Administrator

Administrator

ዲጂታል የክፍያ ስርዓትን የሚከተሉ ከ40 በላይ ተቋማት የሚሳተፉበት “ዲጂታል ፋይናንስ ኢትዮጵያ 2022 ሾውኬዝ” የፊታችን ረቡዕ ጥቅምት 9 ቀን 2015 ዓ.ም በኢንተር ሌግዠሪ ሆቴል ይከፈታል፡፡
“The Digital Financial Services Working Group” በተሰኙ ቡድኖች  የተዘጋጀውና በተባበሩተ መንግስታት የካፒታል ፈንድ (UNCDF) የሚደገፈው ይሄው ሾውኬዝ፤ ሶስት ዋና ዋና አላማዎች ያሉት ሲሆን እነዚህም ትብብርና ኔትወርክ መፍጠር፤ የዘርፉን ተዋንያንና የመንግስት አካላትን እርስ በእርስ በማገናኘት በዘርፍ ዙሪያ እንዲወያዩና በሚያጋጥሙ ችግሮች ላይ የመፍትሄ ሀሳብ በማፍለቅ  ዲጂታል ገበያው እንዲሳለጥ ማድረግ እንዲሁም ስለ ዲጂታል ፋይናንስ የማህበረሰቡን ግንዛቤ ማሳደግ እንደሆኑ የሥራ ቡድኑ ዋና ሊቀ መንበር አቶ ዩሴፍ ክብረት ተወካይ ናኤል ሀይለ ማርያም ተናግረዋል፡፡
ባለፈው ረቡዕ ከሰዓት በኋላ በአዋሽ ባንክ ዋናው መሥሪያ ቤት አውደ ርዕዩን አስመልክተው አዘጋጆቹ በሰጡት መግለጫ፤ ይህ ዓለም አቀፍ አውደርዕይ በዋናነት የተዘጋጀው የኢትዮጵያ የዲጂታል ኢኮኖሚ 2025 አጀንዳንና የብሄራዊ ባንክን የዲጂታል ክፍያ ስትራቴጂ መሰረት በማድረግ ሲሆን በአውደ ርዕዩ ላይ ባንኮች፤ የማይክሮ ፋይናንስ ተቋማትና በአጠቃላይ በዲጂታል የአሰራር ስርዓት ላይ የተሰማሩ ከ40 በላይ ተቋማት  ይሳተፋሉ ብለዋል።  ጥቅምት 9 እና 10 በኢንተር ሌግዠሪ ሆቴል በሚካሄደው አውደርዕይ ላይ ተቋማቱ አገልግሎታቸውን ለእይታ የሚያበቁ ሲሆን በዘርፉ ላይ የተሰማሩ ተቋማት አመራሮች ፤የመንግስት የስራ ሀላፊዎችና ባለድርሻ አካላት የፓናል ውይይት እንደሚያደርጉና የስራ ትስስሮች እንደሚፈጠሩም አዘጋጆቹ ገልፀዋል፡፡ የአውደርዕይ መግቢያ በነፃ ሲሆን በሁለቱ ቀናት ህብረተሰቡ አውደርዕዩን በነፃ እንዲጎበኝ አዘጋጆቹ ጋብዘዋል፡፡

     3 ሚሊዮን ዶላር ወጪ ተደርጎበታል
                       
        በአገራችን በየዓመቱ ከሚመዘገበው አጠቃላይ የሞት ምጣኔ መካከል 6 ነጥብ 23 በመቶውን የሚሸፍነውን  ስትሮክ  በአገር ውስጥ ለማከም የሚያስችል የህክምና ማዕከል 3 ሚሊዮን ዶላር በሚጠጋ ወጪ ተገንብቶ አገልግሎት መስጠት ጀመረ።  
ማዕከሉ ከደም ቱቦ መዘጋት፣ መርጋትና መጥበብ ጋር በተያያዘ አካልን መንቀሳቀስ እንዳይችል በማድረግ ሚሊዮኖችን ለሞትና ለአካል ጉዳት ሲዳርግ ለኖረው የስትሮክ በሽታ፣ በውጪ አገር የሚሰጠውን ህክምና ሙሉ በሙሉ በአገር ውስጥ ለመስጠት ያስችላል ተብሏል ።
ማዕከሉ ለአንጎል ቀዶ ህክምና የሚያገለግል መሳሪያ በ1.5 ሚሊዮን ዶላር መግዛቱ ተገልጿል።
ከአሥር ዓመታት በላይ በኢትዮጵያ አገልግሎት ሲሰጡ  ከቆዩት  የአሜሪካ ሜዲካል ማዕከልና  ሰማሪታን የቀዶ ሕክምና ማዕከል ጋር በትብብር አገልግሎት መስጠት የጀመረው አክሶል የስትሮክና ስፓይን ማዕከል፤በስትሮክ ሕክምና ስፔሻላይዝድ ባደረጉ ብቁ የሕክምና ባለሙያዎች በውጪ አገር የሚሰጡ ህክምናዎችን ሙሉ በሙሉ በአገር ውስጥ ለመስጠት እንደሚያስችል ተገልጿል። በዚህም ህሙማን ለሕክምና  ወደ ውጪ አገር በመሄድ የሚያባክኑትን ከፍተኛ ገንዘብና ጊዜ  እንደሚያስቀር ተጠቁሟል፡፡ ህሙማን በማዕከሉ ለሚሰጠው ሕክምና  የሚያወጡት ወጪ ወደ ኬንያና ህንድ አገሮች ቢሄዱ ከሚያወጡት በአሥር እጥፍ ያነሰ እንደሆነም ተገልጿል።
 የአክሶል  የስትሮክ እና ስፓይን ማዕከል አጋር መሥራችና ዋና ሥራ አስኪያጅ ዶ/ር ወንደወሰን ገብረ አማኑኤል እንደተናገሩት፤ ማዕከሉ ባለፉት ስድስትና ሰባት ወራት ውስጥ የድንገተኛ ክፍል፣ የቋንቋ ቴራፒዎች፣ የአካል ቴራፒዎችና ሌሎች ባለሙያዎችን ሲያሠለጥን ቆይቷል፡፡ አገራችን ድሀ ከመሆኗ አንፃር ትኩረት መደረግ ያለበት ቅድመ መከላከል ላይ መሆኑን የጠቆሙት ዋና ሥራ አስኪያጁ፣ በቅድመ መከላከሉ ላይ ያተኮረ ትምህርት በስፋት ለመስጠት መዘጋጀታቸውንም ገልጸዋል ።
የጤና ሚኒስትር ሊያ ታደሰ (ዶ/ር) በበኩላቸው፣ የአክሶል ስትሮክ እና ስፓይን ማዕከል  በአገራችን መከፈቱ በኢትዮጵያ የስትሮክ ሕክምናን አንድ ምዕራፍ ወደፊት የሚወስድ ነው ብለዋል፡፡ ላለፉት ዓመታት ተላላፊ ያልሆኑ በሽታዎች የሚያስከትሉት ሞት እየጨመረ መምጣቱን የገለጹት ሚኒስትሯ፣ ችግሩን ከመቅረፍና ከመከላከል ጎን ለጎን የስፔሻሊቲ ሕክምና አገልግሎት ለማስፋፋት የአሥር ዓመት ፍኖተ ካርታ ተዘጋጅቶ እየተተገበረ መሆኑንም አስረድተዋል። የጤናው ዘርፍ በርካታ መሻሻሎችን እያሳየ መሆኑን የጠቀሱት ሚኒስትሯ፤ ተላላፊ ባልሆኑ በሽታዎች ብዙ የሚቀሩ ሥራዎችን ወደፊት መሥራት ይጠበቃል ብለዋል።
የአክሶል የስትሮክና ስፓይን ማዕከል አጋር መሥራች ዶ/ር  አከዛ ጠአመ  በበኩላቸው፤ ማዕከሉ በኢትዮጵያ አዲስ አገልግሎት የሚሰጥ መሆኑንና አገልግሎቱ የሚሠጠው ለአገር ውስጥ ታካሚዎች  ብቻ ሳይሆን ከጎረቤት አገሮች ለሚመጡ ታካሚዎችም ጭምር  እንደሚሆንና በዚህም ለአገራችን ከፍተኛ የውጪ ምንዛሬ እንደሚያስገኝ ተናግረዋል ፡፡
በዓለም ላይ በየአመቱ ከ13 ነጥብ 7 ሚሊዮን በላይ ሰዎች በስትሮክ በሽታ የሚጠቁ ሲሆን  ከ5 ሚሊዮን በላይ ሰዎችም ህይወታቸውን በዚሁ በሽታ ሳቢያ ያጣሉ።
በኢትዮጵያ በየዓመቱ ከሚመዘገበው አጠቃላይ የሞት ምጣኔ መካከል 6 ነጥብ 23 በመቶው የሚከሰተው  በስትሮክ ሳቢያ ነው።





Saturday, 08 October 2022 09:48

ሙሾ አውራጅነት ቢቃጣኝ

ሙሾ አውራጅነት ቢቃጣኝ
ለማዲንጎ ላውርድ ብዬ፣ የገጣሚ ቃል ቢወጣኝ
እንዲህ ነበር የሚያሰኘኝ፡-
ወይ ዋይ ዋዮ- ዋይ
ዋይ ዋይ ዋዮ- ዋይ
እሱ ከመሬት፣ ድምፁ ከላይ!
*    *    *
እናንት ቀባሪዎች፣ ዝቅ አርጋችሁ ማሱ
አይበቃውምና፣ ለድምፁና ለሱ!
*    *    *
አይ ያቀንቃኝ ነገር፣
አይ የቀን-ቃኝ ነገር፣
ልቡ የሸፈተ፤
ውርስ ስጠን ቢባል፣ ድምፁን ትቶ ሞተ!
*    *    *
አያዋጣም ስለው፣ እያዜሙ መኖር
አልበም ሰጥቶኝ ሄደ፣ የአዝመራውን መከር!
*    *    *
አይ የዘመኑ ሰው
አወይ እንዳንድ ሰው
ደስ እንዳለው መስሎ፣ ደስ እንዳለው ሆኖ
አለሁኝ እያለ
ጨረስኩኝ እያለ
እሱው ያልቃል ዘፍኖ
ክለቡን አድምቆ
ክቡን አሙቆ
ይሄዳል መንኖ!

እንደ መግቢያ
ማዲንጎ!
እንዲህ ነወይ ዜና ማለት?
እንዲህ ነወይ መርዶ ማለት?
እንዲህ ነወይ ድምጽ ቅጭት?!
ያ ከሆነ ሞትም ይሙት!
ያ ከሆነ አብሮህ ይሙት!
ተዘፍኖ እንጂ፣ ተለቅሶ አይደል
ያንተን መሳይ ሰው ስንብት!

ዋ! ማዲንጎ!
ማዲንጎ፤
አንተ የዜማ ዐይነ- በጎ!
ማን ፀነሰህ እጥበብ ቤት ማን ወለደህ አሳድጎ?!
 ማዲንጎ! አድጎ መወለድ ብሎ ቃል፣ አሁን እሄ አማርኛ ነው?
ሆኖም ያ ባንተ አየነው!
የቅላፄህ ስጋ- መንፈስ
እንዳሻህ በቦዩ ስንዲፈስ
ማን ቃኘህ ድምፀቱን ክኖ በሙዚቃ ግብር ድግስ?
ስትጠል መረዋ ቃጭል፣ የነጥላሁን ቡቃያ
ስትገዝፍ ብራቅ ነጎድጓድ የካሣ ተሰማ እኩያ፡-
“ከባልንጀራው ማታ የተለየ
እንደ አጥቢያ ኮከብ ሲነጋ ታየ!
… አባረርካቸው በቃ ተመለስ
ማንን ይተኳል አንተ ብትጨረስ!”
የሚባልልህ… አንት አንጀት አርስ
ማዲንጎ!
ምነው ጀምበርህ ዘመመ?
ያንገት በላይ ህመም እንጂ፣ የድምፅ ቅጭት የታለ?
የዘመን ትዝታህ እንጂ፣ ጠርህ መች ጎላ ተባለ?
ማዲንጎ!
ሬንጀ-ብዙ ሬንጀር መሰል፣
የጥበብ ጦር ልዩ ደወል
ወራጅ- ውሃን የሚያባብል
(የ) ደወል-ምላስ፣ የደዋይ ድል
ሰዓት ደርሷል “ንቁ” እምትል፣
የአንተም ሰዓትህ ደረሰ?
የድምፅህ ምት ለሰለሰ?
ያ እስግምግምታው ቀነሰ?!
ዋ ማዴዋ!
ነበርክ እኮ ቅን መለከት፣
ሲሻህም ድምፀ- ነጋሪት፣
አሊያም ደግ አንጎርጓሪ
ማልደህ እንደ ወፍ ዘማሪ፣
ነግተህ እንዳዝማሪ ጥሪ፤
ቃል ውሃ ልክህ ምጥን… ሆኖም ንፍገትን እማይዋጅ፤
ጠብታ- ጎርፍህ ገደል-ናጅ
ለስንት ወጣት ፈርእሚያበጅ
የስንቱ ወጣት አዋላጅ
አንት የጠዋት የጥበብ አዋጅ።
ጉሮሮ አንጀትን ሲስበው
ትንፋሽ ስንኝን ሲቃኘው
ማወቅ ለሚሻ ለገባው ያተ ፍሰት ነው ማስረጃው!
ሲመቸው  በደንገላሳ፣ እንደፈረሰ በሶምሶማው
ወይ እንደሰጋር በቅሎ ስግረት፣  ዘለግ ባለ ጅናኔው
ከበገናም ክራር አውታር በተሸረበ ምጣኔው
ድርብ- ነጠላ ሲያስኬደው
ምን ይላል ያ ያሬድ ሲሰማው
ዋይ ዜማ! ሲል የዘመረው
ዋ ዜማ! ሲል የዘፈነው
ማዲንጎ ላንተም እኮ ነው!
መጥኔ ለቅላፄህ ጠረፍ
ካጣሱት ለማይገኝ ፅንፍ!
እንደክት ልብስ ብርቅ ሆኖ፣ ሁሌ አሲድ ስንኝ ለሚያመጥቀው
ፅርሃርያም ለሚከትተው!
አወይ ለማዲንጎ /መጥኔ፣ ሰምና ወርቅ ---- በሰው!!
በድንገት ሄድክ አሉኝ እንጂ
አለህ ማዲንጎ ከኛ ጋር፣ ድምፅ እንደ ዕድሜ አይቀጭም።
እንደ ጠጅ ሣር፣ ለም ቄጤማ፣ ይለመልማል ዝንተ ዓለም!
አይገርምህም ማዲንጎ?
ክፉን ዘመን ተገን አርጎ
ለክፉ ዕጣ አደግድ
ሞት እኳን ዘፈን አማረው
የወሰደህ… ትዘፍንለት፤ ወይ ታንጎራጉር መስሎት ነው
ሞትስ ይሙት- ፍግም ያረገው!
እኛስ በድምፅህ ኗሪ ነን
እያሰብንህ እንኮራለን
ዛሬም ቃኖህ ኑርልን!
ዋ!ማዲንጎ!
አንተ ዜማ ዐይነ-በጎ!...
ከነቢይ መኮንን (ለማዲንጎ አፈወርቅ መታሰቢያ በሰይፉ በኢቢኤስ መነሻነት የተሸፈ)
መስከረም 22 ቀን 2015


      ህፃናት ለጦርነት እየተመለመሉ መሆኑን አውግዟል

                        ህፃናት ለጦርነት እየተመለመሉ መሆኑን አውግዟል

       የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ ከትላንት በስቲያ በኢትዮጵያ ጉዳይ ከተወያየ በኋላ ባወጣው የውሳኔ ሃሳብ፤ በሰሜኑ የኢትዮጵያ ክፍል ግጭት በአስቸኳይ ቆሞ በትግራይና በአዋሳኝ ክልሎች ያለአንዳች ቅድመ ሁኔታ ተኩስ አቁም እንዲደረግ ጠይቋል።
በሰሜኑ ግጭት ህፃናት ለጦርነት ይመለመላሉ መባሉንና ነፍጥ አንግተው በጦር ግንባር እንዲሰለፉ መደረጉን  እንደሚያወግዝም ህብረቱ አስታውቋል።
“በጦርነት በተጎዱ አካባቢዎች ለሚገኙ ወገኖች በሙሉ የተሟላ፣ ደህንነቱ የተጠበቀና ዘላቂ የሰብአዊ እርዳታ እንዲደርሳቸው የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ አባላት ይሻሉ” ብሏል፡፡
ህብረቱ  ባወጣው የውሳኔ ሃሳብ፡፡ የሰላማዊ ሰዎችን ሆነ ብሎ ዒላማ ማድረግና ህፃናትን ለውትድርና መመልመል በጦር ወንጀልና በሰብአዊነት ላይ የሚፈፀም  ወንጀል መሆኑን  ፓርላማው አውስቷል፡፡
የሰሜን ኢትዮጵያን ጦርነትን ተከትሎ በትግራይ ከሚገኙት ከ5 ዓመት በታች ከሆኑት ሶስት ህጻናት ውስጥ አንዱ የምግብ እጥረት እንደሚያጋጥመው የጠቆመው ፓርላማው፣ የትግራይ ነብሰ ጡር ከሆኑና ከሚያጠቡ እናቶች መካከል ደግሞ ገሚሱ የምግብ እጥረት ተጠቂ መሆናቸውን አመልክቷል፡፡
በክልሉ በጦርነቱ ሳቢያ ከትምህርት ገበታ የተለዩ ህፃናት ቁጥር 1.39 ሚሊዮን እንደሆነም ፓርላማው ጠቁሟል።
ህብረቱ ባወጣው የውሳኔ ሃሳብ፤ ተፋላሚ ሃይሎች ልዩነቶቻቸውን በውይይት እንዲፈቱ የጠየቀ ሲሆን በተለይም በአፍሪካ ህብረት መሪነት የሚደረገውን የሰላም ጥረት እንደሚደግፍ አስታውቋል፡፡
አንዳንድ አስተያየት ሰጪዎች፤ የአውሮፓ ህብረት ፓርላማ ህፃናት ለውትድርና መመልመላቸውን ማውገዙ ተገቢ ቢሆንም፤ በእጅጉ ግን ዘግይቷል ሲሉ ተችተዋል፡፡ አማፂው ህውሓት ቡድኑ ብዙ ሺህ ህፃናት ለጦርነቱ ተመልምለው ማለቃቸውን በመግለፅ፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት የዛሬ ዓመት ግድም ጀምሮ የአማፂው ቡድን ህፃናትን ነፍጥ አሲዞ ለጦርነት እያዘመተ መሆኑን በማጋለጥ ዓለማቀፉ ማህበረሰብ ድርጊቱን እንዲያወግዝ በተደጋጋሚ ቢወተውትም ዓለማቀፉ ማህበረሰብ ያልሰማ መስሎ አልፎታል ሲሉ ነቅፈዋል፡፡


   የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ) ሰኔ 7 ቀን 2014 ዓ.ም. በጋምቤላ ከተማ ላይ በኦሮሞ ነጻነት ሠራዊት (በተለምዶ ኦነግ ሸኔ) እና የጋምቤላ ነጻነት ግንባር (ጋነግ) ጥቃት መፈጸማቸውን ተከትሎ በጋምቤላ ክልል የጸጥታ ኃይሎችና በታጣቂ ቡድኖቹ የተፈጸሙ የሰብአዊ መብቶች ጥሰትን አስመልክቶ ያከናወነውን የምርመራ ሪፖርት መስከረም 18 ቀን 2015 ዓ.ም ይፋ ማድረጉ ይታወሳል።
በሪፖርቱ በዝርዝር እንደተመለከተው፤ ከሰኔ 7 እስከ 9 ቀን 2014 ዓ.ም. ሲቪል ሰዎች ላይ የደረሱትን ጉዳቶች አስመልክቶ ኮሚሽኑ ከክልሉ ፖሊስ ኮሚሽን፣ ከክልሉ ሰላምና ጸጥታ ቢሮ፣ ከክልሉ የመንግሥት ኮሙኒኬሽን ጽሕፈት ቤት፣ ከፌዴራል ፖሊስ የምዕራብ መምሪያ ጋምቤላ ቅርንጫፍ ሬጅመንት፣ ከከተማው ማዘጋጃ ቤትና ከጋምቤላ አጠቃላይ ሆስፒታል ስለ ጉዳዩ መረጃና ምላሽ ተቀብሏል።
የፌዴራል ፖሊስ የምዕራብ መምሪያ ጋምቤላ ቅርንጫፍ ለኮሚሽኑ በሰጠው ምላሽ፤ ሰኔ 7 ቀን 2014 ዓ.ም. ኦነግ ሸኔ እና ጋነግ ታጣቂዎች በከፈቱት ውጊያ ከመንግሥት በኩል “የፌደራል ፖሊስ፣ የክልሉ ልዩ ኃይሎችና መደበኛ ፖሊሶች መሳተፋቸውን”፤ እንዲሁም “በውጊያው ወቅት በተወሰነ መልኩ የሰው እንቅስቃሴ በከተማ ውስጥ ስለነበር፤ በበራሪ ጥይቶች የተመቱ ሲቪል ሰዎች ሊኖሩ እንደሚችሉ” ግምት የነበራቸው ቢሆንም፣ “ከውጊያው በኋላ ባደረጉት ማጣራት የክልሉ ልዩ ኃይሎች በተለይ ሰኔ 8 እና 9 ቀን 2014 ዓ.ም. በከተማው በሲቪል ሰዎች ላይ ጥቃት እንዳደረሱ መረዳታቸውን” ገልጸዋል።
አክለውም መረጃው እንደደረሳቸውም ከሚመለከተው የመንግሥት ኃላፊ ጋር በመነጋገር ድርጊቱ መቆም እንዳለበት፣ ጥቃት አድራሾችም በሕግ አግባብ መጠየቅ እንዳለባቸው፣ በድርጊቱም የተነሳ ጥቃት የደረሰባቸው ሰዎች ካሳ እንዲከፈላቸው አቅጣጫ ማስቀመጣቸውን ለኢሰመኮ አስረድተዋል። ከሰኔ 23 ቀን 2014 ዓ.ም. ጀምሮ በክልሉ ፕሬዚዳንት የሚመራ ሕዝባዊ ውይይት ከሀገር ሽማግሌዎች፣ ከክልሉ ምሁራን፣ ከከተማው ነዋሪዎችና የክልሉ የመንግሥት ኃላፊዎች ጋር መደረጋቸውንም ጨምረው አስረድተዋል፡፡
 ሆኖም የሪፖርቱን ይፋ መደረግ ተከትሎ በማኅበራዊ ትስስር ድረ-ገጾችና መገናኛ ብዙኃን የተሳሳተ፣ አነሳሽና ዛቻ ያዘሉ መረጃዎች ሲሰራጩ፤ እንዲሁም በኢሰመኮ ባልደረቦች ላይ ያነጣጠሩ የጥላቻ መልእክቶች ሲዘዋወሩ ቆይተዋል ያለው ኮሚሽኑ፤ ጉዳዩን ከሚመለከታቸው ኃላፊዎች ጋር በመነጋገር መፍታት እንደሚቻል በማመን ምላሽ ከመስጠት ተቆጥቦ እንደነበር ጠቁሟል።
ይሁን እንጂ መስከረም 25 ቀን 2015 ዓ.ም. በቡድን ሆነው የመጡ ሰዎች ወደ ኢሰመኮ ጋምቤላ ጽሕፈት ቤት በመሄድ የተለያዩ የጥፋት ድርጊቶችን የፈጸሙ ሲሆን፣ በኢሰመኮ ባልደረቦች ላይ ዛቻና ማስፈራሪያም አድርሰዋል ብሏል። በተጨማሪም፣ በከተማዋ የተለያዩ የሰብአዊ መብቶች ሥራዎችን በሚያከናውኑ ሌሎች ድርጅቶች ላይ ተመሳሳይ ጥፋት አድርሰው ድርጅቶቹ “ከከተማው ለቅቀው እንዲወጡ” ማስፈራራታቸውን ኮሚሽኑ ጠቁሟል፡፡  
ኮሚሽኑ በሕገ መንግሥት የተቋቋመ ፌዴራል የብሔራዊ ሰብአዊ መብቶች ተቋም መሆኑንና የኮሚሽኑ ሠራተኞችም በአዋጅ የልዩ መብት ጥበቃ የሚደረግላቸው መሆኑን ያስታወሱት የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ፤ “ኮሚሽኑ የክትትልና የምርመራ ሥራውን በሚያከናውንበት ወቅት የተለያዩ ተግዳሮቶች የሚገጥሙት ቢሆንም፤ ይህንን ዐይነት በብሔራዊ ሰብአዊ መብቶች ተቋምና ሠራተኞች ላይ ያነጣጠረ ጥቃት ፈጽሞ ተቀባይነት የሌለውና በክልሉ የሰብአዊ መብቶች አያያዝ ላይ ከፍተኛ አሉታዊ ምልከታ የሚጥል በመሆኑ የፌዴራልና የክልሉ መንግሥት ተባብረው በአፋጣኝ እንዲያስቆሙ ኮሚሽኑ በጥብቅ ያሳስባል” ብለዋል።
ከሰኔ 7 እስከ ሰኔ 9 ቀን 2014 ዓ.ም. በተፈጸሙ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶች ተጎጂዎችና የተጎጂ ቤተሰቦች አሁንም ሟቾች የተቀበሩበትን ቦታ ለማወቅና ፍትሕ ለማግኘት በመጠባበቅ ላይ በመሆናቸው የኮሚሽኑ ምክረ ሃሳቦች በአፋጣኝ እንዲተገበሩም የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ በድጋሚ አሳስበዋል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን ልክ እንደ ደራሲ ስብሐት ልብ ወለድ ባሕሪ፤ እንደ አጋፋሪ እንደሻው፤ ሞትን የሚፈሩና የሚሸሹ አቶ መርኔ የሚባሉ ባላባት ነበሩ፡፡ የሰፈሩ ሰው አብዬ መርኔ እያለ ነው የሚጠራቸው፡፡
አቶ መርኔ ሞትን ለማሸነፍ ሲሉ ወደፊት የሚሆነውን ነገር የሚተነብዩ ኮከብ ቆጣሪዎች ዘንድ ሄደው ያውቃሉ፡፡ ኮከባቸውን አስቆጥረዋል፡፡ የወደፊታቸው ሁኔታ፣ ፍፃሜያቸው ምን እንደሚሆን ለማወቅ ከጅለው፡፡
የመዳፍን መስመር እያዩ የሰውን የወደፊት ዕጣ ፈንታ የሚናገሩ መዳፍ አንባቢዎች ዘንድም ሄደዋል፡፡ ዕጣዬን እዩልኝ ብለው የተለያዩ አዋቂዎችን  ጠይቀው አስነብበዋል።
ሞራ ገላጮች የሚባሉ የሰው መፃዒ ዕድል ተናጋሪዎችም ጋ ሄደው የወደፊት ፍፃሜ ሕይወታቸውን ለማረጋገጥ ሞክረዋል፡፡ የቡና ስኒ አይተው ስለ ዕድል የሚናገሩ ሰዎች ቤትም ሄደው “መጨረሻዬን ንገሩኝ እባካችሁ?” ብለው ተማጥነዋል፡፡
በየመፅሐፍ - ገላጩ ሰፈር እየዞሩ የነገ ሕይወታቸውን አላፊ ዕድሜ ሊያስጠኑ ጥረት አድርገዋል። አብዬ መርኔ ያልሄዱበት ቦታ የለም፡፡
ሁሉም አዋቂዎች የሚሞቱባትን ሣምንት ጠቅሰው፣ ”የፈለጉትን ጥንቃቄ ቢያደርጉም፤ የሚሞቱት በእሾህ ተወግተው ነው!” ሲሉ ነገሩዋቸው፡፡
አብዬ መርኔም በልባቸው፤
“እንዲያማ ከሆነ እኔ እሾክ የደረሰበት አልደርስም! እንዲያውም ከእነአካቴው ከቤቴ አልወጣም” ይሉና በነዚያ በተጠቀሱት ቀናት እቤታቸው ክትት ብለው ሰነበቱ፡፡
ከተባሉት አንድ ቀን ብቻ ነው የቀራቸው፡፡ ቤታቸው በረንዳ ላይ ተቀምጠው አላፊ አግዳሚውን የሰፈራቸውን ሰው ሰላም እያሉ፣ “እንዴት ሰነበትክ ?” ሲሉ አመሹ፡፡
ወደ ቤታቸው ሊገቡ ጥቂት ሲቀራቸው፣ የከብት እረኛቸው፣ ላሞችና በጎች እየነዳ መጣ፡፡
አብዬ መርኔ ከግልገልነቱ ጀምሮ ያሳደጉትን በግ አዩ፡፡ በጣም ደስ አላቸው፡፡ በጉ ያውቃቸዋልና እየሮጠ ወደሳቸው መጣ፡፡ እያሻሹ ሲያጫውቱት ድንገት በፀጉራም ቆዳው ውስጥ የነበረ አንድ እሾክ መዳፋቸውን ጠቅ አደረጋቸው! ደማቸው ክፉኛ ፈሰሰ፡፡ ቁስሉ አልሽር አለ፡፡ ለካ ያ እሾክ መርዝነት ያለው ኖሮ፣ ብዙም ፋታ ሳይሰጣቸው ለሞት አበቃቸው!
“ዓለም አላፊ ነው
መልክ ረጋፊ ነው
ፎቶግራፍ ቀሪ ነው!”
ይላሉ የጥንት ሰዎች፡፡ ከተፃፈልን ቀን አናልፍም፡፡ የዕጣ-ፈንታችን ነገር ነው፡፡ በሕይወት የምንኖርባትን እያንዳንዷን ደቂቃ እንጠቀምባት እንጂ ነገን አንጠብቅ፡፡ በእጃችን ያለውን ወርቅ ቀን ሳንውል ሳናድር እጥቅም ላይ እናውለው፡፡
ሀገራችን የጦር አውድማ ከሆነች አያሌ ዓመታት  ተቆጥረዋል። ስደት እንደ አዘቦት ቀን ልብስ ከተዘወተረ ከራርሟል። መፈናቀልና ቀዬን ለቅቆ መሄድ ወረት መሆን ከተወ ቆይቷል። ይሄም ያልፋል እያሉ እጅን አጣጥፎ መቀመጥ ሞኝነት ሆኗል። መንግሥትም፤ “የበላችው አቅሯታል፣ በላይ በላዩ ያጎርሳታል!” እንደሚባለው፤ ነጋ ጠባ የማይፈጸም ቃል መግባቱን ቀጥሎበታል። “ለምን አልፈጸምክም?” ብሎ መንግስትን አፋጥጦ ለመጠየቅ ህዝብ ወኔ አጥቷል። አሊያም በተደጋጋሚ በደረሰበት ውስብስብ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ ምስቅልቅል፣ ቁምስቅሉን እያየ፤ ያረገው ነገር ቸግሮታል። አንገቱን ደፍቷል!
ያውቃሉ የተባሉት ምሁራንም ዱሮ ይባል እንደነበረው፡-
“እናውቃለን። ብንናገር እናልቃለን!” የሚሉ ይመስላል። ወይም ፍርሐት ቤቱን ሰርቶባቸዋል። ረዥም ዕድሜን ከዘለዓለማዊነት እያምታቱ (They took longevity for eternity እንዲሉ)፣ ያልፍልናል እያሉ ራሳቸው ያልፋሉ! የእርግማን እስኪመስልባቸው ድረስ አድር-ባይነትን፣ ስግብግብነትን፣ ሁሉን ለእኔነትን ተያይዘውታል! የሩቅ ምስራቅ ጠበብት፤”የአንድ ህብረተሰብ ጥንካሬ በምሁሩ መዓዛ ሽታ ይለካል” የሚሉት ብሂል፣ ለሀገራችን ምሁራንም መጠቀስ ያለበት ሀቅ ነው ብንል ከማጋነን አይጣፍብንም፡፡ በሌላ ጎኑ ደግሞ ከተፈጥሮም ጋር ትግል ይጠበቅብናል። ጎርፍ፤ ድርቅና የአየር መዛባት በተደጋጋሚ አባዜው አልለቀን ስላለ ለከባድ ቸነፈር እና ርሀብ መጋለጣችን በየአስርት ዓመቱ የምናየው ክፉ እጣ መስሎብናል፡፡ ይህን የሚቋቋም ብርቱ ጫንቃ ያለው ትውልድ ከመፍጠር ይልቅ፤ “ጦርነቱ አገርሽቷል” የሚል ዜና የሚያዳምጥ ማህበረሰብ አቅፈንና አዝለን፤ መቀመጥን ሥራዬ ብለን ረዥም መንገድ ዳክረናል!
አሁን፤ያለፈው ይበቃን ዘንድ ወደፊት ለመራመድ መቁረጥ አለብን፡፡ የመለወጥ/ድፍረቱ ሊኖረን ይገባል፡፡ ድህነትንም ሆነ ድህነትን የሚያመጣብንን ሁሉ ለመቋቋም መነሳት ግድ ነው። በአንድ በሀገር ጉዳይ ሁላችንም ተጠያቂ መሆናችንን አንርሳ። ያየነውን አይተናል ለማለትና እንከንም ካለበት ለመጠቆም፤ ለመዋጋት ወደ ኋላ አንበል፡፡ እንድፈር፤ እንነጋገር፡፡
“አሁን ለምንድነው፤ ፈሪ ማቀንቀኑ
ቅጠል አይበጠስ፤ ካልደረሰ ቀኑ!”
ያሉ አባቶች ያቆዩዋት አገር እንደሆነች አንርሣ! መንገድ ካልጀመሩት አይገፋም፤ ወንበር ካልያዙት የማንም መቀመጫ ነው! ለሁሉም በዚህ ዘመን፤ ልብና ልቦና ይስጠን!

(ድምጻዊ ማዲንጎ አፈወርቅ ሦስተኛ አልበሙን ሲያወጣ የዛሬ 7 ዓመት ከአዲስ አድማስ ጋር ያደረገው ቃለ ምልልስ)


በባህር ዳርና በአዲስ አበባ ከ15 ዓመታት በላይ በምሽት ክበቦች
ሰርቷል፡፡ “ስያሜ አጣሁላት” በሚለው የመጀመሪያ አልበሙ ከህዝብ ጋር
የተዋወቀው ድምፃዊ ማዲንጎ አፈወርቅ፤ሦስተኛ አልበሙን (ስወድላት) ሰሞኑን
ለቋል፡፡ በአዲሱ ስራውም ስለ ሃገር፣ስለ ፍቅር፣ ስለ ታማኝነት፣ ስለ ጎንደር፣
ስለ ወሎና ምንጃር ብዙ አቀንቅኗል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት
ዮሴፍ፤ ከድምፃዊ ማዲንጐ ጋር በአዲሱ አልበሙና በሙያው ዙሪያ ተከታዩን
ቃለ ምልልስ አድርጋለች፡፡

የመጀመሪያ ስራህ “ስያሜ አጣሁላት” የሚል ነበር፡፡ በሁለተኛው “አይደረግም” ብለህ መጣህ፡፡ አሁን ደግሞ “ስወድላት” እያልክ ነው…
የመጀመሪያው አልበሜ የልጅነት ስራዬ ነው፡፡ ያኔ ጠቆር ያልኩ ነበርኩኝ፤ እንዳሁኑ አልገፈፍኩም ነበር፡፡ አሁን እንደ እባብ ቆዳ ቀይሬያለሁ፡፡ የሆነ ሆኖ “ስያሜ አጣሁላት” በልጅነት እድሜ ከህዝብ ያገናኘኝ ስራ ነው፡፡ ወቅቱ የኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ነበር፡፡ ታዲያ “ስያሜ አጣሁላት” እና “አማን ነው ወይ ጎራው” የተሰኙት ሁለት ዘፈኖች በተለየ መልኩ ተወደውልኝ ነበር፡፡ ሁለተኛው ስራዬ የትዝታ ዘፈን ያለበት “አይደረግም” በሚል ስያሜ የወጣው ነው፡፡ አሁን “ስወድላት”ን ይዤ ወደ አድማጭ ቀርቤያለሁ፡፡
በኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት “ስያሜ አጣሁላት” እና “አማን ነው ወይ ጎራው” የተወደዱበት ምክንያት ምንድን ነው? ከጦርነቱ ጋር የተገናኘ ሃሳብ ይዘዋል እንዴ?
በተለይ “ስያሜ አጣሁላት” ከኤርትራ ጠብ አጫሪነት ጋር ሳይያያዝ አይቀርም፡፡ እኔ በወቅቱ እንደነገርኩሽ ልጅ ስለነበርኩ ጉዳዩ አይገባኝም ነበር፡፡ ግጥሙን የፃፈው አንጋፋው የሙዚቃ ግጥም ደራሲ ይልማ ገ/አብ ነበር፡፡ ይልምሽ ደግሞ ወቅታዊ ፈጠራዎችን በመስራት አይታማም፡፡ አሁን ነው የሚገባኝ፡፡ እኔ ከሴት ልጅ ፍቅር ጋር ብቻ ነበር አገናኝቼ የዘፈንኩት። በነገራችን ላይ አሁንም ቢሆን ግጥሙ ከወቅቱ ጦርነት ጋር እንዲሄድ ሆን ተብሎ ይሰራ አይሰራ እርግጠኛ አይደለሁም፡፡ ግምቴን ነው የነገርኩሽ፡፡
ሁለተኛው አልበምህ “አይደረግም” የሶስት አራት ድምፃዊያንን ትዝታ አፈራርቀህ የሰራህበት ሲሆን የትዝታው ዘፈን ድምፅህ የተፈተነበትና ወደ አድማጭ በደንብ የቀረብክበት እንደሆነ ይነገራል፡፡ እውነት ነው?
በጣም ትክክል ነው፡፡ እኔም ባለውለታዬ የምለው ዘፈን ትዝታው ነው፡፡ የእኔ የመዝፈን ብቃት ምን ያህል እንደሆነ ለህዝብ ግልፅ ያደረገ ስራ በመሆኑ በሚባለው ነገር መቶ በመቶ እስማማለሁ፡፡
“አይደረግም” ከወጣ ረዘም ያለ ዓመት ሆኖታል… ባልሳሳት ሰባት ዓመት አካባቢ… ለምን እንደዚህ ቆየህ?
ተቃርበሻል! ስምንት ዓመት አልፏል፤ አልበም ሳልሰራ፡፡ በመሃል ግን የተሳኩና የተወደዱ ነጠላ ዜማዎችን ሰርቻለሁ፡፡ ለምሳሌ “የበላይ ዘለቀ”፣ “አንበሳው አገሳ”፣ ለ“አባይ ወይስ ቬጋስ” ፊልም የሰራሁት ማጀቢያ ሙዚቃ “አባይ ወይስ ቬጋስ”---ህዝቡ ስምንት ዓመት አልበም አለመስራቴን እንዳያስታውስ አድርገውታል፡፡ ከህዝብ ጆሮ አልጠፋሁም ነበር ማለት ነው፡፡ በዚያ ላይ ኮንሰርቶች እሰራለሁ፤ የሰርግ ስራዎችንም እንደዚሁ፡፡ ይህን ስታይው ስምንት ዓመት ሙሉ የጠፋሁ አይመስልም፡፡ ከዚህ በኋላ ግን እንደዚህ አልጠፋም፤ በየሁለት አመቱ አልበም ይኖረኛል፡፡
አዲሱ አልበምህ በግጥማና ዜማ የነማን አስተዋፅኦ አለበት? ምን ያህል ጊዜስ ወሰደ?
በመጀመሪያ ደረጃ የአልበሙን ስራ ኃላፊነት ሙሉ በሙሉ የወሰድኩት እኔ ነኝ፡፡
ምን ማለት ነው?
ይሄ ማለት ግጥምና ዜማ የመምረጡን ስራ ያለምንም ጣልቃ ገብነት የተወጣሁት እኔው ነኝ፡፡ ከልጅነቴ ጀምሮ ሙዚቃ ውስጥ እንደመሆኔ፣ ግጥምና ዜማን በማስተዋል በኩል ጥሩ ተሰጥኦ አለኝ ብዬ አምናለሁ፡፡ የአልበሙን ግጥምና ዜማ የመረጥኩት ራሴ ነኝ፡፡ ነገር ግን ግጥምና ዜማ እንዲሰሩ ትልልቅ የሚባሉና የካበተ ልምድ ያላቸውን ሰዎች አሳትፌአለሁ። ይልማ ገ/አብ፣ ጸጋዬ ደቦጭ፣ አበበ ብርሃኔ፣ አማኑኤል ይልማ፣ ታመነ መኮንን፣ አህመድ ተሾመ (ዲንቢ)፣ መኮንን ለማ (ዶክተሬ) እና መሰል ታዋቂዎች ተሳትፈዋል፡፡ ላለፉት ስምንት ዓመታት የተለያዩ ግጥምና ዜማዎችን ስሰበስብና ስመርጥ ነው የቆየሁት፡፡ 30 ዘፈኖች መረጥኩና ስቱዲዮ ተቀረፅኩ፤ ከ30ው ግን 14ቱን ነው የመረጥኩት፡፡ 14ቱም ዘፈኖች አንዱ ከአንዱ እንዳይበልጥና በጥሩ ሁኔታ እንዲደመጥ ከፍተኛ ጥንቃቄና ጥረት አድርጌያለሁ፡፡ እነዚህ ዘፈኖች የቀደመውን (የወርቃማውን ዘመን) የሙዚቃ ደረጃ እንዲይዙ ነው የፈለግሁት፡፡
የወርቃማው ዘመን ድምፃዊያን የሚባሉት እነማን ናቸው? የአሁኑ አልበህም ያስቀመጥከውን ደረጃ አሳክቷል ብለህ ታስባለህ?
ኤፍሬም ታምሩ፣ ንዋይ ደበበ፣ ፀጋዬ እሸቱ፣ አረጋኸኝ ወራሽ ያሉበት ዘመን  ለእኔ ወርቃማውና የምወደው ዘመን ነው፡፡ እኔም ያን ዘመን ሊያስታውሱ የሚችሉ በሳል ዘፈኖችን ከአሁኑ ትውልድም እንዳይርቁ አድርጌ ሰርቻለሁ፡፡ አልበሙ ሰሞኑን ነው የወጣው፤ በእነዚህ ጥቂት ቀናት ውስጥ የደረሰኝ የአድማጮች አስተያየትና ምላሽ ያለምኩትን ግብ እንደመታሁ አመላካች ነው ብዬ አምኜያለሁ፡፡
በአንድ ወቅት አልበም ማሳተም ተቀዛቅዞ ነበር፡፡ አሁን አሁን ዘፋኞች ደፈር እያላችሁ የመጣችሁ ትመስላላችሁ?
ልክ ነው፤ የአልበም ስራ የተኛበት ጊዜ ነበር፡፡ ይሄ የቅጂ መብት ጉዳይ ዘፋኙንም አሳታሚውንም ተስፋ አስቆርጦት ነበር፡፡ አሁን እነ ሸዋንዳኝ፣ እነ ሚካኤል በላይነህ፣ እነ ታምራት ደስታ፣ እነ አብነትና ሌሎችም ደፍረው አልበም በማውጣታቸው ሌሎቻችንን አበረታተውናል። አሁን ሰውም ኦሪጂናል አልበም የመግዛት ፍላጎቱ እየጨመረ መምጣቱን ያወቅሁት፣ የእኔ አልበም በወጣ በሶስተኛው ቀን እንኳን በጥሩ ሁኔታ በመሸጥ ላይ መሆኑን ስመለከት ነው፡፡
አልበሙን ሰርቶ ለማጠናቀቅ በትክክል ምን ያህል ጊዜ ፈጀብህ?
ግጥምና ዜማ መምረጥ የጀመርኩት ከስምንት ዓመት በፊት ነው፡፡ ነገር ግን ወደ ስቱዲዮ መግባትና ስራውን በደንብ መስራት የጀመርኩት ከአምስት ዓመት በፊት ነው፡፡ ያልገባሁበት ያልወጣሁበት ስቱዲዮ የለም፡፡
ለምንድነው በየስቱዲዮው እየገባህ የወጣኸው?
ያሉትን ግጥምና ዜማዎች ይዤ ስራውን እጀምራለሁ፤ ነገር ግን መርካት አልቻልኩም። አንድ ስራ ይዤ እገባና አያስደስተኝም ትቼ እወጣለሁ፡፡ ይህን ሳደርግ በራሴ የገንዘብ ኪሳራ ነው፤ ዛሬ አንድ ዘፈን ለመስራት ከ20 ሺህ ብር በላይ ይጠይቃል፡፡ ቅንብር 10 ሺህ ብር፣ ግጥምና ዜማ በቀላሉ 10 ሺህ ብር ወጪ ይጠይቃሉ። ሌሎች ጥቃቅን ወጪዎችን ሳይጨምር ማለት ነው፡፡ ከኤሌክትራ ሙዚቃ ቤት ጋር የዛሬ ስድስት ዓመት ነው የተፈራረምኩት። ስንፈራረም ግን በራሴ ስራውን አጠናቅቄ ማስተሩን ላስረክበው ተስማምተን ነው፡፡ ይሄ ማለት ዜማ፣ ግጥም ቅንብር… እያንዳንዱ ወጪና ልፋት በእኔ ላይ ነበር፡፡ ታዲያ ከስድስት አመት በፊት የነበረው ዋጋና የአሁኑ ልዩነቱ ሰማይና ምድር ነው፡፡ በዚያ ላይ ስቱዲዮ ገብቼ ጀምሬ የተውኳቸው አሉ፡፡ ያ ኪሳራ በራሴ ነው፡፡ ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ 30 ዘፈን ሰርቼ፣ 14ቱን ብቻ ነው የመረጥኩት፡፡ 16ቱ ቀሩ ማለት ነው፡፡
ታዲያ ምን ያህል ወጪ ወጣበት አዲሱ አልበምህ?
ያለማጋነን ከ500 ሺህ ብር በላይ አውጥቻለሁ፤ ሆኖም ለህዝብ ጆሮ የሚመጥን ስራ እንደሰራሁ ይሰማኛል፡፡ ራሴን በጣም አስደስቶኛልና፡፡
ከአንተና ከእህትህ ትዕግስት አፈወርቅ ሌላም ታናናሽ ድምፃዊ እህትና ወንድሞች አሉህ ይባላል፡፡ እንደነ አምስቱ እርጎዬዎችና እንደነ ጃክሰን ፋሚሊ “የአፈወርቅ ቤተሰቦች” ለመባል እየተቃረባችሁ ነው ወይስ?
እኛ እንኳን የአፈወርቅ ቤተሰቦች ለመባል አልበቃንም፤ ምክንያቱም በሙዚቃው ነጥረን የወጣነው እኔና ትዕግስት ብቻ ነን። አንድ ወንድሜ ፍላጎት ስላለው በመሞከር ሂደት ላይ ነው፡፡ ካናዳ ነው የሚኖረው፡፡ ጂጂ የምትባለው የታናሼ ታናሽ በጣም የሚገርምና የሚመስጥ ድምፅ አላት፤ ነገር ግን ዘማሪ መሆን ነው የምትፈልገው፡፡ አሁን እንግሊዝ ነው የምትኖረው፤ ስለዚህ የአፈወርቅ ቤተሰቦች ለመባል አልደረሰንም፡፡ እኔና  ትዕግስት ግን ወደፊት አስተዳደጋችንን፣ ባህላችንን የሚያሳይ አንድ ዘፈን የመስራት ሃሳብ አለን፡፡
ብዙ አድናቂዎች እንዳሉህ ይታወቃል፡፡ አንተስ የማን አድናቂ ነህ?
ኢትዮጵያ የቅዱስ ያሬድ አገር ናት፡፡ በቤተ ክርስቲያን ስትቀርቢ ዜማ ማህሌትና የመሳሰሉት ያስደምሙኛል፡፡ ወደ ዘፈኑ ስትመጪ አገራችን ብዙ አንጋፋና ተሰጥኦ ያላቸው ድምፃዊያንን አፍርታለች፤ ከእነ ጥላሁን ገሰሰ ጀምሮ፡፡ እኔ ሞዴል ብዬ የያዝኩትና ወደ ሙዚቃው እንድገባ የተሳብኩት በኤፍሬም ታምሩ ነው፤ በጣም ነው የምወደው፡፡ ሙሉቀን መለሰን፣ ቴዎድሮስ ታደሰን፣ እነ ጸጋዬ፣ አረጋኸኝ… እንዲሁም ቀደም ሲል ወርቃማው ዘመን ላይ የነበሩ ብዬ የገለፅኩልሽን በሙሉ አደንቃለሁ፡፡ ቀደም ካሉት ፍሬው ኃይሉ የቤተ-ክህነት አይነት ድምፅ ስላለው እወደዋለሁ፡፡ ከወጣቶች ጎሳዬ፣ ብዙአየሁ፣ አብነት፣ ቴዲ አፍሮን አደንቃለሁ፡፡
ግጥምና ዜማ ድርሰት ላይ እንዴት ነህ?
ባለፈው አልበም ላይ “አፋር” የተሰኘውን ዜማ ሰርቻለሁ፡፡ “ማን እንደኔ ንገሪኛ”፣ “አባይ ወይስ ቬጋስ” እና “አንበሳው አገሳ” የኔ ዜማዎች ናቸው፤ ዜማ ላይ ምንም አልልም። ግጥም ግን ሰርቼ አላውቅም፡፡ በአሁኑ አልበሜ ላይ በዜማም አልተሳተፍኩም፤ ሁሉንም በሌሎች ባለሙያዎች ነው ያሰራሁት፡፡
በአዲሱ አልበምህ እስካሁን ከመጡት አስተያየቶች በጣም ያስደመመህ አለ?
ያው ብዙ አስተያየቶች ይመጣሉ፡፡ በአብዛኛው አድናቆትና ማበረታታት ናቸው። አንድ ሰው ግን ደውሎ “ለገና ለበግ መግዣ ያስቀመጥኩትን ብር የአንተን ሲዲ እየገዛሁ ለወዳጅ ዘመድ አድዬበታለሁ፤ በጉን አንተ ግዛልኝ” ብሎኛል፡፡ በጣም ገርሞኛል፡፡ አንዳንዴ ሰው ሲወድሽ እንዲህ ሁሉ ያደርጋል፡፡ ሌላው ችሎታህን በአሁኑ አልበም ላይ በአግባቡ ተጠቅመሃል የሚል አበረታች አስተያየት ነው፡፡
ታዲያ ምን አሰብክ… በጉን ትገዛለታለህ?
 እገዛለታለሁ፡፡ ይሄ ሰው እኮ ሲዲውን ሲገዛ ገንዘቤ በተዘዋዋሪ እኔው ኪስ ገብቷል፡፡ ስለዚህ ደስ እያለኝ እገዛለታለሁ፡፡
በመጨረሻስ….
በመጨረሻ እንግዲህ ይሄ አልበም እንዲህ አምሮ እንዲወጣ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ላደረጉት የግጥምና ዜማ ደራሲዎች አመሰግናለሁ። የተለያዩ ጉዳዮችን በማስጨረስ ድካሜን ሲያቀልልኝ የነበረው የአቻሬ ጫማ ባለቤት (አቻሬ) ሳላመሰግነው አላልፍም፡፡ አቀናባሪ ሙሉጌታ አባተና ኤልያስ መልካ፣ እህቴ ትዕግስት አፈወርቅን፣ ማርታ ዘለቀን፣ አህመድ ተሾመንና ሌሎችም በመዘንጋት ስማቸውን ያላነሳሁትን ሁሉ በጣም አመሰግናለሁ፡፡ የሙዚቃው ኢንዱስትሪ በደከመበት በአሁኑ ወቅት ከጎኔ ሆኖ የክብር ስፖንሰር የሆነኝን ዳሽን ቢራንና የኤሌክትራ ሙዚቃ ቤት ባለቤትን አቶ ተሾመ ፀጋዬን እንዲሁም በአስተያየት እየኮተኮተ ያሳደገኝን የኢትዮጵያን ህዝብ በጣም አመሰግናለሁ፡፡ እግዚአብሔር ለሁሉም ብድሩን ይክፈልልኝ እላለሁ፡፡ ለመላው የክርስትና እምነት ተከታዮች እንኳን የገናን በዓል በሰላም አሳለፋችሁ፤ መጪው የጥምቀት በዓል የምትደሰቱበት ይሁን እላለሁ፤ አመሰግናለሁ፡፡

በኮሎኔል አሸብር አማረ የተፃፈው ሀገሬና ሕይወቴ መፅሀፍ መስከረም 14 ቀን 201 ዓ.ም በሂልተን ሆቴል ተመርቋል፡፡
627 ገጾች የያዘ ግለ ታሪክ በ405 ብር ገበያ ላይ ውሏል፡፡

ባለፈው ማክሰኞ መስከረም 17 ቀን 2015 ዓ.ም ለህክምና በራሱ አውቶሞቢል ወደ ክሊኒክ ሄዶ በዚያው ህይወቱ ያለፈው የድምጻዊ ማዲንጎ አፈወርቅ የአሟሟት መንስኤ እስካሁን ያልታወቀ ሲሆን፤ ፖሊስ ተጨማሪ ምርመራ በማድረግ ላይ መሆኑን መግለጹ ይታወሳል፡፡ በሳምንቱ መገባደጃ በተሰማው መረጃ፤ የድምጻዊው ደም ለምርመራ ወደ ጀርመን የተላከ ሲሆን ውጤቱ ሲደርስ ለህዝብ ይፋ እንደሚደረግ ተጠቁሟል፡፡  
ይህ በዚህ እንዳለ የድምጻዊው የቀብር ስነ-ስርዓት በመንበረ ጸባኦት ቅድስተ ሥላሴ ካቴድራል ከትላንት በስቲያ በታላቅ አጀብና ክብር የተከናወነ ሲሆን በሥርዓተ-ቀብሩ ላይ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ፓትርያርክ ርዕሰ ሊቃነ ጳጳሳት ዘኢትዮጵያ ሊቀጳጳስ ዘአክሱም ወእጨጌ ዘመንበረ ተክለሃይማኖት፣ ምክትል ጠ/ሚኒስትርና የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንንን ጨምሮ ከፍተኛ የመንግስት ባለሥልጣናት፣የድምጻዊው ቤተሰቦች፣ ታላላቅ አርቲስቶችና የሙያ ባልደረቦች፣ እንዲሁም ወዳጆችና አድናቂዎች ተገኝተዋል።
የ17 ዓመት ሴት ልጁ ዲቦራ ማዲንጎ የአባቷን ህልፈት ተከትሎ ለመገናኛ ብዙሃን በሰጠችው ቃል፤ “ማዲንጎ አፈወርቅ ቤተሰቡን የሚወድና ለቤተሰቡ ትልቅ ፍቅርና እንክብካቤ የሚያደርግ አባት ነበር።” ብላለች።
አባቷ ለሃገሩም ይሁን ለወገኑ ትልቅ ሥራ የሰራ ሰው መሆኑን የገለጸችው ዲቦራ፤ ዘመን ተሻጋሪ ሥራ ሰርቶ በማለፉ ከማዘን ይልቅ እንደምትኮራበት ተናግራለች። “አባቴ ለሃገርና ለህዝብ መሥራትን አስተምሮኛል” ትላለች - ዲቦራ።
ከቀብር ስነ-ስርዓቱ በኋላ በመኖሪያ ቤቱ ተገኝተው ቤተሰቡንና ሃዘንተኛውን ያጽናኑት የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ-ክርስትያን መምህር ምህረተአብ፣ ከማዲንጎ ጋር ቅርርብ እንዳላቸው ጠቁመው፤ በህይወት ሳለ ድሆችን በመርዳት እንደሚታወቅም ጠቆም አድርገዋል። አርቲስት  ዮሴፍ ገብሬ (ጆሲ) በበኩሉ፤ ማዲንጎ በቋሚነት የሚረዳቸው 300 ያህል ሰዎች እንዳሉ ሰሞኑን ለመገናኛ ብዙሃን ምስክርነቱን ሰጥቷል፡፡  
ድምጻዊ ማዲንጎ ከሰይፉ ጋር በኢቢኤስ ባደረገው ቃለ-ምልልስ፤ ለሱ  ትልቅ ደረጃ መድረስ የወላጆቹ ሚና አይተኬ መሆኑን በመጠቆም፤ መኪና ከመግዛቱ በፊት የወላጆቹን ውለታ መመለስ እንዳለበት ወስኖ እንደነበር አውስቷል። ውሳኔውንም በትክክል መተግበሩን ተናግሯል።
ከዚህም ባሻገር ለታናናሽ ወንድም እህቶቹም ድጋፍ ሆኖ ለቁም-ነገር  አብቅቷቸዋል- ወላጆቹ እሱን ለቁም ነገር እንዳበቁት።
የሙዚቃ ሃያሲው ሰርፀ ፍሬ ስብሃት ስለ ድምፃዊ ማዲንጎ ተጠይቆ በሰጠው አስተያየት፤ መጀመሪያ የተዋወቁት አዲስ ነገር ጋዜጣ ላይ “ማህደረ ቅኝት ማዲንጎ አፈወርቅ” በሚል ርዕስ በጻፈው መጣጥፍ እንደነበር ያስታውሳል፡፡
“እዛ አርቲክል ውስጥ ምስጋናና አድናቆት ብቻ አልነበረም ያለው፡፡ ጥቂት ትችቶችም ነበሩት፡፡ እውነቴን ነው የምልሽ፤ ማዲንጎን ይበልጥ እንዳከብረው ያደረገኝ ደግሞ እነዛን ትችቶች የተቀበለበትና ያስተናገደበት መንገድ ነው፡፡ አየሽ ማዲንጎ ሁሉም ሰው አድናቆት የሚሰጠው ሰው ስለሆነ፤የእኔንም አድናቆት መቀበሉ አይደለም የደነቀኝ፡፡ ቢሻሻሉ ብዬ ያሰብኳቸውንና ከፕሮዳክሽን ጥራት አኳያ ያነሳኋቸውን ሀሳቦች የበለጠ ዋጋና ትኩረት ሲሰጣቸው ሳይ እጅጉን ተደነቅሁ” ብሏል፤ ሰርፀ ፍሬ ስብሃት፡፡
ማዲንጎ የሚጫወታቸው ሙዚቃዎች ያስገርሙኛል የሚለው ሰርፀ፤ በነገራችን ላይ ማዲንጎ አንድ አልበም ለመስራት እስከ 30 እና 40 ግጥሞችና ዜማዎች ነው የሚገዛው፡፡ ይህን የሚገዛው ከተለያዩ ሰዎች ሲሆን መጨረሻ ላይ ተጨምቀው 12ቱ ብቻ በአልበም ይወጣሉ፡፡ የተቀሩት በሙሉ ገንዘብ ወጥቶባቸው ይቀራሉ” ሲል የታዘበውን ተናግሯል፡፡
ድምጻዊ ማዲንጎ አፈወርቅ ሶስተኛ አልበሙን ሲያወጣ የዛሬ 7 ዓመት ግድም ከአዲስ አድማስ ጋር ባደረገው ቃለምልልስ፤ በአልበሙ ውስጥ የተካተቱት ዘፈኖች የቀደመውን የወርቃማውን ዘመን የሙዚቃ ደረጃ እንዲይዙ አድርጌ ነው የሰራሁት ብሎ ነበር። ለማዲንጎ የወርቃማው ዘመን ድምጻውያን እነ ኤፍሬም ታምሩ፣ ንዋይ ደበበ፣ ሙሉቀን መለሰ፣ ፀጋዬ እሸቱ፣ አረጋኸኝ ወራሽ የመሳሰሉት ያሉበት ዘመን ሲሆን፤”ለእኔ ወርቃማውና የምወደው ዘመን ነው” ሲል ተናግሮ ነበር። በእርግጥም ገና ታዳጊ ህፃን ሳለ ነው የእነዚህን አንጋፋ ድምጻውያን ሥራዎች በማቀንቀን ወደ ሙያው የገባው። የሴት ድምጻውያንን ዘፈኖች ሳይቀር እያስመሰለ ይዘፍን እንደነበር በአንድ ወቅት ተናግሯል። የኢቢኤሱ ሰይፉ ፋንታሁን ሰሞኑን በዩቲዩብ በለቀቀው ቪዲዮ፤ ማዲንጎ የ14 ዓመት ልጅ ሳለ መድረክ ላይ የኤፍሬም ታምሩን “እስቲ እንዴት ነሽ” የተሰኘ ዜማ ሲያቀነቅን ይታያል፤ ህዝብ በተሰበሰበበት አዳራሽ።   
ድምፃዊው ከሰይፉ ጋር በነበረው ቃለ-ምልልስ፤ እስከ 10 ዓመቱ ድረስ አባቱ ባወጡለት “ተገኔ” የሚል ስም ሲጠራ ቆይቶ ማዲንጎ የሚለውን ስም ወታደር ቤት እንዳወጡለትና ስሙ በቀላሉ የሚያዝ በመሆኑ በዚያው እንደጸና ይገልጻል - የሚወደው ግን አባቱ ያወጡለትን ተገኔ የሚለውን ኢትዮጵያዊ ስም መሆኑን በመጠቆም።
የመጀመሪያ አልበሜ የልጅነት ሥራዬ ነው ሲል በአዲስ አድማስ ቃለ ምልልስ የተናገረው ማዲንጎ፤ “ያኔ ጠቆር ያልኩ ነበርኩኝ፤ እንዳሁን አልፈገግኩም ነበር። አሁን እንደ እባብ ቆዳ ቀይሬአለሁ” ብሏል፤ በራሱ እየቀለደ፡፡
አፈወርቅ በአገር ወዳድነቱ አይታማም - መለያ መታወቂያው ነው። ከልጅነቱ አንስቶ በሙዚቀኛነት በወታደር ለቤት ማደጉን የሚያወሳው አርቲስቱ፤ ይህም አገሩን ወዳድና ሰውን አክባሪ እንዳደረገው በተለያየ ወቅት ባደረገው ቃለ-ምልልስ ተናግሯል። የአማፂው የህወሓት ቡድን በኢትዮጵያውያን ላይ ጦርነት መክፈቱን ተከትሎ፣ ድምፃዊው ግንባር ድረስ ሄዶ የሰራዊቱ አለኝታነቱን አስመስክሯል - የመከላከያ ሀላፊዎች እንደመሰከሩት፡፡ ለዚህም አስተዋፅኦው ከጠ/ሚኒስትር ዐቢይ እጅ የምስጋናና የዕውቅና ሰርተፊኬት ተቀብሏል።
የመከላከያ  ሚኒስቴር የሕዝብ ግንኙነት ዳይሬክተሩ ኮሎኔል ጌትነት አዳነ በማዲንጎ ስንብት ላይ ባደረጉት ንግግር “ማዲንጎ በህይወት በነበረ ጊዜ ከሄደና ከመጣው ስርዓት ጋር ጎንበስ ቀና የሚል ሳይሆን የሀገርና የህዝብ አለኝታ ከሆነው የሀገር መከላከያ ሰራዊት ጋር በመቆም ሀገሩንና ወገኑን በሀቀኝት ከልጅት እስከ እውቀት አገልግሏል” ሲሉ መስክረውለታል።
በሌላ በኩል፤ ድምፃዊው ከህልፈቱ በፊት ለሰባት ዓመታት የደከመበትና የለፋበትን አራተኛ አዲስ አልበሙን ሰርቶ ማጠናቀቁን ለማወቅ ተችሏል።
“ብሩህ ነፀብራቁ፣
ውበትና ድምፁ፣አንድነት ተሰምተው
አንድነት ቢበርቁ
የሚያውቅለት ጠፍቶ
ሚስጢሩን አካቶ
ተወርዋሪ ኮከብ፣በራሱ ነበልባል፣በራሱ
ነዲድ ላይ ተቃጥሎ የጠፋ
ተወርዋሪ ኮከብ፣በምናውቀው ሰማይ ነበረ
በይፋ፡፡”
በማለት ታላቁ ገጣሚ ዮሐንስ አድማሱ ከተቀኘላቸው ተወርዋሪ ኮከቦች መካከል ድምፃዊ ማዲንጎ አፈወርቅ አንዱ ነው ብንል ማጋነን አይሆንም፤ ይላል ከትላንት በስቲያ በሥርዓተ ቀብሩ ላይ በተዋናይና ጋዜጠኛ ተፈሪ ዓለሙ የተነበበውና በህይወት ታሪኩ ላይ የሰፈረው መግቢያ፡፡


ኦነግ ሸኔ እና በአማራ ኢ-መደበኛ ታጣቂዎች  100 ሰላማዊ ሰዎች ተገድለዋል
በጋምቤላው ውጊያ  የፀጥታ ኃይሎች ቢያንስ 50 ሰላማዊ ሰዎች ገድለዋል
መንግስት የሲቪል ሰዎችን ደህንነት የማስጠበቅ ግዴታውን በአግባቡ መወጣት ይኖርበታል

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን (ኢሰመኮ)፤ በኦሮሚያ ክልል፣ ሆሮጉዱሩ ወለጋ በአሙሩ ዞን፣ በሆሮ ቡልቅ እና በጃርደጋ ጃርቴ ወረዳዎች፣ ከነሐሴ 25 ቀን 2014 ዓ.ም. ጀምሮ ባሉት ሦስት ሳምንታት ውስጥ ብቻ በኦሮሞ ነጻነት ሰራዊት (በተለምዶ ኦነግ ሽኔ)፣ በአማራ ኢ-መደበኛ ታጣቂ ኃይሎችና ግለሰቦች በተከታታይ በተፈጸሙ ጥቃቶች ከ100 በላይ ሰላማዊ  ሰዎች መገደላቸውን መስከረም 16 ቀን 2015 ዓ.ም  ባወጣው መግለጫ አስታውቋል፡፡
ከግድያው በተጨማሪ የግል ንብረትና የቁም ከብቶች መዘረፋቸውን፤በሺዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎችም ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለው ያለበቂ የሰብአዊ እርዳታ አቅርቦት በአስቸጋሪ ሁኔታ ላይ እንደሚገኙ ኮሚሽኑ ከተጎጂ ቤተሰቦች፣ ከአካባቢው የፍትሕና የአስተዳደር አካላት እንዲሁም በአካባቢው ከሚንቀሳቀሱ የእርዳታ ድርጅቶች ማረጋገጡን አመልክቷል፡፡
የኢሰመኮ ዋና ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ፤ ”የክልሉና የፌዴራል መንግሥታት በአካባቢው ብሔርን መሰረት አድርገው የሚፈጸሙ ጥቃቶችን ለመከላከል በመወሰድ ላይ የሚገኙትን እርምጃዎች ችግሩን በሚመጥን ደረጃ በማሳደግ የዜጎችን ደኅንነት የመጠበቅ ኃላፊነታቸውን በአግባቡ ሊወጡ ይገባል” ሲሉ በድጋሚ አሳስበዋል።
በአካባቢው ሰላማዊ ሰዎችን ኢላማ ያደረጉ ጥቃቶች አሁንም ተስፋፍተው መቀጠላቸውን ኮሚሽኑ ጠቅሶ፤ ጉዳዩ እጅግ አሳሳቢ መሆኑን አስገንዝቧል።
በሌላ በኩል፤ በጋምቤላ ከተማ ሰኔ 7 ቀን 2014 ዓ.ም በክልሉ የፀጥታ ኃይሎች፣ በኦነግ ሸኔ  እና በጋምቤላ ነጻነት ግንባር የተደረገውን ውጊያ ተከትሎ፣ ቢያንስ 50 ሰላማዊ ሰዎች በፀጥታ ኃይሎች መገደላቸውን  ኢሰመኮ ባለፈው ረቡዕ መስከረም 18 ቀን 2015 ዓ.ም ባወጣው ሪፖርት አስታውቋል፡፡
በከተማዋ በሰኔ ወር መጀመሪያ ላይ በክልሉ የፀጥታ ኃይሎች እና በአማጺያኑ ታጣቂዎች መካከል የተደረገውን ውጊያ ተከትሎ የተፈጸሙ ግድያዎችን፣ የአካል ጉዳቶችንና ዘረፋዎችን በተመለከተ ኮሚሽኑ ምርመራ ማድረጉን ጠቁሟል፡፡  ሰሞኑን  ይፋ ባደረገው ባለ 13 ገፅ ሪፖርትም፤ ከሰኔ 7 እስከ 9  2014 ዓ.ም  በሰላማዊ ሰዎች ላይ ከሕግ ውጪ ግድያ፣ የአካል ጉዳትና የንብረት ዘረፋ  በመንግሥት የፀጥታ ኃይሎችና በታጣቂዎች  መፈጸሙን አመልክቷል።
ይህንን ድርጊት ሲመሩና ሲያስፈጽሙ የነበሩ ሃላፊዎች ላይ የህግ ተጠያቂነት ሊረጋገጥ ይገባል  ብሏል፤ኢሰመኮ በሪፖርቱ፡፡
በሦስቱ ቀናት ውስጥ የክልሉ የፀጥታ ኃይሎች፣ ሴቶችና የአዕምሮ ህሙማንን ጨምሮ ቢያንስ 50 ሰላማዊ ሰዎችን በተናጠልና በጅምላ ከፍርድ ውጪ መግደላቸውን ኮሚሽኑ አረጋግጫለሁ ብሏል፡፡ በተጨማሪም 25 በሚሆኑ ሰዎች ላይ ቀላልና ከባድ የአካል ጉዳት፣ ቁጥራቸው ያልተጠቀሱ በርካቶች ላይ ደግሞ ድብደባና የማሰቃየት ተግባር መፈጸሙን በሪፖርቱ ተመልክቷል፡፡
ታጣቂዎቹ ከተማዋን ለቀው ከወጡና ከተማው በመንግሥት የጸጥታ ኃይሎች ቁጥጥር ከገባም በኋላ ግድያዎቹ የተፈፀሙ ሲሆን ለዚህም የክልሉ  የጸጥታ ኃይሎች ተጠያቂ መሆናቸውን ኢሠመኮ በሪፖርቱ ጠቅሷል፡፡ ኮሚሽኑ እንደሚለው፤ የክልሉ ልዩ ኃይል፣ መደበኛ ፖሊሶችና  ሚሊሻዎች በዚህ ድርጊት ላይ የተሳተፉ ሲሆን  ከጸጥታ ኃይሎች ጋር የተባበሩ የተወሰኑ ወጣቶች መኖራቸውም ተጠቁሟል፡፡
የፀጥታ ኃይሎቹ “የኦነግ ሸኔ ታጣቂዎች እና መሳሪያ በቤታችሁ እንዳለ ተጠቁመናል፤ የደበቃችሁትን መሳሪያ አውጡ” የሚል ምክንያትም እየሰጡ ነበር  ተብሏል፤በሪፖርቱ።
የኦነግ ሸኔ እና የጋምቤላ ነጻነት ግንባር ታጣቂዎችም ውጊያው በተካሄደበት ዕለት “ተኩሳችሁብናል” በሚል ምክንያት በመንገድ ላይ ሲንቀሳቀሱ ያገኟቸውን ቢያንስ ሰባት ሰዎች መግደላቸውን ኮሚሽኑ ጠቁሟል፡፡
በተጨማሪም፣ በተኩስ ልውውጡ ወቅት በየትኛው አካል እንደተገደሉ ያልታወቁ ስድስት ሰዎች ሕይወታቸው ማለፉንም ሪፖርቱ አመልክቷል።
የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን በበኩሉ  ከውጊያው በኋላ ባደረገው ማጣራት፣ የክልሉ ልዩ ኃይሎች ሰኔ 8 እና ሰኔ 9 ቀን 2014 ዓ.ም. በከተማዋ ሰላማዊ ሰዎች ላይ ጥቃት ማድረሳቸውን ገልጾ፣ መወሰድ ያለባቸውን ተጨማሪ  ሕጋዊ እርምጃዎችን መጠቆሙም ተመልክቷል፡፡
“የመብት ጥሰቶችን የፈጸሙ ሰዎችና ቡድኖችን ተጠያቂነት ለማረጋገጥ የሚደረጉ ጥረቶችን ለማገዝ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ፣ ተጎጂዎች ፍትሕና ተገቢውን የካሳና መልሶ የመቋቋም ድጋፍ እንዲያገኙና” ተፈጻሚነቱንም እንደሚከታተል ኢሰመኮ አሳስቧል።