Administrator

Administrator

Tuesday, 01 January 2019 00:00

የተፈጥሮ አደጋዎች


    በአለማችን የተለያዩ አገራት በፈረንጆች አመት 2018 የተከሰቱ የተፈጥሮ አደጋዎች ከ5 ሺህ በላይ ሰዎችን ለህልፈተ ህይወት የዳረጉ ሲሆን 28.9 ሚሊዮን ያህል ሰዎችንም በአደገኛ የአየር ንብረት ለውጦች ሳቢያ ለአስቸኳይ ጊዜ እርዳታ መዳረጋቸው ተዘግቧል፡፡
የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከሰሞኑ ባወጣው መረጃ እንዳለው፣ በአመቱ የተከሰቱ የመሬት መንቀጥቀጥ፣ ሰደድ እሳት፣ ጎርፍና ሌሎች አደገኛ የተፈጥሮ አደጋዎች በርካቶችን ለሞትና ለመፈናቀል የዳረጉ ሲሆን ፍሎሪዳን የመታው ሃሪኬን ሚካኤል፣ የካሊፎርኒያ የሰደድ እሳት፣ የስፔንና የፈረንሳይ ሃይለኛ ሙቀት፣ የኢንዶኔዢያ የመሬት መንቀጥቀጥና ጎርፍ በአመቱ ከተከሰቱና የከፋ ጥፋት ካደረሱት መካከል ይጠቀሳሉ፡፡

Tuesday, 01 January 2019 00:00

የስደተኞች ቁጥር

በ2018 የስደተኞች ቁጥር በአለማቀፍ ደረጃ በከፍተኛ ሁኔታ ያደገ ሲሆን 6.3 ሚሊዮን ያህል ዜጎቿ የተሰደዱባት ሶርያ በአለማችን እጅግ ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ዜጎች አገራቸውን ጥለው የተሰደዱባት ቀዳሚዋ አገር መሆኗን ዩኤስኤ ቱዴይ ዘግቧል፡፡
ከአለማችን አገራት በርካታ ዜጎችን በማሰደድ የሁለተኛ ደረጃን የያዘቺው 2.6 ሚሊዮን ያህል ዜጎች የተሰደዱባት አፍጋኒስታን ናት ያለው ዘገባው፣  እ.ኤ.አ በ2011 ነጻነቷን ያወጀቺውና እንደ አገር መቆም ተስኗት በእርስ በእርስ ጦርነት ስትታመስ የኖረቺዋ ደቡብ ሱዳን በ2.4 ሚሊዮን ስደተኞች የሶስተኛ ደረጃ ላይ መቀመጧንም አመልክቷል፡፡
ሌላዋ አፍሪካዊት አገር ሶማሊያ በ806 ሺህ ያህል ስደተኞች የአራተኛ ደረጃን ይዛለች ያለው ዘገባው፣ 723 ሺህ ያህል የሮሂንጋ ሙስሊሞች ወደ ጎረቤት አገር ባንግላዴሽ የተሰደዱባት ማይንማር በአምስተኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ አመልክቷል፡፡

 በአመቱ በአለማችን ከተከሰቱ አነጋጋሪና የመገናኛ ብዙሃንን ትኩረት ስበው ከከረሙ ጉልህ አለማቀፋዊ ጉዳዮች መካከል በቱርክ የሳዑዲ አረቢያ ኢምባሲ የተፈጸመው የጋዜጠኛ ጀማል ካሾጊ ግድያ ይጠቀሳል፡፡
ቻይናና አሜሪካ የገቡበትና ዳፋው ለበርካታ የአለም አገራት ይተርፋል ተብሎ የተሰጋው የንግድ ጦርነት፣ አሜሪካ ከኢራን ጋር የገባቺውን የኒውክሌር ስምምነት በማፍረስ ተጨማሪ ማዕቀብ መጣሏና ለኢየሩሳሌም የእስራኤል መዲናነት በይፋ እውቅና መስጠቷ፣ በውዝግብ የታጀበው የእንግሊዝ ከአውሮፓ ህብረት የመውጣት ዕቅድም በአመቱ አለማቀፋዊ ትኩረትን ስበው የከረሙ ጉዳዮች ናቸው፡፡
ተካርረው የከረሙትና ከዛሬ ነገ ወደ ኒውክሌር ጦርነት ይገባሉ ተብሎ አለም በስጋት ይመለከታቸው የነበሩት ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕና የሰሜን ኮርያው አቻቸው ኪም ጆንግ ኡን ባልተጠበቀ መልኩ አቋማቸውን ቀይረው በወርሃ ሰኔ ሲንጋፖር ውስጥ ታሪካዊውን ሰላማዊ ውይይት ማድረጋቸውና ኪም ኒውክሌራቸውን ሊያወድሙ መስማማታቸው የአለምን ትኩረት የሳበ ሌላው ጉዳይ ነበር፡፡
የኮንጎ የኢቦላ ወረርሽኝ፣ የሩስያው የአለም የእግር ኳስ ዋንጫ፣ የደቡብ ሱዳን የሰላም ስምምነት፣ የሳኡዲ አረቢያው ልኡል ሞሀመድ ቢን ሳልማን ሚኒስትሮችንና ባለሃብቶችን በሙስና ሰበብ ድንገት ማሰራቸው፣ የፈረንሳይ ተቃውሞና የዚምባቡዌው ሙጋቤና የደቡብ አፍሪካው ጃኮብ ዙማ ከመንበረ ስልጣን መወገድም በ2018 የመገናኛ ብዙሃንን ትኩረት ስበው ከከረሙ አለማቀፋዊ ጉዳዮች ተርታ ይሰለፋሉ፡፡


---------------

  በ”አዲስ አድማስ” ጋዜጣ በተለያዩ ርዕስ ጉዳዮች ላይ መጣጥፎችን፣ ወጎችንና አጫጭር ልብወለዶችን በመጻፍ የሚታወቀው ደረጀ ይመር ያዘጋጀው “የሕዳሴው መሐንዲስ” የተሰኘ መጽሐፍ ሰሞኑን ለንባብ በቅቷል፡፡
መጽሐፉ፤ እውነተኛው የሕዳሴው መሐንዲስ ታላቁ የኢትዮጵያ ንጉሥ አጼ ቴዎድሮስ እንደሆኑ የሚያትት መጣጥፍን ጨምሮ ሌሎች ማኅበራዊ፣ ፖለቲካዊና ፍልስፍናዊ ይዘቶችን የሚዳስሱ ጽሁፎች፣አዝናኝ ወጎችና አጫጭር ልብወለዶችን አካትቶ ይዟል። በ30 ምዕራፎች ተከፍሎ በ202 ገጾች የተቀነበበው መጽሐፉ፤ በ150 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ መጽሐፉን ጃፋር መጻሕፍት መደብር እንደሚያከፋፍለው ታውቋል፡፡   

 “አዝማሪና ውሃ ሙላት” የሚለው የከበደ ሚካኤል ግጥም እንዲህ ይላል፡-
አንድ ቀን አንድ ሰው፣ ሲሄድ በመንገድ
የወንዝ ውሃ ሞልቶ ደፍርሶ ሲወርድ
እዚያው እወንዙ ዳር፣ እያለ ጐርደድ
አንድ አዝማሬ አገኘ፣ ሲዘፍን አምርሮ
በሚያሳዝን ዜማ፣ ድምፁን አሳምሮ፡፡  
“ምነው አቶ አዝማሪ፣ ምን ትሠራለህ?” ብሎ ቢጠይቀው፤
“ምን ሁን ትላለህ አላሻግር ብሎኝ የውሃ ሙላት
እያሞጋገስኩት በግጥም ብዛት
ሆዱን አራርቶልኝ ቢያሻግረኝ ብዬ
“አሁን ገና ሞኝ ሆንኩ ምነዋ ሰውዬ
ነገሩስ ባልከፋ፣ ውሃውን ማወደስ
ግን እንደዚህ ፈጥኖ በችኮላ ሲፈስ
ምን ይሰማኝ ብለህ ትደክማለህ ከቶ
ድምፁን አያሽካካ መገስገሱን ትቶ
እስቲ ተመልክተው፣ ይሄ አወራረድ
ያልሰማው ሲመጣ፣ የሰማው ሲሄድ፡፡”
ተግሣፅም ለፀባይ ካ ልሆነው አራሚ
መናገር ከንቱ ነው፣ ካልተገኘ ሰሚ!
*   *   *
ስንናገር ሰሚ መኖሩን እናረጋግጥ፡፡ ለነማንና ለማን ነው የምንናገረው እንበል፡፡ አንዳንድ ሰው ብዙ ጆሮ አለው፡፡ አንዳንዱ ደግሞ ፈፅሞ ጆሮ ያልፈጠረበት ነው፡፤
“አሁን የት ይገኛል፣ ቢፈልጉ ዞሮ
መስማት ከማይፈለግ፣ የባሰ ደንቆሮ”  ይሉናል ከበደ ሚካኤል፡፡
“አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት አይነቃም”ም ያስኬዳል፡፡ ሥልጣን ልብ ያደነድናል፡፡ ጆሮ ያደነዝዛል፡፡ ዐይንን ያስጨፍናል! ህዋሳት በድን ሲሆኑ አገር የልማት ትኩሳቷ ይደነዝዛል! የንቃት ዐይኗ ይጨለመልማል! ተስፋና ምኞት ያስለመልማሉ! እኛ በምሁራዊ ልቦናችን የምንመኝላት መንገድ ው መንገድ ነው ኮረኮንች፣ አሊያም ሊሾ አስፋልት ደሞም ቀለበት ሊሆን ግድ ነው!
መለወጣችን ግድ ነው! ለለውጥ መዘጋጀት ግን የለውጥ ግድ ግድ ነው! ዋናው ችግራችን የተለወጥን እየመሰለን ዘራፍ ማለታችን ነው! ብዙዎቻችን የለውጥ ዕውነተኛውና ሁነኛው ሀሳብ ሳይገባን የተለወጥን ይመስለናል! ምነው ቢሉ… ለውጥ የአንድ ጀምበር ጉዳይ ስላልሆነ ነው! እናርገውም ብንል ከቶም ባንድ ጀምበር አንስማማም! ስለዚህ በብርቱ ማሰብ ያለብን “ዛሬም ትግላችን መራራ፣ ግባችን የትየለሌ” መሆኑን ነው! መስዋዕትነትን አንፍራ! የአቅማችንን ያህል ሩቅ ዕቅድና ሀሳብ አንሽሽ! ዛሬ ሁሉን ባቋራጭ የማሸነፍ ፍላጎት ዘመን ነው (It is a time of short - term mechanisms) የረዥም ጊዜ ዕቅድ ገና ባላወቅንበት አገር “አቋራጭ መንገድ” ፍለጋ ስንባዝን ዓመታት አልፈዋል! ገና ያልፋሉ፡፡  
አሁን መሰረታዊ ፍላጎታችን ስለ ፖለቲካዊ ጉዳይ ብቻ አይደለም፡፡ አኮኖሚያዊም ነው! ጉዳያችን ማን በልቶ ይደር ማንስ ጠግቦ ይደር? የሚለው ነው፡፡
ህንዶች፤
“እያንዳንዷ ሩዝ ላይ የሚበላት ሰው ስም ተፅፏል” የሚሉት እንደ እኛ ባለ አገር የሚሰራ ሀቅ ነው!! ይሄን ምኔም ልብ እንበል! ነገም ጥያቄያችን ይሄው ነው!

 የእርዳታ ፈላጊዎች ቁጥር ወደ 8 ሚሊዮን እንደሚያሻቅብ ተጠቆመ

     በቤኒሻንጉልና በምዕራብ ወለጋ አዋሳኝ ሰሞኑን የፀጥታ ኃይሎች የወሰዱትን የህግ ማስከበር እርምጃ ተከትሎ አንፃራዊ መረጋጋት በመስፈኑ ለተፈናቃዮች እርዳታ ማቅረብ መጀመራቸውን የረድኤት ድርጅቶች አስታወቁ፡፡
ቀደም ሲል በግጭቱ ምን ያህል ሰዎች እንደተፈናቀሉ ለማወቅ አስቸጋሪ እንደነበር የጠቆመው የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ ድጋፍ ማስተባበሪያ ፅ/ቤት፤የተፈናቃዮች ቁጥር ሩብ ሚሊዮን መድረሱን አስታውቋል፡፡ ለእነዚህ ተፈናቃዮች አስቸኳይ እርዳታ ለማቅረብም 25.5 ሚሊዮን ዶላር ያስፈልጋል ተብሏል።
ከተፈናቀሉት 255 ሺ ያህል ዜጎች መካከል 57 ሺህ የሚሆኑት በቤኒሻንጉል ጉሙዝ አሶሳና ከማሺ ዞን ውስጥ የሚገኙ ሲሆን 200 ሺ ያህሉ ከቤኒሻንጉል ጉሙዝ ተፈናቅለው፣ በምስራቅና ምዕራብ ወለጋ ውስጥ የሰፈሩ መሆናቸውን ጽ/ቤቱ በሪፖርቱ ጠቁሟል፡፡
ከሰሞኑ ተፈናቃዮች ያሉበትን ሁኔታ ለማወቅ የረድኤት ድርጅቶች ምልከታ ያደረጉ ሲሆን ተፈናቃዮቹ አስቸኳይ የህክምና፣የተመጣጣኝ ምግብና የመጠለያ አቅርቦት እንደሚያስፈልጋቸው አስታውቀዋል፡፡ ተማሪዎችም ትምህርት ማቋረጣቸውም በሪፖርታቸው ተመልክቷል፡፡   
ይህን እርዳታ በአስቸኳይ ለማቅረብም 25.5 ሚሊዮን ዶላር ለህክምና ቁሳቁስ፣ለምግብ፣ ለህፃናትና እናቶች አልሚ ምግብ እንዲሁም ለዘይት መግዣ እንደሚያስፈልግ የተባበሩት መንግስታት የሰብአዊ ድጋፍ ማስተባበሪያ ፅ/ቤት ባወጣው ሪፖርት አስታውቋል፡፡  
በአጠቃላይ በግጭት ምክንያት በሃገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች የተፈናቀሉ ዜጎች ቁጥር በህዳር ወር ከነበረበት 2.2 ሚሊዮን ወደ 2.4 ሚሊዮን ከፍ ማለቱን የጠቆመው ጽ/ቤቱ፤በአዲሱ የፈረንጆች ዓመት 2019 የአስቸኳይ እርዳታ ፈላጊዎች ቁጥር ወደ 8 ሚሊዮን እንደሚያሻቅብ አስታውቋል፡፡ ለእነዚህ ዜጎች እርዳታ ለማቅረብ 1.2 ቢሊዮን ዶላር ያስፈልጋል ብሏል፤የመንግስታቱ ድርጅት፡፡

Saturday, 22 December 2018 13:39

ማራኪ አንቀጾች

 የህልም ነገር

   በህልሜ ጭንቅላቴ ከአንገቴ ተለያይቶና ክንፍ አውጥቶ በጡረታ ድልድይ አናት ላይ እንደ ደመና ሲያንዣብብ አየሁ፡፡ የጡረታ ድልድይ እናቶች በመገረም አንጋጠው ሲያስተውሉ በምጽዐት ቀን የተኮነኑ ነፍሳት ይመስሉ ነበር፡፡
በእንቅልፍ ልብ እራሴን አጽናናለሁ…
“….ማየቱም፣ መናገሩም፣ መስማቱም ያለው ጭንቅላት ላይ ነው፡፡ የሰው ልጅ ምን ሲሆን ከአንገት በታች ተንዘላዝሎ ተፈጠረ? ቢቀር እጅና እግር ነው፣ ለእሱም ቢሆን ክንፍ አለ፣ ኧረዲያ መኖርስ ከአንገት በላይ…
ህልም ሥር የሰደደ ድብቅ ፍርሃት እንደሆነ በራሴ አረጋገጥኩ፡፡ ረድ ሠርዌና አባቱ በእኔ ሟርት ሲወራከቡ፣ ነገሩን ችላ ያልኩት መሰልኩ እንጂ ፍርሃትስ ነበር ማለት ነው፤ ካልሆነ…
የጭንቅላቴ አከናፍ ደክመው አየሩን አልቀዝፍ ሲሉብኝና መውደቄ እርግጥ ሲሆን የጡረታ ድልድይ እናቶች “ተዘጋጅ” እንደተባለ ሰልፈኛ ንቃት ታየባቸው። ምን ሊያደርጉኝ እንደሆን ባላውቅም ፍርሃት አደረብኝ። መቅዘፊያ እንደሌላት ጀልባ ጭንቅላቴ በንፋስ እየተገፋ ሲሄድ ያሰፈሰፉት እናቶች ይንቀሳቀሱ ጀመር፡፡ አቅጣጫውን እያማተሩ ሲደርሱ ጭንቅላቴ ሲወድቅ እኩል ሆነ፡፡ ለመያዝ ሲሻሙ ብርድ ልብሴን እንደ መቃብር ድንጋይ በርቅሼ ተነሳሁ፡፡ ፍርሃቱ አለቀቀኝም፡፡ ቀን ከጐዘጐዝኩበት፣ ማታ ካሸለብኩበት ምንጣፍ ላይ ተነስቼ በሩን ዘጋሁት፡፡ ሰውነቴ በፍርሃት ይንቀጣቀጣል፡፡
“የህልም ዓለም ፍርሃት ስለምን ወደ እውን ዓለም ፍርሃትነት ይሸጋገራል” ስል እራሴን ጠየኩ፡፡ መንፈሳችን የታበተበት የሞት ፍርሃት ልኩ የሚታወቀው በእውን ዓለም ማገናዘብ ሳይሆን በህልም ዓለም ደመ ነፍሳዊ ድንጋጤ ውስጥ ነው፡፡ የእኔ መኖር ለእኔ ሆነ ለተቀረው አለም አስፈላጊነቱ እምን ላይ ነው? እስከ መቼስ ከህልም ዓለም ወደ እውን ዓለም ፍርሃት ሳመላልስ እኖራለሁ?…
…አንዳች የሚስቅብኝ ህቡዕ ልቡና መርማሪ አካል እንዳለ ተሰማኝ፡፡ ስለ ስንፍናዬ በፊቱ ሊያሳፍረኝ እየሞከረ እንደሆነ የገባኝ መሰለኝ፡፡ ያ ልቡናዬን የሚበረብር ኃያል ህቡዕ አካል እርሱ ማነው? ልቡናን የመፈተሽ ስልጣን ማን ሰጠው? እራሱ የሥልጣኑ ሰጪና ተቀባይ ይሆን? ሰጪና ተቀባይ አንድ የሆነበት አካባቢ እንዴት ያለ ፍትህ፣ ንፅህናና ቅድስና ይኖራል?…ይሄ የሰው ልጅ የአፈጣጠር ትብታብ ነው። ሰጪና ተቀባይን፣ አልፋና ኦሜጋን፣ ግዝፈትና ረቂቅነትን በአንድ የሚያዳብል የሰው ልጅ ተንኮል ብቻ ነው፡፡ ግዴላችሁም፤ “ኑ በአካላችን በአምሳላችን እንፍጠር” ያለው ፈጣሪ ሳይሆን እራሱ ሰው ነው፡፡ “ኑ እግዚአብሔርን በአካላችንና በአምሳላችን እንፍጠር”
ከየት ተነስቼ እምን ጋ እንደደረስኩ ጠፋኝ፡፡ ይሁንና ፍርሃቴ ጠፍቶ በሬን ተንደርድሬ በመዝጋቴ በራሴ ላይ ሳቅሁ፡፡ መንፈሴ ተዛና--ለማንበብ አኮበኮብኩ። ወረፋ የሚጠብቁ ብዙ መጻሕፍት አሉብኝ፡፡ አንዳንዶቹ ጀምሬአቸው መንፈሴን ስላጨፈገጉብኝ የተውኳቸው ናቸው፡፡ ለምሳሌ የአልበርት ካሙ “The Plague” ገና ስጀምረው በአይጦች ትርምስ ሲሞላ አቆምኩት፡፡ ሌላው ስሙ የማይያዝልኝ ሩሲያዊ ደራሲ፤ እንግሊዝኛ ተናጋሪዎች በቋንቋቸው ስሙን ሲጽፉ ሳያበላሹበት አይቀርም፡፡ SOLZHENITSYN (ሶልዘኒትሳይን) ይባላል፡፡ “Cancer Ward” ይሄም መጽሐፍ ያው ነው፡፡ ተስፋ የሌለው የነቀርሳ ታማሚ፤ መጨነቅ በመፍራት ተውኩት፡፡ ሦስተኛው የብርሃኑ ዘሪሁን ሦስቱ ማዕበሎች ናቸው፡፡ ረሃብ? ወደ ጐን። አንዳንዶቹን መጻሕፍት ተራ የማስጠብቃቸው የአንድ ደራሲ ሥራዎችን አከታትዬ ላለማንበብ ነው። አንዳንድ ደራሲዎች ደግሞ አንቀጽ የሌለው ሃምሣ ስድስት ገጽ ይጽፋሉ፡፡ ለምሳሌ ፈረንሳዊው ፈላስፋ ሳርት እና አየርላንዳዊው ጀምስ ጆይስ፡፡ ተራራ ወጪ አይደለሁም፤ ገና ዳገት እንዳየሁ ሃሞቴ ፍስስ ይላል። አንቀፅ ያልገባበት ጽሑፍ ደረቱን የሰጠ አቀበት ነው፡፡ አዲዮስ!
ያልተነበቡ መጻሕፍት የሚቀመጡበት ጠረጴዛ የዕዳ መዝገቤ ሆኖ ይወቅሰኛል፡፡ እንደ የንታ ጥምጥም ክርክርም ያለ አመል ያላት የሳጠራ ሼልፍ፣ የድል መዝገቤ ሆና ብሥራቴን ትለፍፋለች፡፡ አንብቤ ባልገቡኝ እንደ ጉርጂፍ እና በርትራንድ ራስል ያሉት ፀሐፍያን ላይም ሥራዎቻቸውን አንብቤ በመጨረሴ ብቻ እኩራራለሁ፡፡
(ከደራሲ ዓለማየሁ ገላጋይ “ታለ በዕውነት ሥም” የተቀነጨበ፤ 2ኛ ዕትም)

    “አቬንጀርስ - ኢንፊኒቲ ዎር” በ2.04 ቢሊዮን ዶላር ቀዳሚ ሆኗል

    በፈረንጆች 2018 አመት በአለማቀፍ ደረጃ ከፍተኛ ገቢ ያገኙ የአለማችን ምርጥ ፊልሞች ዝርዝር ይፋ የተደረገ ሲሆን፣ አቬንጀርስ - ኢንፊኒቲ ዎር የተሰኘው ፊልም በ2.04 ቢሊዮን ዶላር አጠቃላይ ገቢ የአንደኛነት ደረጃ ላይ መቀመጡ ተነግሯል፡፡
300 ሚሊዮን ዶላር ያህል ፈጅቶ የተሰራው አቬንጀርስ - ኢንፊኒቲ ዎር፣ ከ2 ቢሊዮን ዶላር በላይ ገቢ በማግኘት በታሪክ አራተኛው ፊልም ሆኖ መመዝገቡን የዘገበው ዴይሊ ሚረር፣ ፊልሙ በአመቱ በአሜሪካ ብቻ 678.8 ሚሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘቱን አመልክቷል፡፡
ዋካንዳ በተባለችና የኢትዮጵያ ተምሳሌት ናት ተብሎ በሚነገርላት የምናብ አገር ላይ ተመስርቶ የተሰራውና ጥቁር ተዋንያን የሚበዙበት ብላክ ፓንተር በአመቱ 1.34 ቢሊዮን ዶላር ገቢ በማግኘት በሁለተኛ ደረጃ ላይ ተቀምጧል፡፡
210 ሚሊዮን ዶላር ወጪ የተደረገበት ብላክ ፓንተር በፈረንጆች 2018 አመት በአሜሪካ ብቻ ከ700 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገቢ ማግኘቱን የጠቆመው ዘገባው፣ ፊልሙ በርካታ ክብረ ወሰን መስበሩንና በአለማቀፍ ደረጃ ተወዳጅ በመሆን በወረፋ መታየቱን መቀጠሉን ገልጧል፡፡
ዡራሲክ ወርልድ - ፎልን ኪንግደም የተሰኘውና በዩኒቨርሳል ፒክቸርስ ፕሮዲዩስ የተደረገው ፊልም በበኩሉ፤ 1.3 ቢሊዮን ዶላር ገቢ በማግኘት የሶስተኛነት ደረጃን መያዙ ተነግሯል፡፡
ኢንክሪዲብልስ ቱ በ1.2 ቢሊዮን ዶላር፣ ቬኖም በ853 ሚሊዮን ዶላር፣ ሚሽን ኢምፖሲብል - ፎልአውት በ787.4 ሚሊዮን ዶላር ገቢ እንደ ቅደም ተከተላቸው፣ ከአራተኛ እስከ ስድስተኛ ያለውን ደረጃ መያዛቸውንም ዘገባው አክሎ ገልጧል፡፡


 ጋዜጠኞችን በማሰር ቻይና ቀዳሚነቱን ይዛለች

     ስራቸውን በማከናወን ላይ ሳሉ ግድያ የሚፈጸምባቸው ጋዜጠኞች ቁጥር እያደገ መምጣቱንና በ2018 ብቻ በአለማችን የተለያዩ አገራት 63 ያህል ጋዜጠኞች መገደላቸውን ሪፖርተርስ ዊዝአውት ቦርደርስ ባወጣው ሪፖርት እንዳስታወቀ ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ያወጣውን መግለጫ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ በስራ ገበታቸው ላይ እያሉ የተገደሉ ጋዜጠኞች ቁጥር ከአምናው በ15 በመቶ የጨመረ ሲሆን በአለማችን ለጋዜጠኞች እጅግ አደገኛ የተባሉት የመጀመሪያዎቹ ሶስት አገራትም አፍጋኒስታን፣ ሶርያና የመን ናቸው፡፡
በአመቱ በአፍጋኒስታን 15፣ በሶርያ 11፣ በየመን 8 ጋዜጠኞች መገደላቸውን የገለጸው ተቋሙ፣ በአመቱ 6 ጋዜጠኞች የተገደሉባት አሜሪካም ዘንድሮ ለመጀመሪያ ጊዜ ለጋዜጠኞች እጅግ አደገኛ ከሆኑ አስር አገራት ተርታ መሰለፏን አመልክቷል፡፡
በአሁኑ ወቅት በአለማችን የተለያዩ አገራት በድምሩ 348 ያህል ጋዜጠኞች በእስር ላይ እንደሚገኙ የጠቆመው ተቋሙ፣ ቻይና 60፣ ግብጽ 38፣ ቱርክ 33 ጋዜጠኞችን በማሰር ከአለማችን አገራት ቀዳሚነቱን እንደሚይዙ አስታውቋል፡፡
በአለማችን የተለያዩ አገራት ታግተው የሚገኙ ጋዜጠኞች ቁጥር 60 ያህል መድረሱን የጠቆመው ሪፖርተርስ ዊዝአውት ቦርደርስ፣ ሶርያ 31፣ የመን 17፣ ኢራቅ 11 ጋዜጠኞችን አግተው እንደሚገኙ አመልክቷል፡፡
ባለፉት 10 አመታት በመላው አለም የተገደሉ ጋዜጠኞች ቁጥር 702 ያህል መድረሱን የገለጸው ተቋሙ፣ ባለፉት አስርት አመታት በርካታ ቁጥር ያላቸው ጋዜጠኞች የተገደሉት በፈረንጆች አመት 2012 እንደነበርና በአመቱ 87 ጋዜጠኞች መገደላቸውንም አክሎ አስታውቋል፡፡

የቻይናው የቴሌኮም ኩባንያ ሁዋዌ የፋይናንስ ዘርፍ ዋና ስራ አስፈጻሚ ዋንዙ ሜንግ በቅርቡ በአሜሪካ መንግስት ግፊት በካናዳ በቁጥጥር ስር መዋላቸውን የተቃወሙና ቻይናውያን ለአገራቸው ምርት ቅድሚያ እንዲሰጡ ለማበረታታት በማሰብ፣ የተለያዩ የአገሪቱ ኩባንያዎች ለሁዋዌ ሞባይል ተጠቃሚዎች ሽልማት እየሰጡ እንደሚገኙ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ከቻይና ስመጥር የቱሪስት መዳረሻዎች አንዱ እንደሆነ የሚነገርለት ሼኖንግ ማውንቴን ሲኒክ ፓርክ፤ የሁዋዌ ሞባይል ለሚጠቀሙ ጎብኝዎቹ 9.4 ዶላር የሚያወጣውን የመግቢያ ትኬት እየሸለመ እንደሆነ ያስታወቀ ሲሆን በቤጂንግ የሚገኝ አንድ ባር በበኩሉ፤ ለባለ ሁዋዌ ሞባይል ደንበኞቹ የ20 በመቶ ቅናሽ እያደረገ መሆኑ ተዘግቧል፡፡
ሜንፓድ የተባለው ሌላ የቻይና የቴክኖሎጂ አምራች ኩባንያ ደግሞ ሁዋዌ ሞባይል ለሚገዙ ሰራተኞቹ የዋጋ ድጎማ እንደሚያደርግና  በአንጻሩ ደግሞ የአፕል ምርቶችን የሚገዙ ሰራተኞቹን እንደሚቀጣ መዛቱ ተነግሯል፡፡
በአለማችን ሁለተኛው ግዙፍ የስማርት ፎን አምራች ኩባንያ የሆነው የቻይናው ሁዋዌ የፋይናንስ ዋና ሃላፊ ዋንዙ ሜንግ፤ አሜሪካ በኢራን ላይ የጣለችውን የንግድ ማዕቀብ ጥሰዋል በሚል ከሳምንታት በፊት በአሜሪካ ባለስልጣናት ጥያቄ በካናዳ በቁጥጥር ስር መዋላቸውና ጉዳዩ ሁለቱን አገራት ወደ ከፋ ነገር ሊያመራቸው እንደሚችል ሲነገር መሰንበቱ ይታወሳል፡፡