Administrator

Administrator

     ባለፉት 2 ሳምንታት በኡጋንዳ አስተናጋጅነት በተካሄደው የ2016 የሴካፋ ሴቶች ሻምፒዮና የፍፃሜ ጨዋታ ታንዛኒያ  2ለ1 ኬንያን በመርታት የዋንጫው አሸናፊ ሆናለች፡፡ በሻምፒዮናው በአፍሪካ ዋንጫ ሴካፋን በመወከል የምትሳተፈው ኬንያ በ2ኛ ደረጃ ስታጠናቅቅ፤ ኢትዮጵያ 3ኛ ደረጃ እንዲሁም አዘጋጇ ኡጋንዳ 4ኛ ደረጃዎችን አግኝተዋል፡፡ የኪሊማንጃሮ ንግስቶች የሚባሉት የታንዛኒያ ሴቶች ብሄራዊ ቡድን ዋንጫውን ለማሸነፍ የበቁት በሚያስደንቅ የቡድን ጥንካሬ እና ሁሉንም ጨዋታዎች በማሸነፍ ነው፡፡ በሻምፒዮናው የኡጋንዳዋ  ሃሳኒ ናሳና በ6 ጎሎች ኮከብ ግብ አግቢ ሆና ስትጨርስ የሉሲዎቹ አጥቂ ሎዛ አበራ በ5 ጎሎች ሁለተኛ ደረጃ አግኝታለች። የኢትዮጵያ ሴቶች ብሄራዊ ቡድንን በዋና አምበልነት የመራችው ብርቱካን ገብረክርስቶስ ኮከብ ተጨዋች እንደነበረች ታውቋል። ሁለተኛ ደረጃ ያገኘችው ኬንያ  ዞኑን በመወከል ከ2 ወራት በኋላ ካሜሮን ላይ በሚካሄደው የ2016 የአፍሪካ ሴቶች እግር ኳስ ዋንጫ የምትሳተፍ ሲሆን፤ በሴካፋ ሴቶች ሻምፒዮና የነበራት ተሳትፎ ለአፍሪካ ዋንጫው ጠቃሚ ዝግጅት እንደሚሆንላት ተገልጿል፡፡ በሌላ በኩል የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን በቀጣይ የሴካፋ ሴቶች ሻምፒዮናን ቢያስተናግድ በአገሪቱ ለሚካሄደው የሴቶች እግር ኳስ ከፍተኛ መነቃቃት እንደሚፈጥር አስተያየቶች ተሰጥተዋል፡፡
በሴካፋ ሴቶች ሻምፒዮናው ሉሲዎቹ በምድብ 2 ከሩዋንዳ እና ከታንዛኒያ ጋር ተደልድለው ነበር፡፡ በመጀመርያ ጨዋታቸው በሎዛ አበራ ሁለት ጎሎች እና በመስከረም ኮንካ አንድ ተጨማሪ ግብ ሩዋንዳን 3ለ2 አሸነፉ፡፡ በሁለተኛ ጨዋታቸው ደግሞ ከታንዛኒያ ጋር 0ለ0 አቻ በመለያየት በምድባቸው  4 ነጥብ እና አንድ  የግብ ክፍያ ካስመዘገቡ በኋላ በእጣ ሁለተኛ ደረጃ አግኝተው ወደ ግማሽ ፍፃሜ አልፈዋል፡፡ በግማሽ ፍፃሜው  የተገናኙት  ከኬንያ አቻቸው ጋር የነበረ ሲሆን 3ለ2 ተሸንፈው ለዋንጫ ፍልሚያው ሳይደርሱ ቀርተዋል፡፡ በዚህ ጨዋታ ሁለቱንም ጎሎች ያገባችው ሎዛ አበራ ነበረች፡፡ ለደረጃ ጨዋታ የተገናኙት ደግሞ ከአዘጋጇ አገር ኡጋንዳ ጋር  ሲሆን 4ለ1 በሆነ ሰፊ ውጤት በማሸነፍ የሴካፋ ሻምፒዮና ተሳትፏቸውን በ3ኛ ደረጃ ማጠናቀቅ ችለዋል፡፡ በዚህ ጨዋታ  ረሂማ ዘርጋው 3 ጎሎች በማስቆጠር ሃትሪክ ስትሰራ 1ኛውን ጎል ያገባችው ደግሞ ሎዛ አበራ ነበረች፡፡ ሉሲዎቹ ለዋንጫ ቅድሚያ ግምት ቢሰጣቸው በግማሽ ፍፃሜ በኬንያ አቻቸው በገጠማቸው መራር ሽንፈት ሳይሳካላቸው ቀርቷል፡፡  በአጠቃላይ በሴካፋ ሴቶች ሻምፒዮናው ከምድብ አንስቶ እስከ ደረጃ ጨዋታው  4 ጨዋታዎች አድርገው ሁለቱን ሲያሸንፉ በአንድ አቻ ወጥተው በአንድ ጨዋታ ደግሞ ተሸንፈዋል፡፡ በተጋጣሚዎቻቸው ላይ  9 ጎሎች አስመዝግበው 6 ጎሎች ደግሞ አስተናግደዋል፡፡
ኡጋንዳ ስፖንሰር የሌለውን ሲኒዬር ቻሌንጅ ካፕ ሻምፒዮና ማስተናገዷን ያደነቁት የሴካፋ ምክር ቤት ዋና ፀሃፊ ኒኮላስ ሙንሶኜ ናቸው፡፡ ሻምፒዮናው በሴቶች እግር ኳስ  አብዛኛዎቹ የዞኑ አባል አገራት የሚገኙበትን ደካማ  ደረጃ  እንደሚቀይር ሲገልፁም፤ ለአፍሪካ ዋንጫና ሌሎች ኢንተርናሽናል ውድድሮች የሚደረጉ ዝግጅቶችን የሚያግዝ መሆኑን  አመልክተዋል። በሌላ በኩል ሻምፒዮናው በሴቶች እግር ኳስ ላይ የሊግ ውድድሮች ለሚያካሂዱት እና በተለያዩ የእድሜ ደረጃዎች በመስራት ላይ ለሚገኙት የምስራቅ አፍሪካ አገራት ከፍተኛ መነቃቃት እንደሚፈጥርም የሴካፋ ዋና ፀሃፊ አስገንዝበው ፤ በአፍሪካ ዋንጫ ላይ የዞኑ አገራት ተሳትፎ ማደግ እንዳለበት ሲናገሩ የሴካፋ ሴቶች ሻምፒዮናው ይህን የዞኑን ብሄራዊ ቡድኖች ተሳትፎ ለማጠናከር ያለው አስተዋፅኦ ከፍተኛ ነው ብለዋል፡፡ በሴካፋ የሴቶች ሻምፒዮናው ለዋንጫ ከተፋለሙት ታንዛኒያ እና ኬንያ ባሻገር ሁሉም ተሳታፊዎች በተለይ ኢትዮጵያ እና ኡጋንዳ ጥሩ ደረጃ ላይ እንደሚገኙ ታዝበናል የሚሉት ዋና ፀሃፊው በሚቀጥሉት የአፍሪካ ዋንጫዎች ከዞኑ ሁለት እና ሶስት አገራት መሳተፍ የሚችሉ ከሆነ  እድገት መኖሩን ያመለክታል ብለዋል፡፡ በአፍሪካ ሴቶች ዋንጫ ትልቁ የተሳትፎና የውጤት ክብረወሰኖች የተመዘገቡት  ሶስት ጊዜ በ2002፤2006 እና 2012 እኤአ ላይ መሳተፍ በቻለችው ኢትዮጵያ ሲሆን ሉሲዎቹ በ2006 እኤአ ላይ በአፍሪካ ዋንጫው ባገኙት አራተኛ ደረጃ የዞኑን ከፍተኛ ውጤት ነበራቸው፡፡ ታንዛኒያ በ2010 እኤአ ላይ ሴካፋን በመወከል በአፍሪካ ዋንጫው የተሳተፈች ሲሆን ለኬንያ የ2016 የአፍሪካ ሴቶችዋንጫ የመጀመርያው ይሆናል። ካሜሮን ለምታስተናግደው የ2016 የሴቶች አፍሪካ ዋንጫው የምድብ ድልድሉ ሰሞኑን የታወቀ ሲሆን ኬንያ በምድብ ሁለት ከናይጄርያ፤ ጋና እና ማሊ ጋር ስትደለደል በሌላ በኩል በምድብ 1 ካሜሮን፤ ግብፅ፤ ደቡብ አፍሪካና ዚምባቡዌ እንደሚገኙ ተገልጿል፡፡
ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ፌደሬሽኖች ማህበር ፊፋ ከ2014 ጀምሮ እስከ 2018  እኤአ በመላው ዓለም በሴቶች እግር ኳስ ተግባራዊ የሚሆን የእድገት ፕሮግራም በመንደፍ ሲንቀሳቀስ ቆይቷል፡፡  ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር አባል አገራቱ  የሴቶች እግር ኳስን በማሳደግ እንዲሰሩ የባለሙያ ክትትል ማድረግ፤ የአቅም ግንባታ ስልጠና በመስጠት፤ የገንዘብ ድጋፍ በማበርከትንና የፕሮሞሽን ተግባራትን በማከናወን እያገዛቸው ይገኛል፡፡  ፊፋ በዚህ የሴቶች እግር ኳስ የእድገት ፕሮግራሙ  በሁሉም የእድሜ ደረጃዎች አገር አቀፍ፤ ክፍለ አህጉራዊ እና አህጉራዊ ውድድሮች እንዲካሄዱ ድጋፍ የሚያደርግ ሲሆን በስሩ ያሉ 209 አባል አገራት ለተግባራዊነቱ የስራ እቅዶችና ስትራቴጂዎች ነድፈው እንዲያቀርቡ በመጠየቅ የሚሰራበትን ሁኔታ እስከ 2018 እኤአ የሚቀጥልበት ይሆናል፡፡  ከዚህ ጋር ተያይዞ ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር የሴቶች እግር ኳስ የእድገት ፕሮግራሙን በ2014 እኤአ ላይ ተግባራዊ ማድረግ ከመጀመሩ በፊት የሰራው ጥናት ነበር፡፡ ከአባል አገራቱ መካከል  177 የእግር ኳስ ፌደሬሽኖች በጥናቱ ላይ የተካተቱ ነበሩ፡፡ በዚህ የዓለም ሴቶች እግር ኳስ አጠቃላይ ጥናት ላይ የተሳተፉት 177 ፌደሬሽኖች በዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር በሴቶች እግር ኳስ ላይ በሚያደርጓቸው እንቅስቃሴዎች ዙርያ ላቀረበላቸው ጥያቄዎች 85 በመቶ ምላሽ ሰጥተዋል። በየአባል አገራቱ የሴቶች እግር ኳስ እድገትን የሚፈታተኑ ሁኔታዎች ተብለው በጥናቱ ከተጠቀሱት መካከል የሊግ ውድድሮች አለመሻሻል፤ አስተዳደራዊ ድክመቶች፤ የባለድርሻ አካላት በቅንጅት አለመስራት፤ በስፖርቱ የሴቶች ተሳትፎ ማነስ፤ ደካማ ኢንቨስትመንት፤ በአጠቃላይ የግንዛቤ ማነስ እና የሚዲያ ትኩረት ቀዝቃዛ መሆን ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ በ2014 እኤአ ላይ ዓለም አቀፉ የእግር ኳስ ማህበር ይፋ ባደረገው ይህ ጥናት በመላው ዓለም በእግር ኳስ ስፖርት ከ30 ሚሊዮን በላይ ሴቶች በተጨዋችነት እና በሌሎች ሙያዎች የሚሳተፉ መሆኑን ይገልፃል፡፡ በፊፋ የተመዘገቡት ሴት እግር ኳስ ተጨዋቾች ብዛት ከ4.8 ሚሊዮን በላይ እንዲሁም  በታዳጊ ፕሮጀክቶች የታቀፉት ደግሞ  እስከ 1.2 ሚሊዮን እንደሚገመቱ አመልክቷል። በጥናቱ የተሳተፉት 177 የእግር ኳስ ፌደሬሽኖች በአጠቃላይ በሴቶች እግር ኳስ እንቅስቃሴያቸው በዓመት እስከ 157 ሚሊዮን ዶላር በጀት ያወጣሉ፡፡ በየፌደሬሽኖቹ በእግር ኳስ አስተዳደርና ልዩ ልዩ ሃላፊነቶች የሴቶች ተሳትፎ 23 በመቶ፤  የሴቶች ዋና ብሄራዊ ቡድን ያላቸው 80 በመቶ፤ የወጣቶች ቡድን ያላቸው 50 በመቶ፤ የሊግ ውድድሮችን የሚያካሂዱ 78 በመቶ መሆናቸው ተረጋግጧል፡፡ በሌላ በኩል በእግር ኳስ ፌደሬሽኖቻቸው ስራ አስኪያጅ ኮሚቴዎች የሴቶች ተሳትፎ 8 በመቶ ፤ የሴት አሰልጣኞች 7 በመቶ እንዲሁም የሴት ዳኞች ተሳትፎ 10 በመቶ ብቻ እንደሆነም ጥናቱ አመልክቷል፡፡
የሴካፋ ምክር ቤት በዞኑ የወጣቶች እና የሴቶች እግር ኳስ ላይ ለመስራት የአምስት ዓመታት ስትራቴጂ በመቀየስ መንቀሳቀስ የጀመረው በ2014 እኤአ ፊፋ ባካሄደው 64ኛው ጠቅላላ ጉባኤ በተወሰነው ፕሮግራም መነሻነት  ነው፡፡ በመካከለኛውና ምስራቅ አፍሪካ ያሉ 12 አገራትን በአባልነት ያቀፈው የሴካፋ ምክር ቤት ፊፋ በነደፈው ፕሮግራም እና አቅጣጫ ለመስራት ስትራቴጂውን ነድፎ ቢንቀሳቀስም ውድድሮችን ለማዘጋጀት የአባል አገራቱ ፍላጎት ማነስ እና የስፖንሰሮች እጥረት እየተፈታተነው ይገኛል፡፡ በ2015 እኤአ የሴካፋ ሲኒዬርስ ቻሌንጅ ካፕ በኢትዮጵያ መስተናገዱ የሚታወስ ቢሆንም በቀጣይ ውድድሩን የሚያዘጋጅ አገር ጠፍቶ 2016 ላይ ላይካሄድ እንደሚችል ስጋት ተፈጥሮ ነበር።  ከዋናው የሴካፋ ሲኒዬር ቻሌንጅ ካፕ ባሻገር የምስራቅ አፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮና ካጋሜ ካፕ ፤ የሀ17 የሀ20 የእግር ኳስ  ሻምፒዮናዎችን ለማካሄድ በነበሩት እቅዶችም ሲቸገር ቆይቷል።  ይህ ሁኔታም በዞኑ የእግር ኳስ አስተዳደር ላይ ንትርኮችን እየፈጠረ ሲሆን፤ ዋንኛው ማስረጃም ምክርቤቱን በዋና ፀሃፊነት እና በተለያዩ የስራ ድርሻዎች ለ15 ዓመታት ሲያገለግሉ የቆዩት ኬንያዊው ኒኮላስ ሙንሶኜ ተጠያቂ ተደርገው ከሃላፊነታቸው ለማንሳት ዘመቻ በሩዋንዳ ፊት አውራሪነት መጀመሩ ይጠቀሳል። የሴካፋ ምክር ቤት አንዳንድ አባል አገራት ውድድሮችን ማካሄድ አስቸጋሪ እየሆነ መምጣቱ እና ስፖንሰሮችን ማቆየት አለመቻሉን  እንደ አስተዳደራዊ ድክመት በመቁጠር ዋና ፀሃፊውን  ኒኮላስ ሙንሶኜ እንዲባረሩ እየጠየቁም ነበር፡፡  ኒኮላስ ሙንሶኜ ከሴካፋ ምክር ቤት ከተሰናበቱ በኬንያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ፕሬዝዳንትነት ለመስራት ፍላጎት እንዳላቸው በአፀፋዊ ምላሻቸው ያስታወቁ ሲሆን ምናልባትም በኡጋንዳ አስተናጋጅነት የሴካፋ ሴቶች ሲኒዬርስ ቻሌንጅ ካፕ በተሳካ ሁኔታ መካሄዱ ህልውናቸውን እንደሚወስን እየተገለፀ ነበር፡፡ በኡጋንዳ አስተናጋጅነት ከሰላሳ ዓመታት በኋላ የሴቶች ሻምፒዮናው በስኬት መከናወኑን ተከትሎ  ግን የሴካፋ     ምክር ቤት አንዳንድ ውድድሮችን እነማን እንደሚያስተናግዱ  በይፋ አስታውቋል፡፡ዋና ፀሃፊው ኒኮላስ ሙንሶኜ ሰሞኑን በኡጋንዳዋ ከተማ ጂንጃ በሰጡት መግለጫ ኬንያ የ ሴካፋ ሲኒዬርስ ቻሌንጅ ካፕ እና የክለቦች ሻምፒዮና የሆነው ካጋሜ ካፕ በማከታተል እንድታስተናግድ መመረጧን እንዲሁም ኡጋንዳ የሀ17 ኻምፒዮናውን እንደምታዘጋጅ አስታውቀዋል፡፡ ኬንያ ሁለቱን ውድድሮች ለማዘጋጀት በምታደርገው ጥረት የሴካፋ ምክር ቤት ሙሉ ድጋፍ እንደሚኖርቃል የገቡት ዋና ፀሃፊው የውድድሮቹ መካሄጃ ሳምንታት በቅርብ ጊዜ ይወሰናሉ ብለዋል፡፡ የሁለቱ የሴካፋ ውድድሮች መቀራረብ በተለይ በብሄራዊ ቡድን እና በክለብ አሰልጣኞች በተጨዋቾች አስፈላጊነት ዙርያ ቅራኔዎችን እንደሚፈጥር የተሰጋም ሲሆን በተለይ ከአፍሪካ ሌሎች ውድድሮች ጋር የጨዋታ መደራረብ መኖሩ እያከራከረ ነው፡፡  የሴካፋ ሲኒዬር ቻሌንጅ ካፕ ሱዳን እንዲሁም የሴካፋ ክለቦች ሻምፒዮና ካጋሜ ካፕን ሱዳን ለማስተናገድ ተመርጠው እድሉን ሰርዘዋል፡፡ በ2016 የሴካፋ ሴቶች ሻምፒዮና ስኬታማ መስተንግዶ የነራት ኡጋንዳ በ2017 ደግሞ የዞኑን የሀ17 ውድድር እንደምታስተናግድም ይጠበቃል፡፡ ቀጣዩ የሴካፋ ሴቶች ሻምፒዮናን ማን እንደሚያዘጋጅ የተገለፀ ባይሆንም የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ይህን እድል ለመጠቀም መንቀሳቀስ ይኖርበታል፡፡

   የቀድሞው የብራዚል ፕሬዚዳንት ሉላ ዳ ሲልቫ ከታዋቂው የአገሪቱ የነዳጅ ኩባንያ ፔትሮባርስ 1.14 ሚሊዮን ዶላር በጉቦ መልክ መቀበላቸው በመረጋገጡ የቀረበባቸው የሙስና ክስ በፍርድ ቤት ተቀባይነት ማግኘቱንና በቅርቡ ፍርድ ቤት ይቀርባሉ መባሉን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
በ70 አመቱ ዳ ሲልቫ ከነዳጅ ኩባንያው ጋር የተጠቀሰውን ገንዘብ በጉቦ መልክ መቀበላቸውንና ኦኤኤስኤስኤ ከተባለው የአገሪቱ የኮንስትራክሽን ኩባንያ ጋር በተያያዘ የሙስና ወንጀል መፈጸማቸው በበቂ ማስረጃዎች መረጋገጡን የጠቆመው ዘገባው፤የዳ ሲልቫ ሚስትና ሌሎች ስድስት ግለሰቦችም በሙስና ወንጀሉ ተሳታፊ ናቸው መባላቸውንም ገልጧል፡፡
ዳ ሲልቫ ሶስት የሙስና እና አንድ የገንዘብ ማጭበርበር ክሶች እንደተመሰረቱባቸው ያመለከተው ዘገባው፤ የቀረቡባቸው ክሶች እያንዳንዳቸው ከ10 እስከ 16 አመት የሚደርስ የእስራት ቅጣት የሚያስጥሉ እንደሆኑም ጠቁሟል። ብራዚልን እ.ኤ.አ ከ2003 እስከ 2011 ያስተዳደሩት ሉላ ዳ ሲልቫ የቀረበባቸውን የወንጀል ክስ በመቃወም፣ የተባለውን የወንጀል ድርጊት በፍጹም አልፈጸምኩም፤ የውሸት ክስ ነው የተመሰረተብኝ በማለት ክደዋል ተብሏል፡፡
ፔትሮባርስ ከተባለው የአገሪቱ የነዳጅ ኩባንያ ጋር በተያያዘ የተፈጸመውንና በኩባንያው ባለአክሲዮኖችና በግብር ከፋዩ ህዝብ ላይ የ12.6 ቢሊዮን ዶላር ኪሳራ ያስከተለውን ከፍተኛ የሙስና ቅሌት በተመለከተ ላለፉት ሁለት አመታት ምርመራ ሲደረግ መቆየቱንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

    ነዋሪነቱ በአሜሪካ የሆነ አንድ የቴሌኮም ኢንጂነር ከሰሜን ኮርያ ከፍተኛ የመረጃ ተቋም ባገኘው ድንገተኛ መረጃ፣ በአገሪቱ አገልግሎት እየሰጡ የሚገኙ ድረ-ገጾች 28 ብቻ መሆናቸውን እንዳረጋገጠ ዘ ጋርዲያን ባለፈው ረቡዕ ዘግቧል፡፡
በአገሪቱ አገልግሎት በመስጠት ላይ ከሚገኙት ከእነዚህ ድረ-ገጾች አብዛኞቹ የመንግስት መስሪያ ቤቶችና በመንግስት ቁጥጥር ስር ያሉ መገናኛ ብዙሃን ናቸው ያለው ዘገባው፤ድረገጾቹ የመንግስት ፕሮፓጋንዳዎችን ከማሰራጨት ያለፈ ፋይዳ እንደሌላቸውም ገልጧል፡፡ ቢቢሲ በበኩሉ፤ ሰሜን ኮርያ ዜጎቿ የኢንተርኔት አገልግሎት እንዳይጠቀሙ መከልከሏን በመጥቀስ፣ በአገልግሎት ላይ ከሚገኙት ከእነዚሁ የአገሪቱ 28 ድረ-ገጾች መካከል አብዛኞቹ ዘገምተኛ ፍጥነት ያላቸውና ይዘታቸው ወቅቱን ጠብቆ የማይስተካከል እንደሆኑ ዘግቧል፡፡
በስራ ላይ ከሚገኙት የአገሪቱ ድረ-ገጾች መካከል አብዛኞቹ የአገሪቱን ፕሬዚዳንት ትርኪ ምርኪ የእለት ውሎዎች የሚያስነብቡ እንደሆኑ የገለጸው ዘገባው፤ሌላኛው ድረ-ገጽ ደግሞ የሰሜን ኮርያን ባህላዊ ምግቦች አዘገጃጀት የተመለከቱ መረጃዎችን የያዘ እንደሆነ አስረድቷል፡፡

 - ተቃውሞውን ያስነሳው መንግስት የክፍያ ጭማሪ ማድረጉ ነው

     የደቡብ አፍሪካ መንግስት በመጪው አመት የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ክፍያ እንደሚጨምር ማስታወቁን ተከትሎ ባለፈው ማክሰኞ ተማሪዎች ባደረጉት ተቃውሞ ውድመት መድረሱንና ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ኬፕታውንን ጨምሮ ሌሎች ታላላቅ የአገሪቱ ዩኒቨርሲቲዎች አገልግሎት መስጠት አቁመው መዘጋታቸውን ሮይተርስ ዘገበ፡፡
“መንግስት በክፍያ ላይ ጭማሪ ማድረጉ አግባብ አይደለም”፣ #ትምህርት በነጻ ሊሰጥ ይገባል” በሚል በአገሪቱ የተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ተማሪዎች ተቃውሞ ማድረጋቸውንና ብጥብጥ መከሰቱን ተከትሎ በተፈጠረው የጸጥታ ስጋት ሳቢያ፣ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ኬፕታውን፣ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ዘ ዊትዋተርስራንድ፣ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ፕሪቶሪያን የመሳሰሉ ተቋማት መዘጋታቸው ተነግሯል፡፡
የአገሪቱ መንግስት ባለፈው ሰኞ በቀጣዩ አመት በዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ክፍያ ላይ የ8 በመቶ ጭማሪ እንደሚያደርግ ማስታወቁን ያስታወሰው ዘገባው፤ይህ መግለጫ ያስቆጣቸው የአገሪቱ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ከፍተኛ ተቃውሞ ከማሰማት ባለፈ የዩኒቨርሲቲዎችን ንብረቶች በከፍተኛ ሁኔታ ማውደማቸውን ጠቁሟል፡፡  

የብሩንዲ መንግስት በዜጎቹ ላይ ግድያና አሰቃቂ ድብደባን ጨምሮ የተለያዩ አስከፊ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን እየፈጸመ እንደሚገኝ የጠቆመው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት፤ሁኔታዎች በዚህ ከቀጠሉ በአገሪቱ ዳግም የዘር ማጥፋትና እልቂት ሊከሰት እንደሚችል አስጠነቀቀ፡፡
የተመድ የሰብዓዊ መብቶች ምክር ቤት መርማሪዎችን ሪፖርት ጠቅሶ አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ እንደዘገበው፤ የአገሪቱ መንግስትና ተላላኪዎቹ በዜጎች ላይ የከፋ የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት እያደረሰ የሚገኝ ሲሆን በሺህዎች የሚቆጠሩ ዜጎች የግርፋት፣ የጾታዊ ጥቃትና የእስራት ሰለባ መሆናቸው ተረጋግጧል፡፡ የብሩንዲ መንግስት በዜጎች ላይ በሚፈጽመው የሰብዓዊ መብቶች ጥሰት ላይ ስር ነቀል ለውጥ ካላደረገና አለማቀፉ ማህበረሰብ ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶ ችግሩን ለመፍታት ካልሰራ አገሪቱ ወደማትወጣው የጥፋት አዘቅት መግባቷ አይቀሬ ነው ብለዋል፤የተመድ ባለሙያዎች፡፡
የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ በሚያዝያ ወር 2015 ለሶስተኛ ጊዜ በምርጫ እንደሚወዳደሩ ማስታወቃቸውን ተከትሎ በአገሪቱ ከፍተኛ ተቃውሞና ብጥብጥ መከሰቱን ያስታወሰው ዘገባው፤ የተመድ የሰብአዊ መብቶች ምክር ቤትም ባለፈው ወር በአገሪቱ የሚደርሱ የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን የሚያጣራ ቡድን ማሰማራቱን ጠቁሟል፡፡
ቡድኑ ከ277 የአገሪቱ ዜጎችና የሚመለከታቸው አካላት ጋር ባደረገው ቃለ መጠይቅና ማጣራት፣ ብጥብጡ ከተከሰተበት ጊዜ አንስቶ ከ1 ሺህ በላይ የሚገመቱ የአገሪቱ ዜጎች መገደላቸውንና ከ300 ሺህ በላይ የሚሆኑትም አገራቸውን ጥለው መሰደዳቸውን ማረጋገጡን አስታውቋል ብሏል ዘገባው፡፡ የብሩንዲ ፕሬዚዳንት ቃል አቀባይ ዊሊ ኒያሚትዌ በበኩላቸው፤ ተመድ ያወጣውን ሪፖርት ፖለቲካዊ አንድምታ ያለውና በተጨባጭ ማስረጃዎች ላይ ያልተመሰረተ በማለት እንዳጣጣሉት ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡
እ.ኤ.አ በ2006 በተጠናቀቀው የብሩንዲ የእርስ በእርስ ጦርነት ከ300 ሺህ በላይ የአገሪቱ ዜጎች ለሞት መዳረጋቸውንም ዘገባው አስታውሷል፡፡

     የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተልዕኮ ማስተማርና ጥናትና ምርምር ማካሄድ ነው፡፡ ጥናትና ምርምር ካላካሄድን ከ2ኛ ደረጃ በምን እንሻላለን? ይላሉ የአድማስ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሞላ ፀጋይ፡፡
አድማስ ዩኒቨርሲቲ የዛሬ ሳምንት ‹‹የትምህርት ጥራትና የዩኒቨርሲቲ ኢንዱስትሪ ትስስር›› በሚል ርዕስ በሳሮ ማርያ ሆቴል 10ኛውን ዓመታዊ ሀገር አቀፍ የጥናትና ምርምር ኮንፈረንስ አካሄዶ ነበር፡፡ በዚህ ኮንፈረንስ ላይ በተለያዩ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ የተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች ምሁራን 8 ጥናታዊና የምርምር ጽሑፎች አቅርበው ውይይት ተደርጎባቸዋል፡፡ የዩኒቨርስቲው ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሞላ ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር፤ ዩኒቨርሲቲው በመቶ ሺዎች የሚቆጠር ገንዘብ እየመደበ፤ በየዓመቱ ጥናትና ምርምር እንደሚካሄድ ገልጸው፣ ከዚህ ቀደም ዘጠኝ ዓመታዊ ሀገር አቀፍ ኮንፈረንሶች፣ አንድ ዓለም አቀፍ የምርምር ኮንፈረንስ፣ ስድስት የተማሪዎች የምርምር ሲምፖዚየም ማካሄዳቸውን ጠቁመዋል፣ ጥናትና ምርምር የሚያካሂዱት በራዕይና ተልዕኮአቸው በግልጽ በመስፈሩ፣ በአገሪቷ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የፖሊስ ምርመር ማካሄድን ግዴታ በማድረጉ ከፍተኛ የትምህርት ተቋማት የፈጠራ፣ የለውጥና የክህሎት ማበልጸጊያ ማዕከላት እንዲሆኑ በተቆጣጣሪ አካላት ከፍተኛ ትኩረት ስለ ተሰጠው እንደሆነ አመልክተዋል፡፡
የዘንድሮውን የጥናትና ምርምር ርዕስ፤ ‹‹የትምህርት ጥራትና የዩኒቨርሲቲ ኢንዱስትሪ ትስስር›› የሚል ርዕስ የያዘው ጉዳዩ የሕዝብና የመንግስት ከፍተኛ የትኩረት አቅጣጫ በመሆኑ ነው ብለዋል፡፡ ከኢንዱስትሪዎች ጋር ስላላቸው ግንኙነት ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ ሲመልሱ ከኢንዱስትሪዎች ጋር ያለን ትስስር በአንፃራዊነት ጥሩ ነው፡፡ ተቋሙ ከዩኒቨርሲቲው ጋር ያለው ትስስር ሲጎለብት ጠንከር ብሎ  ይታያል፤ ላላ ሲል ደግሞ ድክመቶች ይስተዋላል፤ ክፍተቶች ግን የሉም ማለት አይቻልም ብለዋል፡፡
ዩኒቨርሲቲው በዋናነት የሚሰጣቸው ኮርሶች በቢዝነስ ላይ ያተኮሩ እንደሆነ ገልጸዋል፡፡ አካውንቲንግ ፋይናንስ፣ ማኔጅመንት፣ ማርኬቲንግ፣ ሆቴል ማኔጅመንት፣ አይቲ፣ ኮምፒዩተር ሳይንስ መሆናቸውን ጠቅሰው፤ ኢንዱስትሪዎች በዚህ ሙያ ይህን ያህል ምሩቃን ላኩልን እያሉ ይጠይቃሉ፡፡ የብዙዎችንም ጥያቄ እኔ ስለምፈርም፤ በአሁኑ ወቅት ሰልጥኖ ሥራ ያልተቀጠረ ተማሪ ይኖራል ብዬ አልወስድም ብለዋል፡፡
ብዙ ጊዜ የምርምር ግኝቶች የኅብረተሰቡን ችግሮች ሲፈቱ አይታዩም፡፡ ዕጣቸው መደርደሪያ ላይ ሆኖ አቧራ መልበስ ነው፡፡ በዚህ ረገድ የእናንተ ጥናትና ምርምር ምን ያህል ወደ ኅብረተሰቡ ወርዷል? በማለት ጋዜጠኞች ላቀረቡት ጥያቄ ዶ/ር ሞላ ሲመልሱ፤ ‹‹ብዙ አሉ፡፡ ለአብነት ያህል በአንድ ወቅት ጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞች ያሉባቸው ችግሮች ምንድናቸው? በማለት ጥናት አካሄድን፡፡ በውጤቱም የዕቅድና የአመለካከት ችግር እንዳለ አመለከተን፡፡ ስለዚህ በአዲስ አበባና ዙሪያዋ ያሉ የጥቃቅንና አነስተኛ ኢንተርፕራይዞችን በማስታወቂያ ጠርተን ሥልጠና ሰጥተናል›› በማለት ገልጸዋል፡፡

 ቶታል ኢትዮጵያ ለ66 ዓመታት በአገሪቷ ሲሰጥ የቆየውን የኢነርጂ ንግድ ለማሳደግና ለማዘመን ባለው ፍላጎትና ባደረገው ጥረት በአገሪቷ በዓይነቱ የመጀመሪያ የሆነና ዓለም አቀፍ ደረጃ ያለው እጅግ ዘመናዊ የነዳጅና የጋዝ ዴፖ አሰርቶ ከትናንት በስቲያ አስመረቀ፡፡
ከአዲስ አበባ ከተማ በስተደቡብ ዱከም አካባቢ በ5.5 ሄክታር መሬት ላይ የተሰራው ዴፖ፤ 270 ሚሊዮን ብር የፈጀ ሲሆን 8 ሚሊዮን ሊትር ነዳጅና 200ሺህ ሊትር ፈሳሽ ቤንዚን የመያዝ አቅም እንዳለው ታውቋል። ሙሉ በሙሉ በኤሌክትሪክ የሚሰራው ዴፖው፤ ዘመኑ ያፈራቸው እጅግ ዘመናዊ የቴክኖሎጂ ውጤቶች የተገጠሙለት ሲሆን በታንኩ ውስጥ ያለው ነዳጅ ምን ያህል እንደሆነ የሚያሳየው መሳሪያ አውቶማቲክ ነው፡፡ የፈሳሽ ነዳጅ መያዣው ታንከር ድርብ ከመሆኑም በላይ ዴፖው አንዳች እክል ቢገጥመው የሚጠቁም (የሚጮህ) እጅግ ዘመናዊ አላርም ተገጥሞለታል፡፡ አንድ ቦታ ላይ ኤሌክትሪክ ቢበላሽ፣ ጋዝ ቢፈስ፣ እሳት ቢነሳ፣ ጪስ ቢፈጠር፣ ፈሳሽ የሃይድሮጂንና ካቦርን (ሃይድሮካርቦን) ቢፈስ አደጋ ከማስከተሉ በፊት ወዲያውኑ የሚጠቁም የኤሌክትሪክ ሲስተም ስላለው ከአደጋ የተጠበቀ ነው፡፡
የአካባቢ ብክለትንና የአሰራሩን ደህንነት የሚያረጋግጥ የርቀት መቆጣጠሪያ መሳሪያ አለው፡፡ ፕሮግራም ተደርጎ እንቅስቃሴዎችን መቆጣጠር የዚህ ዴፖ ልዩ ባህሪው ሲሆን፣ ለአጠቃቀም ቀላልና የዕለት ተዕለት እንቅስቃሴ የሆኑትን ደረሰኝ አጠቃቀም፣ ያለውን የክምችት መጠን፣ ወጪ የሆኑ ምርቶችን ለማወቅና የአደጋ ጊዜ ሁኔታን ምቹ መቆጣጠሪያ መሳሪያ መሆኑን ያመለክታል፡፡  
የእነዚህ በጣም ውድ የሆኑ የደህንነት መጠበቂያና መቆጣጠሪያ መሳሪያዎች መገጠም፣ ቶታል ኢትዮጵያ ለደህንነትና አካባቢን ከብክለት ለመጠበቅ ያለውን ከፍተኛ ቁርጠኝነት እንደሚያመለክት ለማወቅ ተችሏል፡፡ 

   ድምፃዊ ሙሉቀን ዳዊት፣ ቃቆ ጌታቸውና ብስራት ሱራፌል በጋራ ያቀነቀኑበት ‹‹መንገደኛ›› የተሰኘ አዲስ የሙዚቃ አልበም ለአድማጭ ቀረበ፡፡ ግጥምና ዜማው በዓለማየሁ ደመቀ፣ በሙሉቀን ዳዊት፣ በጃሉድና በብስራት ሱራፌል የተሰራ ሲሆን ሙዚቃውን ያቀናበረው ካሙዙ ካሳ ነው ተብሏል፡፡ ‹‹መንገደኛ››ን ጨምሮ 13 ዘፈኖች በአልበሙ መካተታቸውም ታውቋል፡፡ በፍቅርና በማህበራዊ ጉዳይ ላይ የሚያጠነጥኑ ዘፈኖች የሚቀነቀኑበት ይኸው አልበም፤ ቴክሼል የተሰኘ ድርጅት ፕሮዱዩስ ያደረገው ሲሆን ቮካል ሪከርድስ እያከፋፈለው እንደሚገኝ ድምፃዊያኑ ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡

   የገጣሚ ሄኖክ ስጦታው ሶስተኛ ስራ የሆነውና ‹‹መንገድ›› የተሰኘው የግጥም መድበል ገበያ ላይ ዋለ፡፡ ገጣሚው የተለያዩ የህይወት ፍልስፍናዎቹን ያሳየባቸው 64 ያህል ግጥሞች የተካተቱ ሲሆን በመፅሀፉ ጀርባ ‹‹ጠፈጠፍ›› በሚል ርዕስ ገጣሚ አበባ ብርሃኑ በማህበራዊ ጉዳይ ላይ የሚያጠነጥኑ ግጥሞቿን በጋራ አሳትማለች፡፡ በመቶ ገፅ የተቀነበበው መፅሀፉ፤ ለአገር ውስጥ በ49 ብር ከ60 ሳንቲም፣ ለውጭ አገራት በ15 ዶላር ለገበያ የቀረበ ሲሆን አከፋፋዩ ጃፋር መፅሐፍት መደብር ነው፡፡ ገጣሚ ሄኖክ ስጦታው በ1994 ዓ.ም ‹‹ነቁጥ››፣ በ2005 ዓ.ም ደግሞ ‹‹ሀ-ሞት›› የተሰኙ የግጥም መጽሐፍትን ለንባብ ማብቃቱ ይታወሳል፡፡

       ከ20 ዓመታት በላይ በሬዲዮ ጋዜጠኝነት፣ በሬድዮ ድራማና ትረካዎች ስራ ላይ የሚታወቀው በድምፁ ብዙዎች የሚያደንቁት ጋዜጠኛ ቢኒያም ደረሰ ድንገት በደረሰበት ትንታ ባለፈው እሁድ ህይወቱ ያለፈ ሲሆን ሰኞ እለት በገነተ ኢየሱስ ቤተክርስቲያን ጓደኞቹ፣ ወዳጅ ዘመዶቹና የሙያ አጋሮቹ በተገኙበት ሥርዓተ ቀብሩ ተፈፅሟል። ጋዜጠኛ ቢኒያም ደረሰ በተለይም በኢትዮጵያ ሬዲዮ የቅዳሜ መዝናኛ ላይ የሬዲዮ ድራማዎችን፣ ጭውውቶችንና ትረካዎችን በማቅረብ ይታወቅ ነበር፡፡  ጋዜጠኛው በባህሪው ጭምትና ሆደ ሰፊ እንደነበር የገለፀው ጓደኛው የፋና ሬዲዮ የመዝናኛ ፕሮግራም አዘጋጅ ጋዜጠኛ ደረጀ አያሌው፤ለስራ እንኳን ተፈልጎ እንደሚገኝና ብዙ ልታይ ልታይ እንደማይል አስታውሶ ብዙ ትኩረትና እድል በማጣት ሳንጠቀምበት ያጣነው ድንቅ ባለሙያ ነው ሲል ምስክርነቱ ሰጥቷል፡፡ ጋዜጠኛ ቢኒያም ደረሰ ላለፉት ሶስት ዓመታት በፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ይተላለፍ በነበረው ‹‹መሀል ቤት›› የተሰኘ ድራማ በመሪ ተዋናይነት ሰርቶ ማጠናቀቁንና አሁንም በፋና በሚተላለፈው ‹‹እኛን ነው ማየት” የተሰኘ ድራማ ላይ መሪ ተዋናይ ሆኖ እየሰራ እንደነበር ደረጀ ገልጿል፡፡ ቢኒያም ባለትዳርና የሁለት ሴቶች ልጆች አባት እንደነበር ለማወቅ ተችሏል፡፡