Administrator

Administrator

ሼክ መሀመድ አሊ አላሙዲ ለመቄዶኒያ አረጋውያንና የአዕምሮ ህሙማን መርጃ ማዕከል የትንሳኤን በዓል ምክንያት በማድረግ 16 ሚ. ብር ለገሱ፡፡ እርዳታውን ለማዕከሉ ያስረከቡት የሞሀ ለስላሳ መጠጦች ኢንዱስትሪ ስራ አስኪያጅ አቶ ጌታቸው ቢርቦ ሲሆኑ የተረከቡት ደግሞ የማዕከሉ መስራችና ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ቢኒያም በለጠ እንደሆኑ ታውቋል፡፡
ከርክክብ ስነስርዓቱ በኋላ የመቄዶኒያ መስራች አቶ ቢኒያም በለጠ ባደረጉት ንግግር፤ ሼክ አሊ አላሙዲ ከዚህ ቀደም እንደነ ደርባ ሲሚንቶ፣ ኒያላ ሞተርስ፣ የላይኛው አዋሽ አግሮ ኢንዱስትሪ፣ አዲስ ፓርክ፣ አዲስ ጐማ፣ ኤልፎራ፣ ኩዊንስ ሱፐር ማርኬትና ሚድሮክ አንሊሚትድ ፓኪንግ ፋክተሪ በመሳሰሉ ድርጅቶቻቸው በኩል ከ10 ሚሊዮን ብር በላይ መለገሳቸውን አስታውሰው፤ በሼኩ የተለገሱት አምቡላንሶችም ከ800 በላይ ተጨማሪ እርዳታ የሚፈልጉ ደካሞችን ከየጐዳናው ለማንሳት እንዳገዟቸው ተናግረዋል፡፡
አቶ ቢኒያም አክለውም መቄዶኒያ በአሁኑ ወቅት በማዕከሉ ከአንድ ሺህ በላይ አረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማንን እየረዳ መሆኑን ጠቅሰው ለዕለት ፍጆታ ብቻ በየወሩ ከ1ሚ. ብር እንደሚያወጣ ገልፀዋል። ከ300 ሚ.ብር በላይ ለሚያስፈልገው ማዕከል ግንባታ ማህበረሰቡ እያደረገ ያለውን ድጋፍ አድንቀው ድጋፉ ተጠናክሮ እንዲቀጥል የተማፀኑት መስራቹ፤ ሼክ አላሙዲ የለገሱት 16 ሚ. ብርም ለማዕከሉ ግንባታ እንደሚውል ተናግረዋል፡፡
የሞሃ ለስላሳ መጠጦች ኢንዱስትሪ ሥራ አስኪያጅ አቶ ጌታቸው ቢርቦ ባደረጉት ንግግርም፤ መቄዶኒያ እያከናወነ የሚገኘውን በጐ ተግባር አላሙዲን እንደሚያደንቁ ገልፀው ወደፊትም እርዳታቸው ከማዕከሉ እንደማይለይ ጠቁመዋል፡፡

Saturday, 07 May 2016 13:37

ይበለኝ በገዛ እጄ!

    ያዕቆብ ይባላል፡፡ ሙሉ ቀን መለሰ “ሰንደቅ ያሰቅላል”ን ለሴት ቢያዜመውም ያዕቆብን በሚገባ ይገልፀዋል፡፡ የአርባዎቹን አጋማሽ እየተሻገረ ቢሆንም ግርማ ሞገሱ፣ቅልጥፍናውና ሽንቅጥቅጥ ማለቱ ገና በሰላሳዎቹ ማለዳ ላይ ያለ ያስመስለዋል፡፡ ተምሯል፤የገንዘብም የዲግሪዎችም ሀብታም ነው፡፡ በአንድ አህጉራዊ ጉዳዮች ላይ በሚንቀሳቀስ ትልቅ ተቋም ውስጥ በኃላፊነት ደረጃ ይሰራል፡፡ ዘወትር ሙሉ ልብስ ግዴታው ነው፡፡ እንደሱ የሚያምርበትም አላየሁም፡፡ ታዲያ በዕረፍት ቀኖቹ ቀለል ያለ ልብስ ሲለብስ ሌላ ሰው ይመስላል፡፡ ልውጥ ይላል፡፡ባሌ ነው፤ የምወደው ባሌ፡፡ ምን ዋጋ አለው? ጥሎኝ ሄዷል፡፡ ሁለት ሳምንቱ … በገዛ እጄ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ጥሎኝ መሄዱን እንጂ ጠልቶኝ መሄዱን አላምንም፡፡ ጠልቶኝ ካልሆነ ደሞ ክዶኝ ሊሆን አይችልም፡፡ የጋብቻችንን ዘጠነኛ ዓመት ለማክበር የቀረንም ሁለት ሳምንት ብቻ ነበር … ዝግጅታችንን በጋራ አቅደን ጨርሰንም ነበር፡፡
“ካልሆነልን ለምን እንጨነቃለን አቡቲዬ” ውይ ቁልምጫው ሲጥመኝ….አበባ ብሎ ጠርቶኝ  አያውቅም፡፡
“ምንም አይሰማህም?”
“አልዋሽሽም … በቃ ማመን ካለብን ማመን ወይም ተማክረን አማራጭ …”
ቀለል ሲያደርገው ማን አክብጂው አለኝ … በገዛ እጄ!
ከዘጠኝ ዓመት በፊት ወደ ምሰራበት ግብረሰናይ ድርጅት ቢሮ መጣ፡፡ የኛን ድርጅት የሚረዱ … የውጭ ተቋማት ከነሱም ጋር ይሰራሉ፤ ተመሳሳይ ዓላማዎች ሲገጥሙን አብረን እንሰራለን፡፡ እኔ ደሞ የድርጅታችን ዋና ኃላፊ ነኝ፡፡ ወደ ቢሮዬ ሲገባ ዓይኖቼ ከቁጥጥሬ ወጥተው አጠር ያለች ቁመቴ ረዝማብኝ እየሳብኳት ብድግ ብዬ ተቀበልኩት፡፡ ዘንጣፋ ሰውነቱን እጥፍ አርጎ በአክብሮት ጨብጦኝ ተቀመጠ፡፡ ቢሮዬን እንደሱ የሞላው ሰው አልገጠመኝም፡፡ በግርማው ተጥለቀለቀች፡፡ ለስንትና ስንት ጥላ ቢሶች የሚተርፍ ግርማ፣ የቀልቤን መዝረክረክ ይወቅብኝ አይወቅብኝ እንጃ፡፡ እንደ ምንም የመጣበትን ጉዳይ ተነጋግረን ሄደ፡፡ ለሱ ነው የሄደው፤ ለኔ ቢሮዬ ነበር የዋለው፡፡
ጉዳዮች አመላለሱት፤ቀጥሎም እኔ ጉዳዩ ሆንኩና … ልቤ ላይ በድብቅ ስትንፈራፈር የነበረችውን የፍቅር ፅንስ ነፍስ ዘራባት፡፡
እኔን ድንገት ላየኝ ሰው፣ ክልስ ልመስለው እችላለሁ፡፡ “ቀይ ሰው መልክ አይፈጅም” ቢባልም ሳይጋነን ፈጅቻለሁ፡፡ ከ27 ወደ 28ኛ ዓመቴ በመሸጋገር ላይ ነበርኩ፡፡ አስጨናቂ የዕድሜ ዳገት ነው ለኛ ለሴቶች፡፡ ብዙ ወንዶች እንዳዩኝ ቢሸነፉም እኔ በቀላሉ አልሸነፍም፡፡ እየፈለግሁ እንኳን አይሆንልኝም፡፡ ዕውቀት፤ ስራ፤ ጥሩ ደሞዝ፤ ጥሩ ኑሮ አለኝ፡፡ ለእህቶቼ ተርፌያለሁ፡፡ በየመንገዳቸው ሄደው ርቀዋል … የእናቴን ድህነት ታሪክ አድርጌ ቀብሬዋለሁ፡፡
 ጎድሎኝ የነበረውን ያቆብ ሞላው … ስንላመድ እንደ ልጅ ያደርገን ጀመር፡፡ ያልኖርነውን እንደ መኖር … በኋላም ምርጫ አጣን፤ ከመጋባት በቀር፡፡ … በቃ አደረግነው፡፡ ተጋባን፡፡  በቅርብ ጓደኞቻችንና ወላጆቻችን ብቻ ታጅበን … በእማዬ “እልልታ” ደምቀን፣ “በወልዳችሁ ሳሙ” ምርቃት እየሰፈፍን ወደ ያቆቤ የሪል ስቴት ቪላ ገባን፡፡ ኑሮ ደመቀ … ጣፈጠ … ግን አልሞላም … ሁሉም ላይሞላ ቢችልም ደርበብ የሚያደርገው የእማዬ ምርቃት ሰሚ አጣ፡፡ በየወሩ ጠባዬን … ሆድ ሆዴን ትከታተላለች፡፡ ያቆቤም ይጠብቃል፡፡ ሁለት ጊዜ እያሳየ ነሳኝ፡፡ ደስታችንን ሳናጣጥም ጨንግፎ አጨነገፈን … ከዚያ በቃ ዝም ሆነ፡፡ እናቴም “ፈጣሪ ያልፈቀደውን እሷን ምን አርጊ እላታለሁ?” ብላ ነው መሰል ዝም …. እምምምም ብላ ቀረች፡፡ ያቆብም አመነ፡፡ ከዕውነቱ ጋር ታረቀ፡፡ እኔ ግን ጭንቀት የውስጥ ልብሴ ሆነ፤ከላይ ድምቅ ፅድት ውስጤ ግን …
ሰሞኑን ሃዘን ላይ ነኝ፤ ከፍራሽ ላይ ሳልወርድ እንባዬን ደብቄ አወርደዋለሁ፡፡ የሰርጋችንን ቪዲዮ ማየት የዘወትር ስራዬ ሆኗል፡፡ ያቺን ብርቅ ቀን፣ ያንን ድንቅ የፍቅር ሰው እያሰብኩ እንባዬ ሊያልቅ ነው፤ ሚዚዬ ሔዋንም የለችም፤ አብሮ አደጌ፣ ከራሴ እኩል ከማያቸው ሰዎች አንዷ ናት፡፡ ያሉኝም እነዚሁ ናቸው፡፡  እናቴ --- ያቆብ --- ሔዋን!!
… እናቴ የያቆቤን መጥፋት ማወቅ የለባትም፤ሌላ ህመም ይሆንባታል፡፡ በገዛ እጄ ራሴን ክፉኛ ቀጣሁት፡፡
“አቡቲ”
“ወዬ..”
“ራስሽን እያስጨነቅሽ ነው”
“ደህና ነኝ”
“እያየሁሽ …. ለምን በጉዲፈቻ አናሳድግም” ለስሜቴ እየተጠነቀቀ
“ከስራሽም ጋር ስለሚያያዝ….”
“እስኪ … አንድ የማሰላስለው ነገር አለ … እሱን …”
“ምንድነው አቡቲዬ?”
“ሰሞኑን እነግርሃለሁ”
ቢሮ ገባሁ አልገባሁ ለውጥ አልነበረውም፡፡ የስራ መንፈሴ ሸሽቶኛል፤ የአዕምሮዬም አቅም ተዳክሟል፡፡ ስልኩ ላይ መደወል መደወል … ዝግ ነው፤ ቢዚ ነው፤ ሊገኝ አይችልም …ይለኛል፡፡ አንዴ በመሃል ላይ ድምጹን ሰማሁት፡-
“ሃሎ አቡቲ” ጥሎኝ ሄዶም አቡቲ ማለቱ ገረመኝ፡፡
“ያቆቤ” ሳግ እየተናነቀኝ አወራሁት …
“ኬንያ ነኝ … ስመለስ እደውላለሁ” አጣድፎኝ ሥልኩን ዘጋው፡፡ ስራው ከሀገር ሀገር እንደሚወስደው አውቃለሁ፡፡ ሳይነግረኝ ግን የትም ሄዶ አያውቅም፡፡ ወደ ቢሮው ስሄድ መውጣቱን ይነግሩኛል፡፡ ዝም ብዬ ግራ ስጋባ ሰነበትኩ፡፡
ከጉዲፈቻው አማራጭ በፊት ያሰብኩትን ይዤ ሔዋን ጋ ሄጄ ነበር፡፡ እኩያዬ … ከወዲያኛው ጫፌ እስካለሁበት የምታውቀኝ፡፡ ቆንጆ ነች፤ደስ የምትል ቆንጆ፡፡ ትምህርት ዕጣ ክፍሌ አይደለም ብላ ሁለተኛ ደረጃን ጀምራ ትታዋለች፡፡ በማያዛልቁ ስራዎች ወጣ ገባ ስትል ወንዶች አዩዋት፡፡ ሁሉንም ነገር ቀድማን ነው ያደረገችው፡፡ ቸኩላ አገባች፤ ሁለት ወለደች፤ ሳይቆይ ባሏ በሞት ተለያት፡፡ ብዙም አላዘነችም፤ ኑሮዋንም አለስልሶላት ነበር ያለፈው፡፡ ወጣ ገባዋን ቀጠለች፡፡ የባሏ ዘመዶች በቅርብ ርቀት አዩዋት፤ ገመገሟት፡፡ በመጨረሻ “አንቺ ጥሩ ወላጅ እንጂ ጥሩ እናት አይደለሽም” ብለው ልጆቿን ወሰዱባት፡፡ ጭራሽ ተመቻት አማረባት፤ ተስማማት፤ ያለውን ወንድ የመረቧ ሲሳይ ማድረግ ሆነ ስራዋ፡፡
“ሔዊ ምን ይሻለኛል?” ስላት … እየሳቀች፤ “ወልጄ ልስጥሽ እንዴ?” አለችኝ፡፡ ደንታ የሌላት ናት፡፡ በላች ጠጣች፤ ይዛ ወደቀች .. በቃ ኖረች…
“እኔም ያሰብኩት …”
“አትቀልጅ …”
“ተመሳሳይ ነው ---” ልጅነታችንን … መወለድ ቋንቋ እንደሆነ ያየንባቸውን ዓመታት … ፍቅራችንን እያሰብኩ አማከርኳት …
የዛኑ ቀን … ማታ … መኝታ ክፍላችን ውስጥ … ክንዱን አንተርሶኝ ከሔዋን ጋር የተመካከርነውን ስነግረው … እመር ብሎ ተነሳና አየኝ፡፡ መቆጣት አይችልበትም፡፡ ሄዋንን  እንዳገኛት አይፈልግም ነበር፡፡ “አብሮ ማደግ አብሮ ማርጀት መሆን አለበት” ይለኛል … ሌላ ጊዜ ደሞ “ያኔ እኩል ነበራችሁ … አሁን ግን አይደላችሁም” እያለ ግንኙነታችንን ይቃወም ነበር፡፡
 እኔ ግን ሔዋንን እንደሱ ላያት አልቻልኩም፡፡ ላስረዳው ሞከርኩ፡፡ በማግባባት--- በመለመን --- ረታሁት፡፡
“የግድ ካልሽ … ይሁና” አለና ዞሮ ተኛ፡፡ በግድ ሳዞረው የቀይ ዳማ ፊቱ ላይ ጭንቀት፤ ፍርሃት፣ ግርምት … በየተራ እየበሩ ሲጠፉ አየሁ
ዛሬ አስራ ሰባተኛ ቀኑ ከጠፋ፡፡ አቅሜ ተዳክሟል፡፡ ስልኩ አይመልስም፤ ቢሮዬን ትቼ ወጣሁ፡፡ ባልደረቦቼ የሚያደርጉልኝ ጠፍቷቸው እንጂ ጭንቀቴ አስጨንቋቸዋል፡፡ መኪናዬ ራሷ ትምራኝ ደመነፍሴ እንጃ … ብቻ እየበረረች ነው፡፡ ያለ ቀልቤ መኪናዬን ዳር አውጥቼ ሳቆማት፣ ከፊቴ የማውቃትን መኪና ያየሁ መሰለኝ፡፡ ወረድኩ፡፡ አዎ የማውቃት መኪና ናት … ሰውነቴ ባንዳፍታ አልታዘዝ አለኝ፡፡
እግሬ እየመራኝ ጥቂት ተራመድኩ፡፡ የልጅነት ጓደኛዬ፣ሚዜዬ ቤት በራፍ ላይ ደረስኩ፡፡
ሳላንኳኳ በሩን ገፍቼው ገባሁ፡፡ ከደፉ ግን ማለፍ አልቻልኩም፡፡ ዓይኔን ማመን አቃተኝ፡፡ እውትና ቅዠት ተምታታብኝ፡፡ ቅዠት ቢሆንልኝ ተመኘሁ፡፡ ምኞቴ ግን አልሰመረም፡፡
የማፈቅረው ባሌ ያቆቤ----ከራሴ እኩል የማያት የልጅነት ጓደኛዬ ሔዋን---- አንድ ላይ የተሰፉ መስለዋል፡፡ ጠፍተዋል፡፡ አንጎሌ ለአፍታ ማሰብ ያቆመ መሰለኝ፡፡ ሁሉነገሬ ዝም አለ፤ጭጭ፡፡ “ሔዊ ለአንድ ቀን ከያቆቤ ጋር …” ብላት … የልጅነቴን ፀጋ … በረከቴን ሁሉ ነጠቀችኝ፡፡ በአንዲት ቀን ጦስ ባሌን በሞገደኛዋ ሔዋን ጭን ስር አስቀረሁት፡፡ ጓደኛዬንም ባለቤቴንም አጣኋቸው፡፡ ፊቴን አዙሬ ወደ መኪናዬ መራመድ ጀመርኩ፡፡ ያየሁት አስክሮኛል፤ አፌም አይኔም ደርቀዋል፡፡ እነሱ ግን ምን አጠፉ? የራሴ ጠላት ራሴ ነኝ፤ ሁሉም የሆነው በገዛ እጄ ነው፡፡ መኪናዬ ውስጥ ከገባሁ በኋላ እንዲህ የሚል ሃሳብ በግድ መጣብኝ፡- “ያንን ሁሉ ዓመት በኔ ደስተኛ አልነበረም ወይስ ከሁሉም ሾራ የምታሾረው ሔዋን ሌላ ተዓምር አሳየችው ?!”
ይበለኝ፤በገዛ እጄ ነው! የራሴ ጠላት ራሴ ነኝ !!







ዓለማቀፍ የፕሬስ ቀን ባለፈው ማክሰኞ ሚያዝያ 25 በሀገራችን የተከበረ ሲሆን በመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤት አዘጋጅነት በፍሬንድሺፕ ሆቴል የግማሽ ቀን
የፓናል ውይይት ተካሂዷል፡፡ በፓናል ውይይቱ ወቅት የሀገሪቱን የመገናኛ ብዙኃን ሁኔታ የሚዳስሱ ሶስት ጥናታዊ ጽሑፎች ቀርበው በሠፊው ውይይት ተደርጐባቸዋል፡፡
“የሚዲያ ብዝሃነትን ያከበረች ሀገር - ኢትዮጵያ” የሚል መሪ ቃል የተሰየመለትን የዘንድሮ የፕሬስ ቀን መነሻ በማድረግ፣ በተለይ በአገራችን ያለውን ተጨባጭ እውነታ
በተመለከተ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ የጋዜጠኝነት መምህራንን፣ የጋዜጠኛ ማህበራት አመራሮችን፣ ጋዜጠኞችን፣ ፖለቲከኞችንና ምሁራንን አነጋግሯል፡፡
ሃገሪቱ በመሪ ቃሉ ላይ እንደተጠቀሰው በእርግጥም የሚዲያ ብዝሃነትን ያከበረች ሀገር ናት? አስተያየት ሰጪዎቹ በጉዳዩ ላይ ሃሳባቸውንና ዕይታቸውን ሰንዝረዋል፡፡

“ብዝሃነት መሬት ላይ ያለን ሃቅ
ለመደፍጠጥ የዋለ ቃል ነው”
በ1920 እና 30ዎቹ ጆርጅ ኦዌል “1984” የተሰኘ መፅሃፍ ነበረው፡፡ በዚህ መፅሃፍ ውስጥ “ፖለቲካና ቋንቋ” በሚል ርዕስ ባሰፈረው ፅሁፍ፤ “መሬት ላይ ያለን የፖለቲካ ችግር በቋንቋ ለመሻገር መሞከር” ይለዋል፡፡ ቋንቋን በመጠቀም የተወሰነ ርዕዮተ ዓለማዊ ግብን መምታት ማለት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ያለውን የሚዲያ ሁኔታ ገምግም ከተባልኩ በሁለት መንገድ ነው የማየው፡፡ አንደኛው ክፍል ራስን ሳንሱር በማድረግ (ሰልፍ ሴንሰርሺፕ) ውስጥ ያለ ነው፡፡ ሰልፍ ሴንሰርሺፑ አንዳንዴ ከመንግስት ጫና በላይም ሊሻገር ይችላል፡፡ አሁን እያየነው ያለው ያንን ነው፡፡ ደርግና ኢህአዴግ የሚለያዩት እዚህ ላይ ነው፡፡ ደርግ በግልፅ አታድርግ ይልሃል፡፡ ኢህአዴግ የሴንሰርሺፕ ተቋም አላቋቋመም፤ ነገር ግን “ይሄን ካደረግህ ዋ ኮንትራት አንሰጥህም” ይላሉ፡፡ “ብዝሃነት” የሚለው ቃል እንግዲህ ቋንቋ ሰርቆ መሬት ላይ ያለን ሃቅ ለመደፍጠጥ የዋለ ቃል ነው፡፡ ከዚህ ውጪ ምንም አይገልፀውም፡፡ ይሄን ካልን ብዙም “ብዝሃነት አለ፣ የለም” የሚል ክርክር ውስጥ መግባት አይጠበቅብንም፡፡

              ዶ/ር ዳኛቸው አሰፋ
(የፍልስፍና ምሁር)

=========================================

“ሚዲያው የሃሣብ ብዝሃነትን
የሚፈራ ነው”

ኤልያስ ገብሩ
(የ“አዲስ ገፅ” መጽሔት ዋና አዘጋጅ)

የፕሬስ ብዝሃነት ማለት የተለያዩ አስተሳሰቦች የሚስተናገዱበት ማለት ነው፡፡ ኢህአዴግን ደግፎም ሆነ ነቅፎ መፃፍ መቻል ማለት ነው፡፡ ብዝሃነት ቃሉን እንዲሁ ለፕሮፓጋንዳ ተጠቀሙት እንጂ አሁን መሬት ላይ ካለው ሃቅ ጋር ፈጽሞ የማይሄድ ነው፡፡ እስከ ዛሬ እንደውም ሚዲያው የሃሣብ ብዝሃነትን የሚፈራ ሆኖ ነው የሚታየው፡፡ ኢቢሲን ብንመለከተው ለአንድ ወገን ወግኖ የሚሠራ ነው፡፡ የተለያዩ ሃሳቦችን የሚያስተናግድ አይደለም፡፡ በምርጫ ክርክር እንኳ ተቃዋሚዎች በጣት የምትቆጠር ደቂቃ ነበር የተሰጣቸው፡፡ ይሄ ኢህአዴግን በሃሳብ የበላይነት አሸንፈን ስልጣን እንይዛለን ለሚሉ ተቃዋሚዎች ምን ይጠቅማቸዋል? ራሳቸውን እንኳ ለማስተዋወቅ የማይበቃ ጊዜ ነው፡፡ ታዲያ እንዴት ነው የሚዲያ ብዝሃነት ተፈጥሯል ልንል የምንችለው? መንግስት ብዝሃነትን አስቦ ቢንቀሳቀስ ኖሮ፣ እነ እስክንድር ነጋ፣ እነ ውብሸት ታዬ፣ እነ ተመስገን ደሣለኝና የመሳሰሉ ጋዜጠኞች አይታሠሩም ነበር፡፡ በሃሳብ ብዝሃነት የሚያምን መንግስት ቢኖር ኖሮ፣ ፖለቲከኞች በየጊዜው እየታሠሩ ባልተፈቱ ነበር፡፡
አለማቀፍ ተቋማት የሀገሪቱን የፕሬስ ሁኔታ አስመልክቶ የሚያወጡት ሪፖርት መሬት ላይ ያለውን ሃቅ የሚገልጽ ነው፡፡ እኛም ሪፖርት እንስራ ብንል ከዚህ የተለየ አይሆንም፡፡ በሚዲያ ጉዳይ ጥናት የሚያደርግ የሀገር ውስጥ ተቋም ቢኖር፣ ከእነሱ የከፋ ሪፖርት ሊያወጣ እንደሚችል አልጠራጠርም፡፡ ዛሬ ጋዜጠኝነት የአደጋ ቀጠና ሆኗል፡፡ በሙያው ተመርቀው የሚወጡ ተማሪዎች እንኳ ወደ ሙያው መቀላቀል አደገኛ መሆኑን እያዩ እየሸሹ ነው፡፡

================================

“ሚዲያዎች በሞኖፖሊ ስር ነው ያሉት”
አቶ ወንድወሰን ተሾመ
(የኢትዮጵያ ነፃ ጋዜጠኞች ማህበር ፕሬዚዳንት)

  በየአመቱ የሚከበረውን የፕሬስ ቀን በፊት ያከብር የነበረው የኢትዮጵያ ነፃ ጋዜጠኞች ማህበር (ኢነጋማ) ነበር፡፡ እለቱ ታሣቢ የሚያደርገው የታሠሩትን የተሰደዱትን፣ በሙያቸው ጫና እያረፈባቸው ያሉትን ነው፤ መከበር ያለበትም ከዚህ አንፃር ነው፡፡ አሁን ሞኖፖሊ የሠፈነበት ጊዜ ላይ ነው ያለው፡፡ የግል ፕሬስ አለ ማለት የማይቻልበት ደረጃ ላይ እየተደረሰ ነው፡፡ ሞኖፖሊ ሲበዛ የሚዲያ ብዝሃነት የምንለው ነገር ይጠፋል፡፡ የግል ፕሬሶች በወረቀት ዋጋ መናርና በሌሎች ምክንያቶች እየተዳከሙ ነው፡፡ የኤሌክትሮኒክስ ሚዲያዎች በግል የተያዙ ያሉ ቢሆንም ብዝሃነት ያለው ሃሣብ የማንሸራሸር አቅም ሲፈጥሩ አልታዩም፡፡ በሞኖፖሊ ስር ነው ያሉት፡፡ በሙያቸው ጋዜጠኛ ሆነው የምናቃቸው ሰዎች፤ መንግስት በሌላ ጉዳይ ወንጀለኛ ሆነው አግኝቻቸዋለሁ በማለቱ አሁን በእስር ቤት የሚገኙ አሉ፡፡ መንግስት በዚህ ቀን እነዚህን ሙያተኞች ቢለቃቸው ምን ይጐዳል? እንደውም ክብር ያገኝበታል፡፡ የተከሰሱት በሌላ ቢሆንም እኛ የምናውቃቸው በጋዜጠኝነታቸው ነው፤ ቢለቀቁ በሙያው ላይ የራሳቸውን ድርሻ ያበረክታሉ፡፡ የመንግስትን ገጽታ በአለማቀፍ ደረጃ የሚያበላሸውና የተለያዩ ሪፖርቶች ላይ የሚንፀባረቀውም ይኼው ነው፡፡

==================================

“ሁሉም አመለካከቶችና ሃሳቦች የሚንፀባረቁበት እድል አልተፈጠረም”

አቶ አንተነህ አብርሃም
(የኢትዮጵያ ብሔራዊ ጋዜጠኞች ማህበር ፕሬዚደንት)
   የፕሬስ ቀን አከባበሩ ላይ እንድንገኝ ተጠርተን ነበር፤አልተገኘንም፡፡ ያልተገኘነው ክብር ስለነፈጉንና ስላዋረዱን ነው፡፡ አንደኛ፤ ተገቢውን እውቅና ነስተውናል፡፡ በበአሉ ላይ መጥታችሁ ቁጭ ትላላችሁ፤ከዚያ ሲያልቅ ትሄዳላችሁ ነው ያሉት፡፡ ስለዚህ ነው የተውነው፡፡ እኛ ተሳታፊዎች ብቻ መሆን አይገባንም፤ ባለድርሻዎች ነን፤ ንግግር ለማድረግ አስበን ነበር፡፡ እነሱ ግን እንደ ማንኛውም ሰው ትመጣላችሁ፤ የሚባለውን ሰምታችሁ ትሄዳላችሁ ነው ያሉን፡፡ እኛ ደግሞ ይሄ አምባገነንነት ነው፤አምባገነንነትን መሸከም አንችልም ብለናቸዋል፡፡ እኛ እስከ ዛሬ ከመንግስት ጋር በጋራ ስንሰራ ነበር፡፡ አሁን እኛን ከስርአቱ ጋር የማጋጨት ሥራ ነው የተሰራው፡፡ መንግስት በፊት ያደርግልን የነበረውን ድጋፍም አሁን እየነፈገን ነው፡፡ ድጋፍ ማድረግ አቁሟል፡፡ ለምን አቆመ? መንግስት ራሱ ነው የሚያውቀው፡፡ የፕሬስ ነፃነት ቀን አከባበር ላይም አያገባችሁም ተብለን ተገፍተናል፡፡  
ይሄ መገፋት ግን እኛን ለሀገራችን ከምናደርገው አስተዋፅኦ አያግደንም፡፡
አንዳንድ የመንግስት የስራ ኃላፊዎች፣ የመንግስትን አቋም አይደለም እያንፀባረቁ ያሉት፤ የራሳቸውን ነው፡፡ ወደ ርዕሰ ጉዳዩ ስመለስ፤ “የሚዲያ ብዝሃነት” ማለት የተለያዩ ሃሳቦችና አመለካከቶች የሚንሸራሸሩበት ምቹ ሁኔታ መፍጠር ማለት ነው፡፡
በዚህም ሁሉም እኩል የመናገር፣ የመደመጥና ሃሳቡን የማንፀባረቅ መብት ያገኛል ማለት ነው፡፡
 ከዚህ አንፃር ካየነው አሁን ላይ ሁሉም የዚህ እድል ተጠቃሚ ሆኗል ብዬ አላምንም፡፡ ሁሉም አመለካከቶችና ሃሳቦች የሚንፀባረቁበት እድል አልተፈጠረም፡፡ ይሄን ስል ክልከላ አለ ማለቴ አይደለም፤ ክልከላው ባይኖርም የበለጠ ሙሉ የሆነ ምቹ ሁኔታ መፍጠር ይቻል ነበር፡፡ አሁን ጭራሽ ያለውና የነበረው ነገር እየኮሰመነ ነው፡፡
በተወሰኑ የመንግስት ኃላፊዎች የሚፈለገው፣የጋዜጠኞች ማህበራት እንዲዘጉ ነው፡፡ ይሄ የመንግስት አቋም አይደለም፤የግለሰቦች ነው፡፡ ውይይት የሚፈልግ ጉዳይ ነው፡፡
 ውይይት እናድርግ ስንል ደግሞ ፍቃደኛ አይደሉም፡፡
እነዚህ ሁኔታዎች የአምባገነንነት አዝማሚያ ፍንጮች ናቸው፡፡ እነዚህን ሁኔታዎች ደግሞ እኛ ልንሸከማቸው አንችልም፡፡

================================

“ብዝሃነት ያለው ሚዲያ ቢኖርማ እኛም ባልተከራከርን”
ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ
(የመድረክ ሊቀመንበር)

  እኛም ከተያያዝናቸው የትግል አጀንዳዎች አንዱና ዋነኛው ሃሳብን በነፃነት የመግለጽ ጉዳይ ነው፡፡ ባለፉት የፖለቲካ ትግላችንም ለዚህ ስንከራከር ቆይተናል፡፡ ብዝሃነት ያለው ሚዲያ ቢኖርማ እኛም ባልተከራከርን፤ በዚህ ላይ ጊዜያችንን ባላጠፋን ነበር፡፡ ህገመንግስቱ የሚዲያ ነፃነት እንደሚከበር ደንግጓል፡፡ ነገር ግን ስርአቱ በጉልበት ህገ-መንግስታዊ መብቱን ገድቦታል፡፡ የፕሬስ ነፃነት ጉዳይ ዝም ብሎ የሚታይ አይደለም፡፡ አሁን ያለው ሁኔታ መቀየር አለበት፡፡ መሬት ላይ ያለው ሃቅና በመንግስት የሚነገረው የተለያየ መሆኑ የሚታወቅ ነው፡፡ አለማቀፍ ሪፖርቶችም በየጊዜው የሃገሪቱ የፕሬስ ሁኔታ አደጋ ውስጥ እንዳለ እንጂ በመልካም ሁኔታ ላይ መሆኑን አያንፀባርቁም፡፡ ጋዜጠኞች ጠንከር ብለው መንግስትን ሲተቹ፣ ሽብርተኛ ተብለው እንደሚታሠሩ እናውቃለን፡፡
ይሄን ሽሽት ጋዜጠኞች ያልተሰደዱበት የአለም ሃገርም የለም፡፡ ይሄ እንዲህ ባለበት ሁኔታ “የሚዲያ ብዝሃነትን ያከበረች ሀገር” ማለት የህዝብ ንቀት ነው፡፡

==============================

“በሌላው ሀገር መንግስት በፕሮፓጋንዳ አይፎክርም”

በፍቃዱ ኃይሉ (የዞን 9 ብሎገርና
የ“ውይይት” መፅሄት ዋና አዘጋጅ)

   በአገሪቱ የሚዲያ ምህዳር ውስጥ እየኖርኩበት ነው፤ዋጋም የከፈልኩበት ነው፡፡ ስለዚህ እኔ ከአለማቀፍ ሪፖርት ሳይሆን በዚህ መንገድ የሀገሪቱን የሚዲያ ምህዳር አውቀዋለሁ፡፡ “የሚዲያ ብዝሃነትን ያከበረች ሀገር - ኢትዮጵያ” የሚለውን መፈክር ስሰማ እንደ ስላቅ ነው የወሰድኩት፡፡ ፀሐፊዎቹ ራሳቸው አምነውበት የፃፉት አይመስለኝም፡፡ መፈክር ራሱ የፕሮፓጋንዳ ስራ ነው፡፡ በሌላው ሀገር መንግስት እንደዚህ በፕሮፓጋንዳ አይፎክርም፡፡ እኔ ከምኖርበት አንፃር ይሄን መፈክር ከስላቅ ለይቼ አላየውም፡፡ በምርጫ ማግስትና በምርጫ ዋዜማ ላይ የሚዲያዎች ቁጥር እኩል አይደለም፡፡ በምርጫ ዋዜማ ላይ ጠንካራ ፕሬሶች ይዘጋሉ፣ ይከሰሳሉ፣ ጋዜጠኞች ይሰደዳሉ፡፡ ይሄን በ2007 ምርጫ አይተነዋል፡፡ የፕሬሱ አስተዋፅኦ አስፈላጊ በሚሆንበት ሰአት ላይ በፍጥነት እንዲወገዱ ይደረጋል፡፡ ተፅዕኖ መፍጠር በማይችሉበት ወቅት ደግሞ ዝም ይባላሉ፡፡ በሀገሪቱ ያለው የሚዲያ ሃቅ ይሄ ነው፡፡ ይህም ሆኖ ዛሬ ከ10 ሺህ በላይ ኮፒ ያለው ጋዜጣ የለም፡፡ በየቀኑ የሚወጣ ጋዜጣ የለም፡፡ ሬዲዮ ጣቢያዎችም የግል ቢኖሩም ራስን በራስ በመመርመር የሀሳብ ተአቅቦ ያደርጋሉ፡፡ ፖለቲካ ሽሽት መዝናኛና ስፖርት ላይ ያተኩራሉ፡፡ ከዚህ አንፃር የሚዲያ ብዝሃነት ፅንሰ ሀሳብን ራሱ መንግስት በቅጡ የተረዳው አይመስለኝም፡፡


===============================

“የሚዲያ ብዝሃነት አለመኖር ለመንግስት ውድቀት ነው”

እንግዳወርቅ ታደሰ
(በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ፣ የጋዜጠኝነት መምህር)

ባለፉት 25 ዓመታት ፕሬሶች ቁጥራቸው አንዴ ይጨምራል፣ ሌላ ጊዜ ይቀንሳል፡፡ የመንግስት ሚዲያዎችን ካየን በቁጥር እየጨመሩ ነው፡፡ የብሮድካስት ዘርፍ በቁጥር ደረጃ ከፕሬሱ የተሻለ እየተስፋፋ ነው ማለት ይቻላል፡፡ ነገር ግን ለኛ ሀገር የሚያስፈልገን የሃሳብ ብዝሃነትን ሊያመጣ የሚችል ሚዲያ ነው፡፡ ከዚህ አንፃር የግል ፕሬስ በቁጥር ሊያድግ ይገባዋል፡፡ በብሮድካስቱ ከሚገኙ የግል ጣቢያዎች ውስጥ እንኳ መረጃ ከማግኘት አንፃር ግልፅ ልዩነት ይታይባቸዋል፡፡ ፋና ከመንግስት የሚያገኘውን መረጃ ያህል ሌሎቹ አያገኙም፡፡ ያሉትን ውስን የግል ጋዜጦችም ብንመለከት መረጃ አያገኙም፤ራሳቸውን በራሳቸው ሳንሱር የማድረግ ችግርም አለባቸው፡፡ የሃሳብ ልዩነት በሰፊው የሚያንሸራሽሩ ጋዜጦች እድሜያቸው አጭር ሲሆን አይተናል፡፡
በብሮድካስት በኩል እየበዛ ያለው በቁጥር እንጂ የተለያዩ አስተሳሰቦችን በማንፀባረቅ ደረጃ አይደለም፡፡ በየክልሉ የተመሰረቱ ብሮድካስት ሚዲያዎች ከኢቢሲ ጋር ተመሳሳይ ይዘት ነው ያላቸው፡፡ እንደኔ በቁጥር መስፋፋታቸው ጥሩ መስሎ የሚታየኝ፣ ስቱዲዮዎች ከመገንባታቸውና መሰረተ ሚዲያው ከመዋቀሩ አንጻር ነው፡፡ ኢቢሲን ነጥለን ብንመለከት ብሮድካስት ኮርፖሬት ሲሆን ራሱን እያስተዳደረ መንግስትን ሳይሆን ህዝብን እንዲያገለግል ተብሎ የተዋቀረ ነው፡፡ ግን አሁን ይሄን በተግባር እየሰራ ነው ወይ? የሚለውን መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ ከህትመት ሚዲያው፣ጠንካራ ጉዳዮችን የሚዘግቡት ከሁለት አይበልጡም፡፡ ይሄን ስናይ በቁጥርም በይዘትም ብዝሃነት አለው ለማለት እንቸገራለን፡፡ የሚዲያ ብዝሃነት ከሌለ ደግሞ መንግስት ድክመቶቹን መረዳት የሚችልበት አማራጭ አያገኝም፡፡ ይሄ ለመንግስት ውድቀት ነው፡፡ ብዝሃነት ስንል የሃሳብ ብዝሃነት እንጂ ቁጥር ላይ ካተኮርን ስህተት ነው፡፡ ለምሳሌ ተቃዋሚ ፖለቲከኞች በአሁን ሰአት ሃሳባቸውን የሚያቀርቡበት አማራጭ የላቸውም፡፡ ፕሬሱም የሚገባውን ያህል ቦታ እየሰጣቸው ያለ አይመስለኝም፡፡ በጥቂቱ የማየው አንዳንድ ጋዜጦች በተለያዩ ወቅታዊ ጉዳዮች ላይ ሲያወያዩዋቸው ብቻ ነው፡፡ ይሄ ጥቂትም ቢሆን የነሱን ሀሳብ ማግኘት ለሚፈልግ ህዝብ እጅግ ጠቃሚ ከመሆኑም በላይ መንግስት አቋማቸውን በተዘዋዋሪ እንዲረዳና ምክራቸውን የሚቀበል ከሆነ እንዲቀበል ይረዳዋል፡፡ በዚህ መንገድ ውስጥ ያሉ ፕሬሶች የሃሳብ ብዝሃነት ትርጉሙ የገባቸው ይመስለኛል፡፡ መንግስት በበኩሉ፤የሚዲያ ፖሊሲውን ልማታዊ ብሎ ጠቅልሎ ጨርሶታል፡፡


===============================


“ራስን በራስ ሳንሱር የማድረግ ችግር አለ”

ዶ/ር ነገረ ሌንጮ
(በአ.አ.ዩ.የጋዜጠኝነትና ኮሚኒኬሽን ት/ት ክፍል ዲን)

የአንድ ሚዲያ እድገት የሚለካው አንደኛ የተቋሙ ብቃት፣ የህግ ማዕቀፉ አሠሪነት ምን ያህል አሳታፊ ነው የሚሉት መታየት አለባቸው፡፡ የባለሙያ ደረጃውስ ምን ይመስላል የሚለውንም ማየት አለብን፡፡ ከፕሬስ ነፃነት ጋር ተያይዞ የሚነሳው የፖለቲካል ኢኮኖሚው ለሚዲያ የሚሰጠው ግምት ምንድን ነው የሚለውን ማየት ይኖርብናል፡፡ ከዚህ አኳያ የኛን ሀገር ስንመለከት፣ በኢትዮጵያ ውስጥ ስለ ሚዲያ ነፃነት መናገር ከጀመርን ሁለት አስርት አመታት ብቻ ነው ያስቆጠርነው፡፡
ስርአቱ ራሱ የሚዲያ ጉዳይን ህጋዊ አድርጓል፡፡ በህገመንግስቱም፣ በሚዲያ ህጐችም የሚዲያ ነፃነት ተደንግጓል፡፡ መረጃ ማግኘት የዜጐች መብት እንደሆነ፣ መንግስት ደግሞ ስልጣኑን የሚያገኘው ከህዝብ እንደሆነ ተደንግጓል፡፡ ይሄ እንዴት ነው ተግባር ላይ እየዋለ ያለው ስንል፣ የጋዜጠኞች ብቃትንና የሚዲያ ተቋማትን ጥንካሬ ይጠይቃል፡፡ በአተገባበሩ ላይ ክፍተቶች እንዳሉ የማይካድ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች ሁሉም ሃላፊነት ተሠምቷቸው በትክክል ይሠራሉ ብለን ብንጠይቅ፣ የሚሠሩም አሉ የማይሰሩም አሉ፡፡ ከመንግስት ባለስልጣናትም ህጉን በተገቢው የማያስፈጽሙ ይኖራሉ፡፡ በአለማቀፍ ሪፖርቶች፣መንግስት ሚዲያን ያፍናል የሚል ሪፖርት ይወጣል፡፡ እንደዚህ አይነት ችግር ሊኖር ይችላል፡፡ ነገር ግን በትክክል የጋዜጠኝነትን ሙያዊ መሠረቱን ጠንቅቀው አውቀው የሚሠሩት ናቸው የሚታሠሩት? የሚሰደዱት? ብለን መጠየቅ አለብን፡፡ እንደኔ ጋዜጠኞቹም መንግስትም ጋ ችግር አለ፡፡ አንዳንድ ጋዜጠኞችም ራሣቸውን በራሳቸው አላስፈላጊ ሳንሱር ያደርጋሉ፡፡ ይሄ ሲሆን ለህዝብ የተሰጠው መረጃን የማግኘት መብት ይጨፈለቃል፡፡ እኔ ችግር ያለው ከህገ-መንግስታዊ ስርአቱ አይመስለኝም፤የግለሰቦች ችግር ነው፡፡ ባለፉት 20 አመታት በእነዚህ ውጣ ውረዶች ውስጥ አልፎ የመጣ ፕሬስ እየተገነባ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡
“የሚዲያ ብዝሃነትን በእርግጥስ ያከበረች ሀገር ነች ወይ” የሚለው ጥያቄ፣ በኢትዮጵያ ይቅርና አደጉ በተባሉ ሃገሮች እንኳ “አዎ” እና “አይደለም” በሚል የሚመለስ አይደለም፡፡ ለምሣሌ መጽሐፍት የፈለጋቸውን ሃሳብ እያንፀባረቁ ይታተማሉ፡፡ አልፎ አልፎ ደግሞ ገደብ የሚጣልበት ሁኔታ አለ፡፡ ይሄ ተገቢ አይሆንም፡፡ የህዝብ ሚዲያዎች ላይ ሃሳብ ምን ያህል ብዝሃነት አለው የሚለውን ስናይ፣ ትንሽ ችግር አለ፤ተከልክለው አይደለም፡፡ የግለሰቦች ራስን በራስ ሳንሱር የማድረግ ችግር ነው፡፡ በመርህ ደረጃ ብዝሃነት ይኑር የሚል አመለካከት አለ፤ ይሄን ወደፊት በተግባር ማምጣት አለብን፡፡



በጥበባዊ ዝግጅት የታጀበ ነበር

    የዛሬ ሁለት ዓመት ከዚህ ዓለም በሞት የተለየው የአንጋፋው ደራሲ ስብሃት ገ/እግዚአብሔር 80ኛ ዓመት የልደት በአል በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ድህረ ምረቃ አዳራሽ ከትናንት በስቲያ በድምቀት የተከበረ ሲሆን በእለቱ ደራሲውን የሚዘክሩ ሰፋ ያሉ ኪነጥበባዊ ዝግጅቶች ተካሂደዋል፡፡
“ሌቱም አይነጋልኝ”፣ “ትኩሳት”፣ “7ኛው መልአክ”፣ “5፣6፣7” በተሰኙ ድርሰቶችና አዲስ አድማስን ጨምሮ በበርካታ ጋዜጦችና መፅሄቶች ላይ በመፃፍ የሚታወቀው ደራሲ ስብሃት ገ/እግዚአብሔርን የሚዘክረውን ዝግጅት ያስተባበረው ኢጋ ሚዲያና ኮሙኒኬሽን ሲሆን የሃሳቡ አመንጪ አቶ ደምሰው ኃይለሚካኤል ነው ተብሏል፡፡
በዝግጅቱ ላይ ስብሃት ለመጨረሻ ጊዜ ከፃፋቸው “እሴት ያለው ህይወት ኑር” የሚለውን ደራሲ እንዳለጌታ ከበደና ጋዜጠኛ ጌጡ ተመስገን ለታዳሚው አቅርበዋል፡፡ ስብሃት ገ/እግዚአብሔር ከአብዮቱ በፊት ምን ይመስል ነበር የሚለውንና ከወዳጆቹ ጋር ያለውን ግንኙነት የተመለከተ ፅሁፍ ፕ/ር ሽብሩ ተድላ ያቀረቡ ሲሆን ደራሲና ሃያሲ አለማየሁ ገላጋይ በበኩሉ፤ ስብሃት ከአብዮቱ በኋላ ምን ያስብ ነበር የሚለውንና የስብሃት አንዳንድ እውነታዎች በሚል አቅርቧል፡፡
የቀድሞ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር አቶ መሰረት አበጀ በስብሃት ስራዎች ላይ በተለይ በ“ሰባተኛው መልአክ” ላይ ዳሰሳዊ ፅሁፍ ያቀረቡ ሲሆን አቶ ሄኖክ በሪሁን ደግሞ “5፣6፣7”ን  በመድረክ ላይ ተውኖታል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ከዳር አገር ወደ ዋናው ከተማ የመጡ አዛውንት ለንጉሱ አቤቱታቸውን ለማቅረብ ከዙፋን ችሎቱ ዘንድ ተቀምጠው ተራቸውን ይጠብቃሉ፡፡
ባለሟሎች ስነ-ስርዓት እያስከበሩ ሁሉን በወግ በወግ ያስተናግዳሉ፡፡ አንዱ ሲጨርስ ሌላው ግባ ይባላል፡፡ በዚሁ ደንብ እኒያ የዳር-አገር መኳንንት ተራቸው ይደርስና ይቀርባሉ፡፡ ንጉሱ ገና ከሩቁ አውቀዋቸዋል፡፡ ጃንሆይ፤
“እህስ ምን ችግር ገጠመህና ከሩቅ አገር ድረስ ወደ እኛ መጣህ?”
አዛውንቱም፤
“ንጉሥ ሆይ! ከዚህ ከንጉሱ ከተማ እኛ ወዳለንበት ዳር-አገር ከሚመጡ ሹማምንት መካከል አንዱ ከብቶቹን በግፍ ነድተውብኛል … ያላግባብ ሰብሌን ወስደውብኛል፡፡ ሌላው ቀርቶ ለዘር ያወጣሁትን እህል እንኳ አልተውም፤ መዝብረውታል፡፡ እኔ ከላይም እግዚሃርን፣ ከታችም እርስዎን አምኜ የተቀመጥኩ አንድ ደሀዎ፣ በአገር አማን ይሄ ሁሉ በደል እንደምን ይደርስብኛል?”
ጃንሆይ፤
“ዕውን ይሄ ሁሉ በደል ደርሶብሃል? ለዚህ ዕማኝ አለህ?”
አዛውንቱ፤
“አዎን ጃንሆይ፤ አገር ይመሰክርልኛል፡፡ አገሩ ሁሉ ለእኔ ሲል አልቅሷል፡፡ “ነግ በኔ” እያለም ስጋት አድሮበታል፡፡
ጃንሆይ፤
“ይህ የሚለው ዕውነት ከሆነ በእርግጥ ተበዳይ ነውና ተጣርቶ ካሣ ይከፈለው፡፡ ግምቱ ተሰልቶ እህል ይሰጠው” አሉ፡፡
አዛውንቱ፤ ቀጠሮ ተሰጥቷቸው፣ እየተደሰቱ ወደ አገራቸው ተመለሱ፡፡ በቀጠሮአቸው መሰረት ወደ ንጉሱ አገር ተመለሱና ችሎት ቀረቡ፡፡ ባለሟሉ የአዛውንቱን የተጣራ ውጤት ለንጉሴ አቅርቧል፡፡
ጃንሆይ ተጣርቶ የቀረበላቸውን በጥንቃቄ ካዩ፣ ካስተዋሉ በኋላ፤
“ይህ ሰው በደል ደርሶበታል፡፡ ለመሆኑ ይሄን ያህል በደል ሲፈፀምብህ እስከዛሬ ለምን ዝም አልክ?” ሲሉ አዛውንቱን ጠየቁ፡፡
አዛውንቱም፤
“እኔማ ንጉሥ ሆይ! ‹ደንጊያና ቅል ተላግቶ፣ ዜጋና ሹም ተጣልቶ› አይሆንም ብዬ ነው፡፡ ሲብስብኝ በቀጥታ ወደ እርስዎ የመጣሁት፣ በየደረጃው መጎሳቆሉን ፈርቼ ነው፡፡ እርስዎ ባይደርሱበት ነው እንጂ ሹማምንቱን ያስደሰተ እየመሰለው እኛን ሱሪ ባንገት የሚያስወልቅ ስንት አዛዥ ናዛዥ አለ መሰለዎ?”
ጃንሆይ፤
“መልካም፤ ባለፈው እንዳልኩት በደሉ ተገምቶ ተመጣጣኝ እህል ይዞ አገሩ ይግባ” ብለው ፈረዱላቸው፡፡
ይህ በሆነ በሁለተኛውም፣ በሶስተኛውም ሳምንት አዛውንቱ ምንም ያገኙት ነገር የለም፡፡ የተፈረደላቸው ፍርድ አልተፈፀመላቸውም፡፡ ይቀርባሉ፡፡
ጃንሆይ፤
“ዛሬስ ምን ሆነህ መጣህ?” ይሏቸዋል፡፡
አዛውንቱ፤
“ዛሬም አልተፈፀመልኝም ጃንሆይ”
ንጉሡ ደግመው ትዕዛዝ ይሰጣሉ፡፡
ታዛዦቹ ሹማምንት “እሺ ጃንሆይ እናስፈጽማለን” ይላሉ፡፡ በተግባር ግን ምንም አይታይም፡፡
አዛውንቱ በመጨረሻ ንጉሱ ዘንድ ይቀርባሉ፡፡

ጃንሆይ፤
“እህ ምን ችግር ገጠመህ?” አሏቸው፡፡
አዛውንቱም፤
“ንጉሥ ሆይ! ዛሬስ አጋሰስ ልጠይቅ ነው የመጣሁት፡፡ ሁሉ ቀርቶብኝ፤ አንድ አሥራ አምስት ያህል አጋሰሶች ይሰጡኝ!”
ጃንሆይ፤
“ለምንህ ነው አጋሰስ የፈለግኸው?”
አዛውንቱ፤
“የሸዋን መኳንንት “እሺታ” ልጭንበት!” አሉ፡፡
***
የሀገራችን የአፈፃፀም ችግር የጥንት የጠዋት ነው፡፡ ህግጋት ይደነገጋሉ፡፡ መመሪያዎች ይወጣሉ፡፡ ማዘዝ ቁልቁለት ነውና ትዕዛዛት ይፈስሳሉ፡፡ ግን በተግባር ሥራ ላይ ውለው አይገኙም፡፡ በየእርከኑ ያሉ ጉዳዩ የሚመለከታቸው አካላት፤ ወይ ነገሩን ከጉዳይ አይጥፉትም፤ ወይ በግላቸው እንዳይፈፀም ይሻሉ፤ አሊያም ሥፍር ቁጥር የሌላቸው ምክንያቶች እየደረደሩ ባለጉዳይ ማጉላላታቸውን ይያያዙታል፡፡
ስብሰባዎች የኑሮ ዘዴ እስኪመስሉ ድረስ በተደጋጋሚ “ስብሰባ ላይ ናቸው”ን መስማት የተለመደ ሆኗል፡፡ ከአንድ ቢሮ ወደ ሌላ ቢሮ ጉዳይ የያዘ ፋይል ሲንፏቀቅ ይከርማል፡፡ ዳር የደረሰው ፋይል ደግሞ “ይሄ ይሄ አልተሟላም” ተብሎ ጉዳዩ መልሶ ጥሬ ይሆናል፡፡ የደከመው ባለጉዳይ እርም ብሎ ከነጭርሱ ነገሩን ይተወዋል፡፡ ያልታከተው ባለጉዳይ ሥራ ያቀላጥፍልኛል ወዳለው ሹም በአማላጅ ለመሄድ ይጥራል፡፡ ይሄ የባለጉዳይ መጉላላት እጅግ ሲደጋገም “ጉዳይ አስፈፃሚ” የሚል ታርጋ ያለው፤ በውል በ “ቢ ፒ አር” የማይታወቅ ማዕረግ ያነገበ፣ ሠራተኛ ፈጥሮ ቁጭ ይላል፡፡ ዛሬ በማናቸውም መሥሪያ ቤት ያለ ሥራ፣ ከተቋሙ ውጪ በሚኖር “ጉዳይ አስፈፃሚ” የሚተዳደር ይመስላል፡፡ የቢሮክራሲውን ቀይ ጥብጣብ (bureaucratic red tape) የሚበጥሱ ጉዳይ አስፈፃሚዎች” ናቸው፡፡ “ከእያንዳንዱ አሸናፊ ወንድ ጀርባ አንድ ሴት አለች” ይባል የነበረው፤ በዛሬው የአገራችን ሁኔታ፤ “ከእያንዳንዱ ስኬት ጀርባ አንድ ጉዳይ አስፈፃሚ አለ” የሚባልበት ወቅት ተፈጥሯል፡፡ አንዳንድ ውስጥ አዋቂዎች እንደሚሉት፤ በስሪያ ቤት ውስጥ ያሉ ሠራተኞች እርስ በርስ ሥራውን ለማሳካት “ጉዳይ አስፈፃሚ” ይፈልጋሉ ተብሏል፡፡
“ገንዘብ የደም ሥር ነው” የሚለው የጥንት አባባል፣ ዛሬ ዐይን ባወጣ መልኩ እንደ ዱላ ቅብብል ሥራ ማስኬጃ መሆኑ የአደባባይ ፀሐይ የሞቀው ጉዳይ ነወ፡፡
ከአንድ ቢሮ ጉዳይ ለማንቀሳቀስ ህጉ፣ ባለጉዳዩ የያዘው ገንዘብ ነው፡፡ ፀሐፊዋ ያለገንዘብ፣ ፋይል ለአለቃ አታቀርብም፡፡ በአንዳንድ አጋጣሚ በፈገግታ “ጉዳይህ ምንድነው” ለማለት ገንዘብ ትሻለች፡፡ አለቃዋ፤ አሉ የሉም፤ ለማለትም ገንዘብ ያስፈልጋታል፡፡ ጉዳይ ከተፈፀመ በኋላም ገንዘብ እንደማህተም የሚያገለግል የፋይሉ አካል ነው፡፡ ይሄን እንደምሳሌ ጠቀስን እንጂ ከተላላኪ እስከ ሥራ አስኪያጅ፣ ከዚያም እስከ ቦርድ ሰብሳቢ ድረስ፤ መላው ይሄ ሆኗል፡፡ እንግዲህ ይሄ አካሄድ “እየተሻሻለ መጥቷል” በተባለው የመልካም አስተዳደር ዘይቤ ውስጥ ያለ ነው፡፡ “ፍትሐዊ አሠራር እየሰፈነ ነው” በሚባልበት አገር ነው፡፡ “እጅህን እኩሬው ውስጥ ክተት፡፡ ወይ አሣ ታገኛለህ፤ ካልሆነም እጅህን ታጥበህ ትወጣለህ” ነው የትም ቦታ ያለው ሙስናዊ መርህ፡፡ አንዳንድ ሰፈር፤ “አለዛ (ያለገንዘብ) እንዴት ሥራ ይሠራል?” የሚለው አነጋገር የመጽሐፍ ቃል ይመስላል፡፡
አንድ ፀሐፊ እንዳለው፤ “የአፍሪቃ አማፂያን ድል ባደረጉ ማግስት ገንዘብ ማርባት ይጀምራሉ፡፡ ከዚያም ራሳቸው ይሰባሉ፡፡ በመጨረሻም ዕውነተኛው ግብ ራስን ማድለብ ይሆናል”፡፡ (At the end, the real goal becomes fattening oneself) ስለፈጣን ልማት እያወራን ፈጣን ስባት ውስጥ ከገባን፣ ልማቱን ወደ ፈጣን ጥፋት ለወጥነው ማለት ነው፡፡ በቪላዎች፣ በፎቆች፣ በመሬት ብዛት፣ በባንክ ደብተሮች ቁጥር ብዛት፣ በልጅ በዘመድ አዝማድ ውክልና ብዛት ወዘተ… በአጠቃላይ በግል ልማት፤ የአገርን ልማት ተክተን የምንንቀሳቀስ ከሆነ፤ ወሰን-የለሽ መንኮታኮት ገና ይጠብቀናል፡፡ እስር ቤቶች ያለጥርጥር ሞልተው ይትረፈረፋሉ፡፡ የሚገርመው፤ የሚሞሉት በጉቦ ተቀባይ ብቻ ሳይሆን በጉቦ-ሰጪም ነው፡፡ ዛሬ ዛሬ፤ ጉቦ-ተቀባዩ በምን መልክ መቀበል እንዳለበት ተጨንቆ ተጠቦ መላ የሚዘይድለት ራሱ ጉቦ-ሰጪው የሆነበት ደረጃ በመድረሱ ወደ ባህልነት ተሸጋግሯ፡፡ ጉዳይ አስፈፃሚው እንደ ህግ አማካሪ ማገልገሉም አይገርምም - የልምድ አዋላጅነት ፈጣን ገቢ የማከማቻ አቋራጭ ሆኗልና! በአቋራጭም ሆነ በረዥሙ መንገድ መንጋ በላተኛ ፈጥረናል፡፡ ደላሎቹ እንደሚሉት፤ “የሥራው ፀባይ ነው” ማለት በሙስናም ረገድ የማያሳፍር አባባል ነው፡፡ ትላልቅ ውሸቶች የጥቃቅንና አነስተኛ ውሸቶች መድብል ናቸው፡፡ አያሳፍሩም፡፡ ገንዘብህን የበላ፣ መሬትህን የበላ፣ ንብረትህን የበላ፤ አንተን ከመብላት ወደ ኋላ አይልም - “መብላት የለመደ ሲያይህ ያዛጋል” የሚባለው ለዚህ ነው!!

      ታዋቂው ሰዓሊ መዝገቡ ተሰማ የሰራቸው ትልልቅና አዳዲስ ስዕሎች፣ “የአዲስ አባ ልጅ” በሚል ስያሜ፣ ሐሙስ  በብሔራዊ ሙዚየም ለተመልካቾች ይታያሉ፡፡ምናባዊ ፈጠራንና ተዓማኒነትን ባጣጣመ ድንቅ የስዕል እውቀትና ክህሎት የላቀ የጥበብ ደረጃ ያሳየ አርቲስት እንደሆነ የሚነገርለት ሰዓሊ መዝገቡ፤ “ንግስ” በተሰጥኦ ትርኢት ያቀረባቸው  ስዕሎች ከፍተኛ አድናቆት አትርፈውለታል፡፡ በታሪክ ተጠቃሽ የሆኑ የስዕል ስራዎቹንና ምርጥ ችሎታውን ማሳየት የጀመረው ከ20 ዓመታት በፊት ቢሆንም፤ በየጊዜው የፈጠራና የችሎታ ምጥቀትን የሚመሰክሩ ስራዎች በማበርከት ይታወቃል፡፡ ከሁለት ዓመት በፊት “ንግስ” በሚል ስያሜ ያቀረባቸው ስዕሎች በበርካታ የሚዲያ ተቋማት መነጋገሪያ  ርዕስ ለመሆን የበቁትም፤ ስዕሎቹ በፈጠራ ሃሳብና በስዕል ችሎታ አዲስ ደረጃን ያሳያሉ በሚል ነበር፡፡ በርካታ ተመልካቾችን የማረከው ይሄው “ንግስ” የስዕል ትርዒት፣ እንደገና ለእይታ እንዲከፈት በተደጋጋሚ ሲጠየቅ የነበረ ሲሆን፤ የተወሰኑት ስዕሎች በአሁኑ ትርዒት እንዲካተቱ ተደርጓል፡፡ “የአዲስ አባ ልጅ” ለተሰኘው ትርዒት የተሰሩ  አዳዲስ የመዝገቡ ስዕሎች፤ ከወትሮው የተለዩ አይደሉም፤ እንደ ወትሮው በአዳዲስ የፈጠራ ሃሳቦችና በጥበብ ክህሎት  የተሰሩ ስዕሎች ናቸው፡፡ የፊታችን ረቡዕ ምሽት ተመርቆ ሐሙስ ለተመልካች የሚከፈተው ትርኢት 20 ስዕሎችን የያዘ ነው፡፡


“የኢትዮጵያ ባህላዊ መድኃኒትና ሕክምና የምዕተ ዓመት ጉዞ” የተሰኘ መጽሐፍ ሰሞኑን ለንባብ በቅቷል። መጽሐፉ በዐይነቱም ሆነ በጥልቀቱና በይዘቱ የተለየና የመጀመሪያው ነው የተባለ ሲሆን ለረጅም ጊዜ ተዘንግቶ የኖረውን የሀገረሰብ ህክምና ታሪክ በማጐልበት ረገድ ከፍተኛ ድርሻ እንዳለው ተገልጿል፡፡ አዘጋጁ ዶክተር ባልቻ አሰፋ ከተለያዩ የሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች በርካታ የቃልና የጽሑፍ ማስረጃዎችን፣ 63 ያህል የሀገረሰብ ህክምና ባለመያዎችን ቃለ ምልልሶችና ሌሎች በርካታ ግብአቶችንም ተጠቅመዋል፡፡ በ10 ምዕራፍ የተከፋፈለውና በ377 ገፆች የተቀነበበው መጽሐፉ፣ በ150 ብር ዋጋ ለገበያ ቀርቧል፡፡

Saturday, 30 April 2016 11:40

ተናዳፊ ግጥም

እንግዳ ነፍስ አዝላ
የበረከት በላይነህ “ተቃርኖ”
ምርጫና ሂስ ፥ ዕዝራ አብደላ

  በረከት በላይነህ  ከወጣት ብዕሮች በመነጠል በሶስት ዘርፍ -የሬድዮ ድራማ፥ ተውኔትና ሥነግጥም- የግሉን ፈር ቀዷል።  ለረጅም ጊዜ የተደመጠለት የሬድዮ ድራማ አለው፤ እንደ ጸሐፌ ተውኔት በስላቅ፥ በጉንተላ፥ በትዝብት ... ማኅበራዊና ፖለቲካዊ ጉዳይ በአንድ ተዋናይ ይመደረካል። ደራሲና ሀያሲ ዓለማየሁ ገላጋይ “እያዩ ፈንገስ”ን ከሮማኒያው ትያትር አነጻጽሮ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ ጽፏል፤ ያስተዋለው ያወያያል። “የ`እያዩ ፈንገስ` ባለታሪክ እውነታን በጤንነት ከማየት ሆን ብሎ ያፈገፈገ አሽሟጣጭ ነብይ ነው። ሳቅ እንጂ ሰው አልከበበውም። ስለ ጐረቤት ያወራል ጐረቤት የለውም። ስለ ደንበኛ ያወራል ደንበኛ የለውም። ስለ ሙሰኞች ያወራል ሱባኤ የሚገባለት የለውም።
እያዩ የዘመኑ ነብይ ነው። ቀልድ ታጥቋል፥ ቀልድ ሰንቋል። ቀልዱ ከአፎት እንደ ተመዘዘ ሰይፍ በሰው አንገት ላይ ያሽካካል። ከመሳቅ ግን አንታቀብም፤ እየሳቁ መሞት ዕጣ ፈንታችን ሆኖ ይሆን?” ]   
የበረከት ስላቅ በግጥም ሆነ በቃለ-ተውኔት ተራ አይደለም። “`ሁለት ዛፍ በሁለት ሺህ!` ይሉትን መፈክር በእኩል ድምጽ ሰምተው፤/ ጥቂቶች ሲተክሉ፥/ ብዙዎቹ ቆረጡ፥ ሁለት አስቀርተው።” [የመንፈስ ከፍታ፥ ገፅ 84] ክፋትና በጐነት ተማሰሉ። “የለቅሶ ቤት አዝማች” ግጥሙ ይህን እሳቦት ያባብሰዋል።
ገጣሚው መብሰክስክ ሲገባው የሚፈዝ፥ የሌላው እንግልት ሊያሳስበው ሲችል የሚገለፍጥ ተደራሲ አይመቸውም። ለንባብ፥ ለዕይታ ብቻ ሳይሆን ኑሮን በጥሞና አለማፍተልተል ያውከዋል። ይህን በብስለት“መራራቅ”  ባለቅኔን ይሻክረዋል።
ቅዠታም አዳሩን፥
ጨፍጋጋ ውሎውን፥
ዝብርቅርቅ ተስፋውን፥
በዩልኝታ ከፈን እየጠቀለለ፥
 ከጥርሱ ሲጥለው፤
ተቀባይ ይሻማል፥ ሳቅ እየመሰለው። [ገፅ 68]
በፋርስ አንጋፋ ገጣሚያን የመንፈስ ከፍታ የተደመመው በረከት፥ በአማርኛ ለዛ ውስጥ እየደፈቀ ዳግም ፈጠራቸው። የግል ግጥሞቹም ተናዳፊ ናቸው፤ እስቲ በአንዱ ብቻ አብረን እንመሰጥ።
-- ቁጥር 8 --
[ተናዳፊ ሥሩ ነደፈ ነው። ተሰማ ሀብተ ሚካኤል ሲተረጉሙት የቃሉ ጨረር አይመክንም። (ገጽ 667) “ ንብ ነደፈ፥ በመርዙ ጠዘጠዘ ወጋ ጠቀጠቀ ” ወይም “ በፍቅር ተነደፈ ተያዘ ተቃጠለ ” እንዲሁም“ ባዘቶውን አፍታታ በረበረ ” ..... ግጥም ለጭብጡ፥ ለስንኝ አደራደሩ ወይም ለቋንቋው ምትሀት ምናባችንን ከቧጠጠ ተናዳፊ ነው፤ አንብበነው የምንዘነጋው፥ ጥፍሮቹ የተከረከመው ግን ኢ-ግጥም ነው።]
     ተቃርኖ
ያልሰማችው ጥሪ ያልገባት ብዛቱ
የሽሽቷ ጥጋት ያልገባት `ርቀቱ፤

ከትላንት በሚሸሽ አይደክሜ ሶምሶማ፤
ግለኛ ተስፋዎች ስታሳድድ ከርማ፤

ትዝታን በረሳ ጥድፍድፍ በረራ፤
አጥር-አልባ ድንበር ስታካልል ኖራ።
ድንገት!
`ያ ሳቋ` የሌለበት፥
`ያ ዕንባዋ` የሌለበት፥
`ያ ጐኗ` የሌለበት፥ እንግዳ ነፍስ አዝላ፤
እጆቿን ዘረጋች፥ “ተቀበሉኝ” ብላ።

ዝም አላት መንደሩ፤
አኮረፈ አድባሩ፤
ፊት ነሳት ሀገሩ።

ይብላኝ ለእሷ አይነቶች!
የቤት ጥሪ ንቀው መጓዝ ለወደዱ፤
የመጡ መስሏቸው፥ ርቀው ለሄዱ፤
ለጭፈራ መጥተው፥ ሙሾ ለወረዱ።
------------------------------------
     © በረከት በላይነህ
     [ የመንፈስ ከፍታ፥ ገፅ 86]

ተናጋሪው ስለ አንዲት እንስት እየወቀሳት ያወጋል። ገለልተኛ ታዛቢ ወይም ለገፀባህሪዋ የሚያደላ አይደለም፤ በመከፋት ድምፀት ታፍኗል። በአስራ ስምንት ስንኞች፥ በስድስት አንጓ የተቀረፀው ግጥም ለቆምታ እንጂ ለጥድፊያ ያዳልጣል። ከግጥሙ የፈለቀ የስንኞች ንዝረተ-ዜማ፥ ስሜት እየለጠጠ ያረግባል። ትሸሻለች፥ ተመልሳ ትመጣለች። ያልሰከነ መዋከብ አለ እንጂ፥ የእንስቷ ድምፅ አይሰማም። ተናጋሪው እንደ ጥፋተኛ ይኰንናታል። ግጥሙ እንደ ርዕሱ “ተቃርኖ” የሚፋለሱ ሁነቶች ተርመሰመሱበት። “የመጡ መስሏቸው፥ ርቀው ለሄዱ” ሲል ጉዞው አካላዊ ብቻ ሳይሆን ምኞታዊም ነው። ከሄደችበት ርቀት አቀርቅራ ወይም ደንዛ ብትመለስም ገላዋ እንጂ ልቦናዋና ስሜቷ እንደ ባይተዋር ጉዞ ላይ ናቸው ማለቱ ይሆን? “አጥር-አልባ ድንበር፥ ስታካልል ኖራ” መፋለስን ያባብላል። አካለለ አንድም አዋሰነ ነው፤ አንድም ብዙ ቦታ ዞረ ነው። የሀገር ድንበር ከሆነ በዘብ ይጠበቃል፤ የቤት ከሆነና አጥር-አልባ ከተባለ ማንም ይመላለስበታል። ጥረቷ፥ ልፋቷ የመከነባት መሰለ።
“ያልሰማችው ጥሪ፥ ያልገባት ብዛቱ” ሲል፥ ተናጋሪውን ምን ያክል እንመነው? ገብቷት ከሆነስ? ብዙሃኑን ማድመጥ ታክቷት አንዳች የምትሾልክበት ሰርጥ ስታስስ ከሆነስ? “የሽሽቷ ጥጋት፥ ያልገባት ርቀቱ” ሲል ይህ ስንኝ የነከሰው ምስል አይዳኝም። አልተመቻትም ወይም ርዕይና ህልም ፋታ አልሰጡዋትም። ያልፍልኛል ብላ ኮከብ ተከትላ የምትጓዝ ሣይሆን የትም ይሁን ብቻ ተፈትልካ የሆነ መወሸቅያ ስፍራ ታፈላልጋለች። ያልሰማችው ጥሪ ምንድነው? ከምንስ ነው እንዲህ የምትሸሸው? ተናጋሪው ፍርጥ ያደረገው ምክንያት የለም። አሻሚነት -ambiguity- ብቸኛ አንድ ትርጉም አይደምቅበትም። ለጥቂት ፍካሬዎች የቋጠረው ሰበዞች ይመዘዛሉ። አሻሚነት ግጥምን ጥልቀት ይለግሰዋል። ግጥም ግን ሲያነቡት የማይገባን፥ የማይለዝብ የተድፈነፈነ ከሆነ ይህ ደብዛዛነት -obscurity- ጥበባዊ ጣዕሙን ያቸከዋል፤ ለግጥም ጠንቅ ነው። ይህ የበረከት በላይነህ “ተቃርኖ” አሻሚ ነው ደብዛዛ? ጥሬ ቃላት፥ የነተበ ሀረግ ሆነ ስንኝ ስላልተሰገሰገ ቋንቋው ይመስጣል። የተናጋሪው ስሜት፥ ስለ ሴቷ የሰቀዘው እኩይ ግምትና የእሷ አለመስከን ያልገታው እንቅስቃሴ፥ ለድርጊቶች “ምንም” ምክንያት አለመገለጡ ወደ ደብዛዛነት ያስጐነብሰዋል። የውጭ ሁኔታዋን እየተረከ ተሳለቀባት እንጂ ለማኅበረሰቡ ጀርባዋን አዙራ፥ ጆሮዋን ደፋፍና ሌላ መሸሸጊያ፥ የሩቅ ከለላ ሳትታክት ለምን ትቃብዝ ነበር? ለምንስ “ግለኛ ተስፋዎች” ከኅላዌ ለመንጠቅ መንጠራራቷ አስወቀሳት? ለነዚህ መልስ የለንም።
 ተናጋሪውን እንዴት እንመነው? ከልጅቷ ነፍስ መብከንከን ተፈናጥሮ፥ በአጠቃላይ ጉዳይ ትረካውን ደመደመው። “ይብላኝ ለእሷ አይነቶች!/ የቤት ጥሪ ንቀው፥ መጓዝ ለወደዱ፤”  ሲል ሁሉንም አንድ ቅርጫ ውስጥ አጐራቸው። እነኚህ ሁለት ስንኞች የግብረገብ አቋም ሆነው፥ ለግጥሙ ሰንኮፍ አክለው የግለሰቧን ማኅበራዊ እንግልት አድበሰበሱት።
እንስቷ ማኅበረሰቡን መምሰል በነሱ መመራት ያልፈቀደች ናት። የ Ionesco “አውራሪስ” ተውኔትን ታስታውሰኛለች። ለዕውነታዊ ትያትር ብቻ ይታደም የነበረን ተደራሲ፥ ከእሳቦት ይልቅ ወደ ህልም ወደ ታህተ-ንቃት subconcious ሰዋዊ ቅዠት እንዲመጣ ካለማመዱት ጸሐፍተ ተውኔት አንዱ ፈረንሳዊ Ionesco ነበር። የአንድ መለስተኛ ከተማ ነዋሪዎች ተራ በተራ ወደ አውራሪስ ይለወጣሉ። አብይ ገፀባህሪ ብቻ ነው አልታዘዝ ብሎ ሰው ሆኖ የቀረው። ለማኅበረሰቡ ጥያቄ አልገዛ ብሎ ከጀማው ያፈነግጣል። ብቻውን ስለቀረ፥ ኅላዌውን መጠራጠር ጀመረ -- ቋንቋውን፥ ሰው መምሰሉን፥ አእምሮውን ጭምር። የ“ተቃርኖ” እንስት እንደ ግለሰብ ስለአፈነገጠች፥ ለመንደሩ ነዋሪ ጥሪ፥ እምነትና ፍላጐት አልዳኝ ማለቷ ተናጋሪውን ኮሰኮሰው። ልክ በአንድ ወቅት ያፈቅራት የነበር፥ የግል ንብረቱ እንድትሆን መረቡን ቢዘረጋላትም ሾልካ ያመለጠች ይመስል ቂም ቋጠረ። ችላ ብላው ሌላ ፍለጋ መቃተቷ የጐዳው ተናጋሪ፥ የቆሰለ ማንአህሎኝነት ለማስታገስ አበሻቀጣት እንጂ ገጣሚው እቺን እንስት ሲቀርፃት ረቀቀ። ወንበር ላይ ተኮፍሳ ከመማቀቅ፥ ለስሜቷ ለህልሟ ተስፋን ለማባበል ሸፈተች፥ ተጓዘች። ከመንደሯ ውጭ ከራርማ ተመለሰች።
ድንገት!
`ያ ሳቋ` የሌለበት፥
`ያ ዕንባዋ` የሌለበት፥
`ያ ጐኗ` የሌለበት፥ እንግዳ ነፍስ አዝላ፤
እጆቿን ዘረጋች፥ “ተቀበሉኝ” ብላ።

ዝም አላት መንደሩ፤
አኮረፈ አድባሩ፤
ፊት ነሳት ሀገሩ።
እጅጉን ተለውጣ ተመለሰች። እንደ ማንም ትስቅ፥ ታለቅስ የነበረች ጭምት ብቸኛ (ያለ ጐኗ?) ሆና ዘመድ፥ መንደሬ ብላ ተንደረደረች። እጆቿን ብትዘረጋም፥ ገላመጧት እንጂ አላቀፏትም፤ አሁንም እንደ አቄሙ፥ እንደ አኮረፉ ናቸው። እመጫት ሆና ጨቅላ አዝላ ተመልሳለች የሚያሰኝ አንድምታ ቢኖርም፥ በአራስ በማይድህ ህፃን ወግ አጥባቂው ባህል አይጨክንም። ይልቅ ያለ ሳቋ፥ እንባዋና ጐኗ “እንግዳ ነፍስ አዝላ” ሲል ስለ ማንነቷ ነው። የሆነ የርዕይ መነጠቅ፥ ሽንፈት የመሰለ ገፅታ፥ ይህን ነፍሷን አዝላ አስጠጉኝ ያሰኛት ጉጉት አንድምታው ያደናግዛል። ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራ ለደበበ የተቀኘው ግጥም ይወክላታል።
አንተን በእኔ ውስጥ አየሁት፤
ዘመንን አኩርፎ፥
በራፉን ቆልፎ፥
ካንዲት ቀሪ ወዳጁ፥ ከነፍሱ ተቃቅፎ።
[እውነት ማለት፥ ገፅ iv]
በረከት በላይነህ “ተቃርኖ” ሲል የእንስቷ የተፋለሰ ድርጊትን ለመግለፅ ያኮማተረው ርዕስ አይደለም።
 ግለሰቧ የተወሳሰበች ፍጡር ብትሆንም ተናጋሪው ሊገነዘባት አልቻለም። ገጣሚው የነዘረው በገፀባህሪዋና በተናጋሪው መካከል በተሰነጠቀ ተቃርኖ ነው።
 እንደ Frued አባባል “Neurosis is the inability to tolerate ambiguity” የሰውን አሻሚ ባህሪያት፥ የግለሰብን ውስብስብነት መታገስ አለመቻል ማለት የሚደብት የአዕምሮ በሽታ ነው እንደማለት። ይህ ኑሮሲስ ተናጋሪ ነው ያመፀች፥ ከመንደሯ ውጭ ከራርማ፥ ተስፋን ከየጥሻው ስር ስትቃርም ተግታ፥ ድንገት ስትጨምት በረገገ። እሱ ለገፈተራት፥ እሱ ለገረመማት መንደር፥ ሀገርና ታቦት እሱን እንዳገዙት ቆጠረው። እምብዛም በአማርኛ ሥነግጥም ያልተለመደ ተራኪና ገፀባህሪ የተገፈታተሩበት ግጥም ነው በረከት በላይነህ ያስነበበን። በረከት ይህን “የምኞት ቅኔ” ይለዋል።
ከሰኞ እስከ እሁድ፥
ከመስከረም ጷጉሜ፤
የትኛው ነው ኑሮ?
የትኛው ነው ዕድሜ?
[ገፅ 83]
 ግራ ቀኝ ገላምጣ ድባቡ ሲጨፈግግባት፥ ለኑሮ ይሁን ለፍቅር ጉዳይ ያመፀች እንስት ልንስገበገብላት ይገባል። ግን ነገረኛ ሰው አለ፡፡ ጐረቤትና መንደርተኛ አይንሽ ላፈር እንዲሏት የሚቀሰቅስ፤ ይህ ተቃርኖ የኅላዊ አንኳር ጠባይ ነው።                * * *


   ከዕለታት አንድ ቀን መልኩ ወደ ቁራ የሚሄድ አንድ ጥቁርና ነጭ ዥጉርጉር ወፍ በአንድ ጫካ ውስጥ ይኖር ነበረ፡፡ በእርሻ ማሳው ውስጥ የሚያማምሩ ነጫጭ እርግቦች እየተመገቡ፣ ብር ትር እያሉ ሲጫወቱ አየ፡፡ ከወፋፍርነታቸው መልካም ተመግበው እንደኖሩ ያስታውቃሉ፡፡ የገላቸውና የላባቸው ንጣት ዐይን ይስባል፡፡ ያ ዥጉርጉር የቁራ ዝርያ የሆነ ወፍ እጅግ አድርጐ ቀና፡፡
“ምነው እኔም መልኬ እንደነዚህ እርግቦች ሙሉ በሙሉ ነጭ በሆነ ምነው… ምን በድዬ ነው እኔን አምላክ አስቀያሚ ዥጉርጉር አድርጐ የፈጠረኝ?” ሲል አማረረ፡፡
ጥቂት ቆይቶ ግን አንድ መላ መጣለት፡-
“ቆይ እኔስ እንደ እርግቦቹ ለመሆን ምን ያንሰኛል? ሙሉ ለሙሉ ከእግር እስከ አናቴ ነጭ ብቀባና ከነሱ ብቀላቀልኮ እንደነሱ እበርራለሁ፤ እንደነሱም እመገባለሁ፡፡ እንደነሱም አምራለሁ” አለ፡፡
እንዳሰበው ሙሉ ነጭ ተቀባና እንደ እርግቦቹ መሰለ፡፡ ሄዶም ከእርግቦቹ ጋር ተቀላቀለ፡፡ ምንም ድምጽ ሳያሰማ፤ በሰላም ከእርግቦቹ ጋር መቀገሩን ተያይዘው፡፡ ለጥቂት ጊዜም ደስተኛ ሆነ፡፡
አንድ ቀን ግን ያልታሰበ ነገር ተከሰተ፡፡
“እስከ መቼ ዝም ብዬ እዘልቀዋለሁ፤ እኔም ከነሱ ጋር መጫወት አለብኝ፤” ብሎ በራሱ ቋንቋ ሊያናግራቸው ሞከረ፡፡
እርግቦቹ እስከ ዛሬ ሲያጭበረብራቸው እንደከረመ ነቁበት፡፡ በጋራ ይጠቀጥቁት፤ ይተከትኩት ገቡ፡፡
“አንት ወስላታ አጭበርባሪ! ያለቦታህ መጥተህ እስካሁን አታለልከን! ሂድ ድራሽህ ይጥፋ! ወገኖች ህጋ ተቀላቀል!” ብለው አባረሩት፡፡
ዥጉርጉሩ ወፈ አዝኖና ተስፋ ቆርጦ ወደ ራሱ ዝርያዎች ሄደ፡፡ ሆኖም እዚያም እንደዚህ መልኩ ነጭ የሆነ ወፍዘ ከኛ ዝርያ ውስጥ የለም፡፡ ከእኛ ጋር መኖርም ሆነ መመገብ የለበትም” ብለው አባረሩት፡፡ ከዚያን ጊዜ ጀምሮ ቤት - የለሽ፣ ዘመድ - የለሽዘ ብቸኛ ሆኖ ቀረ!
*   *   *
መምሰል ክፉ በሽታ ነው! ያልሆኑትን ሆኖ ለመታየት መሞከር ዕውነተኛ ማንነትን ማጣት ከመሆኑም በተጨማሪ የተነቃለታ ትልቅ ኪሣራ ያስከትላል፡፡ ወገን የሚመስሉን ወገኖችም ቢሆኑ “ከጠላትህ ውሰድኀ ወደ ዘመድህ ዞረህ ጉረስ” የሚለውን ተረት አሳምረው ያውቁታል፡፡ ይህን አለማስተዋል የማታ ማታ ዋጋ ያስከፍላል!
“መሆንህ እንጂ፣ መምሰልህ፣ ከቶ ለኔ ምን ፋይዳ አለውኀ ዓለምን ዓለም ያረጋት፣ መልክ ሳይሆን ማንነት ነው” የሚለውን ግጥም አለመዘንጋት ነው፡፡
ሀገራችን ብዙ አስመሳዮችን አስተናግዳለች፡፡ ነገም ገና ብዙ ታስተናግዳለች፡፡ የአስመስሎ ማደር ወይም አድርባይነት ጊዜያዊ ወረት ነው፡፡ ወረቱ ሲያልቅ “ጨዋታው ፈረሰ፣ ዳቦው ተቆረሰ” ማለት ግድ ይሆናል፡፡ የዚህ ዓይነት ጨዋታዎች ሲፈርሱ፤ በአፄ ኃይለሥላሴም፣ በደርግም፣ በኢህአዴግም ዘመን፣ ታዝበን አልፈናል፡፡
“ጠላትማ ምንጊዜም ጠላት ነውኀ አስቀድሞ መቅጠፍ አሾክሻኪውን ነው”
የሚለውዘ ለረዥም ጊዜ ስንሰማ የኖርነው ቀረርቶ ነው!
ሌላው ችግር ትምህርት ነው፡፡ ኩረጃና የትምህርት ጥራት እንዲህ ለያዥ ለገራዥ ያስቸግራል ብሎ ማሰብ አስገራሚ ነው፡፡ በልማት ላይ ላለች አገርዘ በብሔራዊ ደረጃ ኩረጃ ችግር ሲሆን ያሳፍራል። ምን ዓይነት ትውልድ እየቀረፅን ነው ብለን ስናስብዘ “በእንቅርት ላይ ጆሮ ደግፍ” ይሆንብቀሐል፡፡ ህብረተሰባችን ራሱ ስለ ትምህርት ጽሕለው አመለካከት እየተንሸዋረረ ነው፡፡ የት/ቤት ገንዘብ መክፈል፣ የትምህርት ቁሳቁስ መግዛት፣ ብቻውን የትምህርት ጤናማነት ማረጋገጫ አይደለም፡፡ የተማሪዎቹ ባህሪ በሚገባ መጤን አለበት፡፡ ክትትል፣ ክትትል፣ አሁንም ክትትል ያስፈልጋል!
ሌላው ችግር ጤና ነው፡፡ የህክምና ስህተቶች፣ የኮንትሮባንድ መድሀኒቶች አላግባብ መግባት፣ የሀኪሞች ስግብግብነት፣ የነርሶች ንዝህላልነት፣ የበሽተኞች መጉላላት ወዘተ… በከፍተኛ ደረጃ በሚታይበት አገር፤ ስለ ጤና ልማት ማሰብ ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ የክሊኒኮች መብዛት ለበለጠ ብዝበዛ የሚዳርግ ከሆነ ስለ ጤና ልማት ማለም  ሞኝነት ነው፡፡
በሀገርና በህዝብ ጉዳይ ምን ጊዜም ደግ ደጉን፣ ቀና ቀናውን ማሰብም ቢያንስ አዎንታዊነትና ብሩሃዊነት (Optimistic) መሆን ነው፡፡ መንገድ መስራት መልካም ልማት ነው፡፡ የትራፊክ አደጋ ከበዛ ግን የመንገዱን መሰራት አሉታዊ ያደርገዋል፡፡ ይሄን ችግር ለመፍታት ትራፊኩ ሰውዬ ጉቦ የሚበላ ከሆነ ደግሞ የመንገዱ አዎንታዊነት ይብስ አሉታዊ እየሆነ መጣ ማለት ነው፡፡ ሰንሰለታዊ ብልልት (Chain Reaction) አለበት ውስጡ፡፡ መሰረተ ልማት ውስጥ መብራትና ውሃ ተገጠመ ማለት ዋና ነገር የመሆኑን ያህል፣ መብራትም፣ ውሃም፣ ከሌለ ግን ቅርፅ ብቻ ይሆንብናል፤ ከጥቅም የተለየ ልማት የለምና፡፡ ይሄ በህዝብ ዘንድ የመንግስትን ህዝባዊነት ጥያቄ ላይ ቢጥለው በህዝብ አይፈረድም፡፡ መብራት ለምን ይጠፋል - እስኪሰለቸን ድረስ ተነግሮንም ቢሆን ማወቅ አለብን፡፡ ለሱዳንና ለጅቡቲ እየሸጥን እኛ ለምን ይቸግረናል? የሚለው ጥያቄ፣ መሬት የያዘ መልስ ቢኖረው፤ ቢያንስ “የዐባይን ልጅ ውሃ ጠማው” ከሚለው ተረት እንገላገላለን፡፡ አንዳንዴ ዝርዝር ላይ ስናተኩር ትልቁ ስዕል ይጠፋብናል (እናምታታዋለን Lose sight of the forest for the trees - ይላሉ ፈረንጆች፡፡
ደህንነታችን መደፈሩ ያሰጋናል፡፡ ሉዓላዊነታችን እንዲጠበቅ መፈለጋችን የማንደራደርበት ነው። ለማናቸውም ጥቃት፣ የምንከፍለው አፀፋ ከብሔራዊ ማንነታችን ጋር በጥኑ የተሳሰረ ነው፡፡ ዛሬም “ባለቤቱን ካልናቁ አጥሩን አይነቀንቁ” ወቅታዊ ተረት ነው፡፡ ዛሬም “ዳሩ ሲነካ መካከሉ ዳር ይሆናል” ወቅታዊ ተረት ነው፡፡ ችግሮች መቆሚያ ሊያጡ በፆም አንጀት ሆኖብን “ግዴለም፣ እንችለዋለን” እያልን ይሆናል፡፡ ነገሩ በፍስክ ሲቀጥል ግን ስጋታችን ዕጥፍ ድርብ ይሆናል፡፡ የዜጎቻችን አላግባብ መጨፍጨፍ የሚያወላዳ ምላሽን ይሻል፡፡
በምንም ሰበብ ይከሰት የዜጎቻችን እልቂት ያሳስበናል፡፡ ወደን እደለም ደግሞ እንዲህ ያለ ግልፅ ጭፍጨፋ በግላጭ አጋጥሞን ስለማያውቅ ነው! የከብቶቻችን ይዞታ የራሳችን እስከሆነ ድረስ፣ ማንም ምንም ዓይነት የባለ ይዞታን ዕምነት አለኝ ቢል ከቶም ለኛ ለውጥ አያመጣም! የእኛ ንብረት የእኛ ነውና! አሁንም ጠንቀቅ ብለን በብቃት መጠበቅ አለብን፡፡ የጎረቤት ሰላም ደፈረሰ ማለት የሁላችንም ውስጣዊ ህልውና ደፈረሰ ማለት ነው፡፡ ሰላም ለዘለዓለም ትኑር!
ዛሬ ያልተፈተሸ ብዙ ተቋማት፣ ብዙ ማህበራት፣ ሆስፒታሎች፣ ክሊኒኮች፣ ትላልቅ ሆቴሎች፣ የሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች፣ ከመንግስት መስሪያ ቤቶች ጋር ጥብቅ ቁርኝት ያላቸው ተሞዳማጅ መንግስታዊ ድርጅቶ ወዘተ እንካ በእንካ ተያይዘው ሳሉ ችግሮቻቸው በልማት ስም እየተሸፋፈነላቸው፡፡ ንፁህ መስለው በኩራት ይኖራሉ፡፡ አካሄዳቸው አገርንና ህዝብን ጎጂ መሆን አለመሆኑን በግድ መመርመር ያስፈልጋል፡፡ “ተሸፋፍነው በተኙ፣ ገልጦ የሚያይ አምላክ አለ” የሚለውን አባባል በቅጡ ጨብጦ ነገሮችን ማብጠልጠል ተገቢ ነው፡፡ “የተሰነጠቀ ቅልን ለማወቅ ውሃ ጨምርበት” ነው ነገሩ፡፡
ለክርስትና አማኞች የትንሳኤ በዓል የሞቀ የደመቀ ይሆን ዘንድ ከልብ እየተመኘን፤ የኢትዮጵያንም ትንሳኤ እንደዚሁ ይባርክልን እንላለን!!

እንደሻው እምሻው
(የሰማያዊ የፅ/ቤትና አስተዳደር ኃላፊ)

   ባለፈው ሚያዝያ 8 ቀን 2008 ዓ.ም በወጣው የጋዜጣችሁ፣የነጻ አስተያየት አምድ ላይ “ሰማያዊ ፓርቲ አደጋ ላይ ነው; በሚል ርዕስ፣ ከፓርቲያችን ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ጋር ያደረጋችሁትን ቃለ ምልልስ አነበብኩት፡፡ ሊቀመንበሩ አንድም ጊዜ እንኳን እየመራሁት ነው የሚለውን ፓርቲ መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ ሳይጠቅስ፣ የፓርቲውን ተቋማት ሁሉ እንደፈለገው ሲዘልፋቸው በመታዘቤ እኔም ይህን መልስ ለመጻፍ ተገደድኩ፡፡
ፓርቲያችን ሰማያዊ ጠቅላላ ጉባኤውን በነሀሴ 16 እና 17 2007 ዓ.ም ባደረገ ወቅት በብዙ ጉዳዮች ላይ የተወያየ ሲሆን ብሔራዊ ምክር ቤቱን፣ኦዲትንና ሊቀመንበሩን መርጦ ነበር የተጠናቀቀው፡፡ በፓርቲያችን መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ 6፣ ንዑስ አንቀጽ 2 መሰረትም፤ እኔም ሆንኩ አሁን የስራ አስፈጻሚ አባላት የሆኑት ለብሔራዊ ምክር ቤት አባልነት ተወዳድረናል፡፡ ጠቅላላ ጉባኤውም 37 ቋሚ፣ 13 ተለዋጭ የምክር ቤት አባላትንና አምስት የኦዲትና ምርመራ ኮምሽን አባላትን ከመረጠ በኋላ፣ የምክር ቤቱ አራተኛ ዓመት መስራች ስብሰባ ጳጉሜ 1 ቀን 2007 ዓ.ም ተካሂዶ፣ አቶ ይድነቃቸው ከበደን የምክር ቤቱ ሰብሳቢ አድርጎ መረጠ፡፡ ከዛም በኋላ ከፓርቲው የጠቅላላ ጉባኤ ሰነድ ጋር ጳጉሜ 3 ቀን 2007 ዓ.ም አሁን የሰማያዊ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባል የሆኑት (ያን ጊዜ የም/ቤት አባላት ነበሩ) ዝርዝራቸው ለምርጫ ቦርድ ገባ፡፡
እንግዲህ ተመልከቱ፤ሊቀመንበሩ ሁለት ገጽ ሽፋን በተሰጠው ቃለ ምልልስ፣ አንድም ጊዜ የፓርቲውን መተዳደሪያ ደንብ ጠቅሶ ለማብራራት አልሞከረም፡፡ እንደገና የም/ቤቱ አራተኛ ዓመት አንደኛ መደበኛ ስብሰባ መስከረም 9 ቀን 2008 ዓ.ም ሲደረግ ይልቃል ለስራ አስፈጻሚነት ያጫቸውን እጩዎች በም/ቤቱ እንዲጸድቅለት ሲጠይቅ፣ ከቋሚ የም/ቤት አባላት ውስጥ ስምንቱን፣ ከተለዋጭ አባላት ውስጥ ደግሞ ሁለቱን አምጥቶ ስምንቱ እጩዎች የም/ቤት ድምጽ የመስጠት መብታቸው ሳይነሳ ድምጽ እየሰጡ ሰባቱ ካለፉ በኋላ ቀሪዎቹ ባለባቸው ችግር ምክንያት ም/ቤቱ ጣላቸው፡፡ ይህ እንግዲህ የሆነው በፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ መሰረት ነው፡፡
ከዛ ተራው የፅ/ቤትና አስተዳደር ኃላፊ ሆነና ይልቃልና አዲሱ የም/ቤት ሰብሳቢ ተነጋግረው፣ በአንድ የስራ ቀን ሰብሳቢው ቢሮ መጥቶ፣“ከፅ/ቤት ኃላፊነትና ከም/ቤት አባልነት የቱን ትመርጣለህ; ብሎ ጠየቀኝ፡፡ እኔም “እዚሁ የፅ/ቤትና አስተዳደር ኃላፊ ሆኜ መቀጠል ነው የምፈልግው; በማለት ከመለስኩለት በኋላ የም/ቤት አባልነቴን ለቅቄያለሁ፡፡ እንግዲህ ይልቃል ይህን እያወቀ ነው ደንብ ሳይጠቅስ ዳር ዳሩን እየሄደ፣ የኢትዮጵያን ሕዝብና አባላትን ለማደናገር የሚሞክረው፡፡ ሌላው የፓርቲያችን መተዳደሪያ ደንብ አንቀጽ 37 የፅ/ቤትና አስተዳደር ኃላፊው ተጠሪነቱ ለም/ቤቱና ለሊቀመንበሩ ነው ይላል፡፡ ከዛ ደግሞ አንቀጽ 10/8 ደግሞ ከፓርቲው አባላት መካከል በምክር ቤት ሰብሳቢውና በሊቀመንበሩ በጋራ ተመርጦ የፅ/ቤትና አስተዳደር ኃላፊ ይሆናል ካለ በኋላ የምክር ቤት አባል ከሆነ ወንበሩን ለቆ በተለዋጭ አባል ይተካል ይላል፡፡ እንዲሁም አንቀጽ 10/13፤ የፅ/ቤት ኃላፊው በራሳቸው ፈቃድ ከለቀቁ ወይም የዲስፕሊን ጉድለት መፈጸማቸው አግባብ ባለው አካል ተረጋግጦ ከኃላፊነታቸው እንዲለቁ ሲደረግ፣ በቦታቸው በአንቀጽ 10/8 መሰረት ሌላ ሰው ይተካል ይላል፡፡
ሊቀመንበሩ ውሃ በማይቋጥር ቃለ ምልልሱ፤ አውቆ ሳይሆን የሚመራውን ፓርቲ መተዳደሪያ ደንብ ስለማያውቀው፣ ስለ እኔ ኃላፊነት ብዙ አውርቷል፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ የፅ/ቤት ኃላፊው ንብረትና ማህተም አላስረክብም ብሎ አሻፈረኝ ብሏል ይላል፤ማን ጠይቆኝ ለማንስ ላስረክብ ? እሱ እንዳደረገው ወይም እንደጻፈው ደብዳቤ፣ (“በሶስት ቀን ውስጥ ንብረት አስረክበህ ውጣ; ብሎ ነበር) ላድርግ? አላደርግም፡፡ ደንባችንም አይፈቅድም፡፡ ም/ቤቱም ሆነ ኦዲትና ምርመራ ኮምሽንም ከደንባችን አኳያ ይህን እንዳደርግ አልፈቀዱም፡፡
ይልቃል ስለ ጠቅላላ ጉባኤው፣ አራምባና ቆቦ የሚረግጥ መልስ ይሰጣል፡፡ ጉባኤው ከመድረሱ ሁለት ቀን በፊት ዮናታን ለይልቃል ድምጽ እንደሚሰጥ በፌስቡክ ገልጾ ነበር፡፡ የማይደርስ የለምና ጉባኤው ደርሶ ነሀሴ 17 ቀን 2007 ዓ.ም በተደረገው የሊቀመንበርነት ምርጫ ላይ ግን ሌሎቹ የተጠቆሙት አንወዳደርም ሲሉ፣ ዮናታን እንደ ይልቃል በግሉ እንደሚወዳደር በመግለጽ ለእጩነት ቀረበ፡፡ በሁለቱ መካከል በተደረገ የምርጫ ክርክርም፤ ዮናታን የውሸትም ቢሆን የጉባኤተኛውን ቀልብ ሳበ፡፡ በእያስጴድና በዮናስ ከድር አማካኝነት በጉባኤተኛው መካከል እየገቡ ዮናታንን እንዳትመርጡ እያሉ በመቀስቀሳቸው በውጤቱ ዮናታን 66 ድምጽ፣ ይልቃል ደግሞ 136 ድምጽ በማግኘት ምርጫውን ቢያሸንፍም በኋላ ላይ ሁለቱም ስለ ምርጫው የተሰማቸውን አስተያየት እንዲሰጡ በአስመራጭ ኮሚቴው እድል ይሰጣቸዋል፡፡ ዮናታን በሰጠው አስተያየት፤የዛሬ ሶስት ዓመት ሰላሳ ዓመት ስለሚሞላኝ ልምድ ይሆነኛል ሲል፣ ይልቃል ግን በገዛ እጄ አስጠግቼ ጉድ ሆኜ ነበር ብሏል፡፡ የጉባኤውን ፊልም በማየት ይሄን ማረጋገጥ ይቻላል፡፡ ዮናታንም በአዲሱ የይልቃል ካቢኔ የም/ቤቱን ሙሉ ድምጽ በማግኘት የሕዝብ ግንኙነቱን ስልጣን በድጋሚ ቢረከብም አንድ ወር እንኳን ሳይሰራ ከኃላፊነቱ ለቀቀ፡፡ በኋላም ለእስር በቃ፡፡
በደንባችን አንቀጽ 13 የስራ አስፈጻሚው ስልጣንና ተግባር በሚለው ላይ፣ የስራ አስፈጻሚው ተጠሪነቱ ለሊቀመንበሩና ለስራ አስፈጻሚው መሆኑን ይደነግጋል፡፡ ከአንድ እስከ 13 ያሉት ንዑስ አንቀጾች በሚያዙት መሰረትም፤ይልቃል ሊቀመንበር ስለሆነ ስራ አስፈጻሚውን ይከታተል ነበር ወይ ለሚለው መልሱን ለራሱ ትቼዋለሁ፡፡ አሁንም ሆነ በፊት የነበሩት ስራ አስፈጻሚዎች አንዳቸውም ቢሆኑ በተለይ አንቀጽ 13 ንዑስ አንቀጽ 10 በሚያዘው መሰረት፤መመሪያውን አዘጋጅቶ በስራ አስፈጻሚ ያጸደቀ የለም፡፡ ይልቃልም እንዲያዘጋጁ አይፈልግም፡፡ ይህን የሚያውቀው እሱ ብቻ ነው፡፡ ም/ቤቱም ይጨቀጭቃል፤ እሺ በማለት ይታለፋል፡፡ እኔም እንደ ኃላፊነቴ፤ በስንት ጭቅጭቅ የፅ/ቤት መመሪያ አዘጋጅቼ በስራ አስፈጻሚው ጸድቆ እየተሰራበት ነው፡፡ ሌላው ደግሞ የፋይናንስ መመሪያው ሲሆን በኃላፊው ተረቆ  በስራ አስፈጻሚው ተገምግሞ፣ በም/ቤቱ የጸደቀ ቢሆንም በመመሪያው መሰረት የገንዘብ አወጣጥ ስርዓቱ ባለመጠበቁ፣አሁን ለተፈጠረው የገንዘብ ሌብነት ምክንያት ሆኗል፡፡  
ይልቃል ከጉባኤ በፊት በሊቀመንበርነት ዘመኑ፣ በደንባችን አንቀጽ 26 መሰረት መስራት ከነበረበት ውስጥ ስንቱን ሰርቷል? በዛን ጊዜ በደንባችን ውስጥ የሌለ፣ በመመሪያ ያልተገለጸ በቃለ ጉባኤ ያልተያዘ ቢሆንም፣ የሙሉ ቀን ሰራተኛ ሆኖ የአምስት ሺህ ብር የወር ደሞዝ ተከፋይ ነበረ፡፡ ክፍያው አሁንም ድረስ ቀጥሏል፡፡ በእነዚህ ሶስት ዓመታት ውስጥ ቀኑን ሙሉ ቢሮ ሲውል ግን አንድ ነጠላ ወረቀት ፅሁፍ እንኳን ለፓርቲው አበርክቶ አያውቅም፡፡ አንቀጽ 26/6፤ በብሔራዊ ምክር ቤቱና በስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ ውሳኔ መሰረት የሚወጡ ደብዳቤዎችና ሰነዶች ላይ ይፈርማል ይላል፡፡
በእርግጥም እሱን ሲያደርግ ቆይቷል፡፡ ከእዚያ ውጪ እድሜ ለቴክኖሎጂ፣በሞባይሉ ጌም ሲጫወትና ሌሎች ተግባራትን ሲያከናውን ነው ጊዜውን የጨረሰው፡፡ አሁን ደግሞ የማያመጣው ሰበብ የለ፣ ከመደብደብ ብዬ ቢሮዬን ወደ ካፌዎች አዛውሬያለሁ ይለናል፡፡
ሌላው ደግሞ በእሱ በኩል ካለው ጎራ፣ ብዙ ተተኪ አመራር ሊሆኑ የሚችሉ ወጣቶች አሉ ይለናል፡፡ ለመሆኑ ይልቃል ደጋፊ እንጂ አባል የሚሆኑ ወጣቶችን በዙሪያው ያስጠጋል? አጠገቡ ያሉት እስቲ በሚጽፉት የፌስቡክ ፅሑፍ ይመዘኑ፡፡ ከይልቃል አመራር ጋር ወደፊት የሚሉና ድርጅትን ሳይሆን ግለሰብ አምላኪ፣እድሜያቸውም ከሃያ አራትና ሃያ አምስት የማይበልጡ እኮ ናቸው፡፡ በመጨረሻ ለይልቃል ጥቂት ጥያቄዎች ላቀርብለት እወዳለሁ፡- “እስቲ በዙሪያህ ሆነው ያንተን ስልጣን ይናፍቁና ይጠብቁ ከነበሩ ወጣቶች ውስጥ ምን ያህሉ ከጠቅላላ ጉባኤ በኋላ እስር ቤት ገቡ? ምን ያህሉ አገር ጥለው ተሰደዱ? ምን ያህሉን በወያኔነት ፈረጅካቸው?; ይህንን ነው መመለስ ያለበት፡፡ ቅድም እንዳልኩት፤ የፓርቲውን መተዳደሪያ ደንብ አንቀጾች በግድ ግለጽ አልለውም፡፡
 ለምን ቢባል ? እሱ ቀርቶ አሁን በስራ ላይ ያሉት የስራ አስፈጻሚ አባላት ቁጥር ሰባት መሆናቸውን እንኳን ዘንግቶ፣ስራ አስፈጻሚው በተሟላ መልኩ ስራውን እየሰራ እንደሆነ ነግሮናል፡፡ እናም አልፈርድበትም፡፡