Administrator

Administrator

በመዲናዋ አዲስ አበባ የውጪ ጣልቃገብነትን የሚያወግዝ ህዝባዊ ሰልፍ ዛሬ ከጠዋቱ 12፡00 ጀምሮ የሚካሄድ ሲሆን በዚህ ሰልፍ ላይ ከ1 ሚሊዮን በላይ ህዝብ ይሳተፋል ብሎ እንደሚጠበቅ ተገልጿል። ህዝባዊ ሰልፉ  በዋናነት መንግስት የኢትዮጵያን ግዛታዊ አንድትና ሉአላዊነት ለማስከበር በሚያደርገው የመከላከል እርምጃ የውጭ ጣልቃ ገብነትን፣ ኢትዮጵያን ሉአላዊነት የሚጋፉ፣ ሀገራትንና የኢትዮጵያን ገፅታ  ለማበላሸት እንቅልፍ አጥተው የሚሰሩ የውጭ ሚዲያዎችን የሚያወግዝ ነው ተብሏል።
ይህ የሀገርን አንድነትና ክብር ለመጠበቅና የውጭ ጣልቃ ገብነትን በሚያዎግዘው ህዝባዊ ሰልፍ ላይ ህዝቡ በነቂስ ወጥቶ እንዲሳተፍ የአዲስ አበባ የሙያና ሲቪክ ማህበራት እዲሁም የፖለቲካ ፓርዎች የጋራ ምክር ቤት በጋራ በሰጡት መግለጫ ጥሪ አቅርበዋል።

የስኳር ምርት ላይ ለውጥ ማምጣት ባይቻልም፣ የስንዴ እርሻ እንደተሻሻለ ተገልጿል።
የስንዴ ምርት ላይ እየታየ የመጣው እድገት በምሳሌነት የሚጠቀስ ነው ብለዋል- የአፍሪካ ልማት ባንክ ፕሬዚዳንት።
በዓመት ለውጭ ዕዳ 2 ቢሊዮን ዶላር መንግስት ከፍሏል (ለወለድና ለዋናው)።
እንዳለፉት ዓመታት ባለፈው ዓመትም፣ 500 ሚሊዮን (ግማሽ ቢሊዮን) ዶላሩ ለወለድ የተከፈለ ነው።
እስከ ዛሬ ባልታየ ሁኔታ፣ የመንግስት የውጭ እዳ፣ በግማሽ ቢሊዮን ዶላር ገደማ ቀንሷል።
ነገር ግን፣ ከዚህ ጎን ለጎን ከፍተኛ የዶላር እጥረት ተፈጥሯል።

የመንግስት የውጭ እዳ ሪፖርት ላይ እንደተገለጸው፤ ባለፈው ዓመት ከውጭ አገራትና ከዓለማቀፍ ተቋማት የተገኘው ብድር፣ ከ800 ሚሊዮን ዶላር በታች ነው።
ቀደም ባሉት ዓመታት፣ መንግስት በየዓመቱ ከ2 ቢሊዮን ዶላር የሚበልጥ ብድር ያገኝ ነበር።
በየዓመቱ ለእዳና ለወለድ ከሚያወጣው ወጪ ጋር የተቀራረበ ወይም የበለጠ ብድር ሲያገኝ የነበረው የኢትዮጵያ መንግስት፣ ባለፈው ዓመት በብድር እጥረት ክፉኛ ተቸግሯል። የዕዳ ክምችቱን ለማርገብ ብቻ ሳይሆን፣ ለመቀነስም ችሏል።
ነገር ግን፣ በዶላር እጥረትም ክፉኛ ተወጥሯል። ከሰሞኑም በበርካታ ቁሳቁሶች ላይ፣  የውጭ ንግድ ጊዜዊ እገዳ ጥሏል።
ከዚህ ጎን ለጎን፣ ከውጭ የሚመጣ ብድርና ወደ አገር የሚገባ ሸቀጥ ሲቀንስ፣ የገበያ እጥረት ላይ የራሱን ተፅዕኖ ማሳደሩ አልቀረም።
የኮረና ወረርሽኝ፣ የአገር አለመረጋጋትና ግጭት፣ ከዚያም የጦርነት ምስቅልቅልተጨምሮበት፣… የራሺያና ዩክሬን ግጭትም ከአለማቀፍ የኢኮኖሚ ቀውስ ጋር ተደማምሮ፣ የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ብዙ ፈተናዎች ተደራርበውበታል።
ትልቁ ፈተናውም፣ የዋጋ ንረትና የኑሮ ውድነት ሆኗል።
በ2010 ዓመተ ምህረት፣ 100 ብር ገደማ የሚፈጅ ሸቀጥ፣ ዛሬ በአማካይ ከ300 ብር በላይ ዋጋው እንደናረ የማዕከላዊ ስታትስቲክስ ባለስልጣን ወርሃዊ መረጃዎች ይገልጻሉ።
ከቅርብ ወራት ወዲህ፣ የዋጋ ንረቱ ባይቀንስም፣ የንረቱ ግልቢያ የመርገብ ምልክት ያሳያል።
እንዲያም ሆኖ ዓመታዊው  የዋጋ ንረት፣ አሁንም 30 በመቶ ገደማ ላይ እንደሆነ የመስከረም ወር ሪፖርት ያመለክታል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ የዶላር እጥረትንና የዋጋ ንረትን ለማቃለል፣ የአገር ምርትን ማሳደግና የኤክስፖርት እድሎችን ማሻሻል እንደሚያስፈልግ የአፍሪካ ኢንቨስትመንት ባንክ ጠቅሷል።
የስኳር ምርት ለውጥ ባይታይበትም፣ የስንዴ ምርት ግን ለኤክስፖርት ሊተርፍ ይችላል ብለዋል።

በአፍሪካ ህብረት አደራዳሪነት በደቡብ አፍሪካ ይደረጋል የተባለው የሰላም ድርድር የፊታችን ሰኞ ጥቅምት 14/2015 ዓ.ም ይካሄዳል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተገልጿል፡፡
የአፍሪካ ህብረት ኮሚሽን የሰላም ድርድሩ በሚመጣው ሰኞ በጁአንስበርግ እንዲደረግ ያቀረበውን ጥያቄ ሁለቱም ወገኖች ተቀብለውታል፡፡
የጠቅላይ ሚኒስትሩ የደህንነት አማካሪ አማባሳደር ሬድዋን ሁሴን መንግስት ለሰላም ድርድር ከህብረቱ ኮሚሽን ጥሪ እንደደረሰው አመልክተው በመንግስት በኩል በድርድሩ ለመሳተፍ ዝግጁ መሆኑን ተናግረዋል። የህወሐቱ ቃለ-አቀባይ አቶ ጌታቸው ረዳ በበኩላቸው የአፍሪካ ህብረት በሚመራው የሰላም ድርድር ሂደት ላይ ለመሳተፍ ዝግጁ መሆናቸውን ቀደም ሲል ማሳወቃቸውን ጠቅሰው አሁንም በተጠቀሰው ጊዜ ለድርድሩ ወደ ጁአንስበርግ ለማቅናት ዝግጁ ነን ብለዋል፡፡
የጠቅላይ ሚኒስትሩ የደህንነት አማካሪ አምባሳደር ሬድዋን ሁሴን መንግስት እየወሰደ ባለው የመከላከል እርምጃ ሳቢያ ከተለያዩ አካላት በቀረበበት የተሳሳተ ክስ ማዘናቸውን ገልፀው በሰላም ድርድሩ ላይ ለመሳተፍ ቁርጠኝነታችንን በድጋሚ እናረጋግጣለን ብለዋል፡፡
በመጪው ሰኞ በጁአንስበርግ ሊደረግ በታሰበው የሰላም ድርድር አሸማጋይ ይሆናሉ ከተባሉ 3 አፍሪካውያን አንዱ የሆኑት የኬንያው የቀድሞ ፕሬዝዳንት ኡሁሩ ኬንያታ ከድርድሩ እራሳቸውን ማግለላቸውን እንዳገለገሉ ይታወሳል፡፡  


- ንግድ ባንክ ከቀጣይ ሳምንት ጀምሮ በሽሬ ከተማ አገልግሎት መስጠት ይጀምራል።
- ከሁለት ዓመታት በላይ ተዘግተው የቆዩት ጎንደርን ከሽሬና ወሎን ከመቀሌ የሚያገናኙ መንገዶች በቅርቡ ይከፈታሉ ተብሏል


  መንግስት በተቆጣጠራቸው የትግራይ ክልል ከተሞች ውስጥ ለሚኖሩ ዜጎች ሰብአዊ እርዳታን መስጠት ሊጀምር ነው። ወልዲያ፣ ቆቦ፣ አላማጣና ሽሬ ሰብአዊ እርዳታው እንዲደርስ እየተደረገ ነው።
የሰብአዊ እርዳታውን በተሻለ ሁኔታ ለማዳረስ በሚያስችሉ መንገዶች ሁሉ ለመጠቀም ዝግጅት እየተደረገ ሲሆን የሽሬ አውሮፕላን ማረፊያ ዕርዳታውን ለማድረስ አገልግሎት እንዲሰጥ ይደርጋል ተብሏል።
ከህውሓት አስተዳደር ነፃ በወጡ የትግራይ ክልል ከተሞች መንግስት መዋቅሩን መልሶ እያደራጀ መሆኑንና በቅርብ ቀናት ውስጥም የሰብአዊ እርዳታ መስጠት እንደሚጀመር ከውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቢሮ የተገኘው መረጃ ያመለክታል።
የሰብአዊ እርዳታውን በተገቢው መንገድ ለማዳረስ ከጠቅላይ ሚኒስትር ጽ/ቤት፣  ከውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ከብሔራዊ መረጃ ደህንነት አገልግሎት ከአገር መከላከያ ሠራዊት፣ ከፌደራል ፖሊስ ከኢትዮያ አደጋ ስጋት አመራር ኮሚሽን የተውጣጣ ቡድን መቋቋሙንና ሰብአዊ እርዳታ የሚደርስባቸውን መንገዶች እያስፋፋ መሆኑን መንግስት ኮሚዩኒኬሽን አገልግሎት ሰሞኑን መግለፁ ይታወሳል።
በሰሜን ጎንደር በኩል ወደ ሽሬ የሚወስደውንና ጎንደርን ከመቀሌ የሚያገናኘውን እንዲሁም ከኮምቦልቻ ደሴ ወልዲያ ቆቦ አላማጣ  ያለውን መንገድ ለመክፈት እየሰራ መሆኑን መንግስት አስታውቋል።
ከህውሓት ሃይሎች ነፃ በወጡ የትግራይ ክልል ከተሞች ውስጥ መሰረታዊ አገልግሎት የሚሰጡባቸው ተቋማትን የማደራጀትና ወደ ስራ እንዲገቡ የማድረጉ ተግባር እየተከናወነ ሲሆን  የኢትዮጵያ ንግድ ባንክ በሽሬ ከተማ ውስጥ የሚሰጠውን አገልግሎት በመጪው ሳምንት ይጀምራል ተብሎ እንደሚጠበቅ ታውቋል። በተያያዘ ዜና የተባሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ፀሐፊ አንቶኒዮ ጉተሬዝ ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ አለማቀፉ ማህበረሰብ ለሲቪሎች የሰብአዊ እርዳታ የሚሰጥበትን ሁኔታ ማመቻቸት እንደሚገባቸው ጠቁመው በትግራይ  ክልል እየተካሄደ ያለው ጦርነት በአስቸኳይ እንዲቆምና የነፍስ አድን ሰብአዊ እርዳታ ለማድረስ የሚቻልበት መንገድ እንዲመቻች ጠይቀዋል፡

በብሄራዊ ባንክ ደንብና መመሪያ መሰረት በስድስት አደራጆች የተቋቋመው “አኩፋዳ” ማይክሮ ፋናንስ ተቋም ዛሬ ረፋድ ላይ ዋና መስሪያ ቤቱ በሚገኝበት ደብረ ብርሃን ከተማ በይፋ ስራ ይጀምራል። ተቋሙ ከ1 ሺ 886 ባለአክስዮኖች በሰበሰበው 21 ሚሊዮን የተከፈለና 33 ሚሊዮን የተፈረመ ካፒታል መቋቋሙን አደራጆቹ በሳምንቱ አጋማሽ በስራ አምባ ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ አስታውቀዋል።
አኩፋዳ ማይክሮ ፋይናንስ ሀገራዊ ባህልና እሴቶችን የማይንዱ ኢንቨስትመንቶችን ለመደገፍ፣ የስራ ዕድል ለመፍጠር፣ የቢዝነስ ክህሎት ሥልጠናዎችን ለመስጠትና የቁጠባና ብድር አገልግሎትን ለማሳደግ አልሞ የተነሳ ተቋም መመሆኑን የገለፁት ሃላፊዎቹ በተለይም የባንክ አገልግሎት ተጠቃሚ መሆን የማይችሉና በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙትን የማህረተሰብ ክፍሎች በተመጣጣኝ ወለድ የብድር አገልግሎት ለማቅረብ አይነተኛ ሚና ይጫወታል ብለዋል- ሃላፊዎቹ።
በአሁኑ ወቅት በሀገራችን እየተከሰተ ያለውን የኑሮ ውድነትና የዋጋ ንረት መቋቋም ያቃታቸውና ልዩ ትኩረት የሚሹ የህብረተሰብ ክፍሎች ባላቸው አቅም አማራጭ የስራ መስኮችን እንዲመለከቱ ለማስቻል ከሌሎች አቻ ተቋማት አንፃር በዝቅተኛ ወለድ ብድር ለማቅረብ መዘጋጀቱንም የተቋሙ ሃላፊዎች ጨምረው ገልጸዋል።
“ስኬትን በተግባር” የሚል መሪ ቃል ይዞ የተነሳው አኩፋዳ ማይክሮ ፋይናንስ በሁሉም የሀገሪቱ ክፍል ቅርንጫፍ የሚከፍት ሲሆን በዚህ ዓመት መጨረሻ እስከ ሰኔ 30 የቅርንጫፎቹን ብዛት 50 የማድረስ እቅድ ያለው ሲሆን በቀጣዮቹ 3 ዓመታት ተቋሙ በሀገሪቱ ካሉ የግል የማይክሮ ፋይናንስ ተቋማት መካከል አንዱና ተቀዳሚው ሆኖ እንዲገኝ በትጋት እንደሚሰሩም ሃላፊዎቹ አብራርተዋል፡፤
ተቋሙ ከሌሎች የማይክሮ ፋይናንስ ተቋማት እለይባቸዋለሁ ያላቸውን አሰራሮች በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ ያብራራ ሲሆን፣ ከነዚህም መካከል ወጣቶችንና ሴቶችን ተጠቃሚ ማድረግ፣ በዝቅተኛ ወለድ መጠን ብድር ማቅረብ፣ የፋይናንስ ተቋማት አገልግሎት ያልደረሰባቸውን የገጠር ክፍሎች ተደራሽ ማድረግ፣ “የቆሎ ተማሪ” የተሰኘ የቁጠባና ብድር አገልግሎት መስጠት፣ የፈጠራና ቱሪዝም ስራዎችን በፋይናንስ በመደገፍ ዘርፎቹ ሚናቸውን እንዲወጡ መስራትና ሌሎችም ይገኙበታል።
አኩፋዳ ማይክሮ ፋይናንስ ዋና መስሪያ ቤቱን ከአዲስ አበባ ውጪ ያደረገ የመጀመሪያው ተቋም ነው የተባለ ሲሆን ይሄም ከባለአክስዮኖቹ አብዛኞቹ በደብረ ብርሃን ስለሚገኙ መሆኑን ሃላፊዎቹ ገልጸዋል። ዛሬ  በይፋ ስራውን በሚጀምርበት ጊዜ የመንግስት የሥራ ሃላፊዎች፣ የግልና የመንግስት የማይክሮ ፋይናንስ ተቋማት ሃላፊዎች፣ ባለአክስዮኖችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ይታደማሉም ተብሏል።

ኔዘርላንድ በብሄራዊ ደረጃ ለሁለተኛ ጊዜ በአውደ ርዕዩ ትሳተፋለች

በኢትዮጵያ የንግድ ትርኢት በማዘጋጀት ቀዳሚ የሆነው “ፕራና ኢቨንትስ” መቀመጫውን ሱዳን ካደረገው አጋሩ “ኤክስፓ ቲም” ጋር ትብብር በየዓመቱ የሚያዘጋጀው  11ኛው የዶሮ ኤክስፖ (Ethiopex) እና ሰባተኛው የአፍሪካ የእንስሳት ሀብት ጉባኤ (ALEC) የፊታችን ሀሙስ ጥቅምት 17 ቀን 2015 ዓ.ም ረፋድ ላይ በኢትዮጵያ ስካይላይት ሆቴል ይከፈታል።
አዘጋጆቹ በሳምንቱ አጋማሽ ላይ በስካይላይት ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳስታወቁት በኤክስፖው የዶሮና የእንስሳት ሀብት ቴክኖሎጂ፣ ግብአትና መፍትሄዎች በስፋት የሚቃኝበትን ይህንን ጉባኤ  ከጥቅምት 17-19 ለሶስት ቀን ያካሂዳሉ ተብሏል።
እነዚህ ሁነቶች በወተት፣ በዶሮና የስጋ እሴት ሰንሰለቶች ልማት ላይ የገበያ ትስስር በመፍጠር፣ አዳዲስ ቴክኖሎጂዎችን በማስተዋወቅ፣ የእውቀት ሽግግርን በማምጣት፣ የኢንቨስትመንት ዕድሎችን በማስተዋወቅና የዘርፉ ዋና ዋና ተግዳሮቶች ላይ በመምከር የዘርፉን ምርታማነት ለማፋጠንና ለማሳደግ ጥሩ አጋጣሚን እንደሚፈጥሩ የሁነቶቹ አዘጋጅ የፕራና ኢቨንትስ ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ነብዩ ለማ አብራርተዋል።
በዘንድሮ የዶሮ ኤክሰፖና የእንስሳት ሀብት ጉባኤና አውደ ርዕይ ላይ ኔዘርላንድስ በብሔራዊ ደረጃ ተሳትፎ እንደምታደርግ የተገለጸ ሲሆን፣ ከኔዘርላንድ በተጨማሪም ከ10 ሀገራት ማለትም ከኢትዮጵያ፣ ፈረንሳይ፣ ጀርመን ሃንጋሪ፣ ህንድ፣ ኬንያ፣ ስኮትላንድ፣ ቱርክና ዩናይትድስቴትስ የተውጣጡ ከ70 በላይ ኩባንያዎች እንደሚሳተፉም ተገልጿል። አውደ ርዕዩንና ጉባኤውን ከመላው ኢትዮጵያና ከጎረቤት ሀገራት የሚመጡ ከ4 ሺህ በላይ የዘርፉ የንግድ ባለድርሻ አካላትና ባለሙያዎች የንግድ ግንኙነት ለመፍጠር በዝግጅት ላይ መሆናቸውም ተገልጿል።
ጋዜጣዊ መግለጫው ላይ አንድ እንቁላል ከ13 ብር በላይ እየተሸጠ ባለበት ሀገር የዶሮ ኤክስፖው ምን ፋይዳ ያመጣል በሚል ከጋዜጠኞች ለተነሳው ጥያቄ በተለያዩ ምክንያቶች የእንስሳት በተለይም የዶሮ መኖ በመወደዱ የእንቁላል ዋጋ መወደዱን የገለጹት የኢትዮጵያ  የዶሮ አርቢዎች ማህበር ፕሬዚዳንት አቶ ኤርሚያስ ዓለማየሁ ምርትና ምርታማነትን በማሻሻል የዶሮን ሀብት ማሳደግና የእንቁላልን ዋጋ መቀነስ ይቻላል ያሉ ሲሆን ለዚህ ደግሞ እንደዚህ አይነት ሁነቶችና መድረኮች መዘጋጀታቸው መፍትሄዎችን ለማፋጠን ይረዳል ብለዋል።
በሶስት ቀኑ አውደርዕይና ጉባኤ ከባለድርሻ አካላት፣ ከመንግስት የስራ ሃላፊዎችና ከፖሊሲ አውጪዎች ጋር የዘርፉ ችግሮች ላይ ትኩረት ያደረጉ ውይይቶችና ንግግሮች እንደሚካሄዱም ታውቋል።

ፐርፐዝ ብላክ ኢትዮጵያ የወቅቱ የማህበረሰቡ አንገብጋቢ ችግሮች ናቸው ባቸውና የኑሮ ውድነቱን አንረውታል ባላቸው ነጥቦች ላይ ከባለ ድርሻ አካላት ጋር ውይይት አካሄደ። ረቡዕ ጥቅምት 9 ቀን 2015 ዓ.ም ለግማሽ ቀን በተካሄደው ውይይት በተለይም የግብርና ውጤቶች ላይ የቫት ታክስ ማሻሻያ ዋና የትኩረት ማዕከል አድርጎ ተወያይቷል።
በዚህም መሰረት ለውይይት የቀረቡት ነጥቦች የግብርና ምርቶች በተለይም ለደሀው ማህበረሰብ የዕለት ከዕለት ጉርሱ በሆኑ ምርቶች ላይ ቫት ማስከፈሉ ተገቢነት አለው ወይ? በአንፃሩ ቫት የተነሳላቸው እንቁልልና ወተት በእርግጥ አሁን ላይ የአብዛኛው ህብረተሰብ ክፍል ፍላጎት ናቸው ወይ? ህጉ ገንዘብ ያለውን ብቻስ ተጠቃሚ አያደርገውም ወይ? የቫት ትርጉሙ እሴት መጨመር ላይ ያተኮረ እስከሆነ ድረስ ከገበሬው በቀጥታ መጥተው ምንም እሴት ሳይጨመርባቸው የሚከፋፈሉ የግብርና ምርቶች ላይ የቫት ታክስ መጨመሩ አግባብነት አለው ወይስ የለውም? ቫት ይጨመር ቢባል እንኳ ተመዝጋቢ ያልሆነ ያለቫት እየሸጠ ተመዝግቦ ግብር የሚከፍለውና የስራ እድል የሚፈጥረው ብቻ ቫት እንዲከፍል መገደዱ በሸማቹና በነጋዴው መካከል ኢ-ፍትሃዊ የሆነ ስርዓትን አይፈጥርም ወይ ሚሉና በአጠቃላይ በኑሮ ውድነቱ ላይ ያተኮሩ የውይይት ሀሳቦች ተነስተዋል።
የፐርፐዝ ብላክ ኢትዮጵያ መስራችና ዋና ሥራ አስፈጻሚ ፍስሃ እሸቱ (ዶ/ር) በበኩላቸው በነዚህ ማህበረሰቡን ባጎበጡ ችግሮች ላይ ውይይት ከተደረገ በኋላ በጉባኤው የሚነሱ ግብአቶችንና የመፍትሄ አቅጣጫዎችን በማቀናጀት ወደ ቀጣይ እርምጃ እንደሚሄዱ አስታውቀዋል።




      አንድ ከተማ ውስጥ የሚኖሩ ሦስት ሌቦች ነበሩ። ሌቦቹን የሚያውቅ ሰው በግልጽ ስለማይናገር ሁሌ የመንደሩ አዛውንቶች ህዝቡን እየሰበሰቡ አውጫጭኝ ያስደርጋሉ። እውነተኞቹ ሌቦች ግን በጭራሽ ሊገኙ አልቻሉም። ሶስቱ ሌቦች ከህዝቡ ጋር እየተቀመጡ ጭራሽ አፋላጊ ሆነዋል።
ነገሩ “የሌባ ዓይነ-ደረቅ መልሶ ልብ ያድርቅ” ዓይነት መሆኑ ነው። አንድ ቀን አንድ አዛውንት ባለቅኔ በዚያው በአውጫጭኙ ላይ ተገኝተው፤ ሲፈሩ ሲቸሩ እጃቸውን አወጡ።
ሰብሳቢው፡-
 “እሺ አባቴ የሚናገሩት አለዎት?”
አዛውንቱ፡-
 “አዎ”
ሰብሳቢው ፡-
“እሺ ምንም ሳይፈሩ በግልጽ ይናገሩ”
አዛውንቱ፡-
“አሳምሬ ነው የምናገረው፤ ያውም ጥንት የቅኔ ተማሪ ቤት አስተማሪዬ የነገሩኝን ነው የምገልጸው።”
ሰብሳቢው፡-
“እኮ ቶሎ ቶሎ ይናገሩ?”
አዛውንቱ፡-
 “ጌቶቼ፤ ይሄ የአውጫጭኝ ስብሰባ እንደ እኔው የሰለቻቸው ባለቅኔ እንዲህ አሉ ይባላል።
ጎበዝ ሌባው ስማ!
ቢተው ይተው
አለዚያ ግን እኛ ጀምበር በሰረቀ ቁጥር፣ በአውጫጭኝ ስብሰባ ስንሰቃይ አንኖርም!” ብለው ደመደሙ።
በዚህ ዓይነት የሰፈሩ ሦስት አደገኛ ሌቦችን ስም ይፋ አደረጉ። እነሱም አቶ ለማ፣ አቶ ቢተው እና አቶ ጀምበር የተባሉ አገር ያሰለቹ ሌቦች መሆናቸው ታወቀና ተመንጥረው ተይዘው ወህኒ ወረዱ።
***
ያየነውን የሰማነውንና በአካባቢያችን ያለን አደገኛ ነገር አለማጋለጥ ለሁላችንም ጎጂ ባህል ነው።
ዜመኛው፤ “ያንተ ቤት ሲንኳኳ ይሰማል እኔ ቤት” ያለው ይሄንኑ አደራ ሊለን ነው። የጉርብትናችን አይነተኛ ጥቅም፤ አንዳችን ለአንዳችን ማሰባችንና መረዳዳታችን ነው። እንኳንስ በአንድ ሀገር ውስጥና በአንድ ከተማ፤ በሁለት አገሮች ያለ ጉርብትና እንኳን ክቡርና ወሳኝ ነው። ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ባህላዊ ትስስራችን ትላንትን እንደ ታሪክ፣  ዛሬን እንደ ወቅታዊ ሂደት፤ ነገን እንደ ራዕይ ጨብጠን የተሻለ ዓለም ለማየት ምንጊዜም ዝግጁ መሆን አለብን። ለሀገራችን መልካም አማራጭ የምንሆነው፡-
1ኛ/ የድል አጥቢያ አርበኞችን ስንዋጋ
2ኛ/ ልማደኛ አድር ባዮችን ገለል ስናደርግ እና
3ኛ/ ሰርግ ቤት ሲያገኙን ዘፈን አውጪ፣ ሃዘን ቤት ሲያገኙ ሙሾ አውራጅ የሚሆኑና የየዘመኑ ተራማጅ የመሆን አባዜ ከተጠናወታቸው የመንግስትም ሆነ ከመንግስት ውጭ ያሉ ሹሞች፣ ባለስልጣኖችና ዜጎችን ስንጠነቀቅ ብቻ ነው - ወደ ቀናውና ጤናማው መንገድ የምናመራው!
እንዲህ ያሉት በየትውልዱ ውስጥ ያደፈጡ ጠላቶች መሆናቸውን አንርሳ! ከእባብ እንቁላል የእርግብ ጫጩት አይፈለፈልም!? ስለሆነም ከወዲሁ አካፋን አካፋ ማለት ይገባል! (Call a spade a spade)
በየመሥሪያ ቤቱ የተሰገሰገውን መሰሪ ሸቃይ፣ አጋፋሪና አሽቃባጭ ለይቶ ማውጣት ቢያንስ ለጤናማ የነገ ውሎአችን ይበጀናል። አበው፤ “አንዴ ሌባ ካሉት ቢቆርብም አያምኑት” ያሉት ወደው አይደለም። በለመደ እጁ ምን እንደሚወስድ፣ ምን እንደሚመነትፍ አይታወቅምና! ሁሌም ቢሆን አገር ሲበዘበዝና ህዝብ ሲዘረፍ ዝም አንበል። “ዝምታ ለበግም አልበጃት” እንዲል መጽሐፉ።


    ፕ/ር መረራ በአፍሪካ ህብረት አደራዳሪነት እምነት የላቸውም
                    
        የህዝብ ተወካዮች ም/ቤትና የፌዴሬሽን ም/ቤት ሁለተኛ ዓመት የሥራ ዘመን በፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ንግግር የተከፈተ ሲሆን በንግግራቸውም የ2014 ዓ.ም የመንግስት ዕቅድ  አፈጻጸምና አዲሱን ዓመት የ2015 ዓ.ም የመንግስት የትኩረት አቅጣጫዎች አቅርበዋል።
ባለፈው ዓመት የዜጎች የጅምላ ግድያ፣ መፈናቀል፣ ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰቶች የተፈጸመ ሲሆን በሚሊዮን የሚቆጠሩ ህጻናት በከፋ የምግብ እጥረት ለሞት አደጋ መጋለጣቸውን ፕሬዚዳንቷ ጠቁመዋል። የዚያኑ ያህል አስደማሚ ስኬቶችም መመዝገባቸውን ያነሱት ፕሬዚዳንቷ ከህዳሴ ግድብ ሶስተኛ ዙር የውሃ ሙሌት እስከ ለኤክስፖርት የሚቀርብ ስንዴ ምርት የሚደርስ ስኬት ተመዝግቧልም ብለዋል። በዚሁ የፕሬዚዳንቷ ንግግር አስተያየታቸውን የጠየቅናቸው የተቀዋሚ ፓርቲ አመራሮች አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡
በሀገሪቱ የሚታየው የመተላለቅ ፖለቲካ ወደ ድርድር ፖለቲካ ካልተቀየረ፣ ዘላቂ ሰላም እንደማይመጣ የተናገሩት የኦሮሞ ፌዴራሊስት ኮንግረስ (ኦፌኮ) ሊቀ መንበር ፕ/ር መረራ ጉዲና፤ አሁን በሀገሪቱ ያለው የእርስ በርስ ደም መፋሰስና እልቂት ወደ እውነተኛ ድርድር ካልተቀየረ ችግሩ እየባሰ እንጂ እየተሻሻለ እንደማይሄድ ተናግረዋል። ፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ባቀረቡት ንግግር ላይ አስተያየታቸውን በስፋት የሰጡት ፕ/ር መረራ መንግስት ችግሩ አንዱንም የተናገረውን ጉዳይ በተግባር አለመፈጸሙ ነው፤ ንግግር ብቻውን ደግሞ የሚያመጣው ፋይዳ የለም ብለዋል። ውጤት የሚያመጣው ንግግር ብቻ ሳይሆን በተግባር ላይ ማዋል ነው ያሉት ፕሮፌሰሩ የኢትዮጵያ መንግስት እስካሁን የተናገረውን ተግባር ላይ በማዋል ላይ አልተሳካትም፤ ወደፊት የሚሳካለት ከሆነ አብረን እናያለን ብለዋል።
ግን መንግስት ይሳካለታል ብለው ይጠብቃሉ ወይ በሚል ተጠይቀውም፣ “አሁን እየተሄደበት ባለው መንገድ ብዙ የሚሳኩ ነገሮች ያሉ አይመስለኝም፤ ጦርነቱ ላይ በርትተናል፤ እሱ ከተሳካ አላውቅም ሲሉም መልሰዋል።
ፕሬዚዳንቷ  “መንግስት ሁሌም ለሰላም ድርድሩ ዝግጁ መሆኑንና ህወሓት የሰላም ድርድሩን  ከረገጠ ግን የማስታገሻ እርምጃ ይወስዳል በሚል የተናገሩትን እንዴት ያዩታል? በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ  “መንግስት ጠንካራ አቋም ላይ ተመስርቶ መናገሩ ሲሆን ህውሃት ሰላም ካልፈለገ ግን ከፍተኛ እርምጃ የመውሰድ አቅም አለኝ የሚለውን መልዕክት ለማስተላለፍ ፈልጎ የተናገረው ነው” ብለዋል። ዞሮ ዞሮ ነገሩ አዲስ አይደለም ባለፉት አራት ዓመታት ሲባል የቆየና የተለመደ አባባል ነው- ብለዋል ፖለቲከኛው።
በፕሬዚዳንቷ ንግግር ያልተዳሰሰ ወሳኝ አገራዊ ጉዳይ ይኖር እንደሆነ ጠይቀናቸውም፤ “እኔ በአብዛኛው ጉዳይ ተስፋ እየቆረጥኩ ስለመጣሁ፣ መንግስት የሚናገራቸውና የሚሰራቸው ጉዳዮችም የተገናኙ ባለመሆናቸው ቢነሳም ቢቀርም ትርጉም የለውም” ሲሉ ስሜታቸውን ገልጸዋል። ለምሳሌ ስለ ኑሮ ውድነቱና ስለ ዋጋ ግሽበቱ ብዙ ጉዳዮች የተነሱ ቢሆንም፣ ምንም የተጨበጠና የሚይታይ ለውጥ እንዳልመጣ፣ እንዲያውም በአስደንጋጭ ሁኔታ የኑሮ ውድነቱና የዋጋ ግሽበቱ ጣሪያ መንካቱን ነው የጠቆሙት፡፡ መንግስት የኑሮ ውድነቱን ለማረጋጋትና የዋጋ ግሽበቱን ለመቀነስ የሚናገረውን ያህል እየሰራም ሆነ አዳዲስ ፖሊሲዎችን ይዞ ወደፊት እየመጣ አይደለም ሲሉም ፖለቲከኛው ተችተዋል፡፡
በሌላ በኩል የሰላም ጉዳይ በፕሬዚደንቷ የተነሳ ቢሆንም የኢትዮጵያ መንግስት አሁን እየገፋ ባለበት አካሄድ የሚሳካ አይመስልም ብለዋል፡፡ “በተለይ አሁን የሰላም ጉዳይ ሲነሳ የሚነሳው ትግራይ ያለው ጦርነት ብቻ ነው” የሚሉት የኦፌኮው ሊቀመንበር፤ በአብዛኛው የሀገሪቱ ክፍል በተለይ በኦሮሚያ ግጭቶች መኖራቸውንና እሱንም ለማስተካከል የቀረቡ ጥያቄዎች መልክ አለመያዛቸውንና ምላሽ አለማግኘታቸውን ነው ፕሮፌሰሩ የገለጹት፡፡ በኦሮሚያ ፤በቤኒሻንጉል ጉሙዝ በጋምቤላና በሌሎችም አካባቢዎች ግጭቶች መኖራቸውን ያስታወሱት ፕሮፌሰሩ፤ የነዚህ  ግጭቶች ምንጭ ፖለቲካ መሆኑንና ይህንን ምንጭ የኢትዮጵያ መንግስት እየሸሸ፣ ከላይ ከላይ የሚታየው ላይ ብቻ ማተኮር ተገቢም አይደለም ዘላቂ ሰላምም አያመጣም፤ ሲሉ አሳስበዋል፡፡
“ድርድሩንም በተመለከተ የኢትዮጵያ መንግስት የሙጥኝ ያለው አፍሪካ ህብረትን ነው” ያሉት ፕሮፌሰር መረራ፤ ይሁን እንጂ አፍሪካ ህብረትም ሆነ ከህብረቱ ቀድሞ የነበረው “አፍሪካ አንድነት ድርጅት ከተመሰረተ ከ6 አስርት ዓመታት በላይ እድሜ ቢኖረውም በነዚህ አመታት ሁሉ እዚህ ግባ የሚባል አፍሪካዊ ችግር ሲፈታ አላየንም ብለዋል። “ለአፍሪካዊ ችግር አፍሪካዊ መፍትሄ” የሚል መፈክር  በየጊዜው ከመስማት ውጭ ብለዋል። “እኔ የፖለቲካ ሳይንስ አስተማሪ እንደመሆኔ ብዙ ጉዳዮችን እከታተላለሁ ህብረቱ ይሄ ነው የሚባል የረባ ነገር ሲሰራ አይቼ አላውቅም የሚሉት ፕ/ር መረራ፤” ህብረቱ ላይ የሙጥኝ ቢባልም መፍትሄ ያመጣል በዬ አላምንም  ብለዋል።
ኮንጎ፤ ላይቤሪያ፤ ደቡብ ሱዳን፤ ሩዋንዳ፤ ሱማሊያና ሌሎችም የአፍሪካ ሀገራት በግጭትና በችግር ሲታመሱ ህብረቱ የሰራው ስራ የለም ሲሉም ለትችታቸው ማጠናከሪያ ማስረጃ አቅርበዋል።
ፈረንጆቹ ጉልበትም ቢሆን ጨምረውበት ችግሩ ከተፈታ እንጂ አፍሪካ ህብረት ላይ ሙጥኝ ማለት ችግሩ እንዲቆይ ከማድረግ ያለፈ ሌላ ፋይዳ አይኖረውም ብለዋል፡፡
“ለምሳሌ የቀድሞው የናይጄሪያ መሪ ኦሊሴንጎን ኦባሳንጆ ለምርጫው ጊዜ ኢትዮጵያ መጥተው አግኝቻቸው እንደ አንድ አዛውንት የአፍሪካ መሪ፣ የኢትዮጵያን መንግስት ብትመክር ይሻላል ምርጫው ዋጋ የሌለው ምርጫ ስለሆነ ለመታዘብ አትቸገርም” አፍሪካ ጥሩና ትክክለኛ መንገድ እንድትይዝ እንደ አንጋፋ የአፍሪካ መሪ ምከር ብለዋቸው እንደነበረ አስታውሰዋል፡፡ “አባሳንጆ ምን እንዳለ ባላውቅም በሶስተኛው ወይም በአራተኛው ቀን ምርጫው ሰላማዊና ፍትሃዊ ነው ብሎ ሚዲያ ላይ ተናግሮ ሲሄድ ብቻ አይቻለሁ” ብለዋል፡፡ የሆነ ሆኖ የድርድሩን ጉዳይ ከአፍሪካ ህብረት ቢያወጡት ጥሩ ነበር ሲሉም ምክር ለግሰዋል፡፡
ድርድሩ ከአፍሪካ ህብረት ይውጣ ካሉ በየትኛው አካል ቢካሄድ ይመርጣሉ ስንል ጠይቀናቸው “በዓለም ላይ በቂ ተሞክሮና እውቀቱ ያላቸው ትንሽም ቢሆን መግፋት የሚችሉ አገራት አሉ ያሉት ፖለቲከኛው፤” በምሳሌነት እንዲጠቅሱልን ጠይቀናቸው” የተሻሉና ገለልተኛ የሚባሉት የስካንዲኒቪያን ሀገራት ለምሳሌ እነ ኖርዌይ፤ ሲዊዲንና ኔዘርላንድ የመሳሰሉት በዴሞክራሲ ግንባታ ላይ የሚሰሩ ብሎም ለኢትዮጵያ ብዙ እርዳታና ድጋፍ የሚያደርጉ አገራት አሉ፤ ልምድም ተሞክሮዎችም በዓለም አቀፍ ደረጃ አዳብረዋል። ጉዳዩን እነሱ ቢያዩት ይሻላል ሲሉ ሀሳብ ሰጥተዋል፡፡ እነዚህ አገራት ከኋላቸው ጉልበት አለን የሚሉትን እንደነ አውሮፓና አሜሪካ ያሉ ሀያላንን መያዝ ይችላሉም ብለዋል፡፡ “ይሁን እንጂ ጉዳያችን የራሳችን ስለሆነ መደራደርም መነጋገርም ያለብን እዚሁ አገራችን ላይ እርስ በርሳችን መሆን ነበረበት” ሲሉም ተናግረዋል። እነዚህ ከላይ የተጠቀሱት አገራት አመቻቾች ናቸው የሚሉት ፕ/ር መረራ መገዳደል አቁመን መደራደር መጀመር ያለብን  ግን እኛው እራሳችን ነን ሲሉም መክረዋል፡፡
በምዕራብ ወለጋ በአማራ ተወላጆች ላይ ኦነግ ሸኔ በሚባል አሸባሪ ቡድን የሚፈፀመውን ግድያና ጥቃት በተመለከተ በመንግስት በኩል የመፍትሄ እርምጃ አልተቀመጠም የሚሉ ወገኖች አሉ፡፡ በዚህ ላይ የእርሶ አስተያየት፣ ምንድን ነው ተብለው ለተጠየቁትም “በዚያ አካባቢ የተደበላለቁ ነገሮች ስላሉ እኛ ደጋግመን በገለልተኛ አካል ይጣራ፤ መንግስት እየወሰደ ያለው እርምጃ መፍትሄ አምጪ አይደለም፤ በሁለቱም በኩል ብዙ ሰዎች እንደተገደሉና አሁንም እየተገደሉ እንደሆነ እናውቃለን ግን የመጣ መፍትሄ የለም ብለን ስንጮህ ቆይተናል” ያሉት ፕ/ር መረራ ይሄ ጉዳይ ፓርላማም ላይ መነሳቱንና ነገር ግን መንግስት አካባቢው ላይ ያለውን ግድያና መፈናቀል ለማቆም በቁርጠኝነት የሚሰራቸው ስራዎች አንድ ሁለት ሶስት ተብለው እስካልተቀመጡ ድረስ ጉዳዩ በአስቸጋሪነቱ እንደሚቀጥል ነው የገለፁት።
በጉዳዩ ዙሪያ በግልፅ ቋንቋ በተደጋጋሚ እንደ መድረክ መግለጫ አውጥተናል” ያሉት ፕ/ር መረራ፤ በገልተኛ አካል ያንን ማን እንደሚሰራ ባለመጣራቱና መንግስት ባለመስራቱ አሁንም በአካባቢው ግድያና መፈናቀሉ ቀጥሏል ብለዋል። አሁንም እኔ ለሁሉም መግለፅ የምፈልገው ለዚህ ሁሉ ችግር መፍትሄ የሚሆነው የመገዳደልን ፖለቲካ ወደ መደራደር ፖለቲካ በመቀየር ነውና በአስቸኳይ ከመገዳደል ወደ መደራደር እንግባ ስል ጥሪ አቀርባለሁ ብለዋል፡፡ ይህን ማድረግ ካልቻልን ፈረንጅም መጣ አፍሪካ ህብረትም መጣ ዋጋ የለውም ብለዋል፡፡
የፓርላማ አባላት (የህዝብ እንደራሴዎች) የወከሉትን ህዝብ መብትና ነፃነት ከማስከበር አኳያ ምን አይነት ሚና ሊጫወቱ ይገባል፤ አስከዛሬስ የተጫወቱት ሚና አለ ወይ? የሚል ጥያቄም ተነስቶላቸው፤ “በዓለም ላይ ፓርላማ በሶስት ይከፈላል” በማለት ማብራራት የጀመሩት ፕሮፌሰሩ፤ አንደኛው “ጠንካራ ፓርላማ” የሚባለው ሲሆን ጥሩ ጥሩ ህጎችን የሚያወጣና እነዚያ ህጎች በትክክል ስራ ላይ መዋላቸውን ለመቆጣጠር የሚችል ነው ብለዋል፡፡
ሁለተኛው አይነት ፓርላማ ደግሞ ጥሩ ጥሩ ህጎችን ማውጣት ይችላል፤ ስራ ላይ መዋላቸውን መቆጣጠር እንኳን ባይችል ለሀገር ለህዝብ የሚጠቅሙ ህጎችን ያወጣል፤ ሶስተኛው አይነት ፓርላማ ደግሞ ብዙ ጊዜ በዓለም ላይ የሚታወቀውና ፈረንጆች “talking shop” የሚሉት ነው፡፡ ያሉት ፕ/ር መረራ ይህ ፓርላማ ቢያንስ ንግግርና ጫጫታ የሚሰማበት ነው ሲሉ አብራርተዋል፡፡
ታዲያ የእኛ አገር ፓርላማ ከሶስቱ የትኛው ምድብ ላይ ይገኛል ስንል ጠይቀናቸው “ በጣም የሚያሳዝነው የሶስቱም በታች ሆኖ መገኘቱ ነው” በማለት የሀገራችንን ፓርላማ አጣጥለውታል፡፡ ምክንያታቸውንም ሲያስረዱ ቢያንስ ጫጫታውና ብሶት ማሰማቱም የለም ያሉት ፕ/ሩ እኛ ፓርላማ በነበርንበት ጊዜ ለአምስት አመት ጫጫታ ( የህዝብ ብሶት) ማሰማት ችለን ነበር በማለት የቀድሞውን ፓርላማ የተሻለ  መሆን ገልፀው፣ በአሁኑ ጊዜ ከዚያ አንሰን የኋልዮሽ ጉዞ ጀምረናል በማለት አገሪቱ ላይ ያለው ችግር ከላይ እስከታች አሳሳቢ ስለመሆኑ አስምረውበታል። ዞሮ ዞሮ ፓርላማውም የህዝብን ብዞት በማሰማት ተፅዕኖ መፍጠር አለበት መንግስት የመገዳደልን ፖለቲካ ወደመደራደር ማምጣት አለበት። ከዚህ ውጪ ያለው መፍትሄ አያመጣም ሲሉ አስተያየታቸውን ቋጭተዋል።
የፕሬዚዳንት ሳህለወርቅ ዘውዴ ንግግር መንግስት በ2015 ዓ.ም ትኩረት ይሰጥባቸዋል ተብሎ የሚታሰቡ ዋና ዋና ነጥቦች ላይ ያተኮሩ ናቸው ያሉት የኢዜማ ስራ አስፈጻሚ አባል አቶ ግርማ ሰይፉ፣ ይሁን እንጂ ፕሬዚዳንቷ ቢያነሷቸው ጥሩ ነበር የሚሉ ሀሳቦችን ቀድመው እንዳይናገሩ የሚያግዳቸው እንዳለና የፓርቲያቸው የፓርላማ ተጠሪ በማሻሻያ ሞሽኑ ላይ  ያቀርበዋል ብለው እንደሚያምኑ ጠቁመው በዚህ ላይ አስተያየት ከመስጠት ተቆጥበዋል።
ፕሬዚዳንቷ ቅድሚያ ሰጥተው ያነሷቸው ሁለት ነጥቦች እንዳሉ የጠቆሙት አቶ ግርማ፣ እነዚህም ሰላም ዴሞክራሲና በተለይ አሁን በየአካባቢው ያሉ ግጭቶች በሰላም የሚፈቱበት መንገድ አንዱ ሲሆን ሁለተኛው የአገራዊ ምክክሩ ጉዳይ መሆኑን አመልክተዋል፡፡
በሁለቱ የፕሬዚዳንቷ ንግግሮች ላይ ትኩረታቸውን ያደረጉት አቶ ግርማ፣ መንግስት ሁሌም ለሰላም እጁን እንደሚዘረጋና ችግሮችን በሰላምና በውይይት በሚፈቱበት መንገድ ላይ አጠናክሮ በመቀጠል ጠብመንጃ ያነሱ ሃይሎ ወደ ውይይት የሚመጡ ከሆነ በግራም በቀኝም  የሚሞቱ ሰዎችን ህይወት ለማትረፍ ትልቅ አጋጣሚን ይፈጥራል ብለዋል። ለነዚህ ጉዳዮች ሲባል የሰላምን እጅ መዘርጋት ጥሩ ነው ያሉት የኢዜማ አመራር ይህ ሳይሆን ቀርቶ ጉዳያችንን በጉልበት እናስፈጽማለን ከተባለ ግን መንግስት አስፈላጊውን እርምጃ መውሰዱ አይቀሬ ነው በማለት አቋማቸውን አንፀባርቀዋል፡፡
“ይሄ ማለት ግን መንግስት እጁን ሊጠመዝዙ የሚፈልጉ ሰዎችን እሹሩሩ እያለ ይኖራል ማለት አይደለም” የሚሉት አቶ ግርማ፤  ይዋል ይደር እንጂ እውነትን የያዘ ያሸንፋል። ለሌላ ጥቅም የቆሙ አካላትም ጥቅማቸው ሲቋረጥባቸው ሃሳባቸውን ይቀይሩ ይሆናል ብለዋል። በመንግስትና በህወሓት መካከል ባለው ግብግብ የትግራይ ህዝብና ድንበር አካባቢ ያለው የአማራና የአፋር ህዝብ እየተጎዳ ነው ያሉት አንጋፋው ፖለቲከኛ በመላው ኢትዮጵያ ያለ ሀይል ተንቀሳቅሶ ይህንን ለመመከት ሲል ደግሞ የህይወት የሃብትና የንብረት ኪሳራ እየደረሰ መሆኑን ገልፀዋል። “ይህንን ጥፋትና ውድመት ለአንድ ቀንም ሆነ እስከ መጨረሻው ተስማቶ ማቆም ይጠቅማል” የሚሉት የኢዜማው አመራር፣ ከዚህ አንፃር ወደ ውይይት መምጣት አማራጭ የሌለው ጉዳይ መሆኑን አስምረውበታል፡፡ ወደ ውይይት ለመምጣት ግን ቅድመ ሁኔታ ማስቀመጥ፣ መሳሪያ ይዤ እያስፈራራሁ እደራደራለሁ ማለትና መሰል ጉዳዮች ካሉ መሳሪያ ታጥቆና ሀይል አስተባሮ የአገርንና የህዝብን ሰላም የመጠበቅ መብት ያለው መንግስት ስለሆነ ይህንን ማስፈጸም አለበት ብለዋል።
አቶ ግርማ አክለውም ፤ለምንድን ነው መንግስት አቅም ካለው እስከዛሬ ጦርነቱን ያላጠናቀቀው ለተባለው “ጦርነት አቅም ስላለሽ ብቻ የምትጨርሽው ወይም አቅም ስለሌለሽ ተሸንፈሽ የምትወጪበት ሜዳ አይደለም” ሲሉ የጦርነትን ውስብስብ ባህሪ የገለፁ ሲሆን፣ መንግስት ተገድዶ የገባበትን ጦርነት ሁሉንም ደምስሼ አሸንፋለሁ ብሎ ካመነ በመሃል የሚደርሰው ኪሳራ ከባድ መሆኑንና በተለይ ህዝቡን ምሽግ አድርጎ የተነሳን አሸባሪ ለመምታት አስቸጋሪ በመሆኑ ጦርነት በታሰበውና በታቀደው ሰዓት አይጠናቀቅም ፤አቅምና ትጥቅ ስላለም ብቻ ቶሎ አይቋጭም ሲሉ ተናግረዋል።  
ስለሆነም መንግስት ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ አለበት ያሉት አቶ ግርማ “ አሳውን ለመያዝ ባህሩን ማድረቅ” የሚባለው አይነት አካሄድ አክሳሪና የማያዋጣ መሆኑን አስረግጠው የተናገሩት ፖለቲከኛው፣ ህወሃትን ለመደምሰስ በሚደረግ ውጊያ የትግራይን ህፃናት፣ አረጋውያንና ሌሎችንም የህብረተሰብ ክፍሎች ደህንነት ማረጋገጥ ያስፈልጋል ብለዋል።
የህወሓት ሃይሎችም ይህ አካሄድ እንደማያዋጣቸው አውቀው ወደ ውይይት ጠረጴዛ በመምጣት የሚቀርብላቸውን አማራጭ በመቀበል እስከዛሬ ከደረሰው የሰብአዊና ቁሳዊ ኪሳራ የበለጠ ተጨማሪ ኪሳራና ውድመት እንዳይደርስ ማድረግ ይቻላል “ይህን አማራጭ የማይቀበሉ ከሆነ ግን መንግስት ከፍተኛ ጥንቃቄ እያደረገም ቢሆን የእነዚህን ሃይሎች እጅ መያዝ አለበት” ሲሉም መክረዋል።
አገራዊ ውይይቱን በተመለከተ አቶ ግርማ ሲናሩ፣ ፕሬዚዳንቷ ካለፈው አመት የቀጠለውን ይህንን ውይይት ማንሳታቸውን አድንቀው ሌሎቻችንም በዚሁ ልክ ትኩረት ሰጥተንና የመንግስት ደጋፊ እንባላለን ከሚል መሸማቀቅ ወጥተን እንዲሁም የፖለቲካ ቁማር ከማድረግ ወጥተን ውይይቱ የተሳካ የሚሆንበትን ተሳትፎ ማድረግ አለብን ሲሉ አሳስበዋል።
በምዕራብ ወለጋ በአማራ ተወላጆች ላይ በኦነግ ሸኔ የሚደርሰውን ዘር ተኮር ግድያና ጥቃት በተመለከተ መንግስት ምን መፍትሄ እርምጃ መውሰድ አለበት በሚል ተጠይቀው “አሸባሪው ህወሓት አገርን ከመረበሽና ከማሸበር አጀንዳዎቹ አንዱ አድርጎ የፈጠረው በመሆኑ ውይይቱና ድርድሩ ከተሳካ አብሮ የሚቆም ነው” ብለዋል። ጉዳዩን ወደ ውይይትና ወደ ድርድር ማምጣት የብዙ ችግሮች መፍትሄ ሊሆን እንደሚችልም በአፅንኦት ተናግረዋል፡፡
የቀድሞውን ጠቅላይ ሚኒስትር ታምራት ላይኔንና የቀድሞውን የኢዴፓ አመራር ልደቱ አያሌውን የሰሞኑን ለህወሃት ያደረጉትን ውግንና በተመለከተ ለቀረበላቸው ጥያቄ አቶ ግርማ ሲመልሱ፣ በግድ ባርነትን የመሻትና የማስቀጠል አባዜ ስላለባቸው በዚህ ላይ ብዙ ማለት አልፈልግም  “በተለይ አቶ ልደቱ መጀመሪያ የለውጡ አራጋቢ ሆኖ የነበረ ቢሆንም ዶ/ር አቢይ የምጠላቸውን ጠራርጎ ያባርርልኛል ብሎ የጠበቀው ነገር ባለመሳካቱ ብስጭቱንና ንዴቱን ለማስታገስ ነው የሚጮኸው” ብለዋል፡፡ “እስከዛሬ ይህ ሰው ልቡን እንደሚያመው ነበር የምናውቀው፤ አሁን ግን፤ ጭንቅላቱን የታመመ ይመስለኛልም” ብለዋል፡፡ አቶ ታምራት ላይኔም ቢሆኑ የቀድሞውን በህውሃት ውስጥ የነበሩበትን ባርነት ከመናፈቅ የመጣ እንጂ ሌላ ነገር አይደለም ያሉት አቶ ግርማ፤ የሆነ ሆኖ የሁለቱ ግለሰቦች ጩኸት በኢትዮጵያ ፖለቲካ ላይ የሚያመጣው አንዳችም ለውጥ የለም ሲሉም ቋጭተዋል።




 የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅትን ለማስተባበርና ለመወከል የተቋቋመው የኢትዮጵያ የሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ም/ቤት ፤ በሰሜን ኢትዮጵያ የሚካሄደውን ጦርነት በዘላቂነት ለማስቆም መንግስትና ህውሃት በቅን ልቦና እንዲደራደሩ ጠይቋል- በሳምንቱ መጀመሪያ ባወጣው መግለጫ፡፡
መንግስትና ህውኃት በሰላም ድርድሩ በሃገሪቱ ውስጥ ያሉ ዜጎችን ሁለንተናዊ ደህንነት የሚረጋግጥ ስምምነት ላይ ይደርሱ ዘንድ የሚመለከታቸው አካላት ሁሉ ግፊት እንዲያደርጉም መክሯል-ም/ቤቱ፡፡
በሰሜኑ የሃገሪቱ ክፍል ያለው የትጥቅ ግጭት እያስከተለ ያለውን ከፍተኛ የህይወትና የአካል ጉዳት ከግምት ውስጥ በማስገባት፤ በመንግስትና በህውሐት በኩል ወደ ድርድሩ ለመመለስና ሰላምን ለማስፈን እየታየ ያለውን ተነሳሽነት ያደነቀው ም/ቤቱ፤ የአፍሪካ ህብረት የሰላም ሂደቱን በመደበኛነት ለመያዝና ለመምራት የማያደርገውን ጥረትም አመስግኗል፡፡
በሌላ በኩል፤ በምዕራብ ኦሮሚያ በሰላማዊ ዜጎች ላይ እየደረሰ ያለው ከፍተኛ የሰብአዊ መብት ጥሰት፤ የጅምላ ጭፍጨፋና ሁከትን ለመግታት የተወሰደው እርምጃ በቂ አለመሆኑ እጅጉን እንደሚያሳስበው ም/ቤቱ በመግለጫው አስታውቋል፡፡ ከዚህ አንፃርም ውዱን የሰው ልጅ ህይወት ለመታደግና በአካባቢው መረጋጋትን ለማስፈን፤ መንግስት ከወትሮው በተሻለ ከፍተኛ ጥረት እንዲያደርግና የዜጎችን ደህንነት እንዲያረጋግጥ ም/ቤቱ ጥሪውን አቅርቧል፡፡
የኢትዮጵያ ሲቪል ማህበረሰብ ድርጅቶች ም/ቤት፤ ለዓለም አቀፍ ማህበረሰብ ባቀረበው ጥሪም፤ የሰላም ሂደቱን ገንቢ በሆነ መንገድ እንዲደግፍና ግጭቶችን በሰላማዊ መንገድ ለመፍታት የሚደረገውን ጥረት ከሚያሰናክሉ ማናቸውም ተግባራት እንዲታቀብ በአፅንኦት ጠይቋል፡፡
ም/ቤቱ በተጨማሪ ምሁራንና መገናኛ ብዙኃን ከፍተኛ ሚና የሚጫወቱ የማህበረሰቡ ወሳኝ ባለድርሻ አካላት መሆናቸውን ጠቁሞ፤ ሁለቱም አካላት በሰላሙ ሂደት እንዲሁም በሰብአዊ ድጋፍ  እርዳታ ላይ ገንቢ ሚና እንዲጫወቱም  ጥሪ አቅርቧል፡፡
በመጨረሻም በዚህ ወሳኝ ወቅት በትጥቅ ግጭቱ ዳግም መቀስቀስ ሳቢያ ለጉዳት ለተዳረጉ በሺዎች ለሚቆጠሩ ዜጎች ሰብአዊ እርዳታ በማድረስ ረገድ አፋጣኝ ምላሽ ለመስጠት የሚመለከታቸው አካላት በሙሉ እንዲረባረቡም አሳስቧል፡፡
በዚህ ረገድ ም/ቤቱ የሲቪል ማህበረሰቡን በማደራጀትና በማስተባበር፤ የሰላም ግንባታና የሰብአዊ ድጋፍ ሥራዎችን አጠናክሮ ለመቀጠል ያለውን ዝግጁነትና ቁርጠኝነት በድጋሚ እንደሚያረጋግጥም አስታውቋል-በመግለጫው፡፡
“በምዕራብ ኦሮሚያ የዜጎችን ግድያ ለማስቆም በቂ እርምጃ አለመውሰዱ ያሳስበኛል”