቶን ውድድሮች በመሳተፍ የሚያገኟቸውን የሽልማት ገንዘቦች ሌሎች ጥቅማጥቅሞች ትተዋል። ማራቶኒስቶቹ በፕሮጀክቱ ላይ በሚኖራቸው ተሳትፎ የትጥቅ ስፖንሰራቸው ከሆነው ናይኪ በይፋ ያልተገለፁ ክፍያዎችን እንዳገኙ ግን መረጃዎች አውስተዋል፡፡ በተለያዩ የሙያ እና የእውቀት መስኮች ከተሰባሰቡ የዓለማችን ምርጥ የአትሌቲክስ ስፖርት የባለሙያዎች ቡድኖች ጋር ዝግጅቶቻቸውን አድርገዋል። በስፖርት ሳይንስ፤ ስልጠና፤ ህክምና አዳዲስ አሰራሮችን በመመራመር በBreaking2 ፕሮጀክት ላይ የሰሩት  ከ20 በላይ ሳይንቲስቶች ናቸው፡፡ ይህም በፕሮጀክት አይነቱ ግቡ የባለሙያዎች ስብስብ ነው ናይኪ አዳዲስ የመሮጫ ጫማዎች እና ማልያዎችን ከማቅረቡም በላይ፤ በላቀ ደረጃ የሳይንስ፤  ቴክኖሎጂ፤ የአመጋገብ፤ የውሃ እና ሃይል ሰጪ መጠጦችን አዘጋጅቶላቸዋል፡፡ ከ30 በላይ ምርጥ አሯሯጮችን በመመደብም በስፋት ተንቀሳቅሷል። ለዚሁ ሙከራ ተብሎ ዙም ሱፕርፍላይ ኤሊት የተባለ የመሮጫ ጫማን ለሶስቱ አትሌቶች በአዲስ መልክ ናይኪ ያመረተ ሲሆን በውድድሩ ወቅት ሰዓቱንና የአሯሯጭ እና የራጮቹን ፔስ የሚለካ የኤሌክትሪክ መኪናም ነበር፡፡
በፕሮጀክቱ ስኬታማነት የስፖርቱን የወደፊት እድገት ለማነሳሳትና ለፕላኔታችን ምርጥ አትሌቶች መነቃቃትን የመፍጠር ዓላማን ያነገበው ናይኪ፤ ሁሉም ባለድርሻ አካላት በፕሮጀክቱ በሚያደርጉት እልህ አስጨራሽ ትንቅንቅ ሚሊዮኖችን የሚያነሳሳ ውጤት  ይመዘገባል በሚል ተስፋ ነበረው፡፡
በBreaking2 የሙከራ ውድድሩን ፕሮጀክት ማራቶንን ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት ናይኪ የመጀመርያ የሙከራ ውድድሩን ያደረገው በጣሊያኗ ከተማ  በሚገኘው  አውቶድሮሞ ናዚዮናሌ ሞንዛ በተባለ ዝግ ስታድዬም ነበር፡፡ የፎርሙላ ዋን የመኪና ሽቅድምድም መወዳደርያ ትራክ ላይ ነበር የአንድ ዙር መሙ ርዝማኔ 100 ሜትር የሆነው የስታድዬሙ ትራክ በመጠምዘዣዎቹ ምቹነት እና አካባቢ ተስማሚ የአየር ሁኔታ በናይኪ ተመራጭ እንደሆነ ተገልጿል፡፡ በማራቶን የምንግዜም ፈጣን ሰዓቶች ደረጃ ሶስተኛ ሆኖ የተቀመጠውን 2፡03፡05 በ2016 እኤአ ላይ በለንደን ማራቶን ሲያሸንፍ ያስመዘገበውና የኦሎምፒክ ሻምፒዮኑ ኤሊውድ ኪፕቾጌ በፕሮጀክቱ የመጀመርያ ሙከራ ከባዱን ፈተና በአስደናቂ ብቃት በመወጣት ልዩ መነቃቃትን ፈጥሯል፡፡ የማራቶኑን ርቀት ሲጨርስ የገባበት ሰዓት 2፡00፡25 ነበር፡፡ ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት  በ26 ሰከንዶች በመዘግየቱ አልተሳካለትም ፤ ይሁን እንጅ የመኪና መወዳደደርያ ትራኩን የ100 ሜትር መም 422 ጊዜ ሲዞር እያንዳንዱን ዙር በ17 ሰከንዶች መሸፈኑ ለብዙዎች የገረመ ብቃት ነበር፡፡ የዓለም ማራቶን ሪከርድ በ2014 የኬንያው ዴኒስ ኪሜቶ በበርሊን ማራቶን በ2፡02፡57 የተመዘገበው እንደሆነ ይታወቃል፡፡ በናይኪ ፕሮጀክት የተሳተፈው ኪፕቾጌ የገባበት ሰዓት ይህን የዓለም የማራቶን ሪከርድን በ2 ደቂቃ ከ32 ሰከንዶች ቢያሻሽልም በክብረወሰንነት ግን የሚመዘገብ አይደለም፡፡ የመጀመርያው ምክንያት የመወዳደርያው ትራክ በአይኤኤኤፍ እውቅና ያገኘ ባለመሆኑ ሲሆን በውድድሩ ላይ የተመደቡ አሯሯጮች እየተቀያየሩ መስራታቸው ሌላው ነው ፡፡ ኪፕቾጌ ከውድድሩ በኋላ ያስመዘገበውን ሰዓት ታሪካዊ ክስተት ብሎታል፡፡ በአጠቃላይ ግን  የናይኪ ማራቶንን ከ2 ሰዓት በታች የመግባት ሙከራ የመላው ዓለምን ትኩረት የሚስብ ትልቅ ክስተት ሲሆን የዓለም ሚዲያዎች አውስተዋል፡፡ ከኤሊውድ ኪፕቾጌ ሌላ መብቃቱን ዘረሰናይ ታደሰ እና ሌሊሳ ዴሲሳ በተመሳሳይ ፕሮጀክት ታቅፈው እየሰሩ ቢሆንም አልሆነላቸውም፡፡ የዓለም ግማሽ ማራቶን ሪከርድ ባለቤት የሆነው የኤርትራው ዘረሰናይ  በ2፡06፡51 ሲጨርስ የኢትዮጵያ ሌሊሳ ደሲሳ ደግሞ በ2፡14፡10 ርቀቱን ሸፍኗል፡፡
ለታሪካዊው የማራቶን ከፍተኛ ውጤት በተለያዩ ፕሮጀክቶች ቅድሚያ ግምት የሚያገኙት ከሁለቱ የምስራቅ አፍሪካ አገራት ኬንያና ኢትዮጵያ የሚወጡ ማራቶኒስቶች ናቸው፡፡ በተለይ ደግሞ በኢትዮጵያ በቆጂ በምትባለዋ የክልል ከተማ እንዲሁም በኬንያ ኤልዶሬት እና ኢቴን በተባሉት ከተማዎች እንደሚገኙ የብዙዎች እምነት ነው፡፡ በእነዚህ የምስራቅ አፍሪካ የገጠር ከተሞች በማራቶን ፈጣን ሰዓቶችን የሚያመዘግቡ እና ትልልቅ ውድድሮችን የሚያሸንፉ ሯጮች በብዛት እንደሚገኙ የሚታወቅ ነው፡፡ በየከተሞቹ ያሉት መልክዓምድራዊ ሁኔታዎች፤ የድህነት ኑሮ፤ የስኬታማ ማራቶን ሯጮች መብዛት፤ ባህላዊ የአመጋገብ ስርዓቶች ለማራቶን ስኬታቸው ተጠቃሽ ምክንያቶች ናቸው፡፡
ከዚህ አንፃር በናይኪ Breaking 2 ፕሮጀክት ኤሊውድ ኮፕቾጌ ያስመዘገበው ውጤት ግምቱን ወደ ኬኒያ አትሌቶች እንዲያጋድል አድርጎታል፡፡ ኢትዮጵያዊው ሌሊሣ ዴሢሣ የገባበት ሰዓት ከምርጥ ማራቶኒስቶች አማካይ ሰዓት የራቀ መሆኑ የኢትዮጵያን አትሌቲክስ የሚያስቆም ነው፡፡  
ናይኪ በመጀመርያ የሙከራ ውድድሩ ከ2 ሰዓት በታች የመግባት እቅዱን ማሳካት ባይችልም በማርኬቲንግ እንቅስቃሴዎቹ ተሳክቶለታል፡፡ በተለይ በዓለም አቀፍ ደረጃ በማህበራዊ ሚዲያዎች ያገኘው ትኩረት የስፖርት ትጥቅ አምራቹን ብራንድ ያሳደገ ነበር፡፡ ስለBreaking2 የሚለው የፕሮጀክቱ በሚሊዮኖች እየተጠቀሰ በመላው ዓለም በትልቅ የአትሌቲክስ ስፖርት ዘጋቢ ድረገፆች፤ መፅሄቶች፤ ጋዜጠኞች እንዲሁም በማህበራዊ ሚዲያዎች ተዋውቋል፡፡ ናይኪ በዚህ ፕሮጀክት ላለፉት 3 ዓመታት ሲሰራ ለማስታወቂያ የመደበው በጀት ከ800 ሚሊዮን ዶላር በላይ ነው፡፡ ብራንድዎች የተባለ ተቋም ይፋ ባደረገው መረጃ በማህበራዊ ሚዲያዎች ስለሙከራው ከ600ሺ ጊዜ በላይ መጠቀሱን 400ሺ ጊዜ #Breaking2 የሚለው ቃል መፃፉን አስታውቋል፡፡ በዓለም አቀፍ ደረጃ በአትሌቲክስ ዙርያ ትንታኔ የሚሰሩ ድረገፆች እና ኤክስፐርቶቻቸውም አድናቆት ሰጥተውታል፡፡ በላይቭ ስትሪሚንግ በኢንተርኔት ድረገፅ ውድድሩ ባገኘው ስርጭት በ2 ቀናት 5 ሚሊዮን ተመልካች ማግኘት ችሏል፡፡ እነ ኪፕቾጌ የሮጡበት ቫፖርፍላይ ኤሊት የተሰኘው የናይኪ የጫማ ምርት በ250 ዶላር የሚሸጥ ሲሆን የሙከራ ውድደሩ የምርቱን ገበያ አሟሙቆታል፡፡
ማራቶን ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት እንደሚቻል በማቀድ በፕሮጀክት ደረጃ የሚንቀሳቀሰው ናይኪ ብቻ አይደለም፡፡   ስኮትላንዳዊው ፕሮፌሰር ያኒስ ፒስተሊደስ በsub2hr ፕሮጀክታቸው ከጀርመኑ የትጥቅ አምራች ኩባንያ አዲዳስ ጋር በመንቀሳቀስ ፈርቀዳጅ ሆነው ይጠቀሳሉ፡፡ ማራቶንን ከ2 ሰዓት በታች መግባትን አስመልክቶ በርካታ በአትሌቲክስ ላይ በሚያተኩር ዘገባቸው በሚታወቁ መፅሄቶች፤ ድረገፆች እና የመረጃ ሚዲያዎች በየጊዜው ትንታኔዎች መቅረባቸውን ቀጥለዋል፡፡ በአጀንዳው ላይ በማተኮር የተፃፉ ታዋቂ መጽሐፍትም አሉ፡፡ በተለይ በኤድ ሲዛር የተፃፈውን “The quest to Run Impossible Marathon መጥቀስ ይቻላል፡፡  
ማራቶንን ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት በርካታ ወሳኝ ሁኔታዎችን እና አስተዋጽኦዎች ይኖራሉ፡፡ 1፡59፡59 ሰዓትን በማራቶን ለማስመዝገብ 1 ማይል ርቀትን በ4 ደቂቃ ከ34 ሰኮንዶች መሸፈን ግድ ይሆናል፡፡ ከወቅታዊ ሪከርድ በየማይሉ በ7 ሰኮንዶች በፈጠነ አሯሯጥ ነው። የስፖርቱ  ሳይንቲስቶች የማራቶን ርቀትን በሰው ልጅ የተፈጥሮ ብቃት ለመሸፈን የሚቻልበት የመጨረሻው የሪከርድ ሰዓት ወሰኑ 1፡57፡57 እንደሆነ የሚገልፁ ሲሆን ይህም ማራቶን ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት እንደሚቻል የሚያመለክት ነው፡፡  
ስፖይክ የተባለና ከዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር ጋር የሚሰራ ድረገፅ በአንድ ወቅት  በሰራው ዘገባ ማራቶንን ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት የሚያስፈልጉ 13 ወሳኝ ሁኔታዎችን ዘርዝሯል፡፡ ከሪኮርዱ 5 ደቂቃዎች ባለፉት 20 ዓመታት መቀነሳቸው፤ አሁን ከተያዘው ሪኮርድ ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት የሚቀሩት ከ3 ያነሱ ደቂቃዎች መሆናቸው፤ ከ2 ሰዓት 05 ደቂቃዎች በታች የሚገቡ አትሌቶች ከ30 በላይ ማለፋቸው፤ በማራቶን የፈጣን ሰዓቶች ደረጃ በየዓመቱ እስከ 30ኛ ደረጃ አዳዲስ አትሌቶች በብዛት መግባታቸው፤ በመጀመሪያ ማራቶናቸው ከ2፡04 በታች የሚገቡ አትሌቶች መገኘታቸው፣ በትራክ ከፍተኛ ልምድ ያካበቱ አትሌቶች ወደ ማራቶን በመግባት ስለሚሳካላቸው የሚሉት ይጠቀሳሉ፡፡ በአትሌቲክስ ስፖርት አሰለጣጠን በሳይንሳዊና ቴክኖሎጂ የምርምር ተግባራት የተጋዙ ፕሮጀክቶችንም በትኩረት መስራትን ወሳኝ እንደሆነ የሚገልፁ አሉ፡፡
የሰው ልጅ በሚችለው ብቃት ማራቶንን ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት  የስልጠና ሳይንስ እና ቴክኖሎጂም ለውጥ የሚፈጥሩም ናቸው፡፡ ከ40 አመት በፊት የነበረው ስልጠና አሁን በከፍተኛ ደረጃ በምርምሮች ማደጉ እንደ አጋዥ ምክንያት ሊጠቀስ የሚችል ነው።  በአዲዳስ፤ በናይኪ እና በፑማ የትጥቅ አምራች ኩባንያዎች የሚቀርቡ የመሮጫ ማልያዎችና ጫማዎችም የሚኖራቸው አስተዋፅኦ ቀላል አይደለም። በማራቶን ውድድሮች የሚመደቡ አሯሯጮች ልዩ ብቃት እና በማራቶን ውድድሮች ዳጎስ ያሉ ሽልማቶች፤ የስፖንሰርሺፕ እና የቦነስ ክፍያዎች ከፍተኛ ገቢ መገኘቱ ሌሎቹ አስተዋፅኦዎች ናቸው፡፡
በመላው ዓለም ከሚካሄዱና የሪከርድ ሰዓት ህጋዊ ከሚሆንባቸው ትልልቅ  ውድድሮች መካከል ከ2 ሰዓት በታች ለመግባት ዋና እጩዎች የሚባሉት በበርሊን እና ለንደን ከተሞች  የሚዘጋጁት ማራቶኖች ነበሩ፡፡ ናይኪ የመጀመርያ ሙከራን በመኪና ውድድር ትራክ ላይ ማድረጉ ብዙዎችን አላስደሰተም፡፡
ማራቶንን ከ2 ሰዓት በታች መግባት በተለያዩ ጥናቶች እና ትንታኔዎች እስከ 2028፤ 2035 ወይም 2041 እኤአ ላይ እንደሚሳካ ይገመታል፡፡ በናይኪ Breaking2 ፕሮጀክት በ2017 ለማሳካት ታቅዶ አልሆነም፡፡ ስኮትላንዳዊው ፕሮፌሰር ያኒስ ፒስታሊደስ በበኩላቸው ከአዲዳስ ጋር በሚሰሩበት በsub2hr ፕሮጀክታቸው እስከ 2019 እኤአ የሚገኝ ውጤት ነው በሚል ስራቸውን ቀጥለዋል፡፡