Administrator

Administrator

Tuesday, 21 November 2017 00:00

ማስታወሻ

 የ‹‹ዘበት እልፊቱ››ን የሰለሞን ደሬሳን እልፊት ለመዘከር፤ አላፊው ራሱ “The Tree” በሚል ርዕስ፤ እንደ ወርቅ አንጥሮ - እንደ ጨርቅ ጠቅልሎ በእንግሊዝኛ የነደፈውን እውነት እና ውበት፤ በላይ ግደይ እንዲህ ወደ አማርኛ ተረጎመው፡፡ እኔ የተርጓሚው ወዳጅ አነበብኩት፣ ወደድኩት እናንተም እንድታዩት ለአዲስ አድማስ ላኩት፡፡
ዛፉ

ፍሬ ዘር ይኖር ኣለ       
እንዳቅሚቲ ለዘላለም፡ ክንብንቤ ወድቆ፡    
‘ተወለደ፡ ሞተ’ ምን ቢኾንም፡ ልደት ናፍቆ፤                             
ቱክ… ቱክ…ቱክ… ለዅልኽም፡ ለያንዳንድኽ፡        
ቱክ…ቱክ… እንዳለች ናት፡
ቱክ… ቱክ… ባይዋ ሰዓት፤       
‘ያው እንደኔው፡ እኔን ሰምታ፡’ ድልልዋም ልብ፡ ልቢት ከንቱ፡               
ጊዜ ላይ ትልታዩን፡ የጊዜን ቍርጭራጭ፡ የጊዜን ኰረቱ ----  

ዱሮ ቀንበጥ! እዩትልኝማ፡     
ይሣሡለት ለጋ፡ ያባባ ድንቅዬ፡                   
እንዳይኗ የማሙዬ                                              
ስታይ እምነት ጥላ፤                                                       
ጕጉ፡ ድንግል እንዳራስ ናላ፤          
ዕሺ፡ ዕሰየው ለየቱም ትንፋሽ፤       
ተራቢ የርጥብ ዓፈር፡ የርጥብ መሬት፡
ተጠሚ የማይ ሕይወት፡
ሙላው ሥራሥሩ
ለምለም ከንፈር የማሙዬ፡        
ለወትሮው ስትደቀን        
ኣነፍንፋ ከጡት ጠረን----

ይኸው ደሞ ያቅል ጌታ ኣድጎ፡ ተመንድጎ!    
ከቆመበት ጸንቶ ሺ ዓመት እሱ
ይኸው ይኖር ዛፍ ለጋሱ።
ኣድባር፡ ኣውጋር ኣምኖ ኣበባዉን ይገልጥ፡                 
ጫፉ፡ ቅርንጫፉ ሙሉ ዓቅሙን ይለጠጥ፡-  
ድባብ የላይ
ለዘረ ወፍ ለተንጫጪ፡              
ለፍንድቅ ልጅ ለቦራቂ:           
ለጦጣ ዥውዥው ባይ፤
ለወፊቷ ጎጆ ወጪ፡         
ለርጅናው ለጥላ ሻይ፤                                         
ለሩቅ ኺያጅም ቢራቢሮ።   
ለኒኽ ኹላ በላይ ኑሮ
ዃላ ሊንቀለቀል አለለከት      
በራሱ፡ በደረቀ፡ በገዛው ሞት።

ዛፉ፡ ዛፉ!
ትዕግሥት ኣያልቅበት ዲበ መምህር፤
ዘፈንዋ ስለ ፍቅር                   
ለሰማዩ ውዷ ከታች ምድር።
ለሕማሙ፡ ለ(ዕ)ጹቡ ድንቅ፡ እማኝ፤
መካያው ላይ ክንዶቹም የዛፉ
ዓሳረኛው ሥጋን ያሳረፉ።  

የትልቁ ሠሪ ቢጋር ውቅር፡                    
ኣጐበር  ለኪዳኑ፤ ኣበውም ጐምቱው ከሥር፤            
ዓዛኝ ኣጋር ለደጋግ ተመስጦ፡ ለንቃቱ፤  
  ዛፉ፡ ኣዎን፡ የሰጠኝ የሰጠዅ
  ለበኽሯ ፍቅሬ ያበባ በረከት ከበኵራቱ።     

ዝም ዕክሙ ልባይምሮ ሥሩ ጠሊቅ  
ከለፍላፊት ራሴ ይልቅ፤
ማርያም ማርያም ካሉባቱ፡ ከቦታዪት ጭገሬታ- -
የሚሰማኽ ዘመድ፡ የሚያምኽ ቋሚ ወዳጅ፡
ስማኝና ብቅ በል፡ ብቀል ካላውቀው መቃብሬ፤
ሥሥ ኣሥራውኽ ይዝለቁና ወደ መለያያ
ያጥንቶቼ፡       
ዋጠኝ ባቅልኽ፡ በትዕግሥቶች፡
ዋጠኝ ወደጦፉት፡ ወዳንድነት የፍቅረኞች።

ታዲያ፡ ታዲያ፡ ከቶ ኣይጠፋኝ ደጉ ዕውቀት፤         
እኔ’ንጂ መች ኣንተ ትፈራና የነበልባል ብናኝ
ዕርገት።        
ኣዎ፡ ዓውቃለዅ፡
ስትኼድ እኔም የለዅ፤
ኣንተም ብትኾን የለኽ፡ ኣልቀኽ።  

 ግልጽ ደብዳቤ ይድረስ  ለአቶ  ለማ  መገርሳ፤  የኦሮሚያ  ክልል  ፕሬዚደንት ይድረስ  ለአቶ  ገዱ አንዳርጋቸው፤
 የአማራ  ክልል  ፕሬዚደንት
     የፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶሎሳ

   ፍቅርን፣ ሰላምን፣ አንድነትንና ኢትዮጵያዊነትን አስመልክቶ በቋንቋ ላይ ከተገነባ ጎሰኝነት ይልቅ በደም፣ በተዋልዶና አብሮ በመኖር ላይ የተመሰረተ ኢትዮጵያዊነትን ክህዝባችሁ ጋር ሆናችሁ አብስራችሁና አውጃችሁ፣ በባህርዳር ከተማ፣ ከኦሮሞና ከአማራ ዘመዶቻችሁ ጋር በቅርቡ ያደረጋችሁት ውይይት ልቤን ነክቶታል። በእዚህ ጉዳይ ዛሬ እኔ ክማንም በላይ ሃሴት አደርጋለሁ። ቅድስት ኢትዮጵያ እንድትከበርና የኢትዮጵያዊነት ስሜት እንዲያንሰራራ ላለፉት 28 ዐመታት አቅሜ የሚችለውን ሁሉ አድርጌአለሁና።  ኢትዮጵያዊነት እንደ እርኩስነት በተቆጠረበት በቀውጢዎቹ  28 ዐመታት ውስጥ፣ በትንሿ አቅሜ፣ ኢትዮጵያዊነት ቅድስና እና ልእልና መሆኑን ለማንፀባረቅ ሞክሬአለሁ።  ይህን በማድረጌ የዘለፋና የስድብ ውርጅብኝ ደርሶብኝ ስለነበር፣ አሁን እናንተ በፍቅር ተገናኝታችሁ ኢትዮጵያዊነትን ከፍ ከፍ ስታደርጉ ሳይ፣ ይህ ክስተት በህልሜ ነው በውኔ፣ ብዬ ራሴን ጠይቄአለሁ። የኢትዮጵያን ህዝብ የሚያዛምደውና የሚያስተሳስረው፣ እንዲሁም  አብሮ ለመኖር የሚያስችለው ኢትዮጵያዊነት እና ኢትዮጵያዊነት ብቻ ነው።  በእርግጥም እንደ ተራራ ለተቆለለው የኢትዮጵያ ችግር መፍትሄው ኢትዮጵያዊነት እና ኢትዮጵያዊነት ብቻ ስለሆነ፣ እናንተ በትክክለኛው ጥርጊያ መንገድ ላይ መጓዝ ጀምራችኋል። የጉዟችሁን መጨረሻ እግዚአብሄር ያሳምረው። ጅማሮአችሁ እንዳይጠለፍ ወይም እንዳይደመሰስ  ይጠብቀው። እናንተም ነቅታችሁ ጠብቁት።
ጉራጌ፣ አማራ፣ ተጋሩ፣ አፋር፣ ኦሮሞ፣  ከምባታ፣ ሀዲያ፣ ሲዳማ፣ ሱማሌ እና ሌሎቻችንን በኢትዮጵያም ሆነ በውጪ ሀገር የምንኖረውን ኢትዮጵያውያንንና ትውልደ ኢትዮጵያውያንን ሁሉ የሚያዛምደን ኢትዮጵያን በስሙ ያስጠራት የንጉሦች ንጉሥ፣ የካህኖች ካህን የነበረው አባታችን ኢትዮጵ ነው። ኢትዮጵ የኖረው በጣና ደሴቶች ላይ ሲሆን ዘመኑም ከ4000 ዐመታት በፊት ነው። እሱም 10 ወንድ ልጆች ወልዶ ነበር። እነዚህ 10 ወንድ ልጆች 10 ነገዶች ሆነው፣ ለ4000 ዐመታት በመባዛት እኛን የዛሬዎቹን ኢትዮጵያውያንን አስገኝተዋል። የኢትዮጵ አስሩ ወንድ ልጆች ስሞችም፡- አቲባ፣ ቢዖር፣ ተምና፣ አቴር፣ አሻን፣ አክዚብ፣ በሪሳ፣ ቴስቢ፣ ቶላ፣ እና አዜብ ነበሩ። የዛሬ 4000 ዐመት ከወጡት ከእነዚህ ስሞች ውስጥ አንዳንዶቹ አሁንም ድረስ ኢትዮጵያ ውስጥ አሉ። ለምሳሌ ወለጋ ውስጥ ይኖር የነበረው የኦሮሞው አጎቴ ስም ቶላ ነበር። ኢትዮጵ ከኦሮሞዎች ጋር ዝምድና ስለአለው ነው፣ የዛሬ 4000 ዐመት ለልጁ የሰየመው ስም ዛሬ የኦሮሞው የኔ አጎትና የሌሎችም ኦሮሞዋች  ስም ሊሆን የቻለው። ከአባታችን ከኢትዮጵ በኋላ የተክተሉት ነገሥታት ልጆቹ፣ የኢትዮጵያን ስልጣኔ በመላው አፍሪካ አሰራጭተው፣ ዛሬ አፍሪካ የሚባለው ሰፊ ምድር እስከ ዛሬ ሁለት መቶ ዐመታት ድረስ ኢትዮጵያ ተብሎ ይጠራ ነበር። LOWER እና UPPER ETHIOPIA ብለው ከፍለውት ነበር።  ከእዚህም በላይ የህንድ ውቅያኖስና ከምእራብ አፍሪካ ብብት ስር ያሉት ውቅያኖሶች ሁሉ የኢትዮጵያ ውቅያኖሶች ነበር የሚባሉት፡፡ ለማመሳከርያ ከዚህ ፅሁፍ እግርጌ የሰፈሩትን ሁለት ጥንታዊ የአፍሪካ ካርታዎች ተመልከቱ።
አሁንም ቢሆን አፍሪካ፣ አፍሪካ የተባለችው በእኛው በአፋሮች ስለሆነ ደስ ይለናል እንጂ አንቆጭም። እስያም እስያ የተባለችው ንግሥተ ሳባ ዙፋኑን በተካችው በዐፄ እስያኤል ስለሆነ በእዚህም እንታበያለን። ኢትዮጵያ የሚለው ቃል ትክክለኛ ትርጉሙ “የተቃጠለ ፊት” ሳይሆን “ቢጫ ወርቅ” ስጦታ ለእግዚእብሄር ነው። ቅዱስ ስሟን ለመፋቅ ወይም ለመቀየር የተመኙ ሁሉ የኢትዮጵያ ስም ከእግዚአብሄር ጋር የተያያዘ በመሆኑ ምኞታቸው ከሽፎ ቀርቷል። ኢትዮጵያን ሊያገንን የተነሳ ሁሉ ይገንናል። ኢትዮጵያን የሚያከብር ሁሉ ይክብራል። ኢትዮጵያን ያኮሰሰ ሁሉ ይኮስሳል።  ኢትዮጵያን ያንቋሸሸ ሁሉ ይንቋሸሻል።  
የእግዚአብሄር ዐይኖች ኢትዮጵያ ላይ ተተክለዋል። በቅዱስ መፅሐፉ ውስጥ እግዚእብሄር ኢትዮጵያን ደጋግሞ የሚጠራት ያለ ምክንያት አይደለም። ከማንም ይልቅ ኢትዮጵያን ስለሚወዳት ነው። በነቢዩ አሞፅ አፍ እግዚአብሄር እንዲህ ይላል፡- “እናንተ የእስራኤል ልጆች ሆይ፤ እናንተ ለኔ እንደ ኢትዮጵያውያን ልጆቼ አይደላችሁምን?”  (አሞፅ 9: 7) ከዚህ ጥቅስ የምንማረው እኛን ኢትዮጵያውያንን እግዚአብሄር ክእስራኤላውያን ይበልጥ ወይም እኩል እንደሚወደን እና ልቡ ውስጥ እንዳለን ነው። ስለዚህ እሱ ጥሎ አይጥለንም።  
የሁለቱ ትልልቅ ህዝቦች፣ ማለትም የኦሮሞና የአማራ በሰላምና በፍቅር መኖር ለሁሉም ኢትዮጵያውያን ዋስትና ነው። ኦሮሞና አማራ እየተጫረሱ እኔ ተገልዬና ተዘልዬ ግንብ አጥሬ፣ ለዘላለም በሰላምና በብልፅግና ለብቻዬ እኖራለሁ ብሎ የሚያስብ ጅል ብቻ ነው። የሁለቱ ጠብ ዳፋ ለሁሉም መዳረሱ አይቀርም፡፡ ደሞም ሁለት ዝሆኖች ሲራገጡ ሳሩ መጎዳቱ አይቀርም፡፡ እንግዲህ ኢትዮጵያ ሰላምና መረጋጋት ትጎናፅፍ ዘንድ ኦሮሞና አማራ በፍቅርና ሰላም አብረው እንዲኖሩ ግድ ይላል። የአማራና ኦሮሞን ቤቶች የሚያነደው እሳት ካልጠፋ፣ ወደ ሌሎቹም ቤቶች መዛመቱ አይቀሬ ነው።
የኢትዮጵያዊነት ብሄራዊ ስሜት በእርግጥም በኢትዮጵያውያን ልቦች ሁሉ ሰርጎ የገባ ፍቅር ነው። ይህ ባለፉት 4000 ዐመት በቅሎ ስር የሰደደ ፍቅር፣ በ30 ዐመታት ውስጥ ሊተን አይችልም። ከእዚህ ጋር በተያያዘ የአቶ መለስ ዜናዊን ስህተት ያስታውሷል። አቶ መለስ ዜናዊ፤ “የአክሱም ሃውልቶችና የጎንደር ቤተ መንግሥቶችን የተጋሩ የጎንደር አማራዎች እንጂ ለኦሮሞና ለጉራጌው፣ እንዲሁም ለሌላው ኢትዮጵያዊ ምኑም አይደሉም፣” ብለው ለሟቹ ለፕሮፌሰር ዶናልድ ሌቪን ቃለመጠይቅ ሰጥተው ነበር። እኔም ለዚህ ስህተት እጸፋውን በዛው ሰሞን በኢትዮጵያን ሪቪው መፅሄት ላይ በእንግሊዝኛ መልሼለት ነበር። እንዲህ ስል፤ “አቶ መለስ ተሳስትሃል። በኋላ በጉራጌነት የተጠሩ ህዝቦች በትግራዩ ተወላጅ በአዝማች ግርማይ መሪነት በዛን ጊዜ የትግራይ ክፍል ከነበረው ከጉራእ ተነስተው ሸዋ ላይ ሰፍረው ነበር። ስለዚህ አክሱም የጉራጌዎችም ነው። ኦሮሞም በጎንደር ቤተ መንግሥት ውስጥ ከመጀመሪያው  አንስቶ አፄ ቴዎድሮስ  እነ ትንሹን ራስ አሊን ከእቴጌዋ እናታቸው ጋር አስወጥተው እስከ አባረሯቸው ጊዜ ድረስ ይፈነጭበት ነበር። ስለዚህ አቶ መለስ ሆይ፤ ስህተትህ አጥፍ ድርብ ነው።”
አቶ መለስ ለዶናልድ ሌቪን ለማስተላለፍ የፈለገው መልዕክት፤ ኢትዮጵያውያን የኢትዮጵያዊነት ብሄራዊ ስሜት የላቸውም የሚል ነበር። እንደ እሱ አባባል፤ ትግራይ የተጋሩ ብቻ ስለሆነች ትግራይ ስትወረር ተጋሩ ያልሆኑት ኢትዮጵያውያን ለትግራይ ደማቸውን ማፍሰስ አልነበረባቸውም። እኛን ምን አገባን? ብለው እጃቸውን አጣጥፈው ማየት ነበረባቸው። ሀቁ ግን የድሉ ተጠቃሚዎች ሌሎች ቢሆኑም በሃገር ፍቅር ተቃጥለው በመቶ ሺህ የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ደማቸውን ለትግራይ  ነፃነት ገብረዋል።  ያኔ ኢትዮጵያውያን ለትግራይ ባይሞቱ ኖሮ፣ ምናልባት ዛሬ ነፃይቷ ትግራይ ባልኖረች ነበር።     
አቶ መለስ ብሄራዊ ስሜት የለውም ያለው ኢትዮጵያዊ ሁሉ፤ በእርግጥም ኤርትራ ትግራይን በወጋች ጊዜ ህገሬ በጠላት ተወረረች ብሎ የብሄራዊ ስሜት ሲቃ ይዞት፣ ግር ብሎ እየተመመ ከድፍን ኢትዮጵያ ተነስቶ ትግራይ ላይ ተሰባስቦ፣ ለሃገሩ ሉአላዊነት ደሙን አፈሰሰ። በዚያን ጊዜ ለአቶ መለስ ዜናዊ በእንግሊዝኛ  ግልፅ ደብዳቤ ፅፌ ተበቀልኩት፡---”አየህ፤ የኢትዮጵያ ህዝብ ሁሉ ሞትን ከመጤፍ የማያስቆጥረው እሳታዊ የእናት ሃገሩ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ስሜት አለው፣” ብዬ። አሁንም ቢሆን ይህ የኢትዮጵያዊነት እሳት በጎሰኝነት አመድ ቢዳፈንም አመዱ ሲበን ተገልጦ ዳግም እየተንቀለቀለ ይነዳል። ሰሞኑንም መንደድ ጀምሯል።
ፕሬዚደንቶች ለማ መገርሳ እና ገዱ አንዳርጋቸው ሆይ!                 
አሁን እናንተ ኦሮሞዎችና አማሮች ወንድማማቾች፣ በባህርዳር ተገናኝታችሁ ያረጋገጣችሁት ዝምድና  እና ትስስር፣ ሁለታችሁም ባነበባችሁት  “የኦሮሞ እና የአማራ እውነተኛው የዘር ምንጭ” በተሰኘው መፅሀፌ  በግልፅ ተንፀባርቋል። ከመፅሀፌ እንደተገነዘባችሁት፣ በእውነትም አሁን ኢትዮጵያ ላለችበት ችግር መፍትሄው ኢትዮጵያዊነት እንጂ በቋንቋ ላይ የተገነባ ጎሰኝነት አይደለም። ጎሳ ማለት ቋንቋ ማለት ነው፡፡ እሱም “ጎሰአ” ማለትም  ተናገረ  ከሚለው የግዕዝ ቃል የፈለቀ ነው። ስለዚህ ቋንቋ ማለት ጎሳ ነው። ጎሳ ማለትም ቋንቋ ነው።  በሌላ አነጋገር፣ ጎሳ የቋንቋ ክፍል እንጂ የደም ወይም የዘር ዘርፍ አይደለም። አንድ ዐይነት ቋንቋ የሚናገሩ ሰዎች በሞላ በዛ ቋንቋ አፍ ከፈቱ፣  የዚያ ቋንቋ ወይም ጎሳ አባላት ይሆናሉ። ይህን በምሳሌ ላሳይ፡- እኔ በፈረንሳይ፣ በጀርመንና አንግሊዝ ሃገሮች ኖሬ፣ ሶስት ልጆች ብወልድና እነሱ ፈረንሳይኛ፣ ጀርመንኛና እንግሊዝኛ ቢናገሩ፣ የእኔ አፍ መፍቻ ደግሞ ኦሮምኛ ቢሆን ልጆቼ ሶስት የተለያዩ ቋንቋዎች በመናገራቸው ጎሳቸው ፈረንሳይ፣ ጀርመንና እንግሊዝ ቢሆንም የርስበርስ ዝምድናቸው አይፋቅም። እኔም ኦሮምኛ ስለተናገርኩ ጎሳዬ ኦሮሞ ቢሆንም አባትነቴ አይሰረዝም። እኛን የሚያዛምደን  ደም ወይም ዘር እንጂ ቋንቋ ወይም ጎሳ አይደለምና።  ስለዚህ ሰዎችን በስጋ የሚያዛምድ ደም ወይም ዘር ነው እንጂ ቋንቋ ወይም ጎሳ አይደለም። ደሞ ቋንቋ ሊረሳም ሊለዋወጥም ስለሚችል አስተማማኝ የማንነት መለያ ሊሆን አይችልም። ኢትዮጵያ ውስጥ 82 ቋንቋዎች እንዳሉ ይነገራል። ቋንቋ ማለት ጎሳ ማለት ስለሆነ በዚህ ቁጥር መሰረት 82 ጎሳዎች አሉ ማለት ነው። በልጆቼ ምሳሌ እንደምናየው፣ ደም አንጂ ቋንቋ አያዛምድም።  እነዚህ ሁሉ የቋንቋ ተናጋሪዎች በደም ወይም በዘር የሚዛመዱት ሁሉም ከኢትዮጵ ወይም ከእሱ 10 ልጆች አብራክ ስለፈለቁ ብቻ ነው። በተጨማሪ ደግሞ በጋብቻ ደም ስለተደበላለቁና በኢትዮጵያ ግዛት ለሺዎች ዐመታት አብረው ኖረው በባህል፣ በልቦና እና እምነት ስለተሳሳቡ እንዲሁም ስለተወሳሰቡና የጋራ የማንነት እሴቶችን ስለአካበቱ  ነው።  እንግዲህ እናንተም የኢትዮጵያን ህዝቦች የሚያዛምዳቸውና አንድ የሚያደርጋቸው፣ ክዛም አልፎ የሚያኗኑራቸው ኢትዮጵያዊነት አንጂ ጎሰኝነት ወይም በቋንቋ ላይ የተመሰረተ ክልል አለመሆኑን ተረድታችሁ፣ሁለታችሁም ከኢትዮጵ ዘር ከወረደው አባታችሁ ከፈላስፋውና ከነብዩ ደሸት፣ የዛሬ 3600 ዐመት አካባቢ በተፈጠራችሁበት በጎጃም ተገኝታችሁ፣ ኢትዮጵያዊነትን መዘመራችሁ ያስመሰግናችኋል። ይህ ሊሆን የቻለው የእግዚእብሄር መንፈስም ዘንቦባችሁ እንደሆነ አኔ አልጠራጠርም። የደም ወተቷን እያጠባች ያሳደገቻቸው ልጆቿ፣ ኢትዮጵያ አመድ-አፋሽ ሆና፣  ጡት ነካሽ ሆነውባታል።  ምንም እንኳን እሷ ብታወፍራቸውና ብታፋፋቸውም፣እንዲሁም ብታቶጅራቸውም፣ ርእሰ ብሄሮቿ እንኳ ሳይቀሩ ለ28 ዐመታት ኢትዮጵያ ብለው ስሟን ለመጥራት ሳይደፍሩ፣ “ሃገሪቱ፣ ይች ሃገር” ይሏት የነበረችውን እናታችንን ኢትዮጵያን፤ እናንተ ከፍ ከፍ አድርጋችኋታል። ነገር ግን ተግባራችሁ በእዚህ ብቻ እንዲገታ አይገባም። አንድ እርምጃ ወደፊት መሄድ አለባችሁ።
ግን ምን ዐይነት እርምጃ? ከዝምድናችሁ በተጨማሪ፣ በቁጥር ብዛታችሁና ክዚህ ቀደም ለኢትዮጵያ ህልውና አብራችሁ የተሰለፋችሁትን መለስ ብላችሁ በማጤን፣ የአመራር ሚና እየተጫወታችሁ ሌሎች ኢትዮጵያውያንንም፣ ማለትም ብዙሃኑን የአፋርን፣ የተጋሩን፣ የሲዳማን፣ የጉራጌን፣ የሃዲያን፣ የከምባታን፣ የሱማሌን፣ የከፋንና ሌሎቹን ሁሉ የኢትዮጵያ ህዝቦች ጋብዛችሁ ተመካክራችሁ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ፍትህና ርትእ፣ የሰብአዊና የሃብት እኩልነትን አስከብሩ። የንግግርና የፅሁፍ ነፃነት፣ በድፍን ኢትዮጵያ የመንቀሳቅስና የመኖር መብትን አስተግብሩ። በጎሰኝነት ጦስ በከንቱ የሚፈሰውን ደም አስቁሙ። የፖለቲካ እስረኞችን ሁሉ በአስቸኳይ አስፈቱ። ኢትዮጵያ ውስጥ እና ከኢትዮጵያ ውጪ ያሉትን  የፖለቲካ ፓርቲዎችና የህብረተሰባዊ ማህበራትን ሳትንቁ በማሰባሰብ፣ ከእናንተ ጋራ ሆነው፣ እነሱም የሃገራቸውን እጣ ፈንታ እንዲወስኑ እድል ስጡአቸው። የእንቅስቃሴአችሁንም አርማ እስከ መጨረሻው ኢትዮጵያዊነትን አድርጉ። አሁን በሃረር የሶማልያ ክልል፣ በእብሪተኞች መሰሪነት ከመኖሪያቸው የተፈናቀሉት ኦሮሞዎችና ከነሱ ጋር በሰላም ለዘመናት የኖሩት ሶማሌዎች ወደ ቀድሞ ቦታቸው እንዲመለሱ ጣሩ። የጎንደር ህዝብ ጥያቄ እንዲመለስ የተቻላችሁን ፈፅሙ።  ይህን ሁሉ ብትፈፅሙ ኢትዮጵያ ውስጥ ሰላም፣ ፍቅር፡ አንድነት፣ እኩልነት፣ የንግግርና የፅሁፍ ነፃነት፣ የመሬት ባለቤትነት፣ የሰብአዊ መብት፣  ዲሞክራሲና የህግ የበላይነት ይሰፍናሉ። ኢትዮጵያም በነፃነቷ ለዘላለም ትኖራለች።  
ፕሬዚደንት ለማ መገርሳ፤ የኢትዮጵያዊነት ስሜት በልብና ደም ስር ውስጥ መገኘቱንና እንደሚያሰክር ልዩ ዕፅ መሆኑን ለመግለፅ  ሞክረው ነበር። እኔ ከዚህ ቀደም ስለ ኢትዮጵያዊነት በጥልቅ አስቤበት የደረስኩበትን መደምደሚያ ከዚህ በታች አያይዤዋለሁ። የኢትዮጵያዊነት ማኒፌስቶ ወይም መግለጫ ብዬዋለሁ። ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን ለምን በኢትዮጵያዊነታችን  መኩራት እንደሚገባንም ዘርዝሬአለሁ። በኢትዮጵያዊነት ጉዞአችሁ ይህ መግለጫ ፋና ይሆናችሁ ዘንድ አበርክቼላችኋለሁ። ከእሱ በተጨማሪ፣ እናንተ ከዚህ ቀደም ባነበባችሁት “የኦሮሞ እና የእማራ እውነተኛው የዘር ምንጭ” በተሰኘው መፅህፌ፣ እና አሁን ሰሞኑን ባሳተምኩት ሥራዬ  ውስጥ፣ ማለትም “የተሰወረውና ያልተነገረው የአይሁዳውያን እና የኢትዮጵያውያን ታሪክ” በሚለው መፅሀፌ ውስጥ ኢትዮጵያዊነት ፍንትው ብሎ ስለሚታይ በእነሱም ልትመረኮዙ ትችላላችሁ።  በዚሁ በአይሁዳውያንና አትዮጵያውያን የታሪክ መፅሃፍ ውስጥ የኢትዮጵያዊነት ምንነት ዝርዝር፣ በተቀፅላ በቋሚነት ስለተቀመጠ መፅሃፉን እንደ አሻችሁ እየገለጣችሁ፣ እሱን ለመመልከት የሚያግዳችሁ ነገር የለም።     
የኢትዮጵያዊነት ምንነት መግለጫ እና ለምን በኢትዮጵያዊነታችን መኩራት እንደሚገባን
MANIFESTO OF ETHIOPIANISM
 ክፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶሎሳ ጅግሳ የጽፈት ጠረጴዛ
ኢትዮጵያዊ መሆን እጅግ የሚያኮራ ነገር መሆኑን ባለመገንዘባችንና “ኢትዮጵያ” የሚለውን ቃል ትክክለኛ ፍቺ ባለማወቃችን፣ አንዳንዶቻችን በኢትዮጵያዊነታችን እናፍራለን።  
“ኢትዮጵያዊነት” ምን ማለት እንደሆነ  ለማብራራት የቃሉን ትርጉም  ምንጭ ማወቅ ግድ ይላል፡፡ “ኢትዮጵያ” ማለት ቢጫ ወርቅ ስጦታ (ለእግዚአብሄር ማለት) ነው፡፡ ይህ ስም የተሰጠው ለኢትዮጵያ መስራችና የኢትዮጵያውያን አባት ለሆነው ለኢትዮጵ ነው፡፡ እንግዲህ ኢትዮጵያ የሚለው ቃል ወርዶ፣ ወርዶ  ወደ እኛ የደረሰው ከሱ ስም ነው ማለት ነው፡፡ “ኢትዮጵያዊ” ማለት በግሪክ ቋንቋ የተቃጠለ ፊት ነው  የተባለው ነጭ ውሸት ነው። በግሪክ መዝገበ ቃላት ውስጥ እንደዚህ የሚል ቃል የለም። ደሞም የኛ ፊት የተዋበ እንጂ የተቃጠለ አይደለም።     
ኢትዮጵያውያንን ሁሉ አንድ የሚያደርጋቸው፣ ከፍ ሲል ኢትዮጵያን በስሙ ካስጠራው ከካህኑና ከንጉሠ ነገሥቱ ከኢትዮጵ፣ ዝቅ ሲል የሱ ዘር ከሆነው ከነቢዩና ከፈላስፋው ከደሸት መውረዳቸው ነው፡፡ ኢትዮጵ የዛሬ 4000 ሺ ዐመት አካባቢ ዐስር ወንድ ልጆች ወልዶ ነበር። ስማቸውም እንደሚከተለው ነው፡፡--
አቲባ፣ ቢኦር፣ ተምና፣ አቴር፣ አሻን፣ አክሲብ፣ በሪሳ፣ ቴስቢ፣ ቶላ እና አዜብ ናቸው፡፡ ከእነዚህ ስሞች ውስጥ አሻን፣ በሪሳ፣ ቶላ እና አዜብ አሁንም ድረስ ኢትዮጵያ ውስጥ አሉ። የኢትዮጵ ዘር፣ የነቢዩ ደሸት ልጆች ደግሞ መደባይ፣ መንዲ፣ ጂማ እና ማጂ ይባሉ ነበር፡፡ ማጂ ማራ (አማራ) ን እና ጀማን ወለደ። ሰዎቹ የተሰየሙት የዛሬ 3600 ዐመት ቢሆንም፣ እነዚህ ስሞች አሁንም ኢትዮጵያ ውስጥ አሉ፡፡
የኢትዮጵ 10 እና የደሸት 4 ልጆች ተባዝተው ዛሬ ኢትዮጵያ ውስጥ የአሉት ሰዎች በሞላ ሆነዋል። በኢትዮጵያና በመላው ዐለም ባሉት ትውልደ ኢትዮጵያውያን የደም ስሮች ውስጥ የኢትዮጵ እና የደሸት ደም ይዘዋወራል፡፡ ስለዚህ ኢትዮጵያውያን በሞላ ምንጫቸው አንድ እና አንድ ነው፡፡ ስለዚህም ቋንቋቸው  ቢለያይም ደምና ዘራቸው አንድ ነው። ቋንቋ ደግሞ የመግባቢያ መሳሪያ እንጂ ዘርን አመላካች ወይም የዘር ክፍል አይደለም፡፡ ቋንቋ ማለት ጎሳ ማለት ነው፡፡  
ቅዱስ ዳዊት በመዝሙሩ ጎስአ (ጎሳ)  ልብየ ሰናይ ይላል፡፡ ልቤ መልካም ተናገረ፣ ማለት ነው። አገሳ ወይም ከውስጥ አወጣ፣ የተሰኘውም ቃል ከዚህ የመነጨ ነው። ጎሳ ማለት አንድ ዐይነት ቋንቋ የሚናገሩ ሰዎች ነው። ዘር ማለት አይደለም።  ለምሳሌ አንድ አባትና እናት ወደ ፈረንሳይ ሃገር ሄደው ልጅ ቢወልዱና ፈረንሳይኛ ቢናገር፣ ከዛም ወደ አሜሪካን አገር ተጉዘው፣ ሌላ ልጅ ወልደው እንግሊዝኛ ቢናገር፣ ልጆቻቸው ሁለት የተለያዩ ቋንቋዎች ስለተናገሩ ወንድማማችነታቸው አይፋቅም፡፡ ወላጆቹም አማርኛ፣ ኦሮምኛ ወይም አፋርኛ በመናገራቸው ወላጅነታቸው አይደመሰስም፡፡ ደምና ዘራቸው አንድ ነውና። ስለዚህ ወሳኙ ቋንቋ ሳይሆን ደምና ዘር ነው፡፡ ቋንቋ ወይም ጎሳ ወሳኝ አይደለም። መግባቢያ ነው እንጂ፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥም ከ80 በላይ ቋንቋዎች የሚናገሩ ጎሳዎች አሉ፡፡ ሆኖም እነዚህ ጎሳዎች በቋንቋ ቢለያዩም በደማቸው አንድ የኢትዮጵ ልጆች ናቸው፡፡ የሚያገናኛቸውም ኢትዮጵያን በስሙ ያስጠራው ኢትዮጵ አባታቸው ነው፡፡
ከ200  ዐመታት በፊት መላው አፍሪካ ኢትዮጵያ ይባል ነበር። የዚህ ምክንያቱ የኢትዮጵ ተወላጆች በመላው አፍሪካ ተሰራጭተው፣ አፍሪካን አሰልጥነው ስለኖሩበት ነው። የአውሮፓ ቅኝ ገዢዎች አፍሪካን በቅኝ መግዛት ከጀመሩ ወዲህ ግን ኢትዮጵያ የሚለው ቃል ቀርቶ አህጉሩ አፍሪስካውያን በተባሉት አፋሮች አፍሪካ መባል ጀመረ። አሁንም ድረስ ስሙ ክእኛው ስለ አልወጣ ቅር አንሰኝም።
አንድ ኢትዮጵያ ውስጥ የተወለደ ወይም ትውልደ-ኢትዮጵያዊ ሰው በሁለት ምክንያቶች ኢትዮጵያዊ ይሆናል። አንደኛ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ በመወለዱ። ሁለተኛ፣ ትውልደ-ኢትዮጵያዊ በመሆኑ። ሁለቱንም የሚያገናኛቸው በደምና በዘራችው ክኢትዮጵ መውረዳቸው ነው።  ኢትዮጵያዊነት ማለት በዐለም ልዩ የሆነ፣ ኢትዮጵያ ውስጥ ብቻ  የሚገኝ፣ ዮጵ የተባለ ቢጫና ብርቅዬ ወርቅነት ማለት ነው። ክዚህም በላይ፣ ለዐለሙ ፈጣሪ ለእግዚአብሄር ብቻ የሚቀርብ ልዩ ገጸ-በረከት ማለት ነው።
 ኢትዮጵያዊነት ማለት የህይወት ምንጭነት፣ የሰብእና  መገኛ ስፍራ ማለት ነው።
ኢትዮጵያዊነት ማለት የስነመለኮት ከፍታ፣ የስልጣኔ መጀመሪያ፣ የሰው ዘር አርአያ፣ የስነምግባር ልእልና ማለት ነው።
ኢትዮጵያዊነት ማለት የህርነት፣ የጀግንነትና የፍትሀዊነት ተምሳሌነት ነው።
ኢትዮጵያዊነት ማለት የእኩልነትና የሰው ልጅ ክቡርነት አርማ ነው።
እትዮጵያዊነት ማለት የታማኝነትና የተአማኒነት እንዲሁም የመለኮት ማህደርነት ነው።
ኢትዮጵያዊነት ማለት የፅናት፣ የብርታትና የትእግስትና የዘላቂነት ምልክት ነው።
ኢትዮጵያዊነት ማለት የሀቀኝነትና የእውነተኛነት ምሳሌ ነው።
ኢትዮጵያዊነት ማለት የርህራሄና የቸርነት ናሙናነት ነው።
ኢትዮጵያዊነት ማለት ሰው አክባሪነት፣ እንግዳ ተቀባይነት፣ ይሉኝተኝነትና አዙሮ ተመልካችነት ነው።
ኢትዮጵያዊነት የጥበበኝነት ቁንጮ፣ የብልህነት እራስ ማለት  ነው።
ኢትዮጵያዊነትማለት የቅድስና እና የብጹእነት ጫፍ ነው።
ኢትዮጵያዊነት ማለት የወንድማማችነትና የእህትማማችነት፣ የመተዛዘን ማማነት ነው።
ኢትዮጵያውያንና ትውልደ ኢትዮጵያውያን በሞላ በሚከተሉት ምክንያቶች በኢትዮጵያዊነታቸው ሊኮሩ ይገባል። የኩራቶቹን ሁሉ ምክንያቶች ለመዘርዘር ጊዜም ቦታም ስለሚፈጅ ጥቂቶቹ ብቻ ይቀርባሉ።  
1.  ኢትዮጵያ በሳይንስም ሆነ በመፅሐፍ ቅዱስ የሰው ዘር መገኛ በመሆኗ፣
2.  ከ4500 ዐመታት በፊት በንጉሥ ስብታህ አማካኝነት የጋዜጣንና የፖሊስን ሥራ ከዐለም ቀድማ ኢትዮጵያ በማቋቋሟ፣
3.  በዐለም ላይ የሌለ ከኖህ ጀምሮ ስሞቻቸውና የነገሡበት አዝማናት የተመዘገበ ነገሥታት በመኖራቸው፣
4. አባታችን ኢትዮጵ እና ሚስቱ እናታችን ሲና እንቁዮጵግዮን፣ መሲሁ እየሱስ ሲወለድ፣ ልጆቻቸው ወደ እስራኤል ተጉዘው ገዳ  እንዲያበረክቱለት በእግዚአብሄር ትዕዛዝ ከኢየሩሳሌም  ወደ ኢትዮጵያ መምጣታቸውና ጣና ጎጃም ላይ በተልእኮ በመስፈራቸው፣
5. የኢትዮጵና የእንቁዮጳግዮን  ልጆች ታላላቅ ነገሥታት ሆነው በአፍሪካ፣ በመካከለኛው ምስራቅና እስያ በመንሰራፋታቸው፣ ስልጣኔአቸውን በማሰራጨታቸውና መላውን አፍሪካ ኢትዮጵያ በማሰኘታቸው፣
6.  አጼ እስያኤል እስያን አሰልጥኖ በስሙ አህጉሩን እስያ በማሰኘቱ፣ እጽዋትንና እንስሳትን አዳቅሎ አዲስ ውጤት ያስገኘው በዐለም የመጀመሪያው ጄኔቲክ ኢንጂኔር በመሆኑ፣ ክ3000 ዐመታት በፊት ይኽው ትልቅ ሰው ምናልባት በዐለም የመጀመሪያ የሆነውን ሰንደቅ አላማችንን በመፈልሰፉ፣
7. በንግሥተ ሳባ ትልቅነት--- ኢትያኤል የተባለች የሳባ ንግሥት በመጽሃፍ ቅዱስ ውስጥ የተጠቀሰች፣ የዐለሙ ፈጣሪ እየሱስ ክርስቶስ ስሟን ጠርቶ፣ የንጉሥ ሰለሞንን ጥበበኝነት ለመፈተን ኢየሩሳሌምን መጎብኝቷን የመሰከረላት ትልቅ ሰው በመሆኗ፣
8.  በአፋሮች ትልቅነት---አፍሪካ በአፋሮች አፍሪካ ስለተባለች። ከ3000 ዘመናት በፊት አፋሮች ታላቅ መርከብ ገንቢዎችና መርከበኞች እንዲሁም በመካከለኛው ምስራቅና በእስራኤል ስመጥር የኦፊር ወርቅ ነጋዴዎች ከመሆናቸውም በላይ ተጽእኖ አሳዳሪዎች በመሆናቸው፣
9.  የኢትዮጵ ዝርያዎች 12 ጠበብት ነገሥታት ሆነው እስራኤሎቹ የሚጠብቁት መሲህ መወለዱን ሳያውቁ የእኛዎቹ ከሩቅ ሆነው የመሲሁን መወለድ ተረድተው፣ ከኢትዮጵያ ተነስተው በኮከብ እየተመሩ፣ ቤተልሄም ደርሰው ለመሲሁ ለኢየሱስ ክርስቶስ ገዳ በማቅረባቸው፣
10.   በዐለም ላይ ከአሉት ነገሮች ሁሉ በጣም ውድ እና ብርቅ የሆነው  የታቦቱ ማረፊያና መኖርያ አድርጎ እግዚአብሄር ከእስራኤል ይልቅ ኢትዮጵያን በመምረጡ፣
11.  ኢትዮጵያ በዳዊት መዝሙርና በሌሎችም መጽሃፍ ቅዱስ ገጾች ውስጥ በእግዚአብሄር በመጠራትዋ፣
12. ከእግዚአብሄር በታች ኢትዮጵያ አይሁዳውያንን በእግራቸው ስለማቆማቸው፣ ከነብዩ ከሙሴ ጊዜ ጀምሮ ኢትዮጵያ አይሁዳውያንን ወደ ግዛትዋ እያስገባች ጥገኝነት፣ መሬት እና ንግሥና ሳይቀር እየሰጠች አስተናግዳለች። በሌላ ሃገራት ግን እስራኤላውያንን ያሳድድዋቸው፣ እንዲሁም ይገድሏቸው ነበር። በእኛ በጎ አድራጊነት እንኮራለን።  ክዚህ በተጨማሪ፣ እስራኤላውያን በባርነት በባቢሎን 70 ዐመት ሲሰቃዩ ቆይተው ወደ ኢየሩሳሌም ተመልሰው ቤተመቅደሳቸውን ካደሱ በሁዋላ መጻህፍት አጡ። መጽሃፍ ቅዱስን እና ሌሎች ብርቅዬ መጻህፍትን ኢትዮጵያ ስለላክችላቸው እንታበያለን።  
13.  ትልቅ ለሚባለው ለሙሴ ጥገኝነት እና ሚስት ኢትዮጵያ ሰጥታ፣ የፍትህንና የሕግ አስተዳደርን እንዲሁም ነገረ መለኮትን ስለአስተማረችው፣
14.  ከባለፉት 3800 ዐመታት ጀምሮ ኢትዮጵያ በርካታ  የሴት ነገሥታትን በኢትዮጵያና በግዛቶቿ ላይ ሾማ የሴቶችን መብት በማስከበር በዐለም ግንባር ቀደም በመሆኗ፣
15. ኢትዮጵያ ክጣና ሃይቅ ተነስታ ወደ ኑብያና ግብጽ ወርዳ፣ የግብጽንና ኑብያን ስልጣኔ በመፍጠርዋ፣ ሕልቆ መሳፍርት ወንዶች ፈርኦኖችንና ህንድኬ በሚል ማእረግ 19 የሴት ነገሥታትን በግብጽ፣ በሊቢያና ኑብያ ላይ በመሾሟ፣   
16.  አጼ አክሱማይ የዐለም አባት፣ የነገሥታት እራስ ተብሎ ከባቢሎን ሳይቀር በንጉሦች የተበደሉ ዜጎቹ ለአቤቱታ ወደ እሱ ሲመጡ እምባቸውን ስለአበሰላቸው፣   
17.  ኢየሱስ ክርስቶስ፣ ቅድስት ማርያምና ቅዱስ ዮሴፍ በኢትዮጵያ ግዛት፣ በግብጽና በኢትዮጵያ ውስጥ ጥገኝነት አግኝተው በመኖራቸው፣
18.  ኢየሱስ ራሱን ለዐይሁዳውያን ሳይገልጽ በ22  ዓመት ዕድሜው ወደ ኢትዮጵያ መጥቶ፣ ለኛ ቅድሚያ ሰጥቶ ራሱን ለኛ ገልጾ፣ እስከ 25 ዓመት ዕድሜው ድረስ ሲያስተምርና ሲፈውስ ሃገራችን ውስጥ በመኖሩ፣
19. ኢየሱስ ወደ ኢትዮጵያ ሊገባ ሲል ግብጽ ሳለ ጥገኝነት የሰጠውን ንጉሥ አማናቱ ተትናይን እግረመንገዱን  ጎብኝቶ፣ ለአንድ ሳምንት እሱ እልፍኝ ውስጥ ሰንብቶ ነበር። ኢየሱስ ወደ ኢትዮጵያ ድንበር እንደተሻገረ እልፍኙን ንጉሥ አማናቱ ተትናይ ቤተክርስትያን አደረገው:። ኢየሱስ ክርስቶስ በህይወቱ እያለ እኛ በዐለም የመጀመሪያውን  ቤተ ክርስቲያን በመመስረታችን፣
20. የንግሥት ሕንደኬ ዣን በጅሮንድ በቅዱስ ፊሊፖስ መጠመቁና እሱ ከአውሮፓውያን ክርስትያንነት ቀድሞ ክርስትናን ወደ ኢትዮጵያ በማስገባቱ፣
21.   አውሮፓውያን ወደ ክርስትና የተሽጋገሩት ከአረማዊነት ሲሆን ኢትዮጵያውያን ግን ከኦሪት ሃይማኖት ነው። ይህ በመሆኑም የክርስትና እውቀታችንን ከአውሮፓውያን ለማጥለቅና ለማበልጸግ አስችሎናል። በእዚህም እንኮራለን።
22. ኢየሱስ ክርስቶስ፣ “ኢትዮጵያውያን ውስጣቸው የኖርኩ ዘመዶቼ ናቸው፣ በእኔ ያምናሉ፣ እናንተ እነሱን  ለማሳመን ሳትደክሙ አጥምቃችሁ አቁርቡአቸው፣” ብሎ ደቀመዛሙርቱን በርጠለሚዎስን፣ ማቴዎስን፣ ቶማስን ናትናኤልን፣ እንድርያስን እና ማርቆስን ወደ ኢትዮጵያ ልኳቸው፣ ክሃዋርያቱ ግማሾቹ ወደ ኢትዮጵያ መጥተው ስለአስተማሩ፣ በእግዚአብሄር እንደተከበርን ስለሚሰማን፣
23. ኢትዮጵያውያን ክርስትያናት እና አይሁዳውያን ያለ ደም መፋሰስ ተስማምተው የኦሪትንና የክርስትናን አምልኮ ስርዐቶች የሚተዉትን ትተው፣ የተረፉትን ወደ ክርስትና በማሸጋገራቸው፣
24. ክኢትዮጵ እስከ አጼ እስያኤል ድረስ የኢትዮጵያ ነገሥታት ክእግዚአብሄር ጋራ በቀጥታ የሚነጋገሩ ሊቀካህናት መሆናቸውና በፈሪሃ እግዚአብሄር ህዝባቸውን በፍትህና ርትህ በማስተዳደራቸው፣ይህም ክስተት በዐለም ላይ የሌለ በመሆኑ፣
25. ነብዩ መሃመድ በችግር ላይ ሳለ ዘመዶቹን ወደ ኢትዮጵያ ልኮ ኢትዮጵያ ጥገኝነት ስለሰጠቻቸው፣ መሃመድ ራሱ ሙስሊም ከመሆኑ በፊት ኢትዮጵያ በመካና በመዲና ውስጥ የራስዋ ቤተክርስትያን ስለነበራትና እሱ የኢትዮጵያ ቤተክርስትያን ተጠቃሚና የሊቀካህናቱ ወዳጅ በመሆኑ፣ እንዲሁም በመጀመሪያ አላሁ አክበር ብሎ የጮኸው ድምጸ-መረዋው ኢትዮጵያዊ ቢላል ሃበሽ በመሆኑ፣ ነብዩም “ካልነኳችሁ ኢትዮጵያውያን ላይ ጂሃድ አታኪያሂዱ” በማለቱ፣
26.  በዐለም ላይ በሌለ አኳኋን  ኢትዮጵያ ውስጥ  ሙስሊሞችና ክርስትያኖች በሃይማኖት ልዩነቶች ካለመጋጨታቸውም በላይ ተፋቅረውና ተባብረው፣ ቤተክርስትያኖችና መስጊዶች አንዱ ለሌላው በመገንባታቸው፣ አብረው በመጸለያቸውና ከተዋደዱ ያለ ብዙ ችግር መጋባት በመቻላቸው፣
27.  ቀዳማዊ አባቶቻችን  በዐለም ላይ የሌሉ ብርቅዬ የሱባ እና የሳባ ፊደላትን ፈጥረው ስለአቆዩልን፣
28.  እንደ አክሱምና ላሊበላ ዐይነት ያልተለመዱ ቤተክርስትያናት መኖራቸው፣ ክነሱ የተገኘው ቅዱስ ያሬድ ልዩ ማህሌትን በመድረሱና ክአውሮፓውያን 700 ዐመታት አስቀድሞ የዜማ ምልክቶችን በመፈልፈሰፉ፣ እንዲሁም  የማንንም የማይመስል ቅዳሴና ስርዐተ ዐምልኮ ስለአለን፣
29. በቀለማችንና በተክለ-ሰውነታችን የተቅለመለምን አበቦች ከመሆናችንም በላይ የተለያዩ አልባሳት፣ ዳንኪራዎችና ባህላዊ እሴቶች ስለአሉን፣
30. ከተለያዩ የምግብ አሠራር ሙያዎች በተጨማሪ ለዐለም ምግቦች ያበረከትናቸው እንደ ቡና እና ጤፍ የመሳስሉ አዝእርት ስለአሉን፣
31. ኢትዮጵያ፣ ባለፉት 4000 ዐመታት ጠላቶችዋን ሮማውያንን፣ ግብጾችን፣ አረቦችንና ሌሎችንም በጦርነቶች ድባቅ እየመታች፣ ነጻነታችንንና ክብራችንን በማስጠበቋና ለዐለም ጥቁር ህዝቦች ሁሉ የነጻነትና የድል አድራጊነት ዐርማ እና ተምሳሌት በመሆንዋ እንኮራለን። አባቶቻችን በኮሪያ ዘምተው፣ በተሰማሩበት የጦር ሜዳ ሁሉ ድል-አድራጊዎች ክመሆናቸውም በላይ አንዳቸውም ባለመማረካቸውና ጠላት ሬሳቸውን አንኳን ለመያዝ ባለማቻሉ ደጋግመን እንኮራለን።     
32. ቀጥሎም፣ ደረታችንን የሚያስነፋን በኢየሱስ ክርስቶስ የደም ስር ውስጥ የእኛ የኢትዮጵያውያን ደም መፍሰሱ ነው። እንዴት ቢሉ፣ ኢየሱስ ክርስቶስ የቅዱስ ዳዊት ዘር በመሆኑና የእሱም እናት አይሁዳውያን አዶልያ ወይም አዴል የሚሏት፣ እኛ ደግሞ ሀብሌ የምንላት የኢትዮጵ የቀጥታ ተወላጅ ኢትዮጵያዊት በመሆኗ።
33. በመጨረሻም በቀዳማዊ ወላጆቻችን ክህነታዊ ማእረግና ክብር እንኮራለን። እግዚአብሄር ሁለት ዐይነት የክህነት ማእረግ ሰጥቶአል። አንደኛው ዝቅተኛውና ለዐይሁዳውያን ብቻ የሰጠው የአሮን ክህነት ሲሆን ሁለተኛው እጅግ ከፍተኛው ለኢትዮጵ አባት ለሳሌሙ ንጉሥ ለመልከጸዲቅ ያቀደው ነው። የአሮን ሹመት ካህንነት ብቻ ሲሆን የመልከጸዲቅ ግን የንጉሥ ንጉሥነት እና የካህን ካህንነት ነው።
መለኮታዊ እና ዐለማዊ ማእረግ ነው። ራዕየ ዮሃንስ አንድሚተነብይልን፤ የዐለሙ ፈጣሪ ኢየሱስ ከርስቶስ ወደፊት በመልከጸዲቅ ስርዐት የካህን ካህን፣ የንጉሥ ንጉሥ ሆኖ በኢየሩሳሌም ላይ የራሱን ምድራዊ መንግሥት መስርቶ ይነግሣል። በዛም ጊዜ አባታችን ሆይ መንግሥትህ ይምጣ፣ ብለን የጸለይነው ይፈጸማል። የኢየሱስ ክርስቶስ ክህነትና ንግሥና በአባቶቻችን በመልክጸዲቅ፣ በኢትዮጵ እና በልጆቹ ስርአት ስለሆነ እጅግ እንኮራለን።
የሚያኮሩንን ሁሉ ነገሮች በእርግጥ ዘርዝረን አንጨርሳቸውም። ከብዙ በጥቂቱ ከላይ የሰፈሩት ናቸው። እነሱን መስፈንጠሪያ ኢድርገን፣ ደረታችንን ነፍተን፣ በኢትዮጵያዊነታችን ታብየን፣ እርስ በርሳችን ተከባብረን፣ ተፋቅረንና ተቃቅፈን በእኩልነት ወደፊት እመር! እንላለን። እንግዲህ ጥንታዊ አባቶቻችንና እናቶቻችን ትልቅ ከነበሩ፣ እኛም የእነሱን አርአያና ፈለግ ተከትለን በመነሳሳት፣ ወደፊት ትልቅ የማንሆንበት ምክንያት የለም።
መላው አፍሪካ ድሮ ኢትዮጵያ ይባል እንደነበር የሚመሰክር ጥንታዊ ካርታ ከዚህ በታች ሰፍሮአል። ያኔ አፍሪካ የታችኛውና የላይኛው አፍሪካ ተብሎ ነበር የተከፈለው። ዝቅ ብለው እሱን ከማየት አይዘናጉ።

Saturday, 18 November 2017 12:42

ማስታወሻ

 የሄድንበትን እንሄድበታለን ወይ?

   የዚህ መጽሐፍ ዓላማ ያለፈውን ለመውቀስ አይደለም፤ ያለፈ የሚመስለውንና አሁንም በውስጣችን ያለውን እውነት ለማውጣትና ለማሳየት፣ ለመናገርም ነው፤ ያለፈው ትውልድ የፈጸመውንና አሁንም በእኛ ውስጥ ያለፈውን ማውጣት ያለፈውን መውቀስ ሳይሆን ያለውን ለማጽዳት መሞከር ነው፤ አንዳንድ ሰዎች ቀድመው እንደተገነዘቡት አውቃለሁ፤ ለምሳሌ ወይዘሮ ባዩሽ በፌስቡክ የሚከተለውን ብላለች፡- -- ‹‹ኢትዮጵያዊ ራሱን ከመውደድ ያልወጣን ነን፤ አገራዊ ስሜት አልገባንም፡፡›› (ኢትዮጵያዊያን ራሳችንን ከመውደድ አልወጣንም፡፡) የኔ ዓላማ ያለውና ወደፊት የሚመጣው ራሱን ለማስተካከል ራሱን በአለፉት ውስጥ አይቶ ራሱን እንዲታዘብ ነው፤ ራሱን ታዝቦ ራሱን እንዲለውጥ ነው፡፡
በተለያዩ መንገዶች የረዱኝን ብዙ ሰዎች ለማመስገን እፈልጋለሁ፤ ነገር ግን ዘመኑ ወንጀል በንክኪ በሰዎች ላይ የሚለጠፍበት ስለሆነ ማመስገን ማስወንጀል ይሆናልና በደፈናው እግዚአብሔር ከጨለማ ያውጣንና ስሞቻችሁን እየጠራሁ እንዳመሰግናችሁ ያብቃኝ በማለት አልፈዋለሁ፡፡
በ966 አንድ ትንሽ ጽሁፍ ‹‹ኢትዮጵያዊነት፡- ልማት በኅብረት›› በሚል ርእስ አሳትሜ ነበር፤ በዚያ ጽሑፍ ውስጥ የተማሪዎች ንቅናቄ የሚባለውን በጨረፍታ ነቅፌው ነበር፤ አራት ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርሲቲ የሚያስተምሩ ንዑሳን ምሁራን በአዲስ ዘመን ጋዜጣ ላይ በረዥሙ ልባሼ እንዳሸጥ አድርገው አንጀታቸውን አራሱ፤ በዚያን ጊዜ እኔ በፓርላማው ለመርማሪ ኮሚስዮን በከፍተኛ ድምጽ እኔ ሳልፈልግ በመመረጤ ተቃጥለውም ነበር፤ ከአራቱ ንዑሳን ውስጥ የኅሊናውን ሬሳ ተሸክሞ የቀረው አንድ ብቻ ነው፤ ሦስቱ የመጨረሻው ጥሪ ደርሷቸው ሄደዋል፤ ይህንን የማነሣው በአገርና በሕዝብ ጉዳይ ጽፎ ወይም ተናግሮ ከየጎሬአቸው እየወጡ የሚሳደቡትንና የሚወነጅሉትን ችላ ለማለት ግድ መሆኑን ለማመልከት ነው፤ በነዚህ ሰዎች ስድብ ተስፋ የምንቆርጥ ከሆነ ሁላችንም ተስፋ-ቢስ እንሆናለን፤ ጦር የሚወረወርብን ከፊትለፊት ብቻ ሳይሆን ከጎንም ነው፤ ትግሉ ከገዢዎቹ ጋር ብቻ ሳይሆን ተቃዋሚ ነን ከሚሉ የሥልጣን ጥመኞች ጋርም ነው፡፡
ሌላም ነገር ለማስታወስ እፈልጋለሁ፤ የዛሬ ሃያ አምስት ዓመት ግድም ጌቶቻችን ገና የተሳለ ጥርሳቸውን ማሳየት ሲጀምሩ አካሄዳቸው ስላላማረኝ ‹‹የክህደት ቁልቁለት›› በሚል ርእስ አንድ ትንሽ መጽሐፍ አሳትሜ ምን ያህሉ እንደገባው፤ ከገባውም ውስጥ ምን ያህሉን ለተግባር እንደቀሰቀሰው አላውቅም፤ ኢትዮጵያውያን የመናገር እንጂ የመደማመጥ ችሎታ የለንም፤ ስለዚህም አብዛኛው ሲንጫጫ እኛን ለመጉዳት ተግባር የተሰለፉት ሥራቸውን ሲሠሩ እያለቀስን ቆመን እንመለከታቸዋለን፤ ሲሞቱም እናለቅሳለን፤ ለውጭ ተመልካች ጭቆናውና አፈናው፣ ሕግ-አልባነቱ የተስማማን ይመስላል፡፡
ዛሬ ሁላችንም የምናለቅስበት ዕለት የደረሰ ይመስላል፤ ለጨቋኞቹ ገዢዎቻችን የገነቡት ሁሉ የማያድሩበት ቤት እየሆነባቸው ተጨንቀዋል፤ በትዕቢት ዓይኖቻቸውና ልቦቻቸው ተደፍነው ሃያ አምስት ዓመታት ቀርቶ ሃያ አምስት ቀኖች አርቆ የማየት ችሎታ እንደሌላቸው በብዙ መንገድ ብዙ ጊዜ አሳይተውናል፤ ያከማቹት ብር ነፋስ የሚወስደው እየሆነባቸው ነው፤ መሰብሰቡም እየከበደ ነው፤ አንድ ማን እንዳለው የማላውቀው የእንግሊዞች አባባልን ያስታውሰኛል፡- ምንም ሳይጨምር ሁልጊዜ የሚያወጣ ቶሎ ብሎ መጨረሻው ላይ ይደርሳል፤ (By always taking out and never putting in one soon reaches the bottom.) ገዢዎቻችን ቢጠፉም ቢለሙም በሥራቸው ነው፤ እኛ ግን የምንጠፋው በዝምታችንና በወላዋይነታችን ነው፡፡
የኢትዮጵያን ሕዝብ ጠባይና ታሪክ ለተረዳ ያንዣበበብን አደጋ ቀላል አይደለም፤ ከጀመረም በቀላሉ የሚመለስ አይሆንም፤ እንዳያጫርሰን አንጀምረው፤ ከ1966 ዓ.ም ቀደም ብሎ የጀመረው የጎረምሶች የሥልጣን ጥም አሁን ያገረሸበት ይመስላል፤ ከሆነላቸው አዲሶቹ ጎረምሶች ደግሞ ለሚቀጥሉት ሀምሳ ዓመታት ያህል ያተራምሱናል፤ ቁጭ ብሎ መጠበቅና ማየት ነው!
ቅድመ-ነገር
ከሰባ ዓመት ዕድሜ በላይ ለሆኑ ኢትዮጵያውያን ይህ መጽሐፍ ለብዙዎች የቡና ወሬ፣ ምናልባትም ለጥቂቶች አእምሮን የሚኮረኩር ነገር ያገኙበትና ያዳብሩት ይሆናል፤ መጽሐፉ አእምሮአቸውን የሚኮረኩራቸው ኢትዮጵያውያን የወደፊትዋን ኢትዮጵያ ለመቅረጽ ትልቅ አስተዋጽኦ እንደሚያደርጉ አልጠራጠርም፤ የማስተዋል አድማሳቸውን ሰፋ አድርገው ለረጅም ጊዜ ጥልቀትና ዘላቂነት ባለው የሚለዋወጥ ለውጥ፣ የኢትዮጵያ ሕዝብ አእምሮው እንዲነቃ፣ ኅሊናው እንዲበራ፣ ልቡ ከቂምና ከክፋት እንዲጸዳ አድርጎ ወደጠመዝማዛው የዳገት ጉዞ ውስጥ የሚያስገባውን መንገድ እንዲያገኝና እንዲከተል ማገዝ ይችላሉ፡፡
የኢትዮጵያ ወጣቶች ደግሞ የአጠቃላዩን የዓለም ሁኔታ በልዕለ ኃያላኑ በአሜሪካ፣ በሩስያና በአውሮፓ ፉክክር የሚታመስ መሆኑን፣ የመሀከለኛው ምሥራቅ በእስራኤልና በአረቦች ጥላቻና ፍጥጫ እየቆሰለ የሚደማ መሆኑን፣ የአፍሪካ ቀንድ በልዕለ ኃያላኑና በመሀከለኛው ምሥራቅ ወኪሎቻቸው ለብጥብጥ እየተዘጋጁ መሆናቸውን መገንዘብ ያለምንም ጥርጥር የሚገጥሟቸውን ችግሮች ለመቋቋም ይረዳቸዋል፤ የዓለም ሕዝብ ተያይዟል፤ አንድ ቆራጥ ሰው ብቻውን የዓለምን ሕዝብ ማተራመስ የሚችልበት ዘመን ነው፤ በጥቂት ግለሰቦች አልጠግብ-ባይነት በብዙ ሚልዮን የሚቆጠሩ ሰዎች በደሀነት የሚደሙበትና የሚሞቱበት ሁኔታ በሙሉ-ዓለም (GLOBALIZATION) ሥርዓት እየታየ ነው፡፡
ዋናው ነገር የኢትዮጵያን ሕዝብ ከፍርሃት ቆፈን ማውጣት፣ እንደልቡ እንዲያስብና ሀሳቦቹን በግልጽና በአደባባይ ለመወያየትና ለመከራከር እንዲችል ለማድረግ፣ በፈለገው መንገድ እየተደራጀ መሪዎቹን የመምረጥ መብት በተግባር መግለጹን ማረጋገጥ ቁልፍ የእድገት ለውጥ ጠቋሚዎች ይሆናሉ፤ በተለይም የኢትዮጵያ ወጣቶች የእነዚህ መብቶች የተረጋገጡ ባለቤቶች እስቲሆኑ ድረስ የመረረ ትግል ማካሄድ የማይቀር ይመስላል፤ አብዛኛው ወጣት ይህንን ዓይነት የመብቶች ትግል የሚደግፍ ሳይሆን አይቀርም፤ ነገር ግን ለወጣቶች በጣም አስቸጋሪ የሚሆነው ከመብቶች ጋር እኩል ሆነው ጎን ለጎን መሄድ የሚገባቸውን ግዴታዎች መቀበል ነው፤ የመብቶችና የግዴታዎች ሚዛን ካልተሰራና ሁለቱንም እኩል የሚያስተናግድ ሥርዓት ሳይኖር የሕግን የበላይነት መትከል አስቸጋሪ ይሆናል፤ የመብቶችና የግዴታዎች መቆራኘት በቅድሚያ ሊታሰብበት ይገባል፡፡
ነገ የወጣቶች ነው፤ ትናንት የሽማግሌዎች ነበር፤ ይባላል፤ በትክክልና በጥሞና ካልታሰበበት ይህ የተለመደ አባባል ስሕተተኛ ብቻ ሳይሆን አደገኛም ነው፤ እኔ አርባ ዓመት አልፎኝ ወጣት በነበርሁበት ጊዜ ኢትዮጵያን የሚያሽከረክሯት ሽማግሌዎች ነበሩ፤ ‹‹ይሄ ልጅ›› ይሉኝ ነበር! አርባ አራት ዓመት ግድም ሲሆነኝ ኢትዮጵያን የሚያሽከረክሯት ወጣቶች ሆኑና ‹‹ይሄ ሽማግሌ›› ይሉኝ ጀመር! ‹‹ይሄ ልጅ›› ሲሉኝ ልሠራ የምችለውን ብዙ ነገር የማልችል አደረጉኝ፤ እንደዚሁም ‹‹ይሄ ሽማግሌ›› ሲሉኝ በጣም ደካማና ኋላ-ቀር አድረጉኝ፤ ራስን ከፍ ለማድረግ ሲባል ሌላውን ዝቅ ማድረግ የሥልጣን ጥመኞቹን የሚረዳ ቢሆንም ማኅበረሰቡን በጣም ይጎዳል፡፡
አሥራ አምስት ዓመት ከሆነኝ በኋላ የሚበልጠውን ዕድሜዬን የተገዛሁት በወጣቶች ነው፤ እናትና አባቴም የተገዙት በወጣቶች ነበር (ዚያሱ፣ ዘውዲቱ፣ ተፈሪ፣ … መንግሥቱ፣ መለስ)፤ ስወለድ የተሰጠኝ ገዢ ኃይለ ሥላሴ ጉዳቸውን በካባቸው ውስጥ ደብቀው ለአርባ ዓመታት ያህል ገዙ፤ እምሩ ኃይለ ሥላሴ፣ ተክለ ሐዋርያት ተክለ ማርያም፣ ገብረ ሕይወት ባይከዳኝ፣ ማርቲን ወርቅነህ፣ መኮንን ደስታ፣ ይልማ ዴሬሳ፣ … በወጣቱ ተፈሪ እየተደቆሱ ፍሬ-አልባ ሆነው የቀሩ ወጣቶች ናቸው፤ በመንግሥቱ ኃይለ ማርያምም የአገዛዝ ዘመን ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ወጣቶች፣ በሆነው ባልሆነው በመንፈስ ብቻ ሳይሆን በአካልም ተደቁሰዋል፤ በወያኔ የአገዛዝ ዘመንም የባሰበት ነበር።
ገነ የወጣቱ ነው ስንል፤ ያለፉትን አርባ ዓመቶች (ከ1966 ዓ.ም ጀምሮ) በጥሞና እንድናስብ እንገደዳለን፤ የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ አገዛዝ ሲወድቅ ሳይረከብ እየዘለለ ወንበሩ ላይ የወጣው ወጣት የሚባለው ነበር፤ ለአለፉት አርባ ሦስት ዓመታት ኢትዮጵያን በቁልቁለት እየነዳ፣ ለሥልጣን መገዳደልን ባህል አድርጎ ወንድምንና ወንድምን እያፋጀ የኢትዮጵያን ሕዝብ ለችግርና ለችጋር፣ ለስቃይና ለመከራ፣ ለሙስና፣ ለስደትና ለአጉል የዕጽ ሱስ የዳረገ የጎረምሶች አገዛዝ ነው፤ የጎረምሶች አገዛዝ ያለፈውን አያውቅም፤ የሚመጣውን መገመት አይችልም፤ በጊዜያዊ ስሜት ብቻ እየተንደባለለ እንደ ቁልቁለት የሚያስደስተው መንገድ የለውም፡፡
(ከፕ/ር መስፍን ወልደ ማሪያም
“እንዘጭ! - እምቦጭ! የኢትዮጵያ ጉዞ” የተቀነጨበ፤ 2010 ዓ.ም)

Monday, 13 November 2017 10:43

ልጅነት

  የንጋት ጮራ
ዓይኔ ላይ አበራ
ጮ¤ ፎከረ አቅራራ
ልቤ እንዳይደነግጥ
እንዳልሸበር እንዳልፈራ፡
የምሽት ዳፍንት
የሽምግልና ጥፊ
ወንድ አንጀት አለስላሽ
ልጅነት ቀጣፊ
እንደቱታ ራስ ሚመታ
ሳይቀጥፈኝ በሽታ
የንጋት ጮራ እንዳይጠፋ
ወኔዬ እንዳታንቀላፋ
ጩህ ሸልል አቅራራ
ልጅነቴ አደራ
እንዳልሸበር እንዳልፈራ
(ልጅነት፣ ሰለሞን ደሬሳ፣ 1963 ዓ.ም)

ጋሽ አስፋው ዳምጤ፣ ስለ ሰሎሞን ደሬሳ…
 “…ሰሎሞን አንባቢ ነበረ፡፡ በጣም በጣም በጣም አንባቢ!... ቮረሺየስ አንባቢ!... ለትምህርቱ ግድ የለውም፡፡ በኋላ ላይ ሳስበው፣ ሰሎሞን ዩኒቨርሲቲ ኮሌጁን ማደሪያውና መኖሪያው እንጂ፣ መማሪያው አላደረገውም ነበር - ቁርስና ምሳ እየበላ ማደር፡፡ ትምህርቱን አይፈልገውም ነበር፡፡ እሱ ራሱን ነው የሚያስተምረው፡፡ ቤተ-መጻህፍት ሄዶ የሚያነብበው ሌላ ነገር ነበር እንጂ፣ ለክፍል ፈተናው አልነበረም…”
(ደራሲና ሃያሲ አስፋው ዳምጤ፣ ከጥቂት ወራት በፊት በአዲስ አድማስ  ጋዜጣ፣ ከጋዜጠኛ ሰሎሞን አበበ ቸኮል ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፣ ስለ ገጣሚ ሰሎሞን ደሬሳ ከተናገሩት የተወሰደ)

  ‹የጥንታዊ ኢትዮጵያን ጥበብ› የሚዳስሱ መረጃዎችን ለመሰብሰብ ስውተረተር፤ ‹Encarta 2009›ን ስለ ኢትዮጵያ ፍልስፍና ምን እንደያዘ ጠየቅኩት:: የአውሮፓ ነው ያለውን ከጥንታዊት ግሪክ ጀምሮ እስከ ዘመናዊ አሜሪካ ድረስ ያሉ የፍልስፍና ዓይነቶችን ዘርዝሮ አቀረበልኝ፤ ወደ ህንድና ቻይናም ሔዶ አማረጠኝ፤ ወደ መካከለኛው የእስልምና ዓለም ፍልስፍናም ወስዶ አስጎበኘኝ። ምንም እንኳን በዚህ መልክ ቢያማርጠኝም፤ እኔ ግን ‹ጥያቄዬ አልተመለሰም› አልኩት፡፡ ሐቀኛው Encarta እንኳን በኢትዮጵያ በአጠቃላይ በአፍሪካ፣ ፍልስፍና መኖሩን እንዳማያውቅ እቅጩን አረዳኝ፡፡ ይህም የቀድሞው የቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዩኒቨርስቲ ፕሬዝዳንት የነበሩት ዶክተር አክሊሉ ሀብቴ የተናገሩትን አስታወሰኝ፡፡
ዶ/ር አክሊሉ፣ ለአሜሪካን ኮንግረስ የአፍሪካ ክፍል በአቀረቡት የመወያያ ሐሣብ፤በእ.ኤ.አ.1958 በካይሮ ላይ ‹Mutual appreciation of western & Eastern cultural values› በሚል ርዕስ በተካሔደ ጉባኤ፤ የአፍሪካ አስተምህሮ አለመነሳቱ አስገርሟቸው ‹አፍሪካ የት ናት?› የሚል ጥያቄ ለመጠየቅ መገደዳቸውን አንስተው፣ የተሰጣቸው መልስም ‹አፍሪካ ያላት ማሐይም ማኅብረሰብ ነው› የሚል ዓይነት እንደነበር አስታውሰዋል፡፡ እኔም Encarta ሐቀኛ መልሱን ከነገረኝ በኋላ ብዙ ጥያቄዎች ተግተለተሉብኝ፡፡
ከጥያቄዎቹ መካከል አንዱ፤ ‹ለምን የእኛ ዕውቀት ሳይመዘገብ ቀረ?› የሚል ነው፡፡ Encyclopedia of Philosophy የሚለውን ባለ አሥር መድበል የዕውቀት መዝገብ አገላበጥኩት፡- ‹ከየት ላምጣልህ?› የሚል መልስ ነበር ያገኘሁት፡፡ ጉድ! ብላችሁ ሃዘን እንዳትቀመጡ፤ ሰጋሁ፡፡ ቢያንስ እነ ዘርዓ ያእቆብን አለማወቁ አይገርማችሁም? እውን ኢትዮጵያ፤ የእኔ የምትለው የራሷ ጥበብ የላትም? ነው እንዳይታወቅ የተፈለገበት ምክንያት አለው? ግን ለምን? ኢትዮጵያ አሁን እንዳለችበት ሳትሆን በፊት በተለይም በጥንት ዘመናት የሥልጣኔዎች ምንጭ የነበረች ሀገር ናት። በቅርብ ጊዜያት የተከሰቱ ጉድፈቶችን ለመዛግብተ ቃሎቻቸው ማብራሪያ እንደ ምሳሌ ለማስቀመጥ የፈጠኑ አውሮፓውያን፤ ለምን በአጠቃላይ የአፍሪካን በተለይም የኢትዮጵያን ፍልስፍና መዝግበው ለማሳወቅ ሳይችሉ ቀሩ? ከእነ ደካርትና ካንት ፍልስፍና ጋር ይመሳሰላል የሚባለውን የዘርዓ ያዕቆብን ፍልስፍና ያላካተቱበት ምሥጢሩ ምንድነው? አለማወቅ? ዘረኝነት? ወይስ ሌላ ጉዳይ?
 የኢትዮጵያ ፍልስፍና ማጠንጠኛ
ከላይ የጠቀስኳቸውን ጥያቄዎች እያብሰለሰልኩም፤ ‹ራሱ ፍልስፍና ምንድን ነው?› የሚል ጥያቄ መጣብኝ፡፡ በጣም የከነከናችሁን ጥያቄ ስትጠይቁ፣ መልሱን ቶሎ ካላገኛችሁ የበለጠ ጥያቄ ይጎለጎልባችሁ የለ? ስለዚህ የፍልስፍና ምንነትን ማብሰልሰል ጀመርኩ፡፡ ፍልስፍና በነጠላ ትርጉሙ፤ ‹ጥበብን ማፍቀር› ማለት እንደኾነ  መጀመሪያ ቃሉን ተናገረው ከተባለው ከፊጣጎረስ (Pythagoras) መረዳት ችያለሁ፡፡ ሶቅራጥስም የፍልስፍና መሠረቱ መደነቅ መቻል መኾኑን ነግሮኛል፡፡ በጥበብ ፍቅር ተነድፎ በመደነቅ ምርምር የሚደረገውም ትክክለኛው እውነት ጋር ለመድረስ መሆኑንም ተረድቻለሁ፡፡ እና ኢትዮጵያውያን በታሪካቸው የዚህ ዓይነት ጥበብ አልነበራቸው? ይህንን ለማረጋገጥም የኢትዮጵያውያንን የጥንታዊ የትምህርት መስኮች (ጉባኤያት) መዳሰስ አስፈላጊ ኾኖ አገኘሁት፡፡ በዚህም ‹የኢትያጵያ ፍልስፍና ምን ዓይነት ነው?› ለሚለው ጥያቄ መልሱን ማፈላለግ ጀመርኩ፡፡ ከዚያም የሚከተሉት ነጥቦች የኢትዮጵያውያን ጥበብ ዋና ዋና ማጠንጠኛዎች መስለው ታዩኝ፡፡
 ሃይማኖት የጥበብ መነሻና ማዕቀፍ
የኢትዮጵያ ጥበብ መሠረቱ ዕውቀት ሳይሆን ሃይማኖት (እምነት) መሆኑን ተረዳሁ፤ ስለሆነም ‹የጥበብ መጀመሪያ እግዚአብሔርን መፍራት ነው።› ይላል፡- በኢትዮጵያ የተመለከትኩት ፍልስፍና። በዚህም የተነሳ፤ ‹በእግዚአብሔር መኖር ላይ ተማምኖ መፈላሰፍ ይቻላል? ወይስ አይቻልም?› የሚለው ጥያቄ መጥቶ ድንቅር አለብኝ፡፡ ለዚህ የሚሆን መልስ ሳፈላልግም፣ አብዛኞቹ የጥንታዊት ግሪክ ፈላስፎች፣ የአንድ አምላክ መኖርን የሚደግፉ ሆነው አገኘኋቸው፡፡ እነ ኤራቅሊጠስ፣ ዜኖፎን፣ ሶቅራጥስ፣ ፕሌቶ፣ አርስጣጣሊስና ሌሎችም አጠራራቸው ቢለያይም፣ በእግዚአብሔር መኖር ግን እንደሚስማሙ ሳያብሉ መሰከሩልኝ። ለማጠናከር ብዬ ወደ ሮማያውያን ተሸጋገርኩ። እነ አውግስቲን ኋላም እነ ቶማስ አኳይነስ “የፍልስፍናችን መሠረትና ጉልላት የእግዚአብሔር መኖር ነው” ብለው መለሱልኝ፡፡ ምስክር በሦስት ይፀናል ብዬ ወደ ዘመናዊያን ፈላስፎች ተጠጋሁ፤ እነ ደካርት፣ በርክሌይ፣ ካንትና መሰሎቻቸው የፍልፍናችን መሠረት እግዚአብሔር ነው አሉኝ። ከዚህ በኋላ እንግዲያውስ፣ የኢትዮጵያውያንም ጥበብ መሠረቱን ‹እግዚአብሔርን መፍራት› ማድረጉ ከፍልስፍና ውጭ አያስወጣውም አልኩኝ። በእምነት ላይ የተመሠረተ ፍልስፍና አይኖርም ያለው ማን ነው?
 እንደውም ፍልስፍና በእምነት ላይ ሲመሰረት አሳማኝነት ይኖረዋል ብዬ ገመትኩ፤ እምነት አልባ ፍልስፍና ግን መሠረቱ አጨቃጫቂ ነውና፤ አጨቃጫቂ ነገርም ተቀባይነት አይኖረውም፡- የሚል እምነት ሰረፀኝ፡፡ ምክንያቱም የፍልስፍና መሠረት እምነት ነው ካልን፤ የእምነት ዋናው መሠረትም፣ የእግዚአብሔር መኖር ነው፤ እግዚአብሔር ደግሞ በባሕርዩ ፍጹም ስለሆነ ሌላ አያስፈልገውም፤ የአስተሳሰብ ሁሉ መደምደሚያ ነው፡፡ ነገር ግን ፍልስፍና የእምነት መሠረት ከሌለው በምን መነሻ መስማማት ይቻላል? ስለዚህ የኢትዮጵያውያንም ፍልስፍና በእምነት ላይ መመሥረቱ አስተውሎታዊ ነው እንጂ አለማወቅ አይደለም፤ ብዬ ወሰድኩት፡፡
 የጥበብ በሥነ ምግባር መቃኘት
ሁሉም ጥበባቸው በሥነ-ምግባር የተቃኘ መሆኑን ዐየሁ፤ ለዚህም የተረጎሟቸው የታዋቂ ፈላስፎች ጽሑፎች ሳይቀሩ በምስክርነት አረጋገጡልኝ፡፡ አንጋረ ፈላስፋን (የፈላስፎች አነጋገር) አገላብጬ ተመለከትኩት፤ የብዙ ፈላስፎች ሥነ ምግባራዊ ንግግር ወይም መልካም ምክር በኢትዮጵያውያን መንፈስ ተቃኝቶ ተሰብስቦበታል፡፡ እንደውም አብዛኞቹ የመጽሐፉ ጥቅሶች፤ ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት የራሳቸውን ፍልስፍና ደብቀው በሌሎች ፈላስፎች ስምና ባልታወቁ ፈላስፎች መልክ የሰገሰጉባቸው መሆናቸውን ጠረጠርኩ፡፡ ጥርጣሬዬ ያለምክንያት አይደለም፤ ኢትዮጵያውያን ሊቃውንት ትህትና ስለሚያጠቃቸው ዐዋቂ ሰው መስለው መታየት እንደማይፈልጉ ከጻፏቸው የሃይማኖት መጻህፍት   ተገንዝቤአለሁ፡፡ ስለዚህ ይህም ጥርጣሬ የኢትዮጵያውያንን የትህትና ልምድ በማየት የመጣ ነው፡፡ በተጨማሪም የዘርአያዕቆብንና የወልደሕይወትን ፍልስፍናዊ መጣፎች ተመለከትኩ፤ በዋናነት በሥነምግባር ዙሪያ የሚያጠነጥኑ ወይም በሥነ ምግባር ፍልስፍና የተቃኙ ናቸው፡፡ ሥነ-ምግባር ደግሞ አንዱና ዋናው የፍልስፍና ትምህርት ክፍል መሆኑን ዐውቃለሁ። እንደውም ሥነ-ምግባር አልባ ፍልስፍና ሰብዕና አልባ ዕውቀት እንደሚሆን አልጠራጠርም፡፡ ስለዚህ የጥንት ኢትዮጵያውያን ፍልስፍና በሥነ ምግባር ገመድ መሸበቡ፣ መልካምና ጥሩ ፍልስፍናዊ ዕይታ መሆኑን አጤንኩኝ፡፡
  የጥበብ ዕምቅነት፣ ኅብራዊነትና አመሥጥሯዊ ትርጓሜ
ፍልስፍናቸው በዋናነት በኅብር ትርጓሜያት የሚፈታ መሆኑንም የተመለከትኩት መለያው ነው፡፡ በመጀመሪያ ቅኔዎቻቸውን ተመለካከትኩ፤ የሚደንቁ ዕይታዎችንና ልዩ አቀራረቦችን ሳገኝ ‹ይህማ የትም የማይገኝ የኢትዮጵያውያን ብቸኛ ፍልስፍና ነው!› እስከማለት ደረስኩ፤ ተደንቄ፡- መፈላሰፍ ልጀምር! ቅኔያቸው ሥጋና ነፍስ የተዋሐዱበት እንጂ በአጥንትና ሥጋ ብቻ የተወሰነ አይደለም፤ ሰው ሕይወት ዘርቶ የሚንቀሳቀሰው ነፍስ ያለው ከሆነ ነውና፡፡ ይህ ደግሞ የሚገለፀው በኅብርነት ነው፡፡ ተፈጥሮ የተሠራችው ታምቃ በኅብርነት ስለሆነ የኢትዮጵያም ጥበብ ኅብርነት ማጠንጠኛው መሆኑን ታዘብኩኝ፡፡ ይህንን በሚመለከት የኔታ ዓለማየሁ ሞገስ፤ “መልክዐ-ኢትዮጵያ” በሚለው መጽሐፋቸው፡-
‹የኅብር አገር ጎጆ መግቢያና መውጫው፣
ሊቃውንት የሠሩት ኹለት በር አለው፤
ምንም ኹለት ቢኾን ሦስት አራትም፣
ጠባብ ስለኾነ ደንቁር አይገባም፡፡› ብለዋል፡፡
የትርጓሜ መጻሕፍታቸውን ቃኘሁ፤ እያጋጩና እያነጻጸሩ ሲያብራሩና ትክክለኛውን አንድምታ አንጥረው ሲያወጡ ዐይቼም፤ ‹እና ከዚህ በላይ ፍልስፍና ምን ዓይነት ነው!?› ብዬ ራሴን ጠየቅሁ፤ ለምንስ ትርጉም አስፈለገ? አልኳቸው በጨዋነቴ፡፡ ‹ፊደል ይገላል፤ ምሥጢር ግን ሕይወትን ይሠጣል› ብለው የተሸፈነውን፣ ነፍስ የሆነውን መልዕክት ለመረዳት፣ መተርጎም እንዳለበት አስረዱኝ፡- “አዬ! የልጅ ነገር፤ አሁን ይኼ ይጠየቃል!” ብለው እኮ ነው፡፡
እንዲሁም አባባሎቻቸውን፣ ምሳሌያዊና ፈሊጣያዊ ንግግሮቻቸውን፤ እለታዊ ጨዋታቸውን በማየት ድንቅ ለዛቸውንና ዐስተውሎታዊ ንግግራቸውን፣ በዐጭሩ እነሱ ‹እንደ ወርቅ አንከብሎ እንደ ሸማ ጠቅልሎ› እንደሚሉት ሆኖ አገኘሁት። በዚህ ላይ ወሬ አምሮኝ፣ በልጅነት ጠጋ ጠጋ ብላቸው እኮ፣ ለልጅ በሚገባ መልኩ ‹ዕንቆቅልህ!› ማለታቸው አይቀርም! እኔማ ምን እመልሳለሁ ‹ምን ዐውቅልዎት!› ከማለት ውጭ፡፡ ጉድ! ምሥጢር እየሣበኝ እኮ ብዙ ወሸከትኩ፡፡ በጥቅል ላውራ፤ አዎ በጥቅሉ በኢትዮጵያውያን ፍልስፍና፤ መንፈሳዊነት የሌለው አስተያየት የለም፤ መንፈሳዊነቱም ያለ ሥጋዊ ግዙፍ ነገር አይገለጽም፡፡ ስለዚህ ኅብረ-ነገር (ኅብረ-ፍልሰፍና) የኢትዮጵያውያን ዕውቀት ድረ-ማግ ነው፡፡
  አስማትም ጥበብ ነው!
ከዚህ ሌላ ስለ ደብተራዎች ድንቅ ግብር (አስማተ-መተት) አንስቼ አላውራ እንጂ እነሱን እኮ ጠላት አይደፍራቸውም! አልተወራላቸውም እንጂ ኢትዮጵያ ከጥንት ጀምሮ ነፃነቷን ጠብቃ የኖረችው በእነሱ የመተት ጥበብ ጭምር ነው! … ካላመናችሁ ባለ ቅኔ ‹ገሞራው›ን ምስክር ልጥራ፡- የደብተራውን ግብር ያውቃልና እንዲህ አለ፡-
‹…በሩቅ አነጣጥሮ- በራዳር አስማቱ፣
ቶርቦዶ የሚያደርግ- ባንደርቢ ድግምቱ፣
ካድማስ የሚያወርድ- ሳተላይት ምትሃቱ፣
ድባቅ የሚመታ- ባዙቃ አንደበቱ፣
ድምጥማጥ አብንኖ- ጠላት አርጊ ከንቱ፣
ታላቅ ግብር(Role) ነበረው- ደብቴ ታጋይ ብርቱ፣…..›
(አቢሲኒያ መጽሔት ቅጽ 1፣ ቁጥር 16 ጥር 1993)
በሞቴ ስለ ደብተሮች አንድ ታሪክ ላውራ! የልጅ ወሬም ቢሆን ያዳምጡኝ፡፡ ወሎ ውስጥ ነው አሉ፡- ላስታ አካባቢ፡፡ አንድ መሪጌታ ናቸው፡- ድብትርናቸው ያልታወቀባቸው ሊቅ፡፡ የመጀመሪያ ልጃቸውን የቀለም ቀንድ ያደርጉታል፤ አጅሬው ከሳቸውም አልፎ ጠቢብነትን ይዞ እቤቱ ‹ከች!›። አንድ ቀን ታዲያ እናቱ ክሽን ያለች ዶሮ ወጥ ለአባወራዋ ትሠራለች፤ አባት ግን ከልጅ ጋር መሻማት አልፈለጉም፡፡ ስለዚህ ልጃቸው ከቤት የሚወጣበትን ዘዴ ቀይሰው ዘመድ ጋር መልዕክት ይልኩታል፤ ይች ዘዴ የገባችው ልጅ ደግሞ በድግምቱ ድስቲቷን ቆልፏት ይሔዳል፤ ማን ወንድ ይክፈታት! አባት ተናደዱ፤ ልጁም መልዕክቱን አድርሶ መጣ፡፡ የተናደዱት አባት ግን ልጃቸው ገና በሩ ላይ ሲገባ ዐሠሩት፡- መውጣት አይችል መግባት አይሆንለት፤ የበር መዝጊያ መስሎ ቆመ፡- እንሞካከር ማለት እኮ ነው - በደብተራኛ፡፡
እሱስ ቢሆን ያስመሰከረ ሊቅ አይደለ? አባቱን ዐያቸው፤ ፊት ለፊቱ በአንድ እግራቸው መሬት እረግጠው በሌላው ደግሞ ካልጋው ጠርዝ ላይ አንፈራጠው ይመለከቱታል፡፡ ሊቁ ልጅም ጦርነቱን ዝም ብሎ አልተሸነፈም፤ አባቱን ከመሬትና ካልጋ ጋር ጠፈራቸው፡- መዘዋወር የለ! መንቀሳቀስ። አሁን ተግባቡ፤ “በል ልጄ ፍታ! ልፍታ!” አሉ አባት፤ ተፈታተው አብረው በሏታ! ክሽንዋን የዶሮ ወጥ። ጎበዝ ለጎበዝ ከተገናኘ ይከባበራል፡፡ አዩልኝ፤ ይህንን ጥበብ! የመስተፋቅር ጥበባቸውንማ ሁሉም የሚያውቀው ነው! ምን አወራዋለሁ!፡- ካስነኩ በቃ! በፍቅር ክንፍ ነው፡- እንቅልፍ የለ! ምግብ አያሰኝ! ዝም ብሎ በፍቅር መንፏቀቅ!
ከፊደል እስከ ሰዋሰው ሥርዓት ያለው ጥበብስ?
በኢትዮጵያ ሊቃውንት ዕውቀት መዋቅራዊ ጥበብ ተገረምኩ፡፡ ከፊደል ገበታ ጀምሮ እስከ ሰዋሰዋዊና አጠቃላይ የቋንቋ መዋቅር ስልታቸውን ሳይ መልሴ ምን ሆነ? ‹ዕፁብ! ዕፁብ! ውእቱ!› የፊደል ገበታ እኮ የኢትዮጵያ ማንነት የተጻፈበት ካርታ ነው፡- የሚያነበው ቢገኝ:: ስለሆነም ነው ሊቁ አስረስ የኔሰው፤ ‹“ፊደል ሐውልት ነው … ፊደል መልክ ነው … ፊደል አባት ነው … ፊደል ልጅ ነው … ፊደል ወሰን ነው … ፊደል ዓላማ ነው … ዓላማም የኩራት ምልክት ነው፡፡ ኩራትም ነፃነት ነው፡፡ … የማንኛው ነገር መጠቅለያ ፊደል ነው፡፡” ብለው የመሰከሩት፡፡ (አስረስ የኔሰው፤ “የካም መታሰቢያ የኢትዮጵያ ፊደል መሠረትነት መታወቂያ” 1951 ዓ.ም)፡፡ አረ ለመሆኑ! የእኛን ፊደል የሚያስንቅና የሚቀድም የዓለም ፊደል (አልፋ ቤት) ይምጣና እስቲ ይወዳደር ብዬ ልፎክር እንዴ? ይኸው ፎከርኩ!
የሰዋሰው መዋቅሩም እኮ የተፈጥሮ ግልባጭ ነው፤ ምን ልበል!:- ሰማይና መሬት በዕውቀት የተገናኙበት መሰላል ማለት እንጂ፡፡ በአዕማዳት ቆሞ፣ በአለቃ ተደራጅቶ፣ በሠራዊት የሚጠበቅ፣ በመራሂያን የሚፍታታ፣ በዓቢይና በንዑስ አግባባት እየተዋሐደና እየተበተነ የሚታሠር አስደናቂ የዕውቀት ድርጅት ነው እኮ ሰዋሰዋችን! ስለዚህ የዕውቀት ድርጅት እኔማ ምን እላለሁ? ሊቃውንቱ ቢያወሩት ይሻላል እንጂ! የእኔ ግብር ‹አባ በሌሉበት…› ዓይነት ነው፡፡
በአጠቃላይ ስለ ባህላችን ልናገር እንዴ? ስለ ትውፊታችን ልመስክር እንዴ? ስለ ገዳ ሥርዓት፣ ስለ ሥነ መንግሥት፣ ስለ ዘመን አቆጣጠራችን፣ … ስለተጠየቅ ልጠየቅ፣ ስለ በልሃ ልበለሃ--- ክርክር ላውራ እንዴ? ጊዜ አይበቃማ! ባላዋቂነት ይበላሻላ! አቅም የለማ!... በዐጭሩ የኢትዮጵያውያንን አስደናቂ ፍልስፍና ተመልክቼ፣ ጥበበኛነታቸውን ማረጋገጥ ቻልኩ፡፡ ከዚያም እንዲህ አልኩ፤ ‹እኔ የዚህን ያህል ዐይቼ፣ ፍልስፍናቸው ከማረከኝ፣ ዐስተዋይ የፍልስፍና ሊቅ ቢፈትሸውማ! ምን ሊል ነው?› ግን እስከዛሬ በአግባቡ ያልተፈተሸው ለምንድን ነው? መልሱን በአግባቡ ማግኘት አልቻልኩም፡፡ በወፍ በረር የሞካከሩት እንዳሉ ግን መመልከቴን አልሸሸግም፡፡
ማሳረጊያ
ሐሣቤን ልቋጭና ልሰናበት፡፡ በእኔ አቅም የኢትዮጵያውያንን አስገራሚ አስተውሎቶች፣ የጥበብ ፍቅር፣ እውነት ለማግኘትና ለማረጋገጥ የሚሔዱበትን እርቀት ዐይቼ ተደንቄያለሁ፡፡ እኔ እንደተረዳሁት ኢትዮጵያውያን የሥልጣኔው ምንጭ ነበሩ፡፡ የሥልጣኔ ምንጭ ለመሆን የቻሉት ደግሞ የራሳቸው ዐተያይ፣ አስተምህሮና የዕውቀት ክምችት ስለነበራቸው ነው፡- ገና ጥንት፡፡ ሊኖራቸው ከሚችለው ዕውቀት ውስጥ ደግሞ ፍልስፍና ቅድሚያውን ይይዛል፡፡ ስለዚህ ‹ኢትዮጵያውያን የራሳቸውን ፍልስፍና ያዳበሩ ሕዝቦች ነበሩ፤ አሁንም ናቸው› ብዬ ደመደምኩ፡፡
 ሆኖም በውስጤ ለተፈጠረብኝ ‹ለምን?› የሚል ጥያቄ፣ መልስ ማግኘት አልቻልኩም፡፡ የእኛን ፍልስፍና፤ ዓለም አቀፍ መዝገበ ቃላትና ዕውቀተ መዝገብ የማያውቁት፣ በእኛ ስንፍና ሳይሆን አይቀርም፡፡ ወይስ የእኛ ፍልስፍና እንዳይታወቅ  ማዕቀብ ተደርጎብናል? ችግሩ ከእኛ ከሆነስ፣ ለምን ፍልስፍናችንን ለቀረው ዓለም ለማሳወቅ ዳተኛ ሆንን? እስቲ መልስ አምጡ!

 የአውቶሞቲቭ ኢንዱስትሪው የደረሰበት እመርታ አንዱ መገለጫ እንደሆነ ሲነገርለት የነበረው አዲሱ ሾፌር አልባ አውቶብስ፤ በአሜሪካ ላስቬጋስ ውስጥ 15 መንገደኞችን አሳፍሮ የመጀመሪያውን የሙከራ ጉዞ በጀመረ በሰዓታት ጊዜ ውስጥ በአቅራቢያው በቀስታ ሲጓዝ ከነበረ የባለሾፌር የጭነት መኪና ጋር መጋጨቱ ተነግሯል፡፡
በአሜሪካ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ መኪኖች በሚንቀሳቀሱበት ጎዳን ላይ የሙከራ ጉዞ በማድረግ የመጀመሪያው ነው የተባለውና ናቪያ የተባለው ታዋቂ የፈረንሳይ የአውቶሞቲቭ ኩባንያ የምርምር ውጤት የሆነው ይህ ሾፌር አልባ አውቶቡስ፤ በድንቅ ፈጠራነቱ በመገናኛ ብዙሃን ተወድሶ ሳያበቃ፣ በሰዓት 25 ኪሎ ሜትር ፍጥነት በመጓዝ ላይ እያለ ግጭቱ እንደደረሰበት ቢቢሲ ዘግቧል፡፡ ምንም እንኳን ክስተቱ የብዙዎችን ትኩረት ቢስብም፣ አደጋው ቀላል ግጭት እንደሆነና በተሳፋሪዎች ላይ ምንም አይነት ጉዳት አለመድረሱን የላስ ቬጋስ ከተማ ቃል አቀባይ መናገራቸውን ዘገባው አመልክቷል፡፡
ትኩረት ያገኘው ሾፌር አልባው አውቶቡስ ቢሆንም፣ በወቅቱ በአካባቢው የነበሩ የትራፊክ ፖሊሶች ግን፣ “ሾፈር አልባው አውቶብስ በአግባቡ እየተጓዘ እያለ አቅጣጫውን ስቶ አደጋውን ያስከተለው ባለሾፌሩ የጭነት መኪና ነው” ሲሉ ለሾፌሩ የቅጣት ወረቀት መቁረጣቸውንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡

 የኮሎምቢያ ፖሊስ በህገወጥ መንገድ ወደ አሜሪካ ሊላክ ተዘጋጅቶ የነበረ 12 ሺህ ኪሎ ግራም ኮኬይን የተባለ አደንዛዥ ዕጽ በቁጥጥር ስር ማዋሉን ያስታወቀ ሲሆን ግምቱ 360 ሚሊዮን ዶላር ያህል እንደሆነም ተነግሯል፡፡
ይህን ያህል ክብደት ያለው አደንዛዥ ዕጽ በአንድ ጊዜ በፖሊስ ቁጥጥር ስር ሲውል ይህ በአገሪቱ ታሪክ የመጀመሪያው ነው ያለው ቢቢሲ፤ የአደንዛዥ ዕጹ ባለቤትም ገልፍ ክላን የተባለው እጅግ አደገኛ የወንጀለኞች ቡድን ፊታውራሪ ዳሪዮ ኡሳጋ የተባለ ግለሰብ መሆኑን  ጠቁሟል፡፡
የአገሪቱ ፖሊስ ቀንደኛውን ወንጀለኛ ዳሪዮ ኡሳግን ለመያዝ ለአመታት ደፋ ቀና ቢልም አሁንም ድረስ እንዳልተሳካለት የጠቆመው ዘገባው፤ ፖሊስ ይህንኑ ቡድን ለመቆጣጠር በጀመረው ዘመቻ፣ ዕጹ በአገሪቱ ሰሜናዊ ግዛት በአንድ የሙዝ እርሻ ውስጥ ተደብቆ ማግኘቱን አመልክቷል፡፡
የሽብር ቡድኑ አባላት የሆኑ ከ1 ሺህ 500 በላይ ግለሰቦችን በቁጥጥር ስር ያዋለው የአገሪቱ ፖሊስ፤ ከአደንዛዥ ዕጹ ጋር ንክኪ አላቸው ያላቸውን የቡድኑ ግብረአበሮች የሆኑ አራት ግለሰቦችን መያዙን የጠቆመው ዘገባው፤ ባለፉት ሁለት ወራት ብቻ በአገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች 20 ቶን ያህል አደንዛዥ ዕጽ መያዙንም አስታውሷል፡፡

  የዚምባቡዌን መሪ የጤና አምባሳደር አድርጎ በመምረጡ ዓለማቀፍ ውግዘት የገጠመውና የሾማቸውን ሙጋቤን ባፋጣኝ ከሻረ አንድ ወር ያልሞላው የዓለም የጤና ድርጅት፤ ቡና፣ ሞባይልና የታሸጉ የስጋ ምርቶች ለካንሰር በሽታ ያገልጣሉ የሚል ሃሰተኛ የጥናት ውጤት ይፋ አድርጓል በሚል አዲስ ውንጀላ ቀርቦበታል፡፡
ሮይተርስ የዜና ወኪል የዓለም የጤና ድርጅት በቅርቡ ይፋ ባደረገው ካንሰርን የተመለከተ የጥናት ውጤት ላይ ባደረገው ጥልቅ ምርመራ፣ ጥናቱ ከመውጣቱ በፊት በነበረው ሰነድ ላይ ቡና፣ ሞባይልና የታሸጉ የስጋ ምርቶች ለካንሰር በሽታ ስለማጋለጣቸው ምንም አይነት ነገር አለመጠቀሱን ጠቁሞ፣ ድርጅቱ ባወጣው የመጨረሻ ይፋዊ ሰነድ ላይ ግን ለካንሰር ያጋልጣሉ ብሎ  አዛብቶ ማውጣቱን  ማረጋገጡን አስታውቋል፡፡
ይህን ተከትሎም ሁለት የአሜሪካ የኮንግረስ አባላት የአለም የጤና ድርጅት ቡና መጠጣት፣ ሞባይል መጠቀምና የታሸጉ የስጋ ምግቦችን መጠቀም ለካንሰር ስለማጋለጣቸው ተጨባጭ ማስረጃውን ይስጠን ሲሉ መጠየቃቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ ጉዳዩ በተቋሙ ተሰሚነት ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ ሊፈጥር ይችላል መባሉን አክሎ ገልጧል፡፡

 በአሜሪካ መንግስት አደንና ክትትል ከ6 አመታት በፊት በፓኪስታኑ አቡታባድ የተገደለው የአልቃይዳው መሪ የኦሳማ ቢንላደን ልጅ ሃማዝ፤ ጂሃዲስቶች በአሜሪካ ላይ ከፍተኛ የሽብር ጥቃት በመፈጸም የአባቱን ግድያ እንዲበቀሉለት ሰሞኑን ባወጣው የድምጽ መልዕክት ጠይቋል፡፡
ሃማዝ ቢን ላደን፤ “ጂሃዲስቶች በአሜሪካውያን በተለይ ደግሞ አባቴን ለመግደል በተደረገው የግፍ ዘመቻ ተሳታፊ በሆኑት ላይ ሁሉ በቻሉት መንገድ የሽብር ጥቃት በመፈጸም እንዲበቀሉልኝ እጠይቃለሁ” ሲል በአልቃይዳ የፕሮፓጋንዳ ማሰራጫዎች በኩል ባስተላለፈው መልዕክት መናገሩን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡
“አባቴ የጂሃድን መንፈስ የቀየረ ጀግና ሰማዕት ነው” በማለት ቢን ላደንን ያወደሰው የ28 ዓመቱ ሃማዝ፤ 25 ደቂቃ ያህል እርዝመት ባለው የድምጽ መልዕክቱ፣ የአፍጋኒስታኑን ታሊባን ቢያደንቅም አይሲስን በተመለከተ ግን ምንም ነገር አለማለቱን ዘገባው አመልክቷል፡፡
አሜሪካ በ2011 ቢን ላደንን በገደለችበት ወቅት የሃማዝ ወንድም ካሊድ መገደሉን ያስታወሰው ዘገባው፤ የአሜሪካው የስለላ ተቋም ሲአይኤ ባለፈው ሳምንት ከዚህ በፊት ታይተው የማይታወቁ ከቢን ላደን ጋር ተያያዥነት ያላቸውን በርካታ መረጃዎች ይፋ ማድረጉንም አስታውሷል፡፡

 ከዕለታት አንድ ቀን አንድ እጅግ የሚያምር ልጅ፤ ከአሸዋ ላይ አንዲት ትንሽ ጉድጓድ ቆፍሮ፣ እዚያች ውስጥ ከባሕሩ ውሃ በትንሽ ዛጎል ሳያቋርጥ ቶሎ ቶሎ እያመላለሰ ይጨምር ነበር፡፡ ውሃውን ለማቆር እየሞከረ ነው ማለት ነው፡፡
አንድ የተማረና የተመራመረ በጣም የረቀቀ ቅዱስ፤ ያንን ልጅ ባየ ጊዜ ሀሳቡ ተሳበ። ወደ ልጁ ቀረበና፤
“አንተ ልጅ ምን እያደረግህ ነው? እዚች ትንሽዬ ጉድጓድ ውስጥ ውሃ ለመጨመር ይህን ያህል አዕምሮህ እስቲጠፋ ድረስ የምትደክመው ለምንድን ነው?” ሲል ጠየቀው።
ልጁም፤
“ባህሩን አጠንፍፌ ውሃውን ሁሉ እዚህ ጉድጓድ ውስጥ ለመጨመር እፈልጋለሁ” ሲል መለሰለት፡፡
ቅዱሱም፤
“ያንን ለማድረግ ፈፅሞ አይቻልም፡፡ ባሕሩ ምን ያህል ትልቅና ሰፊ መሆኑንና እንደዚች ባለች ትንሽ ቀዳዳ ውስጥ ይህንን ስፍርና ልክ የሌለውን ውሃ ለማግባት እንደምን እችላለሁ ብለህ ታስባለህ? የማይቻልን ነገር ለማድረግ መሞከርስ ትርፉ ድካም መሆኑን መገንዘብ እንዴት ያቅትሃል?” አለው ቅዱሱ ሰው፡፡
ልጁም፤ እጅግ የረቀቀ ትርጉም ባለው አስተያየት ትኩር ብሎ ተመለከተውና ወዲያው፤
“እኔ ባሕሩን ለማጠንፈፍና ከዚች ጉድጓድ ውስጥ መክተት ዕውን አልችልምን? ለምን ሙከራዬን ታናንቅብኛለህ? አንተ ከባሕሩ ሚሊዮን ጊዜ የሚበልጠውን የሥላሴዎችን ምስጢርና ባሕሪያቸውን ለማወቅ ትፈልግ የለምን? እዚህ አሸዋ ላይ ካደረግኋት ከትንሿ ጉድጓድ ይልቅ ወሰን ከሌለውና ይህ ይቀረዋል ከማይባለው የአምላክ ዕውቀት፤ በጣም ያነሰውን ናላህ ውስጥ አኑረህ ለመሸከም ጥረት ታደርግ የለምን?” ሲል ጥያቄያዊ ምላሽ አቀረበለት፡፡ ከዚያም ልጁ የሰማይ ብርሃን ተጎናፅፎ ወዲያው ተሰወረ፡፡ ይህ ህፃን የአምላክን ትልቅ መልዕክት ለቅዱሱ ሊናገር የተላከ ነበር ይባላል!
*       *      *
ትልቁ ነገር የሀገርን ትልቅ ስዕል ማየት ነው! ምንጊዜም ትናንሽ ችግሮች ይኖሩብናል። ልንፈታቸው የሚገባን ግን ትልቁን የሀገር ስዕል ካስተዋልን ነው! አያሌ መንገዶች ወደ መፍትሔ ሊመሩን ይችላሉ፡፡ ከመንገዶች ሁሉ የተሻለውን ለመምረጥ ግን ልዩ ዕይታን ይጠይቃል፡፡ ትልቁ ቁምነገር ጥመትን አስቀድሞ ከላይ ማስወገድ ነው፡፡ ብላቴን ጌታ ማህተመ ሥላሴ ወ/መስቀል እንዲህ ይሉናል፡-
“ምንም ወፍጮ መፍጨት፣ ውሃ መቅዳት፣ እንጀራና ዳቦ መጋገር፣ ወጥ መስራት፣ ለሴት የተለመደ የዘወትር ተግባሯ ቢሆንም፤ ማታ ማታ ባሏን እራት ካበላች በኋላ ጥጧን አቅርባ በእሳት ዳር ሆና ትፈትላለች፤ በቡልጋ ድርና ማጉን ፈትሎ እዚያው በሚገኘው ሸማኔ አሰርቶ ለቤተሰብ አስፈላጊ የሆነውን ልብስ ማዘጋጀት የተለየ የሴቶች ባልትና ነው፡፡ በዚህም ጊዜ እንዲህ ስትል ታንጎራጉራለች፡-
“ባሰላው ባሰላው እንቢ አለኝ እንዝርቱ
 ከታችም አይደለ ከላይ ነው ጥመቱ”
ጥመቱ ከላይ ሲሆን፣ ብልሽቱ ከላይ ሲመጣ፣ አደጋው የትየለሌ ነው፡፡ ታች ድረስ ይሰማል፡፡ ይናጋል፡፡ የሥርዓት መናድ ያስከትላል፡፡ ይህን ሁኔታ ለማስተካከል ጊዜ፣ የሰው ኃይልና አንጡራ - ሀብት መውጣት ይኖርበታልና የሚያስከፍለው ዋጋ ከባድ ነው! አያሌ ችግሮች አሉብን- የላይኛው መዋቅር መዛባት፣ የፍትሕ መዛባት፣ የዲሞክራሲ መቃወስ፣ የሀብት ክፍፍል መላ - ቅጥ መጥፋት፣ የገዢና ተገዢነን አግባብ ማጣት፣ የነባራዊ ሁኔታና የህሊናዊ ሁኔታ አለመጣጣም- ወዘተ… የሥርዓት መናጋት ሥራዬ ብሎ አለማጤን፤ ለሁሉም ወገን አለመረጋጋት ይዳርጋል፡፡ ከሁሉ በላይ የሥልጣን ገዋ (Power vacuum) ቢፈጠርስ ማለትም ደግ ነው! ጉዳዮችን በመልክ በመልካቸው ሰድሮ ለማየት ቅንነትና ከተንኮል - የፀዱ መሆንን ይጠይቃል፡፡ ሆኖም ቀናት ብቻውን፣ ያለ ፖለቲካ ብስለት የትም አያደርስም፡፡ ምክንያቱም ቀናነት ወደፈለጉት አቅጣጫ አጣመው ለራሳቸው ጥቅም የሚያውሉ እኩያን ሊኖሩ ይችላሉ!
የይስሙላ ፍቅር፣ የይስሙላ አጋርነት፣ የይስሙላ ጓድነት እጅግ ጊዜያዊ ዕድሜ ያለው፤ “ላያዘልቅ ፀሎት ለቅስፈት” የሚባለውን አይነት ነው፡፡ ለወጉ “ዘላቂነት ዘላቂነት” ብንል …መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች መፈክር ከመሆን አያልፍም፡፡ ያለንበት የሚመስለን ኳስ ጨዋታ ለተለዋጭነት (ለቤንችነትም) የማያበቃን ሆኖ ሊገኝ ይችላል፡፡ “የት ይደርሳል የተባለው ባህር ዛፍ ቀበሌ ቆረጠው፡፡” ከመባል አያልፍም። ነኝ የምንለውን ነገር፣ በእርግጥ ነን ወይ? ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ በፖለቲካ ትግል ውስጥ ፈጣን ተለዋዋጭ ሁኔታ (Volatility) ያለ ነገር ነውና እርግጠኝነት ወደ ፍፁምነት አድጓል ብሎ መፈጠም የዋህነትም፣ አዳጋችም ነው፡፡ “ገንፎ እፍ እፍ ቢሉሽ ሊውጡሽ” ነው፤ ዕውነት አይምሰልሽ!” የተባለው ተረት ቁም ነገሩ ይኸው ነው!