Administrator

Administrator

Saturday, 18 March 2023 20:22

ከሶሻል ሚዲያ በጨረፍታ

 “መሃይምነትና ድንቁርና ይለያያሉ”


     “...በነገራችን ላይ መሃይምነትና ድንቁርና ሁለቱ የተለያዩ ነገሮች ናቸው። መሃይም የሚባለው የትምህርት እድል ያላገኘ ነው። ድንቁርና ግን የትምህርት እድልም አግኝቶ በመሃይምነት ግርሻ የተጠቃው ነው። ፈረንጆች ምን ይላሉ --- arrogance (እብሪተኝነት) Ignorance (አለማወቅን) ያመጣል።  arrogance እና  Ignorance ይመጋገባሉ። መሃይምነት ሲያገረሽብህ እብሪተኛ ትሆናለህ፤ እብሪተኛ ስትሆን ደግሞ የበለጠ መሃይምነት ያገረሽብሃል። እናም ብዙዎቻችን በዲግሪያችን ጀርባ በድንቁርና ነው የምንኖረው። ሰውም እንዳይመክረን ዲግሪ አላቸው ይባላል። በእድርም ስትሄድ ዶክተር ይናገር ነው የሚባለው። ግን ሰውየው መሃይምነት ውስጥ ነው ያለው።.... እና ምንድነው እየሆነ ያለው ብላችሁ ያያችሁት እንደሆነ... መደማመጥ የሌለው፣ መነጋገር የሌለበት፣ የማንተማመነው፣ ለችግሮቻችን መፍትሔ የማናገኘው የምሁር ቁጥር እንጂ የአዋቂ ቁጥር ስለሌለ ነው። ለምን ያላችሁ እንደሆነ፤ አብዛኞቻችን በመሃይምነት ግርሻ ውስጥ ስላለን ነው። የዲግሪ ፎቶ በየቤቱ ስትሄዱ ግድግዳ ላይ ታያላችሁ። በትክክል ያ የሚያሳየው ሰውዬው በመሃይምነት መኖሩን ነው። ምክንያቱም ማረጋገጫው ያ ብቻ ነው። ሌላ ምን ያሳያል? ምን እናሳያለን ሌላ?....”
 (ዶ/ር አለማየሁ አረዳ፣ በአማራ
ቴሌቪዥን ከተናገሩት)
____________________________________

                 “እንደ ብልህ አብረን መኖር ካልቻልን፣ እንደ ሞኝ አብረን እንጠፋለን”
                      ዘላለም ጥላሁን


       ያለፈውን ዘመን ሳስታምመው ትዝ ሲለኝ ከሞከርነው ይልቅ ያልሞከርነው ነው የሚቆጨኝ” እንዳለው ሎሬቱ፣ የኢትዮጵያ ልጆች ያልሞከሩት የእርስ በርስ ትግል የለም። ከወረቀት እስከ ጥይት፣ ከሐሳብ እስከ ሒሳብ፣ ከመንደር እስከ ሀገር፣ ከዘር እስከ ስናይፐር፣ ከረሃብ እስከ ጥጋብ፣ ከሰፈር ንትርክ እስከ ሀገር ታሪክ፣ ከገጀራ እስከ ሚሳኤል ሁሉንም አብሮ የመጥፊያ መንገዶችን ሞክረዋል።
ረጅሙ የንትርክ ታሪካችን፣ አድዋ፣ ማይጨውንና ካራማራን በመሰሉ አጭር የአብሮነት ታሪኮች ባይገመድ ኖሮ፣ ይኸኔ  ተበትነን ነበር። “እንደ ብልህ አብረን መኖር ካልቻልን፣ እንደ ሞኝ አብረን እንጠፋለን” እንዲሉ፣ መፍትሔው አብሮና አብ’ሮ መኖር ነው።
አብሮ ለመኖር “ትናንትን በይቅርታ እያለፉ፣ የዛሬን ቀዳዳ እየሰፉ፣ ነገን በተስፋ መንደፉ” ያልሞከርነው መንገድ ነው። ከሞከርነው ያልሞከርነው ብዙ ነው።
አብረን ከመጥፋት ይልቅ አብረን ለመኖር የምትመች ሀገር ለመፍጠር ህሊናዊ አስተውሎትና ብስለት ከመሪ እስከ ተመሪ ተነፈግን። ሁሉም ነገር የጅብ እርሻ ሆነ-እየጎለጎሉ ማረስ፣ እየገነቡ ማፍረስ።  ህሊናችን በጥላቻ ቆሸሸ፣ በመጠላለፍ ሟሸሸ። ተስፋችንና ህልማችን ሁሉ እንደ አመዳይ ወየበ። ስጋትና ብሶት የየቀን ቀለባችን ሆነ። ሁላችንም ከቃላችን ከህሊናችን ሸሸን።
ለአንድ ህይወታችሁ፣ ለአንድ ሆዳችሁ፣ ለአንድ የስልጣን ምኞታችሁ፤ ሀገርንና ህዝብን አደጋ ላይ የሚጥል ተንኮል ውስጥ የገባችሁ አደብ/ቀልብ ብትገዙ ምን አለበት? ቆም ብላችሁ ህሊናችሁን ጠይቁ፣ እራሳችሁ ለራሳችሁ ጥያቄ አርቅቁ (ህዝብማ መች ትሰሙና?)።
ሀገሪቱን  ሌላ ሴራ፣ ሌላ መከራ፣ ሌላ ኪሳራ ውስጥ  አትክተቷት። ቢያንስ ቢያንስ መጀመሪያ ከራሳችሁ ከህሊናችሁ ታረቁ። ከዚያ መንገዱ ቀላል ይሆናል.... ያልተሞከረውን ሞክሩ፣ ያልተሄደበትን መንገድ አሳብሩ..... .መጀመሪያ ከህሊናችሁ ታረቁ፣ ነፃ ውጡ። ነፃ ያልወጣ ህሊና፣ እንኳን ህዝብን ግለሰቡን ነፃ አያወጣም። አሊያ “እንደ ብልህ አብረን መኖር ካልቻልን፣ እንደ ሞኝ አብረን እንጠፋለን”፡፡
________________________________________

                      አጠቃላይ ቅኝት "እስከ መቼ በአጼዎቹ እያሳበብን እንሳነፋለን?"


         ሰሞኑን በመጠኑ የቃኘነዉ ኪታብ /ኢንቲሻር…/ ‹‹ታሪካችን በወጉ አልታጻፈም ወይም ሆነ ተብሎ ተዘሏል፤ ጠልሽቷል ወዘተ›› በሚለዉ በኃይማኖትና በዘዉግ ፖለቲካ አቀንቃኞች ዘንድ በተለመደ ሙሾ የተወጠነ ነዉ፡፡ በኪታቡ መግቢያ (ተምሂድ) ለዚህ ሙሾ ይሁንታ ተችሮ ለዚሁ አገልግሎት በአማርኛ የተጻፈች አንዲት አርቲክል እንደወረደች ወደ ዐረብኛ ተተርጉማ ነግሳበታለች፡፡
ጥንትም ሆነ በቅርቡ የኢትዮጵያን ታሪክ ለመጻፍ ብዕር ያነሱ ጸሀፍት፤ Selection, Omission, Demonization, Interpretation or misinterpretation የተሰኙ አራት ዘዴዎችን በመጠቀም  ታሪክ እንዳዛነፉ አርቲክሏ ታትታለች፡፡ ሌሎች ወንድሞችም አርቲክሏን የመጽሀፍ መግቢያ ሲያደርጓት ታዝቤያለሁ፡፡
በወጉ ያልተመዘገበ የታሪክ ክፍል ሊኖር ስለመቻሉ አልከራከርም፡፡ ሆኖም ታሪክ ላለመዘገቡ እንደ ምክንያት ሊመዘዙ ከሚችሉ በርካታ ሰበዞች መካከል ሴራን ለይቶ ሁሉንም ችግር በርሱ ላይ መደፍደፍ  የ‹‹conspiracy mentality›› አባዜ ነዉ፡፡ ለታሪክ ዘገባዎች ያልተሟሉ መሆን ሊጠቀሱ ከሚችሉ ሰበቦች መሀል፡-
1.  የጽሁፍ ባህል አለመዳበርን ማንሳት ይቻላል፡፡ በአሀዝ ረገድ በርከት የሚሉ የሀገራችን ጎሳዎችና ነገዶች ሳይቀር የጽሁፍ ባህል ሳያዳብሩ ለዘመናት በመኖራቸዉ ታሪካቸዉን በአፈታሪክ መልክ ከትዉልድ ትዉልድ ከማስተላለፍ በስተቀር በጽሁፍ መዝግበዉ ማሻገር አልቻሉም፡፡ በጽሁፍ ያልተሰነደ ነገር ደግሞ በጊዜ ሂደት መጥፋቱ፣ መበረዙና መከለሱ፣ መጨመሩና መቀነሱ አይቀርም። የጽሁፍ ባህል በአንጻራዊነት የዳበረባቸዉ አካባቢዎች ጸሀፍት የሚጽፉት በዙሪያቸዉ ስላለዉና ስለሚያዉቁት ህዝብ፣ ሀይማኖትና ባህል፣ በተለይም ደግሞ ስለ ነገስታቱ ገድል እንደሆነ ዕሙን ነዉ፡፡ ወንዝ ተሻግረዉ የሌላዉን ለመጻፍ የቦታ ርቀት፣ የቋንቋ አለማወቅ፣ የባህል ወዘተ ዉስንነቶች እንደሚኖሩ ይታወቃል፡፡ ይህም ሆኖ አንዳች አጋጣሚ ሲፈጠር የሌላዉን አካባቢ ከመጻፍ ወደ ኋላ እንደማይሉ ማሳያዎችን መጥቀስ ይቻላል። ለምሳሌ አባ በሕሪይ የተባሉ የጋሞ መነኩሴ፣ በ16ኛዉ ክፍለ ዘመን የነበረዉን የኦሮሞ ታሪክ ክፍል በዓይን ምስክርነት አሳምረዉ ከትበዉታል፡፡ ይህ የመነኩሴዉ  ሥራ፣ የዚያ ዘመን ታሪክ አብይ ምንጭ ሆኖ በማገልገል ላይ ይገኛል፡፡ ፕሮፌሰር ጌታቸዉ ኃይሌ ‹‹የአባ ባሕሪይ ድርሰቶች…›› በሚለዉ ድንቅ መጽሀፋቸዉ፤ ግዕዙን ወደ አማርኛ በመመለስ ከሌሎች የታሪክ ምንጮች ጋር እያሰናሰሉ ጠቃሚ ዳሰሳ አድርገዉለታል፡፡ አሁናዊ ሁኔታዎችን ሳይቀር በወጉ ለመረዳት በእጅጉ ስለሚጠቅም ብታነቡት ታተርፉበታላችሁ፡፡
2.  በሙስሊሙ ወገን የጽሁፍና የምርምር ባህል ከጥንት ጀምሮ የነበረ ቢሆንም፣ የሀገራችን ሊቃዉንት የአትኩሮት ማዕከል ሀይማኖታዊ መጽሐፍትን ማዘጋጀትና መተንተን፣ እንዲሁም የነብዩ ሙሀመድ ዉዳሴ (መድህ) በመሆኑ፣ የሀገር ቤቱ የእስልምና ታሪክ በነርሱ ተገቢዉ ትኩረት አልተቸረዉም፡፡ ሊቃዉንቶቻችን ለሀይማኖታዊ ትምህርት አገልግሎት የሚዉሉ ኪታቦችን በአስደናቂ ብቃት መጻፋቸዉና ማብራሪያ (ሸርህ) መስራታቸዉ የሚታወቅ ነዉ፡፡ የነብዩ ዉዳሴ (መድህ) ድርሳኖቻቸዉም መሳጭና ዘመን ተሻጋሪ ናቸዉ፡፡ ዓለማቀፍ ዕዉቅናን ከተጎናጸፉ ጸሀፊዎቻችን መካከል በ662 ሂጅሪያ የሞቱት የሀዲስ ጥናት አዋቂ ጀማሉዲ ዐብደላህ እብን ዩሱፍ፤ ‹‹ነስቡራያ ፊተኽሪጂ አሀዲሲል ሂዳያ›› የተባለ መጽሐፍ አዘጋጅተዉ ለዓለም አሰራጭተዋል፡፡ በ643 ሂጅሪ የሞቱት የሀነፊ መዝሀቡ ሊቅ ፈኽሩዲን ዑስማን እብን ዐሊ ‹‹ተብይነል ሀቃኢቅ ፊሸርህ ከንዘ ደቃኢቅ››፣ ‹‹ሸርህ ጃሚዑል ከቢር›› የተሰኙና ሌሎችንም ለሀነፍይ መዝሀብ በዓለማቀፍ ደረጃ ‹‹ሪፈረንስ›› የሆኑ ዕዉቅ ኪታቦችን አዘጋጅተዋል፡፡
በ1230 ሂጅሪይ የሞቱት ጀማንጉስ፣ በ1240 የሞቱት ተማሪያቸዉ ሸኽ ሰይድ እብን ፈቂህ ዙበይር፣የራያዉ ጀማሉዲን አልዐኒ ወዘተ በርካታ የምርምር ሥራዎችን ከሠሩ ሊቃዉንቶቻችን መካከል ናቸዉ፡፡ በዚህ ረገድ የሀገራችን ዑለሞች አስተዋጽኦ በ‹‹ኢንቲሻር…›› ኪታብ ዉስጥ በሚያምር ሁኔታ ተጽፏል። በነብዩ ዉዳሴ (መድህ) ቅኔዎች ረገድም እነ ሸኽ ጫሌ የመሳሰሉ ማዲሆች በዐረብኛም በአማርኛም እጅግ መሳጭ ሥራዎችን ለሀገር አበርክተዋል፡፡ አበልቃሲም የሊቃዉንቶቻችንን ብቃት ሲመሰክሩ፡-
‹‹በዚህ ዘመን በሙስሊሙም ሆነ በዐረቡ ዓለም ከሚገኙ ዑለሞች ዉስጥ የፊቅህና የነህዉ ረቂቅ ሚስጥራትን በመረዳቱ ረገድ የሀበሻ ዑለሞችን የሚገዳደር እንደሌለ ነዉ የማምነዉ። ይህም የሆነዉ የመማር ማስተማር ሂደታቸዉ የተበጠረና የነጠረ በመሆኑ ነዉ፡፡›› (አዕላም 159)
ሆኖም ይህን ያህል ብቃት ላላቸዉ ሊቃዉንቶቻችን ታሪክን መዝግቦ ለትዉልድ ማስተላለፍ የትኩረት ማዕከላቸዉ አልነበረም። አስበዉበት ቢሆን ኖሮ የኢትዮጵያችንን ታሪክ የተሟላ የሚያደርጉ ግሩም ጥናቶችን እናገኝ ነበር፡፡
ስለዚህ ታሪክን መዝግቦ የማስተላለፍ፣ ቅርስን ጠብቆ ለትዉልድ የማስቀረት ወዘተ ባህል በሊቃዉንቶቻችን ዘንድ እምብዛም አለመኖሩ ለታሪካችን በወጉ አለመጻፍ እንደ አንድ ምክንያት ሊጠቀስ ይችላል፡፡ ይህም ስለሆነ አብዛኞቹ የሊቃዉንቶቻችን (መሻኢኾቻችን) ገድሎች የተላለፉት በጽሁፍ ሳይሆን በአንደበት (በቂሷ) ነዉ፡፡ ታሪክን በጽሁፍ ያስተላለፉ በጣት የሚቆጠሩ ሊቃዉንት ቢኖሩንም የሚጽፉት በዐረብኛ በመሆኑና መኖሩም ስለማይታወቅ ለሀገራችን ታሪክ ጸሀፊዎች እንደ ምንጭ አላገለገለም፡፡ ከነዚህ የዐረብኛ ሥራዎች መካከል የህትመት ብርሀን ያገኙት ኢምንት ናቸዉ፡፡ አሁን አሁን በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፊሎሎጂ ትምህርት ክፍል የተወሰኑ ኪታቦች ለሁለተኛና ለሶስተኛ ዲግሪ ማሟያ ጥናት እየተሠራባቸዉ መሆኑ ጥሩ ጅምር ቢሆንም፣ ከሚፈለገዉና ከሚጠበቀዉ አኳያ የተሠራ ነገር አለ ለማለት ይቸግራል፡፡
በጥቅሉ በሙስሊሙ ወገን የተከወነዉን የኢትዮጵያ ታሪክ ክፍል፣ እንዲሁም ቅርሶቻችንን እምብዛም ጠብቀን ማቆየት አልቻልንም። ይህ መሆኑ የኢትዮጵያን ታሪክ ያልተሟላ እንዳደረገዉ የታሪክ ጸሀፊዎች ይናገራሉ፡፡ ለምሳሌ ፕሮፌሰር ጌታቸዉ ሀይሌ በአባ ባህሪ ድርሰቶች ቅኝታቸዉ ዉስጥ ይህን መሰል ነጥብ አንስተዉ ‹‹ያልተሟላዉን ስለማሟላት›› ሀሳብ አጭረዋል፡፡ እናም በራስ በኩል የተፈጠረን ክፍተት ‹‹ከአጼዎቹ›› ወይም ከ‹‹ጭቆና›› እያገናኙ መነጫነጭ ፍትሀዊ አይደለም ብቻ ሳይሆን፤ ችግሩ በትክክል ታዉቆ መፍትሄ እንዳይበጅለት እንቅፋት ይሆናል፡፡
ጥንት ይቅርና አሁንም በዕዉቀት፣በተለይም በታሪክ ዕዉቀት ምርትና ልማት ዘርፍ ሁነኛ ሚና አለን ብዬ አላምንም፡፡ ይህ የሆነዉ ‹‹አጼዎቹ›› ስለከለከሉን ወይም ‹‹ስለጨቆኑን››፣ ወይም ደግሞ ‹‹ደብተራዎች›› ስላሴሩብንና ‹‹ኦርቶ-አማራ›› ስላቀበን ሳይሆን እንደ ማህበረሰብ ለትምህርትና ለዕዉቀት ልማት ያለን ግንዛቤ እጅግ አናሳ በመሆኑ ነዉ፡፡ ምን ያህል የፊሎሎጂ፣ የታሪክ ወይም የአንትሮፖሎጂ ወዘተ ተማሪዎች አሉን? ካሉት ተማሪዎቻችን መሀል ምን ያህሎቹ ትምህርታቸዉን በወጉ ያጠናቅቃሉ? ስንቶቹስ በተማሩበት መስክ ይሠራሉ? ስንቶቹ ወደ ላይ በትምህርት ይገፋሉ? ከነርሱ መካከል ብቁ ተመራማሪዎች ምን ያህል ናቸዉ? የትኞቹስ በሙስሊሞች ጉዳይ ላይ ያተኮሩ ጥናቶችን ይሠራሉ? ለመሥራት ቢያስቡስ ምርምር የሚጠይቀዉን የገንዘብና የሞራል ድጋፍ ሊሰጥ የሚችል የማህበረሰብ ክፍል ወይም ተቋም አለን? የቅርስ ጥበቃ ባህላችን ምን ይመስላል? ለነዚህና መሰል ጥያቄዎች የምንሰጠዉ መልስ ተጨባጫችንን ቁልጭ አድርጎ ያሳያል፡፡ ስሙን መጥቀስ የማልፈልገዉ ወጣት የፊሎሎጂ ዶክተርና ተመራማሪ ሁኔታዎች ስላልተመቹት ዕድሜ ልኩን የለፋበትን ትምህርትና ምርምር እርግፍ አድርጎ ትቶ ልብስ እንደሚቸረችር አዉቃለሁ፡፡ አንድ ጉምቱ የታሪክ ፕሮፌሰር -ልክ እንደ ሀዲስ ሊቁ ሀጅ ራፊዕ- በደሳሳ የቀበሌ ጎጆ ዉስጥ ኖሮ አልፏል፡፡ ዕዉነታዉ ይህ ሆኖ እያለ ‹‹እገሌ ታሪኬን አልጻፈልኝም›› እያሉ አሁንም ድረስ ማላዘን፣ አጼዎችን መዉቀስ፣ የታሪክ ሰናጆቻችንን ‹‹በሙስሊም ጠልነት›› መክሰስና ሥራዎቻቸዉን ማራከስ ተገቢነቱ አይታየኝም፤ ጠቀሜታም የለዉም፤ ለችግራችንም መፍትሄ አይሆንም፤እንዲያዉም ራሳችንን በወጉ ፈትሸን ችግራችንን እንዳንረዳና ወደትክክለኛዉ አቅጣጫ ጉዞ እንዳንጀምር ማሳነፊያ ይመስለኛል፡፡ ችግርን ወደ ሌሎች ማላከክ ቅንጣት መፍትሄ አይሆንም፡፡ እስከ መቼ በአጼዎቹ እያሳበብን እንሳነፋለን?
3.  የሀገራችን ታሪክ ጸሀፊዎች ታሪክን በጎሳና በሀይማኖት ሸንሽነዉ የመጻፍ ልምድ እምብዛም አላቸዉ ብዬ አላምንም፡፡ በነርሱ አዕምሮ ዉስጥ የነበሩት ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዉያን እንጂ ኦሮሞ፣ አማራ፣ ትግሬ፣ ጉራጌ … አይደሉም። ስለአጤ ዮሀንስ ሲጽፉ ትግሬነታቸዉ፣ ስለአጤ ቴዎድሮስ ሲጽፉ አማራነታቸዉ፣ ስለጎበና ዳጬ ወይም ስለጅማ አባጅፋር ሲጽፉ ኦሮሞነታቸዉ ከጸሀፊዎቻችን ስሌት ዉስጥ እምብዛም አልገባም፡፡ ቢበዛ ከሸዋ፣ ከጎንደር፣ ከሀረር ወዘተ እያሉ አካባቢ ሊጠቅሱ ይችላሉ እንጅ ዘዉግ ዋነኛ ጉዳያቸዉ አልነበረም፡፡ ክስተቶችን (ለምሳሌ ዶጋሊን፣ የአምባላጌን፣ የጉደትና ጉራን ወይም የአድዋን ፍልሚያዎች) ሲዘግቡ የሚያተኩሩት በሂደቱና ‹‹በራስ እገሌ የተመራ ጦር እንዲህ አደረገ›› በሚሉት ጉዳዮች ላይ እንጅ በጎሳና ነገድ ሽንሸና ላይ አይደለም፡፡ የዘዉግ/ብሄር ነገር መላቅጡን እያጣ የመጣዉና የፖለቲካ መቧደኛ በመሆን ሀገር ሊያፈርስ የደረሰዉ ከ1960ዎቹ ወዲህ ነዉ፡፡ ስለዚህ ከዚያ በፊት ታሪክ የመዘገቡ ወገኖችን ከዚያ ወዲህ በመጣ እኩይ አስተሳሰብና ዝንባሌ መመዘን ተገቢ አይደለም፡፡
ባይሆን ለክስተቶች ሀይማኖታዊና መንፈሳዊ ትርጓሜ (interpretation) መስጠት የዚያ ዘመን አጻጻፍ ባህሪ ነዉ፡፡ ለምሳሌ ጸሀፊዉ የርሱ ወገን ሲያሸንፍ ‹‹መላእክት ረድተዉት፣ ፈረሰኛዉ ጊዮርጊስ አብሮት ተዋግቶ፣ታቦቱ ተከትሎት…›› የሚል ምክንያት ይሰጥና ሲሸነፍ መሸነፉን ዘግቦ፣ ግና ከመንፈሳዊነት ጋር ሊያይዘዉ ይችላል፡፡ ለምሳሌ ‹‹ሰይጣን ከጠላቶቹ ጎን ስለሆነ ወይም ጾም ጸሎት ስለተዘናጋ ወይም የማርያምን ቤተ ክርስቲያን ስላላሠራ፣ ስለቷን ስላላስገባ፣ በባዕል ቀን ስራ ስለሰራ ወዘተ›› እያለ ለሽንፈቱ መንፈሳዊ ምክንያት ይደረድር ይሆናል። ይህ ዓይነቱ አጻጻፍ በየትኛዉም ሀይማኖት ታሪክ ጸሀፊዎች ዘንድ የተለመደ ነዉ፡፡ ‹‹ፉቱሀል ሀበሽ››ን ለናሙና በማየት ይህን ማጤን ይቻላል፡፡ ዐረብ ፈቂህ የኢማሙን እንቅስቃሴዎች፣ ዉጊያዎች ማፈግፈጎች፣ ድሎችና ስኬቶች በአንድ በኩል፣ የተቃራኒያቸዉን ሁለንተናዊ ድርጊቶችና እንቅስቃሴዎች፣ በሌላ በኩል የሚገልጹበትና የሚተረጉሙበት መንገድ ከመንፈሳዊና ሀይማኖታዊ ቃናና ዝንባሌ ዉጭ አይደለም፡፡ የጥንት ዘመን የታሪክ አጻጻፍ መንገድ እንደዚሁ ስለሆነ ገለልተኛ ተመራማሪ ከሁለቱም ወገን መንፈሳዊ ትርጉሞችን፣ የተጋነኑ ገለጻዎችንና የዉገና ዝንባሌዎችን አበጥሮ በመለየትና ወደ ጎን በመተዉ ክስተቶችን ብቻ ወስዶ በሳይንሳዊ መንገድ ያጣራል፣ ያቀናጃል፣ ይተነትናል። የዘመናዊ የታሪክ አጻጻፍ ጅማሮ የሆኑት ተክለጻድቅ መኩሪያ ‹‹የግራኝ አህመድ ወረራ›› መጽሀፋቸዉ ዉስጥ በ‹‹ፉቱሀል ሀበሺ››ም በግእዙም የታሪክ ድርሳናት ወገን የሚገኙ ተመሳሳይ ገለጻዎችንና ግነቶችን እየተከታተሉ በመመርመር ሲሀይሱ በብዛት ይስተዋላል፡፡
‹‹ኢትዮጵያ ዉስጥ የብሄር ጭቆና ነበር›› የሚለዉ ስሁት ተረክ፤ ሀሰቶች ተደርተዉበትና አለቅጥ ተጋኖ አየሩን በማጨናነቁ፣ ብዙ ጸሀፍት የዚህ ተረክ ሰለባ ሲሆኑና ከርሱ ባሻገር ለማየት ሲቸገሩ ይስተዋላል፡፡ ይህ የጭቆና ተረክ ባለፉት 700 ዓመታት የጊዜ ሂደት ዉስጥ ተፈጽመዋል ‹‹የሚባሉ›› ‹‹ክፉ ነገሮች›› ሁሉ ለአማራ የሚያሸክም አይዲዮሎጂ ሆኖ ይህን መከረኛ ህዝብ ላለፉት 30 ዓመታት ሲያስጨፈጭፈዉ ኖሯል፡፡ አሁንም እያስጨፈጨፈዉና በሚሊዮኖች እያፈናቀለዉ ይገኛል፡፡ ‹‹ኢንቲሻሩል ኢስላም…›› መጽሐፍ ከዚሁ ‹‹የብሄር ጭቆና›› ዝንባሌ ረገድ የደረሰበት ተጽእኖ ይኖር ይሆን? በምን ያህል መጠን? የሚሉ ጉዳዮችን በሌላ ጊዜ ከሌሎች መጽሐፍት ጋር በማሰናሰል እንመለስባቸዉ ይሆናል፡፡
እስልምና ለዘለዓለም ጭቆና የሚዳርግ ‹‹ንጥረ-ነገር›› በዉስጡ የያዘ፣ መጨቆን የሙስሊሙ ህብረተሰብ የሁልጊዜ ‹ቀደር›› እስኪመስል ድረስ የሃይማኖት ጭቆና አቀንቃኞች ይህን የ‹‹ተጨቁነን ኖረናል›› ተረክ አብዝተዉ ሲያራግቡት ይስተዋላል፡፡ ለቅሶን ለፖለቲካ ዓላማ የሚጠቀሙ ወገኖችም እጅግ አጋነዉና አግዝፈዉ፣ ወይም የተሳሳተ የትንተና ስልትን ተጠቅመዉ በዚሁ ሙሾ የተቃኙ ድርሳን ማዘጋጀታቸው ይታወቃል፡፡ ይህ ተረክ በ‹‹ኢንቲሻር…›› ኪታብ ላይ ጥላዉን በምን ያህል መጠን እንዳጠላ ተገቢዉን ፍተሻ ማድረግ አስፈላጊነቱ እንዳለ ሆኖ ተረኩ የፈጠረዉን ጭጋግ የሚገፍና በኢትዮጵያ የሙስሊሞችን የድልና የስኬት ክንዋኔዎች ጨምሮ ነባራዊዉን ሁኔታ ሳያጋንንና ሳያቀጭጭ እንዳለ የሚያቀርብ መጽሐፍ በባለሞያዎች የመሠራቱ አስፈላጊነት አሁን ጊዜዉ ይመስላል፡፡
የያዝነዉን መጽሀፍ ቅኝት ለጊዜዉ እዚህ ላይ ልግታ፡፡ የቀሩ ነጥቦች እንዳሉ ዕሙን ነዉ። ሆኖም ለፌስቡክ አቅም እስካሁን የቀረቡት ሀሳቦች ከበቂ በላይ ናቸዉ፡፡ ቀሪዎቹ ሰፋ ባለ ሌላ ‹‹ፕላትፎርም›› ይቀርቡ ይሆናል። ከመጽሀፉ ዉስጥ ለናሙና ያየናቸዉና ሌሎችም የ‹‹ፋክት››፣ የቅኝትና የትንታኔ እንከኖች እንደተጠበቁ ሆኖ መጽሐፉ በዉስጡ ጠቃሚ መረጃዎችን የያዘ በመሆኑ ማንበቡ አትራፊ ያደርጋል፡፡
በመጨረሻም ደራሲዉ ዓመታትን ፈጅተዉ አድካሚዉን የምርምር ሥራ በማከናወን ለሀገራችን የታሪክ ምርምር ግብአት የሚሆን ድርሳን ስላበረከቱልን ሊመሰገኑ ይገባል። አሁን ያላቸዉን ጥሩ የምርምርና የመጻፍ ክህሎት የበለጠ አዳብረዉ ሌሎች ጠቃሚ የጥናት ዉጤቶችን እንደሚያስነብቡን ተስፋ አደርጋለሁ፡፡
በወርሀ ረመዳን ሁኔታዎች ከተመቻቹ ከወሩ መንፈሳዊ ድባብ ጋር የሚሄዱ ጽሁፎችን አጋራ ይሆናል፡፡ የመጽሀፍት ዳሰሳዎችና ሌሎች አጀንዳዎችን ግን ከረመዳን ማግስት እመለስባቸዋለሁ፡፡
መልካም የዒባዳ ጊዜ!!!

 ኢትዮጵያ እንዳላት የታሪክ የባህልና የተፈጥሮ ጸጋ፤ የቱሪዝም ዘርፉ ተጠናክሮ ለአገሪቱ የሚገባትን ያህል ጥቅም እያስገኘ አይደለም የሚለው ሃሳብ ሲወተወትበት የኖረ ጉዳይ ነው፡፡ ምንም እንኳን አገሪቱ እንዳላት አቅም ያህል ባይሆንም እስከ 2019 እ.ኤ.አ. ድረስ የቱሪዝም ዘርፉ ከፍተኛ እመርታን እያሳየ ነበር፡፡
በ2019 እ.ኤ.አ. ከ800 ሺህ በላይ ጎብኚዎችን አገሪቱ ተቀብላ አስተናግዳለች፡፡ ይህም በ2000 እ.ኤ.አ. ከነበረው ከ136 ሺህ የጎብኚዎች ቁጥር አንፃር እጅጉን የተሻለ ሆኖ ተመዝግቧል፡፡ ይህም ብቻ ሳይሆን ከ2019 እ.ኤ.አ. በፊት ዘርፉ ከአምስት በመቶ በላይ ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚ እያበረከተ ቆይቷል፡፡
ይህ ሁሉ የዘርፉ ተስፋ ከ2019/20 እ.ኤ.አ. በኋላ ጨላለመ፡፡ የኮሮና ቫይረስ አለም ላይ ከደቀነው አደጋ የከፋ የሚባለው የቱሪዝም ዘርፉ ላይ ያደረሰው መሆኑን መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ሆቴሎች ተዘጉ፤ ሰራተኞቻቸው ተበተኑ፤ አንዳንድ ሆቴሎች ወደ ጤና ማዕከልነት እስከመቀየር ሁሉ ደረሱ፤ የአስጎብኚ ድርጅቶች የሥራ ዘርፋቸውን እንዲቀይሩ ተገደዱ! ውርጅብኙ በአለም ታሪክ ውስጥ ታይቶ የማይታወቅ ተብሎም ተመዘገበ፡፡
የኮሮና ቫይረስ የደቀነው ስጋት በአለም ላይ ጋብ እያለ ቢመጣም፣ የኢትዮጵያ የቱሪዝም ዘርፍ ግን ለብቻው ሌላ ተግዳሮት ተጋርጦበት ቆይቷል፡፡ ኢትዮጵያ ከ2013 እ.ኤ.አ. ጀምሮ በተለያዩ ፖለቲካዊ ውጥንቅጦች ውስጥ ማለፏ ይህ ውጥንቅጥ በአጠቃላይ ለንግድ እንቅስቃሴው በተለይ ደግሞ የቱሪዝም ዘርፉ ጉሮሮ ላይ በመቆም አላላውስ ብሎት እንደዘለቀ የቅርብ ግዜ ትዝታ ነው፡፡
የአገሪቱ የፖለቲካ ውጥንቅጥ በተለይ ደግሞ ባለፉት አራት አመታት አይነቱን ቅርጹንና ምክንያቱን እየቀያየረ በቱሪዝም ዘርፉ ላይ ተግዳሮት መሆኑን ቀጥሏል፡፡ አሁንም በ2020 እ.ኤ.አ. በሰሜን ኢትዮጵያ የፈነዳው ጦርነት  በአይነቱ ልዩ የሆነና ከባድ ማነቆን በዘርፉ ላይ ጥሎ ከርሟል፡፡ ይኸኛው ተግዳሮት የቱሪስት መስህብ የሆኑ አካባቢዎች ላይ ጉዳት እስከ ማድረስና በዘርፉ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የተለያዩ ግለሰቦችና ተቋማት አገልግሎታቸውን አቁመው ሰራተኞቻቸውን እስኪበትኑ ያደረሰ ከባድ ጊዜም ነበር፡፡
ምንም እንኳን የቱሪዝም ዘርፉ ላይ ቀጥተኛ ተጽዕኖ እያሳደሩ ያሉና እዚህም እዚያም የሚስተዋሉ የጸጥታ ችግሮች እስካሁንም እንደቀጠሉ ቢሆንም፤ በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል የነበረው ሲካሄድ የቆየው ጦርነት በሰላም ስምምነት መቋጨቱ እንደተቀረው ኢኮኖሚ ዘርፉ ለቱሪዝም ዘርፉም እፎይታን መፍጠር ነበረበት፡፡
እንዳለመታደል ሆኖ ይኼ አልሆነም፡፡ በቅርቡም የመሆን ተስፋ አይታይበትም መንግስት የዜሮ የተጨማሪ እሴት ታክስ ተጠቃሚ ብሎ በአዲስ ረቂቂ አዋጅ ላይ ካስቀመጣቸው ዘርፎች መካከል የቱሪዝም ዘርፉ የማይገኝበት መሆኑ ታውቋል፡፡ ይህ የፖሊሲ አቅጣጫ ትክክል እንዳልሆነ የዘርፉ ተዋናዮች ብዙ አመክንዮዎችን በማንሳት ይሞግታሉ፡፡
በቅድሚያ የአስጎብኚዎችና የሆቴል እንዲሁም መሰል እንቅስቃሴዎች በዘርፉ ውስጥ የተሰማሩትን የንግድ ተቋማት እጅግ ብዙ ወጪ የሚያስወጡ ቢሆንም ሁሉም እነዚህ ወጪዎች ግን በግብር ስርዐቱ አለመሸፈናቸው አንዱ ትልቁ ተግዳሮት መሆኑን ይገልፃሉ፡፡
አንድ ሆቴል የምግብ አገልግሎቱን ለማቅረብ የሚገዛቸው ቁሳቁሶች በሙሉ ለማለት በሚያስችል ደረጃ፣ በደረሰኝ ተገዝተው በወጪ መልክ ከገቢዎች ጋር መወራረድ የሚችሉ አይደሉም፡፡ በተመሳሳይ መልኩም፤ አንድ አስጎብኚ ድርጅት አስጎብኚዎችን ይዞ ከአንድ የቱሪዝም ቦታ ወደ ሌላኛው ሲያዘዋውር የሚያወጣቸው የትራንስፖርት፤ የጉብኝት ቦታዎች ክፍያዎችና መሰል ወጪዎች ሁሉም ደረሰኝ ሊሰበሰብላቸው የሚችሉ ባለመሆናቸው እንደወጪ ተመዝግበው በገቢዎች ደረጃ ሊወራረዱ አይችሉም፡፡
ከዚህም በተጨማሪ፣ በዘርፉ ውስጥ አገራቸውን በአለም ደረጃ ለማስተዋወቅና ለራሳቸውም ገቢ ለማግኘት ከአገር ውጪ የተለያዩ ክፍያዎችን በመፈጸም የተለያዩ ማስታወቂያዎችን ማሰራት፤ ከአገር ውጪ እይታን የሚጨምሩ እንቅስቃሴዎች ላይ መሳተፍና ለነዚህም እንቅስቃሴዎች ክፍያን መፈጸም ይጠበቅባቸዋል፡፡ አንድ ሆቴል፤ አሊያም የአስጎብኚ ድርጅት ከፍቶ ቁጭ ስለተባለ ብቻ ጎብኚዎች ይመጣሉ ማለት እንዳልሆነ ልብ ይሏል፡፡
በቅድሚያ የትኞቹም እነዚህ ወጪዎችን እንዲያደርጉ የውጪ ምንዛሬ እንዲያገኙም ሆነ የክፍያ ስርዐቱን በማመቻቸት በኩል ከመንግስት የትኛውንም ድጋፍ ሳያገኙ በግል ጥረት እነዚህን ክፍያዎች በራሳቸው እየከፈሉ ጎብኚዎችን ወደ አገር ውስጥ ሲያመጡ ነው የኖሩት፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የትኞቹም እነዚህ ወጪዎች በአገር ውስጥ እንደ ወጪ ተመዝግበው የሚወራረዱበት መንገድ አለመኖሩን ከግምት ውስጥ ያስገባ አይመስልም-አዲሱ የተጨማሪ እሴት ታክስ ረቂቅ አዋጅ፡፡
አዲሱ የረቂቅ አዋጅ ከግምት ውስጥ ያላስገባቸው እውነታዎች በዚህም የሚያበቁ አይደሉም። ኢትዮጵያ ከኮሮና እና ከፖለቲካዊ አለመረጋጋቶቹ በፊት በአመት ከ800 ሺህ በላይ የሚሆኑ ጎብኚዎችን ያስተናገደችበት ወቅት ነበር፡፡ እነዚህ ጎብኚዎች ወደ አገር ቤት መጥተው ኢትዮጵያን እንዲገበኙ በማሳመኑ ረገድ የአንበሳውን ድርሻ የሚጫወቱት እነዚህ አስጎብኚ ድርጅቶች ናቸው፡፡
በዚህ ሚናቸው ለራሳቸውና ለቀጠሯቸው ሰራተኞች የገቢ ምንጭ ከመሆን አልፈው ለአገሪቱ የውጪ ምንዛሬ ምንጭ ሆነው ዘልቀዋል፡፡ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ የትኛውንም ያህል እያደገ ቢመጣም፣ አንድ ሊቀርፈው ያልቻለውና ህልውናውን እጅጉን እየተፈታተነ ያለው ተግዳሮት የውጪ ምንዛሬ እጥረት መሆኑ ይታወቃል፡፡
የውጪ ምንዛሬ እጥረት በአገር ውስጥ ተጠቃሚው ላይ ዋጋን ከማናሩ ባሻገር፣ መንግስታዊና መንግስታዊ ያልሆኑ እንቅስቃሴዎች በአጠቃላይ መካሄድ እንዳይችሉ እንቅፋት ሲሆን ማስተዋል የተለመደ ሆኗል፡፡ ኢትዮጵያ ገፋ ሲልም ለአንድ ሳምንት የሚሆን የውጪ ምንዛሬ ብቻ ሲቀራት የሞት ሽረት ጥረት እየተደረገ የኢኮኖሚውን ህይወት ማራዘም የተለመደ የመንግስት ተግባር ከሆነም ሰነባብቷል፡፡
እንዲህች ባለች አገር ውስጥ ለኢኮኖሚው አንድም ተጨማሪ ዶላር ሊያመጣ የሚችል ዘርፍ በምሉዕ አቅምና ፍላጎት መደገፍ አንድምታው በዘርፉ ውስጥ ከሚንቀሳቀሱ ግለሰቦችና ተቋማት አልፎ አገራዊ እንደሆነ መገመት ብዙም አዋቂ መሆንን አይጠይቅም፡፡
በአለም ላይ በቱሪዝም ዘርፍ ውስጥ የሚንቀሳቀሱ የንግድ ተቋማት ላይ ግብር ከምንጥል እነሱ ተበረታተው ከሚያመጡት የንግድ እንቅስቃሴ ብንጠቀም ይሻለናል ብለው በነዚህ ተቋማት ላይ ምንም ግብር ካለመጣል በጣም አናሳ ግብር እስከመጣል የሚደርስ ድጋፍን የሚያደርጉ በርካታ አገራት አሉ፡፡ አጅግ የሚያስገርመው ደግሞ እነዚህ አገራት እንደ ኢትዮጵያ እጅግ ከፍተኛ የውጪ ምንዛሬ እጥረት እንኳን ያለባቸው አገራት አለመሆናቸው ነው፡፡
በእነዚህና በሌሎች በርካታ ምክኒያቶች የቱሪዝም ዘርፉን የተጨማሪ እሴት ታክስ ዜሮ ሊደረግላቸው ከታሰቡ ዘርፎች ዝርዝር ውስጥ አለማካተት እንድምታው ከዘርፉ አልፎ በአጠቃላይ በአገር ኢኮኖሚ ላይ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ የቱሪዝም ዘርፉ ከኮሮና እና ከጦርነት እንዲሁም ግጭት ጠባሳዎች እንዲያገግም፤ አልፎ ተርፎም ለአገር በውጪ ምንዛሬ አምጪነት መሪ ሚናውን እንዲጫወት፣ የመንግስትን ከወትሮው የተለየ እርዳታ ይሻል፡፡
ኢትዮጵያ ዘመናዊ በሆነ መልኩ ከዘርፉ ሙሉ አቅሟን የሚመጥን ጥቅም ማግኘት እንድትችልና የቱሪዝም ዘርፉ ያንን ማድረግ ይችል ዘንድ የበኩሉን አስተዋጽኦ እንዲያደርግ ያሉበትን የግብር ማነቆዎች ለመፍታት ጊዜው አሁን ነው፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ምናልባትም ለአገሪቱ አለኝታ ሊሆን እንደሚችል የቱሪዝም ዘርፉ፣ ከእነ አካቴው አደጋ ውስጥ ሊገባ እንደሚችል ልብ ሊባል ይገባል፡፡


Saturday, 18 March 2023 20:11

የግጥም ጥግ

(አልተቀየምኩሽም። ተመለሺ ቅሪ!
ወደጀመርንበት ፊትሽን አዙሪ
ይንጋልሽ በምልሰት
ልቤ ይቀድመኛል
ዱካው ይታየኛል
እንድረስ- እንድረስ- እንድረስ
የተባባልንበት የዘላለም ዳርቻ
ተሰዷል ለብቻ
ወደኋላ አያይም- መብረር አያቆምም
እንባ ሽቅብ ደፍቷል
አልፋ እና ኦሜጋ
መቅረትሽን ሰምቷል
እንዳይተናኮልሽ
የመሸው ትዝታ- ሸኝሻለሁ ባይኔ
ለሁለታችንም እኛን ላስታውስ እኔ
ልቤ ይቀድመኛል
ዱካው ይታየኛል
ዱካው የራሴ ነው
እከተለዋለሁ
ደርሼ ብይዘው
አብረሽው እንደሌለሽ
እንዴት ነግረዋለሁ
ሳይፈነዱ ገና
የጸሐይ እንቡጦች- ወደሚበቅሉበት
ልቤ መንገድ ስቷል
… ኮኮብ ሊቀጥፍልሽ
ባዶ ዘላለም ውስጥ
ብናኝ ሆኖ ጠፍቷል።
… ተመለሺ መሽቷል
ሌሊሳ ግርማ

 በበጀት ዓመቱ መጀመሪያ ላይ ሥራውን በ 31% ማሳደጉን የገለጸው ኤምሬትስ፤ እ.ኤ.አ ከመጋቢት 26 ቀን 2023 ጀምሮ በቅርብ በተዘጋጀው የሰሜናዊ የበጋ መርሃ ግብር መሰረት የመቀመጫ አቅሙን ለማሳደግ ተጨማሪ እቅድ ማቀዱን ጠቁሟል፡፡
ባለፉት ወራት አየር መንገዱ የኔትወርክ ስራዎችን ፈጣን እድገት በማቀድና በማስፈፀም፣ አገልግሎቶችን ለ5 ተጨማሪ ከተሞች ማስተዋወቅ፣ ወደ 1 አዲስ መዳረሻ (ቴል አቪቭ) በረራ መጀመር፣ 251 ሳምንታዊ በረራዎችን በነባር መስመሮች ላይ ማከልና  በአየርና በመሬት ላይ የአገልግሎት ማሻሻያዎችን መልቀቅን መቀጠል ከእቅዶቹ መካከል የሚጠቀሱ መሆናቸውን በመግለጫው አመልክቷል።
የኤምሬትስ ዋና የንግድ ሃላፊ አድናን ካዚም በሰጡት ማብራሪያ፤ “ኤምሬትስ ዓለም አቀፋዊ መረቡን ማስፋፋቱንና በዓለም ዙሪያ የጉዞ ፍላጎትን ለማሟላት አቅሙን ማሰማራቱን ቀጥሏል። በዱባይ ዓለማቀፍ  አውሮፕላን ማረፊያ የታቀደው የሰሜናዊ አውሮፕላን ማረፊያ ማገገሚያ ፕሮግራም በሰኔ ወር እስኪጠናቀቅ ድረስ የእኛን የፋይናንስ አመት በአንፃራዊነት ጀምረናል። ከጁላይ 2022 ጀምሮ የማያቋርጥ መስፋፋት ታይቷል።” ብለዋል፡፡
አክለውም፤ “የደንበኞቻችን ፍላጎት በጣም ጠንካራ ነበር፣ የእኛ የማስተላለፍ ቦታ ማስያዝም ጠንካራ ነው። ኤምሬትስ በተለያዩ ግንባሮች ላይ ጠንክሮ እየሰራ ሲሆን፤ ስነ-ምህዳሩ ማስተዳደር በሚችለው ፍጥነት የመስሪያ አቅምን ወደነበረበት ለመመለስ፣ እንዲሁም የእኛን መርከቦችና ምርቶቻችንን በማሻሻል ደንበኞቻችን ሁልጊዜ በተቻለው የኤምሬትስ ተሞክሮ እንዲደሰቱ ለማድረግ እስካሁን 4ቱ ኤ380 አውሮፕላኖቻችን በአዲሱ የካቢን የውስጥ ክፍልና የፕሪሚየም ኢኮኖሚ መቀመጫዎች ሙሉ በሙሉ ታድሰዋል፣ እንዲሁም ሌሎች የ2 ቢሊዮን ዶላር ካቢኔና የአገልግሎት ማሻሻያ ፕሮግራማችን በፍጥነት ወደ አገልግሎት ይገባሉ” ብለዋል።
በመጪዎቹ ወራት ወደ አውሮፓ፣ አውስትራሊያና አፍሪካ መስመሮች በርካታ የኤምሬትስ በረራዎች አገልግሎት ይሰጣሉ፤ በምስራቅ እስያ ተጨማሪ ከተሞች ደግሞ የበረራ መስመር ዳግም መጀመራቸው እየታየ ነው፤ ተብሏል።
ኤሚሬትስ የA380 ስራውን ማሳደግ መቀጠሉን የጠቆመው መግለጫው፤ ከጨመራቸው ስምሪቶች መካከል፣ ግላስጎው (እ.ኤ.አ ከመጋቢት 26 ጀምሮ)፣ ካዛብላንካ  (እ.ኤ.አ  መጋቢት 15)፣ ቤጂንግ (እ.ኤ.አ  ከግንቦት 01)፣ ሻንጋይ (እ.ኤ.አ  ከ04 ሰኔ)፣ ኒስ (እ.ኤ.አ ከሰኔ 1)፣ በርሚንግሃም (ከሀምሌ 1)፣ ኩዋላ ላምፑር (ከነሀሴ 01) እና ታይፔ (ከነሀሴ 01) ለአብነት ጠቅሷል።


ህንዶች እንዲህ የሚል ተረት አላቸው።
አንድ ጊዜ አሞራዎችና ቁራዎች ስምምነት ላይ ደረሱ አሉ። ስምምነታቸውም ከጫካ የሚያገኙትን ማንኛውንም ነገር እኩል ሊካፈሉ ነው።
አንድ ቀን በአዳኞች ተመትቶ ቆስሎ መነቃነቅ የማይችል አንድ ቀበሮ ዛፍ ሥር ተኝቶ ያገኛሉ። በዙሪያው ተሰበሰቡ።
ቁራዎቹ፡- “ከወገቡ በላይ ያለው የቀበሮ ገላ ክፍል ሊደርሰን ይገባል” አሉ።
አሞራዎቹ፡- “እሺ እኛ የገላውን የታችኛውን ግማሽ እንወስዳለን” አሉ።
ይሄኔ ቀበሮ እየሳቀ፡-
“እኔ ሁልጊዜ አምን የነበረው አሞራዎች ከቁራዎች የበለጡ ፍጡሮች ናቸው የሚለውን ነበር። ስለሆነም መውሰድ ያለባቸው የአካሌን የላይኛውን ክፍል ነው ብዬ ነበር የማምነው። የላይኛው የአካላቴ ክፍል ራሴና አንጎሌ አለ። በጣም ጣፋጭና ስባት ያለው ክፍል ነው” አለ።
አሞራዎቹም ሀሳባቸውን ይለውጡና፡-
“ቀበሮ ያለው ትክክል ነው። እኛ መውሰድና መብላት ያለብን ከወገቡ በላይ ያለውን ክፍል ነው” አሉ።
ቁራዎቹ፡- “አይደለም፤ እኛ መውሰድ ያለብን እስካሁን በተስማማነው መሰረት መሆን አለበት። የላይኛው ክፍል የእኛ ቅርጫ ነው” አሉ።
ጠብ ተነሳ። ጠቡ ወደ ጦርነት ተሸጋገረ። ተተካተኩ። ከሁለቱም ጎራ ነብስ ጠፋ። ብዙ ሬሳ ተዘረረ።
የተረፉት ከሁለቱም ወገን እየሸሹ በመከራ ከጦር ሜዳው አምልጠው ወጡ።
አያ ቀበሮም አጠገቡ የተዘረሩትን አሞሮችና ቁራዎች ያለሀሳብ እያማረጠ እየበላ ከቁስሉ አገግሞ ዘና ብሎ እየተጎማለለ፣
“ኃያላን ሲናቆሩ ደካሞች ይጠቀማሉ” እያለ ሰፈሩን ለቆ ሄደ።
***
“ሁለት ፓርቲዎች ሲጣሉ፡-  ተቦጫጭቀው እስኪዳከሙ ጠብቅ። ቀስ ብለህ ትጠቀምባቸዋለህ። በጣም ቀስ ብለህም አስታራቂያቸው ልትሆን ትችላለህ” የሚል እሳቤ ያላቸው አያሌ ናቸው። የሀገራችን ፖለቲካና ፖለቲከኞች የቅርጫ ስርዓት እስከዛሬ እንዳስቸገረ አለ።
ሚቼላ ሮንግ የተባለችው ፀሐፊ፡ “አሁን መብላት የኛ ተራ ነው”፤ (የኬንያው ፊሽካ- ነፊ (ጋዜጠኛ) ታሪክ (The story of a Kenyan whistle-blower) በሚለው መፅሐፏ የምትነቁጣቸው ነጥቦች አይናችንን እንድንከፍት ይረዱናል።
“እነዚያን አንፀባራቂ ባለተስጥኦ አፍሪካውያን አስታወስኩ። አንዴ ይፋለሙት የነበረውን ሥርዓት አወድሰው፣ እስከነጭራሹም ጦርነት ፈጥረው ይዋሃዱታል። አሁን ነው የለውጥ ሰዓት። አሁን ጊዜው በስሏል ይላሉ። የማታ ማታ ግን ያው እየፈወስነው ነው የሚሉት ሥርዓት አንቅሮ ይተፋቸዋል። አዋርዶ ያባርራቸዋል”
“ኢትዮጵያና ኬንያ ምንና ምን ናቸው?...” እያሉ መግጠም የተለመደ ነገር ነው።
የፖለቲካ ተንታኙን ዤራር ፕሩኒያን ማዳመጡም አይከፋም።
“ኬንያ ከነፃነት በኋላ የፈጠረችው የአገዛዝ ስልት የጎሳዊ-ምሁርነት (ethno-elitism)፤ በየዘመኑ የሚሽከረከሩ ተፎካካሪ ምሁራን የሚቀመጡበት ለሁሉ እኩል እድል ይሰጣል የተባለውን ነገር መሳለቂያ የሚያደርግ ሥርዓት ነው። የአንድ ቡድን ጥቅም የሚጠበቅበትና ሌሎቹ ሁሉ ሙልጭ የሚወጡበት ድምሩ ዜሮ የሆነ ግጥሚያ ነው። አንዱ “ይሮ!” ሲል ሌላው “ኩም አልን!” የሚልበት ሥርዓት ነው።”
በፈረንሣይ ተናጋሪ የአፍሪካ አገሮች ይህ ሥርዓት፤ Ote-toi de la,que je m’y mette- “አንተ ዞር በል፤ እኔ ልቀመጥ” የሚሉት ዘዴን የያዘ ነው። በእንግሊዝኛ ተናጋሪ የአፍሪካ አገሮች ደግሞ አገላለጹ የበለጠ “ፈጣጣ” ነው -  It’s our turn to eat (“አሁን መብላት የእኛ ተራ ነው” እንደማለት ነው) በፓርላማ መቀመጫ፣ በሚኒስትሮች ሹመት፣ በቢሮክራሲ ድልድል ሁሉ እያንዳንዱ መንግሥት ከራሱ ባኮ እያወጣ የራሱን ሰው ብቻ ማከማቸቱን ይያያዘዋል።
ዳሩ “የዲሞክራሲ ፅጌረዳ በኬንያ ሥር የለውም” ብለዋል ኦራፕ ሞይም´ኮ።
ሙስናም ከአንዱ ደጅ አንዱ ደጅ እየተዟዟረ፣ ከአንዱ እጅ አንዱ እጅ እየተሸጋገረ፣ መቼም አፍሪካ “ቀልቀሎ ስልቻ፣ ስልቻ ቀልቀሎ…” መሆኑ አይታበልም። በር ሲዘጉበት በመስኮት፣ በመስኮት ሲሉት በጣራ እየሾለከ መከራ እንዳሳየን ነው።
እዚህ ላይ ስለ ኬንያ ይሁን እንጂ (እሳት ካየው ምን ለየው) የጠበቃ ቺራ ማይና ሃሳብ ቁምነገር አለው።
“ኬንያ ውስጥ ሙስና ከክልል ክልል ይሰደዳል እንጂ በመዋቅር መለዋወጥ (reform) አይወገድም።”
አንድ ሥርዓት ተለውጦ ሌላ  ሥርዓት ሲመጣ፣ አንድ ምርጫ ተካሂዶ ሌላ የአመራር አካል ሲለወጥ፣ ወይም አዲስነቱን “ለማረጋገጥ” ያለፈውን ሲያወግዝ፡ ያለውን ሱሪ በአንገት እስከማለት ድረስ “ይሄን አርግ”፣ “ይሄን ፍጠር” ሲል፣ ዘመን በተለወጠ ቁጥር ህዝብ ወከባና ግራ-መጋባት ውስጥ ሊገባ ይችላል።
በአገራችን ለውጡ ይዞት በመጣው ነውጥ፣ ህዝቡ ኑሮው ሲመሳቀልና ማህበራዊ ቀውስ ውስጥ ሲገባ እያስተዋልን ነው፡፡ “አዲስ እረኛ፣ ከብት አያስተኛ” የሚባለው ይሄኔ ነው።  



Sunday, 12 March 2023 11:54

ሳጣሽ ነው ውበትሽ

 ሳጣሽ ነው ውበትሽ

በተንጣለለው ዝርግ ሰማይ….
በዙሪያ ከዋክብት ዶቃ
በዛፎች ጥቁር ጥላ ስር….
ኢምንት ብርሀኗን ፈንጥቃ
የጎንዮሽ የሌብዮሽ…
የታየች ጊዜ አጮልቃ
እንደውብ ኮረዳ ገላ…
እንደምታሳይ ደረቷን ሰርቃ
እንደቆነጃጅት ዳሌ….
እንደሚጠበቅ በምጥ ሲቃ
ባየሁሽ አላየሁሽ ሙግት…
አንገት ሸሽጋ ሰብቃ
ሄደች ሲሏት ሽር-ብትን…
በጉማጉም ተደብቃ
ሳይጠግቧት የጠፋች ለታ…
ለዓይን ሙሉ ሳትበቃ
ተጠምተው ያጧት ቅፅበት ላይ…
ያኔ ነው ውበቷ የጨረቃ።
ተመስገን አፈወርቅ
(ያገሬ ምስጥ ይላሰኝ) 1993

  • ኢትዮጵያ ለሆላንድ ከ25 ቶን በላይ ቡና በእርዳታ መላኳንም አንድ ጥንታዊ ደብዳቤ አረጋግጧል


        እ.ኤ.አ በ1953…
የካቲት 1 ቀን ንጋት ላይ…
የእንግሊዝና የስኮትላንድ ምሥራቃዊ የባህር ዳርቻ አካባቢዎች በአስከፊ የጎርፍ አደጋ ተመቱ፡፡ በእንግሊዝ 307፣ በስኮትላንድ ደግሞ 19 ሰዎችን ለህልፈተ ህይወት የዳረገው አስከፊ የጎርፍ አደጋ፣ ሃያ አራት ሺህ ቤቶችን ክፉኛ ሲያፈራርስ፣ ሰላሳ ሺህ ሰዎችን ከመኖሪያቸው አፈናቀለ፡፡
ስለ አደጋውም ሆነ የአገራቱ መንግሥታት በጎርፉ አደጋ የተጎዱትንና የተፈናቀሉትን ወገኖች ለማቋቋም ስላደረጉት ጥረት መገናኛ ብዙሃን ብዙ ቢሉም፣ ኢትዮጵያ በወቅቱ ለእንግሊዝ መንግሥት በእርዳታ መልክ ስለላከችው ታላቅ ስጦታ በጥቂቱም ቢሆን መወራት የተጀመረው ግን አደጋው ከተከሰተ ከ60 ዓመታት በኋላ ነበር፡፡
እ.ኤ.አ በ2012፣ ጥር 18 ቀን፤ ጎልዲንግ ያንግ የተባለው የእንግሊዝ አጫራች ኩባንያ፣ በሊንከን የሽያጭ ማዕከሉ ለእለቱ ቀጠሮ የያዘለትን ጨረታ ደወል አስደውሎ በይፋ አስከፈተ፡፡ ኩባንያው በዕለቱ ለጨረታ ካቀረባቸው ነገሮች መካከል፣ በጨረታ መለያ ቁጥር 345 ለሽያጭ የቀረበው ለዘመናት ታሽጎ የኖረ አንድ ታሪካዊ ጣሳ ይገኝበታል፡፡
“እ.ኤ.አ በ1953 በተከሰተው የጎርፍ አደጋ የተጎዱትን ለማቋቋም፣ ከግርማዊ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገስት፣ ለግርማዊት ንግሥት በስጦታ መልክ የተበረከተ፣ እሽግ የቡና ጣሳ” የሚል አጭር የጽሁፍ መግለጫ ሰፍሮበታል ጣሳው፡፡
ግርማዊ ቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ በወቅቱ ወደ እንግሊዝ የላኩት ይህ መጠነኛ የቡና ጣሳ፣ በዕለቱ በተከናወነው ጨረታ፣ በ22 የእንግሊዝ ፓውንድ መሸጡን በአንግሎ ኢትዮጵያን ሶሳይቲ ድረ-ገጽ ለንባብ የበቃ አንድ ጽሁፍ ያስታውሳል፡፡
አና ፓርሰንስ የተባለች እንግሊዛዊት የጻፈችው ይህ ማስታወሻ፣ ማርክ ሰርጃንት የተባለ አንድ እንግሊዛዊ እ.ኤ.አ በ2007 ታይም ኤንድ ታይድ በተባለው ሙዚየም በተዘጋጀ ኤግዚቢሽን ላይ በጨረታ ከተሸጠው ጣሳ ጋር ተመሳሳይ የሆነ ሌላ የኢትዮጵያ ቡና ጣሳ ለእይታ ቀርቦ ማየቱንም ይጠቅሳል፡፡
ቢቢሲ በበኩሉ፤ እ.ኤ.አ በ2013 ጥር ወር ላይ ሜልቪን ኢን ዘ ሞርኒንግ በተባለው የሬዲዮ ፕሮግራሙ፣ የጎርፍ አደጋውን 60ኛ አመት ማስታወሻ በተመለከተ በሰራው ዘገባ፣ ኢትዮጵያ ለእንግሊዝ የአደጋው ተጎጂዎች ማቋቋሚያ የላከችውን ቡና ጉዳይ በአጭሩ ጠቅሶታል፡፡
በአንግሎ ኢትዮጵያን ሶሳይቲ ድረ-ገጽ ስለጉዳዩ የጻፈችው አና ፓርሰንስ፣ ኢትዮጵያ ለእንግሊዝ የላከችውን የቡና እርዳታ በተመለከተ ተጨማሪ መረጃዎችን ለማግኘት ባደረገችው ጥረት፣ ሱዛን ኒኮላስ የተባለች አንዲት እንግሊዛዊት፣ እ.ኤ.አ በ2013 በአባቷ ጋራዥ ውስጥ ስላገኘችው ተመሳሳይ በርሜል መስማቷንም ትጠቅሳለች፡፡
የዚህ መጽሔት ዝግጅት ክፍል ከላይ የጠቀስናቸውን መረጃዎች ይዞ በጉዳዩ ዙሪያ ተጨማሪ ፍንጮችን ለማግኘት ባደረገው ጥረት፣ የገንዘብ ሚኒስቴር ከጥቂት ጊዜያት በፊት፣ በሊንክዲን ድረገጹ ይፋ ያደረገውን አስገራሚ መረጃ ሊያገኝ ችሏል፡፡ ጥንታዊ ደብዳቤ፣ ኢትዮጵያ በ1947 ዓ.ም የጎርፍ አደጋ ደርሶባት ለነበረችው ሆላንድ (ኔዘርላድ)፣ 25 ቶን ከ500 ኪሎ ግራም የሚመዝን ቡና በእርዳታ መልክ መላኳን ያረጋግጣል፡፡
ሚያዝያ 26ቀን 1947 ዓ.ም፤ የኢትዮጵያ ንጉሠ ነገሥት መንግሥት የገንዘብ ሚኒስቴር፣ ለጠቅላይ ግምጃ ቤት የጻፈው ይህ ደብዳቤ፣ የኢትዮጵያ መንግሥት በወቅቱ ለሆላንድ በእርዳታ መልክ የላከው ቡና፣ ከእነ መላኪያውና ሌሎች ተያያዥ ወጪዎች ጋር፣ በወቅቱ የገበያ ዋጋ፣ 67,656.30 ብር (ስድሳ ሰባት ሺህ ስድስት መቶ ሃምሳ ስድስት ብር ከ30 ሳንቲም) እንደሚገመትም ያመለክታል፡፡
 በዚህ ደብዳቤ የተገለጸው የቡና እርዳታ ወደ ሆላንድ የተላከበት ጊዜ፣ ቀደም ብለው የተጠቀሱት የቡና እርዳታዎች ወደ እንግሊዝ ከተላኩበት ጊዜ ጋር ተመሳሳይ መሆኑን ከግምት ውስጥ በማስገባት ፣ እንዲሁም የተለያዩ የመረጃ ምንጮች በዚያ ጊዜ በእንግሊዝም በሆላንድም ተመሳሳይ የጎርፍ አደጋዎች ተከስተው እንደነበር ማረጋገጣቸውን በማጤን፤ በሁለቱ የቡና ስጦታዎች መካከል ግንኙነት ሊኖር እንደሚችል መገመት አያዳግትም፡፡
(የኢትዮጵያ ቡና ማህበር 50ኛ ዓመት ልዩ መጽሔት፤ የካቲት 2015)



“የአገዛዝዎ ብልሹ አሰራርን ማስተካከያ እድሉ አሁን ነው”


        አዲስ አበባ፣ ኢትዮጵያ
የካቲት 29 ቀን 2015 ዓ.ም
ለተከበሩ ዶ/ር ዐቢይ አህመድ፤
ለኢትዮጵያ ሀገራችን ትውልድና ታሪክ ተሻጋሪ የሆነ ለውጥ ያመጣሉ በሚል ተስፋ የኢትዮጵያ ዳያስፖራ፣ እርስዎንና መንግሥትዎን እስከዛሬ ድረስ በሙሉ ልብ ድጋፉን በመስጠት፤ ወደ እናት ሀገሩ የእርዳታ ገንዘብ በመላክ፤ መዋዕለ ንዋዩን በማፍሰስ፤ በድርቅና በግጭት በመፈናቀል ብዙ ጉዳት የደረሰባቸዉን ዜጎቻችንን በመርዳትና መልሶ በማቋቋም፤ በኮቪድ ወረርሽኝ ወቅት በሞያ የተደገፈ ምክር በመስጠትና በቁሳቁስ በማገዝ ዳያስፖራው ለሀገሩ ከፍተኛ አስተዋጽኦ አበርክቷል። ከእነዚህ በተረፈ፣ ለዐባይ የህዳሴ ግድብ ስኬት ገንዘብ በማዋጣትና በዲፕሎማሲው መስክ ድጋፍ በመስጠት ሰፊ የሆነ ያልተቋረጠ እገዛ አድርጓል። ሀገራችን ኢትዮጵያ በሰሜኑ የትግራይ ጦርነት ሳቢያ ከፍተኛ ውጥረት ውስጥ በገባችበት ወቅትም ዳያስፖራው ከእርስዎ፣ ከኢትዮጵያ ሕዝብ፣ ከመከላከያና የጸጥታ ኃይሎች ጎን በመቆም፣ ሀገራችንን ለማዳን በተደረገው ከፍተኛ እርብርብ፣ በተለይም በዓለም አቀፉ መስክ ግንባር ቀደም በመሆን በዲፕሎማሲና ሕዝብ ግንኙነት ዙሪያ  ያደረገውን ታላቅ ተጋድሎና አስተዋጽኦ ምንግዜም ታሪክ አይረሳዉም።
በጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም. (Nov 4, 2020) ህወሐት በሰሜን እዝ ላይ ድንገተኛ ጥቃት በመክፈት፣ በሺህ የሚቆጠሩ ንጹሀንን በተኙበት ሳይቀር ጨፍጭፎ፣ በአማራና አፋር ክልሎችም በዘመተበት ወቅት፣ ኢትዮጵያ በታሪኳ አይታው የማታውቀው የዲፕሎማቲክ ዘመቻ፣ የኢኮኖሚ ማዕቀብ እና ከምዕራባውያን እና የአለም አቀፍ ሚዲያዎች ከፍተኛ ጫና ገጥሟት ነበር። ይህን ለመቋቋም በዓለም ዙሪያ ያለው የኢትዮጵያ ዳያስፖራ ከጫፍ እስከ ጫፍ በመነሳትና በየሲቪክ ማህበሮቻችን በመደራጀት፣ ከፍተኛ የሆነ የዲፕሎማቲክ እንቅስቃሴ አድርገን፣ የጥብቅና ዘመቻዎችን በማደራጀት፣ ዲፕሎማሲያዊ ድጋፍ በመስጠት፣ በተለይም የዩናይትድ ስቴትስ ኮንግረስን፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅትን እና ሌሎች አለም አቀፍ አካላትን ሎቢ በማድረግ ታላላቅ የዲፕሎማሲ ስኬቶችን አስመዝግበናል። በተጨማሪም ከሰላም ደጋፊ “ፓን-አፍሪካን” አጋሮቻችን ጋር በመተባበርና፤ ትግላችንን በማቀናጀት የ“#በቃ” (#NOMORE) ሰፊና ሕዝባዊ ንቅናቄ በዓለም ዙሪያ የህወሓትን የሀሰት ፕሮፓጋንዳ በማክሸፍ፤ የኢትዮጵያ ችግር የአፍሪካ ሁሉ ችግሩ ሆኖ እንዲታይ፤ የምዕራብ አለም ዜጎች አብረውን እንዲቆሙና ድምጽ እንዲሆኑ ታላቅ አስተዋጽኦ አድርገናል። በአምስት አህጉራትና ከሰላሳ ሁለት በላይ አገሮች ውስጥ ታሪካዊ ታላላቅ ሰለማዊ ሰልፎችን በማድረግ፣ ኢትዮጵያ በአለም አደባባይ የተነፈገችውን ትኩረት ድምጽ ልንሆንላት ችለናል።
እኛ፥ ከእዚህ ደብዳቤ በታች የፈረምነው ዓለም አቀፍ የዳያስፖራ ድርጅቶች፣ ግንባር ቀደም መሪ በመሆን ሌትና ቀን ያለእረፍት በመታገል፤ ለሀገራችን ኢትዮጵያ በምንችለው ሁሉ አቅም፣ በእውቀት፣ በሞያ፣ በገንዘብ፣ በጉልበትና በጊዜ ከፍተኛ መስዋእትነትን የከፈልን ነን። በከፍተኛ የሀገር ፍቅር ስሜትም ተነሳስተን ይህን አስተዋጽኦ ለማበርከት በመቻላችን ልዩ ኩራት ይሰማናል። ይሁን እንጂ፣ ይህን ስናደርግ የእርስዎን “የብልጽግና ፓርቲ” አጠራጣሪ ታሪክ ማለትም፤ የህወሓትን (ኢህአዴግ) ጠባብ የብሄር፣ የዘረኝነትና ከፋፋይ የፖለቲካ መስመርና፣ በሕዝብ ላይ የፈጸመውን ግፍና ደባ ለአፍታም ቢሆን በመርሳት አይደለም። ያንን ሁሉ በሆዳችን ይዘን፤ ሀገራችን ኢትዮጵያን ወደ ላይ ከፍ በማድረግ፤ ለሕዝባችን ነጻነት፣ ፍትሕ፣ እኩልነትና ብልጽግና የሰፈነበት ስርአት እንዲገነባ “እናሻግራታለን” ያሉንን ቃል ኪዳን ተስፋ በማድረግና በማመን ነበር ከጎንዎ የቆምነው። ይሄም በብዙዎች ዘንድ መደገፍ የማይገባውን ሥርአት እንደደገፍን አስቆጥሮን ነበር። አሁን እርስዎና መንግሥትዎ በሕዝብ ላይ የሚያደርሱትን በደልና ግፍ ስናስተውል ግን፤ እኛም ከሕዝባችን ጋር አብረን የተከዳን አይነት ስሜትና ቁጭት ነው የሚሰማን።
በሚያሳዝን ሁኔታ፣ ለኢትዮጵያ ሕዝብ ቃል ገብተው ባፈረሱት ቃል ኪዳን የተነሳ፣ በእርስዎ አመራር ላይ ያለን እምነት ከምንጊዜውም በበለጠ አዘቅት ወርዷል። ሀቁ እንደሚያሳየው፣ እርስዎ ከአምስት አመት በላይ በመንግሥት ሥልጣን መሪነት በቆዩባቸው አመታት ውስጥ፣ ሀገራችን ኢትዮጵያ እጅግ በሚዘገንን ሁኔታ ላይ ትገኛለች፤ በሺዎች የሚቆጠሩ ንጹሀን ዜጎች ተጨፍጭፈዋል፤ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ተፈናቅለዋል፤ የሕዝቡ ሰብአዊና ዴሞክራሲያዊ መብቶች ከምንጊዜውም በበለጠ ተጥሰዋል፤ መንግሥት እራሱ ህገ መንግሥቱን አያከብርም፤ የህግ የበላይነትና ተጠያቂነት የሚባሉት በሀገሪቱ ስማቸውም ተረስቷል፤ ሌብነትና  ሙስና እንዲሁም  የኑሮ ውድነት ሕዝቡን አስመርሮታል፤ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ንጹሀን ዜጎች ለረሀብና ለስደት ተጋልጠዋል፤ ችግሩ ተዘርዝሮ አያልቅም!
ከእዚህ በታች ዋና ዋና የሚያሳስቡንን፤ ለሀገራችን ሠላም፣ ለሕዝባችን ደህንነትና ለህልውናዋ የሚያስጨንቁንንና፤ ሌትና ቀን ቁጭት የሚያሳድሩብንን ክስተቶች ለመዘርዘር እንሞክራለን፥
በሚዘገንን ሁኔታ እያየን ያለነውና መግታት ያቃተዎት የሰብአዊ መብቶች ጥሰት  እጅግ አድርጎ ያሳስበናል፤ በእርስዎ አመራር ስር በዘር እየተለየ የሕዝባችን በገፍ መታሰርና መንገላታት፤ በጠራራ ጸሀይ መገደል፤ የመናገር፣ የመጻፍ፣ የመሰብሰብና ሰላማዊ ሰልፍ የማድረግ፤ የማምለክ ነጻነት መገፈፍ፤ በነጻ ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀስ መብቶች ወዘተ መቆም፤ ከባድ የሆኑ በሰው ልጅ ላይ  እየተፈጸሙ ያሉ ወንጀሎች፤ ከመጠን በላይ ብቻ ሳይሆኑ፣ መንግስትዎ እያወቀ መሆናቸው፤
ጋዜጠኞች እና የሰብአዊ መብት ተሟጋቾችን ጨምሮ የተቃውሞ ድምጽ ያሰሙ ወይም የአገዛዙን ፖሊሲዎች የሚቃወሙ ታስረዋል። በመላው ኢትዮጵያ በግፍ የታሰሩ የህሊና እስረኞች ቁጥር፣ ከመብዛታችው የተነሳ፣ ይህ ነው ለማለት አዳጋች ነው፤
ሕዝቡ በእርስዎ አስተዳደር ላይ ተስፋ እየቆረጠ ነው፤ ሌላዉ ቀርቶ፣ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትን ወደ ጎን በመተው፣ ተቃዋሚ የሚባሉትን ጥቂት ድምጾች፥ ለስሙ እንኳን ሳያዳምጡ በአንገብጋቢ የሀገር ጉዳዮች ላይ እንደፈለጉ በግልዎ ውሳኔ ይሰጣሉ፤
ህወሓት የፕሪቶሪያን የሰላም ስምምነት በግልፅ እየጣሰ፣ የእርስዎ አስተዳደር የህወኃትን ወንጀለኛ ድርጅት መልሶ ለማቋቋም በትጋት ሲሰራ በከፍተኛ ስጋት እየተመለከትን ነው፤
ይህን ሁሉ ዓመት በኦሮሚያ ክልል በሰላማዊ ሕዝብ፤ በተለይም ዘራቸው እየተለየ በአማራ ዜጎች ላይ የሚደርሰውን አስከፊ ጭፍጨፋ ለማስቆም ባለመቻልዎ፤ እንዲሁም የኦሮሞ ብልጽግና አባላትና የመንግስት ባለሥልጣኖች በሀገሪቱ ፓርላማ “አሸባሪ” ተብሎ ከተሰየመው የ“ኦነግ ሠራዊት” ጋር መነካካታቸውን እያወቁ ባለማስቆምዎ እጅጉን አዝነናል፤
በሰው ልጆች ላይ አሰቃቂ ወንጀል ሲፈጸም፤ በደቦ ድብደባና ግድያ፤ ሴቶችን እናቶችንና ህጻኖችን መድፈር፤ ከእርጉዞች ጽንስ በሳንጃ እያወጡ ማረድ፤ ወንዶችን አንገታቸውን መቅላት፣በአንድ ቤት ውስጥ በማጎር በእሳት በማጋየትና ሌሎችንም ለጆሮ የሚዘገንኑ ወንጀሎች እያዩ፣ ይህን ያህል ዓመት ድንግጥ ብለው በማዘን፤ የመንግሥትዎን ኃይል ከሕዝብ ጋር አስተባብሮ በጋራ በመጠቀም እንዳይቀጥል ማስቆም አለመቻልዎ፤
በተለይም በአማራ ኢትዮጵያውያንና የኦርቶዶክስ እምነት ተከታዮች፤ እንዲሁም በሌሎች ብሄረሰቦች በጉራጌና ጌዲኦ፣ እንዲሁም በሻሸመኔ ኗሪዎችና በመሳሰሉት የደረሰውን ግፍ አለማስቆምዎና፤ ወንጀለኞችንም ለፍርድ ማቅረብ አለመቻልዎ፤
በምእራብ ኦሮሚያ (ወለጋ) በተለይ በደርግ ዘመን፣ በ1970ዎቹ  በተደረገው የድርቅ ሰፈራ ከሰሜን የመጡ አማራ ዜጎች ላይ እየተካሄደ ባለው የዘር ማጥፋት ወንጀልና ጭፍጨፋ ማንንም በህግ ተጠያቂ በማያደርግ መልኩ አሁንም እየቀጠለ በመሆኑ፤
በተለይም የክልሉ አስተዳደርና ፖሊስ፤ ወንጀለኞች ይህን የተደራጀ የዘር-ማጥፋት ግፍ ሲፈጽሙ ድንገት እንደተቀሰቀሰ የጎሳ ግጭት አድርጎ፣ አይቶ እንዳላየ ማለፍ፣ ወይንም ለሚያደርጉት ትብብር በኢትዮጵያና በዓለም ዙሪያ ያሉ የሰብአዊ መብት ተሟጋች ኃይሎችን እጅግ አስቆጥቷል፤
ህገ መንግሥቱን በመጣስ፤ የእርስዎ መንግሥት በተደጋጋሚ በኃይማኖት ጣልቃ እየገባና ፖለቲካ እየሰነቀረ፤ ብዙ ጉዳት እያደረሰና የሀገራችንን ሰላምና አንድነት በማናጋት ለህልውናዋም አስጊ እየሆነ በመምጣትና የኃይማኖት አባቶችንም መናቅና ማሰቃየት፤
በተለይ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን የእርስዎ መንግሥት ኢላማ ለመሆኑ፤ በቅርቡ መንግሥት በኃይማኖት ላይ ጣልቃ በመግባቱ ሳቢያ ሲኖዶሱን ለሁለት በመክፈል፣ በሀገሪቱ አንዣቦ የነበረው  አደጋና፤ በሕገወጥ በተሾሙ ጳጳሳት ምክንያት በሻሸመኔ የኦርቶዶክስ ምእመናን ላይ የተደረገው ጭፍጨፋ፤ እንዲሁም በቅርቡ የአድዋን ድልንና የቅዱስ ጊዮርጊስን በዓላት ለማክበር በወጡት ምእመናን ላይ የደረሰው ድብደባና ግድያ፤ በአስለቃሽ ጭስ መታፈን በቂ ምስክሮች ናቸው፤
ገና ውጤቱ ያልታየውንና ስኬቱ የሚያጠራጥረውን “የብሄራዊ ምክክር ኮሚሽን” ከማቋቋም ባለፈ፣ መንግሥትዎ እስካሁን ድረስ በቅንነትና በቆራጥነት ተነሳስቶ፣ በህወሓት-ኢህአዴግ የተመሠረተውንና በብሄር ፖለቲካ ላይ የቆመውን የዘረኝነት ሥርአትና፣ ህገ መንግሥቱን ለማሻሻል ወይም ለመቀየር ይህ ነው የሚባል እርምጃ ሲወስድ አይታይም፤
ከ3.6 ሚሊዮን ዜጎች በላይ ከቀያቸው መፈናቀል፣ ኢትዮጵያን በሀገራቸው-ዉስጥ በተፈናቀሉ ዜጎች ቁጥር ከዓለም አንደኛ አድርጓታል፤
የከተሞች ልማት በሚል ሰበብ፤ በአዲስ አበባ ዙሪያ ለአመታት የኖሩ በሺዎች የሚቆጠሩ ኦሮምኛ የማይናገሩ ዜጎችን፤ ያለምንም ማስጠንቀቂያ በማንነታቸው እየተለዩ ቤታቸውን በሌሊት በላያቸው ላይ በቡልዶዘር እያስፈረሱ፣ ህጻናትን፣ ሴቶችንና አዛውንትን ለረሀብ፤ ለስደትና ለአውሬ ሳይቀር መዳረግ ከፍተኛ የሆነ ኢ-ሰብአዊ ግፍና ወንጀል ነው፤
አስተዳደርዎ ህገ መንግሥቱን ኢ-ፍትሐዊ በሆነና በዘፈቀደ መንገድ እንደሚተገብር በበርካታ ምሳሌዎች ማስረዳት ይቻላል፤ ከእነዚህም በቅርቡ፤ በደቡብ ኢትዮጵያ ለአንድ ብሄረሰብ (ሲዳማ) አዲስ ብሄርን መሰረት ያደረገ ክልል ሲፈጠር፣ በተመሳሳይ መልኩ ለሌሎች ብሄረሰቦች፤ ለምሳሌ እንደ ጉራጌ እና ወላይታ ያሉት ግን መከልከል ብቻ ሳይሆን መብታቸውን ለማስከበር ሰላማዊ ሰልፍ እንኳን እንዳያደርጉና ድምጻቸውን እንዳያሰሙ እየታፈኑ፤ ለእስር ለድብደባና ለእንግልት ተዳርገዋል፤
ሌላው ቀርቶ የመጠጥ ውሀ ለወራት በማጣት ጉዳት ደርሶብናል በሚል ድምጻቸውን ለማሰማት በወልቂጤ ባዶ ጀሪካን በትከሻቸው ይዘው ለሰላማዊ ሰልፍ የወጡትን ንጹሀን ዜጎችና በሻሸመኔ ወደ ቤተ ክርስቲያን ለጸሎት የሄዱትን ዜጎች የጸጥታ ኃይሎች በግፍ ገድለዋል፤ እንደተለመደው ለጥያቄና ለፍርድም አልቀረቡም፤
እርስዎ የሚመሩት መንግሥት፤ ዓለም የሚያደንቃቸውን የሀገራችንን የረዥም ጊዜ ታሪኮችና ቅርሳቅርሶች እንደፈለገው እየበረዘ ደብዛቸዉን ማጥፋት፤ ብሄራዊ አርማዎችን፣ የባህል ተቋሞችንና፣ የጥንት ቅርሶችን ማፍረስ፤ በኅብረ ብሔራዊነት የሚታወቁ ትልልቅ ከተሞችን ወደ አንድ ብሔር የበላይነት መቀየር፣ ከኢትዮጵያዊነት ወደ ዘርና ጎሳ ደረጃ ማውረድን ተያይዞታል፤
ለኢትዮጵያውያን ብቻ ሳይሆን ለአፍሪካ ታላቅ ኩራት የሆነው የአድዋ ድል በዓል እየደረሰበት ያለው ፈተና ለእዚህ ጥሩ ምሳሌ ሊሆን ይችላል፤
አስተዳደርዎ ከመድብለ ባህላዊነት ይልቅ በአንድ የጎሳ የባህል-አብዮት ላይ አተኩሯል። የኢትዮጵያ መዲና እና የአፍሪካ ዲፕሎማሲያዊ ማዕከል የሆነችውን የአዲስ አበባ ባለቤትነት ከአህጉራዊ እና አገራዊ ቦታዎ ዘቅጦ የአንድ ጎሳ የበላይነት ለመውሰድ የሚደረገው ጥረት አሳፋሪ ብቻ ሳይሆን፣ ማለቂያ ወደሌለው ደም መፋሰስና እልቂት ሀገራችንን እንድታመራ እያደረጋት ነው፤
አባቶቻችን ምንም አይነት የዘርና ሀይማኖት፣ የጎጥ ልዩነት ሳያግዳቸው፤ ሀገራቸውን ከጠላት ለማዳን ለነጻነቷ ሲዋደቁና በህይወታቸው መስዋእትነትን ሲከፍሉ፤ የአፍሪካ ሀገራትም ከቅኝ ግዛት ነጻ ለመውጣት ሲታገሉ በኩራት ያነገቡትን አርማ፤ አረንጓዴ ቢጫ ቀይ ህብር የተላበሰውን የኢትዮጵያ ሰንደቅ ዓላማ አታሳዩን እያሉ የመንግሥት ጸጥታ አስከባሪዎች ዜጎችን ሲያስሩና ሲደበድቡ ምንም ሳይባሉ ሲቀሩ፤ አሁን ጭራሽ የአድዋን ድልም በምኒልክ አደባባይ ልታከብሩ አትችሉም መባሉ እጅግ አሳዛኝ የታሪክ ጠባሳ ሆኖአል፤
በየካቲት 23 ቀን 2015 ዓ.ም የአድዋ የድል በዓል በሚከበርበት እለት፤ የመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች ታሪካዊውን የቅዱስ ጊዮርጊስ - የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ግቢ በጉልበት ገፍተው ገብተው፤ በዓሉን በጸሎትና በወረብ በሚያከብሩት ካህናትና ምእመናን ላይ በድንገት አስለቃሽ ጭስ ተኩስ ከፍተው፣ በብዙዎች ላይ ከባድ የመቁሰል ጉዳት ማድረሳቸው፤ በዚህም ዕለት ለበዓሉ የወጡ ንጹሐን ዜጎች በጥይት ተኩሶ በመግደል፣ በጭካኔ እንደ አራዊት በመደብደብ፤ ይህ በሰላማዊ ዜጎች ላይ የተደረገው ግፍ፤ በሀገራችን ኢትዮጵያ ምን ያህል ፍትሕና የህግ የበላይነት እንደጠፋና፤ የፖሊስ አምባገነን አስተዳደር እየገነነ እንደመጣ በግልጽ የሚያሳይ ነው፤
ባለፉት አምስት አመታት፣ በእርስዎና የመንግሥትዎ አገዛዝ ወቅት የሀገራችን ወሰንና ዳር ድንበር በተደጋጋሚ ጊዜ እየተደፈረ ነው። በተለይም በሱዳንና ደቡብ ሱዳን አዋሳኝ ቦታዎች የመንግሥትና የሌሎች ኃይሎች ከጎረቤት ሀገር እየገቡ፤ ኢትዮጵያውያንን ማጥቃት እየተለመደ ሄዷል። በዚህም በርካታ ዜጎቻችን በየጊዜው ህይወታቸው ያልፋል፤ ንብረታቸው ይዘረፋል፤ ከቀያቸው እንዲፈናቀሉም ይደረጋል፤ የሀገራችን መሬትም እየተቀማ ለባዕድ ሀገራት መጠቀሚያ ሲሆን መንግስትዎ ዝም ብሎ ማየትን መርጧል፤
ልክ ከእርስዎ በፊት እንደነበሩት መንግሥታት፣ የእርስዎም አስተዳደር ለዜጎቹ የምግብ ዋስትና ለማምጣት እስከዛሬ አልቻለም፤ እንደ ተባበሩት መንግሥታት የሰብአዊ እርዳታ ጉዳይ አስተባባሪ ቢሮ (OCHA) መረጃ ከሆነ፣ ከ20 ሚሊዮን በላይ የሚሆኑ ኢትዮጵያውያን በህይወት ለመኖር ዛሬ የምግብ እርዳታ ያስፈልጋቸዋል፤ የቅርቡ በረሀብ ተጎጂዎች ደግሞ በኦሮሚያ ክልል ውስጥ በቦረና የሚኖሩት ኢትዮጵያውያን ናቸው። ይህ ሁሉ ከባድ የረሀብ አደጋ በሀገራችን እያንዣበበ እያለ፤ እርስዎ ግን የአስተዳደርዎን “መልካም ገጽታ” ለመገንባት ሲሉ የስንዴ ምርት ወደ ውጭ ሀገር ለመላክ፣ አንድን ጎሳ በዋስትና ለመሸንገል፣ ሽር ጉድ ይላሉ፤
በመንግስት ውስጥ የተንሰራፋው ሙስና፤ የዋጋ ግሽበት እና ወገንተኝነት እጅግ አሳሳቢ ደረጃ ላይ እየደረሰ ሲሆን፤ የእርስዎ መንግሥት ምን ያህል ማስተዳደር እንዳቃተው ቁልጭ አድርገው ያሳያሉ፤
ለእነዚህና ሌሎች ዘርፈ-ብዙ ተግዳሮቶች ከቀን ወደ ቀን እያደጉ ለመጡ የሀገሪቱ ውስብስብ ችግሮች መፍትሄ ለመሻት ቁርጠኝነት ባለማሳየትዎ፤ በተለይም የፌደራልና የኦሮሚያ ክልል የጸጥታና አስተዳደር አካሎች ግፍ ሲፈጽሙ እያዩ እንዳላዩ፤ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ መንገድ ድጋፍ በማሳየትዎ፤ በኢትዮጵያ የስርአት አልበኝነት ባህል እንዲነግስና፤ የህግ የበላይነትና ፍትሕ እንዲጠፉ በሩን ከፍቷል። ለምን እና በማን ስልጣን እንደዚህ አይነት ችግር ያለባቸው ፖሊሲዎች አገሪቱ ተከተለች ለሚለው ጥያቄ፣ ሃላፊነት በእርስዎ ላይ ነው – የሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር፣ የመንግስት ርዕሰ መስተዳድር እና የጦር ኃይሎች ጠቅላይ አዛዥ እርስዎ ስለሆኑ።
አሁንም በቆራጥነትና በቅንነት ተነሳስተው፤ በማስተዋል ወሳኝ የሆኑ መፍትሄዎችን መውሰድና በቶሎ በሥራ ላይ ማዋል ካልቻሉ፤ በዓለም ላይ እራሷን ለማጥፋት የምትጓዝ ብቸኛ ሀገር ኢትዮጵያ ትሆናለች። ያኔ እርስዎና መንግሥትዎ በታሪክ ተወቃሽ ይሆናሉ። ስለዚህ የኢትዮጵያ ዲያስፖራ ድምፅ ለሌለው የኢትዮጵያ ሕዝብ ድምጽ የመሆን ግዴታ አለበት። ለኢትዮጵያ ሕዝብ ቃል የገቡትን ለማክበር፣ የአገዛዝዎ ብልሹ አሰራርን ማስተካከያ እድሉ አሁን ነው።
ይህንን አደገኛ አካሄድ በአስቸኳይ ለመቀየር እና ጥፋቶችን ለማረም፣ ዜጎችን ለመጠበቅ እና ቅሬታዎችን ለመፍታት ቆራጥ የማስተካከያ እርምጃዎች እንዲወስዱ እንጠይቃለን። ዛሬ የመንግሥት መቀጠል ብቻ ሳይሆን፤ የኢትዮጵያ እንደ ሀገር የመቀጠል ህልውና አደጋ ላይ ነው ያለው። አስተዳደርዎ ኢትዮጵያን ከአስገባት ከዚህ አጣብቂኝ ጨለማ ለማውጣት እድሉ በእጅዎ ነው። በሰከነና በእውነት መንፈስ የሚወሰዱ እርምጃዎች ሁሉንም ኢትዮጵያዊ ባለድርሻ አካላት አሳትፎ ሀገራችንን ለማዳን በአስቸኳይ ስራ እንዲጀመር አጥብቀን እናሳስባለን።
ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ልጆቿን ይባርክ!!!
(ማስታወሻ፡- ከላይ የቀረበውን ግልጽ ደብዳቤ ለጠ/ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ ፈርመው የላኩት በአሜሪካ የሚገኙ 15 የኢትዮጵያ የሲቪክና ምሁራን ድርጅቶች ሲሆኑ ብዙዎቹ የጠ/ሚኒስትሩ መንግሥት የሪፎርም አጀንዳ ደጋፊዎች የነበሩ ናቸው፡፡)

 ፍቅር እስከ መቃብር፣… የአገራችን የጥበብ ጉልላት ነው። “የአገራችን” ማለቴ፣ የደራሲውን ተዓምረኛ የጥበብ ብቃት ለመንጠቅና “የጋርዮሽ” ብቃት ለማስመሰል አይደለም። “አለንበት” በሚል ስሜት፣ የክብር ክፍፍልና የኩራት ሽሚያ ለመፍጠርም አይደለም።
የጥበብ አዝመራው፣ ከጥበበኛው ደራሲ የፈለቀ፣ የድንቅ ብቃትና የትጋት ውጤት፣ የተትረፈረፈ በረከት ነው። ክብርም ኩራትም፣ የጥበበኛው ነው።
የሌሎቻችን ፋንታ፣ አስደናቂውን የጥበብ በረከት ማጣጣምና ማመስገን ነው። ደግሞም፣ መታደል ነው። “ፍቅር እስከ መቃብር”ን የመሰለ የጥበብ ስራ፣ በየቀኑና በየዓመቱ ይቅርና፣ በአስር ዓመትም የሚገኝ ቀላል በረከት አይደለም።… ጥበብን የማጣጣም እድል የሚያበረክቱልን ጥበበኞች ይብዙልን እያልን ማመስገን፣ የሁላችንም ሃላፊነትና ችሎታ ነው። ማመስገን ከፈለገ ግን፣ አያቅተንም፣ እንችላለን ማለቴ ነው።
ጥበበኞቹ አድናቆትና አክብሮትም ይገባቸዋል። በጥበብ ስራዎቻቸው ከብረዋልና፣… የዚያኑ ያህል ማክበር ያስፈልጋል። በዚህ ቀና መንገድ ነው፣… የጥበባቸው የመንፈስ ልጅነትን፣ የመንፈስ ወራሽነትንና ተካፋይነትን መላበስ የምንችለው። “የአገራችን” ብለን የመናገር ብቃትንም የምናገኘው።
የጥበብ ማማ ጉልላቱን አይተንና አጣጥመን፣ መንፈሳችንንም አድሰንና አበልጽገን፣ በምስጋናና በአድናቆት ካላከበርን፣ ጉድለቱ ለየራሳችን ነው። የጥበበኞቹን ክብር አይደለም የምናጎድለው። እነሱማ በራሳቸው ድንቅ ስራ ከብረዋል።
የጥበብ ነገሥታትን ካላከበርን፣ በመንፈስ ድህነትና ንፍገት መማሰን ይሆንብናል። አነስ-መለስ ያሉ የጥበብ ባለቤቶችንና የጥበብ ፍሬዎችን የማጣጣምና የማመስገን፣ የማድነቅና የማክበር አቅማችንን እያመከንን ማንነታችንን እናራቁታለን። “ማመስገን፣ ማድነቅና ማክበር ለራስ ነው” የሚባለው ለቀልድ ወይም ለወግ ያህል ብቻ አይደለም።
ደራሲ ሀዲስ ዓለማየሁ፣ ባለቅኔው የትያትር ፀሐፊና ገጣሚ ፀጋዬ ገብረመድህን፣ ዛሬ በዘመናችን ደግሞ ሰዓሊ መዝገቡ ተሰማ፣… በየራሳቸው መስክ መጥቀው የወጡ የጥበብ ብርሃናት ናቸው።
ካበረከቱልን የጥበብ ስራዎቻቸው በተጨማሪ፣ የጥበብ ልሕቀትን የማየት እድል የፈጠሩልን የብቃት አርአያዎች ናቸው። እነዚህን ቁምነገሮች ልብ እንድንል የሚያግዝ አጋጣሚ መፈጠሩ መልካም ነው። ይህን እንደ ምርቃት ልትቆጥሩት ትችላላችሁ። ዋናውና ትልቅ ፀጋ ግን፣ የጥበብ ስራቸው ነው - የሀዲስ ዓለማየሁ ድርሰት።
ድርሰቱን ወደ ቲቪ ድራማ ለመቀየር መታሰቡ መልካም ነው። ታዲያ ድርሰቱን ስናከብር ደራሲውንም እናክብር።


በአንድ ቤተ-መንግሥት ውስጥ ሁልጊዜ የሚከበር አንድ ስነስርዓት ነበር። ማታ እራት ተበልቶ ገበታው ከፍ ካለ በኋላ ወይን ጠጅ በማብረጃ ይቀርብና ወግ ይወጋል። ጨዋታ ይመጣል። ቤተሰባዊ ውይይት ይደራል። ታዲያ ሁሌ ልዑሉ ከንጉሱ ጋር የሚያደርገው ክርክር አለ። ንጉሱ አስፈሪና ጨካኝ ናቸው ብሎ የሚያምነው ልዑል፤ አስተዳደራቸው ግፈኛ መሆኑን ሊያስረዳ ሁሌ ይሟገታቸዋል።
ልዑል፡- እኔ መንግስቴን በምወርስበት ጊዜ አስተዳደሬ ከርስዎ የተለየ ነው የሚሆነው።
ንጉሥ፡- እንዴት?
ልዑል፡- በምንም ዓይነት ህዝቡን አልቆጣም። አላስፈራራም። አልጫንም። “ይሄን ካላደረክ” እያልኩ አዋጅ አላውጅም። ጥቁር ወተት፣ ነጭ ኑግ አምጣ እያልኩ አላስጨንቀውም።
ንጉሥ፡- ተው የዋዛ ህዝብ አይደለም ይሄ! እንደተልባ ሙልጭልጭ ነው። በእግርህ የረገጥከውን ምንጣፍ አንተ ሳትሰማ ከእግርህ ስር ስቦ ሊያወጣ የሚሞክር ምስጥ ህዝብ ነው።
ልዑል፡- ቢሆንም ቢቸግረው እንጂ ከመሬት ተነስቶ አልታዘዝም ብሎ አያምጽም።
ንጉሥ፡- እንግዲህ እኛ በእድሜያችን ያየነው ህዝብ፤ ስትተኛለት አልጋ የሚገለብጥ፣ ስትተኛበት የሚጎረብጥ፣ ዝም ካለ የሚያስፈራ፣ ከተናገረ የሚሸነቁጥ ነው። ሼክስፒር “ዘውድ የጫነች ጭንቅላት ወዮላት!” ያለው በግምት እንዳይመስልህ። በትክክል ተገንዝቦ ነው።
ልዑል፡- ምንም ይባል ምንም እኔ በበኩሌ ህዝብ ይሰቃይ ይረገጥ አልልም። እኛ እጅግ ጥቂት ነን። እኛ አልጋ ይጎረብጠናል ብለን ህዝቡ እንዲጉላላ ማድረግ በጭራሽ ልክ አይደለም።
 እንዲህ እንዲህ ያለ ሙግት በየቀኑ ይሟገታሉ። ብዙ ታሪክ እያነሱ ያወሳሉ። ቆይ ንጉሡ እለተ-ሞታቸው ደረሰና ሙሉ መንግስታቸውን ለልዑሉ ባርከውለት አለፉ። ስርዓተ ንግሱ ተፈጸመና የልዑሉ ዘመነ መንግስት ጀመረ። አዲሱን ንጉስ ህዝቡ ጥያቄ መጠየቅ ጀመረ። እንቅልፍ ነሳው። አንዱን ጥያቄ ሲመልስ ሌላ ይቀጥላል። አንድ አዋጅ አውጆ “አሁን አረፍኩ! ህዝቡ ፈነጠዘ!” ሲል ወዲያው ቤተመንግስቱ ደጃፍ ታድሞ አቤት ሲል ያገኘዋል። መንፈቅ ሳይሞላ ተማረረ።
ባለሟሎቹን ሰብስቦ፡- “በሉ እንግዲህ በአገሩ በጠቅላላ ያለውን ማረሻ ነሽ፣ ማጭድ ነሽ፣ መዶሻ ነሽ፣ የወዳደቀ ብረታ ብረት ሁሉ አንድም ሳይቀር ሰብስቡና አምጡልኝ” አለ። ባለሟሎቹ እንደታዘዙት አደረጉ። በአገሩ ያለውን ብረታ ብረት አንዲት ብሎን ሳትቀር አመጡ።
ንጉሡም፡- “በሉ ይህን ሁሉ ብረት ቀጥቅጣችሁ፣ አቅልጣችሁ የእጅ ሰንሰለትና የእግር ብረት ስሩ” አላቸው።
ባለሟሎቹም፡- “ ምነው ንጉሥ ሆይ ህዝቡን ላያስቀይሙ፣ ላያጉላሉ፣ ላያስሩ፣ ላይገርፉ ቃል ገብተው ነበር እኮ?! ለምን ቃልዎን ይሽራሉ?” ብለው ጠየቁት።
ንጉሡም፡- “እሱ መሬት ሆኜ ያሰብኩት ነው። አልጋው ላይ ስወጣ የተገላቢጦሽ ሆኖ ነው ያገኘሁት። አባቴ እንደዚያ እረግጦ እየገዛ ያቃተውን ህዝብ እኔ ባዶ እጄን አልችለውም። ከብት ህዝብ ነው!! ፈርገጥ ሲል ጥፍር አርጎ ማሰር፣ እምቧ ሲል እምሽክ፤ ማድረግ ያስፈልጋል!” አለ በኃይለ-ቃል።
አንዱ ባለሟልም፤
“ኧረ ንጉሥ ሆይ፤ መክረን ዘክረን ለጥያቄው መልስ ብንሰጥ ይሻላል”
ንጉሱም፤ “ህዝብ እንደ ብዛቱም ሁሉ እንቆቅልሹ አያልቅም። ጥያቄውም አያቆምም። ስለዚህ ትዕዛዜን ፈጽሙ። እናንተም እምቢ ካላችሁ ያው ህዝብ እንደምትሆኑ አትርሱ!” ብሎ አሰናበታቸው።
***
በንግስም ይምጣ በውርስ፣ በምርጫም ይምጣ በርግጫ፣ በትግልም ይገኝ በእድል፣ ስልጣን ከፍተኛ ጭንቀት አለበት። ስልጣን፤ ላወቀው፣ በጥንቃቄ ተዘጋጅቶ፣ ተደጋግፎ፣ አስቦና አስልቶ የሚረከቡት እንጂ ወይ ተሻምተው፣ ወይ አድፍጠው አልያም አድብተው በጮሌነት የሚመነትፉት ከካርቶን የተሰራ ዘውድ አይደለም።
በተለይም እንደ ኢትዮጵያ ምስቅልቅል የአስተሳሰብና  የአስተዳደር ችግር እንዲሁም ያልተፈቱ አንቆቅልሾች መነሀሪያ በሆነች ሀገር ውስጥ ስልጣን ከጽድቁ ጭንቁ ይበዛል!! እጅግ በተለይም ደግሞ አልጋው አድሮ እንደሚጎረብጥ፤ ወንበሩ ሲሞቅ እንደሚቆረቁር፣ የህዝብ አይን ሲፈጥ  እንደሚቆጠቁጥ፣ ከታሪክ ፍርድ እንደማይመለጥ ልብ ሳይሉ፤ የየግለሰብና የድርጅቶችን እኩይ አላማ ለማሳካትና የየራስ እንጀራን ለመጋገር መሯሯጥ የኋላ ኋላ ከላይ እንደተጠቀሰው ልዑል “እግር ብረት ስሩልኝ! ወደማለት ማምራቱ አይቀርም። ቃልን ለመጠበቅ ቃል የሚገቡበትን ጉዳይ በቅጡ ማወቅና ለራስም ሆነ ለህዝብ ታማኝ መሆንን ይጠይቃል። ሰዎች ወንበር በተለዋወጡ፣ የየራሳቸውን ቄጤማ በቆረጡና በጎዘጎዙ ቁጥር የተሻለ አስተዳደርና የተባ ራዕይ መጠበቅ አይቻልም። ማንንም ቢሆን ከአባይ ድልድይ ጠባቂነት አንስተው የአዋሽ ድልድይ ጠባቂነት ቢሾሙት ለውጥ የለውም። “አሮጌ ጠላ በአዲስ ጋን” ከመጥለቅ የተለየ ነገር አይሆንምና። አሮጌ ጋን ውስጥ አዲስ ጠላ ለመጥመቅ ካሻን ደግሞ አሮጌውና የኮመጠጠው ጠላም ሆነ ቅራሪ ከአሮጌው ጋን ውስጥ መፍሰስ አለበት። ከዛ ጋኑ መታጠብ፣ በጭንቅላቱ ተደፍቶም በወይራ መታጠን ይኖርበታል። ከዚያ የማያጋድልበት ጠንካራ ቦታ መቆም አለበት። ከዚያ ደግሞ የጥሩ ባለሙያ እጅ  መገኘት ይኖርበታል ወዘተ…። ይሄ ሁሉ ለህዝብ ሲባል ነው። ጥዋው የህዝብ እንጂ የሹሙ ስላልሆነ ነዋ!!
ለክልልና ለፌደራል ምክር ቤት የተመረጡ፣ ነገም ለየወረዳውና ለየቀበሌው በሚደረገው ምርጫ ከፖለቲካ ፓርቲዎችም ሆነ ከግል ሊመረጡ የተዘጋጁ ሁሉ ጥዋውን ለመንጠቅ ሳይሆን ለመረከብ፣ ተረክበውም በአግባቡ ማህበራቸውን ለመደገስ ንጹህ ልቦና ሊኖራቸው ይገባል። አለበለዚያ “ሳያውቁ በስህተት አውቀው በድፍረት ለሚሰሩት ስህተት” እነሱ እንጂ ሌላ ማን ተጠያቂ ይሆናል?
“ሸክላ ሲሰበር ገል ይሆናል። መኳንንትም ሲሻሩ ህዝብ ናቸው!” እንዲል አንጋረ ፈላስፋ፤ እንደ ሸክላ ላለመፈረካከስ የሕዝብን አደራ አለመብላት ብልህነትም ግዴታም ነው።



Page 1 of 636