Administrator

Administrator

የጸረ ሽብርተኝነት ህጉ ይሻሻል ብለዋል
ከዚህ በፊት በሽብርተኝነት የተፈረደባቸው እንዲፈቱ ጠይቀዋል
41 የሰብዓዊ መብት ተሟጋቾች፣ የፕሬስ ነጻነት አቀንቃኞች፣ አለማቀፍና ክልላዊ የሲቪል ማህበረሰብ ተቋማትና የሙያ ማህበራት መንግስት በቅርቡ የሽብርተኝነት ክስ የመሰረተባቸውን ጋዜጠኞችና የዞን 9 ጦማርያን በአፋጣኝ እንዲፈታ ለጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ ከትናንት በስቲያ በላኩት ደብዳቤ መጠየቃቸውን ብሉምበርግ ኒውስ ዘገበ፡፡
ሂዩማን ራይትስ ዎች፣ አምነስቲ ኢንተርናሽናል፣ አርቲክል 19 ምስራቅ አፍሪካ፣ ሲቪል ራይትስ ዲፌንደርስ፣ ወርልድ አሊያንስ ፎር ሲቲዝን ፓርቲሲፔሽን፣ ፔን አሜሪካና የመሳሰሉት አለማቀፍ ድርጅቶች በጋራ በጻፉት ደብዳቤ፣ መንግስት ጋዜጠኞችንና ጦማርያንን በሽብርተኝነት እየከሰሰ ለእስር መዳረጉን መቀጠሉ ያሳስበናል፣ እየተወሰደ ያለው እርምጃ ተገቢነት የሌለው በመሆኑ መገታት ይኖርበታል ብለዋል፡፡
ሶስቱ ጋዜጠኞችና ስድስቱ ጦማርያን ሶስት ወራት ለሚሆን ጊዜ ይህ ነው የሚባል ክስ ሳይመሰረትባቸው ያለአግባብ በእስር ላይ መቆየታቸውንና አንዳንዶቹም በምርመራ ወቅት እንግልት እንደደረሰባቸው መናገራቸውን የጠቀሰው ደብዳቤው፣ ይህም አግባብ አለመሆኑን ገልጿል፡፡
ጋዜጠኞቹና ጦማርያኑ በተመሰረተባቸው የሽብርተኝነት ክስ በረጅም አመታት እስር ብሎም በሞት ሊቀጡ እንደሚችሉ ስጋታቸውን የገለጹት ድርጅቶቹ፤ ይህም አለማቀፍ ህጎችን የሚጥስና በቀጠናው የተረጋጋ ሰላምና ደህንነት ለመፍጠር የሚደረገውን አለማቀፍ ጥረት ዋጋ የሚያሳጣ እርምጃ ይሆናል ብለዋል፡፡
መንግስት አግባብነት በሌለው የጸረ ሽብርተኝነት ህግ በቁጥጥር ውስጥ አውሎ ክስ የመሰረተባቸውን ጋዜጠኞችና ጦማርያን በአፋጣኝ ከእስር እንዲለቅ አስፈላጊውን ሁኔታ እንዲያመቻቹ ለጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ጥያቄ ያቀረቡት እነዚህ ድርጅቶች፤ ከዚህ በፊት በተመሳሳይ ሁኔታ በጸረ ሽብር ህጉ ተከሰው የተፈረደባቸው ዜጎች ጉዳይ አግባብ አለመሆኑን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሳይቀር እንዳመነበትና እንዳወገዘው አስታውሰዋል፡፡
ከጋዜጠኞቹና ከጦማርያኑ በተጨማሪም፣ ከዚህ በፊት በሽብርተኝነት ተከሰውና ተፈርዶባቸው ያለአግባብ በእስር ላይ የሚገኙ ኢትዮጵያውያንን በሙሉ መንግስት በአፋጣኝ እንዲፈታና የጸረ ሽብርተኝነት ህጉንም አለማቀፍ የሰብዓዊ መብቶች መስፈርቶችን በሚያሟላ መልኩ እንደገና አሻሽሎ እንዲያጸድቅ ጠይቀዋል፡፡ኢትዮጵያ የአለማቀፉ የሲቪልና የፖለቲካ መብቶች ስምምነትና የአፍሪካን የሰብዓዊና የህዝብ መብቶች ኮንቬንሽን ፈርማ የተቀበለች ሃገር እንደመሆኗ፣  መንግስት አለማቀፍ ህጎች የጣሉበትን ግዴታ በማክበር መሰረታዊ መብቶቻቸው ተጥሰው ለእስር የተዳረጉ ዜጎችን በሙሉ ከእስር እንዲለቅ ጠይቀዋል፡፡
ደብዳቤውን የጻፉት ድርጅቶች የሚከተሉት ናቸው፡፡
1. Amnesty International 
2. ARTICLE 19 Eastern Africa 
3. Central Africa Human Rights Defenders Network (REDHAC), Central Africa 
4. CIVICUS: World Alliance for Citizen Participation 
5. Civil Rights Defenders, Sweden 
6. Coalition pour le Développement et la Réhabilitation Sociale (CODR UBUNTU), Burundi 
7. Committee to Protect Journalists 
8. Community Empowerment for Progress Organization (CEPO), South Sudan 
9. Conscience International (CI), The Gambia 
10. East and Horn of Africa Human Rights Defenders Project 
11. Egyptian Democratic Association, Egypt 
12. Electronic Frontier Foundation 
13. Ethiopian Human Rights Project (EHRP) 
14. Elma7rosa Network, Egypt  15. English PEN 
16. Freedom Now 
17. Front Line Defenders, Dublin  18. Human Rights Watch 
19. International Women’s Media Foundation (IWMF) 
20. Ligue des Droits de la personne dans la region des Grands Lacs (LDGL), Great Lakes 
21. Ligue Iteka, Burundi 
22. Maranatha Hope, Nigeria 
23. Media Legal Defence Initiative
24. National Civic Forum, Sudan 
25. National Coalition of Human Rights Defenders, Kenya 
26. Niger Delta Women’s movement for Peace and Development, Nigeria 
27. Nigeria Network of NGOs, Nigeria  
28. Paradigm Initiative Nigeria, Nigeria  
29. PEN American Center  30. PEN International  
31. Réseau africain des journalistes sur la sécurité humaine et la paix (Rajosep), Togo  
32. Sexual Minorities Uganda (SMUG), Uganda  
33. South Sudan Human Rights Defenders Network (SSHRDN), South Sudan 
34. South Sudan Law Society, South Sudan  
35. Tanzania Human Rights Defenders Coalition, Tanzania 
36. Twerwaneho Listeners Club (TLC), Uganda 
37. Union de Jeunes pour la Paix et le Développement, Burundi  
38. WAN-IFRA (The World Association of Newspapers and News Publishers)  
39. West African Human Rights Defenders Network (ROADDH/ WAHRDN), West Africa
40. Zambia Council for Social Development (ZCSD), Zambia
41. Zimbabwe Human Rights NGO Forum, Zimbabwe

     የኢትዮጵያ የጤና መድህን ኤጀንሲ ከ “ጤና ለሁሉም ዘመቻ” ጋር በመተባበር ባዘጋጀው “የጤና መድህንን ለህዝብ የማስተዋወቅ ዘመቻ” አገር አቀፍ የዘገባ ውድድር ያሸነፉ ጋዜጠኞችን ከትናንት በስቲያ በኢሊሌ ኢንተርናሽናል ሆቴል ባከናወነው ስነስርዓት ሸለመ፡፡
የህትመት፣ የቴሌቪዥን፣ የሬዲዮና የድረ-ገጽ በሚሉ አራት ምድቦች በተከፋፈለውና ጋዜጠኞች የማህበራዊ ጤና መድህንን በተመለከተ ለአንባቢ፣ ለተመልካችና ለአድማጭ ያቀረቧቸውን ዘገባዎች ለውድድር ባቀረቡበት በዚህ ውድድር ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ የወጡ አሸናፊዎች ከኤጀንሲው ተጠባባቂ ዋና ዳይሬክተር ከዶ/ር መንግስቱ በቀለ እጅ የላፕቶፕ፣ የዘመናዊ ሞባይል ቀፎ፣ የፎቶግራፍ ካሜራና የሰርተፍኬት ሽልማት ተበርክቶላቸዋል፡፡
ዶ/ር መንግስቱ ሽልማቱን ለአሸናፊዎች ከሰጡ በኋላ ባደረጉት ንግግር፤ ጋዜጠኞች፣ የድረ-ገጽ ጸሃፊያንና መገናኛ ብዙሃን ጉዳዩን በተመለከተ በህብረተሰቡ ዘንድ ግንዛቤ በመፍጠር  ኤጀንሲው ለያዘው ዕቅድ መሳካት ትልቅ ሚና እንደሚጫወቱ ጠቅሰው፣ ኤጀንሲው በቀጣይም መሰል ስራዎችን በቅንጅት መስራቱን እንደሚቀጥል ተናግረዋል፡፡
በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት የ “ጤና ለሁሉም ዘመቻ” ዳይሬክተር ወ/ሮ ህይወት እምሻው በበኩላቸው፣ የጤና መድህን በገንዘብ እጦት ምክንያት ተገቢውን የህክምና አገልግሎት ለማግኘት ተቸግረው በህመም ለሚሰቃዩና ለሞት ለሚዳረጉ ዜጎች ትልቅ መፍትሄ እንደሚሆን ተናግረዋል፡፡
የጤና መድህን ስርዓትን በተመለከተ በህብረተሰቡ ውስጥ በቂ ግንዛቤ በመፍጠር ረገድ ብዙ ስራ መሰራት እንዳለበት ጠቁመው፣ በዕለቱ ለሽልማት የበቁትም ሆኑ ሌሎች ጋዜጠኞች ስርዓቱን ለመዘርጋት በሚደረገው ቀጣይ እንቅስቃሴ ውስጥም የራሳቸውን አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ጥሪ አቅርበዋል፡፡ ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ፣ ከመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳይ ቢሮና ከብሮድካስት ባለስልጣን የተውጣጡ የውድድሩ ዳኞች ባካሄዱት ግምገማ፤ በህትመት ዘርፍ መላኩ ብርሃኑ ከአዲስ ጉዳይ መጽሄት፣ ምህረት አስቻለው ከሪፖርተር ጋዜጣ፣ ስመኝ ግዛው ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ በመውጣት ተሸልመዋል፡፡
በድረ-ገጽ ዘርፍ ጋዜጠኛ አንተነህ ይግዛው፣ ጋዜጠኛ ደመቀ ከበደ፣ ጋዜጠኛ ኢዮብ ካሣ ሲያሸንፉ፤ በሬዲዮ ዘርፍ ጋዜጠኛ ገዛኸኝ ተስፋዬ እና ጋዜጠኛ ገናናው ለማ ከደቡብ ክልል መገናኛ ብዙሃን፣ ጋዜጠኛ ገመቺስ ምህረቴ ከፋና ብሮድካስት ኮርፖሬት እንደ ቅደም ተከተላቸው ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ በመውጣት፤ በቴሌቪዥን ዘርፍ ደግሞ ጋዜጠኛ ሰለሞን ገዳ በብቸኝነት አሸናፊ ሆኗል፡፡

ተቃዋሚዎች በአተገባበሩ ላይ ብሔራዊ መግባባት መፈጠር አለበት ይላሉ
የፀረ-ሽብር ህጉ የዛሬ ስድስት ዓመት ገደማ መውጣቱን ተከትሎ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላትና  ጋዜጠኞች በሽብርተኝነት ተከሰው መታሰራቸው በህጉ ላይ የከረረ ተቃውሞ የሚሰነዝሩ ወገኖች እንዲበራከቱ አድርጓል፡፡ አንድነት ፓርቲ መቃወም ብቻም ሳይሆን ህጉ ከእነአካቴው እንዲሰረዝ “የሚሊዮን ድምፆች ለነፃነት” በሚል ባደረገው የፊርማ ማሰባሰብ ዘመቻ፣ ያቀደውን ያህል ድምፅ ማግኘቱን ጠቁሞ  ጉዳዩን ወደ ፍርድ ቤት እንደሚወስደው መግለፁ አይዘነጋም፡፡
የፀረ-ሽብር ህጉ አወዛጋቢነት በአገር ውስጥ ብቻ የተወሰነ አይደለም፡፡ ዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማት፤የፖለቲከኞችና ጋዜጠኞች መታሰርን በመቃወም መንግስት ህጉን፣ተቺዎቹን ለማጥቂያነት እየተጠቀመበት ነው በማለት ይኮንናሉ፡፡   
 የግንቦት 7 ዋና ፀሃፊ አቶ አንዳርጋቸው ፅጌ የመን ላይ ተይዘው ለኢትዮጵያ መንግስት መተላለፋቸውን ተከትሎ አራት የተቃዋሚ ፓርቲ አመራር አባላት ተይዘው መታሰራቸው (በሽብርተኝነት የተከሰሱትን  ጦማሪዎችና ጋዜጠኞች ጨምሮ) በብዙዎች ዘንድ ስጋትን ፈጥሯል፡፡ ፓርቲዎቹም የፖለቲከኞቹን መታሰር  በመቃወም መግለጫዎች አውጥተዋል፡፡ ለመሆኑ በሽብር ወንጀል እየተጠረጠሩ የሚታሰሩ ዜጐች መበራከት በአገሪቱ የፖለቲካ ሁኔታ ላይ ምን አንደምታ ይኖረው ይሆን? በቀጣይስ ሀገሪቷን ወዴት ይመራታል? በሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ዙሪያ የፓርቲ አመራሮችና የህግ ባለሙያዎች የሰጡንን አስተያየት እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡


“በኢትዮጵያ ሽብርተኛ ማለት ነፃነትን መሻት፣ እውነትን መፈለግ ነው”
(ኢ/ር ይልቃል ጌትነት፤የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር)

ሽብርና ሽብርተኝነት አሁን በኢትዮጵያ ባለው ግንዛቤ፤ እውነት ለሚናገሩ፣ለህብረተሰቡ መብት መከበር ለሚቆሙ፣ መንግስትን አምርረው ለሚተቹ ሰዎች የሚሰጥ ስም ነው፡፡ በየጊዜው ሽብርተኛ እየተባሉ የሚታሠሩት የማህበረሰብ መሪዎች፣ ጋዜጠኞችና የፖለቲካ መሪዎች ናቸው፡፡ ስለዚህ ሽብርተኛ ማለት  ነፃነትን መሻት፣ እውነትን መፈለግና  መንግስትን መተቸት ሆኗል፡፡
መንግስት ሰዎችን በብዛት ማሰሩ አቅመቢስ እየሆነ መምጣቱን ያሳያል፡፡ የህዝብ ጥያቄ እያሸነፈ መንግስት  ተቀባይነት እያጣ ሲመጣ ነው ሁሉን ነገር በጉልበት ለማድረግ የሚፈልገው፡፡ በአንፃሩ እውነትን የሚፈልጉ ሰዎች በታሰሩ ቁጥር የነፃነት ትግሉ እየተፋፋመ እንደሆነ ነው የሚያሳየው፡፡ በዚህ ረገድ እኔ ብሩህ ተስፋ ይታየኛል፡፡ ምክንያቱም ለእውነት ብለው ለመታሰር የሚደፍሩ ሰዎች (እነ አንዷለም ከታሰሩበት ጊዜ ጀምሮ) እየበዙ ነው፡፡ ለመታሰር ዝግጁ የሆኑ ሰዎች በዙ ማለት ወደ ለውጥ መቅረባችንን ያመለክተናል፡፡


አዋጁ በአግባቡ እየተተረጐመ አይደለም”
ዶ/ር ጫኔ ከበደ፤ የኢዴፓ ሊቀመንበር)


በአጠቃላይ መንግስት እየተከተለ ያለው አካሄድ ለዲሞክራሲ ግንባታው በጣም እንቅፋት እየፈጠረ ነው፡፡ በተለይ የፀረ ሽብር አዋጅን በተመለከተ የአተረጓጐም ስህተት እየተከተለ ነው የሚል ግንዛቤ አለን፡፡
የፀረ ሽብር ህግ ቢያስፈልገንም አተረጓጐሙ ግን በአግባቡ መሄድ አለበት፡፡ መንግስት የራሱን ጥቅም ለማስከበርና የገዥውን ፓርቲ እድሜ ለማራዘም ብቻ የተናገረውንም፣ ጦር ይዤ እታገላለሁ የሚለውንም፣ የሚጽፍበትንም--- በአጠቃላይ ገዥውን ፓርቲ የማይደግፈውን  ሁሉ በሽብር ስም ማሠሩ የተሳሳተ አካሄድ ነው፡፡
ይሄ አጠቃላይ የዲሞክራሲ ሂደቱን የሚያስተጓጉል ሲሆን የህብረተሰቡንም መብት የሚጫን፣ የፖለቲካ ፓርቲዎቹንም አካሄድ ሊያበላሽ የሚችል፤ ወደ ኋላ እየመለሰን ያለ አካሄድ እንደሆነ ኢዴፓ ያምናል፡፡
ከዚህ አንፃር ገዥው ፓርቲ፣ ለዲሞክራሲ ግንባታ ምንም አይነት ቁርጠኝነት እያሳየ አለመሆኑን እንዲሁም  የስርአት ለውጥ በተጨባጭ ከምርጫ ሳጥን እንዳይገኝ፣ መጪውን ምርጫ ለማበላሸት እየተከተለው ያለው መንገድ ነው ብለን እናምናለን፡፡
የኛ ፓርቲ ብሔራዊ መግባባትን እንደ አንድ ትልቅ አጀንዳ ይዞ ይንቀሳቀሳል፡፡ መንግስት ብሔራዊ መግባባት መፈጠር አለበት ሲባል “የተጣላ ሰው የለም፤ማንን ከማን ለማግባባት ነው” የሚል መልስ ይሰጣል፡፡ ነገር ግን ገዥው ፓርቲ ቆም ብሎ በዚህ ጉዳይ ላይ ማሰብ አለበት፡፡ ሌሎች ተቃዋሚ ፓርቲዎችም በተለያዩ ዲፕሎማሲያዊ አካሄዶች መንግስትን ብሔራዊ መግባባት እንዲፈጠር የምንጠይቅበትን አካሄድ በጋራ መፈለግ ይገባናል። አለበለዚያ ለህዝባችን ምንም ነገር ሳንሰራ፣ የቆምንለትን አላማ ሳናሳካ እንዲሁ ዝም ብለን ጊዜ መፍጀት ይሆናል፡፡
በፀረ ሽብር ህጉም ላይ ቢሆን የጋራ ግንዛቤና መግባባት መያዝ ያስፈልጋል፡፡ ህጉ በጣም አስፈላጊ ነው፤ በአተረጓጐሙ ዙሪያ ግን የጋራ ግንዛቤ ሊኖረን ይገባል፡፡ ሲረቀቅ ጀምረን እስካሁን በአተረጓጐሙ ላይ ተቃውሟችንን ስናቀርብ ቆይተናል፡፡ በህጉ አተረጓጐም ላይ የጋራ ግንዛቤ ሊኖረን ይገባል፡፡ ተቃዋሚ ፓርቲዎችም ተቃራኒ ሃሳብን ለማስተናገድ ዝግጁ መሆን ይጠበቅባቸዋል፡፡ እንደውም ተቃዋሚ ፓርቲዎች በጋራ ቁጭ ብለን መግባባት ይኖርብናል፡፡


 “ሽብርተኛ ስለመሆናቸው መንግስት ተጨባጭ ማስረጃ አያቀርብም”

(አቶ ጥላሁን እንደሻው፤ የመድረክ አመራር)


በሠላማዊ ትግሉና ሠላማዊ ታጋዮች ላይ በሽብርተኝነት ስም የሚወሰዱት እርምጃዎች፣ሽብርተኝነት የሚለውን ስያሜ በአግባቡ እንዳንረዳ እያደረገን ነው ያለው፡፡ ሽብርተኝነት ሲባል በአለማቀፍ ደረጃ የታወቁ ነገሮች አሉ፡፡ አሸባሪዎች በሃይል አስፈራርተው የራሳቸውን ፖሊሲና አማራጭ ሌላው እንዲከተል በማድረግ፣ “ይሄን ባታደርግ እንዲህ አደርጋለሁ” የሚሉ ናቸው፡፡ መድረክም ይህን መሰሉን ድርጊት አጥብቆ ይቃወማል፡፡ አሁን በኛ ሀገር እነዚህ አሸባሪ ተብለው የሚወነጀሉ ሰዎች ይሄንን አድርገዋል ወይ? ማንን ነው ያስገደዱት? ማንን ነው ያስፈራሩት? በማን ላይ ነው እርምጃ የወሰዱት? በሚለው ላይ መንግስት በተጨባጭ ማስረጃ አያቀርብም፡፡ በዚህም ሳቢያ እኛም አሸባሪ ስለመሆናቸው ምንም ልንገነዘብ አልቻልንም፡፡ ጭራሽ አሸባሪ በሚለው ጉዳይ ላይ ግራ እንድንጋባ እየሆንን ነው፡፡ ሽብርተኝነት የሚለው በራሱ ግልጽነት ይጐድለዋል፡፡
መንግስት የሽብርተኝነትን ትርጓሜ ጥርት አድርጐ ባለማስቀመጡ፣ ህጉን ሠላማዊ ሰዎችን ለማስፈራሪያነት እየተጠቀመበት ነው የሚል ስጋት አለን፡፡ የሽብር ክሶችና እስራት እየተጠናከረ መቀጠሉ ምርጫው እየተቃረበ ሲመጣ፤ ለማሸማቀቅና የፍርሃት ድባብን ህዝብ ላይ ለመጫን ነው፡፡ ህዝብ በፍርሃትና በመሸማቀቅ የተሣተፈበት ምርጫ ደግሞ ዲሞክራሲያዊ ምርጫ ሊሆን አይችልም። ሰው ተደፋፍሮ ከውስጡ መሸማቀቅና ፍራቻን እንዲያስወግድ ከተፈለገ፣ አሸባሪን ከሰላማዊ ትግል የሚለይ ነገር መቀመጥ አለበት፡፡ አለበለዚያ አሁን የተያዘው የሽብርተኝነት ግንዛቤ በምርጫም ሆነ በፖለቲካ ሠላማዊ ትግል ላይ አሉታዊ ተጽእኖ ያሳድራል፡፡ ግንዛቤውን ለማጥራትም ሆነ ችግሩን ለመፍታት ብሔራዊ መግባባት ያስፈልገናል። ሽብርተኝነት ምንድን ነው በሚለው ጉዳይ ላይ ብሔራዊ መግባባት ሊኖረን ይገባል፡፡ ሽብርተኝነትን እንዴት በጋራ እንታገል በሚለው ላይም በተመሳሳይ የጋራ መግባባት መፈጠር አለበት፡፡ ብሔራዊ መግባባት ካለ የሽብር አደጋዎችን ሁሉ መከላከል እንችላለን፡፡ ገዥው ፓርቲ የውይይት በሮችን ሁሉ መዝጋቱን ትቶ፣ ተቃዋሚዎችን እንደጠላት መመልከቱን አቁሞ፣ ብሔራዊ መግባባት የሚፈጠርበትን የውይይት መድረክ ሊያመቻች  ይገባዋል፡፡

===========
“አዋጁ የምርጫ 97 ውጤት ነው”
(ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው፤ የአንድነት ሊቀመንበር)

ፓርቲዬ አንድነት የፀረ - ሽብር አዋጁ፤ የዲሞክራሲ ሂደቱን የማፈን ጥረት ውጤት ነው ብሎ ያምናል፡፡ በዚህ መሠረት በ“የሚሊዮኖች ድምጽ ለነፃነት” ላይ በዋናነት የፀረ ሽብር ህጉ እንዲሰረዝ ጠይቀናል፡፡ ህጉ ከየት መጣ ብለን ከጠየቅን፣የምርጫ 97 ውጤት ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ኢህአዴግ በነፃ ምርጫ ማሸነፍ እንደማይችል ሲረዳ፣ የዲሞክራሲ ተቋማትን የማፈን እንቅስቃሴ ውስጥ ነው የገባው፡፡ ሚዲያዎችን፣ ፓርቲዎችን፣ሲቪል ማህበራትን ማፈን የሚለውን እንደ አማራጭ ለመጠቀም ስለፈለገ፣ በእያንዳንዱ ጉዳይ አዋጅ አውጥቶበታል፡፡ ስለዚህ የፀረ ሽብር ህጉም የዲሞክራሲ ስርአቱን ሙሉ ለሙሉ ለማዳፈን የወጣ ነው ብለን እናምናለን፡፡
እኛ የፀረ ሽብር ህጉ መሠረዝ አለበት ስንል፣ ሽብርተኝነትን እንደግፋለን ማለት አይደለም፡፡ ከማንም በላይ ሽብር ለሃገራችን አስጊ ነው በሚል እምነት፣ ፓርቲዬም ሆነ እኔ ከመንግስት ጐን ተሠልፈን የምንዋጋው ጉዳይ ነው፡፡ ነገር ግን አሁን  ያለው አዋጅ እየተተረጐመበት ባለው አግባብ ላይ ከፍተኛ ጥያቄ አለን፡፡
ሚዲያው አካባቢ ሲኬድ በከፍተኛ ሁኔታ ራሱን በራሱ የሚገድብ (Self censorship) ሆኗል። ሲቪል ሶሳይቲውም የኢህአዴግን ቡራኬ ካላገኘ መኖር አይችልም፡፡ ይሄ ዲሞክራሲውን በእጅጉ ይጐዳል፡፡
ኢህአዴግ ኳሱ በእጁ ነው፡፡ ሁኔታዎች በዚህ መልኩ ሊቀጥሉ አይችሉም፡፡ የሆነ ቦታ መቆማቸውም አይቀርም፡፡
ስለዚህ ዲሞክራሲው እንዳይቀጭጭ፣ እንዳይጐዳ ኳሱን በእጁ የያዘው ኢህአዴግ ቆም ብሎ ማሰብ ይኖርበታል፡፡ የዲሞክራሲ ሂደቱ በሚፈቅደው መጠንም ብሔራዊ መግባባት ላይ እንዲደረስ መድረኩንም መፍጠር አለበት፡፡ እኛ በዚህ አዋጅ ላይ ብቻ ሳይሆን በአጠቃላይ በፍትህና በዲሞክራሲያዊ ስርአቱ ላይ ከብሔራዊ መግባባት የሚያደርስ ውይይት እንዲፈጠር እንፈልጋለን፡፡ ብሔራዊ መግባባት መኖር አለበት፡፡   


“ህጉ ለኛ አስፈላጊ ነው ወይ?”

(አቶ ተማም አባቡልጉ፤ ጠበቃና የህግ አማካሪ)

ብዙ ሰው ህጉ በአግባቡ መተርጐም አለበት በሚለው ላይ ነው ጥያቄ የሚያነሳው፡፡ እኔ ደግሞ ህጉ ለኛ አስፈላጊ ነው ወይ የሚለውን ነው የምጠይቀው፡፡ ህጉ ላይ የተጠቀሱት ነገሮች እኮ በወንጀለኛ ህጉ ላይ አሉ፡፡ እንደገና በሌላ መልክ መምጣታቸው አግባብ አልነበረም፡፡ በዚህ ጉዳይ የሚከሰሱ ሰዎችን ስንመለከት ፖለቲከኞች ናቸው፡፡ ከዚህ አንጻር “ህጉ ለማጥቂያነት አልዋለምን?” የሚል ጥያቄ ያስነሳል፡፡ የሽብር አዋጅ በየትኛው ዓለም ቢሆን በአገር ላይ የሚደርስን ጥቃት  የሚከላከል እንጂ ፓርቲን፣ ጋዜጣንና ሃሳብን በነፃነት መግለጽን አይደለም መገደብ ያለበት፡፡ ለምሣሌ ሩዋንዳ በህጓ ላይ ሃሳብን የመግለጽ ነፃነትን በተመለከተ፣ ቀጥታ የጅምላ ጭፍጨፋን የሚያነሳሱ ሃሳቦችን ለይታ ነው ገደብ ያበጀችው፡፡ የኛ ግን ጥቅል ነው፡፡ ይሄን አይመለከትም ተብሎ ተለይቶ መቀመጥ አለበት። በእንግሊዝ ሀገር ህጉ ሲወጣ ፖለቲከኞች “አንዴ ስልጣን ላይ የወጣው መንግስት ስልጣን እንዳይለቅ የማድረጊያ መንገድ ሆኗል” ብለው ነው ህጉን ኋላ ላይ ያስቀሩት፡፡ ስለዚህ በኛም ሃገር ህጉ ለፖለቲካ ማጥቂያ አይውልም ተብሎ አይታሰብም፡፡

  •      መንገደኞች በአውሮፕላን መጓዝ እየፈሩ ነው፣ ባለሙያዎች አደጋ ቀንሷል እያሉ ነው
  • የኢንሹራንስ ኩባንያዎች በአመት 65 ሚ. ዶላር ይሰበስባሉ፣ በ5 ወር ብቻ 600 ሚ. ዶላር ካሳ ይከፍላሉ

            አመቱ ለአለማችን የአየር ትራንስፖርት የቸር አልሆነም - በተለይ ደግሞ ለማሌዢያ፡፡ ከወራት በፊት የማሌዢያ አየርመንገድ ቦይንግ 777 አውሮፕላን 239 ሰዎችን ይዞ ከኳላላምፑር ወደ ቤጂንግ በመብረር ላይ ሳለ፣ ድንገት ከራዳር እይታ ውጭ ሆነ፡፡ አለም ድንገት ደብዛው የጠፋውን አውሮፕላን ፍለጋ ውቅያኖስ አሰሰ፤ ከወዲያ ወዲህ ተራወጠ፤ ወደ ሰማይ አንጋጠጠ፡፡ ከዛሬ ነገ ይገኛል በሚል ተስፋ ፍለጋው ለወራት ዘለቀ - ተስፋ እንደራቀ፡፡ አንዳች እንኳን ተጨባጭ መረጃ ሳይገኝ፤ አውሮፕላኑን የበላው ጅብ ሳይጮህ፣ ነገሩ እንቆቅልሽ እንደሆነ ዘለቀ፡፡ ማሌዢያ በላይዋ ላይ የደረበችውን ማቅ ሳታወልቅ፣ ያለፈው ሃዘን ሳይወጣላት፣ በሆነው ነገር ሳትጽናና ሌላ ነገር ሆነ - ሌላ አውሮፕላኗ በአሰቃቂ ሁኔታ ተከሰከሰ፡፡ ይህ ክስተት ለማሌዢያ ብቻም ሳይሆን ለአጠቃላዩ የአቪየሽን ኢንዱስትሪና ለመላው አለም አስደንጋጭ መርዶ ነበር፡፡

የማሊዢያው አየር መንገድ አውሮፕላን ከቀናት በፊት በበረራ ቁጥር ኤም ኤች 17 ከአምስተርዳም ተነስቶ ወደ ኳላላምፑር በመጓዝ ላይ እያለ፣ ዩክሬንንና ሩስያን በሚያዋስነው ድንበር ላይ በሚሳዬል ተመትቶ መውደቁንና 298 ሰዎች መሞታቸውን ተከትሎ፣ ግጭት ባለባቸው አካባቢዎች የአየር ክልል ውስጥ መብረር ወይም አለመብረር የዓለማችን ታላላቅ አየር መንገዶች ዋነኛ ጥያቄና ጭንቀት ሆኗል፡፡ ብዙዎቹ አለማቀፍ የሲቪል አቪዬሽን ተቆጣጣሪዎች በዚህ የግጭት አካባቢ በረራ እንዳያደርጉ በአየርመንገዶች ላይ እገዳ ባለመጣላቸው ወይም ማስጠንቀቂያ ባለመስጠታቸው፤ አብዛኛዎቹ አየርመንገዶች የአየር ክልሉን በማቋረጥ ከአውሮፓ ወደ ደቡብ ምስራቅ እስያ መጓዛቸውን ቀጥለው ነበር፡፡ በአካባቢው የተቀሰቀሰው ግጭት ስጋት ያጫረባቸው ኤር በርሊን፣ ኮሪያን ኤርና ኤር ስፔስን የመሳሰሉ የተለያዩ አገራት አየር መንገዶች ግን፣ ወደዚህ አየር ክልል ድርሽ ማለት ካቆሙና ዙሪያ ጥምጥም መብረር ከጀመሩ ወራት አልፏቸዋል፡፡ “መሰል ግጭቶች ያሉባቸው አካባቢዎች ለአየር መንገዶችና ለአጠቃላዩ የአለማችን የአቪዬሽን ኢንዱስትሪ ስጋት ሆነዋል፡፡

እኛም ስጋት ስለገባን በተቻለን መጠን ከአካባቢዎቹ ስንርቅ ቆይተናል፡፡ ከግጭት አካባቢዎች ለመሸሽ የበረራ መስመሮችን መቀየር፣ ለተጨማሪ ወጪ መዳረጉ አይቀሬ ነው። አየር መንገዳችን ግን፣ ለደህንነት ሲል ተጨማሪ ወጪ ሲያወጣ ነው የቆየው” ብለዋል የኤዥያና አየር መንገድ ቃል አቀባይ፡፡ የማሌዢያ ትራንስፖርት ሚኒስትር ሊሎ ቲዮንግ የአገራቸው አውሮፕላን ከሰሞኑ አደጋ ላይ መውደቁን ተከትሎ ከተለያዩ አካላት ለምን በአደገኛ አየር ክልል ውስጥ በረረ በሚል የተሰነዘረበትን ትችት አልተቀበሉትም፡፡ “ይህን የአየር ክልል እያቋረጥን መጓዝ ከጀመርን አመታት ተቆጥረዋል፡፡ ምንም የገጠመን ችግር አልነበረም፡፡ ደህንነቱ የተረጋገጠ ክልል ነው፡፡ ሌሎች አየር መንገዶችም ይሄን ክልል እያቋረጡ መብረራቸውን ቀጥለዋል፡፡ ታዲያ እኛ ለምንድን ነው የምናቆመው?” ሲሉ ጠይቀዋል ቲዮንግ፡፡ የማሌዢያው አየር መንገድ አውሮፕላን አደጋ ኣለምን አሳዝኖ ሳያበቃ፣ ከቀናት በኋላም ሌላ አሳዛኝ ክስተት ተፈጠረ፡፡

በበረራ ቁጥር ጂ ኢ 222 በረራ ላይ እያለ ባጋጠመው አስቸጋሪ የአየር ጠባይ ሳቢያ፣ በታይዋኗ የፔንጉ ደሴት ለማረፍ በመሞከር ላይ የነበረውና ንብረትነቱ የትራንስ ኤዥያ አየር መንገድ የሆነው አውሮፕላን ታይዋን አካባቢ ተከሰከሰ፡፡ 47 ሰዎችም ለህልፈተ ህይወት ተዳረጉ፡፡ የአቪየሽን ዘርፉ መርዶ አላበቃም፡፡ ባለፈው ረቡዕ ደግሞ ሌላ አሳዛኝ የአቪየሽን ኢንዱስትሪ መርዶ ተሰማ፡፡ 116 ተሳፋሪዎችን ይዞ በበረራ ቁጥር ኤኤች 5017 ከቡርኪናፋሶ በመነሳት ወደ አልጀርስ በመጓዝ ላይ የነበረ ንብረትነቱ የኤር አልጀሪያ አየር መንገድ የሆነ አውሮፕላን በአሰቃቂ ሁኔታ ተከሰከሰ፡፡ ቀጠለናም የታይዋን አየርመንገድ አውሮፕላን ተከስክሶ ከ50 በላይ ሰዎች ለህልፈተ ህይወት ተዳረጉ፡፡ እነዚህ ሰሞንኛ አሰቃቂ አደጋዎች፣ ብዙዎች የአቪየሽን ኢንዱስትሪውን እንዲጠራጠሩት አድርጓል ይላል ዩ ኤስ ቱዴይ፡፡ አደጋዎቹ አንድ ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ መከሰታቸውን በጥርጣሬ ያዩት እንዳሉ የጠቆመው ጋዜጣው፣ የኢንዱስትሪው ኤክስፐርቶች ግን ነገሩ ከሁኔታዎች መገጣጠም የዘለለ ትርጉም የለውም ስለማለታቸው ዘግቧል፡፡ “የማሌዢያው ተመትቶ፣ የትራንስ ኤዢያው ደግሞ በአየር ጠባይ ሳቢያ ነው አደጋ የደረሰባቸው። የሁለቱ አደጋዎች በተቀራራቢ ጊዜ መከሰት አጠቃላዩን ኢንዱስትሪ ስጋት ላይ የሚጥልም ሆነ፣ ተሳፋሪዎች የአውሮፕላን ጉዞ አደገኛ ነው ብለው እንዲደመድሙ የሚያስችላቸው አይደለም” ብለዋል በፍራንሲስኮ አትሞስፌር ምርምር ተቋም የጉዞ ተንታኝ የሆኑት ሄነሪ ሃርቲልት፡፡

ጆን ቤቲ የተባሉት የበረራ ደህንነት ፋውንዴሽን ፕሬዚደንትም ቢሆኑ፣ የአቪየሽን ኢንዱስትሪው እንደተባለው ደህንነት የጎደለውና መንገደኞችን ስጋት ላይ የሚጥል፣ ሌላ አማራጭ እንዲወስዱ የሚያነሳሳበት ደረጃ ላይ አይደለም ባይ ናቸው፡፡ “ባለፉት አስርት አመታት የአለማቀፉ የንግድ አቪየሽን ደህንነት እጅግ የሚገርም ደረጃ ላይ ደርሷል። አልፎ አልፎ መሰል አደጋዎች ሊፈጠሩ ቢችሉም፣ ክስተቶቹ የኢንዱስትሪውን አስተማማኝነት ጥያቄ ውስጥ አያስገቡትም። አደጋዎቹ አሳዛኝ ናቸው፤ የንግድ አቪየሽንም አሁንም ድረስ መቢገርም ሁኔታ ደህንነቱ የተረጋገጠ ነው!” ብለዋል ቤቲ፡፡ አመቱ ለአየር መንገዶች የመከራ ነበር የሚሉ ተበራክተዋል፡፡ የስታር ዶት ኮሙ ዘጋቢ ቫኔሳ ሉ ግን፣ ይህ አመት የአለማችን የንግድ አቪየሽን ከቀደምት አመታት የተሻለ ከአደጋ ነጻ የነበረበት ነው፡፡ የአለማቀፉ የአቪየሽን ደህንነት ኔትዎርክ ፕሬዚደንት ጠቅሶ ዘጋቢው እንዳለው፣ በዚህ አመት የተከሰቱ አደጋዎች ቁጥር ባለፉት አስር አመታት ከተከሰቱት አደጋዎች አማካይ ቁጥር በእጅጉ ያነሰ ነው፡፡ እርግጥ በአንድ አደጋ ለሞት የሚዳረጉ የአውሮፕላን ተሳፋሪዎች ቁጥር እየጨመረ መጥቷል፡፡

በቅርቡ በተከሰከሱት ሁለቱ የማሌዢያ አውሮፕላኖች ብቻ 537 ሰዎች ለሞት ተዳርገዋል፡፡ ዘስታር ዶት ኮም እንደዘገበው፣ በዚህ አመት ብቻ በአለማችን 11 አሰቃቂ የአውሮፕላን አደጋዎች ተከስተዋል፡፡ የአለማቀፉን የአየር ትራንስፖርት ማህበር መረጃ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ባለፈው አመት በተከሰቱ መሰል 11 አደጋዎች የሞቱ ሰዎች ቁጥር 210 ነበር፡፡ ባለፈው አመት በአለማቀፍ ደረጃ ከ36 ሚሊዮን በላይ በረራዎች ተደርገው፣ ከ3 ቢሊዮን በላይ መንገደኞች ያለምንም አደጋ ካሰቡበት መድረሳቸቸውንም መረጃው ያስታውሳል። በመሆኑም የኢንዱስትሪው ደህንነት አደጋ ላይ ነው ብሎ ለመደምደም የሚያበቃ ምንም ነገር የለም፡፡ በቅርብ የተከሰተውን የማሌዢያው አየር መንገድ አደጋ ተከትሎ ስጋት ውስጥ የገቡት መንገደኞችና አየርመንገዶች ብቻም አይደሉም፡፡ የአውሮፕላን ኢንሹራንስ ኩባንያዎች ጭምርም እንጂ፡፡

ኒውዮርክ ታይምስ ከሰሞኑ እንደዘገበው፣ ለአየር መንገዶች የአደጋ ዋስትና የሚሰጡ ታላላቅ የኢንሹራንስ ኩባንያዎች በተደጋጋሚ በሚከሰቱ አደጋዎች ሳቢያ የሚያወጡት ወጪ እየናረ በመምጣቱ ጭንቀት ውስጥ ገብተዋል፡፡ በተለይ ደግሞ በጦርነት ቀጠናዎች አካባቢ ለሚንቀሳቀሱ አውሮፕላኖች ዋስትና የሚሰጡ የኢንሹራንስ ኩባንያዎች የችግሩ ዋነኛ ገፈት ቀማሽ ሆነዋል፡፡ የጦርነት አደጋ ዋስትና ደንበኞቻቸው ከሆኑ አየር መንገዶች በአመት በድምሩ 65 ሚሊዮን ዶላር ያህል ገንዘብ የሚሰበስቡ የኢንሹራንስ ኩባንያዎች፣ ባለፉት አምስት ወራት ብቻ በአውሮፕላኖች ላይ ለተከሰቱ አደጋዎች 600 ሚሊዮን ዶላር የካሳ ክፍያ መክፈላቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ ኩባንያዎቹ ምን ያህል ለከፍተኛ ወጪ እንደተዳረጉና የኪሳራ ሰለባ እየሆኑ እንደሚገኙ ገልጧል፡፡ ተደጋግመው የሚሰሙት የአውሮፕላን አደጋዎች መንገደኞችን ስጋት ውስጥ ከቷቸዋል። ዘጋርዲያን ከትናንት በስቲያ ባስነበበው ጽሁፉ እንዳለው፣ ተደጋግመው የተከሰቱት የአውሮፕላን አደጋዎች አንዳንዶች ይህን የትራንስፖርት ዘርፍ በጥርጣሬና በስጋት እንዲያዩት አድርገዋቸዋል፡፡ በአውሮፕላን መጓዝ ለመሞት ፈቅዶ ትኬት መቁረጥ ነው ብለው ማሰብ የጀመሩ አልታጡም። ዘጋርዲያን ግን፣ ይህ ጅልነት ነው ይላል፡፡

የአለማቀፉን የሲቪል አቪየሽን ድርጅት መረጃ ጠቅሶ ዘጋርዲያን እንደጻፈው፣ ባለፈው የፈረንጆች አመት በአለማቀፍ ደረጃ በተደረጉ በረራዎች የተከሰቱ አደጋዎች ሲሰሉ፣ ከ300 ሺህ በአንዱ ላይ ብቻ ነው አደጋ የተከሰተው፡፡ ይህም በአውሮፕላን አደጋ እሞት ይሆን የሚለው ስጋት ከንቱ መሆኑን ያሳያል ይላል ዘገባው፡፡ እንዲህ ያለ ስጋት የገባችሁ መንገደኞች፣ ከአደጋው ይልቅ ስጋቱ ይገላችኋል ያለው ዘጋርዲያን፣ ለዚህም የአሜሪካውን የመንትያ ህንጻዎች አደጋ በዋቢነት ይጠቅሳል፡፡ አደጋው በተከሰተ በቀጣዩ አመት በርካታ አሜሪካውያን አውሮፕላን ትተው መኪና ወደመጠቀም ዞሩ። የአውሮፕላን ተጠቃሚዎች ቁጥር እስከ 20 በመቶ ቀነሰ፡፡ በአንጻሩ ደግሞ መኪና ተጠቃሚው በመብዛቱ መንገዶች ተጣበቡ፡፡ ረጅም ርቀት ማሽከርከር ታዲያ፣ ከአውሮፕላን የባሰ ለአደጋ የሚያጋልጥ አስጊ ነገር ወደመሆን ተሸጋገረ፡፡ በአቪየሽን መስክ ጥናት በማድረግ የሚታወቁትን ጀርመናዊ ፕሮፌሰር ገርድ ጊገንዘርን ጥናት ጠቅሶ ዘገባው እንደጠቆመው፣ በዚያው አመት በአገሪቱ በመኪና አደጋ ህይወታቸውን ያጡ ሰዎች ቁጥር በ1 ሺህ 595 ጭማሪ አሳየ፡፡ ቀስበቀስም አርም አውሮፕላን ብለው የነበሩ መንገደኞች ምርጫ በማጣት ፊታቸውን ወደ አውሮፕላን መልሰው አዞሩ፡፡

============

ባለፉት ሰባት ወራት በአለማችን የተከሰቱ የአቪየሽን አደጋዎች

ሃምሌ 24 የታይዋን አየር መንገድ አውሮፕላን ሃምሌ 23 የአልጀሪያ አየር መንገድ አውሮፕላን

ሃምሌ 23 የትራንስ ኤዥያ አየር መንገድ አውሮፕላን ሃምሌ 17 የማሌዢያ አየር መንገድ አውሮፕላን

ሃምሌ 7 የቬትናም አየር ሃይል አውሮፕላን

ሃምሌ 5 በፖላንድ የግል አየር መንገድ አውሮፕላን

ሃምሌ 2 የስካይዋርድ ኢንተርናሽናል አቪየሽን አውሮፕላን ሰኔ 14 የዩክሬን አየር ሃይል አውሮፕላን

ግንቦት 31 የማሳቹሴትስ የግል ቻርተርድ አውሮፕላን ግንቦት 17 የላኦስ አየር ሃይል አውሮፕላን ግንቦት 8 የአሊሳና ኮሎምቢያ አየር መንገድ አውሮፕላን ሚያዝያ 20 የሱሜን ኡርሂሊዩሊሜሊጃት አየር መንገድ አውሮፕላን ሚያዝያ 19 የሊኒያስ ኤሪያስ ኮመርሺያሌስ አየርመንገድ አውሮፕላን

ሚያዝያ 8 የሃጊላንድ አቪየሽን ሰርቪስስ አውሮፕላን

መጋቢት 28 የህንድ አየር ሃይል አውሮፕላን መጋቢት 22 የስካይዳይቭ ካቦልቸር አየርመንገድ አውሮፕላን

መጋቢት 18 የሄሊኮፕተርስ ኢንክ ኮሞ ቲቪ ሄሊኮፕተር

መጋቢት 8 የማሌዢያ አየርመንገድ አውሮፕላን

የካቲት 26 የማኦይ አየርመንገድ አውሮፕላን

የካቲት 21 የሊቢያ ኤር ካርጎ አውሮፕላን

የካቲት 16 የኔፓል አየር መንገድ አውሮፕላን

ጥር 20 የስኳላ ሱፐርየራ ዲ አቪየቴ ሲልቫ አውሮፕላን

ጥር 18 የትራንስ ጉያና አየር መንገድ አውሮፕላን

           ከእያንዳንዱ ስኬታማ ወንድ በስተጀርባ ሴት ትኖራለች የሚለው አመለካከት ከዓለም ዋንጫው ጋር በተያያዘ ሲያነጋግር ሰንብቷል፡፡ የታዋቂ እግር ኳስ ተጨዋቾች ሚስቶች፤ እጮኛዎችና የፍቅር ጓደኞች የእንግሊዝ ሚዲያዎች ‹‹ዋግስ› የሚል ስም አውጥተውላቸዋል፡፡ ከዝነኛ ስፖርተኞች ጋር ግንኙነት ያላቸው ሴቶች እንደማለት ነው፡፡ በዓለም ዋንጫው ሰሞን ሴቶቹ ከየብሄራዊ ቡድኑ ተጨዋቾች ጋር በነበራቸው ግንኙነት ዙርያ አሰልጣኞች ያወጧቸው አንዳንድ የስነምግባር ደንቦች አወዛግበዋል፡፡ በተለያዩ ዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃናት የዝናቸው መጠን፤ ቁንጅናቸው፤ ለእግር ኳስ ባላቸው ፍቅር፤ ስለውድድሩ በሚሰጧቸው አስተያየቶች እየተነፃፀሩ ደረጃ ሲሰጣቸውም ነበር፡፡ ባሎቻቸውን ፤ እጮኛዎቻቸው እና ፍቅረኛዎቻቸውን ተጨዋቾችን ለማበረታት በየስታድዬሙ ማልያዎችን በመልበስ እና ባንዲራዎችን በማውለብለብ ድጋፍ በመስጠት ታውቀዋል። እነዚህ በዓለም ዋንጫው የደመቁ ሴቶች ልዩ ልዩ ሙያዎች ያላቸው ናቸው፡፡ ብዙዎቹ ሞዴሎች ናቸው። ተዋናዮች፣ ሙዚቀኞች፣ ጋዜጠኞችና የቤት እመቤቶችም ከመካከላቸው ይገኙበታል፡፡

ከጀርመን ጀርባ የነበረው ምስጥራዊ ግብረኃይል የጀርመን ብሄራዊ ቡድን 20ኛውን ዓለም ዋንጫ አሸንፎ በተሸለመበት የመዝጊያ ስነስርዓት የተጨዋቾች ሚስቶች፤ ፍቅረኛዎች፤ ጓደኞች እና ቤተሰቦች በጋራ ደስታቸውን ሲገልፁ መላው ዓለም በትዝብት የተከታተለው ነበር፡፡ በጀርመን ቡድን ዙርያ የተሰባሰቡት እነዚህ ሴቶች በዓለም ዋንጫው ተሳታፊ ቡድኖች ከታዩ ድጋፎች እንደተሳካላቸው የተለያዩ ዘገባዎች አውስተዋል፡፡ ዴይሊ ሜል ባቀረበው ዘገባ እንዳብራራው ለዓለም ዋንጫ ስኬት የቡድን አንድነት እና የላቀ ብቃት እንዲሁም የአሰልጣኞች የታክቲክ ፍልስፍና ከፍተኛ አስተዋፅኦ ቢኖራቸውም ፆታዊ ፍቅር የማይናቅ ሚና እንደነበረው የጀርመን ድል አረጋግጧል፡፡ የጀርመን ተጨዋቾች ሴቶቻቸውን ቁጥር አንድ ደጋፊዎቻን እያሉ ሲጠሯቸው ነበር፡፡ የተጨዋቾች ሚስቶች፤ ፍቅረኞች እና ቤተሰቦች የሻምፒዮናነት ሜዳልያውን በማጥለቅና ከሻምፒዮኖቹ ጋር ፎቶ በመነሳት እድለኞች ነበሩ። አንዳንዶቹ እንደውም ዋንጫዋን በመንካት እና በማቀፍ የማይገኝ ታሪክ ሰርተዋል፡፡ ከጀርመን የዓለም ዋንጫ ድል በኋላ በነበረው ፓርቲ ከፍተኛ ትኩረት አግኝተው ከነበሩ ዝነኛ ሴቶች ግንባር ቀደሟ በዋንጫው ጨዋታ ለጀርመን ድጋፍ የሰጠችው በርባዶሳዊቷ ሙዚቀኛ ሪሃና ነበረች፡፡

ሪሃና ከጀርመን ተጨዋቾች ጋር ባላት የቀረበ ግንኙት ከሻምፒዮናዎች ጋር አብራ መዝናናቷን ያወሳው ዴይሊ ሜል ጋዜጣ፤ ዓለም ዋንጫዋን በመንካት የፊፋ ስነምግባር እስከመተላለፍ መድረሷን በመጥቀስ ትችት አቅርቦባታል፡፡ ፊፋ ዓለም ዋንጫን ከመንግስታት መሪዎች ከአሸናፊ ብሄራዊ ቡድን አባላት በስተቀር ማንም እንዳይነካ የሚከለክል የስነምግባር ደንብ ነበረው፡፡ ሪሃና ግን ወደ ጀርመን ብሄራዊ ቡድን ሰርጋ በመግባት እንደፈለገች ፎቶዎች ተነስታ በሶሽያል ሚዲያ አሰራጭታለች፡፡ ሚሮስላቭ ክሎሰ፤ ሽዋንስታይገር እና ፖዶሎስኪ ዋና ምክንያቶች ነበሩ፡፡ ሜሲቲ ኦዚል ማልያውን አውልቆ ለሪሃና እንደሸለማትም ዴይሊ ሜል አትቷል፡፡ ጀርመን ዓለም ዋንጫውን ያሸነፈችበትን ግብ ያስቆጠረው ማርዮ ጎትዜ በሽልማት ስነስርዓቱ ላይ ፍቅረኛውን አን ካተሪን ብሮሜል ፍቅሩን እየገለፀ በተደጋጋሚ ሲያመሰግናት ታይቷል፡፡ ‹‹በዚህ ታሪካዊ ድል የቤተሰቤ እና የፍቅረኛዬ አና ድጋፍ ልዩ ነበር፡፡ ሁሉም በእኔ ውጤታማነት ሙሉ እምነት ነበራቸው›› በማለት ማርዮ ጎትዜ የሴቶቹን ሚና ገልፆታል። ጎትዜ የጎሏን ያገባው መታሰቢያነት ለዚህችው የ25 ዓመት እጮኛው አድርጓታል፡፡

አና ካተሪን ብሮሜል በጀርመን የተሳካላት ሞዴል ስትሆን በፒያኖ ተጫዋችነትም እየታወቀች ነው፡፡ ዓለም ዋንጫውን ያደመቁት ሌሎች ሴቶች ጀርመንን የደገፉ ሴቶች በድል አድራጊነት ቢንበሻበሹም በዓለም ዋንጫው በርካታ ሴቶች በየሚደግፏቸው ብሄራዊ ቡድኖች ድምቀት ፈጥረዋል፡፡ የጣሊያኑ አጥቂ ማርዮ ባላቶሊ ዓለም ዋንጫው ሳይጀመር በዋዜማው ሰሞን እጮኛውን በማግኘቱ ቀዳሚውን ትኩረት መሳብ ችሎ ነበር፡፡ 100ሺ ፓውንድ በሚያወጣ ቀለበት ፋኒ ኔጉሻ ከተባለች ፍቅረኛው ጋር የተተጫጨው በብራዚል የባህር ዳርቻ ላይ ነው፡፡ ፋኒ የራሷ ስም የተፃፈበትን የጣሊያን ማልያ በመልበስ ሁሉንም የምድብ ጨዋታዎች ከሌሎች የጣሊያን ተጨዋቾች ሚስቶች እና ፍቅረኛሞች ጋር በየስታድዬሙ በመገኘት ተከታትላለች። ከሮናልዶ ጋር የፍቅር ጓደኝነት ከጀመረች 4 ዓመታት ያስቆጠረችው የ28 ዓመቷ ሩስያዊት ሱፕር ሞዴል ኤሪና ሻይክ በተለያዩ ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች በተሰጣት ሽፋን በቁንጅናዋ፤ በገቢዋ ከፍተኛነት የሚወዳደራት አልነበረም፡፡ የስፔን ብሄራዊ ቡድን ተከላካይ የሆነው ጄራርድ ፒኬ ጋር በፍቅር ጓደኝነት ከተሳሰረች 11 ዓመት ያለፋት ሻኪራ ደግሞ ዓለም ዋንጫ በሙዚቃዋ የገነነችበት ሆኗል፡፡ በ2010 እኤአ ለዓለም ዋንጫ ዜማ የነበረውን ዋካ ዋካ የሰራችው ሻኪም ለእግር ኳሱ ዓለም በመቅረብ የሚፎካከራት የለም፡፡ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ የመዝጊያው ስነስርዓት ላይ ደግሞ የሙዚቃ ኮንሰርቱ ዋና ሙዚቀኛ ኮሎምቢያዊቷ ስትሆን፤ በ2006፣ በ2010 እና በ2014 እ.ኤ.አ ላይ በተከናወኑት የዓለም ዋንጫ የመዝጊያ ስነስርዓቶች ሙዚቃ በማቅረብ የመጀመርያ ሆናለች፡፡ ኮሎምቢያዊቷ በ2010 እ.ኤ.አ የሠራችው “ዋካ ዋካ” የተሰኘው የዓለም ዋንጫ መሪ ዜማ ከዓለም ዋንጫ ዘፈኖች ከፍተኛውን ሽያጭ ያገኘ ነው፡፡ ሻኪራ በመላው ዓለም የአልበሞቿን 70 ሚሊዮን ቅጂዎች በመሸጥ የተሳካላት የላቲን ሙዚቃ ንግስት ናት፡፡

የሊዮኔል ሜሲን የበኩር ልጅ ቲያጐን የወለደችው አንቶኔላ ሬኩዞ በዓለም ዋንጫው ከታዩ እናቶች ተወዳጅነት ያተረፈችው ናት፡፡ ሜሲ 27ኛ ዓመት የልደት በዓሉን ከኢራን ጋር በተደረገ ጨዋታ ላይ አንድ ጎል አስቆጥሮ ሲያከብር አንቶኔላ ከልጃቸው ጋር በስታድዬም ተገኝታ ደስታዋን ገልፃለች፡፡ እስከፍጫሜው ድረስም አንድም የአርጀንቲና ጨዋታ አላመለጣትም፡፡ የዋይኔ ሩኒ የትዳር አጋር የሆነችው ኮሊን ሩኒ ሌላዋ አነጋጋሪ ሴት ናት፡፡ ኮሊን በራሷ ወጭ በዓለም ዋንጫው ሰሞን ካይ እና ክሌይ የተባሉ ሁለት ልጆቿን ይዛ ብራዚል በመገኘት ድጋፍ የሰጠች ነበረች፡፡ የ28 ዓመቷ ኮሊን ከእንግሊዝ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች ሚስቶች ወጭዋን ሸፍና ብራዚል በመጓዝ እና በአሳፋሪ ውጤት በጊዜ በመመለስ የምትጠቀስ ሆናለች፡፡ አብረዋት የ4 ዓመት ልጃቸው ካይ እና ገና 1 ዓመት የደፈነው ሌላ ወንድሙን ይዛ እንግሊዝ በመጨረሻው የዓለም ዋንጫው የምድብ ጨዋታ ከውድድር ውጭ ስትሆን ታድመዋል፡፡ ታዳጊ ሞዴል የሆነችው የኔይማር ጓደኛ ብሩና ማርኪውዚን፤ የዌስሊ ሽናይደር ሚስትና በሙያዋ ተዋናይት የሆነችው ዮላንቴ ሽናይደር ካቡ፤ እንዲሁም ታዋቂ ጋዜጠኛ የሆነችው የኤከር ካስያስ ሚስት ሱዛን ካርቦኔ በ20ኛው ዓለም ዋንጫ ስማቸው ከተነሱ ሴቶች መካከል ይጠቀሳሉ፡፡ የፈረንሳይ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች ሚስቶች እና ፍቅረኞች ቡድናቸው ስታድዬም ገብተው በመደገፍ ተደንቀዋል፡፡

የባካሪ ሳኛ እና የፓትሪስ ኤቭራ ሴቶች በአስጨፋሪነታቸው አልተቻሉም ነበር፡፡በኡራጋይና ጣሊያን ብሄራዊ ቡድኖች የሚገኙ ተጨዋቾች ግንኙነት ያላቸው ሴቶች ያረፉባቸው በየአቅራቢያቸው የሚገኙ ባለ አምስት ኮከብ ሆቴሎች ናቸው። የሆላንዱ አሰልጣኝ ሊውስ ቫንጋል በአንዳንድ ግጥሚያዎች ዋዜማ ለተጨዋቾቻቸው ከቤተሰባቸው ጋር የሚገናኙበትን እረፍት በመፍቀድ ልዩ ውሳኔ አድርገዋል፡፡ የፍቅር ግንኙነት ይጠቅማል፤ ይጎዳል? ከዓለም ዋንጫ ጋር በተያያዘ ስለ ሴቶቹ መዘገብ የተጀመረው ውድድሩ ከመጀመሩ ሁለት እና ሶስት ወራት ቀድሞ ነበር፡፡ ከ32 ብሄራዊ ቡድኖች መካከል አብዛኛዎቹ የተጨዋቾች ሚስቶች፤ እጮኛዎችና ጓደኞች በዓለም ዋንጫው ስለሚኖራቸው ሚና የተለያዩ መመርያዎች አውጥተዋል፡፡ አንዳንድ አሰልጣኞች ከቡድናቸው አቅራቢያ ሴቶች፤ ልጆችና ሌሎች የቤተሰብ አባላት መኖራቸው ተጨዋቾች የልምምድ ሰዓቶችን እንዳያከብሩ፤ በተለያዩ ሁኔታዎች ሃሳብ እንዲገባቸው እና ትኩረታቸውን እንዲያጡ ያደርጋል የሚሉ ምክንያቶችን በመደርደር ጥብቅ ደንቦችን ለማውጣት ተገደዋል፡፡ ተጨዋቾች ከሚስቶቻቸው፤ ከፍቅረኞች እና ከሴት ጓደኞቻቸው ጋር በየጨዋታው ዋዜማ የወሲብ ግንኙነት የሚገድቡ ደንቦች አወዛግበዋል፡፡ አንዳንድ አሰልጣኞች ተጨዋቾች ማናቸውንም የፍቅር ግንኙነት ማድረጋቸው ውጤት ያበላሻል የሚል አቋም ነበራቸው፡፡ የራሽያ፣ ቦስኒያ፣ ቺሊና ሜክሲኮ አሰልጣኞች ምሳሌ ናቸው፡፡

ሌሎች ደግሞ ተጨዋቾች በነፃነት የፈለጉትን እንዲያደርጉ ፈቅደዋል፡፡ ጀርመን፣ ስፔን፣ አሜሪካ፣ አውስትራሊያ፣ ጣሊያን፣ ሆላንድ፣ ስዊዘርላንድና ኡራጋይ ናቸው፡፡ የቦስኒያ እና ሜክሲኮ አሰልጣኞች ከጨዋታ በፊት የሚፈፀም የወሲብ ግንኙነት የአካል ብቃት ያጓድላል በሚል ሲከለክሉ የትኛውም ፕሮፌሽናል ተጨዋች ያለ ወሲብ አንድ ወር ቢያሳልፍ ምንም ችግር አይፈጠርበትም በሚል መከራከርያ ነው፡፡ የብራዚል አሰልጣኝ የነበሩት ሊውስ ፍሊፕ ስኮላሬ በበኩላቸው ክልከላውን ቢደግፉም መመርያቸውን ለዘብ በማድረግ ተጨዋቾች ወሲብ ከፈፀሙ ከልክ ባለፈ ሁኔታ እንዳይሆን በማሳሰብ ነበር፡፡ የስፔን አሰልጣኝ ቪሴንቴ ዴልቦስኬ ማናቸውም ግንኙነት ግጥሚያ በሌለባቸው የእረፍት ቀናት ብቻ እንዲሆን ሲፈቅዱ የአውስትራሊያ፤ የፈረንሳይ እና የአሜሪካ አሰልጣኞች በበኩላቸው በተለያየ ደረጃ ቁጥብ ግንኙነት እንዲኖር አሳስበዋል፡፡

የናይጄርያው አሰልጣኝ ስቴፈን ኬሺ በበኩላቸው ትዳር የመሰረቱ ተጨዋቾች ከሚስቶቻቸው እና ቤተሰባቸው ጋር ግንኙነት እንዲኖራቸው ቢፈቅዱም ከማንኛውም የሴት ጓደኛ ወይም ፍቅረኛ ለሚደረግ ግንኙነት ግን ፈቃድ አልሰጥም ብለዋል፡፡ የቺሊ አሰልጣኝ ደግሞ ተጨዋቾቻቸው ቡድናቸውን ለጥሎ ማለፍ ምእራፍ ካበቁ በኋላ ለማናቸውም ግንኙነት ነፃነት ሰጥተዋል፡፡ የሆላንዱ አሰልጣኝ ሊውስ ቫንጋል ደግሞ ቡድናቸው ያለፈው ዓለም ዋንጫ ሻምፒዮኗን ስፔን 5ለ1 ካሸነፈበት ጨዋታ በፊት ተጨዋቾቹ ባረፉበት ሆቴል ሚስቶቻቸው፤ ፍቅረኞቻቸው እና ጓደኞቻቸው የጉብኝት ሰዓት እንዲፈቀድላቸው በመወሰናቸው ተሳክቶላቸዋል፡፡ ብዙ የእግር ኳስ አሰልጣኞች ከጨዋታ በፊት ተጨዋቾች ወሲብ ማድረግ የለባቸውም የሚል አመለካከትን ይቀበሉታል፡፡ ከጨዋታ በፊት ወሲብ መፈፀም የተጨዋችን ጉልበት ያባክናል፣ ኃይል ያሳጣል እንዲሁም የስነልቦና ዝግጅትን ያቃውሳል በሚልም ያስረዳሉ፡፡ አንዳንዶች ግን የሴቶቹ በዓለም ዋንጫ አካባቢ መገኘት ተጨዋቾች በሞራል እንዲነቃቁ ያደርጋል በሚል እምነት ሰርተዋል፡፡ ስታድዬም ገብተው ድጋፍ የሚሰጡበትን እድል እንደሚፈጥር እና ዝነኛ ሴቶች ከሆኑ ደግሞ የብሄራዊ ቡድኖችን ማልያ በማስተዋወቅ፤ የሚዲያ ሽፋን በማግኘት ብዙ መልካም ገፅታዎችን በመፍጠር ያላቸው አስተዋፅኦ መናቅ እንደሌለብትም የሚያስረዱ አሉ፡፡

“የአዲስ አበባ ጉዶች” እና “ኢትዮጵያን ማን ይታደጋት” በሚሉት መፅሀፎቹ የሚታወቀው ጋዜጠኛና ደራሲ አቤል አለማየሁ፤ “የእኛ ሰው ገመና” የተሰኘውን ሦስተኛ መፅሀፉን በሳምንቱ መገባደጃ ላይ ለንባብ አብቅቷል፡፡ የተደበቁ እውነቶችን ምፀታዊ ወጎች፣ ማህበራዊና ወሲባዊ ጉዳዮችን የሚዳስሰው መፅሀፉ፤ በተለይም በድንግልና ንግድ፣ በሴት ሰዶማውያውን፣ በልቅ ወሲብና በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ ኢትዮጵዊያንን አስገራሚ ገመናዎች በስፋት ያስቃኛል፡፡ ለአፍሪካ ዋንጫ ወደ ደቡብ አፍሪካ ተጉዞ የነበረው አቤል፤ በቆይታው የታዘባቸውን የሀበሻ ልጆች ገመና ዋና የመፅሃፉ ትኩረት ማድረጉን ለአዲስ አድማስ ገልጿል፡፡
በ208 ገፆች የተቀነበበውና በርካታ ማህበራዊ ርዕሰ ጉዳዮችን የሚዳስሰው መፅሀፉ፤ በ49 ብር ከ65 ሳንቲም ለገበያ ቀርቧል፡፡

በኢትዮ ፊልም ኃ/የተ/የግ/ማህበር አስተባባሪነትና ባለቤትነት የሚዘጋጀው “ጉማ ፊልም ሽልማት” የዘንድሮ ፊልሞችን በሽልማት ውድድሩ ለማካተት ምዝገባ መጀመሩን አስታወቀ፡፡ ለሁለተኛው ዙር የሚወዳደሩ የአምና ፊልሞችን ከመጋቢት 29 እስከ ሚያዚያ 3 በጣይቱ ሆቴል መዝግቦ ማጠናቀቁን የገለፀው ኢትዮ ፊልም፤ በሁለተኛው ዙር ውድድር የዘንድሮዎቹን ለማካተት ከሐምሌ 9 እስከ 16 በጣይቱ ሆቴል ምዝገባ እንደሚያካሂድና ለመመዝገብ ፍላጎት ያላቸው ፊልሞች እንዲመዘገቡ ጥሪ አቅርቧል፡፡ ምዝገባው ከቅዳሜ ከሰዓትና ከእሁድ በስተቀር በስራ ቀናት የሚካሄድ መሆኑንም ድርጅቱ በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡

በኢትዮ ፊልም ኃ/የተ/የግ/ማህበር አስተባባሪነትና ባለቤትነት የሚዘጋጀው “ጉማ ፊልም ሽልማት” የዘንድሮ ፊልሞችን በሽልማት ውድድሩ ለማካተት ምዝገባ መጀመሩን አስታወቀ፡፡ ለሁለተኛው ዙር የሚወዳደሩ የአምና ፊልሞችን ከመጋቢት 29 እስከ ሚያዚያ 3 በጣይቱ ሆቴል መዝግቦ ማጠናቀቁን የገለፀው ኢትዮ ፊልም፤ በሁለተኛው ዙር ውድድር የዘንድሮዎቹን ለማካተት ከሐምሌ 9 እስከ 16 በጣይቱ ሆቴል ምዝገባ እንደሚያካሂድና ለመመዝገብ ፍላጎት ያላቸው ፊልሞች እንዲመዘገቡ ጥሪ አቅርቧል፡፡ ምዝገባው ከቅዳሜ ከሰዓትና ከእሁድ በስተቀር በስራ ቀናት የሚካሄድ መሆኑንም ድርጅቱ በላከው መግለጫ አስታውቋል፡፡

ሳሙኤል ጆንሰን “The chief glory of every people a rises from its authors” ይላል። (የአንድ ህዝብ ደማቅ ስምና ታሪክ ከወለዳቸው ፀሐፍትና ደራስያን ጭምር ይፈልቃል እንደማለት ነው) እውነት ነው፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የአንድ ደራሲ የሕይወት ታሪክም የአንድ አገርና ሕዝብ ታሪክም ሲሆን አስተውለናል፡፡ የቅዱስ ያሬድ፣ የአባ ጊዮርጊስ ዘጋሥጫ እና የመሳሰሉት ለውስጣችን ታላቅ ኃይል የሚሰጠን የፈጠራ ስራቸው ብቻ ሳይሆን የዚህች ሀገር መሰረት የሆነው የአኗኗር ዘይቤና ፈሊጣቸው ጭምር ነው፡፡
ፑሽኪን ለሩሲያ፣ ብረሽት ለጀርመን፣ ባልዛክ ለፈረንሳይ፣ ሼክስፒር ለእንግሊዝ፣ ሔሚንግዌይ ለአሜሪካ ሕዝብ የታሪኮቻቸው ምንጮች ናቸው፡፡
እነኚህ ደራሲያንና ሌሎችም ሁሉ በፈጠራቸው የሂደት ወቅት አድሏዊ ሆነው አያውቁም፡፡ ሂሳዊ የማይሆኑትና አልፎ አልፎ ሚዛናቸው የሚዛባው መፍረድ ሲጀምሩ ወይም ፍርድ ሲሰጡ ነው፡፡ ታድያ እነዚህን ሁለት የሥነ ጽሑፍ ምሰሶዎች ጠብቀው የተፃፉ ሥራዎችን ሲያስነብበን የኖረን አንድ የጥበብ ሰው አጥተናል፡፡
ሀገራችንና የጥበብ ወዳጆች የሆንን ሁሉ አንድን ዘርፈ ብዙ የጥበብ ሰው አጥተናል፡፡
ሀገራችን ባለቅኔ፣ ተርጓሚና ትሁት መምህር የሆነውን ልጇን አጥታለች፡፡
ከሁሉም ከሁሉም ታላቁን የወግ አባት አጥተናል፡፡ ወግ ለመቀመር የተፈጥሮ ችሎታውን ከዘመናዊ ትምህርት ጋር አጣምሮ የተካነን ሸጋ ደራሲ አጥተናል፡፡ ባሻው ዘውግ አሳምሮ መፃፍ የሚችል ደመና - ገላጭ ትንሽ ፈጣሪ አጥተናል፡፡
ታላቁ የወግ አባት መስፍን ሀብተማርያም ተለይቶናል፡፡
መስፍን ሀ/ማርያም የወግን ምንነት ያስተማረን ብቻ ሳይሆን በተለይ የርዕዮትንና የአብዮትን ዜማ ብቻ በውድም ሆነ በግድ እንድንጋተው በተገደድንበት በዚያን ዘመን ሆነ ዛሬ በዕውቅ የወግ ሥራዎቹ የህይወትን ጐምዛዛነትና ጫና ሊያቀልልን የጣረ የጥበብ ሰው ነው፡፡
መስፍን ሀ/ማርያም ሕይወትን፣ ተፈጥሮን፣ ኑሮንና እነዚህን የሚያጫፍሩትን ዐብይት ክስተቶች ከግለሰብ እስከ ህብረተሰብ ባለው ማንነት ዙሪያ በገሀድ የሚታዩ ድርጊቶችን በመዘርዘር፣ አካባቢያችንና ዘመናችንን በይበልጥም በሰዋዊ ማንነታችን ስንቀበለው በምንችለውና በሚያረካ ኪነታዊ ጉዞ እንድንቃኝ ያደረገ የጥበብ ጀግናችን ነው፡፡
መስፍን ሀ/ማርያም በሥነ - ወግ፤ ቋንቋችንን የፈተሸ፣ ተራ ቃላት የምንላቸውንና ልንዘነጋቸው የተቃረቡ ዘየዎችን መልሰው ነፍስ እንዲዘሩ ያደረገ የቋንቋ ጠቢብ ነው፡፡
የመስፍን ሀ/ማርያም ወጎች ሁላችንም የምናቃቸው በቋንቋቸው ማራኪና በአቀራረባቸው ሚዛናዊነት፣ በምርጥ ምሳሌያቸው፣ በምጣኔያቸውና ማዝናናት በመቻላቸው ነው፡፡ በተለይ ሥነ - ወግ ዋነኛው ባህሪይው ማዝናናት መሆኑን የምንረዳው ከመስፍን ሀ/ማርያም ጽሑፎች ነው ብንል አልተሳሳትንም፡፡
ማዝናናት ሲባል ፈገግ ማስደረግን፣ ማሣቅን የሚያጠቃልል ቢሆንም ከዚህ በዘለለ የመስፍን ሃ/ማርያም ወጐች በተራነት የማይጠበቅ ት.ግ.ር.ም.ት፣ የማይረሳ አድናቆትና “እንዲህ ነው ለካ” የሚያሰኝ የመንፈስ ደስታ እያላበሱንና እነዚህንም ዘና ባልንበት እያዋዙ፣ ዘና ባልንበት ቁምነገሮችን አሾልከው እየወረወሩ፣ ነፍስና ስጋችንን እያጫወቱ፣ ለብዙ ዘመን ያሸጋገሩን ናቸው፡፡
ተውኔት የቤተ-መቅደስና የቤተ መንግስት ዜና መዋዕል ዘጋቢ ብቻ ከመሆን ታላቋ ፊቷን ወደ ዝቅተኛው የሕብረተሰብ ሕይወት እንድታዞር ፋና ወጊውን ሥራ የፈፀሙ እንዳሉ ሁሉ፣ መስፍን ሀ/ማርያም በተለይ በተለይ በሥነ - ወግ ስራዎቹ የድሐውን ሕዝብ ጓዳ - ጐድጓዳ በርብሮ፣ የድሀ ወገናችንን ወግና - ታሪኩን ደስታና - ሀዘኑን ሕይወትና - ሞቱን በቅርበት እንድንረዳ ያጋዘን የዘመናችን የወግ አባት ነው።
ከሁሉም ከሁሉም የወግ አባቱ መስፍን ሃ/ማርያም፣ ጥበብን - እምነቱ፣ ጥበብን ትሁት ተሰጥኦው…ጥበብን ለይስሙላ ተሳልሟት ያለፈ፣ ገባ - ወጣ እያለ የጐበኛት ሳይሆን በጥበብ ፍቅር ወድቆ (ላይፈታት ተክሊል ደፍቶ) ላይፈታት ቁርባን፣ ቃል ኪዳን ቋጥሮ - ሳይፈታት፣ እድሜ ህይወቱን የሰዋላት ሰው ነው፡፡
መስፍን ሀ/ማርያም በ1937 ዓ.ም ከአባቱ ከአቶ ሀ/ማርያም ሞገስና ከእናቱ ከወ/ሮ ደስታ አየለ ተወልዶ ባለፈው እሁድ በ69 ዓመቱ ከዚህ ዓለም በሞት ተለይቷል፡፡ ጋሽ መስፍን ከ1ኛ እስከ 7ኛ ክፍል ድረስ ሞጆ አንደኛና መለስተኛ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት፣ ከ8ኛ ክፍል ጀምሮ የ2ኛ ደረጃ ትምህርቱን እስካጠናቀቀበት ቀን ድረስ በአንቦ እንዲሁም ከ1958 ዓ.ም እስከ 1962 ዓ.ም በቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ዩኒቨርሲቲ በኢትዮጵያ ቋንቋዎችና ሥነ - ጽሑፍ የመጀመሪያ ዲግሪውን የማዕረግ ተሸላሚ ሆኖ አጠናቋል፡፡
ጋሽ መስፍን በ1964 ዓ.ም ባህር ተሻግሮ ካናዳ ቫንኩቦር በሚገኘው በብሪቲሽ ኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ ልቦለድን፣ ኢ-ልቦለድን፣ ተውኔትንና ሥነ - ግጥምን የጥናቱ ትኩረት በማድረግ “በፈጠራ ሥነ ጽሑፍ” (creative writing) የማስተርስ ዲግሪውን በ1966 ዓ.ም አግኝቷል፡፡
ጋሽ መስፍን ሀ/ማርያም በሥራው ዓለም ለ3 ዓመታት በኤርትራ በተለይ በአስመራና በምፅዋ የአማርኛ ቋንቋን አስተምሯል፡፡
ከ1963-1976 በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የቋንቋዎች ጥናት ተቋም የተለያዩ የሥነ - ጽሑፍ ኮርሶችን ያስተማረ ሲሆን ከዚህ ጐን ለጐን በኢትዮጵያ ሬዲዮና በኩራዝ አሳታሚ ድርጅት ሲሰራ ቆይቷል፡፡
ጋሽ መስፍን በድርሰት ዓለም “የቡና ቤት ሥዕሎች”፣ “አውደ ዓመት”፣ “የሌሊት ድምጾች”፣ እና ሌሎች የወግ መጽሐፍትን አበርክቶልናል፡፡ “አዜብና ሌሎች አጫጭር ልቦለዶችን”፣ እንዲሁም የተረት መጻሕፍትን አሳትሟል፡፡ “በቆንጆ ልጅ ፈተና” ሥነ - ግጥሙም እናውቀዋለን፡፡
ጋሽ መስፍን ወደ 550 የሚጠጉ የተለያዩ መጣጥፎችን በጋዜጦችና በመጽሔቶች ላይ በማውጣት ከዘመን ዘመን እያጫወተና እያስተማረ አሸጋግሮናል፡፡ ጋሽ መስፍን ከድርሰቶቹ በተጨማሪ ሃያሲም ነበር፡፡ ጋሽ መስፍን ሳይቤሪያ በዘመተው የኢትዮጵያ የሰላም አስከባሪ ጦር ጋር በመዝመት በአስተርጓሚነት አገልግሏል፡፡
የአብራኩ ክፋይ የሆኑ የሁለት ወንድ ልጆችና የአራት ሴት ልጆች አባትም ነው፡፡
ጋሽ መስፍን በመጨረሻዎቹ የእስትንፋስ ሰዓታቱ ልጁን ሀ/ማርያም መስፍንንና ቃልኪዳን መስፍንን አሳድጉልኝ፣ ለወግ አብቁልኝ እያለ ሲወተውትና ሲማፀን ነው ሕይወቱ ያለፈችው፡፡
ጋሽ መስፍን The Merchant of Fear የምትሰኝ አጭር ልቦለዱንና ሌሎች ያልታተሙ ሥራዎቹ ለንባብ ይበቁለት ዘንድ ሲማፀን ቆይቶ ለአንዴና ለሁሌም ተለይቶናል፡፡
ይህ ሁላችንም የምንወደው፣ ይህ ትሁት፣ ይህ ቅን፣ ይህ የኑሮ ጫና ሳይበግረው ዘመኑን ሙሉ ያገለገለንን ታላቅ የጥበብ ሰው፣ የመጨረሻ ሰዓት ኑዛዜውን ያገለገለው የሀገራችን ህዝብና የጥበብ ወዳጆች ሁሉ እውን እንደሚያደርጉት የፀና እምነቴ ነው፡፡
በመጨረሻም በዚህ በታላቁ የጥበብ ሰውና የወግ አባት በሆነው በደራሲ መስፍን ሃ/ማርያም የቀብር ስነስርዓት ላይ ተገኝታችሁ ቤተሰቦቹን ያጽናናችሁትን ሁሉ በልጆቹ፣ በዘመዶቹ፣ በኢ.ደ.ማ አባላት፣ በራሴና በጥበብ ወዳጆች ሁሉ ስም ላመሰግን እወዳለሁ፡፡
ታላቁ አምላክ ይህን ፍዳውን ሁሉ በምድር ዓለም የጨረሰን የጥበብ አባት መስፍን ሃ/ማርያምን ነፍሱን በገነት ያሳርፋት ዘንድ እንለምናለን፡፡
አመሰግናለሁ

          በህገወጥ የምግብ፣ የመድሃኒትና የጤና አገልግሎት ላይ ያተኮረ የህዝብ ንቅናቄ መድረክ በደሴ፣ በአላማጣና በሽሬ ከተሞች ባለፈው ግንቦት ወር ተካሂዷል፡፡
የህዝብ ንቅናቄ መድረኩ በተለይ በህገወጥ የምግብና መድሃኒት ንግድ ምንነትና የሚያስከትለው ችግር ላይ ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎችና ባለድርሻ አካላት ጋር በሰፊው ምክክር ለማድረግና ህብረተሰቡን የቁጥጥሩ ባለቤት ለማድረግ ታልሞ የተካሄደ መድረክ ነው፡፡
የኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድሃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን፤ ከህገወጥ የምግብና የመድሃኒት ዝውውር ጋር በተያያዘ በጣም ተጋላጭ በሆኑና በተመረጡ ቦታዎች ላይ የህዝብ ንቅናቄ መድረክ ያካሂዳል፣ በቅርቡም በሶስት ከተሞች ላይ የተከናወኑት መድረኮች የዚህ እንቅስቃሴ አካል ናቸው፡፡
በውይይት መድረኮቹ የጤናና ጤና ነክ አገልግሎትና ግብአት ከየት ወዴት፣ ህገወጥ የምግብና የመድሃኒት ንግድና የጤና አገልግሎት ቁጥጥር ነባራዊ ሁኔታ፣ የምግብና የመድሃኒት ህገወጥ ዝውውር አጠቃቀምና ጤና አገልግሎት ክልላዊ ገጽታ፣ ህገወጥ የምግብ፣ የመድሃኒትና ጤና አገልግሎት እንቅስቃሴን በጋራ ለማስወገድ ቀጣይ አቅጣጫ (የጋራ ዕቅድ) የሚሉ ሰነዶች የቀረቡ ሲሆን ለተሳታፊዎች ጥያቄና አስተያየትም በቂ ጊዜ ተሰጥቶ በርካታ ሃሳቦች ተንሸራሽረዋል፡፡
በጋራ ምክክር መድረኩ ትኩረት አግኝተው ከተነሱት ርዕሰ ጉዳዮች አንዱ “ህገወጥ የምግብ፣ መድሃኒት ንግድና የጤና አገልግሎት ቁጥጥር ስራዎች ነባራዊ ሁኔታ” በሚል በባለስልጣን መ/ቤቱ የኢንስፔክሽንና ቅኝት ዳይሬክቶሬት የቀረበው ገለፃ ሲሆን አላማውም በሀገራችን በምግብ፣ በመድኃኒትና በጤና አገልግሎት ዙሪያ ያለውን ህገወጥ እንቅስቃሴ በማስቃኘት በቀጣይ ህገወጥ እንቅስቃሴን በመከላከሉ ስራ ሁሉም የበኩሉን አስተዋጽኦ እንዲያበረክትና ንቁ ተሳትፎ እንዲኖረው ለማነቃቃት ነው፡፡
አግባባዊ የምግብ ንግድ ስራ
ማንኛውም ምግብ ባለስልጣኑ ወይም የክልል ጤና ጤና ተቆጣጣሪ አካል ሳይፈቅድ መመረት፣ ወደ ሀገር ውስጥ መግባት፣ መላክ፣ መዘጋጀት፣ መከማቸት፣ መከፋፈል፣ መጓጓዝ ወይም ለሽያጭ ወይም ለህብረተሰቡ ሊቀርብ አይችልም፡፡
ማንኛውም ምግብ ጥራቱና ደህንነቱ ተጠብቆ መመረት፣ መታሸግ፣ ገላጭ ጽሑፍ መለጠፍ፣ መከማቸት፣ መጓጓዝና መሸጥ አለበት፡፡
በማንኛውም ምግብ ላይ መጠኑን ወይም ክብደቱን ለመጨመር፣ መልኩን ለማሳመር ወይም ለሌላ ተመሳሳይ ዓላማ ሲባል የሰውን ጤና ሊጐዳ ወይም የምግቡን ጥራትና ደህንነት ሊያጓድል የሚችል ባእድ ነገር መጨመር ወይም መቀላቀል የተከለከለ ነው፡፡
ማንኛውም ለህብረተሰቡ ሽያጭ አገልግሎት የሚውል የታሸገ ምግብ በአማርኛ ወይም እንግሊዝኛ ቋንቋ የተፃፈ ገላጭ ጽሑፍ ሊኖረው ይገባል፡፡
የምግቡ ስም
በምግቡ ውስጥ ያለው ይዘት
የምግቡ አምራች ድርጅት ስምና ሙሉ አድራሻ
የምግቡ መለያ ቁጥር (Batch no)
ምግቡ የተመረተበትና የመጠቀሚያ ጊዜው የሚያበቃበት ቀን
አግባባዊ የመድሃኒት ንግድ ስራ
ማንኛውም መድኃኒት ደህንነቱ፣ ፈዋሽነቱና ጥራቱ ተገምግሞ በአስፈጻሚ አካሉ ሳይመዘገብ በጥቅም ላይ ሊውል አይችልም፣
ማንኛውም መድሃኒት ወደ ሀገር ውስጥ ለማስገባት፣ ለማምረትና ለህብረተሰቡ ሽያጭ ለማዋል መጀመሪያ በባለስልጣኑ በብሔራዊ የመድሃኒት መዘርዝር ውስጥ በመካተት ተመዝግቦ የገበያ ፈቃድ ማግኘት አለበት፡፡
የማንኛውም መድሃኒት ገላጭ ጽሑፍ፡-
የመድሃኒቱ ሳይንሳዊ ስም
በመድሃኒቱ ውስጥ ያለው ይዘት
የመድሃኒቱ አምራች ድርጅት ስምና ሙሉ አድራሻ
መድሃኒቱ የተመረተበትና አገልግሎት የሚያበቃበት ጊዜ
በቀን መወሰድ ያለበት መጠንና የአወሳሰድ ሁኔታ…ሊያካትት ይገባል፡፡
አግባባዊ የጤና አገልግሎት አሰጣጥ
ማንኛውም የጤና ተቋም በሀገሪቱ የተቀመጠውን የጤና አገልግሎት ደረጃ ያሟላ መሆን አለበት
ከሚመለከተው የጤና ተቆጣጣሪ አካል ህጋዊ እውቅና የተሰጠው መሆን ይኖርበታል
ለሚሰጠው አገልግሎት የሚያስፈልጉ በቂ የህክምና መሳሪያዎች እንዲሁም ብቃታቸውና ሙያዊ ስነ ምግባራቸው የተረጋገጠ የጤና ባለሙያዎች ሊኖሩት ይገባል፡፡
ባለስልጣን መ/ቤቱ ከላይ ከተገለፀው አግባባዊ አካሄድ በተቃራኒ የሚካሄዱ ህገወጥ የምግብ፣ የመድሃኒትና የጤና አገልግሎቶችን ይቆጣጠራል፣ በአዋጅ (661/2002) በተሰጠው ስልጣንና ተግባር መሰረት፣ አስተዳደራዊና ህጋዊ እርምጃም ይወስዳል፡፡ ለአብነት ያህል ባለፉት ዘጠኝ ወራት ከደንብና አግባብ ውጪ ሲሰሩ በነበሩ ላይ የተጣሉ ቅጣቶችን ማየት ይቻላል፡፡
ወደ ሀገር ውስጥ እንዳይገቡ የተከለከሉ ምርቶች (ባለፉት 9 ወራት)
የምርት ዓይነት         ብዛት በቶን
ምግብ             45 ቶን
መድሃኒት            27 ቶን
ኮስሞቲክስ         14 ቶን
በቁጥጥር ወቅት የተገኙና ተገቢውን መስፈርት ሳያሟሉ ቀርተው የተወገዱ ምርቶች
የምርት ዓይነት         የድርጅቶች ብዛት
ምግብ             127 ድርጅቶች
መድሀኒት             130 ድርጅቶች
አስተዳደራዊ እርምጃ የተወሰደባቸው ድርጅቶች
705 የምግብ አስመጭዎችና ጅምላ አከፋፋይ ድርጅቶች ላይ ቁጥጥር ተካሂዶ 90 ድርጅቶች የብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀታቸውን እንዲመልሱ ተደርጓል፡፡ 8 ድርጅቶች ላይ የእገዳ አስተዳደራዊ እርምጃ ተወስዷል፡፡
በ321 መድሃኒት አስመጪና አከፋፋይ ድርጅቶች ላይ ቁጥጥር ተካሂዶ በ24 ድርጅቶች ላይ ከማስጠንቀቂያ ጀምሮ እስከ የብቃት ማረጋገጫ የምስክር ወረቀት ስረዛ ድረስ አስተዳደራዊ እርምጃ ተወስዷል፡፡
በህዝብ ንቅናቄ መድረኮቹ ላይ የዞንና የወረዳ ከፍተኛ አመራሮች፣ የክልል ጤና ቢሮ ሃላፊዎች፣ የክልል ተቆጣጣሪ አካላት፣ የፍትህ አካላት (የፍርድ ቤትና ፖሊስ ተወካዮች) የወጣትና ሴት አደረጃጀቶች፣ ከተለያዩ ሴክተር መ/ቤቶች የተውጣጡ ባለሙያዎች (ከገቢዎችና ጉምሩክ፣ ከንግድ ቢሮ፣ ከንግድ አሰራርና ሸማቾች ጥበቃ ባስልጣን….) ተሳታፊዎች ነበሩ፡፡ መሰል የምክክር መድረኮች ችግሮችን በጋራ ነቅሶ ጠቃሚ የመፍትሔ ሃሳቦችን ለመስጠት የሚኖራቸው ፋይዳ ከፍተኛ ነው፡፡ በተለይም በአሁኑ ጊዜ የመላው ማህበረሰብ ችግር የሆነውንና ውስብስብ እየሆነ የመጣውን ህገወጥ የምግብና መድሃኒት ዝውውር ለመግታት፣ የህዝብ ንቅናቄ መድረኮችን ማዘጋጀት የግድ ይላል፡፡ የጤና ጠንቅ የሆነውንና በሁላችንም ህይወት መንገድ ላይ የቆመውን ህገወጥ የምግብና የመድሃኒት ንግድና ዝውውር መግታት የሚቻለው ህብረተሰቡ የቁጥጥሩ ባለቤት መሆን ሲችል ብቻ ነው፡፡ በዚህ ረገድ ባለስልጣን መ/ቤቱ እያደረገ ያለው እንቅስቃሴ የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላትን ብሎም የመላው ማህበረሰብን የተጠናከረ ድጋፍ ይሻል፡፡
ህብረተሰቡ ጥራቱና ደህንነቱ የተጠበቀ ምግብና ጥራቱ፣ ደህንነቱና ፈዋሽነቱ የተረጋገጠ መድሃኒት በመጠቀም ጤናውን ሊጠብቅ ይገባል፡፡ እንዲሁም በምግብ፣ በመድሃኒትና በጤና አገልግሎቶች ላይ ማናቸውም ዓይነት ህገወጥ እንቅስቃሴ ሲገጥመው ለሚመለከተው ተቆጣጣሪ አካልና ለፖሊስ በመጠቆም መተባበር አለበት፡፡
ህገወጥ የምግብና መድሃኒት ንግድና የጤና አገልግሎትን በጋራ እንቆጣጠር!!!
(የኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድሃኒትና የጤና ክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለስልጣን የህዝብ ግንኙነትና ኮሙኒኬሽን ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ)