Administrator

Administrator

 · “በመናገር ነፃነት ላይ የተወሰደ እርምጃ ነው” አምነስቲ
        · “የታሰሩት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን በመጣሳቸው ነው” መንግስት
               
     የአንጋፋው ፖለቲከኛ ዶ/ር መረራ ጉዲና መታሰር የዓለም አቀፍ ሚዲያዎችንና የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችን ትኩረት የሳበ ሲሆን አምነስቲ ኢንተርናሽናል፣ የታዋቂው ፖለቲከኛ እስር  በእጅጉ ያሳስበኛል ብሏል፡፡ ዶ/ር መረራ አመራር አባል የሆኑበት መድረክ በበኩሉ፤ ጠንካራ መሪውን በእስር ማጣቱ የአመራር ክፍተት እንደሚፈጥርበት ጠቁሟል። ከ20 ዓመታት በላይ በተቃዋሚ ፓርቲ አመራርነት የዘለቁት የፖለቲካ ሳይንስ ምሁሩ ዶ/ር መረራ፤ የታሰሩት “ከሽብርተኛ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት መፍጠር ክልክል ነው” የሚለውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን አንቀፅ በመተላለፋቸው ነው ብሏል - መንግስት፡፡ የመድረክ ሊቀመንበር ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ በሰጡት አስተያየት፤ ዶ/ር መረራ በመድረክ ውስጥ የድርጅት ጉዳይን በኃላፊነት ይከታተሉ እንደነበር ጠቅሰው፤ መታሰራቸው በድርጅቱ ስራ ላይ ከፍተኛ ተፅዕኖና የአመራር ክፍተት እንደሚፈጥር ተናግረዋል፡፡
“ዶ/ር መረራ በሌለበት የተሟላ ድርጅታዊ ስራ ልንሰራ አንችልም” ያሉት ፕ/ር በየነ መድረክ በጉዳዩ ላይ ውይይት አድርጎ በቅርቡ የአቋም መግለጫ እንደሚያወጣ ጠቁመዋል፡፡ ‹‹እስካሁን ድረስ ወጥ አቋም ያለው ፖለቲከኛ አልገጠመኝም፤ ብዙዎቹ ተለዋዋጭ አቋም ነው ያላቸው›› ያሉት ፕ/ር፤ “መረራ ግን ወጥ አቋም በመያዝ ጠንካራ የፖለቲካ ፅናት ያለው መሪ ነው” ሲሉ አድናቆታቸውን ገልፀዋል፡፡
የኦሮሞ ፌደራሊስት ኮንግረስ (ኤፌኮ) ሊቀመንበር፤ እንዲሁም የመድረክ ምክትል ሊቀመንበርና የድርጅት ጉዳይ ኃላፊው ዶ/ር መረራ፤ መታሰራቸው በእጅጉ ያሳስበኛል ያለው አምነስቲ ኢንተርናሽናል፤ ‹‹እስሩ ሀሳብን በነፃነት የመግለፅና የመናገር መብት ላይ የተቃጣ እርምጃ ነው” ሲል ኮንኗል፡፡
በኢትዮጵያ ይፈፀማል ስለሚባለው የሰብአዊ መብት በቤልጂየም ብራሰልስ ተገኝተው ለአውሮፓ ህብረት ፓርላማ እማኝነታቸውን እንዲሰጡ የፓርላማው አባል በሆኑት እና ጎሜዝ እንደተጋበዙ የተነገረላቸው ዶ/ር መረራ፤ ከጥቂት ሳምንታት በፊት ወደ አውሮፓ አምርተው በኢትዮጵያ ስላለው ወቅታዊ የፖለቲካ ቀውስ ማብራሪያ መስጠታቸው ተዘግቧል፡፡
ባለፈው ረቡዕ ከብራሰልስ ወደ አገራቸው የተመለሱ መረራ፤ የዚያኑ ዕለት ምሽት 2 ሰዓት ገደማ አሸዋ ሜዳ በሚባለው አካባቢ ከሚገኘው መኖሪያ ቤታቸው እንዳሉ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የኦፌኮ አመራሮች ተናግረዋል፡፡ ከእሳቸው ጋር ይኖሩ የነበሩ ሁለት ወጣቶችም መታሰራቸውን ለማወቅ ተችሏል።
ዶ/ር መረራ በተጋበዙበት በአውሮፓ ህብረት ፓርላማ  በ“አሸባሪነት” የተፈረጀው የ“ግንቦት 7” መሪ ዶ/ር ብርሃኑ ነጋና  በየሪዮ ኦሎምፒክ የማራቶን ውድድር አትሌት ፈይሳ ሌሊሳም ተጋብዘው ነበር ተብሏል፡፡ ዶ/ር መረራ ጉዲና በፖሊስ ቁጥጥር ስር የዋሉት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ አንቀፅ 1 ቁጥር 2 ስር የተመለከተውን ክልከላ ጥሰው ከሽብርተኛ ድርጅቶች ጋር ግንኙነት በማድረጋቸው መሆኑን የኮማንድ ፖስቱ ሴክሬተሪያትን ጠቅሶ ኢቢሲ ከትላንት በስቲያ መዘገቡ ይታወሳል፡፡
ዶ/ር መረራ፤ በአውሮፓ ህብረት ፓርላማ ስለኢትዮጵያ ወቅታዊ ሁኔታ ምስክርነታቸው እንደሰጡ ጋብዘዋቸዋል የተባሉት አና ጎሜዝ በበኩላቸው፤ የፖለቲከኛው መታሰር ቢያስደነግጠኝም አላስገረመኝም ብለዋል፡፡ መረራ መታሰራቸው ተገቢ አለመሆኑን ከትላንት በስቲያ ለቪኦኤ የተናገሩት ጎሜዝ፤ እስካሁን ህብረቱ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ የመለሳለስ አካሄድ ሲከተል መቆየቱን ጠቅሰው ጠንካራ እርምጃ እንዲወስድ የሚያሳስብ ደብዳቤ ለህብረቱ ኮሚሽን መፃፋቸውን አስታውቀዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት በበኩሉ፤ የህብረቱና የኢትዮጵያ ግንኙነት ጠንካራ መሰረት ያለው መሆኑን ገልፆ ግንኙነቱ ይሻክራል የሚል ስጋት እንደሌለው ጠቁሟል፡፡ የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትር ዶ/ር ነገሪ ሌንጮ ትላንት ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤
‹‹ዶ/ር መረራ ጉዲና ለእስር የተዳረጉት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ጥሰው በመገኘታቸው ህግ ለማስከበር ሲባል ነው›› ብለዋል፡፡
በደርግ አገዛዝ ሥርዓቱን በመቃወማቸው መንግስት 8 ዓመታት ያሰራቸው ዶ/ር መረራ፤ በኢህአዴግ የስልጣን ዘመን ሲታሰሩ የአሁኑ የመጀመሪያቸው ነው ተብሏል፡፡  

የሶማሌ ክልል ጉዞ - ከጉማራ ዙምራ

   ”እንዴት ነው ሶማሌ ክልል? አሁን ሰላም ነው አይደል?” ሁሌም ስጋት የማይለየው ሾፌር ጠየቀ፡፡
”አሁንማ ምን አለ? አገር ተረጋግቷል፡፡ ከአምስት ዓመት በፊት ምእራብ ጎዴ ስሰራ፣ በቀኝ በኩል ወታደር፣ በግራ በኩል ሽፍታ እያጀበኝ ነበር የሰራሁት፡፡”
“አሁንም ሽፍታ አለ እንዴ?”
”የለም አቦ፡፡ አቲፍራ፡፡ ወንድ ልጅ አይፈራም!!”
“እንደው ቤተሰብ ያለው ሰው ይጨነቃል ብዬ ነው” ሹፌሩ መለሰ፡፡
”ቆይ አንተ ስንት ልጆች አሉህ?”
“አንድ ልጅ ነው ያለኝ፡፡”
”ሀይ!! አንድ ልጅ ወልደህ ነው፣ ሃረካት የምታበዛው፡፡ አንድ ልጅ ብቻ ምን ያደርጋል! ጨምረህ ውለድ፡፡ ሚስትህን ውለጂ በላት፡፡ እምቢ ካለች ሌላ ሚስት አግባና ውለድ፡፡ ልጅ ኽይር ነው።”
ከአስራ ሁለቱ ወራት፣ እንደ መስከረም የሚሆንልኝ ተናፋቂ ወር የለም፡፡ ምን ያደርጋል? የዘንድሮውን የመስከረም ፀጋ፣ በቅጡ ሳላጣጥመው ነው፣ ወደ ሶማሌ ክልል ለመሄድ እንድዘጋጅ፣ ከመስሪያ ቤት ማሳሰቢያ የደረሰኝ፡፡ መስከረም 10 ቀን 2009 ዓ.ም፣ ጓዜን ሸክፌ ጉዞ ጀመርኩ፡፡ ምስጋና ለፈጣኑ የክፍያ መንገድ ይሁንና፣ አዳማ ላይ ቁርስ አድርሰን፣ ቡናም ጠጥተን፣ የማይቀሬውን ረጅሙን ጉዞ ተያያዝነው፡፡ እኔም መቋጫ የሌለው የጭንቀት ድር ውስጥ መብሰልሰል ተያያዝኩት፡፡
የሶማሌ ክልል ለረጅም ጊዜ ሰላም ርቆት የቆየ መሆኑ ብቻ አይደለም ያስጨነቀኝ፡፡ ጊዜው ጥሩ አልነበረም፡፡ አገሬው ሁሉ በግጭትና በረብሻ ወሬ ውጥረት ውስጥ የገባበት ጊዜ ነው፡፡ ሁከት እና ብጥብጥን እያሰላሰሉ መጓዝ አስቸጋሪ ነው፡፡
‹‹አሁን በዚህ ሰዓት፣ ሰው ቤቱ አርፎ ቁጭ ይላል እንጂ መንገድ ይወጣል? ‹ይሄኛው መንገድ ተዘጋ፤ እዚህ ከተማ መኪና ተቃጠለ› እየተባለ፣ ሰው ገንዘብ አገኛለሁ ብሎ ከከተማ ሊወጣ ይገባል? ኧረዲያ! ክልፍልፍ ሁኜ ነው እንጂ! … ለዚያውም የቤተሰብ ሃላፊ! …›› በጭንቀት መብሰልሰል፣ ጠብ የሚል ጥቅም እንደሌለው አውቃለሁ፡፡ ነገር ግን ጭንቀትን አውልቆ መጣል አይቻልም፡፡ ለካ በክፉ ቀን ውስጥ ያላለፈ ሰው፣ ድንገት አስቸጋሪ ጊዜ በመጣ ወቅት፣ የሚይዘው የሚጨብጠውን አያውቅም፡፡ እኔም የክፉ ቀን ልምድ የለኝም፡፡ በዚህ የሀሳብ ወንዝ መቀጠል አልችልም፡፡ ልምድ ለማግኘት፣ “ ምነው ክፉ ቀን በሰጠኝ” ብዬ እንደመሳለቅ ይሆንባችኋል፡፡
የሶማሌ ክልል ደግሞ ጭንቀትን የሚያረጋጋ አልሆነልኝም፡፡ ለሩብ ምዕተ ዓመት መንግስት አልባ ሆና ከምትተራመሰው አገር ከሶማሊያ ጋር የተጎራበተ ክልል ነው፡፡ ከድንበር ባሻገር፣ በሞቃዲሾ፣ በባይዶዋና በመሳሰሉ የሶማሊያ ከተሞች፣ በአሸባሪዎች ጥቃት  ሰላማዊ ሰዎችና ወታደሮች መገደላቸው፣ … እንደ ዜና አይቆጠርም። የዘወትር ወሬ ነው፡፡ ግን ወሬው ብቻ አይደለም ድንበር ተሻግሮ ወደ ሶማሌ ክልል የሚዘልቀው፡፡ የሽብር ጥቃትና ግድያም፣ አልፎ አልፎ ወደ ሶማሌ ክልል ይሻገራል፡፡ እና አንዳንዶቹ ወረዳዎች ደግሞ የባሰባቸው ናቸው፡፡ “ክልሉ ውስጥ በሚገኙ አንዳንድ ወረዳዎች ውስጥ በእጀባ ልትገቡ ትችላላችሁ፡፡ እጀባ የማታገኙ ከሆነ ግን፣ አሳውቁንና እንዲቀየርላችሁ ይደረጋል” ተብሎ ተነግሮናል፡፡ … እጀባ፣ ወታደር፣ ክላሽ ፣ አስቸጋሪ አቧራማ ጉዞ … እንዲህ የሚረብሹ ሃሳቦች እየተመላለሱብኝ በጭንቀት መናወዜ አልቀረም፡፡ አጥፍቶ ጠፊ በቀበረው ፈንጂ መኪናችን ወደ ሰማይ ተተኩሳ ስትቃጠል .... ወይም አንዱ ሽፍታ በሞርታር ከርቀት ሲያጋየን …  በእዝነ ህሊና ማሰብ ይሰቀጥጣል፡፡  
ታዲያ ስሜቴ አንዱን ሀሳብ ሳይቋጭ፣ ወደ ሌላው ፈተና እየከተተኝ እንደ ፔንዱለም በሃሳብ ስወዛወዝ፣ “አለቃ ምነው ትካዜ አበዛህ”? የሚል ድምፅ አባነነኝ፡፡ አንዱ ባልደረባችን ነው፡፡ “አይ … መቼም የሚታሰብ አይጠፋ” ብዬ መለስኩ፡፡ ረጅም መንገድ፣ ያለጨዋታ አይገፋምና፣ አንዴ ሞቅ አንዴ ቀዝቀዝ እያልን ወደጨዋታ መግባታችን አልቀረም። ፖለቲካ፣ ኢኮኖሚ፣ ማህበራዊ፣ ስፖርት፣ ፊልም፣ የቲቪ ወይም የሬድዮ ቻናል እያነሳን እናወራለን። ጭውውታችን ታዲያ፣ ስለእያንዳንዳችን ተፈጥሮአዊ ዝንባሌ፣ ፍላጎት፣ የፖለቲካ አቋም አንዳንዴም የእውቀት መጠን ለማወቅ የሚያስችል ሁናቴ መፈጠር ጀምሯል፡፡
የስምጥ ሸለቆ ሙቀት እና ወበቁ እየበረታ ሲመጣ፣ ሸሚዝ መክፈት፣ ቀበቶ መፍታት መቁነጥነጥ አብዝተናል፡፡ መተሃራ ከተማ ላይ፣ ቡና ጠጣንና አንዳንዶቹም በርጫቸውን ይዘው፣ በዱአ እና በዝየራ ጉዞአችንን ገፋነው፡፡ ወለንጪቲ፣ አዋሽ 7፣ ሜኤሶ፣ እና ሌሎች  ሞቅ ደብዘዝ የሚሉ ከተሞችን ተሻግረን፣ ጭሮ (በጥንት መጠሪያዋ አሰበ ተፈሪ) ደረስን፡፡ የምሳ እረፍት አድርገን እንደገና “በጠመዝማዛው …  ሽቅብ ቁልቁለት”... በምእራብ ሃረርጌ ዘወርዋራ መንገድ መጋለብ ጀመርን - ትናንሽ የሃረርጌ ከተሞችን እየገመስን፡፡
ከዚያ ሁሉ የተራራ ሰንሰለት በኋላ፣ ሜዳማ የሶማሌ በረሃዎች ይከሰታሉ ብሎ ማሰብ መቼም አስቸጋሪ ነው፡፡ አየሩና ምድሩ፣ ከቅዝቃዜ ወደ ግለት፣ ከአረንጓዴ ወደ አፈርማ ይቀየራል፡፡
ጅግጅጋ ከተማ የደረስነው በማግስቱ ረፋድ ላይ ነው፡፡ ከሶስት ዓመት በፊት የማውቃት ጅግጅጋ፣ እጅጉን ተቀይራለች፡፡ የከተማዋ እድገት ተፋጥኗል። መንገዶች እየተስፋፉ፣ ህንጻዎች እየተገነቡ ነው፡፡ የንግድ እንቅስቃሴው አጃኢብ ያስብላል፡፡ ስራችንን ለመጀመር ወደ ዞን እና ወረዳዎች ከመግባታችን በፊት ታዲያ፣ ከክልሉ መንግስት የትብብር ደብዳቤ መውሰድ ግዴታችን ስለሆነ ወደ ክልሉ ቢሮ ጎራ አልን፡፡ እንደተመኘነው አልቀናንም፡፡
“የቢሮ ሃላፊዋ አስቸኳይ ስብሰባ ላይ ናት” አለችን ጸሃፊዋ፡፡
“ምክትሏስ?” ብለን ስንጠይቅ
“እሱማ፣ አባቱ ሞተው ሃዘን ላይ ነው” ተባልን፡፡
ፍርሃትም ተስፋም ሰንቀን አዳራችንን፣ ወደ አንዱ ባልደረባችን ወዳጅ ደውለን፣ ወደ ቤት ጎራ ብንልስ ብለን ጠየቅነው፡፡ አብዱልአዚዝ ይባላል፡፡ ፈታ የማለት ባህሪ ይታይበታል፡፡
ያለንበት ድረስ መጣ፡፡ “እንዴት ናችሁ አቦ? አማን ናችሁ? … ያ የተኮራረፈ የሚመስለው የአዲስ አበባ ሰው እንዴት ነው አቦ? … ሰው በታክሲ እየሄደ አያወራ፣ አይናገር፣ የሆነ ዝጋታም እኮ ነው። እኔ ይጨንቀኛል፡፡ ሰው ሰው ሆኖ ተፍጥሮ እንዴት አያወራም? ከብት እንኳን በሽታ ሰላም ይባባላል እኮ።”
“እኔ የምልህ አብዱልአዚዝ ሚስት አገባህ አይደል?” ጠየቀ አብሮ አደጉ፡፡
“አዎ! አይሻ ነው ስሟ፡፡ ስታትስቲክስ ነው የጨረሰችው፡፡ ማስተርሷን ደግሞ በዴቨሎፕመንት ኢኮኖሚክስ ከጅግጅጋ ዩንቨርሲቲ አግኝታለች፡፡”
”አሃ ያቺ ባለፈው ስመጣ አብራህ የነበረችው ነች እንዴ?”
”አዎ...አዎ የዛን ቀን እኮ ነው ፍቅር የጀመርነው። ለካ ነበርክ? ወላሂ ጥሩ ሚስት አገኘሁ፡፡ አንተም ገደኛ ነህ አቦ!”
”ስንት ልጆች ወለድክ?”
”ሶስት ወልጃለሁ፡፡ ኢንሻላህ! አሁን ሶስተኛውን ልጃችንን በኦብራሲዮን ወልዳ ቆይ ላገግም አለቺኝ፡፡ ልጅ ኸይር ነው፡፡”(ሶማልኛ ቋንቋ ውስጥ “ፐ” ፊደል ያለ አይመስለኝም)
መኖሪያ ቤቱ፤ ጭናቅሰን መውጫ የሚባል አዲስ ሰፈር ላይ ነው፡፡ መኪና ውስጥ ገባንና ጉዞ ወደ ቤቱ ጀመርን፡፡ አልፎ አልፎ ሰፋፊ ቪላዎች ይታያሉ፡፡
”አየኸው ያን ነጭ ቪላ? የክልሉ ጸጥታ ሃላፊ የነበረ ያሰራው ቤት ነው፡፡”
”እውነትክን ነው?”
”አዎ!! ሞኝ ነው እንጂ፣ ሰው ከመንግስት ብር ሰርቆ፣ ጅግጅጋ ከተማ ላይ ቪላ ይሰራል? ወላሂ ይሄ ሰው አይደለም፡፡”
”ምን ሆነ አሁን?”
”አሁንማ አወረዱት እና አሰሩታ፡፡ ሱማሌ ሲፎግር ቤቱን “የህዝብ ክሊኒክ” ብሎታል፡፡ አታየውም? ክሊኒክ እኮ ነው የሚመስለው ”...ሳቅ
መኖሪያ ቤት ገባን፡፡ ቤት ውስጥ … ሶፋ፣ የሳሎን እቃ ጅኒ ቁልቋል ይኖራል ብላችሁ ካሰባችሁ ተሳስታችኋል፡፡ ዙሪያውን አረቢያን መጅሊስ የተነጠፈበት ሰፊ ሳሎን እና ፓወር ፖይንት ግድግዳው ላይ ተደግኗል፡፡ ከጎኑ ቴሌቪዥን ብቻ አለው፡፡ ፓወር ፖይንቱን ስመለከት፣ ዎርክ ሾፕ ወይም ስልጠና የሚሰጥበት አዳራሽ ነገር መሰለኝ፡፡
“ፓወር ፖይንቱን ምን ታደርግበታለህ?”
“እኔ ቴሌቪዥን የማየው በዚህ ነው፡፡”
ሳቅ...
“ምነው ትስቃለህ? እዛ ግብርና ቢሮ ስሰራ፣ የተሰጠኝ ነው፡፡ ወደ ሌላ ቢሮ ሲቀይሩኝ ለቤት ይሆናል ብዬ ይዤው መጣሁ፡፡ እኔ በዚህ  ማየት ለምጄ ቲሌቪዥን ይደብረኛል አቦ!! በተለይ እግር ኳስ ካለ  ይሄን ግድግዳው ላይ ቲለቃለህ፡፡ በቃ ስክሪን ነው፡፡” ... ሳቅ
”ትራስ አምጪ!” አዘዛት ትልቋን ልጁን፡፡
”አረፍ በሉ፡፡ ውሃ አምጡላቸው፡፡ ምሳ እንብላ?”
”እረ እኛ በልተን ነው የመጣነው፡፡”
”ወላሂ በሉ እስኪ?”
”ወላሂ፡፡”
”በቃ ቃሙ እናንተ እኔ ትንሽ ልብላ፡፡”
”ሃዬ!”
”እንዴት ነው ሶማሌ ክልል አሁን ሰላም ነው አይደል?” ሁሌም ስጋት የማይለየው ሾፌር ጠየቀ፡፡
”አሁንማ ምን አለ፡፡ አገር ተረጋግቷል፡፡ እኔ ከአምስት ዓመት በፊት፣ ምእራብ ጎዴ ስሰራ በቀኝ በኩል ወታደር፣ በግራ በኩል ሽፍታ እያጀበኝ ነበር የሰራሁት፡፡”
”እረ ባክህ፡፡ አሁንም ሽፍታ አለ?”
”የለም አቦ አቲፍራ፡፡ ወንድ ልጅ አይፈራም!!”
“እንደው ቤተሰብ ያለው ሰው ይጨነቃል ብዬ ነው፡፡” ሹፌሩ መለሰ፡፡
”ቆይ አንተ ስንት ልጆች አሉህ?”
አንድ ልጅ ነው ያለኝ፡፡”
”ሀይ!! አንድ ልጅ ወልደህ ነው ሃረካት የምታበዛው፡፡ አንድ ልጅ ብቻ ምን ያደርጋል፡፡ ጨምረህ ውለድ፡፡ ሚስትህን ውለጂ በላት፡፡ እምቢ ካለች ሌላ ሚስት አግባና ውለድ፡፡ ልጅ ኽይር ነው።” ሳቅ
(ይቀጥላል)




• አክሱም ቤቲንግ በአዲስ አበባ 7 ቅርንጫፎች ከፍቶ፤ በ60 ዓይነት ውርርዶች ከ100 በላይ ስፖርቶች እያጫወተ ነው፡፡
• በ20 ብር ትኬት ከ1 እስከ 20 ጨዋታዎችን በአክሱም ቤቲንግ መወራረድ ይቻላል ፤ ከፍተኛው ሽልማት እስከ 250ሺ ብር ነው፡፡
• በዓለም ዙርያ እስከ 3 ትሪሊዮን ዶላር የሚንቀሳቀስበት ኢንዱስትሪ ሆኗል፡፡
• በአፍሪካ በ27 አገራት የስፖርት ውርርድ እየተካሄደ ሲሆን የውርርድ ተቋማት ብዛታቸው 2ሺ ይደርሳል፡፡ በደቡብ አፍሪካ፤ ናይጄርያና ኬንያ ተስፋፍቷል፡፡

የስፖርት ውርርድ ሁሉንም ማህበረሰብ ሊያሳትፍ የሚችል በስፖርት ውጤቶች ላይ በመንተራስ የሚካሄድ አዝናኝና ገቢ የሚያስገኝ ጨዋታ ነው፡፡ የውርርድ ተጨዋቾች እና ተሳታፊዎች የስፖርት ውድድሮችን በመመልከት ከሚኖራቸው መዝናናት ባሻገር፤ በተለያዩ የመወራረጃ መስፈርቶች በሚሰጧቸው ግምቶች የገንዘብ ተሸላሚ የሚሆኑበትን እድል ይፈጥርላቸዋል። አወራራጅ ተቋም በተለያዩ የስፖርት ውድድሮች የውርርድ ዝርዝሮችን በመግለፅ እና የሚሸልመውን ገንዘብ በማሳወቅ የሚሰራ ሲሆን አጠቃላይ አካሄዱም በህግና ስርዓት የተመራ ነው፡፡ በስፖርት የተለያዩ ሁኔታዎች በመወራረድ በህጋዊ መንገድ እየተዝናኑ መጫወት፡፡ ለሀገር የገቢ ምንጭ ከመሆኑም በላይ  የስራ እድሎችን የሚፈጥር መስክ ነው፡፡ የስፖርት ውርርዱን በህጋዊ መንገድ መካሄዱ በህብረተሰቡ ዘንድ ህገወጥ በሆነ መንገድ በመወራረድ የሚፈጠሩ አላስፈላጊ ችግሮች ለመከላከልም የሚያግዝ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ በህጋዊ መንገድ  የሚካሄዱ የስፖርት ውርርዶች በሌሎች የአፍሪካ  አገራት ባሉበት ደረጃ ላይ አይገኝም። ከ4 ዓመታት በፊት ዳጉ ቤት ኢትዮጵያ በተባለ ተቋም በፈርቀዳጅነት ቢጀመርም፤ ብዙ የዘለቀ አልነበረም።  ባለፉት 8 ወራት  ግን ህጋዊ ፈቃድ አግኝቶ መስራት በጀመረው አክሱም ቤቲንግ የተባለ የስፖርት ውርርድ ተቋም መስኩ መነቃቃት ጀምሯል፡፡የብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደር  የስፖርት ውርርድን ለማካሄድ የሚያስችል መመርያ በኢትዮጵያ መንግስት ያፀደቀው ከ5 ዓመታት በፊት ነበር፡፡  ፍቃድ የሚያገኙ ድርጅቶች በህግ ማዕቀፍ ሆነው ውርርዱን እንዲያጫውቱ የሚያደርገው የብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደር አፈፃፀሙን በመከታታል በመቆጣጠር አብሮ ይሰራል፡፡ የትኛውም ድርጅት፤ ተቋም ወይም ግለሰብ ለስፖርት ውርርድ ህጋዊ ፈቃድን ማግኘት እንደሚችል  የብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደሩ ያስታወቀ ሲሆን የሚሰጠው ፍቃድ በየዓመቱ የሚታደስ ነው፡፡
አክሱም ቤቲንግ እና እንቅስቃሴዎቹ
አክሱም ቤቲንግ በ300ሺ ዶላር ካፒታል  የተቋቋመ የስፖርት ውርርድ ተቋም ሲሆን 18 ሰራተኞችን በሂሳብ ሰራተኝነት፤ በሱቆች ማናጀርነት እና በሹፌርነት በመቅጠር የሚያስተዳድር ነው፡፡   በኢትዮጵያ በስፖርት ውርርድ መስክ ከፍተኛ አቅም መኖሩን የተገነዘበው ይህ ተቋም በመስኩ ዘላቂ እቅዶችን በመንደፍ እየሰራ መሆኑን ምክትል ሥ/አስኪያጁ ለስፖርት አድማስ ተናግሯል፡፡ የአክሱም ቤቲንግ ምክትል ሥ/አስኪያጅ፤ የዴቨሎፕመንት እና ሪሰርች ሃላፊ አብርሃም ተክለማርያም ይባላል፡፡ የስፖርት ጋዜጠኛ፤ የእግር ኳስ አሰልጣኝ፤ ቀድሞ በደቡብ አፍሪካ ሱፐርቤቲንግ ከተባለ የስፖርት ውርርድ ተቋም ጋር በመስራት ልምድ ያካበተ ነው፡፡ ለስፖርት ውርርድ ኢትዮጵያ አመቺ መሆኗንም በተለያዩ ማስረጃዎች ማመልከት ይቻላል፡፡ ከ90 ሚሊየን በላይ የህዝብ ብዛት ያለባት ሀገር መሆኗ አንዱ ትልቅ አቅም ነው፡፡ አዲስ አበባ ደግሞ ከተለያዩ የአፍሪካና የዓለም ሀገራት የተውጣጡ ዜጎች መናሀሪያ መሆኗም መስኩን ለማንቀሳቀስ ማመቸቱም ይጠቀሳል፡፡ በአዲስ አበባም ሆነ በሌሎች የክልል ከተሞች የስፖርት ውርርዶች የመዝናኛ አማራጮች መሆን እንዳለባቸው ለስፖርት አድማስ አስተያየት የሰጠው አብርሃም ተክለማርያም፤ የምስራቅ አፍሪካ፤ የአፍሪካን ገበያ ከዚያም አልፎ እስከ ኤስያ አህጉር በመሻገር በስፖርት ውርርድ መስክ ኢትዮጵያ ገበያውን ለመቆጣጠር እንደምትችል በማመን በአክሱም ቤቲንግ እየሰራን ነው ሲል ይናገራል። በአሁኑ ወቅት ከኢትዮጵያ ባሻገር በበርካታ ሀገራት የስፖርት ውርርዶችን እየሰራ የሚገኘው አክሱም ቤቲንግ  በቤለሩስ፣ በሰሜን ኢራቅ፣ በሞልዶቫ፣ በቆጵሮስ፣ በኬንያ፣ በዩጋንዳና በጋና የሚንቀሳቀስ ሲሆን በቀጣይ ወር ደግሞ በታንዛኒያም ቢሮውን የሚከፍት ይሆናል፡፡
ባለፉት 8 ወራት አክሱም ቤቲንግ በኢትዮጵያ የስፖርት ውርርድ ለማስፋፋት ቴክኒካዊ ስራዎችን መሰረት በማስያዝና በማስተዋወቅ ላይ አተኩሮ እየተንቀሳቀሰ ቆይቷል፡፡   ድረ ገፁን በዘመናዊ በዘመናዊ ዲዛይን በተጠቃሚዎቹ በሚመች መልኩ አደራጅቷል። የስፖርት ውርርዶችን ማካሄጃና ውድድሮችን መመልከቻ ስፍራ በዋና መስርያ ቤቱ  22 ከአውራሪስ ሆቴል ፊት ለፊት መክፈቱን ጨምሮ በአዲስ አበባ የተለያዩ አካባቢዎች ሰባት ቅርንጫፎች አሉት፡፡ እነዚህ ቅርንጫፎቹ ሳሪስ አዲስ ሰፈር እናት ባንክ ፊትለፊት፤ በጎተራ ኮንደሚኒዬም በሚገኘው ግቢ ላውንጅ እና ስፖርት ባር፤ ወሎ ሰፈር አካባቢ ሚና ህንፃ ላይ በሚገኘው ፍሬንድስ ኤንድ ባር ሬስቶራንት፤ ቦሌ ማተሚያቤት ጀርባ በሚገኘው ፊደል ባርና ሬስቶራንት፤ መስቀል ፍላወር አካባቢ በዋን ሞር ናይት ላውንጅ እንዲሁም አዲስ አበባ ስታድዬም ዙርያ በዛብሎን ትርጉም ቤት ውስጥ የሚገኙ ናቸው፡፡ የአክሱም ቤቲንግ  ምክትል ሥ/አስኪያጅ አብርሃም ተክለማርያም ለስፖርት አድማስ እንደገለፀው፤ በወቅቱ የሞባይል ኢንተርኔት አገልግሎት ችግር ሳቢያ የነበረ እቅዳቸው ቢስተጓጎልም ከአዲስ አበባም ውጪ በባህርዳር፤ በጎንደር፤ በመቀሌ፤ በአዳማ  እና ሀዋሳ ከተሞች ቅርንጫፎቻቸውን ለመክፈት ፍላጎት አላቸው፡፡
ሰሞኑን 22 አካባቢ ከአውራሪስ ሆቴል ፊት ለፊት ያለውን የአክሱም ቤቲንግ የስፖርት ውርርድ ቤት ጎብኝተን ነበር፡፡ ባለ 45 ኢንች የሆኑ 18 ፍላት ስክሪን ቴሌቪዥኖች አሉ፡፡ የሂሳብ ሰራተኞች በኮምፒዩተሮቻቸው ፈጣን አገልግሎት ይሰጣሉ፡፡ ምቹ የማረፊያ ስፍራዎች ሻይና ቡና በነፃ ነው፡፡ የስፖርት ውድድሮችን በመመልከት ጎን ለጎን ውርርድ የሚካሄድበት ይህ ቤት፤ በእረፍት ቀናቶች በሩ ለሁሉም ክፍት ነው፡፡ የስፖርት ውርርድ ተሳታፊዎች ከጓደኞቻቸው ጋር ገብተው ውድድሮችን በነፃ እየተመለከቱ የስፖርት ውርርዳቸውን እየተጫወቱ ሊስተናገዱበት ይችላሉ፡፡ የአክሱም ቤቲንግ የስፖርት ውርርዶች www.axumbet.com በሚለው ድረገፅ የሚካሄዱ ናቸው፡፡  ከ100 በላይ የስፖርት ውርርዶችን እያጫወቱ ሲሆን እግር ኳስ፣ ቅርጫት ኳስ፣ መረብ ኳስ፣ ቴኒስ፣ ራግቢና ኪርኬት … የሚጠቀሱ ናቸው፡፡  
በኢትዮጵያ ስለ ስፖርት ውርርድ በቂ እውቀትና ግንዛቤ ተፈጥሯል ለማለት አይቻልም፡፡ በርካታ እንቅስቃሴዎች ገና ያስፈልጋሉ፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ ህብረተሰቡ በስፖርት ውርርድ  ላይ እምነት ማሳደር አለበት፡፡ ከዚያም በኋላ ገንዘቡን አውጥቶ በነፃነት ሊጫወት ይችላል፡፡ ምክትል ሥ/አስኪያጅ አብርሃም ስለ አክሱም ቤቲንግ የግብር አከፋፈል ለስፖርት አድማስ ባደረገው ገለፃ ተቋማቸው ከጠቅላላ ገቢው 15 በመቶ ለብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደር፤ 10 በመቶ ለገቢዎች እና ጉምሩክ እንዲሁም 15 በመቶ የአሸናፊነት ክፍያ በመቅረጥ ገቢ ያደርጋል፡፡   ትልቁን ተፅዕኖ እየፈጠረ ያለው የግብር አከፋፈሉ የንግድ መስኩን ለማፋፋት የሚያበረታታ አለመሆኑ ነው፡፡  
የስፖርት ውርርድ የሚያካሂድ ተቋም  ፍላጎት የሚሆነው ከተጣራ ትርፍ 15 በመቶ ለመክፈል ነው፡፡ አሁን ባለው አሰራር ከሚያስገባው ያልተጣራ ትርፍ እስከ 15% ግብር ይከፍልበታል፡፡ ይኸው የግብር አከፋፈል የስራ መስኩን ለማስፋፋት የሚደረገውን ጥረት እንደሚያጓትት ነው የአክሱም ቤቲንግ ሃላፊዎች የሚያስረዱት፡፡ የንግድ መስኩ በበቂ ሁኔታ ከተስፋፋ በኋላ አገሪቱን በከፍተኛ ተጠቃሚ ማድረግ እንደሚችል የሚጠቅሱት የአክሱም ቤቲንግ ሃላፊዎች ከብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደር ጋር ግልፅ መግባባት ፈጥረን ለመስራት ጥረት ማድረጋችን ይቀጥላል ይላሉ፡፡ የስፖርት ውርርድ ላይ  ወዲያውኑ የሚከፈል ነገር የለም፡፡ ተሳታፊዎች ምን ያህል እንደሚያስይዙ፤ በምን ያህል ውርርዶች ላይ እንደሚሳተፉ ወዲያውኑ ማወቅ አይቻልም፡፡ ይህም ገቢዎችን ሰብስቦ ግብር ለመክፈል በሚኖረው ሂደት ላይ ትዕግስት እንደሚያስፈልገው ያመለክታል። ህጋዊ ፈቃድ አውጥተን መስራታችን በሀገሪቱ ህግ መሰረት መንቀሳቀሳችን የስፖርት ውርርድን በኢትዮጵያ ለማስፋፋት በምናደርገው ጥረት የብሄራዊ ሎተሪ አስተዳደር  ድጋፍ ወሳኝ ነው በማለት የአክሱም ቤቲንግ ሃላፊዎች ለስፖርት አድማስ ተናግረዋል። በቀጣይ አክሱም ቤቲንግ ከስፖርት ሚዲያዎች ጋር የመስራት እቅዶችንም ይዟል፡፡ ከሁለት የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ጋር እየተነጋገረ ሲሆን በሌሎች የኤፍኤም ራዲዮ ጣቢያዎችም ከስፖርት ውርርድ ጋር የተያያዙ ፕሮግራሞችን ለመስራት ድርድር እያደረጉ ናቸው፡፡  
በዓለም ዙርያ የሚደረጉ የስፖርት ውርርዶችን ለመወራረድ ወይንም ለመጫወት በአክሱም ቤት ዋና መስርያ ቤት ወይም በቅርንጫፎቹ በመገኘት የጨዋታውን ዝርዝር ወስደው በመመልከት ለመጫወት የፈለጉትን ቡድንና የጨዋታ አይነት ይመርጣሉ፡፡ በሌላ በኩል በድረገፅም በቀጥታ መጫወት ይችላሉ። ድረገፆቸውን ከፍቶ የምዝገባ ቅፅ መሙላት ከዚያም ስልክ ቁጥር ማስገባት፤ የምስጥር ጥያቄ መመለስ፤ ለመወራራጃ የሚያፈልገውን ገንዘብ ገቢ ማድረግ ከዚያም ውርርዱን መጀመር ነው፡፡ በአክሱም ቤቲንግ ማንኛውም ሰው በ20 ብር አንድ ቲኬት በመግዛት ከ1-20 ጨዋታዎችን መወራረድ ይችላል፡፡ በአጠቃላይ የስፖርት ውርርድ ተቋሙ ከ60 በላይ የውርርድ ጨዋታዎችን ለደንበኞቹ የሚያቀርብ ሲሆን ከፍተኛው ሽልማት እስከ 250ሺ ብር ነው፡፡ ውርርዱ የሚካሄድባቸው መንገዶች - አሸናፊውን ቡድን በመገመት መወራረድ - ትክክለኛ ውጤት በመገመት መወራረድ - የጨዋታውን የመጀመሪያ አጋማሸ ውጤት በመገመት መወራረድ - ቀድሞ ጐል የሚያስቆጥረውን ክለብ በመገመት መወራረድ - በመጀመርያው ግማሽ፤ በሁለተኛው ግማሽ እና በሙሉው የመደበኛ ጨዋታ ክፍለ ጊዜ የሚገቡ ጎሎች ብዛት በመገመት መወራረድ - እንዲሁም ሌሎች። በአክሱም ቤቲንግ የውርርድ መመርያ መሰረት በ90 ደቂቃ የእግር ኳስ ጨዋታ ውድድር ውጤት መወራረድ የሚቻል ሲሆን፤ ነገር ግን ውርርዱ የተጨማሪ ሰዓት (30 ደቂቃ) እና የመለያያ ምትን አያጠቃልልም፡፡ ሁሉም ውርርድ የሚካሄደው ጨዋታው ከመጀመሩ በፊት ይሆናል፡፡
ለስፖርት ውርርድ አፍሪካ ምቹ እየሆነች መጥታለች
የስፖርት ውርርድ በዓለም ዙርያ በከፍተኛ ደረጃ እየተስፋፋ የመጣ ሲሆን ትርፋማ ኢንዱስትሪ ሆኗል፡፡  በመላው ዓለም የሚንቀሳቀሱ  የስፖርት አወራራጅ እና አቋማሪ ኩባንያዎችን  በየዓመቱ ከ55ሺ በላይ የስፖርት ውድድሮችን ተንተርሰው በመንቀሳቀስ ላይ ናቸው።  በተለያዩ ጥናታዊ ዘገባዎች እንደሚጠቀሰው በዓለም ዙርያ የስፖርት ውርርድ  በየዓመቱ እስከ  3 ትሪሊዮን ዶላር በሚንቀሳቀስበት ገበያ እየተጧጣፈ ነው፡፡ በህጋዊ እና ህገወጥ የስፖርት ውርርዶችን የሚያካሂዱ አወራራጅ ተቋማት በዓለም ዙርያ ገቢያቸው ከ 700 ቢሊዮን እስከ 1 ትሪሊዮን ዶላር ይገመታል፡፡ በመላው ዓለም የስፖርት ውርርድ 65 በመቶ የገበያውን ድርሻ የተቆጣጠረው የእግር ኳስ ስፖርት ነው፡፡ እያንዳንዳቸው 12 በመቶ የገበያ ድርሻ በመያዝ የሚከተሉት የቴኒስ እና የክሪኬት ስፖርቶች ናቸው፡፡
የስፖርት ውርርድ በአሜሪካ አህጉር ተጀምሮ፤ በአውሮፓ እና በኤስያ አህጉራት በከፍተኛ ደረጃ ከተስፋፋ በኋላ ነው ወደ አፍሪካ አህጉር የመጣው፡፡ ዓለም አቀፍ የስፖርት ውርርድ ተቋማት በአፍሪካ  አህጉር ላይ ባለፉት 5 ዓመታት በትኩረት መስራት ጀምረዋል፡፡  ለዚህም የተለያዩ ምክንያቶች ይጠቀሳሉ፡፡ የመጀመርያው ምክንያት ከአፍሪካ አህጉር አጠቃላይ የህዝብ ብዛት እድሜያቸው ከ15 እስከ 27  እድሜያቸው የሆኑ ከ200 ሚሊዮን በላይ መሆናቸው ነው፡፡ በሌላ በኩል በአህጉሪቱ የየሞባይል አገልግሎት እየተስፋፋ መምጣቱ፤ የአውሮፓ እግር ኳስ ሊጎች በከፍተኛ ደረጃ ተወዳጅነት ማግኘታቸው፤ በየአገራቱ በስፖርት ውርርድ ተቋማት ገቢ ላይ ከአሜሪካ እና ከአውሮፓ አህጉራት ያነሰ የግብር ክፍያ መኖሩም ሊጠቀስ ይችላል፡፡ በአሁኑ ወቅት በአፍሪካ አህጉር በ27 አገራት የስፖርት ውርርድ እየተካሄደ ሲሆን በህጋዊ እና ህገወጥ መንገድ የሚንቀሳቀሱ ተቋማት ብዛት ከሁለት ሺ በላይ መሆናቸውን  መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡
በአፍሪካ የስፖርት ውርርድ ገዝፎ የሚታይባቸው እና የተስፋፋባቸው  3 አገራት ደቡብ አፍሪካ፤ ናጄርያ እና ኬንያ ናቸው፡፡ የኬንያው ስፖርትፔሳ፤ የደቡብአፍሪካ ሱፓቤትስ እና የናይጄርያው ቤት9ጄኤ በአህጉሪቱ ከሚገኙ ግዙፉቹ የስፖርት ውርርድ ተቋማት ግንባር ቀደም ተጠቃሾቹ ናቸው፡፡  ፕራይስዎተርስኩፐርስ የተባለ ዓለም አቀፍ ተቋም ከዓመት በፊት ይፋ ባደረገው ጥናት በ3ቱ አገራት የስፖርት ውርርድ ኢንዱስትሪ በከፍተኛ ደረጃ እያደገ መሆኑ ተጠቅሶ በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት የኢንዱስትሪው ገቢ በዓመት እስከ 50 ሚሊዮን ዶላር ሊደርስ እንደሚችል ተመልክቷል። በአፍሪካ እየተንቀሳቀሱ ያሉት የስፖርት ውርርድ ተቋማት አንድ ተሳታፊ ለሚያስይዘው 1 ዶላር በአማካይ እስከ 500 ዶላር በሚሸልሙበት ደረጃ ላይ ናቸው፡፡
በአፍሪካ ደረጃ የስፖርት ውርርድ በከፍተኛ ደረጃ የሚካሄድባት አገር ደቡብ አፍሪካ ስትሆን በየዓመቱ 21 በመቶ እድገት እያሳየ የሚገኝ ኢንዱስትሪዋ ነው፡፡ ከፍተኛ ደረጃ ካላቸው የደቡብ አፍሪካ የስፖርት ውርርድ ተቋማት መካከል ሱፓቤትስ፤ ስፖርትቤት፤ላድብሮክስ የተባሉት ይጠቀሳሉ፡፡ በደቡብ አፍሪካ የስፖርት ውርርዶች በእግር ኳስ፤ በራግቢ፤ በክሪኬት፤ በአትሌቲክስ ስፖርቶች በስፋት የሚካሄዱ ሲሆኑ የኢንዱስትሪው ዓመታዊ ገቢ 25 ሚሊዮን ዶላር መድረሱንም መረጃዎች ያመልክታሉ። ይህም ከአገሪቱ የስፖርት መስክ ገቢ 14 በመቶ  ድርሻ ይኖረዋል፡፡ በሌላ በኩል የስፖርት ውርርድ በምእራብ አፍሪካ በከፍተኛ ደረጃ የተስፋፋ ሲሆን በተለይ በናይጄርያ እና ጋና እየገዘፈ መጥቷል፡፡ ናይጄርያ ውስጥ በተለይ በስፖርት ውርርድ እድሜያቸው ከ18 እስከ 40 የሚሆኑ ከ60 ሚሊዮን በላይ የውርርድ ደንበኞች እስከ  9 ሚሊዮን ዶላር በድምሩ በነፍስ ወከፍ በየቀኑ  15 ዶላር በማያዝ ተሳትፎ ማድረጋቸው ይጠቀሳል፡፡
የኬንያ የስፖርት ውርርድ ተቋማት
ከምስራቅ አፍሪካ አገራት የስፖርት ውርርድ በከፍተኛ ደረጃ የተስፋፋባት አገር ጎረቤታችን ኬንያ ናት፡፡ በርግጥ አንዳንድ መረጃዎች በአፍሪካ አህጉር በስፖርት ውርርድ ፈርቀዳጅ መሆኗንና በ1950ዎቹ በዓለም አቀፍ የጎልፍ፤ የቴኒስ፤ የእግር ኳስ እና ሌሎች የስፖርት ውድድሮች መጀመሯን ይጠቅሳሉ፡፡ ባለፉት አምስት ዓመታት በኬንያ በከፍተኛ ደረጃ የተስፋፋው የስፖርት ውርርድ ላይ ስኬታማ በመሆንና በየጊዜው እድገት በማሳየት በተለይ 4 የውርርድ ተቋማት ሊጠቀሱ ይችላሉ፡፡ በዓመት እስከ 20 ሚሊዮን ዶላር ገቢ የሚያንቀሳቅሱ ናቸው፡፡
በመጀመርያ ደረጃ የሚጠቀሰው የውርርድ ተቋም በምስራቅ አፍሪካ ብቻ ሳሆን በመላ አህጉሪቱ ከሚንቀሳቀሱት መሰል ተቋማት ግንባ ቀደም ተጠቃሽ የሆነው ስፖርትፔሳ የተባለው የውርርድ ተቋም ነው። ስፖርትፔሳ በ2013 እኤአ ላይ ፔሳን ኢስት አፍሪካ ሊሚትድ በተባለ ኩባንያ የተጀመረ ሲሆን በድረገፁ          አንድ ሚሊዮን በክፍያ የተመዘገቡ ደንበኞች በማፍራት እስከ 40 ሚሊዮን ዶላር በዘርፉ እያንቀሳቀሰ የሚገኝ ነው።  የውርርድ ተቋሙ ድረገፅ በኬንያ ብዙ ጎብኝ ካላቸው 10 ድረገፆች አንዱ ሆኖም ይጠቀሳል።
ስፖርትፔሳ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ፤ የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ፤ ዩሮፓ ሊግ ውድድሮችን በመደበኛነት የሚያወራርድ ሲሆን ሌሎች የአውሮፓ ሊጎችን ጨምሮ፤ በቅርጫት ኳስ፤ በቴኒስ እና በራግቢ የሊግ እና የዓለም አቀፍ ውድድሮችም ይሰራል፡፡ ስፖርትፔሳ በስፖርት ውርርዱ ባለፉት አመታት ባገኘው ስኬት ተምሳሌት ሆኖ ሊጠቀስ የሚበቃ ሲሆን በስኬታማነቱ በአንድ ወቅት የኬንያ የሊግ ውድድር ስፖንሰር ለማድረግ የቻለ፤ ከሞባይል አገልግሎት ተቋማ ጋር ተቀናጅቶ የሚሰራ እንዲሁም የኢንቨስትመንት መስኩን ትልልቅ ፌስቲቫሎችን በማካሄድ የሚያስተዋውቅ ነው፡፡ በኬንያ ከስፖርትፔሳ ባሻገር ሌሎች የስፖርት ውርርድ ተቋማትንም መጥቀስ ይቻላል፡፡
በሁለተኛ ደረጃ የሚጠቀሰው በጃምቦ ቤቲንግ ሊሚትድ ከ4 ዓመታ በፊት ተመስርቶ መንቀሳቀስ የጀመረው ቤትዌይኬንያ ነው፡፡ ይህ ተቋም በዓለም አቀፍ ደረጃ ከፍተኛ እውቅና ያለውና፤ በማልቲስ እና ግራኒሴይ ተቀማጭነቱን ባደረገው እንዲሁም የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ክለብ የሆነውን ዌስትሃም ስፖንሰር የሆነው ቤትዌይ ቅርንጫፍ ሲሆን ዓለም አቀፍ ደረጃ የሚንቀሰቃቀሰው ቤትዌይ ሊሚትድ በተባለ ኩባንያ ነው፡፡ በሶስተኛ ደረጃ የሚጠቀሰው ደግሞ ቤቲንኬንያ የተባለው የውርርድ ተቋም ሲሆን፤ በአፍሪካ እና በአውሮፓ ትልቁ የስፖርት ውርርድ ተቋም ጎልድቤት ስር የታቀፈ እና በኬንያ ጋምኮድ በተባለ ኩባንያ የሚሰራ ነው፡፡ ቤት የቱ፤ ሚቼዛ፤ ኤሊት ቤት ዌይ፤ ጀስትቤት፤ ላኪ2ዩ እና ኬንያ ስፖርት ቤት ሌሎቹ በኬንያ የሚነቀሳቀሱ ህጋዊ የስፖርት ውርርድ ተቋማት ናቸው፡፡

• ስለሜክሲኮ ግንብ እና ስለኦባማኬር ያሉት ነገር የለም
• ሄላሪን ወህኒ አስገባታለሁ የሚለውን ዛቻ እንደማይተገብሩት ተገልጧል

ተመራጩ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ ባልተለመደ መልኩ ባለፈው ሰኞ በዩቲዩብ በኩል ባሰራጩት አጭር የቪዲዮ መልዕክት ስልጣን መያዛቸውን ተከትሎ ቀዳሚነት ሰጥተው የሚያከናውኗቸውን ተግባራትና ዕቅዶቻቸውን ይፋ ማድረጋቸው ተዘግቧል፡፡በመጀመሪያዎቹ 100 የስልጣን ቀናቴ ቀዳሚ ስራዎቼ ይሆናሉ ያሏቸውን ጉዳዮች ያብራሩት ትራምፕ፣ ስልጣን በያዙ በመጀመሪያው ቀን የሚያከናውኑት የመጀመሪያው ነገር፣ ከትራንስ ፓሲፊክ የንግድ አጋርነት ስምምነቶች መውጣት እንደሆነ አስታውቀዋል ብሏል ሲኤንኤን፡፡ ትራምፕ ቀዳሚ ስራዎቼ ይሆናሉ ካሏቸው ጉዳዮች መካከልም፤ በፕሬዚዳንት ኦባማ የተቀመጡ
የአካባቢ ጥበቃ ክልከላዎችን ማስቀረትና የስራ ዕድሎችን መፍጠር የሚሉት ይገኙባቸዋል ብሏል ዘገባው፡፡
አሜሪካን ከተለያዩ ጥቃቶች መከላከል የሚያስችሉ እቅዶችን እንዲያወጡ ለሚመለከታቸው የስራ ሃላፊዎች መመሪያ መስጠትም ከተቀዳሚ ስራዎቻቸው አንዱ እንደሆነ የጠቆሙት ትራምፕ፣በሜክሲኮና በአሜሪካ ድንበር ላይ ግንብ ማስገባትንና
ኦባማ ኬር ተብሎ የሚታወቀውን የጤና መድህን ማስቆምን ጨምሮ በምርጫ ቅስቀሳቸው ወቅት ቃል የገቧቸውን አነጋጋሪ ጉዳዮች በሰኞው መግለጫቸው አለማካተታቸውንም ዘገባው ገልጧል፡፡ የስልጣን ሽግግር ቡድን አዲሱ መንግስታቸው በመጀመሪያዎቹ 100 ቀናት ትኩረት ሰጥቶ ሊሰራባቸው የሚገባቸውን ጉዳዮች በማቀድና የፖሊሲ አቅጣጫዎችን በመንደፍ ረገድ ውጤታማ ስራ እየሰራ እንደሚገኝና ዝርዝር መረጃዎችን ለህዝቡ ይፋ እንደሚያደርጉም ትራምፕ በቪዲዮ መልዕክታቸው አስታውቀዋል፡፡በተያያዘ ዜና ተቀናቃኛቸውን ሄላሪ ክሊንተንን በኢሜይል ቅሌታቸው ሳቢያ ወህኒ እንደሚያስገቧቸው ሲዝቱ የከረሙት ትራምፕ፣ሴትዮዋ በቅሌቱ ሰበብ ከገቡበት ቀውስ እንዲወጡ ድጋፍ ያድርጉላቸዋል እንጂ እንደዛቱት በኤሜይል
ሰርቨራቸው ላይ ምርመራ እንዲደረግ እንደማያዝዙ የትራምፕ ከፍተኛ አማካሪ አስታውቀዋል፡፡አማካሪዋን ኬልያኔ ኮንዌይን ጠቅሶ አይሪሽ ታይምስ እንደዘገበው፣ ትራምፕ ወደ ስልጣን ሲመጡ በሄላሪ የኢሜይል ቅሌት ዙሪያ ምርመራ በማስደረግ ለፍርድ የማቅረብ ሃሳብ የላቸውም፡፡

በ4 ወራት ጊዜ ከስራ የተባረሩ 125 ሺህ፣ የታሰሩ 36 ሺህ ደርሰዋል

ባለፈው ሃምሌ ወር ከተቃጣበት የከሸፈ የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ጋር በተያያዘ በርካታ  ዜጎቹን በማሰርና ከስራ ገበታቸው በማፈናቀል ተጠምዶ የከረመው የቱርክ መንግስት፣ ተጨማሪ ከ15 ሺህ በላይ የመንግስት ሰራተኞችን ማባረሩን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡የአገሪቱ መንግስት ባለፈው ማክሰኞ በወሰደው እርምጃ ከስራ ገበታቸው የተፈናቀሉት እነዚሁ ቱርካውያን በውትድርና፣ በፖሊስ፣ በግብር ምርመራና በሌሎች የስራ መስኮች ላይ የተሰማሩ ናቸው ያለው ዘገባው፣ ይህም ከሃምሌ ወዲህ ከስራ የተፈናቀሉና የታገዱ ዜጎችን ቁጥር ከ125 ሺህ በላይ እንዳደረሰው ገልጧል፡፡ከመፈንቅለ መንግስቱ ጋር ንክኪ አላችሁ በሚል
በአገሪቱ መንግስት የታሰሩ ዜጎች ቁጥር 36 ሺህ ያህል እንደሚደርስ የጠቆመው ዘገባው፣ መንግስት መሰልእርምጃ መውሰዱን እንደሚቀጥል ማስታወቁንም አብራርቷል፡፡ በተያያዘ ዜናም የቱርኩ መሪ ጠይብ ኤርዶጋን ተመራጩን የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕን አምባገነን ናቸው ሲሉ የሚተቹትን ጸረ- ዲሞክራሲ ናቸው በማለት ማውገዛቸው ተዘግቧል፡፡

የካዛኪስታን ርዕሰ መዲና አስታና ስያሜ እንዲቀየርና ከተማዋ በ76 አመቱ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ኑርሱልጣን ናዛርባየቭ ስም እንድትጠራ ለማድረግ የሚያስችል ዕቅድ በፓርላማ መውጣቱን ሮይተርስ ባለፈው ረቡዕ ዘግቧል፡፡ፓርላማው ፕሬዚዳንቱ አገሪቱን በቅጡ በመምራት ላደገሩት አስተዋጽኦ እውቅና ለመስጠት በማሰብ ከተማዋን በስማቸው ለማስጠራት ያቀረበው እቅድ ስኬታማ የሚሆን ከሆነ፣ ወትሮም የግል ዝና በማካበት ሲታሙ የኖሩትንና ላለፉት 27 አመታት አገሪቱን ያስተዳደሩትን ፕሬዚዳንቱን የባሰ ሀሜትና ትዝብት ይጥላቸዋል ተብሏል፡፡የአገሪቱ ርዕሰ መዲና አስታና የሚለውን ስያሜ ላለፉት 18 አመታት ስትጠራበት እንደቆየችና ቃሉበካዛክ ቋንቋ ዋና ከተማ የሚል ትርጉም እንዳለው ያስታወሰው ዘገባው፣ ፕሬዚዳንቱ ፓርላማው ያቀረበውን የስያሜ ለውጥ እቅድ በተመለከተ በሳምንታት ጊዜ ውስጥ ምላሻቸውን ይሰጣሉ ተብሎ እንደሚጠበቅ ገልጧል፡፡ የአገሪቱ ማዕከላዊ ባንክ የፕሬዚዳንት ናዛርባየቭንፎቶ ግራፍ በመገበያያ ገንዘብ ላይ እንደሚያትምና ገንዘቡ ከመጪው ታህሳስ ወር ጀምሮ በስራ ላይ እንደሚውል ባለፈው ሳምንት ማስታወቁንም ዘገባው አክሎ አስታውሷል፡፡

ታዋቂው የግል የኤሮስፔስ ኩባንያ ስፔስኤክስ መሰረቱን በህዋ ላይ ያደረገ አለማቀፍ የኢንተርኔት አገልግሎት ለመዘርጋት የሚያስቸሉ ከ4 ሺህ በላይ ሳተላይቶችን ለማምጠቅ ማቀዱን አስታውቋል፡፡ ኩባንያው እቅዱን ለማሳካት የሚያስችሉትን 4
ሺህ 425 ሳተላይቶች የማምጠቅ ፈቃድ እንዲሰጠው ለአሜሪካ መንግስት ጥያቄ ማቅረቡን የዘገበው ዘ ዴይሊ ሚረር፣ የኩባንያው እቅድ የሚሳካ ከሆነ በየትኛውም የአለማችን ክፍል የሚገኝ ሰው የፈጣን የኢንተርኔት አገልግሎት ተጠቃሚ ሊሆን እንደሚችል ገልጧል፡፡ የኩባንያው የህዋ የኢንተርኔት አገልግሎት ፍጥነት እስከ 23 ጊጋ ባይት በሰከንድ እንደሚደርስ የጠቆመው ዘገባው፣ ፕሮጀክቱ 10 ቢሊዮን ዶላር ያህል ወጪ እንደሚደረግበት የኩባንያው ባለቤት ከዚህ ቀደም ማስታወቃቸውን አስታውሷል፡፡
ስፔስኤክስ የመጀመሪያውን ሳተላይት የሚያመጥቅበትን ትክክለኛ ጊዜ አለመግለጹን የገለጸው ዘገባው፣ ሳተላይቶቹ ወደ ጠፈር በተላኩ ከአምስት እስከ 7 ቸመታት ጊዜ በአገልግሎት ላይ እንደሚቆዩ አስረድቷል፡፡ በአሁኑ ሰአት ምድርን በመዞር ላይ የሚገኙ ስራ ያላቋረጡ ሳተላይቶች ቁጥር 1 ሺህ 419 ያህል እንደሆነም አክሎ ገልጧል፡፡

• አንድ ስዊዘርላንዳዊ በአማካይ 562 ሺህ ዶላር ሃብት አለው
• በአመቱ ጃፓን 20.1 ትሪሊዮን ዶላር ስታገኝ፣ እንግሊዝ 1.5 ትሪሊዮን ዶላር አጥታለች

ክሬዲት ሲዩሴ የተባለው አለማቀፍ የጥናት ተቋም ሰሞኑን ባወጣው የ2016 አለማቀፍ የሃብት ስርጭት ሪፖርት፣ ከአለማችን አገራት መካከል ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ድሆች የሚገኙባት ቀዳሚዋ አገር ህንድ መሆኗንና በአገሪቱ 246 ሚሊዮን ዜጎች በከፋ ድህነት ውስጥ እንደሚገኙ አስታወቀ፡፡  
72 ሚሊዮን የከፋ ድህነት ውስጥ የሚገኙ ዜጎችን የያዘቺው ቻይና በሪፖርቱ በሁለተኛነት ስትቀመጥ፣ ናይጀሪያ በ35 ሚሊዮን ከአለማችን አገራት ሶስተኛ ደረጃን መያዟንም ሪፖርቱ ያትታል፡፡
በአለማችን በከፋ ድህነት ውስጥ ከሚገኙና ከአጠቃላዩ የአለም ህዝብ ቁጥር 20 በመቶ ያህሉን የሚሸፍኑት አንድ ቢሊዮን ያህል ሰዎች ውስጥ፣ ሶስት አራተኛ ያህሉ የሚኖሩት በእስያና በአፍሪካ አገራት ነው ያለው ሪፖርቱ፣ ሩስያና ዩክሬንም በርካታ ድሆች ያሉባቸው አገራት እንደሆኑ ገልጧል።
በአለማችን  33 ሚሊዮን ያህል የሚሆኑና ከአንድ ሚሊዮን እስከ 50 ሚሊዮን ዶላር ሃብት ያካበቱ የተለያዩ አገራት እጅግ ባለጸጋ ዜጎች እንዳሉ የጠቆመው ሪፖርቱ፣ ከእነዚህም መካከል 45 በመቶው አሜሪካውያን መሆናቸውን አስታውቋል።
እጅግ እጅግ ባለጸጎች በሚለውና ከ50 ሚሊዮን ዶላር በላይ ሃብት ያካበቱ የናጠጡ ሃብታሞች በሚካተቱበት መደብ ውስጥ የተቀመጡ የተለያዩ የአለማችን አገራት ዜጎች ቁጥር 140 ሺህ 900 ያህል ደርሷል ያለው ሪፖርቱ፣ ግማሽ ያህሉ አሜሪካውያን፣ 11 ሺህ የሚሆኑት ደግሞ ቻይናውያን ናቸው ብሏል፡፡
እያንዳንዱ አዋቂ ዜጋዋ በአማካይ 562 ሺህ ዶላር ያካበተባት ስዊዘርላንድ የአለማችን ቁጥር አንድ የሃብታሞች ሃገር ናት ያለው ሪፖርቱ፣ አውስራሊያ በ376 ሺህ ዶላር፣ አሜሪካ በ345 ሺህ ዶላር እንደሚከተሏት ያትታል፡፡
በአለማችን በአመቱ ከፍተኛውን የሃብት መጠን ጭማሪ ያሰመዘገበቺው አገር ጃፓን ስትሆን፣ የአገሪቱ የሃብት መጠን ከ3.9 ትሪሊዮን ዶላር ወደ 24 ትሪሊዮን ዶላር አድጓል ተብሏል፡፡
በአንጻሩ ደግሞ በአመቱ የከፋውን የሃብት ኪሳራ ያስተናገደቺው እንግሊዝ መሆኗንና፣ አገሪቱ አንድ እና አንዱ ባልለየለት የአውሮፓ ህብረት አባልነት ሪፈረንደም ሳቢያ 1.5 ትሪሊዮን ዶላር ማጣቷን ሪፖርቱ አስረድቷል፡፡





     ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በስልጣን ዘመናቸው የመጨረሻቸው የሆነውን ታላቁን የፕሬዚዳንቱ የነጻነት ሜዳይ ሽልማት ባለፈው ማክሰኞ ምሽት በዋይት ሃውስ በተካሄደ ስነስርዓት ለ21 ታዋቂ አሜሪካውያን አበርክተዋል፡፡
ኦባማ የእኔ ጀግና ያሏቸውና ታላቁን የነጻነት ሜዳይ ያጠለቁላቸው 21 አሜሪካውያን በተለያዩ መስኮች ለአገራቸውና ለህዝባቸው የጎላ አስተዋጽኦ ያበረከቱ ሲሆኑ  የፊልምና የመዝናኛ ዘርፍ ዝነኞች፣ ሳይንቲስቶች፣ ስፖርተኞች፣ በጎ አድራጊዎችና በሌሎች መስኮች የተሰማሩ መሸለማቸው ታውቋል፡፡  
“ሁሉም የዕለቱ ተሸላሚዎች በአንድም ሆነ በሌላ መልኩ በግሌ ተጽዕኖ የፈጠሩብኝ ናቸው” ሲሉ ተሸላሚዎችን አድንቀዋል፤ ኦባማ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ ባደረጉት ንግግር፡፡
ኦባማ የአሜሪካን ትልቁ የሲቪል ሽልማት  በክብር ካበረከቱላቸው ተጽዕኖ ፈጣሪ ታዋቂ አሜሪካውያን መካከል፣ ከመዝናኛው ኢንዱስትሪ የፊልም ከዋክብቱ ቶም ሃንክስና ሮበርት ዲ ኔሮ፣ ከበጎ ምግባር ስራዎች ቢል እና ሚሊንዳ ጌትስ፣ ከስፖርት ካሬም አብዱል ጀባርና ማይክል ጆርዳን ይገኙበታል፡፡ ከዘንድሮ ተሸላሚዎች በእድሜ ትንሹ የ53 አመቱ የቀድሞው የቅርጫት ኳስ ተጫዋች ማይክል ጆርዳን ሲሆን፣ በዕድሜ ትልቁ  ተሸላሚ ደግሞ የ91 አመት የእድሜ ባለጸጋዋ ተዋናይት ሲስሊ ታይሰን ናቸው፡፡

ናሁሰናይ በላይ
(በአ.አ.ዩ የፖለቲካ ሳይንስ እና የፌደራሊዝም መምህር

ሹም ሽር መደረጉ፣ መንግስት የለውጥ ፍላጎት እንዳለው፣ ምልክት እንደማሳየት ነው፡፡ “የለውጥ ፍላጎት አለኝ፤ ፍላጎቴንም በዚህ በሹም ሽር እዩት” የሚል ምልክት ሰጥቷል፡፡ ነገር ግን፣ ከገጠመን ችግር አንፃር ሲታይ የሚያስፈነጥዝ አይደለም፡፡
እርግጥ ነው፣ ያመጣው ነገር አለ፡፡ እውቀት እና ስራ መገናኘት አለባቸው የተባለ ይመስላል፡፡ እውቀትና ስልጣን ሲገናኙ፣ የተሻለ ነገር መስራት ይቻላል የሚል አቅጣጫ ለማሳየት ተሞክሯል፡፡ ይሄ መልካም ነው፡፡ ነገር ግን መጠንቀቅ አለብን፡፡
ኢትዮጵያ ላይ የተከሰተው ችግር፣ የብዙ ነገሮች ድምር ውጤት ነው፡፡ የመንግስት ቅቡልነት ቀውስ ውስጥ የገባበት ነው፡፡ በጣም ጉልህ የስራ አጥነት ችግር አለ፡፡ እንግዲህ ከገጠመን ችግር አንፃር፣ የመንግስት ጥረት በሹም ሽር የሚያበቃ ከሆነ፣ ሌላ ራሱን የቻለ ችግር ነው የሚሆነው፡፡ ጅምሩ ጥሩ ቢሆንም፣ ከአገሪቱ ችግር አንፃር ትንሽ ነው፡፡
የኢህአዴግ ድርጅቶችን ግምገማ በተመለከተ፣ እኔ ከግምገማዎቹ ብዙ አልጠብቅም፡፡ ኢህአዴግ ችግሩን በቅጡ ያወቀው አልመሰለኝም፡፡ አሁን የችግሩን ምልክቶች ነው እያሯሯጠ ያለው፡፡ በሽታውን ሳይሆን የበሽታውን ምልክቶች ነው እያከመ ያለው፡፡
በዚህ ሁኔታ አሚካሄድ ግምገማና ብወዛ፣ ትልቅ ለውጥ እንዲያመጣ አልጠብቅም፡፡ በእርግጥ፣ ለምሳሌ ኦሮሚያ ክልል ጥሩ የመሻሻል ምልክት ታይቷል፡፡ የተማረና አቅም ያለው፣ ወጣት አመራር ለመፍጠር ዝግጁ እንደሆነ አሳይቷል፡፡ በተቃራኒው በህውሓትና በብአዴን በኩል ሲታይ ደግሞ፣ ፍላጎቱ ያላቸው አይመስልም፡፡ ወንበሩን እንደርስት የያዙ ሰዎች፣ በዚያው እንዲቀጥሉ የሚያስቡ ይመስላል፡፡
ስለዚህ ኢህአዴግም መንግስትም፣ የችግሩን መሰረታዊ ባህሪ በቅጡ ሳይረዱ፣ ችግሩን ያክማል ብለው የሚያመጡት መድኃኒት፣ ችግሩን ከማከም ይልቅ የጎንዮሽ ጉዳት ያስከትላል የሚል ስጋት አለኝ። ዋናው የኢህአዴግ ችግር የሚመስለኝ፣ ችግሩን አለማወቁ ነው፡፡ ወይ ለማወቅ አለመፈለግ፣ አሊያም ለማወቅ አለመቻል፡፡
የፌደራል ስርአቱም ሆነ ህገ መንግስቱ፣ ችግር አለባቸው ብዬ አላምንም፡፡ ፖለቲካው ህገ መንግስቱን መምሰል ስላልቻለ ይመስለኛል እዚህ ሁሉ ጣጣ ውስጥ የገባነው፡፡ በተለያዩ የመንግስት መዋቅሮች ውስጥ ሊኖር የሚገባው ህግንና ህግን ብቻ መሰረት ያደረገ አሰራር፣ ገና አልተፈጠረም። ይሄ የእገሌ ወይም የእገሊት ድክመት አይደለም፡፡ ግን አሁን የተፈጠረውን ችግር ከግለሰቦች ባህሪ ጋር ያገናኙታል፡፡ ይሄ ተስፋን የሚያጨልም ነው፡፡
የፖለቲካ ስርአት ሊበላሽ የሚችለው፣ ከግለሰብ በመነጨ ችግር ብቻ አይደለም፡፡ ግለሰቦች ስልጣን ሲያገኙ አይበላሹም ማለቴ አይደለም፡፡ የሚበላሹ ግለሰቦች ሁሌም የትም አገር ይኖራሉ፡፡ ዋናው ነገር፣ የፖለቲካ ስርዓቱ፣ ባለስልጣናት እንዳይበላሹ የሚቆጣጠር መሆኑና አለመሆኑ ላይ ነው፡፡ ችግሩን በዚህ መንገድ አይቶ ሳይንሳዊ ጥናትና ትንታኔ መስራት ካልተቻለ፣ “እንታደሳለን፤ ቃል እንገባለን” ማለት ብዙም አያስኬድም፡፡