Administrator

Administrator

የኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ጽ/ቤት በንግድ ምልክት፣ በአዕምሮ ፈጠራና በዲዛይን (ንድፍ) ላይ ጥበቃ ለማድረግ በዓለም አቀፉ የአዕምሮ ንብረት ድርጅት (World Intellectual Property Organization) WIPO ትብብር አዲስ የዲጂታል አሰራር መዘርጋቱን አስታውቋል፡፡ ከዚህ ቀደም በማኑዋል የአዕምሮ ንብረቶችን ይመዘግብና ይቀበል የነበረው መስሪያ ቤቱ፤ ከተባበሩት መንግስታት ስፔሻላይዝድ ድርጅቶች አንዱ በሆነው “ዋይፖ” በተደረገለት ድጋፍ በ2.ሚሊዮን ዶላር የተገዙ ሶፍትዌሮችን፣ ሰርቨሮችን፣ ኮምፒዩተሮችንና ፕሪንተሮችን በማስገባት Intellectual Property Automation System (IPAS) ሲስተምን ይፋ አድርጓል፡፡ በእለቱ የዋይፖ ተወካዮች በኢትዮጵያ አዕምሯዊ ንብረት ጽ/ቤት በመገኘት የዘረጉትን ሲስተም ለጋዜጠኞችና ለጽ/ቤቱ ከፍተኛ አመራሮች አስጎብኝተዋል፡፡ በጉብኝቱ ላይ የተገኘችው የአዲስ አድማስ ከፍተኛ ሪፖርተር ናፍቆት ዮሴፍ፤ በተዘረጋው ሲስተም፣ በጠቀሜታውና በዋይፖ ትብብር ዙሪያ ከጽ/ቤቱ ዳይሬክተር አቶ ብርሃኑ አዴሎ ጋር ተከታዩን ቃለምልልስ አድርጋለች፡፡

       የተዘረጋው አውቶሜሽን ሲስተም ጠቀሜታው ምንድን ነው?
እንግዲህ የዚህ ሲስተም በአገራችን መዘርጋት ጠቀሜታው በርካታ ነው፡፡ ከእነዚህ ውስጥ አንዱና ዋነኛው በአዕምሮ ፈጠራ (ፓተንት)፣ በንግድ ምልክትና በዲዛይን (ንድፍ) ባለቤትነት  ጥበቃ ላይ አስተማማኝና ዘለቄታ ያለው ስራን ለመስራት ያስችላል፡፡
 ይህ ሲባል እስከዛሬ አመልካቾች በወረቀት ይዘው የሚመጡት የባለቤትነት ጥያቄ አንድ ጊዜ በዚህ ሲስተም ውስጥ ከገባ ካልተፈለገ የይገባኛል ጥያቄዎች፣ ከመጥፋት ጭቅጭቅና ከመሰል ጉዳዮች ተጠብቆ ይቀመጣል፡፡
ሁለተኛ አመልካቾችን ከጊዜ ብክነትና ከመጉላላት ይጠብቃል፡፡ ባሉበት ሆነው ጉዳያቸውን መከታተል እንዲችሉ ያደርጋቸዋል ማለት ነው፡፡ አንድ አመልካች ፈጠራውን፣ የንግድ ምልክቱን ወይም ዲዛይኑን ይዞ ሲመጣ ኮድ ይሰጠዋል፤ ፋይል ይከፈትና የፋይሉ ቁጥር ሲስተሙ ውስጥ ይመዘገባል፡፡ ሌላ ጊዜ ሲፈለግ ኮዱን ኮምፒዩተሩ ላይ አስገብቶ  በፍጥነት ለማግኘት ያስችላል፡፡ ይህ ቀልጣፋ አሰራርን ይፈጥራል፡፡ ባለንብረትነትን ያረጋግጣል፡፡ አንድ ምርትም በፓተንት፣ በንግድ ምልክትና በዲዛይን ይጠበቃል፡፡ እነዚህ ጥቅሞቹ ናቸው፡
ይህን ሲስተም ለመዘርጋትና ስራ ላይ ለማዋል የዓለም አዕምሮ ንብረት ድርጅት “WIPO” ወደ ሁለት ሚሊዮን ዶላር ወጪ ማድረጉ፣ ሰራተኞቹን በራሱ ወጪ እዚህ ድረስ መላኩና ሲስተሙን መዘርጋቱ ተገልጿል፡፡ ይህን ድጋፍ ያደረገው ለምንድን ነው?
የዓለም የአዕምሮ ንብረት ድርጅት ከUN ስፔሸላይዝድ ድርጅቶች አንዱና በአዕምሮ ንብረት ላይ አተኩሮ የሚሰራ ትልቅ ድርጅት ነው፡፡ መቀመጫውን ስዊዘርላንድ ጄኔቫ ያደረገው ይህ ድርጅት፤ በ60 የዓለም አገራትና በ20 የአፍሪካ አገራት ይሰራል፡፡ ድርጅቱ ከሚሰራባቸው የአፍሪካ አገራት ኢትዮጵያ አንዷ ናት፡፡ ድርጅቱ ሰራተኞቹን ሲልክ ይህ ሶስተኛ ጊዜው ነው፡፡
 ድርጅቱ በተለይ በማደግ ላይ ያሉ አገሮችን ለማገዝ በያዘው ፕሮጀክት፣ ታዳጊ አገሮችን አግዘን የአዕምሮ ንብረት ጥበቃቸውን ማጠናከር አለባቸው ብሎ በማመኑ ድጋፎችን ያደርጋል፡፡ በዚህ መሰረት ሰራተኞችን ወደዚህ ሲልክ፣ የአውሮፕላን ትኬት፣ ሆቴል… ሁሉን ነገር ችሎ ነው፤ ከእኛ የሚጠበቅ ነገር የለም፡፡
በማንኛውም ጊዜ ድጋፍ ስንጠይቅ ፈጣን ምላሽ ይሰጣሉ፡፡ ይህ የድጋፋቸው አንዱ ክፍል ነው፡፡
ሲስተሙን ለመጫን የሚያስፈልጉ ከላይ የጠቀስሻቸውን ንብረቶች ለመግዛት ወደ 2 ሚሊዮን ዶላር ወጪ አድርገዋል፡፡ በቀጣይ የቅጅ መብት ላይ ለምንሰራውም ድጋፍ ለማድረግ ሌላ ፕሮጀክት አላቸው፡
ከዚህ በፊት ምን ምን ድጋፎችን አድርገዋል?
እስካሁን ብዙ ፕሮጀክቶችን ሰጥተውናል፡፡ ለምሳሌ የብሔራዊ አዕምሮ ንብረት ፖሊሲ ድራፍት ይደረግ ብለን ጠይቀናቸው፣ አማካሪ በመቅጠር ድጋፍ ስለሰጡን አሁን ድራፍቱ አልቋል፡፡ እስካሁን በአገር አቀፍ ደረጃ ይህ ፖሊሲ የለም ነበር፤ ሁለት አማካሪ በመቅጠር ጥናቱን ጨርሰዋል፡፡
 በሚቀጥለው ጥር መጨረሻ ላይ ለውይይት ቀርቦ ይፀድቃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡ ሌላው የአዕምሮ ንብረት አካዳሚ (If Academy) ነው፡፡ ይህንንም ፕሮጀክት ቀርፀን አቅርበን ፈቅደውልናል፡፡ ይህ አካዳሚ በቅርቡ ስልጠናና የማስተርስ ስራ ይጀምራል፡፡
ከዚህም በተጨማሪ የቅጅ መብትን አስመልክቶ የፊልም፣ የሙዚቃና የድርሰት ኢንዱስትሪው እያደገ መምጣቱን ተከትሎ ኢንዱስትሪው ለኢኮኖሚው እየጠቀመ ያለው ምን ያህል ነው የሚለውን እንዲጠናልን ጠይቀናቸው 70 ሺህ ዶላር አውጥተው አማካሪ ቀጥረውልን እየተጠና ነው፡፡ ጥናቱም የመጨረሻ ሪፖርት ላይ ደርሷል፡፡ እናም ድጋፍ በጠየቅን ቁጥር ፕሮጀክቶችን ይሰጣሉ፡፡ በተለይ በማደግ ላይ ያሉ አገሮችን በጣም ነው የሚያግዙት፡፡
በአሁኑ ወቅት ድርጅቱ ተወካዮቹን ሲልክ ለሶስተኛ ጊዜ ነው ብለዋል፡፡ ከዚህ በፊት የመጡባቸው ሁለት ምክንያቶች ምን ምን ነበሩ፤ የአሁኑ አመጣጣቸውስ በዋናነት ምን ላይ ያተኩራል?
ከዚህ በፊት ይህንኑ ሲስተም በተመለከተ ስራዎች ነበሯቸው፡፡ አሁን ግን ሶፍትዌሩን ጭነው ባለሙያዎች አሰልጥነውና አስፈላጊውን ነገር አሟልተው፣ ሲሰሙ ስራ ላይ መሆኑን ይፋ ያደረጉበት የመጨረሻ ቀን ነው፡፡ ከዚህ በኋላ የአዕምሮ ፈጠራ የንግድ ምልክትና የዲዛይን ባለቤቶች ሲያመለክቱ፣ በዚህ ሲስተም ነው የሚስተናገዱት ማለት ነው፡፡ በወረቀት የምንቀበልበት አሰራር አብቅቷል፡፡ ይህ አሰራር የመጨረሻ ተጠቃሚ የሚያደርገውም ባለንብረቱን ነው፡፡ ምክንያቱም ከዚህ በፊት በነበረው አሰራር ፋይል እየጠፋና እየተበላሸ መጉላላቶች ይደርሱ ነበር፡፡ አሁን ግን የወረቀት ምልልስ ቀርቶ አውቶሜትድ ሲስተም ስለምንጠቀም፣ ከሁሉም አቅጣጫ ጠቀሜታው የጎላ ነው ማለት ይቻላል፡፡
በአገር አቀፍ ደረጃ ሲስተሙ ሌላ ክልል አለ ወይስ እዚሁ ዋናው ጽ/ቤት ብቻ ነው?
እዚህ  ዋናው ጽ/ቤት ነው ሲስተሙ ያለው፡፡ በአገር አቀፍ ደረጃ የሚሰራው እዚሁ ነው፤ ነገር ግን አሁን አሰራሩ ኤሌክትሮኒክ ስለሆነ የትኛውም አመልካች የአዕምሮ ፈጠራውን፣ የንግድ ምልክቱንና ዲዛይኑን (ንድፉን) ካለበት ሆኖ በኤሌክትሮኒክ ሲስተም መላክና መመዝገብ እንዲሁም መከታተል ይቻላል፡፡
ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶችን በክልል ከፍቶ ለመንቀሳቀስ የታሰበ ነገር አለ?
በቅርቡ በክልሎች ቅርንጫፎችን ለመክፈት ሃሳብ አለን፡፡ አማራና ደቡብ ክልሎችን መርጠናል፡፡ ሌላው አካባቢም በሂደት ለመክፈት ሃሳብ አለ፡፡
ሁለቱ ክልሎች ቅድሚያ ያገኙበት ምክንያት ምንድን ነው?
ሁለቱን ከሌሎች በቅድሚያ የመረጥንበት ምክንያት የሚይዙትን የአካባቢ ስፋት ግምት ውስጥ በማስገባት ነው፡፡
ለምሳሌ አማራ ክልልን ብትወስጂ አብዛኛውን የሰሜኑን ክፍል፤ እነ ትግራይን፣ ከፊል ቤኒሻንጉልንና ከአፋርም የተወሰነውን ክፍል ይዞ  እንዲሰራ በማሰብ ነው፡፡ የደቡቡ ደግሞ የደቡብን አካባቢ አጠቃልሎ እስከ ድሬደዋ ወደ ምዕራብ ጭምር ተንቀሳቀሶ እንዲሰራ ታስቦ ነው፡፡ ለወደፊቱ ግን ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶቹን ወደ አራት ከፍ ለማድረግና ስራችንን የበለጠ ለማቀላጠፍ እቅድ አለን፡፡
የቅጅ መብትን በተመለከተ ከዓለም አቀፍ የአዕምሮ ንብረት ድርጅት ጋር ልትሰሩ ያሰባችሁት ምንድን ነው?
ቅድም እንደገለፅኩት የቅጅ መብት አዋጅ በቅርቡ ፀድቋል፡፡ ይህ አዋጅ ባለ መብቶችን ሁሉንም ተጠቃሚ የሚያደርግ ነው፡፡ እንግዲህ አዋጁን ተከትለን የቅጅ ባለመብቱን ጥቅም ለማስከበር በምን መልኩ ይሰራ የሚለውን የሲስተምና መሰል ድጋፎች ከዋይፖ ጠይቀናል፡፡
እነሱም ፕሮጀክቱን ፈቅደዋል፡፡ የሚሰሩት ስራዎች ወደፊት በሂደት በግልፅ  የሚታዩ ይሆናሉ፡፡ ዋናው ነገር እነሱ አሁንም በማደግ ላይ ያሉ አገራትን ለመርዳት ካላቸው ፍላጎት የተነሳ አስፈላጊውን ድጋፍ ለማድረግ ዝግጁ መሆናቸው ነው፡፡

Saturday, 20 December 2014 12:38

የሴት ኮንዶም

     ኤች አይቪ ኤድስን ጨምሮ ሌሎች ጥንቃቄ በጎደለው የግብረ ሥጋ ግንኙነት ሳቢያ የሚተላለፉ በሽታዎችና ያልተፈለገ እርግዝናን ለመከላከል የሚያስችል የሴት ኮንዶም በዲኬቲ ኢትዮጵያ ወደ አገራችን አስመጥቶ ለገበያ ከቀረበ ቆየት ብሏል፡፡ ኮንዶሙን ሁልጊዜና በአግባቡ ከተጠቀሙበት በግብረ ስጋ ግንኙነት የሚተላለፉ በሽታዎችንም ሆነ ያልተፈለገ እርግዝናን የመካላከል አቅሙ አስተማማኝ እንደሆነም የጤና ባለሙያዎችን ይናገራሉ፡፡ ዲኬቲ ኢትዮጵያ ኮንዶሙን በወሲብ ንግድ ላይ የተሰማሩ ሴቶች እንዲጠቀሙበት በማድረግ አበረታች ውጤት አስገኝቷል ሲባል ሰማሁና ጉዳዩን ከራሳቸው ከተጠቃሚዎቹ አንደበት ለመስማት ወደ ስፍራው ተጓዝኩ፡፡
በአዲሱ የባቡር መንገድ ፕሮጀክት ሳቢያ ምስቅልቅሉ ከወጣው የመርካቶው ሰባተኛ መንደር የደረስኩት ባለፈው ማክሰኞ አመሻሹ ላይ ነበር፡፡ ስፍራው በወሲብ ንግድ ስራ ላይ የተሰማሩ ሴቶች በስፋት የሚገኙበት በመሆኑ በቂ መረጃዎችን እንደማገኝ እምነት ነበረኝ፡፡ ከአዲስ ከተማ የመሰናዶ ት/ቤት ፊት ለፊት የሚገኙት ቅያሶች በሙሉ ወደ እነዚሁ አካባቢዎች የሚያደርሱ በመሆናቸው አንዱን መንገድ ይዤ ቁልቁል ወረድኩ፡፡
በቆርቆሮና በጣውላ እርስ በርስ ተዛዝለው የተሰሩና በሮቻቸው አጫጭር የሆኑትን የሴተኛ አዳሪዎቹን ቤቶች እያለፍኩ ወደመሀል ዘለቅሁ፡፡ የቀድሞው ቀበሌ 12 በርካታ በወሲብ ንግድ የሚተዳደሩ ሴቶች የሚገኙበት አካባቢ ነው፡፡
ሴቶቹ ከተለያዩ የአገራችን ክልሎች የመጡ መሆናቸውንና በወሲብ ንግድ ለዓመታት ተሰማርተው እንደቆዩ ነገሩኝ፡፡ ስለኤችአይቪ/ ኤድስና ጥንቃቄ በጎደለው ወሲብ ሳቢያ ስለሚከሰቱ በሽታዎች በቂ ግንዛቤም አላቸው፡፡ ኮንዶምን ሁልግዜ የመጠቀም ፍላጎት ቢኖራቸውም አብዛኛውን ጊዜ ያለኮንዶም ወሲብ ለመፈጸም የሚፈልጉ አንዳንድ ግድየለሽ ደንበኞቻቸው ያለፍላጐታቸው ከኮንዶም ውጭ ወሲብ እንዲፈፅሙ እንደሚይስገድዷቸው አጫወቱኝ፡፡ “ብዙውን ጊዜ በኃይል እየተጠቀሙ ያለኮንዶም ወሲብ ለመፈጸም የሚፈልጉ ወንዶችን ጮኸን እናስይዛቸዋል፡፡ እርስ በርሳችን በመረዳዳት ሴቲቱን አስገድዶ ያለኮንዶም ሊገናኝ የሚፈልገውን ወንድ በፖሊስ እናሲዛለን፡፡ አንዳንዴ ግን ወንዶች ያለኮንዶም ወሲብ ለመፈፀም የሚያቀርቡልን ማባበያ እያታለለን እኛም በፍቃደኝነት እንፈፅማለን፡፡ አንዳንዱ ወንድ ደግሞ ተስማምተን በኮንዶም ወሲብ ማድረግ ከጀመርን በኋላ ያጠለቀውን ኮንዶም አውልቆ በመጣል ያለኮንዶም ይገናኛል፡፡ ምን ታደርጊዋለሽ፡፡ ህይወት እንዲህ ናት!”
ሴቶቹ ህይወታቸው ስቃይና ሐዘን የተሞላበት እንደሆነና ራሳቸውን እንደ ሰዉ ቆጥረው ተስፋ ለማድረግ እንደማይችሉ ነገሩኝ፡፡ በቅር/ጀ ወደ አገራችን መጥቶ ገበያ ላይ ስለወሰው የሴቶች ኮንዶም ያውቁ እንደሆነ ጠየቅኋቸው፡፡ ሁሉም ሴቶች ስለ ኮንዶሙ ያውቃሉ፡፡ ሞክረውታልም፡፡ እንዴት ነው ታዲያ ስል ጥያቄዬን ቀጠልኩ፡፡
“በወሲብ ንግድ ላይ ተሰማርተሽ በራስሽ ፍላጎትና አማራጭ መጓዝ አትችይም፡፡ ደንበኛሽ ገንዘቡን እስከከፈለ ድረስ እሱ በሚፈልገው መንገድ ማስተናገድ አለብሽ፡፡ ይህንን ስታደርጊ ታዲያ ራስሽን ለበሽታና ለሞት አጋልጠሸ አይደለም፡፡ የሴት ኮንዶም በመምጣቱ ሁላችንም ደስተኞች ነን፤ ምክንያቱም በእኛ ስራ ኮንዶም መጠቀም የደንበኛሽን በጎ ፍቃደኝነትን የሚጠይቅ ነው፡፡ ቅድም እንዳልኩሽ ወንዱ በወሲብ ላይ እያለን ኮንዶሙን በማውለቅ ያለኮንዶም ሊገናኘን ስለሚችል ይህ ኮንዶም ከእነዚህ ችግሮች ይታደገናል፡፡ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ በስካር ኃይል ያለኮንዶም ሊያወጡን ከሚፈልጉ ወንዶች ይጠብቀናል፡፡ አንዳንድ ወንዶች ገንዘባቸውን ከፍለው ለወሲብ ዝግጁ መሆን ሲያቅታቸው ኮንዶሙን አውልቀው ያለ ኮንዶም ማድረግ ይፈልጋሉ፡፡ በዚህ ወቅት የሴት ኮንዶሙን አጥልቀን ዝግጁ ከሆንን ያለ ችግር እናስተናግዳቸዋለን፡፡ ኮንዶሙ እነዚህ ጠቀሜታዎች እንዳሉት ሁሉ ጉዳቶችም አሉት፡፡ የሴት ኮንዶሙ ለስምንት ሰዓታት በማህፀን ውስጥ ሊቀመጥ ይችላል ብለው ነገረውናል፡፡ ስለዚህ ኮንዶሙን ቀደም ብለን አጥልቀን ደንበኞቻችንን እንጠብቃለን፡፡ ደንበኞቻችን በአብዛኛው ደስተኞች አይደሉም፤ አንዳንዶቹ አስተማማኝ አይደለም በማለት ኮንዶም አጥልቀው ይገናኙናል፤ በዚህ ጊዜ ህመም ይሰማናል፡፡ ድርቀት ስለሚፈጠርም ምቾት ያለው ወሲብ አንፈፅምም፡፡ ረዘም ላለ ጊዜ በሰውነታችን ውስጥ ሲቀመጥና በተለይ ብዙ ስንቆም ምቾት ይነሳናል፡፡ ብዙውን ጊዜ የሴት ኮንዶሞችን የምንጠቀመው በበዓላት ዋዜማና ግርግር በሚበዛባቸው ጊዜያት ነው፡፡” ከሴቶቹ ጋር ስለሴት ኮንዶም ያደረግሁትን ቆይታ ካጠናቀቅሁ በኋላ ስለ ሴት ኮንዶም ምንነት ጠቀሜታና የጎንዮሽ ጉዳት እንዲያብራሩልኝ የማህፀን ፅንስ ስፔሻሊስት ዶክተር የኔነህ ታምራትን አነጋገርኳቸው፡፡
የሴቶች ኮንዶም በተለያዩ የዓለማችን አገራት በስፋት በጥቅም ላይ የሚውሉ ቢሆንም በአገራችን እምብዛም የማይታወቅና ከጥቂት ጊዜያት በፊት እንደገባ የገለፁልኝ ዶክተሩ፤ ህብረተሰቡ ስለሴት ኮንዶም ምንነትና አጠቃቀም እምብዛም ባለማወቁ በአግባቡ ጥቅም ላይ አልዋለም ብለዋል፡፡
የሴት ኮንዶሞች በተለያዩ አይነትና ብራንድ በዓለም ገበያ ላይ የሚገኙ ሲሆን  Femidom, Fc femeal condom, Reality, Dominiquie femy, Protectiv care, 7C2, 7C የተባሉት ይገኙበታል፡፡ በአገራችን ገበያ ላይ የሚገኙት 7C2 የተባሉት ኮንዶሞች ናቸው፡፡ የሴት  ኮንዶም ላቴክስ ከሚባልና ከጎማ ተክል ከሚመነጭ ፈሻሽ የሚሰራ ሲሆን በአግባቡና ሁልጊዜ ከተጠቀሙበት ያልተፈለገ እርግዝናንም ሆነ ኤችአይቪ/ ኤድስን ጨምሮ ሌሎች በግብረስጋ ግንኙነት የሚተላለፉ በሽታዎችን ለመከላከል ያስችላሉ፡፡የሴት ኮንዶሞች በመጀመሪያ አካባቢ ለአጠቃቀም  ምቹ አለመሆን፣ ምቾት አለመሰማት አይነት ችግሮች እንዳሏቸው ባይካድም ሲለመዱ ግን ይህ አይነቱ ስሜት እንደሚጠፋም ዶክተሩ ገልፀዋል፡፡ የሴት ኮንዶም ከተጠቀመች ሴት ጋር ወሲብ ለመፈፀም የሚዘጋጅ ወንድ ኮንዶም ማድረግ ይጠበቅበታል ወይ ለሚለው ጥያቄም ዶክተሩ ሲመልሲ ይህ እጅግ አደገኛና ሁለቱንም የወሲብ ተጓዳኞች ችግር ላይ የሚጥል ነገር ነው፤ ሴቷ ኮንዶሙን ከተጠቀመች ወንዱ መጠቀም አይኖርበትም፡፡ ሁለቱም ከተጠቀሙ ግን ድርቀት በመፍጠር ኮንዶሙ የመቀደድና የመላጥ ችግር ያስከትላል፤ ይህም በሽታ በቀላሉ ከአንዱ ወደ ሌላው እንዲተላለፍ ያደርጋል ብለዋል፡፡



አንድ ንጉሥ የመሞቻቸው ሰዓት ሲደርስ ሁለት ወንዶች ልጆቻቸውንና አንዲት ሴት ልጃቸውን ጠርተው፤ “ልጆቼ፤ እንግዲህ ዕድሜዬ እየገፋ፣ ጉልበቴ እየላመ፣ አቅሜም እየደከመ የመጣበት ሰዓት ነውና ከመንግሥቴ የት የቱን መውረስ እንደምትመርጡ ሀሳብ እንድትሰጡኝ እፈልጋለሁ” አሉ፡፡
ታላቅ ወንድም ምንም ሀሳብ ሳይሰጥ ዝም አለ፡፡
ሁለተኛው ወንድም፤
“አባቴ ሆይ! እርስዎ ራስዎ ይሄን ለትልቁ፣ ይሄን ለትንሿ፣ ይሄን ለትንሹ አውርሻለሁ ቢሉን አይሻልም ወይ?” ሲል ሃሳቡን አቀረበ፡፡
ሴቷ ልጅ ደግሞ፤
“አባቴ ሆይ! እኔ የምመኘውንና የማስበውን ብናገር፣ ሌሎቹም የሚያስቡትን ባውቅ በጣም ደስ ይለኛል፡፡ ስለሆነም አባቴ ያሉትን እደግፋለሁ” አለች፡፡
ንጉሡም፤
“አያችሁ ልጆቼ፤ አሁን ከተናገራችሁት የተረዳሁት ሦስት ነገር ነው፡፡
ከመጀመሪያው ልጄ - ዝምታን አየሁ፡፡
ከሁለተኛው ልጄ - ኃላፊነትን ለሌሎች መጣልን አየሁ፡፡
ከሦስተኛው ልጄ - በራስ መተማመንን ነው ያነበብኩት፡፡
በእርግጥ ያየሁዋቸው ሦስት ነገሮች የየራሳቸው ዋጋ አላቸው፡፡ ዝምታ ወቅቱን ከጠበቀ ዋና  ነገር ነው፡፡ ኃላፊነትን ለሌሎች መስጠት አቅምን ከማወቅና የሌሎችን ዋጋ ከማወቅ የመነጨ ከሆነ እጅግ ጠቃሚ እሴት ያለው ነው! በመጨረሻም በራስ መተማመን ከሁሉም የላቀ እሴት ነው፡፡ ያለራስ መተማማመን፤ መንግሥቴን ወዴትም ልታዘልቁት አትችሉም፡፡ በራስ መተማመን የሚመጣው ዕውቀት ሲኖር ነው፡፡ ዕውቀት የሚመጣው ለመማር ፈቃደኛ ከመሆን፣ ከልምድ ራስን ከማሻሻል፤ ሁልጊዜ ለለውጥ ዝግጁ ከመሆን ነው፡፡ እነዚህን ሁሉ አጢኜና መርምሬ ሳስተውል፣ መንግሥቴን መውረስ ያለባት ሴቷ ልጄ ናት” ሲሉ ደመደሙ፡፡
***
የአንድ ህብረተሰብ ዋና ኃይል ልበ - ሙሉነትና በራስ መተማመን ነው! የሀገራችንን የህብረተሰብ አወቃቀር ስናስተውል፤ በተለይ አሁን በደረስንበት የዕድገት ደረጃ፤ የሴቶችን ከባድ ሚና፣ ከባድ ጫና እና ከባድ የሀገር እናትነት ስሜት ማጤን አይሳነንም፡፡ ከተረቶቻችን፣ ከምሳሌዎቻችንና ከጥቅሶቻችን በሰፊው እንደምንረዳው፤ የሴትን የበታችነት አጠንክረው የሚያሰምሩ ቃለ - ኃይሎች እንዳሉ አይካድም፡፡
“በለው በለው ሲል ነው የወንድ አብነቱ
ሴትም ትዋጋለች ከረጋ መሬቱ”
የሚለውን አንድ ምሣሌ ብናይ እንኳ፣ ጉዳችንን በቀላሉ ይነግረናል፡፡ “ለፍታ ለፍታ ሴት ወለደች”ን ስናይ፣ ከንቀታችን ሶስት አራት እጥፍ የሴቶች ጫንቃ ላይ እያሳረፍን እንደከረምን ለማወቅ አያዳግትም፡፡ “ምን ሴት ብታውቅ በወንድ ያልቅ” የሚለውን አደገኛ ካንሠር አከል በሽታ ማስወገድ ይገባናል!! ሴቶችን የረሳ፣ ሴቶችን የናቀ፣ ሴቶችን ተሳታፊ ያላደረገ ሥርዓት ይዞ የትም አያደርስም፡፡ “እንስራዋን ጥላ ወንዝ ወረደች” የሚለው ተረትም አሁንም በሴት ጫንቃ ላይ የተንተራሰ ይሁን እንጂ ቁምነገሩን አንስተውም፡፡
ሀገራችን በተለያዩ የሥራና የህይወት ዘርፎች ያለ ሴት በሣልና ጠንካራ ተሳትፎ ካለመችበት ልትደርስ አትችልም፡፡ ከዚህ አንፃር ሴቷን የለውጥ መዘውር ለማድረግ ለአፍታም ሳንታክት ማሰብና ተግባራዊ ማድረግ ወሳኝ ነው፡፡ ከዚህ ቀደም በመፈክር ላይ በመንጠልጠልና በቀለም በማድመቅ ብቻ የትም እንዳልደረስን አይተነዋል፡፡ በሌላ በኩል ራሳቸውን ለትግል ያበቁ፣ የታገሉና ያሸነፉ ሴት ፋና - አብሪዎች፣ ለድል የበቁት አደራጅተው እንደሆነ እናውቃለን፡፡  በተለያዩ የሙያ ዘርፎች፣ በንግድና ኢንዱስትሪ እንዲሁም በባህላዊ ትሥሥር ዙሪያ ገፍተው ብቅ ብቅ ያሉቱ ምን ያህል ለውጥ ማምጣት እንደቻሉ እያየን ነው፡፡ ገና ግን ብዙ ማደግ፣ በየዘርፉ ብዙ መብቀል፣ ብዙ ማፍራት፣ ብዙ ማልማት ይጠበቅባቸዋል፡፡ ሌላውም የህብረተሰብ ክፍል እንቅስቃሴያቸውን ከአንጀቱ ማገዝና ማጐልበት፣ ትልቅ አስተዋፅዖ ማድረግ ይኖርበታል፡፡ በሙያና በብዙሃን ማህበራት፣ በቤተሰብና በግል ህይወት ውስጥ ሚናቸውን ማረጋገጥ ቁልፍ ጉዳይ ነው፡፡ ብርቱ ጉዞ ይጠብቀናል፡፡ በህብረተሰባችን ውስጥ ሁሉም ቦታ ቦታ እንዳለው አንርሣ! “ቦታ ቦታችሁ ግቡ ቢባል አሎሎ ወደ ጅረት፣ ኩበት ወደ አክንባሎ” የሚባለውም በየቦታው ሁሉም ባለዕሴት መሆኑን ሲነቁጥ ነው!  


  “ ቅ/ ሲኖዶሱ በአድባራት ሓላፊዎች ላይ ያሳለፈው ውሳኔ
          ሕገ መንግሥቱን የሚፃረር ነው ”   /ፓትርያርኩ/
     የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ፣ ‹‹የቤተ ክርስቲያን አባቶችና ቤተ ክርስቲያን ዕውቅና በሰጠችው ማኅበር ላይ ተገቢ ያልኾነ ቃል ተናግረዋል›› ባላቸው አንዳንድ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አድባራት አስተዳዳሪዎች ላይ ያሳለፈው ውሳኔ አፈጻጸም ‹‹ሕገ መንግሥቱንና ሰብአዊ መብትን የሚፃረር ነው›› በሚል ፓትርያርኩ ማገዳቸው ተገለጸ፡፡
ፓትርያርኩ ባለፈው ኅዳር 30 ለመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት በጻፉት ደብዳቤ ‹‹አፈጻጸሙ እንዲቆይ›› በማለት ያገዱት የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ፣ በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከትና በጠቅላይ ቤተ ክህነት በተካሔዱ ጉባኤዎች÷ ‹‹ተገቢ ያልኾነ ቃል ተናግረዋል፤ ይህም አነጋገር ጉባኤውን ቅር አሰኝቷል፤›› ያላቸው የአድባራት አስተዳዳሪዎች፤ቀኖናዊ ምክርና ተግሣጽ እንዲሰጣቸው በአንድ ድምፅ ተስማምቶ ያሳለፈው እንደነበር ተጠቅሷል፡፡
በአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት፣ በመንበረ ፓትርያርክና በጠቅላይ ቤተ ክህነት የስብከተ ወንጌል አዳራሾች በተካሔዱት ስብሰባዎች የቤተ ክርስቲያኒቱን መልካም አስተዳደርና ወቅታዊ ችግሮች የተመለከቱ የጉባኤተኞች አስተያየቶችና ሐሳቦች መቅረባቸውን በደብዳቤያቸው ያስታወሱት ፓትርያርኩ፤ ተሰብሳቢዎቹ ሐሳባቸውንና አስተያየታቸውን በግልጽ መናገራቸውና አሉ የተባሉ ችግሮች መፍትሔ እንዲያገኙ መጠየቃቸው ‹‹በዓለም አቀፍ ደረጃም ኾነ በሀገራችን ለሕዝብ የተፈቀደ ዴሞክራሲያዊ መብት መኾኑ አያጠያይቅም›› ብለዋል፡፡ ሐሳባቸውንና አስተያየታቸውን በግልጽ ያቀረቡ ሰዎችን መገሠጽና መውቀስም ሕገ መንግሥቱን እንደሚፃረር ጠቁመዋል፡፡
ጉባኤዎቹ በቤተ ክርስቲያን ጠሪነት የተካሔዱ እንደነበሩና ተሰብሳቢዎቹም የቤተ ክርስቲያኒቱ ሊቃውንት፣ አገልጋዮችና ሠራተኞች መኾናቸውን ፓትርያርኩ ጠቅሰው÷ የጎደለው እንዲሟላ የጠመመው እንዲቃና ያላቸውን አስተያየት በማቅረባቸው ተግሣጽና ማስጠንቀቂያ እንዲሰጣቸው ቅዱስ ሲኖዶስ ያሳለፈው ውሳኔ ‹‹የስብሰባ ነፃነትንና መብትን ነፍጎ ሐቁ እንዳይነገር›› የሚከለክልና ውጤቱም ‹‹ጊዜ ያለፈበትን አፈና በማንገሥ ችግሮች ተባብሰው እንዲቀጥሉ የሚያደርግ ነው›› ብለዋል፡፡ “በውይይቱ ወቅት ‹‹የዳኅፀ ልሳን ወለምታ›› አጋጥሞም ከኾነ በወቅቱ ማብራሪያና ማስተካከያ ይሰጥበታል እንጂ እንደ ከባድ ጥፋት ተቆጥሮ ሰዎች ሊገሠጹበትና ሊወቀሱበት አይገባም፤ ሕግም አይፈቅድም፡፡” ሲሉ ገልጸዋል - በደብዳቤያቸው፡፡
የቅዱስ ሲኖዶስ ምልዓተ ጉባኤ ‹‹ተገቢ ያልኾነ ቃል ተናግረዋል›› ያላቸው አንዳንድ የአድባራት አስተዳዳሪዎች በጠቅላይ ቤተ ክህነት በኩል ቀርበው ቀኖናዊ ምክርና ተግሣጽ እንዲሰጣቸው ያሳለፈው ውሳኔ ‹‹ሕግንና ሰብአዊ መብትን የሚፃረር›› ብቻ ሳይኾን ‹‹ትልቁን ጉባኤ በታሪክና በሕግ ዐዋቂዎች ዘንድ ግምት ውስጥ የሚጥለው እንዳይኾን አቡነ ማትያስ አስጠንቅቀው፡፡ ቅዱስ ሲኖዶሱ ጉዳዩን እንደገና በጥልቀትና ከሕግ አንጻር ፈትሾ እንዲያጤነው በማለት አፈጻጸሙ እንዲቆይ አስታውቀዋል፡፡
በሕገ ቤተክርስትያን ት/ሲኖዶሱ በሙሉ ድምፅ ተስማምቶ ያሳለፈውን ውሳኔ ፓትርያርኩ የማገድ ሥልጣን እንደሌላቸው ያመለክታል፡፡ ሕገ መንግሥቱ ከተጠቀሰበት አግባብ አኳያም፣ “ቤተ ክርስቲያናችን በቂ ሕግጋት አሏት፤ እነዚህ ሕግጋት ማዕከሉ ተጠብቆ ሊሠራባቸው ይገባል፤” ሲልም ቅ/ሲኖዶሱ አሳስቧል፡፡
ባለፈው መስከረም መጨረሻ “የቤተ ክርስቲንን አስተዳደራዊ አስተሳሰብ ማበልጸግ” በሚል መርሕ በተካሔደው ስብሰባ አንዳንድ የአድባራት አስተዳዳሪዎች፤ ‹‹ፈጣሪ የለም ይላል፤ አሸባሪና አክራሪ ነው፤›› በማለት ቤተ ክርስቲያኗ ዕውቅና የሰጠችውን ማኅበረ ቅዱሳንን ከዓለም አቀፍ ጽንፈኞች ጋራ እያመሳሰሉ መወንጀላቸው ተገቢ እንዳልኾነና የማኅበሩ አገልግሎት ለቤተ ክርስቲያን አስፈላጊ እንደኾነ ቅዱስ ሲኖዶሱ አረጋግጧል፡፡
‹‹ቆራጣ ደብዳቤ ይበቃዋል፤ ከመንግሥት ጋራ በመተባበር እስከ ጫፍ አድርሱልን፤ በቶሎ ቁረጡት›› እያሉ መጠየቅ፤ ሊቃነ ጳጳሳቱንም “ከፈለጉ ቆባቸውን አስቀምጠው ወደዚያው ይግቡ” እያሉ መዝለፋቸውስ በምን መመዘኛ ነው ዴሞክራሲያዊና ሕገ መንግሥታዊ የሚኾነው በማለት የሚገልጹ የስብሰባው ተሳታፊዎች በበኩላቸው፤ ፓትርያርኩ የውሳኔውን አፈጻጸም ማገዳቸው፣ አድሏዊ እንደሚያደርጋቸውና በካህናቱና በምእመናኑ ዘንድ መንፈሳዊ አባትነታቸውንና ታማኝነታቸውን ጥያቄ ውስጥ የሚያስገባው እንደሚኾን ጠቁመዋል፡፡

ኤልጂ ኩባንያ በኦሮሚያ ክልል ሰንዳፋ አካባቢ ለሚገኘው ሙዳ የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤት የተለያዩ የትምህርት መርጃ መሳርያዎች ድጋፍ ማድረጉን አስታወቀ፡፡
ኤልጂ ከወርልድ ቱጌዘር፣ መንግስታዊ ያልሆነ ዓለም አቀፍ የልማትና የግብረሰናይ ድርጅት ጋር በመተባበር እ.ኤ.አ ከ2012 ዓ.ም ጀምሮ በሰንዳፋ አካባቢ ዱግዴራ በተሰኘ መንደር የማህበረሰብ ልማት ፕሮጀክት በመተግበር ላይ እንደሚገኝም ተገልጿል፡፡ ፕሮጀክቱ “ኤልጂ ሆፕ ቪሌጅ” የሚል መጠሪያ ያለው ሲሆን የመንደሩ ነዋሪዎች እራሳቸውን ለዘለቄታው እንዲችሉ በእርሻና በእንስሳት እርባታ ስልጠናና ድጋፍ የሚያገኙበት ነው ተብሏል፡፡
ኤልጂ ግብርና ላይ ከሚያደርገው ድጋፍ በተጨማሪ የተለያዩ የልማት ስራዎችን በማስፋፋት በአካባቢው ለሚገኙ የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤቶች የተለያዩ ድጋፎችን ሲያደርግ የቆየ ሲሆን በሰንዳፋ ወረዳ ለሚገኙ አራት ት/ቤቶች ከማስፋፊያ ግንባታዎች ጀምሮ እስከ ትምህርት መርጃ መሳሪያዎች ድረስ ድጋፍ አድርጓል፡፡
ኤልጂ በስሩ በሚገኘው ኢኖቴክ ኩባንያ አማካኝነት ላለፉት ወራት ለሙዳ የመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤት ድጋፍ ሲያደርግ የቆየ ሲሆን አሁን ደግሞ ት/ቤቱን በማደስ እንዲሁም ለተማሪዎች ቦርሳ፣ የመማሪያ መፃህፍት፣ የመማሪያ ዴስኮች፣ ወንበሮችና ጥቁር ሰሌዳዎችን ባለፈው ሕዳር ወር መጨረሻ በት/ቤቱ በተሰናዳው ዝግጅት አበርክቷል፡፡
ት/ቤቱ ከከተማ ባለው ርቀት የተነሳ በአዲስ መልክ ለመገንባትና በተፈለገው መልኩ ለትምህርት አመቺ ለማድረግ አስቸጋሪ ቢሆንም የመማሪያ ክፍሎቹን ባሉበት በማደስ፣ የቀድሞዎቹን አሮጌና ለመማር ማስተማር አመቺ ያልነበሩትን ክፍሎች የተሻለ ብርሃን እንዲያገኙ፣ እንዲሁም የክፍሎቹ ወለሎችና ግድግዳዎች እንዲፀዱ ተደርጓል፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የተማሪዎች መፀዳጃ በመማሪያ ክፍሎቹ አቅራቢያ እንዲሆን በማድረግ ከዚህ ቀደም ተማሪዎች መፀዳጃ ለማግኘት እስከ 10 ደቂቃ ይወስድባቸው የነበረውን የእግር ጉዞ አስቀርቷል ተብሏል፡፡

Saturday, 13 December 2014 11:24

የሀገሩን ሰርዶ በሀገሩ በሬ

በኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ ማህበራት ከማህበራዊ ህይወት ጅማሮ አንስቶ የሚሰፈር ዕድሜ አላቸው:: በመሆኑም ሰዎች ከአንድ በላይ ሆነው መኖር ከጀመሩበት ጊዜ እስካሁን ድረስ ህልውናቸው ጉልህ ሆኖ ይታያል፡፡ ዓይነታቸውና ቅርፃቸውም እንደ ዕድሜያቸው ሁሉ ለአሀዝ አዳጋች ነው፡፡ለዚህ ጽሁፍ ዓላማ ሲባል ሊቃኙ የታሰቡት በሰዎች የማህበራዊ ህይወት ውስጥ አይነተኛ ድርሻ ያላቸው ማህበራትን ነው፡፡ እነዚህ ማህበራት እንደ እድር፣ ዕቁብ፣ ደቦ፣ አፎሻ፣ ጅጌ፣ ወዘተ በመባል ይታወቃሉ፡፡ እነዚህና መሠል ማህበራት የሰዎችን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ሰርዶ ከሥሩ በመመንገል የማህበራዊ ህይወታችን በሬዎች ለመሆናቸው የሚከራከር ቢኖር አንድም ጣዕማቸውን ያልቀመሰ አልያም በዘመናዊ ቴክኖሎጂ አቀፍ ማህበራዊ ትሥሥር የከነፈ ሊሆን ይችላል፡፡
የሁላችንም የህይወት ተሞክሮ ከተለያዩ የባለሙያዎች ጥናቶች ጋር ተዳምሮ የሚያሳየን ዕውነታ - ዕድሮችና ማህበራት የሰዎችን የመረዳዳት፣ የመተጋገዝ፣ አብሮ የመስራት፣ አብሮ የማዘን፣ አብሮ የመደሰት፣ ወዘተ እሴት እያጎሉ ዘመናትን መሻገራቸውን ነው፡፡
አዎ! በርግጥም ማህበራቱ በዕለት ተዕለት የማህበራዊ ህይወታችን ጉልህ ድርሻን ይጫወታሉ፡፡ ከዚህም አልፎ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የተወሰኑት በማህበረ-ኢኮኖሚያዊ ልማት /socio-economic/ ዘንድ አንቱ የተባለ አስተዋጽዖ እያደረጉ ይገኛሉ፡፡ ለምሳሌ በኤች አይቪ ኤድስ መከላከልና መቆጣጠር፣ በአካባቢ ንፅህናና ጥበቃ፣ በግጭት አፈታት፣ በህፃናት አስተዳደግ፣ ወዘተ ሚዛን የሚደፋ አስተዋጽኦ በማድረግ ላይ ናቸው፡፡ ለአብነት ያህል በኢየሩሳሌም የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት ድጋፍና እገዛ አማካኝነት ወደ አርባ የሚጠጉ ማህበራት ባለፉት ሁለት ዓመታት የሚከተሉትን ተግባራት አከናውነዋል፡፡
ሁለት ሽህ አምስት መቶ ያህል አስዳጊዎች የተለያዩ የንግድ ሥራ ክህሎት ሥልጠና በመስጠትና ከፊል ብድር ድጎማ በማቅረብ የራሳቸውንና የቤተሰባቸውን ህይዎት እንዲያሻሽሉ አግዘዋል፤
አምስት ሺህ ለሚደርሱ ህፃናት የትምህርት መርጃ ቁሳቁስ ደግፈዋል፤
ሁለት ሺህ ያህል አሳዳጊዎቻቸውን ያጡና ተጋላጭ ህፃናት የህክምና አገልግሎት እንዲያገኙ አድርገዋል፤
አንድ መቶ ስልሳ አምስት መደበኛ ትምህርት ቤት መግባት ያልቻሉ ህፃናትን የአማራጭ መሠረታዊ ትምህርት ተጠቃሚ አድርገዋል፤
የከፍተኛ ትምህርት ዕድል ላላገኙ ሰባ ስድስት ህፃናት አስፈላጊውን ድጋፍ በማድረግ የከፍተኛ ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ አድርገዋል፤
ከአምስት መቶ በላይ የቤተሰብ አባላት የሚኖሩባቸውን ሃምሳ ሁለት ቤቶች አስጠግነዋል፤
በከፍተኛ ችግር ላይ ለነበሩ ሁለት ሺህ አምስት መቶ ያህል ህፃናት የአልባሳትና መሰል ድጋፎችን አድርገዋል፤
በተጨማሪም ለስድስት መቶ ያህል ሥራ አልባ ወጣቶች የተለያዩ የሙያ ሥልጠናዎችና የመሥሪያ ካፒታል ብድር በማገዝ ወደ ሥራ አሰማርተዋል፤
ይህንና መሠል ተግራባትን ያከናወኑ ማህበራት የነበሩ፣ ያሉና ምናልባትም የሚኖሩ ማህበራት ሲሆኑ ከነዚህ ውስጥ ዕድሮች፣ የእድር ህብረቶች፣ የአንድ አካባቢ ተወላጆች ማህበር፣ የተወሰነ ትምህርት ቤት የቀድሞ ተማሪዎች ማህበር፣ የመንግሥት ሠራተኞች በራሳቸው አነሳሽነት ለሌሎች ድጋፍ ለማድረግ የተቋቋሙ ማህራት፣ ወዘተ ይገኙበታል፡፡
እነዚህ ማህበራት በውስጣቸው የተሰባሰቡ በርካታ አባላት ያሏቸው ሲሆን በህብረተሰቡ ዘንድ በጣም ተቀባይነት ያላቸው፣ በመተማመንና በመተሳሰብ የሚሰሩ፣ የማህበረሰብ ጥቅምን የሚያስቀድሙ፣ ዲሞክራሲያዊነት - ግልፅነት - ተጠያቂነትን ያሰፈኑ፣ የሚያገለግሉትን የማህበረሰብ ክፍል ለማገልገል ቆርጠው የተነሱና በትትርና የሚሰሩ ማህበራት ናቸው፡፡ እንዲያው ባጠቃላይ ማህበራቱ ተገቢው እገዛ ቢደረግላቸው የሀገራችንን የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ሰርዶ ሲቻል የመመንገል አልያም የማጠውለግ ትልቅ አቅም ያላቸው የማህበረሰብ እንቁ ሀብት ናቸው፡፡
ይሁን እንጂ የሚመለከታቸው አካላት በተለይም መንግሥት፣ ለጋሽ ድርጅቶች፣ መንግሥታዊ ያልሆኑ ተቋማት፣ ራሱ ማህበረሰቡ ማህበራቱን በሚፈለገውም ሆነ በሚጠበቀው መጠን ሲጠቀሙባቸው አይታዩም፡፡ ኢየሩሳሌም የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት የእነዚህ የማህበረሰቡ ምስርት ተቋማትን ልማታዊ አስተዋፅኦ አበክሮ በመገንዘብ በተለይም ካለፉት 15 ዓመታት ጀምሮ በማህበራት ዙሪያ በሥፋት በመሥራት ላይ ይገኛል፡፡ በአሁኑ ሰዓት በላይ ጋይንት፣ አውራ አምባ፣ ባህር ዳር፣ ደ/ማርቆስ፣ አዲስ አበባ፣ ደ/ብርሃን፣ ደ/ሲና፣ ቢሾፍቱ፣ አዳማ፣ ድሬዳዋ፣ ሶማሌ ክልል ሽንሌ ዞን፣ መልካጀብዱ፣ ሻሸመኔ፣ አጄ፣ሃዋሳ፣ ቡታጂራ፣ እምድብር፣ ወልቂጤና ጅማ ከሚገኙ ከ140 ያህል የማህበረሰብ ምስርት ተቋማት/ ማህበራት ጋር እየሰራ ይገኛል፡፡ በመሆኑም የማህበራቱን ነባራዊ አቅም በማጎልበት ማህበራቱ ለየማህበረሰባቸው ከሚሰጡት ማህበራዊ አገልግሎቶች በተጨማሪ በማህበረሰቡ ውስጥ ተንሰራፍቶ የሚገኘውን የህፃናት፣ የወጣቶችና ሴቶች ችግር መፍታት እንዲችሉ ተደርጓል፡፡የኢየሩሳሌም ህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት የማህበራት ልማት / CBOs Development/ ተሞክሮ እንደሚያሳየው፣ የማህበራቱን አቅም በተለይ ፕሮጀክት የመፈፀም፣ ሂሳብ አያያዝና የአካባቢ ሃብት አጠቃቀም ስልትና መሰል ዘመናዊ አሰራሮች ረገድ የማህበራቱን አቅም በማጎልበት ማህበራቱ በፍትሃዊነት፤ ባነሰ ዋጋ፣ በተደራሽነት፣ ወዘተ በርካታ ችግር ፈቺና ልማታዊ ሥራዎችን እንዲሰሩ ማድረግ ይቻላል፡፡
አዎ! በመላ ሀገራችን ያሉ የህብረተሰቡ የሆኑ ማህበራትን በተቀናጀ መልክ ለልማት ማንቀሳቀስ ቢቻል የማይረታ የችግር ሰርዶ አይኖርም፡፡ እነዚህ በርካታ ቁጥር ያላቸው ማህበራት በትንሽ ሀገር በቀል ዕገዛ፣ በሀገርኛ መንገድ፣ ሀገራዊ ችግሮችን የመፍታት ዕምቅ ችሎታና ሀይል አላቸው፡፡ ስለሆነም የኢየሩሳሌም ህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅትና የሌሎችንም ጥቂት ተሞክሮዎች መነሻ በማድረግ የተቀናጀ ድጋፍና እገዛ በማድረግና እንዲሁም ምቹ ሁኔታዎችን በመፍጠር ማህበሮቻችንን ለማህበረሰቡ ፋይዳ እንጠቀም!!
ተስፋዬ ይሁኔ

Saturday, 13 December 2014 11:13

የትራንስፖርት ገጠመኝ

ወያላው    ተሳፋሪ! ተሳፋሪ!
አዲስ አባ በፈሪ

አባት    ምን ማለቱ ይሆን?
ልጠይቅ ምስጢሩን…
ደገመ አሁንም አምርሮ፣
ማንን ፈርቶ ቃል ጨምሮ፡፡
ምን ማለቱ እንደሆን ልጠይቀው ብዬ፣
ጠጋ እያልኩ እየፈራሁ እቃዬን አዝዬ፡፡

ወያላው    ግቡ! ግቡ! ፋዘር መኪናው ፈሪ ነው፣
ሰውም እየበዛ ሲሄድ ቀስ ብሎ ነው፡፡
አትጠራጠሩ በልኩ ይጭናል፣
ሹፌሩ ፈሪ ነው ቀስ ብሎ ይነዳል፡፡
መንገድ ላይ መንከርፈፍ ሁሌ ልማዱ ነው፣
ምናልባት - ምናልባት ነገ ቢገባ ነው፡፡

አባት       ስለዚህ ብሎ… ብዙ ሳያወራ፣
ካፉ ላይ ቀማሁት ይሄን ወሮበላ፡፡
ምን ማለትህ ይሆን? ግራ ገባኝ ባክህ፣
ማከላከልህ ነው ቋንቋ ማሳመርህ፡፡
ዞር በል ከበሩ - ሰው እጠይቃለሁ፣
ከአንተ ጋር ሳወራ - ጊዜ አቃጥያለሁ፡፡

ወያላፋዘር ይቅርቦ ለርሶ አዝኜ ነው፣
መኪናው ቀርፋፋ ነገ ቢደርስ ነው፡፡

አባትምን ታዝንልኛለህ - የትስ ታውቀኛለህ?
በጣም ነው የማዝነው ለካስ ደላላ ነህ፡፡

ወያላይኸው ሚኒባሱ - ፋዘር በዚሂዱ፣
ስለ ንግግሬ ብዙ አይናደዱ፡፡
ወዲያው ይደርሳሉ ካሰቡበት ቦታ፣

አባትብሎ ሳይጨርስ ይሄንን ወስላታ፣
በለው! በለው! አለኝ ወኔዬ መጣና፡፡
እሱ መቼ ፈርቶ ማንንስ አክብሮ፣
መለፍለፍ ቀጥሏል መሬት አቀርቅሮ፡፡

አሠለፈች አበበ ደሳለኝ
አዳማ (ናዝሬት)

Saturday, 13 December 2014 11:11

እስቲ ይሞክሩት

በዓለም ላይ ለመምህራን ከፍተኛ ደሞዝ የምትከፍል አገር ማናት?
በዓለም ላይ ከፍተኛ ዕዳ ያለባት አገርስ?
ከፍተኛ ቁጥር ያለው የጦር ሰራዊት ያላት አገር የትኛዋ ናት?
ብዙ ቢሊዬነሮች ያሉባቸው የዓለማችን ሦስት ከተሞች የትኞቹ ናቸው?
ሦስቱ የዓለማችን እጅግ     ሃብታም አገሮች እነማን     ናቸው?
============    
መልስ
1    ስዊዘርላንድ (በዓመት 68ሺ ዶላር) ኔዘርላንድ፣ ጀርመንና ቤልጂየም ይከተላሉ፡፡
2    አሜሪካ (15,940,978 ዶላር) እንግሊዝ፣ ጀርመንና ፈረንሳይ ይከተላሉ
3   ቻይና (2,285,000) ግብፅ በ10ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች፡፡
4   ሞስኮ (84)፣ ኒውዮርክ (62) እና ሆንግኮንግ (43)
5   ኳታር፣ ሉክሰምበርግ እና ሲንጋፖር (አሜሪካ በ6ኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች)

የአስገድዶ መድፈር ወንጀል ፈፃሚዎች በተለያዩ አዕምሮአዊ የጤና ችግሮች የተጠቁ ናቸው (የስነ ልቦና ባለሙያ)
ህጉ በአስገድዶ ደፋሪዎች ላይ ያስቀመጠው ቅጣት ለወንጀሉ ተመጣጣኝ አይደለም (የህግ ባለሙያ)

አየር ጤና አካባቢ ከሚገኘው ት/ቤቷ ወጥታ ወደ ቤቷ ለመሄድ በተሳፈረችበት ሚኒባስ ታክሲ ውስጥ በነበሩ አምስት ወንዶች ታፍና ተወስዳ በደረሰባት የአስገድዶ መድፈር ጥቃት ህይወቷ ያለፈው የአስራ አምስት ዓመቷ ታዳጊ ሃና ላላንጎ ጉዳይ ከተማችንን ሲንጣት ሰንብቷል፡፡ ታዳጊዋ ታፍና ከተወሰደችበት መስከረም 21 ቀን 2007 ዓ.ም ጀምሮ ለተከታታይ ቀናት የቡድን አስገድዶ መድፈር ጥቃታ ተፈፅሞባት፣ ጦር ኃይሎች ሙሉ ወንጌል ቤተክርስቲያን አካባቢ ተጥላ መገኘቷ መገቡ ይታወሳል፡፡
የህክምና እርዳታ አግኝታ ህይወቷ እንዲተርፍ የተደረገው ሙከራም የተፈፀመባት የአስገድዶ መድፈር ጥቃት እጅግ ከባድ በመሆኑና በስለት በመወጋቷ ሳቢያ ሳይሳካ ቀርቷል፡፡ ይሄ ክፉ ዜና ከተሰማበት ጊዜ አንስቶ ድርጊቱም በህብረተሰቡ ዘንድ ከፍተኛ ቁጣን ቀስቅሷል፡፡ በታዳጊዋ ላይ ይህንን አሰቃቂ ወንጀል ፈፅመዋል ተብለው የተጠረጠሩ አምስት ወጣቶችም በፖሊስ ቁጥጥር ስር ውለው፣ ጉዳያቸው በአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ፍ/ቤት ቂርቆስ ምድብ ችሎታ በዝግ እየታየ ይገኛል፡፡
የሟቿን ታዳጊ ጉዳይ መነሻ በማድረግ ለአስገድዶ መድፈር ወንጀል የሚያነሳሱ አፈንጋጭ የወሲብ ባህሪያትን ምንነትና የሚያስከትሏቸውን የጤና ቀውሶች እንዲሁም ለወንጀሉ የተቀመጠውን ቅጣት አስመልክቶ ከባለሙያዎች ያገኘነውን ማብራሪያና መረጃ የአዲስ አድማስ
ጋዜጠኛ መታሰቢያ ካሳዬ እንደሚከተለው አጠናቅራዋለች፡፡


አስገድዶ መድፈር ከስነ ልቦና
ቀውስ አንፃር
መደበኛ ከሆኑትና ከተለመዱት ወሲባዊ ድርጊቶች በተለየ መንገድ ወሲብን የመከወን ፍላጎት ያላቸው ሰዎች፣ ለአፈንጋጭ ወሲባዊ ባህርይ የተጋለጡ ናቸው ተብሎ ይታመናል፡፡ ከእነዚህም መካከል አስገድዶ መድፈር፣ የቡድን ተራክቦ፣ ግብረ ሰዶማዊነት፣ ሌሎች ወሲብን ሲፈፅሙ በማየት መርካት፣ ግለ ወሲብና በሰዎች  ስቃይ እርካታን ማግኘት ተጠቃሽ ናቸው፡፡ የአስገድዶ መድፈርና በቡድን የሚደረጉ ተራክቦዎች በአብዛኛው የሚፈፀሙት በአልኮልና በተለያዩ የአደንዛዥ እፆች ራስን ስቶ አዕምሮ በአግባቡ እንዳያስብ በማድረግ ነው ይላሉ - ባለሙያዎች፡፡
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የአፈንጋጭ ወሲባዊ ባህርያት አመላካች የሆኑ ድርጊቶች በአገራችን እየተለመዱ መምጣታቸውን የጠቆሙት የሥነ ልቦና ባለሙያው ዶክተር አንተነህ ተስፋው፤ በተለይ ዕድሜያቸው ከ16-25 ዓመት በሚሆናቸው ወጣቶች ላይ ድርጊቱ በስፋት እየታየ መሆኑ በጥናት መረጋገጡን ገልጸዋል፡
ከቴክኖሎጂው እድገትና ወሲባዊ ፊልሞች እንደ አሸን ከመፍላታቸው ጋር ተያይዞ አስገድዶ መድፈር፣ የቡድን ወሲብና ግብረሰዶማዊነት ከጊዜ ወደ ጊዜ እየተስፋፉ መምጣታቸውንም ዶክተሩ ተናግረዋል፡፡
ከአፈንጋጭ ወሲባዊ ባህርያት አንዱ የሆነው አስገድዶ መድፈር የአዕምሮአዊ ጤና ቀውስ ውጤት ነው፡፡ ለአፈንጋጭ ወሲባዊ ባህርያት አጋላጭ ከሆኑ ጉዳዮች መካከል ዋንኞቹ፡-
ከአስተዳደግ ጋር በተያያዘ የሚከሰቱ ስነልቦናዊ ችግሮች
አዕምሮ ላይ የሚደርሱ ጉዳቶች
የሆርሞኖችና ኬሚካሎች መዛባት
የኒውሮኖች ጉዳት ናቸው፡፡
ከአስተዳደግ ጋር በተያያዘ የሚከሰቱ የስነ ልቦና ችግሮች
ችግሩ በአብዛኛው ከአስተዳደጋችን ጋር ተያይዞ የሚከሰት ነው፡፡ ለራስ የሚሰጥ አነስተኛ ግምትና በልጅነት ዕድሜ ለወሲባዊ ጥቃት ተጋላጭ መሆን ለአፈንጋጭ የወሲብ ባህርይ ሊዳርግ ይችላል፡፡
አዕምሮ ላይ የሚደርሱ ጉዳቶች
በአዕምሮአችን ላይ በበሽታም ሆነ በተለያዩ ምክንያቶች አካላዊ ጉዳቶች ሊደርሱ ይችላሉ፡፡ እነዚህ ጉዳቶች ደግሞ የአዕምሮአችንን የወሲብ ክፍል ሊጎዱትና በዚያም ሳቢያ በወሲባዊ ባህርያችን ላይ ተፅዕኖ በመፍጠር ለአፈንጋጭ የወሲብ ባህርይ ሊያጋልጡን ይችላሉ፡፡
የሆርሞኖችና የአዕምሮ ኬሚካሎች መጠን መዛባት
አንድሮጅንና ኤስትሮጅን የተባሉት በሰውነታችን ውስጥ የሚገኙት ሆርሞኖች ወሲባዊ ፍላጐትና ስሜታችንን ለመቆጣጠር የማረዱን ናቸው፡፡ የእነዚህ ሆርሞኖች መዛባት በወሲባዊ ባህርያችን ላይ የሚያስከትሉት ተፅእኖ ቀላል አይደለም፡፡
 የኒውሮኖች ጉዳት
የአዕምሮ ሴሎች እርስ በርስ እንዲተሳሰሩና መልእክት እንዲለዋወጡ የሚያደርጉ የአዕምሮአችን መረቦች በተለያየ ምክንያት ጉዳት በሚደርስባቸው ጊዜ አፈንጋጭ ለሆነ ወሲባዊ ባህርይ ሊያጋልጡን ይችላሉ፡፡
በአጠቃላይ ለአፈንጋጭ ወሲባዊ ባህርይ ልንጋለጥ የምንችለው በተለያዩ ውስጣዊና ውጫዊ ምክንያቶች ሲሆን ችግሩ በወቅቱ ታውቆ የባለሙያ እገዛ ካላገኘ በጊዜ ብዛት አፈንጋጭ የወሲብ ባህርይው ሙሉ በሙሉ የግለሰቡን አዕምሮ በመግዛት በራስ መተማመን የሌለውና ወሲባዊ እሳቤውን ለመቆጣጠር የማይችል ሊያደርጉት ይችላሉ፡፡ የችግሩ ተጠቂ የሆነ ሰው ለራሱ ያለው ግምት እጅግ አነስተኛ ስለሚሆን ራሱን ከማህበረሰቡ ያገላል፡፡ ራሱን ለማጥፋትም ይፈልጋል፡፡ ይህ ከመሆኑ በፊት የችግሩ ተጠቂዎች የስነልቡና ባለሙያዎች ጋር ወይንም የስነ አዕምሮ ሐኪሞች ዘንድ በመሄድ ለችግራቸው መፍትሄ መሻት ይኖርባቸዋል፡፡
የአስገድዶ መድፈር ድርጊት የተፈፀመባት (የተፈፀመበት) ሰው ብቻ ሳይሆን የፈፀመው ግለሰብም ጭምር የህክምና እርዳታ ሊያገኝ የሚችልበት መንገድ መመቻቸት ይኖርበታል ያሉት የስነልቡና ባለሙያው ዶክተር አንተነህ፤ ይህ አሰራር በሌሎች አገራት የተለመደ መሆኑን ጠቁመዋል፡፡
አስገድዶ መድፈርና ህጋዊ ተጠያቂነቱ
በ15 ዓመቷ ታዳጊ ወጣት ላይ የተፈፀመው የቡድን አስገድዶ መድፈር ወንጀል ያስቆጣቸው የከተማዋ ነዋሪዎች የድርጊቱ ፈፃሚዎች በአፋጣኝ ተይዘው ለድርጊታቸው ተመጣጣኝ የሆነና ሌሎችን ሊያስተምር የሚችል (መቀጣጫ የሚሆን) ፍርድ እንዲሰጣቸው ሲጠይቁ ሰንብተዋል፡፡ የወንጀሉ ፈፃሚዎች በሞት እንዲቀጡ አሊያም የእድሜ ልክ ፅኑ እስራት እንዲወሰንባቸው የጠየቁም በርካቶች ናቸው፡፡ ለመሆኑ የወንጀለኛ መቅጫ ህጉ ለዚህ መሰሉ ድርጊት የሚሰጠው የቅጣት ውሳኔ እምን ድረስ ነው? የህግ ባለሙያው አቶ ዳዊት ታዬ ለዚህ ማብራሪያ አላቸው፡፡
የኢትዮጵያ ወንጀለኛ መቅጫ ህግ፤ የአስገድዶ መድፈርን ወንጀል እስከ አስር አመት ሊደርስ በሚችል ቅጣት የሚያስቀጣ ወንጀል አድርጐ አስቀምጦታል፡፡
ድርጊቱ የተፈፀመው አስራ አምስት ዓመት ባልሞላት ሴት ልጅ ላይና በብዙ ሰዎች ተባባሪነት ከሆነ ቅጣቱ እስከ አስራ አምስት አመት ሊደርስ እንደሚችል ይገልፃል፡፡ ድርጊቱ ሞትን የሚያስከትል ሲሆን ደግሞ ቅጣቱ ከፍ ሊል ይችላል፡፡ ሆኖም በአስገድዶ መድፈር ላይ ተፈፃሚ የሚሆኑ የቅጣት ህጐች ደፋሪዎች ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ ለማድረግ የሚያስችል አቅም ያላቸው ናቸው ብሎ ለመናገር እንደማያስችሉ አቶ ዳዊት ይናገራሉ፡፡
“ህጉ የአስገድዶ መድፈር ወንጀል የፈፀመ ሰው ወንጀሉን የፈፀመባትን ሴት ያገባ እንደሆነ ክሱ ቀሪ ሊሆን እንደሚችል ያስቀምጣል፤ ይህም የድርጊቱ ፈፃሚዎች ጋብቻ በመፈፀም ከተጠያቂነት ነፃ ሊሆኑ እንደሚችሉ ስለሚያስቡ ድርጊቱን ከመፈፀም ወደ ኋላ አይሉም፤ ምክንያቱም ወንጀሉን በጋብቻው ካስቀሩ በኋላ ጋብቻውን ደግሞ በቀላሉ ሊተውት ይችላሉና” ሲሉ አስረድተዋል አቶ ዳዊት፡፡
ተጎጂውን ለአካል ጉዳት፣ ለስነ ልቦና ቀውስና ባስ ሲልም ለህልፈት የሚዳርገውን ይህን ፆታዊ ጥቃት ለመከላከልና ከነአካቴውም ለማጥፋት የሁሉንም የጋራ ህብረትና ጥረት ይጠይቃል፡፡
 ጉዳዩ ጊዜ የሚሰጥና ለነገ በይደር የሚተው አይደለም፡፡ ግለሰቦች፣ ቤተሰብ፣ ጎረቤት፣ ማህበረሰብ፣ ፖሊስ (መንግስት)፣ መምህራንና የሥነ ልቦና ባለሙያዎች እንዲሁም የፆታ እኩልነት ተሟጋቾች ዛሬውኑ አገራዊ እንቅስቃሴ መጀመር ይኖርባቸዋል፡፡ ነገ በሃና ላይ ከተፈፀመው ጥቃት የከፋ በሌሎች ላይ ላለመፈፀሙ ምንም ማረጋገጫ እንደሌለን መዘንጋት የለብንም እሳቱን ለማጥፋት ከመረባረብ ቃጠሎ እንዳይነሳ መከላከል የተሻለ አማራጭ ነው፡፡

“አሜሪካ ፆታዊ ጥቃቶችን አጥብቃ ትቃወማለች”
አገራቸው በሴቶች ላይ የሚፈፀሙ ፆታዊ ጥቃቶችን አጥብቃ እንደምትቃወምና የሴቶችን አቅም በመገንባትና በማሳደግ ረገድ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር በህብረት እንደምትሰራ በኢትዮጵያ የአሜሪካ አምባሳደር ፓትሪሺያ ኤም ሃስላክ ገለፁ፡፡ ከህዳር 16 ጀምሮ እስከ ታህሳስ 1 ቀን 2007 ዓ.ም ድረስ በዘለቀው የነጭ ሪባን ቀን፤ በኤምባሲው በተዘጋጁ የተለያዩ ፕሮግራሞች ላይ ከተሳተፉት የአሜሪካ አምባሳደር ጋር የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ መታሰቢያ ካሳዬ የአፍታ ቆይታ አድርጋለች፡፡

አምባሳደር በመሆን ተሹመው ወደ ኢትዮጵያ ከመምጣትዎ በፊት ስለ ኢትዮጵያ ያውቁ ነበር?
በ1980ዎቹ በኢትዮጵያ በተከሰተው ረሃብና የድህነት ችግር ላይ ከአሜሪካ መንግስት ጋር እሰራ ነበር፡፡ በ2010 አለም አቀፍ የድህነት መዋጋትና የምግብ ዋስትና (አሁን Future Initative እየተባለ የሚጠራውን) ድርጅት ወክዬ ወደ ኢትዮጵያ መጥቻለሁ፡፡
አሁን ሲመጡ ምን ለውጥ አዩ?
ብዙ ለውጦች አሉ፡፡ አገሪቱ እያደገች በመሄድ ላይ መሆኗንም ለማየት ችያለሁ፡፡
ፆታዊ ጥቃትን አስመልክቶ ሰሞኑን በተዘጋጁ የተለያዩ ፕሮግራሞች ላይ ተሳታፊ ነበሩ፡፡ ከተደራራቢ የሥራ ኃላፊነትዎ አንፃር ይህን እንዴት ተወጡት?
በሴቶች ላይ የሚፈፀሙ ጥቃቶችን አገሬ አጥብቃ ትቃወማለች፡፡ ለዚህም ነው በፀረ ፆታዊ ጥቃትና ሴቶችን በማብቃት ሥራ ላይ ትኩረት ሰጥተን የምንሰራው፡፡ ይህ የነጭ ሪባን ቀን ደግሞ ለፆታዊ ጥቃቶች ያለንን ተቃውሞ የምናሰማበት ስለሆነ ነው በኤምባሲው በተዘጋጁ ፕሮግራሞች ላይ ሁሉ ተሳታፊ የሆንኩት፡፡ በግሌ ደግሞ ከመሃከለኛው ህዝብ ጋር መሆን ደስታን ይሰጠኛል፡፡ ለሰዎች ድጋፍና ተስፋን ከሚሰጡ ድርጅቶች ጋር አብሮ መስራት እወዳለሁ፡፡ እንዲህ አይነት ቦታዎች ላይ መገኘትም የሚሰጠኝ ደስታ በቀላሉ የሚገመት አይደለም፡፡
በቅርቡ በቡድን በተደረገባት የአስገድዶ መድፈር ጥቃት ህይወቷ ያለፈው ታዳጊ ወጣት ሃና ላላንጐ ጉዳይ በአገሪቱ አነጋጋሪ አጀንዳ ሆኖ ሰንብቷል፡፡ ጉዳዩ በማህበረሰቡ ዘንድ ቁጣን የቀሰቀሰ ቢሆንም አንዳንድ ወገኖች መንግሥት ስለ ጉዳዩ ብዙም ያለው ነገር የለም በማለት ይተቻሉ፡፡ በእናንተ አገር እንዲህ አይነት ጉዳይ ሲያጋጥም የመንግስት ሚና ምንድነው?
የሃና ጉዳይ በኢትዮጵያ ብቻ የተከሰተ ወይንም የሚከሰት ብቻ አይደለም፡፡ በመላው ዓለም የሚከሰትና የተከሰተም ጉዳይ ነው፡፡ ይህንን ለማስቀረት ዋንኛው መፍትሄ ህብረተሰቡን ማስተማር ነው፡፡ ሁሉም ዜጋ ለጉዳዩ ያገባኛል ማለት መቻል አለበት፡፡ ሃላፊነት መውሰድ ይኖርበታል፡፡ ባል ሚስቱን ሲደበድብ ወይም ጐረምሳው ወጣቷን ሲመታ አይቶ በዝምታ ማለፍ አግባብ አይደለም፡፡ ሁሉም ሰው እንዲህ አይነት ፆታዊ ጥቃቶች ሲፈፀሙ ሲያይ ለማስቆም ጥረት ማድረግ ይኖርበታል፡፡ ይህ ከሁሉም ዜጋ የሚጠበቅ ሃላፊነት ነው፡፡ ሴቶች በራሳቸው ላይ የሚፈፀሙ ጥቃቶችን ለማስቆም የሚያስችል አቅም እንዲኖራቸው ለማድረግም ጥረት እናደርጋለን፡፡ በፆታዊ ጥቃቶች ላይ መንግስታችሁ ጥብቅ አቋም እንዳለው አውቃለሁ፡፡ የአስራ ስድስት ቀናቱን የነጭ ሪባን ቀን በማስተባበር እየሰራ የነበረው የሴቶች ጉዳይ ሚኒስቴር ነው፡፡ እናም መንግሥታችሁ በዚህ ጉዳይ ላይ ቁርጠኛ ነው፡፡
የሁለት ሴት ልጆች እናት ነዎት፡፡ አንደኛዋ ልጅዎ በጋዜጠኝነት ሙያ ውስጥ ተሰማርታለች፡፡ የት ነው የምትሰራው? ለጋዜጠኝነት ሙያ ያለዎት ስሜትስ ምን ይመስላል?
ሁለት ሴት ልጆች አሉኝ፡፡ አንዷ ከጥቂት ቀናት በፊት ወደ ኢትዮጵያ መጥታ ለሁለት ሳምንታት ቆይታ ሄዳለች፡፡ ለጋዜጠኝነት ፍቅር አላት፡፡ ከኒውዮርክ ዩኒቨርስቲ ስኩል ኦፍ ጆርናሊዝም ዲግሪዋን ወስዳለች፡፡ በአሁኑ ወቅት ለቢቢሲ ትራቭል እንዲሁም፣ ለኒውዮርክ ታይምስና ለሌሎች መፅሄቶች ትሰራለች፡፡ ለሙያው ጥሩ ስሜት አለኝ፡፡