Administrator

Administrator

የ25 ዓመቷ አሜሪካዊት ጄድ ሲልቪስተር፤ በእርግዝና ወቅት በተፈጠረባት አምሮት መላቀቅ ዳገት ለሆነባት ክፉ ልማድ እንደተጋለጠች ትናገራለች፡፡ ከአንድ ዓመት በፊት ነፍሰጡር ሳለች የጀመረችው የመፀዳጃ ቤት ወረቀት (ሶፍት) የመብላት ልማድ ከወለደችም በኋላ ሊላቀቃት አልቻለም፡፡ ዛሬ ያ አምሮት ወደ ሱስ ያደገ ይመስላል፡፡ በየቀኑ አንድ ጥቅል ሶፍት ታነክታለች፡፡
“ባረገዝኩ በሁለተኛ ወሬ ነው ሶፍት የመብላት አምሮት (ፍላጐት) ያደረብኝ፡፡ ለምን እንደሆነ ግን አሁንም ድረስ አላውቀውም፡፡
 ከጣእሙ ይልቅ ደስ የሚለኝ ሻካራነቱ ነው፡፡ ደረቅነቱን እወደዋለሁ” ያለችው ጄድ፤ “ቤተሰቦቼ ለጤናዬ ጥሩ አለመሆኑን ይነግሩኛል፤ ነገር ግን ለመተው አልቻልኩም” ብላለች፡፡
ልጇን ከተገላገለች አንድ ዓመት ከሦስት ወር ያለፋት ቢሆንም መፀዳጃ ቤት ገብታ በተቀመጠች ቁጥር ሶፍት እየቀረደደች መብላቷን ገፍታበታለች፡፡ በየቀኑም አንድ ሙሉ ጥቅል ሶፍት እንደ ምግብ አኝካና አጣጥማ እንደምትውጥ ተናግራለች፡፡ ነፍሰጡር ሳለች መፀዳጃ ቤት ገብታ ጥቅል ሶፍት ስታይ “ይሄንን መብላት አለብኝ” እያለች ትጐመዥና ትመኝ እንደነበር ያስታወሰችው ጄድ፤ ዛሬ ግን አንዳንዴ ወደ መታጠቢያ ከመሄድ ሁሉ ራሷን እንደምታቅብ ገልፃለች፡፡ “ምክንያቱም ከሄድኩኝ መብላቴ አይቀርም፡፡ ሽንት ቤት በሄድኩ ቁጥር ወደ 8 ገደማ የሶፍት ቁራጮች እበላለሁ አንዳንዴም ሶፍቱን ለመብላት ስል ብቻ መፀዳጃ ቤት ለመሄድ እገደዳለሁ” ትላለች፡፡
ለመብላት የምትመርጠውን የሶፍት አይነት ስትናገር ደግሞ፤ ከውዶቹ ይልቅ በየሱፐርማርኬቱ የሚገኙት ተራና ርካሽ ሶፍቶች ምርጫዋ እንደሆኑ ገልፃለች፡፡
“የተለያዩ የሶፍት ምርቶች የተለያየ ጣእም አላቸው፤ በመፀዳጃ ቤት ውስጥ አንድ ጥቅል ለምበላው፣ አንድ ጥቅል ደግሞ ለተለመደው አገልግሎት አስቀምጣለሁ” ብላለች ጄድ ሲልቪስተር፡፡ የመጨረሻ ወንድ ልጇን ከተገላገለች ጊዜ ጀምሮ (16 ወራት ገደማ ማለት ነው) ሶፍት መብላቷን ለመተው ብዙ ታግላለች፤ ሆኖም አልተሳካላትም፡፡ ልጅ ከወለድኩ በኋላ አምሮቱ የሚተወኝ መስሎኝ ነበር ያለችው ጄድ፤ ነገር ግን ሶፍት መብላቴን ላቆም አልቻልኩም ትላለች - ተስፋ በቆረጠ ቅላፄ፡፡
“ሶፍት መብላቴ ለሰውነቴ መልካም ሊሆን እንደማይችል አውቃለሁ፤ እስካሁን ግን ምንም የጤና ችግር ወይም ህመም አላስከተለብኝም” ያለችው ሚስ ሲልቪስተር፤ ሶፍት ስትበላ ልጆቿ እንዳያዩዋት ለመደበቅ እንደምትሞክር ገልፃ ድንገት ካዩዋት ግን እንደሚቆጧት ተናግራለች፡፡ ጄድ ሲልቪስተር የአምስት ልጆች እናት ናት፡፡ የአገራችን ሰው “አያድርስ ነው” የሚለው ለካ ወዶ አይደለም!!

ከእለታት አንድ ቀን አንዲት ቀበጥ ልጅ ከእናቷና ከሴት አያቷ ጋር አብራ ትኖር ነበር፡፡ ከቀበጥነቷም በላይ የሥራ ዳተኝነቷ አስቸጋሪ ነበር፡፡
እናትና አያት ይወያያሉ፡-
አያት - እንደው የዚችን ልጅ ነገር ምን ብናደርግ ይሻላል?
እናት - እረ እኔም ከዛሬ ነገ እጠይቅሻለሁ እያልኩ ስፈራ ስቸርኮ ነው የቆየሁት፡፡ የአያት አንጀት ሆኖብሽ ስለምታቆላብሻት እንዳትቀየሚ ብዬ ታገስኩ፡፡
አያት - እረ የምን ቅያሜ ነው እሱ?
እናት - እንግዲያው ለምን ቁጭ አድርገን ነገረ-ስራዋ ሁሉ እንዳልጣመንና ከእንግዲህ ቤቷን ቤቴ ብላ በስነ ሥርዓት እንድትኖር እናስጠንቅቃት፡፡
አያት - አዎ፤ መቼም የሙት ልጅ ናትና አባቷ ከሞተ ወዲህ ሀዘኗም ብስጭቷም በዝቶቦታል ብለን ብዙ ታገስናት፡፡ አሁን ግን በዛ!
እናት - መብዛት ብቻ! ተንዛዛች እንጂ! ምግብ በልታ ውልቅ! ጠዋት የወጣች አገሩን ስታካልል ውላ መምጣት! እራቷን በልታ ክልትው!
አያት  አዲስ ሀሳብ አመጡ:-
“ቆይ እስቲ ዛሬ መቼም አዕምሮ አላት፡፡ ታስብበትና ወደ ቀልቧ ትመለስ ይሆናል”
እናት - ምን አድርገሽ ቀልብ እንዲኖራት ታደርጊያታለሽ?
ምን እናድርግ ትያለሽ?
አያት - ወደ አልጋዋ እንጠጋና ወለሉን እኔ ልጥረግ እኔ ልጥረግ እያልን እንጣላ፡፡ ለመጥረግ እንታገል፡፡ ስትነቃ ተዉት እኔ እጠርጋለሁ በማለት ይሉኝታ ይይዛትና ትነሳለች፡፡
እናት - በጣም ድንቅ ሃሳብ! በይ ነይ እንሂድ፡፡
እናትና አያት እንደተባባሉት፤ አንድ መጥረጊያ ለሁለት ይዘው፤
አያት - ተይ ዛሬ እኔ ነኝ የምጠርገው?
እናት - ምን ሲደረግ!? አንቺ አርፈሽ ቁጭ በይ!
አያት - አብደሻል ስንት ዘመን አንቺ ልትጠርጊ ነበርኮ?
እናት - አይሆንም አልኩ አይሆንም!
ትግሉ ቀጠለና ልጅቱ ነቃች፡፡
ከአልጋዋ ቀና አለችና፤
“ለምን ትረብሹኛላችሁ? ቤቱን ለመጥረግ ይሄን ያህል ትግል ምን ያስፈልጋል? አንዳችሁ ዛሬ ጥረጉ፤ አንዳችሁ ደግሞ ነገ ጥረጉ” ብላ ተመልሳ ተኛች፡፡
***
የሥራ ሥነምግባር መሰረቱ ግብረገብነት ነው፡፡ ለእናት ለአባት መታዘዝ ነው! ጥቃቅኖቹን ትዕዛዛት በማክበር ማደግ የእድገትን ቁልፍ መጨበጥ ነው፡፡
“አጓጉል ትውልድ
ያባቱን መቃብር ይንድ”
የሚባለው በዋዛ አይደለም፡፡ በጥንቱ ዘመን “ያልተቀጣ” “አሳዳጊ የበደለው!” የሚል ስድብና እርግማን ትልቅ ዋጋ ነበረው፡፡ በምርቃትም ደረጃ “ትምህርትህን ይግለጥልህ!” ማለት የምርቃት ሁሉ ምርቃት ነው፡፡ ከወላጅ ማክበር ወደ መምህር ማክበር፤ ከዚያም ወደ አለቃ ማክበር ማደግ፤ ለአንድ ወጣት ትውልድ ትልቅ እሴት ነው፡፡ እነዚህ እሴቶች የሀገር ባህል አይናቄ መሰረቶች ናቸው፡፡ የግብረገብነት ባህል ሲያዩት ወይም ሲያወሩት ቀላል፤ ሲመረምሩት ግን ጥልቅ ነገር ነው፡፡ የትምህርት ባህል፣ የሥራ ባህል፣ የአስተዳደር ባህል፣ የፖለቲካ ባህል፣ የኮሙኒኬሽን ባህል፣ የውይይት ባህል፣ የመቻቻል ባህል… የሁሉ ነገር መሰረት ናቸው፡፡
ዴቪድ ቦህም የተባለ ፀሀፊ፡-
“…በውይይት ሂደት መንቃት በተካፋዮቹ በተሳታፊዎቹ መካከል የሚፈጠር የትርጉም መረዳዳት ፍሰት ነው፡፡ በመጀመሪያ ተሳታፊው ሁሉ የየግሉን አቋም/ጐራ ይይዝና ይሄን ብለቅ ሞቼ እገኛለሁ ይላል፡፡ እያደር ግን ከየግል ደረቅ አቋም ይልቅ የወዳጅነት ስሜት የበለጠ እንደሚሆን እየታየ ይመጣል፡፡ ምንም አይነት የወዳጅነት ቀረቤታ ሳይኖር መግባባት ብቻ ድንቅ ባህሪ ይሆናል…” ይለናል፡፡
አንዳችም ልዩና መሰረታዊ ዓላማ ከጀርባው ሳይኖር ወዳጅነትን መፍጠር መባረክ ነው፡፡ ለሀገር ለወገን የሚበጅ እፁብ ነገር ነው፡፡ ስብዕና፣ ዕውቀት፣ ምጥቀተ-ህሊና፣ የጋራ-ቤትን ማፍቀር፤ መሰረታዊ መነሻዎችና ማደጊያዎች ናቸው፡፡ በተለይ ወጣቱ ከመሰረት ከንጣፉ እኒህን ጉዳዮች ማወቅና መገንዘብ መቻሉ ደርዝ ያለው ነገር ነው፡፡ መተሳሰብ፤ መወያየት፣ ማንበብና መናበብ፣ በሥርዓት መኖር፤ የጋራ ምጥቀተ-ህሊና (Consciousness) ያስፈልገዋል - የሀገራዊነት መሰረቱ ይሄው ነውና!
ወጣቱን ሳይዙ ጉዞ ምን ተይዞ ጉዞ ነው፡፡ ወጣቱ ሲባል ደግሞ ለትምህርት ዝግጁ የሆነው፣ ለመንቃት የሚተጋው ራሱን ምንጊዜም ለመለወጥ የሚታትረው፣ አርቆ ማስተዋል ጐዳና ላይ ያለው ነው፡፡ በእርግጥ አገር ተረካቢ ትውልድ መፍጠር ካለብን ከቤተሰብ አስተዳደግ፣ ከትምህርት ቤት መታነፅ፣ ለአካለ - ሥራ መብቃት ጋር የተሳሰረ ወጣት ይዘን መሄድ ይኖርብናል፡፡
የዕውር የድንብር አለመሄድ ትልቁ ጥበብ ነው፡፡ ወጣቱ ህይወትን የሚቃኝበት ኮምፓስ ያሻዋል፡፡ ሌሎችን የሚማርክበት ማግኔት ያለው እንዲሆንም እንጠብቃለን፡፡ በዚህ የመረጃ ዘመን መረጃ - የለሽ ትውልድ እንዳይፈጠር ሁሉም ዜጋ አስተዋፅዖ ሊያደርግ ይገባል፡፡
የጥበብ ዐይኑ የተከፈተ ወጣት የበለፀገ ዕይታ ይኖረዋል፡፡ በኪነጥበብ እንዲጠነክር ማድረግ ያስፈልጋል፡፡ ሳይንስና ቴክኖሎጂን በቅጡ ማወቅ የአንድ ህብረተሰብ የዕድገት ምልክት ነው፡፡ ወጣቱ የህብረተሰብ ክፍል ለዕለት - እንጀራ መፈለጊያ የሚበቃ ዕውቀት ብቻ ሳይሆን ምሉዕነት ያለው የዕውቀት ቀንዲል ለመጨበጥ እንዲነሳሳ ማገዝ ያስፈልጋል፡፡
እጓለ ገብረ ዮሐንስ የተባሉ የአገራችን ደራሲ ስለአቴናውያን ሲፅፉ፤ “እሊህ አቴናውያን የነበራቸው አዲስ ነገር ለመስማትና ለመናገር መጓጓት ንጹሕ ሰብዓዊ ስሜት ነው፡፡ ወደፊት ለመራመድ የቻሉትም በዚህ ምክንያት ነው፡፡ በማናቸውም የአውሮፓ ሥልጣኔ ክፍሎች ዘንድ የነሱን ማህተም ያልተሸከመ ነገር አይገኝም፡፡ ጫፉን ለመጥቀስ ያህል በሳይንስ ረገድ እነ ዲሞክሪቶስ እስከ አቶምፊዚክስ ድረስ የደረሱ ነበሩ፡፡ በፖለቲካ ድርጅት ረገድ እስከ ዲሞክራሲ የደረሱ ነበሩ፡፡ ለዚህ ሁሉ የሥልጣኔ ሀብታት መገኛ ለመሆን የቻሉት በንጹህ ሰብዓዊ ጠባይ እየተመሩ አዲሱን ነገር በመመኘት ስለዚያም በመናገርና በመስማት ነው” ይሉናል፡፡ አዲስ ነገር ለማየት የሚጓጓ ትውልድ ያስፈልገናል፡፡ ይህ ማለት ግን መነሻውን፣ ታሪኩን፣ ባህሉን፣ የዕውቀት ውርሱን በመመርመር ላይ የተመሠረተ ሊሆን ይገባዋል፡፡ “ማናቸውም የህሊና ተግባር በህገ - ምክንያት የተመሠረተ (Causalities) መሆን አለበት” ይሉናል የጠቀስናቸው ፀሐፊ፡፡
ብርሃናማ ነገ እንዲኖር ዛሬ ብርሃናማ ትውልድ የሚወራረሰው የጽሑፍም ሆነ የአፈ - ንግርት ቅርስ እንዲያፈራ፤ ምሁራን በተለይም ፀሐፍት የወጣቱን ዐይን ሊከፍቱለት ይገባል -በዚህ ረገድ የራሳቸውን መክፈልት ሊከፍሉ ይገባል፡፡ እንዲያው በደፈናው ትውልድን መራገም ማብቃት ይኖርበታል፡፡ ሃዋርያና ደቀመዝሙር መሆን አለባቸውና፡፡ ተቀምጠን ከምናላዝን ተንቀሳቅሰን ለነገ ለውጥ እናምጣ ነው ጉዳዩ! “የተቀመጠች ወፍ ሆዷን ስትዳብስ የበረረች ወፍ አፏን ትዳብሳለች” ማለት ይሄው ነው፡፡  

በበርካታ ፊልሞችና የሪያሊቲ የቲቪ ፕሮግራሞች ላይ በትወና የተሳተፈችው ታዋቂዋ ኔዘርላንዳዊት ተዋናይት ላውራ ፓንቲኮሮቮ ፕላን ኢንተርናሽናል በኢትዮጵያ እያከናወናችው የሚገኙ ሥራዎችን ጐበኘች፡፡
“Because I’m a girl” በሚል መሪ ቃል በፕላን ኢንተርናሽናል የሚሰሩትንና የሴቶችን አቋመ በማጐልበትና ህይወታቸውን በመቀየር ላይ ትኩረት ያደጉትንና በደቡብ ክልል የተሰሩትን ሥራዎች የጐበኘችው ተዋናይቷ ባየችው ነገር እጅግ መደነቋንና ሴቶች በእውቀትና በልምድ የዳበር ሰብእና እነዲኖራቸው የሚደረገው ጥረት ሊቀጥልና ሊበረታታ የሚባው እንደሆነ ተናግግራለች፡፡
ተዋናይቷ ከትናንት በስቲያ በጁፒተር ሆቴል በሰጠችው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደተናገረችው ሴቶች በእውቀት ታንፀው ሲያድጉ አቅም ያላቸው በቀላሉ የማይወድቁ በመሆኑ በዚህ ሴቶችን በማብቃቱ ተግባር ላይ የበኩሏን አስተዋፅኦ ለማድረግ ወደ ኢትዮጵያ መምጣቷ እንዳስደሰታት ገልፃለች፡፡
ኔዘርላንዳዊቷ ተዋሃይት ከተሳተፈችባቸው ፊልሞች መካከል X-factory, Stars dancing on ice, my dirty greasy, nasty fiancé, and I’m a star get me out of here የተሰኙት ይጠቀሳሉ፡፡ ተዋናይ ላውራ ለአራት ቀናት በኢተዮጵያ ያደረገችውን ቆይታ አጠናቃ ከትናንት በስቲያ ወደ አገሯ ተመልሳለች፡፡

   የፈረንሳይ ፕሬዚዳንት ፍራንሲስ ኦላንዴ፤ በኢቦላ የተጠቁ የምዕራብ አፍሪካ ሃገራትን የጐበኙ ሲሆን ባለፈው አርብ እለት ጉብኝታቸውን የጀመሩት ከጊኒ ነበር፡፡
ፕሬዚዳንቱ 1200 ዜጐቿን በቫይረሱ ለተነጠቀችው ጊኒ፤ ቀደም ሲል በሀገራቸው መንግስት ስም 100 ሚሊዮን ዩሮ እንደለገሱና ገንዘቡም በአገሪቱ የኢቦላ ህክምና ማዕከላትን ለማቋቋም እንደዋለ ተዘግቧል፡፡ በአሁኑ ጉብኝታቸው 200 አልጋዎችንና የተንቀሳቃሽ ህክምና ማዕከል ድጋፍ እንዳደረጉ ታውቋል፡፡
ፕሬዚዳንቱ በጊኒ የተለያዩ የህክምና ጣቢያዎችን ተዘዋውረው የጐበኙ ሲሆን ከጤና ባለሙያዎችና ተመራማሪዎች ጋር በሽታውን በተመለከተ የጠረጴዛ ዙሪያ ውይይት ማድረጋቸውም ተጠቁሟል፡፡ በኢቦላ የተጠቁ የአፍሪካ ሀገራትን በመጐብኘት የመጀመሪያው የአውሮፓ መሪ ናቸው የተባሉት ፕሬዚዳንት ኦላንዴ፤ ከጊኒው ጉብኝታቸው በኋላ በኢቦላ ወደተጠቃችው ሌላኛዋ አፍሪካዊት ሀገር ወደ ሴኔጋል ተጉዘው የፈረንሳይኛ ተናጋሪ የአፍሪካ ሀገራት መሪዎች ስብሰባ ላይ እንደተሳተፉ ተዘግቧል፡፡
በተመሳሳይም ከስብሰባው ጐን ለጐን በጊኒ እንዳደረጉት ሁሉ በኢቦላ ጉዳይ ከሴኔጋል የጤና ሚኒስትሮችና የሀገሪቱ ፕሬዚዳንት ጋር መክረዋል ተብሏል፡፡
ፕሬዚዳንት ኦላንዴ በሶስት ቀናት ቆይታቸው ከጊኒና ሴኔጋል በተጨማሪ ሴራሊዮንና ላይቤሪያን እንደጎበኙ ታውቋል፡፡  

“የፀሐይ ብርሃንን ጭምር ወደ ኤሌክትሪክ ኃይል እንቀይራለን”

ህዳር 13 ቀን 2007 ዓ.ም ለንባብ በበቃው የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ዕትም ላይ፤የነፋስ ተርባይን የኤሌክትሪክ ሃይልን በተመለከተ ያወጣችሁት ዘገባ ስህተት ነው፡፡ የሃገሪቱ ኢኮኖሚ እያደገ በሄደ ቁጥር የነፋስ ኃይልን ብቻ ሳይሆን የፀሐይ ብርሃንንም ወደ ኤሌክትሪክ ኢነርጂ እንቀይራለን፡፡
 በእርግጥ ከውሃና ከንፋስ ኃይል ውዱ የንፋስ ኃይል ነው፡፡ ነገር ግን ከነፋስ ሃይል ማመንጨት የጀመርነው የሃገራችንን ኢኮኖሚ ጭምር ለማልማት የሚያስችል አቅም እየፈጠርን ስለሄድን ነው፡፡ በውሃ ሃብታችን እስከ 50 ሺ ሜጋ ዋት  ማልማት የምንችል ሲሆን በንፋስ ኃይላችን ደግሞ 1.3 ሚሊዮን ሜጋ ዋት ማመንጨት እንችላለን፡፡
 ይሄን ሃብት ደረጃ በደረጃ በመጠቀማችን እንኳንስ ዜጐች፣የኛን እድገት የማይፈልጉትም ጭምር አዎንታዊ ምላሽ ላይ ተጋንኖ እንደቀረበው እየሰጡ ነው፡፡ ከዚህ አንጻር አገሪቱ የንፋስ ኃይል በመጠቀሟ በጋዜጣው ላይ እንደ ከሰረች ተደርጎ የቀረበው የተጋነነ ነው፡፡ እንደውም “ውዱን ሃብት ጭምር ለማልማት የቻለች፣ እያደገች ያለች ኢትዮጵያ” ብላችሁ ነው መዘገብ ያለባችሁ፡፡
በኃይል በኩል ገና ሊለማ የሚችል ብዙ ሃብት አለን፡፡ በአሁን ሰዓት 2268 ሜጋ ዋት ብቻ ነው ያለን፡፡ ከዚህ ውስጥ 171 ሜጋ ዋት የምናመርተው ከንፋስ ሲሆን በቀጣይ ሊለማ የሚችል ከውሃ እስከ 50 ሺ ሜጋ ዋት፣ ከነፋስ 1.3 ሚሊዮን ሜጋ ዋት እንዲሁም ከምድር እንፋሎት ከ10 ሺ ሜጋ ዋት በላይ እምቅ ሃብት አለን፡፡
ነገር ግን ቀደም ባሉት ዓመታት በአብዛኛው በውሃ ላይ አተኩረን የቆየነው፣ ውሃ በርካሽ የገንዘብ አቅም መልማት ስለሚችል ነው፡፡ አሁን ግን  የሃገራችን  ኢኮኖሚ በማደጉ በውሃ ላይ ጥገኛ ከምንሆን ከንፋስም ጭምር ኃይል እያመነጨን ለሃገራችን ቀጣይነት ያለው የኤሌክትሪክ ሃይል እናቀርባለን፡፡ በአሁኑ ወቅት እየጨመረ የመጣውን ከፍተኛ የኤሌክትሪክ ፍላጎት ለማርካት ከንፋስ ሃይል ማመንጨት የግድ ነው፡፡ ሃገሪቱ ይሄን ሃይል የመፍጠር አቅም ስላጐለበተች ነው ወደዚያ የተገባው፡፡ በመቀጠል  ደግሞ ከፀሐይ የኤሌክትሪክ ሃይል ለማመንጨት በዝግጅት ላይ ነን፡፡
አቶ ምስክር ነጋሽ፤
የውጭ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ
f

“ኤሌክትሪክ በየሰዓቱ ይጠፋል” በሚል ርዕስ ቅዳሜ ህዳር 13 ቀን 2007 ዓ.ም በታተመው ጋዜጣችሁ የወጣውን ፅሁፍ ከአነበብኩት በኋላ ይህንን ሃሳብ ለመሰንዘር ወደድኩኝ፡፡
ፅሁፉ ሙሉ በሙሉ ጉዳዩን የፈተሸ ባይሆንም፣ መደምደምያውም ትክክል ነው ብዬ ባላምንም እንደዚህ ዓይነት አብይ ጥያቄ ይዞ በመነሳቱ ግን አድንቄዋለሁ - በሁለት ምክንያት፡፡ በድፍረትና በተቆርቋሪነት የቀረበ በመሆኑ፣ እንዲሁም በተቻለ መጠን በመረጃ በመደገፉ፡፡ በአሁኑ ጊዜ እነዚህ ነገሮች በብዙ የስራ ዘርፎች የማይታዩ ባህሪዮች ናቸውና፡፡
ወደ አስተያየቴ ስገባ፣ በመጀመሪያ በፅሁፉ በተነሱት አሳሳቢ ጉዳዮች ላይ የራሴን ላክልና በመደምደሚያው ያልተስማማሁበትን ምክንያት አቀርባለሁ፡፡ ከዚያም የራሴን ለየት ያሉ መደምደሚያዎች ደግሞ አስከትላለሁ፡፡ በመሰረቱ በፅሁፉ የቀረቡ ንፅፅሮች ትክክል ናቸው፡፡ ያም ብቻ አይደለም፡፡ ንፋስ በየሰከንዱ የሚለዋወጥ ስለሆነ፣ የንፋስ ጄኔሬተሮች የሚያመነጩት ኃይል በጣም ተቀያያሪ ነው፡፡ ይህም በኦፕሬሽን ላይ ጭምር በጎ ያልሆነ ተፅዕኖ አለው፡፡ ከዚህም ሌላ የንፋስ ጀነሬተሮች በሚጠቀሙት ቴክኖሎጂ መግነጢሳዊ ስበታቸው ከመረቡ የተለየ ስለሆነ ለሲስተሙ ጥንካሬና (stability) በአደጋ ጊዜ ሲስተሙን ወደ ነበረበት ሁኔታ ለመመለስ አያግዙም፡፡ ያም ሆኖ ግን የንፋስ ኃይል ማልማት ተቀባይነት ያገኘበት ጠንካራና አሳማኝ ምክንያቶች አሉት፡፡
በመጀመርያ የንፋስ ኃይል ለማልማት በጣም ፈጣን መሆኑ ነው፡፡ በተለይም ከውሃ ኃይል ጋር ሲነፃፀር የሚወስደው ጊዜ በጣም አጭር ነው ሊባል ይችላል፡፡ አንድን የንፋስ ኃይል ጣቢያ ለማልማት እንደ ሁኔታው ከ16-19 ወራት በቂ ሊሆን ይችላል፡፡ በሌላ በኩልም አንድን መካከለኛ ወይም ከፍተኛ የውሃ ኃይል ማመንጫ ጣቢያ ለማልማት ቢያንስ ቢያንስ 6 እና 8 ዓመት ያስፈልጋል፡፡ ሁለተኛው ጉዳይ የከፍተኛ ኃይል የማምረቻ ጊዜያቸው ተመጋጋቢ መሆኑ ነው፡፡ የአንዱ ምርት ዝቅ በሚልበት ወቅት የሌላኛው ምርት ከፍ ይላል፡፡ የውሃ ሃብታችን ግንቦት ወር አካባቢ ዝቅተኛ ሲሆን የንፋስ መጠኑ ደግሞ በዚህ ወር አካባቢ ይበረታል፡፡ ስለዚህም ጥሩ የሆነ የኃይል አቅርቦት ቅይጥ ይኖረናል ማለት ነው፡፡ በተጨማሪም እስከ አሁን የለሙት የንፋስ ኃይል ጣቢያዎች ከከፍተኛ የኃይል ተጠቃሚ ማእከላት በጥሩ ቅርበት መሆናቸው ነው፡፡ በዚህም ምክንያት የሚዘረጋው የኃይል ማስተላለፍያ መስመር ወጪ በንፅፅር አነስተኛ ነው፡፡ ስለዚህ የንፋስ ኃይል ላይ የወጣው ኢንቨስትመንት እንደ ፅሁፉ አቀራረብ ብክነት ተደርጎ መወሰድ የለበትም፡፡ ከዚህ ውጭ ደግሞ አገራችን በከባቢያዊ ወይም በአረንጓዴ ልማት የበኩሉዋን አስተዋፅኦ ለማድረግ የገባችው ፖለቲካዊ ቃል መረሳት የለበትም፡፡
እንደዚያም ሆኖ ፅሁፉን በበጎ በመረዳት የሚከተሉት ጥያቄዎች መመለስ አለባቸው - በሚመለከታቸው አካላት፡፡ አንደኛ፣ ለኢትዮጵያ የሚያዋጣው የኃይል ልማት ኢንቨስትመንት “ፖርትፎልዮ” ምን መምሰል አለበት? ይህም ማለት የንፋስ ድርሻ (ከቴክኒካዊም ሆነ ከኢኮኖሚያዊ መመዘኛዎች አንፃር) ስንት በመቶ መሆን አለበት ብሎ መወሰን ነው፡፡
ሁለተኛ፣ አሁን ያለው ጠቅላላ የሲስተሙ ኦፕሬሽን ላይ የንፋስ ኃይል ጣቢያዎች ባህሪይ ምን ይመስላል? በጠቅላላ የሲስተሙ መደላድል (stability) ላይስ ያለው ሁኔታ እንዴት ነው? የሚሉት ናቸው፡፡ ከዚህ ዋናው አርእስት ውጭ ስለ መብራት መቆራረጥ ለማንሳት ያህል ደግሞ ችግሩ በኃይል መቆራረጥ ላይ ብቻ የተወሰነ አድርጎ የሚያስብ ካለ ተሳስቷል፡፡
 መቆራረጡ በመብራት ኃይል አጠቃላይ ሲስተም እቃዎች ላይ የማርጀት ሂደት (depreciation) ከሚገባው በላይ እንዲፋጠን እንደሚያደርግ መታወቅ አለበት፤ ተገቢው ገቢ እንዳይሰበሰብ ከማድረጉም በተጨማሪ፡፡ በብዙ ባለሙያዎችና ባለሀብቶች እንዲሁም ድርጅቶች ተደጋግሞ እንደተገለፀውም፣ የኢኮኖሚ እንቅስቃሴውን በተወሰነ መጠን የማቀዝቀዝ ውጤቱ ሳይረሳ፣ እነዚህ ከፍተኛ ችግሮች በዘርፉና በኢኮኖሚው ላይ የሚያስከትሉትን ጉዳይ ለመቅረፍ የኃይል ዘርፋችን የችግር አያያዝ (Crisis/Problem Management) የተዳከመበትና የተዘበራረቀበት ምክንያት ምንድን ነው? ወይም በቀላል አማርኛ ችግሮቹን በተረጋጋ እጅ ለመፍታት ያልተቻለበት ምክንያት ምንድን ነው? የሚለው ጥያቄ መልስ ማግኘት ይኖርበታል፡፡

        ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት እጅግ በጣም ክፉ ሚስት የነበረችው ገበሬ ነበረ፣ ይባላል፡፡ ይህች ሚስቱ ማታ ከእርሻ ተመልሶ፣ ሞተር ቀንበሩን ሰቅሎ ገና እፎይ ሳይል እንዲህ ትለዋለች -
“መጣህ፤ በል ምግቡን አሙቀው”
“እሺ የእኔ እመቤት” ብሎ ፍቅሩን ጭምር ገልፆላት፣ወጡን ምድጃ ላይ ይጥዳል፡፡
“በል ና እግሬን ደህና አርገህ እንድታጥበኝ ውሃ አሙቅ”
“እሺ” ይልና ውሃውን ጥዶ ጣባውን ያቀርባል፡፡ ከዚያም ውሃው ሲሞቅ እግሯን ያጥባል፡፡
“በል እንጀራ ከመሶብ አውጣ፡፡ ወጡን በሳህን አቅርብ” ትለዋለች፡፡
“እሺ የእኔ ቆንጆ” ይላል፡፡ ይበላሉ፡፡
“ጀርባዬን በስብ እሽልኝ” ትለዋለች፡፡
ይሄንንም ያደርጋል፡፡
ጠዋት ቁርስ አቀራርቦ አልጋው ላይ እንዳለች ባፍ ባፏ ያጐርሳታል፡፡ ከዚያ ሞፈር ቀንበሩን አውርዶ፣ በሬዎቹን ጠምዶ ወደ እርሻው ይሄዳል፡፡
ህይወት እንዲህ ይቀጥላል፡፡
አንድ ቀን ባለቤቱ በድንገት ታመመች፡፡ ከላይ ከታች አጣደፋት፤ትኩሳቷ በረታ፡፡ ሌሊቱን አረፈች፡፡
አዝኖ አልቅሶ በሥርዓት አስቀበራት፡፡
ከባለቤቱ ሞት በኋላ ሚስት ሳያገባ ብዙ ዓመታት አለፉ፡፡ በኋላ አገሬው ሸምግሎት ሌላ ሚስት እንዲያገባ ተደረገ፡፡
ይህቺኛዋ ሚስቱ የቀድሞዋ ሚስቱ ፍፁም ተቃራኒ ሆነች፡፡ ደግ የደግ መጨረሻ፤ ታዛዥ የታዛዥ መጨረሻ!!
“እግርሽን ልጠብሽ?”
“ምን ሲደረግ! እኔ ነኝ እንጂ እማጥብህ!”
“ምግብ ላቅርብ?”  
“ምን ሲደረግ እኔ የት ሄጄ!” ትላለች፡፡
“በይ ጀርባሽን ልሽሽ!”
“ምን ቆርጦህ እኔ ነኝ እንጂ የማሽልህ!”
ፍቅር በፍቅር ይሆናሉ፡፡
ይህ ገበሬ የዚችኛይቱ መልዐክነት በጣም ስሜቱን ነክቶት ጧት ማታ ትገርመዋለች፡፡
ታዲያ አንድ ማታ እሷ ቀድማው ተኝታለች፡፡
ፀሎቱን ሲፀልይ እንዲህ አለ፤
“አምላኬ ሆይ፤ ከዚች እጅግ ደግ ከሆነች ባለቤቴ የበለጠች የምትመጣ ከሆነ ምነው እቺም በሞተች!!”
***
Human wants are unlimited ይላል በኢኮኖሚ ንድፈ - ሀሳብ አኳያ ፋና - ወጊ ከሆኑት ሊቃውንት አንዱ የሆነው  Adam Smith (አዳም ስሚዝ)፡፡ ሰው በቃኝ አያቅም እንደ ማለት ነው - ከላይ እንዳየነው ገበሬ፡፡ የመጨረሻውን ሀብት፣ የመጨረሻውን ፍቅር፣ የመጨረሻውን ረዥም ዕድሜ ቢሰጠው በቃኝ አለማለት የሰው ልጅ ጠቅላይ - ባህሪ ነው፡፡ ከዚህ የባሰ የሚስገበገቡ፤ በመመዝበር፣ በመስረቅና በመሞሰን የተካኑ ሰዎችን ማሰብ ያስደነግጣል - ይብስም ያሰጋል!
ሮበርት ግሪን የተባለው ድንቅ ፀሐፊ እንዲህ ይለናል፡-
“አንዳች የሀገር ችግር ጠሎ ጠሎ bአንድ ነጠላ ጠንካራ ግለሰብ ምክንያት የመጣ ሊሆን ይችላle፡፡ ያ ግለሰብ ዋና በጥባጭ፣ ዋና ትዕቢተኛ፣ ዋናው መልካሙን ሁሉ መራዥ ይሆናል፡፡ እንዲህ ያሉትን ሰዎች የመንቀሳቀስ ዕድል ከሰጠሃቸው ብዙዎች ተከታዮችና በእነሱ ተፅዕኖ ሥር የሚወድቁ ሰዎች ተፈጠሩ ማለት ነው፡፡ በእነሱ አማካኝነት የሚባዛውንና የሚራባውን ችግር በጭራሽ ጊዜ መስጠት አያስፈልግም፡፡ በጭራሽ መደራደር አያስፈልግም፡፡ የማይመለሱ፣ የማይቀለበሱ፣ የማይድኑ ናቸውና፡፡ በማራቅ ወይ በማጥፋት ብቻ ነው ተፅዕኗቸውን ማሟሸሽ ወይም መገላገል የሚቻለው፡፡ የችግሩን ሥረ መሰረት ፈልገህ ምታ፤ ከዚያ አጃቢው መንጋ ይበተናል”
እንዲህ ያሉ ሰዎች መናኸሪያ አንድም ቢሮክራሲው፣ አንድም ደግሞ የስልጣን መንበር ዙሪያ ነው፡፡ አንዱን አውራ በመፍራት አያሌ የተነካኩ ሰዎች እንዳይጠየቁ፣ እንዳይጋለጡ ማድረግ ይዘወተራል፡፡ ተጠያቂዎቹ ሰዎች ብጤዎቻቸውን በንፍቀ - ክበባቸው ስለሚኮለኩሉ የአይነኬነት ምህዋራቸውን ያሰፋሉ፡፡ ማንም እንዳይደርስባቸው አጥር ያጥራሉ፡፡ ይሄን አይነት የተተበተበ የወገናዊነት፣ የእከክልኝ ልከክልህ፣ “እኔ - እያለሁ - ማንም - አይነካህ”፣ “ማ - ባቀናው - አገር - ማን - ይኖራል?” የሚል ባህል ዋና የመሰንበቻ ሙስና ነው፡፡ ከመንጋው በፊት አውራውን ማግኘት ግድ የሚሆነው ለዚህ ነው፡፡ የቢሮክራሲ መረብ ከአስተዳደር ብልሹነት እስከ ፖለቲካዊ ዝቅጠት መቀፍቀፊያ ኢንኩቤተር ነው፡፡ በዝምድና መስራት፣ በፖለቲካ መሞዳሞድ፣ ንፁህ መስሎ ባደባባይ መጮህ፣ የአስተሳሰብ ንቅዘት፣ በመፈክር የልብ ባዶነትን መሸፈን ወዘተ … ነቀርሳ - አከል የሀገራችን ችግሮች ናቸው፡፡ ችግሮች በዋሉ ባደሩ ቁጥር ማጎንቆላቸው አይቀሬ ነው፡፡ አልፈው ተርፈው መለመዳቸውና “ይሄ‘ኮ ያለ ነገር ነው!” መባላቸው በተደጋጋሚ የታየ ነገር ነው፡፡ በግለሰብ፣ በቡድን አሊያም በፓርቲ ደረጃ የዕብጠትና የማናለብኝ አባዜ ሌላው ያፈጠጠ ጦር ነው፡፡ ይህን ይዞ ዲሞክራሲያዊ ጎዳና ላይ ነኝ ማለት ቢያንስ ራስን ማሞኘት ነው - “እኔ ባልኩህ መንገድ ብቻ ሂድ - አለዛ …” እያሉ ዲሞክራሲ የለምና!
ሌላው አሳሳቢ ችግር በአንድ ምህዋር ላይ መሽከርከር ነው፡፡ ፎቶ - ካሜራ ዐይን ውስጥ ያለ ሰው እራሱን አያይም ይባላል፡፡ ከምህዋሩ ወጥቶ በአንድ ቅኝት የሚሽከረከረውን ሰው ማየት ያስፈልጋል፡፡ ለውጥ ለማምጣት የአዘቦቱን ነገር መተውና በተለየ ዐይን ማየት (out of the box እንዲሉ) ያስፈልጋል፡፡ ከቶውንም ዐይናችንን ሳናሽ መፈፀም፣ በተግባር ማሳየት ያለብንን የዲሞክራሲያዊ መብቶች ጉዳይ፣ የሰብዓዊ መብቶች ጉዳይ፣ የፍትሕ መጓደል ጉዳይ፣ ከሁሉም በላይ ደግሞ ነገ ዛሬ ማለት የሌለብንን የሙስናና የማጭበርበር ጉዳይ ለአፍታም ቢሆን ሳይዘገይ በግልፅ እርምጃ ወስደን ማሳየት አለብን፡፡ አለበለዚያ “ከሞትና ከህይወት የቱን ትመርጣለህ?” ቢባል፤ ሲያስብ ዘገየ፤ እንደሚባለው ይሆናል!

“የፓርቲዎች ትብብር” በሚል ስያሜ በዘጠኝ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የተመሠረተው ቡድን፤ “ነፃነት ለፍትሃዊ ምርጫ” በሚል መርህ የተለያዩ የተቃውሞ እንቅስቃሴዎች ለማድረግ መዘጋጀቱን አስታውቋል - ምንም እንኳን ያለፈው ሳምንት ዕቅዱ ሳይሳካ ቢቀርም፡፡ ዛሬና ነገ ለመጀመሪያ ጊዜ በሚያካሂደው የ24 ሰዓት የአዳር ተቃውሞ፣ እስከ 150ሺ ሰዎች ይሳተፋሉ ብሎ እንደሚጠብቅም ትብብሩ ጠቁሟል፡፡ እንዲያም ሆኖ ግን ተቃውሞውን በመስቀል አደባባይ ለማካሄድ ከአዲስ አበባ መስተዳድር ፈቃድ አላገኘም፡፡ ዓለም አቀፍ ድርጅቶችና የመንግስት ተቋማት የሚበዙበት እንዲሁም ልማት የሚካሄድበት ሥፍራ በመሆኑ ቦታውን እንድንቀይር በደብዳቤ ተገልጾልን ነበር ያሉት የሰማያዊ ፓርቲ ፕሬዚዳንትና የትብብሩ ሊቀመንበር ኢ/ር ይልቃል ጌትነት፣ ተቃውሞውን የሚያደርጉት መንግስት እንዲሰማቸው በመሆኑ የቦታ ለውጥ እንደማያደርጉ ለመስተዳድሩ መግለጻቸውን ተናግረዋል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ፤ ከኢንጂነር ይልቃል ጋር ባደረገው ሰፊ ቃለ ምልልስ፤ ዛሬና ነገ እናካሂደዋለን ባሉት የአዳር ተቃውሞ፣ በግንቦቱ ምርጫና በሰማያዊ ፓርቲ የፖለቲካ ስልትና ፖሊሲ ዙሪያ አነጋግሯቸዋል፡፡  
ከኢንጂነር ይልቃል ጌትነት ጋር የተደረገ ቃለ ምልልስ
መስተዳድሩ ለመስቀል አደባባይ የተቃውሞ  ስብሰባ እውቅና አልሰጠም  

  • ትብብሩ፤ “እውቅና የመስጠትና የመከልከል ሥልጣን የለውም” ብሏል
  • “አባቶች ይፀልዩ ስንል ኢህአዴግ በፀሎት ይወርዳል ማለት አይደለም”
  • መንግስት አልሰማ ስላለን፣ ብርድ እየመታን ጥያቄያችንን እናቀርባለን

        ትብብሩ በቅርቡ በሰጠው መግለጫ ለ1 ወር የሚዘልቅ “ነፃነት ለፍትሃዊ ምርጫ” የሚል የተቃውሞ መርሃ ግብር እንደቀረፀ አስታውቆ ነበር፡፡ እስካሁን ባለው ሂደት ምን ስኬትና ኪሳራ ገጠማችሁ?
ስኬት እንግዲህ አተያዩ ይለያያል፡፡ ለምሳሌ ሚዲያውን በማግኘት፣ በአጠቃላይ ለህብረተሰቡ ተደራሽ በመሆን እንዲሁም ለዓለም አቀፉ ህብረተሰብና ለሚመለከተው አካል ጥያቄያችን ምን እንደሆነ በማሳወቅ በኩል ከፍተኛ ተቀባይነት አግኝተናል፤ ስኬታማ ነበርን ማለትም ይቻላል፡፡ በእስካሁኑ እንቅስቃሴያችን የአለማቀፉን ማህበረሰብም ሆነ የሚዲያዎችን ቀልብ መያዝ ችለናል፡፡ ሌላው ያቀድናቸው የአደባባይ ስብሰባዎች ነበሩ፤ ነገር ግን ይሄን ለማድረግ ስንነሳ የመንግስት ጫና ተባባሰ፡፡
የጫናው መብዛት ነፃነት የለም የሚባለው ትክክል መሆኑን ያሳያል፤ መንግስትም ፈርቷል ማለት ነው፡፡ ምንም አይነት የተለየ አማራጭ ማየት ስለማይፈልግ፣ ከእለት እለት ሸምቀቆውን እያጠበቀ መጥቷል፡፡ ይሄም ከምርጫው በፊት ነፃነት እንደሚያስፈልግ የሚያረጋግጥ ነው፡፡ መንግስት የአደባባይ ስብሰባዎችን ለማሰናከል የሄደበት ርቀት፣ ጥንካሬያችንን እንዲሁም ጥያቄያችን ትክክል እንደነበር ያሣያል፡፡ ከምርጫው አንዳች ነገር በቀላሉ ይገኛል ብሎ የሚገምት የዋህ ካለም፣ ምንም ነገር እንደማይገኝ የተረጋገጠበት ሂደት ነው፡፡
አሁን ህዝቡም ከእኛ ጋር መሆን እንዳለበት የተገነዘበ ይመስላል፡፡ እኛም የመንግስት ፍርሃትና ጭንቀት መጨመሩን ተገንዝበናል፡፡ ይሄ ፍርሃቱ ወደ በለጠ ጭካኔ ይወስደዋል ወይስ ህዝቡ እንዲተነፍስ ነፃነቱን ለቀቅ ያደርግለታል? በራሱ በኢህአዴግ ምርጫ መልስ የሚያገኝ ጥያቄ ነው፡፡
በዘመቻ መልክ ተቃውሞ ከማድረግ ይልቅ በድርድር ጫና መፍጠር የተሻለ እንደሆነ የሚገልጹ ወገኖች አሉ፡፡ በእናንተ እምነት ከመደራደርና በዘመቻ የአደባባይ ተቃውሞ ከማድረግ  የትኛው ተጨባጭ ውጤት ያመጣል ትላላችሁ?
የፖለቲካ ድርድር የሚመጣው ከነባራዊ ሁኔታዎች ተነስቶ ነው፡፡ ከድርድሩ ሁሉም ሃይል እጠቀማለሁ ብሎ ሲያስብ ነው፡፡ ወደ ድርድር ለመግባት የሚቻለው በዚያኛው ወገን ያለው አካል አማራጭ የፖለቲካ ሃይል መሆናችንን ሲያምንበትና እውቅና ሲሰጠን ነው፡፡ ለመደራደር የድርጅት የድጋፍ ሃይልና ተቀባይነት ወሳኝነት አለው፡፡ በመሠረታዊ ሃሳብ ደረጃ ግን እኛ ወደ አደባባይ ለመውጣት ከማቀዳችን በፊትና ስምምነቱም ከመፈረሙ አስቀድሞ 12 ፓርቲዎች ሆነን፣ ለምርጫ ቦርድ መጀመሪያ በደብዳቤ የጠየቅነው ድርድር ነው፡፡ ከጊዜ ሠሌዳው በፊት ቦርዱ ገለልተኛነቱ እንዲረጋገጥ የሚመለከታቸውን ወገኖች ያወያይ ብለን ጠይቀን ነበር፡፡
ነገር ግን በመንግስትም ሆነ በምርጫ ቦርድ በኩል ለጥያቄያችን መልስ መስጠት አልተፈለገም፡፡ እኛ ቲያትረኛ ወይም የአርት ሰዎች አይደለንም፤ ዝም ብለን መጮኽ ምን ያደርግልናል?
የፖለቲካ ግብ አለን፤ ግባችንን ከዳር ለማድረስ መወያየት እንዳለብን አምነን፣ በዚያ መንገድ ተጉዘን ነበር፤ ሆኖም አልተሳካም፡፡
ምርጫ ቦርድ ገለልተኛ አይደለም እያላችሁ በምርጫው ሂደት እንደምትሳተፉ ገልፃችኋል፡፡ ባላመናችሁበት ጉዳይ ላይ መሳተፉ አንዳንዴ ራሳችሁ እንደምትሉት “ኢህአዴግን” ወይም ሂደቱን ማጀብ አይሆንም?
በፖለቲካ ውስጥ ወቅታዊ መሆንና ያለውን እድል ተጠቅሞ የጠበበውን እያሰፉ መታገል ተገቢ ነው፡፡ አኩራፊና ተስፋ ቆራጭ ህብረተሰብ፣ ለዲሞክራሲ ስርአት ግንባታ አይሆንም፡፡ ዲሞክራሲ የሚመነጨው ከህዝብ ነው፡፡ ዲሞክራሲ ከውጤት በላይ ለሂደት ይጨነቃል፡፡ ለምሣሌ ሰሞኑን የምርጫ ምልክት ውሰዱ ተብሏል፤ አንወስድም ብለን ብንቀመጥና ጥርና የካቲት ላይ ነገሮች ቢስተካከሉ ተመልሰን ምልክት የምንወስድበት አማራጭ የለም፡፡ ስለዚህ በሂደቱ መቆየት ነገሮቹ ከተስተካከሉ፣ ካለንበት ቦታ ሆነን ለመቀጠል ያስችለናል፡፡ አሁን ባለበት ሁኔታ ግን እንኳን ምርጫ ሊታሰብ፣ ሰው ተሰብስቦ መነጋገር አልተቻለም፡፡
ኢህአዴግ በህዝብ ዘንድ የነበረው ተቀባይነት ስላለቀ፣ ያለ ማፈርና ያለ ይሉኝታ የሚችለውን ሁሉ እያደረገ ነው፡፡ በዚህ በኩል ምንም ተስፋ የሚሰጥ ነገር የለም፡፡ ግን ህዝቡ ለነፃነቱ የቆመ መሆኑን ካረጋገጠ፣ ብዙ ነገሮች ይለወጣሉ የሚል እምነት አለን፡፡ አሁን ባለው ሁኔታ ኢህአዴግ ስልጣን የሚያሳጣው ነገር እንዳለ ተገንዝቧል፡፡ ስለዚህ ስልጣኑን ለማስጠበቅ ይሟሟታል፡፡ ነገር ግን ህዝቡ “ስልጣኑ የኔ ነው፤ እፈልገዋለሁ” ካለ፣ ኢህአዴግ ሳይወድ በግድ ወደ ድርድር ይገባል፡፡ በአጠቃላይ በምርጫው ሂደት የምንሳተፈው ሂደቱን ለማስተካከል እንጂ በአሁኑ አያያዝ ነፃ ምርጫ ይካሄዳል የሚል እምነት የለንም፡፡
እስቲ ያለፉትን ሁለት አገራዊ ምርጫዎች ከዘንድሮ  ቅድመ ምርጫ ሂደት ጋር ያነፃፅሩልኝ?
በቀላል ቋንቋ ሂደቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተበላሸ ነው፡፡ ለምን እንዲህ ሆነ ብለን ስንመለከት፤ በኢህአዴግ የውስጥ ባህሪ ምክንያት የመጣ ነው፡፡ “አምባገነን”ና የፈለግሁትን አደርጋለሁ ብሎ የተነሳ አገዛዝ ነው፡፡ ነገር ግን በ1997 ምርጫ የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትር በአለማቀፍ ደረጃና በአፍሪካ ጉዳዮች ከፍ ከፍ ብለው የታዩበት ወቅት ነው፡፡ በቶኒ ብሌር የተመሠረተው የአፍሪካን ፓርትነርስ ኢንሼቲቭ ሰብሳቢ ሆነው ነበር፣ በG-8 እና G-20 ስብሰባ ላይ ይጠራሉ፣ የአፍሪካ የአዲሱ ትውልድ መሪ እየተባሉ ይሞካሻሉ፡፡ ያ ጊዜ ደግሞ የተቃዋሚው ሃይል ደካማና የተከፋፈለ ነው የሚል ግምት ስለነበራቸው፣ ምርጫውን የራሳቸውን ክብር ለማሳደግ ሲሉ ክፍት አደረጉት -“እንከን የለሽ ምርጫ” አሉት፡፡ በዚያች በተከፈተች ቀዳዳም የኢትዮጵያ ህዝብ አይቶት በማያውቀው ሁኔታ የተማሩና በማህበራዊ ደረጃቸው የተከበሩ ሰዎች ዘው ብለው ወደ ምርጫው ገቡበት፡፡ የኢህአዴግ ተሳስቶ በሩን መክፈትና የነዚያ ትላልቅ ሰዎች በምርጫው ላይ መሳተፍ፣ ያልተጠበቀ ክስተት ፈጠረ፡፡ ያኔ ኢህአዴግ ተደናገጠ፡፡ ከዚያም በድንጋጤ በሩን ጥርቅም አድርጎ መልሶ ዘጋው፡፡ ተቃዋሚዎችን እስር ቤት ከተተ፣ አፋኝ ህጐችን ማውጣት ጀመረ፡፡ በዲሞክራሲ መቀለድ አይቻልም ተባለ፡፡
ኢህአዴግ ራሱን አውራ ፓርቲ ብሎ ሰየመና በ99.6 በመቶ ድምጽ ማሸነፉን አበሰረን፡፡ ይሄ ውጤት “ዲሞክራሲያዊ ነኝ በሚል ስርአት ውስጥ የማይጠበቅ ነበር፡፡ ውጤቱ ድንጋጤ ሲፈጥርባቸው፣ እድገትና ትራንስፎርሜሽን የሚል እቅድ አመጡ፡፡ ያ የተለጠጠ እቅድ ግን  መፈፀም የማይቻል ሆነ፡፡ የሰብአዊ መብት ጥቃቱ ተባብሶ ቀጠለ፣ የሃይማኖት ጣልቃ ገብነት፣ የዜጐች መፈናቀል፣ ስራ አጥነት-- እያየለ  መጣ፡፡ በዚህ የተነሳ አሁን ህዝቡ “ከኢህአዴግ ውጪ የትኛውም አካል ይምጣልኝ” የሚልበት ደረጃ ላይ ደርሷል፡፡ ይሄን ደግሞ ኢህአዴግም ህዝቡም ተገንዝበውታል፡፡ ከፍርሃቱ የተነሳም ተቃዋሚዎችን ወደ ማፈን ተሸጋግሯል፡፡ ይሄኛውን ዘመን ለየት የሚያደርገው፣ ህዝቡ ለውጥ መፈለጉ ነው፡፡ ኢህአዴግ አሁን በመርህ ደረጃ  ተሸንፏል፡፡ የመውጫ መንገድ የማጣትና የመፍራት ነገር ነው የሚታየው፡፡
ኢህአዴግ በመርህ ደረጃ ተሸንፏል ከተባለ፣ ሰማያዊ ፓርቲን ጨምሮ አሁን ያሉት ተቃዋሚዎች በምርጫው ውጤት ማምጣት ይችላሉ?
ስለ ሌሎቹ ፓርቲዎች ብዙ ማለት አልችልም፡፡ ሰማያዊ ግን የሚቻለውን ሁሉ እየጣረ ነው፤ ከነ አስቸጋሪ ሁኔታዎቹ ማለቴ ነው፡፡ ወጣት ሃይል ወደ ፖለቲካው እንዲገባ እያደረገ ነው፤ በውጪም በሀገር ውስጥም ያሉ ዜጐች ፖለቲካውን እንዲቀላቀሉ እየተጋ ነው፡፡ ግን ሀገሪቱ ካለችበት ሰፊ ችግር አንፃር “በቂ ነው ወይ?” ከተባለ፣ ጥርጥር የለውም በቂ አይደለም፡፡ ነገር ግን በእኔ እምነት መንገዱን ይጠርገዋል ብዬ አስባለሁ፡፡
የምርጫው ሂደት እናንተ በምትፈልጉት መንገድ ቢሆን፣ አሁን ባላችሁ አቋም የግንቦቱን ምርጫ የምታሸንፉ ይመስልዎታል?
ማሸነፍ ብቻ አይደለም፤ ያኔ ኢህአዴግ ያስመዘገበው 99.6 በመቶ ውጤት፣ ዞሮ እኛ ጋ እንደሚመጣ ነው የምናስበው፡፡ ምክንያቱም ምህዳሩ ከተከፈተ “ለኢህአዴግ ልቡን ሰጥቶ የሚመርጠው ማን ነው?” ተብሎ ቢፈለግ አይገኝም፡፡ ሙስሊሙ፣ ክርክስቲያኑ፣ ወጣቱ፣ የተማረው ያልተማረው ፣ የመንግስት ሠራተኛው… የትኛው ነው የሚመርጠው? በእኔ እምነት የራሱም አባሎች ከዚህ በኋላ አይመርጡትም፡፡ ስለዚህ ኢህአዴግ የተሸነፈ ድርጅት ነው፡፡ መንገዱ ከተከፈተ ምንም ጥርጥር የለውም እናሸንፋለን፡፡ ለዚያም የሚሆን ነገር እንደ አቅማችን እየሠራን ነው፡፡
ሠማያዊ ፓርቲ  የተቃውሞ ሰልፍ ከማድረግ ውጪ ህብረተሰቡ ፖሊሲውን እንዲረዳለት ያከናወነው ሥራ አለ ብለው ያምናሉ?
የፖለቲካ ፓርቲ ሲኮን አንደኛ በስልጣን ላይ ያለ መንግስት የተሳሳታቸውን ነገሮች እንዲያርምና ማሻሻያ እንዲያደርግ ግፊት የማድረግ ስራ ነው ያለው፡፡ ሁለተኛ ደግሞ መንግስት ቢሆን የሚሠራውንና ያለውን አማራጭ ማቅረብ ነው፡፡ ሁለቱም ተለያይተው የሚታዩ አይደሉም፡፡ ተቃውሞን አንዳንዶች እንደ መንቀፍና እንደ ማጥላላት ያዩታል፤ ነገር ግን ዲሞክራሲያዊ በሆኑ ሀገሮች የመንግስትን ጉድለቶች የማስታወሻ ደንበኛ ስራ ነው፡፡ ፖሊሲውን ማስተዋወቅ በስፋት የሚሠራው በቃለ መጠይቅ፣ በስልጠና፣ በአዳራሽ ስብሰባዎች ነው፡፡ ሰማያዊ ፓርቲ ከሌሎች በተሻለ ሁኔታ  ፖሊሲውን በዚህ መልኩ አስተዋውቋል፡፡
በሁሉም ጉዳዮች ላይ ያሉንን ፖሊሲዎች ምሁራንን በሚገባ አወያይተናል፡፡ በፓርቲው ልሣን አስተዋውቀናል፡፡ ሁልጊዜ ቅዳሜ በፖሊሲያችን ላይ ውይይት አለን፡፡ ኢህአዴግ ራሱ ፖሊሲያችንን ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ ለዚህ ነው የብሔር ብሔረሰቦችን ሉአላዊነት የማይቀበሉ፣ የድሮ ስርአት ናፋቂዎች የሚለን፡፡ እንደውም እኛ የምንታማው የአይዲዮሎጂ ቀኖናዊነት ያጠቃቸዋል እየተባልን ነው፡፡
የፓርቲያችሁ ርዕዮተ ዓለም ምንድን ነው?
እኛ “ሞደሬት ሊበራሊዝም” የተሰኘ አይዲዮሎጂ ነው ያለን፡፡ በሂደት መንግስት ከኢኮኖሚ ውስጥ እየወጣ የሚሄድበት ፖሊሲን የሚያበረታታ ነው፡፡ መንግስት በሂደት ከኢኮኖሚው እጁን እየሰበሰበ ውስንነት እንዲኖረው የሚያደርግ ነው፡፡ የኢህአዴግ ፖሊሲ ደግሞ መንግስት ሁሉን ነገር ይቆጣጠር የሚል ነው፡፡ በኛ ፖሊሲ መሬት የግል ይሆናል፣ ፌደራል ስርአቱ ዘርን መሠረት ያደረገ ብቻ ሳይሆን አኗኗርን፣ ጂኦግራፊያዊ አቀማመጥ የመሳሰሉትን መሠረት ያደረገ ይሆናል፡፡ በፓርላማ አወቃቀር፣ የላይኛውና የታችኛው ምክር ቤቶች እንዲሁም ሴኔት ይኖራሉ፤ የሚፈጠረው ስርአት ፕሬዚዳንታዊ ይሆናል፡፡ ከዚህ ውጭ ብዙ ዝርዝር የፖሊሲ ጉዳዮች አሉን፡፡
ህዳር 7 ቀን ልታደርጉት በነበረው የአደባባይ ስብሰባ ከከተማ አስተዳደሩ ጋር እሰጥ አገባ ውስጥ እንዴት ገባችሁ? በወቅቱ የተወዛገባችሁበት ጉዳይስ ምንድን ነው?
ሰልፍ ስናደርግ የደብዳቤ ምልልሱ ሁልጊዜም አለ፡፡ ወይ ቦታና ቀን ቀይሩ ይላሉ ወይ የፀጥታ ሃይል የለንም ይላሉ፡፡ እንዲህ ሲሉ እኛም መልሳችንን እንጽፋለን፡፡ አሣማኝ በሆነ መልኩ መልስ ከሰጡን ችግር የለብንም፤ ነገር ግን ደብዳቤውን ተቀብለው መልስ ካልሰጡን ማወቃቸው ብቻ በቂ ነው፡፡ ሌላ እወቁልን አትወቁልን የሚል ጣጣ ውስጥ መግባት አያስፈልገንም፡፡ ሰልፍ ማድረግ ህገ መንግስታዊ መብት ነው፡፡ ግን መብታችንን ስንጠቀም የሌላውን መብት እንዳንጐዳ የፀጥታ ሃይል መመደብ የመሳሰሉትን ማድረግ ይችላሉ፡፡ ይህ ከሆነ የሚያጣላን ሌላ ነገር የለም፡፡ መከልከል ከተፈለገ ግን ምንም ማድረግ ይቻላል፡፡
ኢህአዴግ የሃሰት ወንጀል እየፈበረከ የፓርቲ አመራሮችን በሚከስበት አገር፣ ሰማያዊ ፓርቲ ህግ ተላልፎ ምህረት ይደረግለታል ብሎ ማሰብ የዋህነት ነው፤ ወይ ኢህአዴግ ካልሆንን በስተቀር፡፡ እንደው “ሰባሁ እረዱኝ” አይነት ነገር ብናደርግ ምን ሊመጣ እንደሚችል ማሰብ ያስፈልጋል፡፡
ችግሩ ምንድን ነው? መንግስት እስከ መጨረሻው ቢሄድ የተለዋወጥነው ደብዳቤ ሃቁን ያወጣዋል፤ ያንን ስለሚያውቅ ነው እኛ እንደ ጀብደኛ እንድንታይ ከሚያደርግ ፕሮፓጋንዳ ያለፈ እርምጃ ሳይወስድ የሚቀረው፡፡
ባለፈው ሳምንት እሁድስ በምን ምክንያት ነው የአደባባይ ስብሰባው ያልተካሄደው? ጥያቄያችን ተቀባይነት ቢያጣም ለስብሰባው ከመውጣት ወደ ኋላ አንልም ብላችሁም ነበር ..
ደብዳቤውን በፖስታ ቤት ላክን፣ የሚቀበለው አጣ፣ መልስም እኛ ጋ አልመጣም፡፡ እነሱ ጋ ስንሄድ ደርሶን በፖስታ ቤት መልሰነዋል አሉን፡፡ ሆኖም መልሰናል ያሉት ደብዳቤ ለኛ አልደረሰንም፡፡ በዚህ ሂደት ውስጥ እያለን ተቃውሞ መውጣት ተገቢ አይሆንም፡፡ ምንም አይነት ህጋዊ መሠረት የለንም ማለት ነው፤ ስለዚህ በመጣው ሰውም ሆነ በፓርቲዎቹ ላይ እርምጃ ቢወሰድ አላስፈላጊ መስዋዕትነት ተከፍሎ ትግሉን ወደ ኋላ ሊመልሰው ይችላል፡፡
እኛ ዋጋ ስንከፍልም አንዲት ህጋዊ ልታደርገን የምትችል ነገር ይዘን ነው፡፡ ህጋዊ የሚያደርገንን ነገር ይዘን እንዳንወጣ ካሰብነው ቀን አሣልፈው በ22 ደብዳቤውን አምጥተውልናል፡፡ እሁድ ለማድረግ ለተጠየቀ ስብሰባ ሰኞ መልስ ተሰጠ ማለት ነው፡፡ ኢህአዴግ ዲሞክራሲ አለ፣ ምርጫ አለ፣ እያለ የአፍሪካ መዲና በሆነችው አዲስ አበባ ላይ ሰው ተሰባስቦ መነጋገር ካልቻለ፣ ገጠር ደግሞ ምን ሊሆን እንደሚችል መገመት አያቅትም፡፡ በዚህ ሁኔታ ነጻ ምርጫ ይኖራልን? የሚለውን ጥያቄ ለህዝቡም ሆነ ለኢህአዴግ በተዘዋዋሪ መንገድ እያቀረብን መሆኑ መዘንጋት የለበትም፡፡ ኢህአዴግን በዚህ መንገድ ማጋለጥም የተቃዋሚዎች አንዱ ስራ መሆኑ ሊታወቅ ይገባል፡፡ ዛሬ እና ነገ  ለሚደረገው የአዳር ስብሰባ ግን አስፈላጊውን ዝግጅት የጨረስን በመሆኑ ይካሄዳል፡፡
ጥያቄያችሁ ተቀባይነት አግኝቷል ማለት ነው?
ደብዳቤያችንን በፖስታ ቤት በኩል አድርሰናል፡፡ እንዲህ ያደረግነው መስተዳድሩ በአካል ደብዳቤ ይዘን ስንቀርብ ስለማይቀበል ነው፡፡ አሁን ደብዳቤው እንደደረሳቸው ከፖስታ ቤት ማረጋገጫ አግኝተናል፡፡ ደብዳቤው ከደረሳቸው ህጋዊ ነን ማለት ነው፡፡
ለደብዳቤያችሁ ምላሽ ተሰጥቷችኋል?
አዎ! መልስ ሰጥተውናል፤ እኛም የመልስ መልሱን ልከንላቸዋል፡፡
ምንድን ነው የተሠጣችሁ መልስ?
የመረጣችሁት አካባቢ ልማት የሚካሄድበት፣ የመንግስት ተቋማት የሚበዙበት ነው፤ አለማቀፍ ድርጅቶች አሉበት የሚል አስተያየት ሰጥተው “አልፈቀድንም፤ እውቅና አልሰጠንም” ብለዋል፡፡ እኛ ደግሞ አዋጁን ጠቅሰን “እውቅና መስጠት ያለ መስጠት የእናንተ ስልጣን አይደለም፡፡ ቀንና ቦታ ቀይሩ ማለት እንጂ እውቅና ሰጪ መሆን አትችሉም፤ በመንግስት ተቋማት ስለምታልፉ ለተባለው በመሠረቱ ሰልፍ የሚደረገው የመንግስት አካላት እንዲሰሙት ነው” ብለን መልስ ልከናል፡፡ “በታሰበው ጊዜና ቦታ ሰልፉንና ስብሰባውን እንደምናካሄድ አውቃችሁ፣ አስፈላጊውን ትብብር እንድታደርጉልን” ብለን ጠይቀናቸዋል፡፡
የ24 ሰአት ሰልፍ እናደርጋለን ስትሉ ምን ማለት ነው?
እንግዲህ እስከ ዛሬ ብዙ ጮኸናል፤ ሰሚ አላገኘንም፡፡ አሁን ደግሞ ምርጫ ብላችሁናል፤ ምርጫ እንዲኖርም ሆነ ጥያቄዎቻችን መልስ እንዲያገኙ ብርድ እየመታንም ጥያቄ እናቀርባለን፤ ስሙን የሚል አቤቱታ ለማሰማት ነው፡፡ ለሰአታት የምናደርገው ሰልፍ ውጤት ስላላመጣ እዚያው መስቀል አደባባይ አድረን፣ ብርድ እየመታን ድምፃችንን እናሰማለን፡፡ “የምናደርገው ስብሰባ ከዚህ ሰአት እስከዚህ ሰአት ነው፤ ከዚያ ውጪ ያለውን ሃላፊነት አንወስድም” ብለንም ለሚመለከተው አካል አሳውቀናል፡፡
ምን ያህል ህዝብ ይገኛል ብላችሁ ነው የምትጠብቁት?
ከ100ሺ እስከ 150ሺ ህዝብ ይገኛል ብለን እንጠብቃለን፡፡ ለመንግስት አካል ስናመለክትም ይሄን ሁሉ አካትተናል፡፡
ከዚህ በፊት ሰማያዊ ፓርቲ በጠራቸው ሰልፎች ላይ የተገኘው ከፍተኛ የተሳታፊ ቁጥር ስንት ነበር?
አንዳንዶች ከ70 ሺ እስከ 100 ሺ በማለት ዘግበውታል፡፡ ነገር ግን በ10 ሺዎች የሚገመቱ እንደተገኙ መገመት ይቻላል፡፡
እንዳሰባችሁት በ100 ሺ የሚቆጠር ህዝብ ቢመጣ የምግብ፣ የመፀዳጃና ሌሎች  አገልግሎቶች ተዘጋጅተዋል?
ሁሉም ሰው ቀለል ያሉ ደረቅ ምግቦችንና የታሸጉ ውሃዎችን በየግሉ ይዞ እንዲገኝ በመግለጫዎቻችን ስናስታውቅ ከርመናል፡፡ መፀዳጃ ቤትን በተመለከተ ሰው እዚያው ታግቶ ይውላል አልተባለም፡፡ ከስብሰባው እየወጣ አገልግሎት በሚገኙባቸው ቦታዎች ተጠቅሞ መመለስ ይችላል፡፡ ተጨማሪ ምግብና መጠጥ የሚፈልግም እንደዚያው ማድረግ ይችላል፡፡
የሃይማኖት አባቶች በፀሎት ያስቡን--- ስትሉ ምን ማለታችሁ ነው?
የኢትዮጵያ ህዝብ አማኝ ነው፡፡ የሃይማኖት አባቶች ስለ ሃገራቸው ይፀልዩ ለማለት ነው እንጂ ፀሎት ተደርጐ ኢህአዴግ ይወርዳል ማለት አይደለም፡፡ አላማው የሰውን ልብና አዕምሮ ማግኘትና የውይይት አጀንዳ ማድረግ ነው፡፡ በየቤተክርስቲያኑ ወይም በየመስጊዱ ምህላ ይደረግ ለማለት አይደለም፡፡

40 ገደማ የሚሆኑ የዲላ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነትና ኮሙኒኬሽን ትምህርት ክፍል የሶስተኛ ዓመት ተማሪዎች ከትናንት በስቲያ የአዲስ አድማስ ጋዜጣ ዝግጅት ክፍልን ጐበኙ፡፡
ካዛንቺስ በሚገኘው የአዲስ አድማስ ዝግጅት ክፍል ተማሪዎቹ ለሰዓታት ባደረጉት ቆይታ የዝግጅት ክፍሎቹንና “ዕውቀትና ትጋት የአሰፋ ጎሳዬ መታሰቢያ ቤተ መፃሕፍት”ን የጎበኙ ሲሆን በጋዜጣው የዲዛይን ክፍልም የሌይ አውት አሰራር ማብራሪያ ተሰጥቷቸዋል፡፡
የጋዜጣው ዋና አዘጋጅ ገጣሚ ነቢይ መኮንን፤ ስለ ጋዜጣው አመሰራረትና የ15 ዓመት ጉዞውን የሚመለከት አጭር ገለፃ ያደረገላቸው ሲሆን ስለጋዜጠኝነት ሙያም ከልምዱ አካፍሏቸዋል፡፡
የጋዜጠኝነት ሙያ ከንድፈ ሃሳብ ይልቅ የተግባር ትምህርትን የበለጠ የሚጠይቅ አንደሆነና፣ መረጃዎችን አግኝቶ፣ ሚዛናዊነታቸውን ጠብቆ ለህብረተሰቡ በማድረስ ሂደት የሚያጋጥሙ ችግሮችን ለማለፍ ብርቱ ጥንቃቄ እንደሚያስፈልግ ለተማሪዎቹ ያስረዳው ዋና አዘጋጁ፤ የሙያውን ሥነምግባር ጠብቆ፣ ሁልጊዜም ለማወቅና ለመማር ዝግጁ ሆኖ መገኘት የአንድ ጋዜጠኛ ተግባር ሊሆን ይገባል ብሏል፡፡
በጉብኝቱና በተደረገላቸው ገለፃ መደሰታቸውን የጠቆሙት ተማሪዎቹ፤ ጋዜጣው ሙያዊ ስነ ምግባርን ጠብቆ በመስራት ለዚህ በመድረሱ ከፍተኛ ከበሬታ እንዳላቸው ተናግረዋል፡፡ ባለፈው ዓመትም የዲላ ዩኒቨርሲቲ የጋዜጠኝነትና ኮሙኒኬሽን ትምህርት ክፍል 40 ተማሪዎችን ለተመሳሳይ ጉብኝት መላኩ ይታወሳል፡፡  

* “ብዙ ብር ከፍለን የዓይን ብርሃናችንን አጥተን ተመልሰናል”  -ታካሚዎች
* ከመነሻው የማዕከሉ አደረጃጀት አዋጁን የሚቃረን ነው - - የአዲስ አበባ ጤና ቢሮ
* ማዕከሉ በየዓመቱ የሚታደስ የህክምና አገልግሎት ፈቃድ አልተሰጠውም

             ከአንድ ዓመት ተኩል በፊት የተሻለ የአይን ህክምና ለመስጠት፣ ለኢትዮጵያውያን ሀኪሞች የቴክኖሎጂ ሽግግር እንዲያደርግና በዘርፉ ምርምርና ጥናት እንዲያካሂድ ታስቦ በዘውዲቱ ሆስፒታል ግቢ ውስጥ የተገነባው የህንድ የአይን ህክምና ማዕከል በታካሚዎች ላይ ጉዳት እያደረሰ መሆኑ ተገለፀ፡፡
ጉዳት የደረሰባቸው ታካሚዎች እንደተናገሩት በማዕከሉ በተሰጣቸው ህክምና ሳቢያ የዓይን ብርሃናቸውን አጥተዋል፡፡ በማዕከሉ የሚሰሩ ኢትዮጵያውያን ባለሙያዎች ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት የተሟላ የህክምና ቁሳቁስ፣ በዘርፉ በቂ እውቀት ያላቸው ባለሙያዎችና ደረጃውን የጠበቀ ግንባታ ሳያሟላ የሚሰጠው ጥራቱን ያልጠበቀ አገልግሎት ዜጎችን ለአይነ ስውርነት፣ ለተጋነነ ወጪና ለእንግልት እየዳረገ ነው፡፡
ማዕከሉ ለኢትዮጵያውያን ሃኪሞች የቴክኖሎጂ ሽግግር ያደርጋል ቢባልም ሁሉም የህክምና ቁልፍ ቦታዎች በህንዳዊያን በመያዛቸው እቅዱ እንዳልተሳካና ከስምምነት ውጪ በተጋነነ የደሞዝ ክፍያ ምዝበራ እንደሚፈፀም ተገልጿል፡፡
የአይን ህክምና ማዕከሉ ከተለያዩ ተቋማት ገምጋሚ ተመድቦለት የአንድ ዓመት ተኩል የስራ አፈፃፀሙ በተገመገመበት ወቅት ከግንባታው ጀምሮ ችግር እንዳለበት በመግለፅ ችግሩ ሳይቀረፍ የትኛውም የመንግስት አካል ለማዕከሉ ድጋፍ እንዳያደርግ ገምጋሚዎቹ ቢያስጠነቅቁም ፈቃድ አግኝቶ ደረጃ ሳይወጣለት፣ ጥራቱን ሳይጠብቅና ባለሙያና መሳሪያ ሳያሟላ ወደ ስራመግባቱ ተገቢ አልነበረም ተብሏል፡፡ መንግስት በተቋሙ ላይ አስፈላጊውን እርምጃ መውሰድ እንዳለበትም ገምጋሚዎችና የማዕከሉ ሰራተኞች አሳስበዋል፡፡
ከመነሻው የኢትዮጵያ ነዋሪዎች በጎ አድራጎት ድርጅት መሆኑ እየታወቀ የጤና ማዕከሉ፣ ሜዲካል ዳይሬክተር፣ ስራ አስኪያጁ፣ የሃብት ማፈላለጉና ሌሎች ከፍተኛ ኃላፊነቶች በውጭ ዜጎች መያዛቸው የፌደራል በጎ አድራጎት ድርጅቶችና ማህበራት ኤጀንሲ አዋጅን ፍፁም የሚቃረን ነው ያሉት በአዲስ አበባ ጤና ቢሮ የጤና ፕሮጀክት ክትትል እና ድጋፍ ባለሙያ አቶ ጥላሁን አለሙ፤ ማዕከሉ በርካታ  ዘርፈ ብዙ ችግሮች ያሉበት መሆኑንና የተጠቃሚን አቅም ያላገናዘበ፣ ባለሙያ ያልተሳተፈበትና በከተማ አስተዳደሩ ስልጣን በተሰጠው አካል ያልፀደቀ የክፍያ ተመን በማውጣት የተጋነነ ክፍያ የሚያስከፍል፣ በጤና ንግድ ስራ ላይ የተሰማራ ድርጅት ነው ብለዋል፡፡
የጤና ማዕከሉ ካሉበት ችግሮች ውስጥ የማዕከሉ የውጭ ሞያተኞች የጤና የስራ ፈቃድ ከመውሰዳቸው በፊት ከኦፕሬሽን ጀምሮ ሌሎች የህክምና አገልግሎቶችን እየሰጡ እንደሆኑ የገምጋሚዎቹ ሪፖርት ያመለክታል፡፡ በተጨማሪም ማዕከሉ በየዓመቱ የሚታደስ የህክምና አገልግሎት ፈቃድ ያልተሰጠው ህገ-ወጥ ተቋም ነው ሲልም ሪፖርቱ ገልጿል፡፡
አቶ ወ/ፃዲቅ ማናዬ ይባላሉ፤ የ62 ዓመት አዛውንት ናቸው፡፡
አዲስ አበባ ቂርቆስ ክ/ከተማ ኦሎምፒያ አካባቢ ይኖራሉ፡፡ “አምና መጋቢት ወር ላይ ዓይኔን ታምሜ ወደ OIA የሄድኩት ህንዶቹ ጥሩ ህክምና ይሰጣሉ ተብዬ ነው ያሉት አዛውንቱ፤ በመጀመሪያ የሞራ ግርዶሽ ነው ተብለው 4250 ብር ከፍለው የቀዶ ህክምና ማድረጋቸውን ይናገራሉ፡፡ “በመጨረሻ እራሳቸው በፈጠሩት ስህተት ከአንድም ሶስት ጊዜ ኦፕራሲዮን ተደርጌ ሬቲናዬን አበላሹት” የሚሉት አዛውንቱ፤ ከዚያም በኋላ ያለ ምንም መድሃኒትና እርዳታ ዝም ብለው እንዲጠብቁ በመደረጋቸው ቀኝ አይናቸው ሙሉ ለሙሉ ከጥቅም ውጭ ሆኖ ማየት እንደተሳናቸው በምሬት ገልፀዋል፡፡
ያለ ምንም መድሃኒት ለሁለት ወር ቀጠሮ ሰጥተውኝ ስመለስ “ያንተ የሬቲና ችግር ነው አሉኝ” የሚሉት አቶ ወ/ፃዲቅ፤ “የሬቲና ችግር ከሆነ ለምን ሶስት ጊዜ አደንዝዛችሁ ሞራ ነው በማለት ኦፕሬሽን አደረጋችሁኝ” በማለት ህንዳዊ ሀኪሞቹን መጠየቃቸውን፤ ነገር ግን ከማመናጨቅ ውጭ ቀና ምላሽ ማጣታቸውን ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡ “ወደ ሌላ ህክምና ለመሄድ ሪፈር ፃፉልኝ፤ አለበለዚያም እናንተ ጋር ያደረግሁትን አጠቃላይ የህክምና መረጃ ስጡኝ” ብለው መጠየቃቸውን የሚናገሩት አዛውንቱ፤ የምናውቀው ነገር የለም የፈለጋችሁበት ሄዳችሁ ክሰሱን፤ ምላሽ እንሰጣለን” በማለት አመናጭቀው እንደሸኟቸውና እይታቸውን አጥተው ቤት ውስጥ ከተቀመጡ 10 ወር እንዳለፋቸው ገልፀው፤ ማንበብና መፃፍ ሁሉ እንደተሳናቸው ተናግረዋል፡፡
በዚሁ የአይን ህክምና ማዕከል የህክምና ስህተት ተፈጽሞብኛል ያሉት የ65 ዓመቱ አዛውንት አቶ ኮሬ ወ/ማርያም፤ ባለፈው ዓመት ግንቦት ወር ላይ ለህክምና ሲሄዱ የሞራ ግርዶሽ ነው ተብለው አምስት ሺህ ብር ከፍለው ኦፕሬሽን መደረጋቸውን አስታውሰው፣ በ15ኛው ቀን አይናቸው ሙሉ በሙሉ ጠፍቶ ወደ ማዕከሉ ተመልሰው መሄዳቸውን ይናገራሉ፡፡
“አይኔ መጥፋቱን እያወቁ አንድም ጠብታ ሳያዙልኝ ወደ ምኒልክ ሆስፒታል እንድሄድ ነገሩኝ” የሚሉት አዛውንቱ፤ ምኒልክ ሆስፒታል ሁለት ሶስት ጊዜ ቢመላለሱም ምንም እርዳታ ሳያገኙ ሲኤምሲ አትሌቲክስ ህንፃ ላይ በሚገኘው “ብሩህ ቪዥን” ክሊኒክ እንዲታከሙ እንደተነገራቸው ገልፀዋል፡፡
“ብሩህ ቪዥን አንዴ በመርፌ፣ ሌላ ጊዜ በመሳሪያ ይታይ እያሉ ለተጨማሪ 7ሺህ ብር ወጪ ተዳርጌያለሁ” ያሉት እኚህ ታካሚ፤ አራት ወር እንደሆናቸውና አይናቸውንም አጥተው፣ 12 ሺህ ብራቸውን በማፍሰስ ለተጨማሪ ችግር በመዳረጋቸው ተጨማሪ ወጪ እንደሚጠብቃቸው ተናግረዋል፡፡
“የተሟላ መሳሪያ ሳይኖር፣ በዘርፉ የሰለጠነ በቂ ሀኪም በሌለበት የህክምና ማዕከሉ እንዴት ፈቃድ ተሰጠው?” ሲሉ የሚጠይቁት አቶ ኮሬ፤ “መንግስት ለዜጎቹ የሚጨነቅ ከሆነ እንዲህ አይነቶቹን ተቋማትና ሰራተኞች ለፍርድ ማቅረብና ኢንሹራንስ ለተጎጂዎች እንዲከፍሉ፣ ከዚያም በአስቸኳይ ማዕከሉን ዘግቶ ከጥፋታቸው ማስቆም ያስፈልጋል” በማለት ብለዋል፡፡
ወደ ህክምና ማዕከሉ ከመሄዳቸው አስቀድሞ መኪና መንዳት ይችሉ እንደነበር የተናገሩት  የ66 ዓመቱ አዛውንት፤ ከአንድ ዓመት በፊት ህክምና መጀመራቸውን ይናገራሉ፡፡ “ችግሩ የሞራ ግርዶሽ ነው፤ ይህን በቀላሉ እንገፍልሃለን ብለው ኦፕሬሽን ካደረጉኝ በኋላ ጭራሽ አይኔ ማየት አቁሞ ቤት ተቀምጫለሁ” ሲሉ በምሬት የገጠማቸውን ችግር ገልፀዋል፡፡
“ከዚያ በኋላ አይኔ ጠፋ ብዬ በተከታታይ ብመላለስም ምንም መፍትሄ ሳላገኝ እስካሁን አለሁ” ያሉት አዛውንቱ፤ “እርግጥ እኔ የካርድ 40 ብር ከመክፈል በስተቀር ያወጣሁት ወጪ የለም፤ ምክንያቱም የነፃ ህክምና ወረቀት አፅፌ ነበር የሄድኩት” ብለዋል፡፡ እሳቸው ደግሞ የጨረር ህክምና ተደርጐላቸውም መሻሻል እንዳላሳየ ገልፀው ወደ ምኒልክ ሆስፒታል ሪፈር እንደተፃፈላቸው ይናገራሉ፡፡ “ሚኒልክ ሆስፒታል ሄጄ ስመረመር አይንህ ተበላሽቷል፤ የማየትም ተስፋ የለውም ብለው መለሱኝ” የሚሉት ተጎጂው፤ ተስፋ ቆርጠውና እይታቸውን ተነጥቀው ቤት መቀመጣቸውን ጠቅሰው ወዴት አቤት እንደሚባል ግራ እንደገባቸው፤ ይህን ላድርግ ቢሉም አቅምና የእይታ ችግር እንደማይፈቅድላቸው ተናግረዋል - “እግዜር ይክሰሳቸው” ሲሉም በምሬት ተናግረዋል፡፡
በአንድ የመንግስት የሚዲያ ተቋም ውስጥ የሚሰራ ጋዜጠኛ ነው፡፡ ለህክምና ወደ ማዕከሉ መሄዱንና መቶ ብር ከፍሎ ካርድ ማውጣቱን ይናገራል፡፡ እንደ ሌሎቹ የሞራ ግርዶሽ ችግር ሳይሆን ረጅም ርቀት እይታ ችግር እንዳለበት ተነግሮት፤ ለህክምናው መዘጋጀቱን ነገር ግን በመሃል ወረፋ ሲጠብቅ ስለ ማዕከሉ መጥፎ መጥፎ ነገሮች ሲነገሩ በመስማቱ ህክምናውን እንዳቋረጠ ይናገራል፡፡ “ችግሬን ከድጡ ወደ ማጡ አላደርግም ብዬ ህክምናውን አቁሜ ይልቁንም ክሊኒኩ ውስጥ አለ የተባለውን አሻጥር እየመረመርኩ ነው” ያለው ጋዜጠኛው፤ በማዕከሉ ከሚሰሩ ኢትዮጵያውያን የህክምና ባለሙያዎች የሰማው እጅግ የሚዘገንን ህገ-ወጥ አሰራር አይነ ስውር ከመሆን ያተረፈውን አምላኩን እንዲያመሰግን እንዳደረገው አጫውቶኛል፡፡
ማዕከሉ ከዚህ በተጨማሪም በብልሹ አሰራሮች መተብተቡን የግምገማ ሪፖርቶቹ ይጠቁማሉ፡፡ በሪፖርቱ ከተጠቀሱት ችግሮች መካከል የፋይናንስ፣ የግዢና የሰው ሃብት አስተዳደር ማኑዋሎች የሌሉትና ለምዝበራ የተመቻቸ መሆኑ፣ ማዕከሉ በአዋጅ ኃላፊነትና ስልጣን በተሰጠው ደረጃ መዳቢ አካል ደረጃ ያልወጣለት መሆኑና በምስራቅ አፍሪካ አንደኛ የተባለው ማዕከል ምንም አይነት የላብራቶሪ፣ የጠቅላላ ሰመመን፣ የድንገተኛና መሰል የአገልግሎት ክፍሎች ያልተሟሉለት መሆኑ ይገኙበታል፡፡
በሃገር ውስጥ ሊሟሉ የሚችሉ የቢሮ ቁሳቁሶች በከፍተኛና ወጪ ከውጭ ከመግባታቸው በተጨማሪ ተፈራራሚ አካላት ቢያንስ በፅሁፍ እንዲያውቁት አለመደረጉ የተጠቆመ ሲሆን የፕሮጀክት ክለሳ ሳይደረግ ከእቅድ ውጭ ለሆነ ግንባታ 634ሺ 986 ዶላር እንዲሁም ለህክምና መሳሪያና ለቢሮ ቁሳቁስ 315ሺ 171 ከ37 ሳንቲም በድምሩ 950ሺ 157 ከ37 ዶላር ያለ አግባብ ወጪ መደረጉን የገምጋሚው ኤክስፐርት ሪፖርት አመልክቷል፡
ጉዳዩን ለማጣራት ወደ ማዕከሉ ሄደን የተለያዩ ህንዳዊያን ሃኪሞችን ለማነጋገር የሞከርን ሲሆን የማዕከሉ ዋና ዳይሬክተር ወደ ህንድ በመሄዳቸው መረጃ ማግኘት የምንችለው እሳቸው ሲመለሱ ብቻ እንደሆነ ተገልፆልን ተመልሰናል፡፡