Administrator

Administrator

Saturday, 17 November 2018 11:11

በእርግጥም የጀግኒት ዘመን!!

 ኢትዮጵያ በአዲስ የታሪክ ምዕራፍ ላይ ትገኛለች፡፡ ጠ/ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ በቅርቡ ካቢኔያቸውን ሲያዋቅሩ፤ 50 በመቶ የሚኒስትርነቱን ድርሻ ለሴቶች መስጠታቸው ከፍተኛ ውዳሴን  የተቀዳጀው በኢትዮጵያ ብቻ አይደለም፡፡ በአፍሪካ እንዲሁም በመላው ዓለም በእጅጉ ተደንቋል፡፡
ሴቶችን ወደ ከፍተኛ የመንግስት ሥልጣን የማምጣት እርምጃ በዚህ ብቻ አላበቃም፡፡ ኢትዮጵያ ከንግስት ዘውዲቱ ወዲህ የመጀመሪያዋን ሴት ርዕሰ ብሄር አግኝታለች፡፡ ሴት ፕሬዚዳንት በመሾም በምስራቅ አፍሪካ የመጀመሪያዋ አገር ሆናለች - ኢትዮጵያ፡፡ ሳምንት ባልሞላ ጊዜ ውስጥ ደግሞ የመጀመሪያዋ የጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት ተሹመዋል፡፡ ሰሞኑን የተሾሙት የጠ/ሚኒስትሩ የፕሬስ ሴክሬተሪ ሃላፊ (ቃል አቀባይ) እና ምክትላቸውም እንዲሁ ሴቶች ናቸው፡፡ በእርግጥም የጀግኒት ዘመን ነው፡፡  
የተባበሩት መንግስታት ሴቶች ዋና ዳይሬክተር ፉምዚሌ ምላምቦ፣ ሴቶች የአመራር ዕድል ከተሰጣቸው ስኬታማ እንደሚሆኑ ሲመሰክሩ፤ ‹‹የሴቶች አመራር ሰጪነት በጎ ተጽዕኖዎችን የሚያሳዩ ከበቂ በላይ ማስረጃዎች አሉ፡፡ ሴቶች አገሮችን፣ ከተሞችን፣ኢኮኖሚዎችንና ጠንካራ ተቋማትን ስኬታማ በሆነ መንገድ ገንብተዋል፣ መርተዋልም›› ይላሉ፟።
 በሴቶች ወደ ከፍተኛ የመንግስት ሥልጣን መምጣት የማይበርዳችሁም ሆነ የማይሞቃችሁ ሰዎች፣ ለአገራችን ትልቅ ጉዳይ መሆኑን መዘንጋት የለባችሁም፡፡
እንኳን ለእኛ የዲሞክራሲ እናት ነኝ ለምትለዋ አገረ አሜሪካም ጭምር። ለዚህ ነው ሰሞኑን በአሜሪካ በተካሄደው የአማካይ ዘመን ምርጫ፤ሴቶች በከፍተኛ ቁጥር ለኮንግረስ መመረጣቸው፣ ትልቅ አጀንዳ ሆኖ የሰነበተው፡፡ የሴቶች መብት ተሟጋቾች፤ “ምርጫው ለሴቶች ድል ነው” ብለውታል፡፡ እናላችሁ፤ “ኢት  ኢዝ ኤ ቢግ ዲል!” ለማለት ነው። በዚያ ላይ አገሪቱ የጀመረችው ሁለንተናዊ የለውጥ እርምጃ አካልም መሆኑን አትዘንጉት፡፡  
የኢትዮጵያ ሴቶች በአገሪቱ ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ በርካታ ቁልፍ የመንግስት ሥልጣኖችን መቆጣጠራቸው በራሱ ትልቅ ስኬት ቢሆንም፣ ሃላፊነታቸውን በአግባቡ ተወጥተው፣ብቃታቸውን እንደሚያሳዩንም  አልጠራጠርም። በነገራችን ላይ ከሰሞኑ የሴቶች ሹመት ጋር ተያይዞ፣ ለዘመናት በወንዶች ብቻ በሞኖፖል ተይዞ የቆየውን የመንግስት ስልጣን የተነጠቁ የመሰላቸው አንዳንድ ወንዶች፤ “የወንዶች መብት ተሟጋች” ድርጅት ለማቋቋም ማሰባቸውን ፍንጭ  ሰምቼ ፈገግ ብያለሁ፡፡    
ወደ ቁምነገሩ ስንመጣ፣ የጠ/ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ፤ከፍተኛ የሴት ሹማምንት ቁጥር ምን ያህል እንደደረሰ ታውቁ ይሆን? ባታውቁም አትጨነቁ፤ ዝርዝራቸውን  እነሆ፡-
ወ/ሮ ሙፈረያት ካሚል - የሠላም ሚኒስትር
ኢንጅነር አይሻ ሞሃመድ - የመከላከያ ሚኒስትር
ወ/ሮ ፈትለወርቅ ገ/እግዚአብሔር - የንግድና ኢንዱስትሪ ሚኒስትር
ወ/ሮ ዳግማዊት ሞገስ   - የትራንስፖርት ሚኒስትር
ዶ/ር ሂሩት ወ/ማርያም - የሳይንስና ከፍተኛ ትምህርት ሚኒስትር
ወ/ሮ ያለም ጸጋዬ  አስፋው - የሴቶች ህጻናትና ወጣቶች ሚኒስትር
ዶ/ር ኤርጎጌ ተስፋዬ - የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚኒስትር
ዶ/ር ሂሩት ካሣው - የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር
ወ/ሮ አዳነች አበበ - የገቢዎች ሚኒስትር
ዶ/ር ፍጹም አሰፋ - የፕላንና ልማት ኮሚሽን ሚኒስትር
አምባሳደር ሣህለ ወርቅ ዘውዴ - ርዕሰ ብሔር
ወ/ሮ መዓዛ አሸናፊ - የጠቅላይ ፍ/ቤት ፕሬዚዳንት
ወ/ሪት ቢልለኔ  ሥዩም - የጠ/ሚኒስትሩ ፕሬስ ሴክሬተሪ ሃላፊ
ወ/ሪት ሄለን ተስፋዬ   -  የጠ/ሚኒስትሩ ፕሬስ ሴክሬተሪ ምክትል ሃላፊ

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ጉደኛ ትንሽ ልጅ ነበረ፡፡ ይህ ልጅ የደምብ ልብሱን በንፅሕና ይይዛል፡፡ በሰዓቱ ወደ ትምህርት ቤት ይሄዳል፡፡ በሰዓቱ ይመለሳል፡፡ ገና ትንሽ ልጅ ነው፡፡

ሆኖም አስተዋይ ነው፡፡
አንድ ቀን ሳያስበው አንድ ብርጭቆ ሰበረ፡፡ ታላቅ ወንድሙ መጥቶ በጣም ተቆጣውና ገሰፀው፡፡
“እየውልህ አንድ ነገር ከማድረግህ በፊት አስብ፡፡ ብታስብ ኖሮ ይሄን ብርጭቆ አትሰብርም ነበር፡፡ ስለዚህ
1ኛ/ አስብ
2ኛ/ አስብ
3ኛ/ አስብ” አለው፡፡
ልጁም
“እሺ በቃ፡፡ ከዛሬ ጀምሮ አስባለሁ” አለ፡፡
ከቀናት በኋላ ልጁ ታላቅ ወንድሙን፤
“ወንድም ጋሻ እፈልግሃለሁ” አለው፡፡
“እሺ ምን ልርዳህ ታናሼ” አለና ጠየቀው፡፡
“ወንድም ጋሻ አንድ ጥያቄ ብጠይቅህ ቅር ይልሃል?”
“በጭራሽ! የፈለከውን ጠይቀኝ”
“ወንድም ጋሻ፤ ማሰብ አስተምረኝ?”
ወንድም ጋሼ አይኑ ፈጠጠ፡፡ ለካ ማሰብን ማስተማር አይቻልም፡፡
ሌላ ቀን፤ ይሄው ጉደኛ ልጅ ከትምህርት ቤት ተመልሶ ይመጣል፡፡ እያለቀሰ ነው የመጣው፡፡
እናቱ፤
“ምን ሆነህ ነው የምታለቅሰው ልጄ?”
“የኔታ ገረፉኝ!”
“ለምን ልጄ? ምን አጥፍተህ ነው?”
“ምንም”
“ምንም ሳታጠፋማ አይመቱህም፡፡ ዕውነቱን ንገረኝ?”
“ `ሀ` በል አሉኝ፡፡ አልልም፤ አልኳቸው፡፡ ከዛ ገረፉኝ፡፡”
እናትየውም፤
“የሞትክ! ሀ ማለት አቅቶህ ትገረፋለህ?” አለችው፡፡
ልጁም፤
“አይ እማዬ፤ የየኔታ ጉዳቸው መች ያልቃል?
“ሀ” ስል “ሁ” በል ይሉኛል፡፡ “ሁ” ስል “ሂ” በል ይሉኛል፡፡ “ሂ” ስል “ሃ” በል ይሉኛል፡፡ እንዲህ እያሉ እስከ “ፐ”  ድረስ ሊያስለፉኝ እኮ ነው” አላት፡፡
*   *   *
የልጆችን ጭንቅላት አለመናቅ ትውልድን መንከባከብ ነው፡፡ ትውልድን መንከባከብ ህብረተሰብን ከማናቸውም ችግር ማዳን ነው፡፡ ሁሉም ነገር ከቤታችን ይጀምራል፡፡ ልጅ ከቤት ሳይገራ

ውጪ ከወጣ በኋላ እናርምህ ብንለው ከንቱ ድካም ነው፡፡ የሀገራችንም የፖለቲካ ተዋንያን ከመሠረቱ ሳይስተካከሉ ደጅ ከወጡ በኋላ፣ አደባባይ ከወጡ በኋላ፣ ሥልጣን ላይ ከወጡ

በኋላ ማረቂያ አይኖራቸውም፡፡ ዐይን ያወጣ ሌብነት ሰለባ የሆንነው ለዚህ ነው፡፡ የትልቁ አሳና የትንሹ አሳ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀር የባለተራ ደወል አይቀሬ ነው… For whom

the bell tolls እን
ዳለው ነው ሔሚንግዌይ! ተረኛ ጊዜውን ጠብቆ መግባቱ ግድ ነው፡፡ አገር ዘርፎ፣ አገር መዝብሮ እንቅልፍ የለም፡፡ ሼክስፒር እንደሚለው፤ “ከእንግዲህ እንቅልፍ የለችም
የእረፍት አድባር አጣች መቅኖ
ማክቤዝ እንቅልፍን ገደላት
በእኩለ - ሌሊት አፍኖ” … ለማለት የምንደፍርበት ጊዜ ነው፡፡ ዕውር ቢሸፍት ከጓሮ አያመልጥም እንደሚባለው፣ መርከብ ቢሸፍትም ከውሃው አይወጣም፡፡ ዛሬም፤ They

shout at most, against the vices they themselves are guilty of እንላለን፡፡ “ጅራፍ ራሱ ገርፎ ራሱ ይጮህ” እንደማለት

ነው:: የተነቃ ለታ ሁሉም እጁን ይሰጣል፡፡
“…የእጅ ሰንሠለት እረ አመቻቹ
ለእነ እንዳይበቃኝ ለቀማኞቹ!” መባሉ ለፌዝ አልነበረም፡፡
የኢትዮጵያውያንን መልካም ስም ያጐደፈ፣ ኢትዮጵያዊነትን የዘረፈ ከየትኛውም ባላንጣችን የማይተናነስ ጠላት ነው፡፡
“ገንዘቤን የሰረቀኝ ሰው ወሰደ እንበል ከንቱ ነገር
የእኔም የሱም የሷም ነበር
ግና ስሜን የሰረቀኝ የማያከብረውን ወስዶ እኔን በግልጽ አደኸየኝ” ማለት ይሄኔ ነው!
እስከ ዛሬ አያሌ ዘራፊዎችን፣ መዝባሪዎችን፣ የአየር - በአየር ሌቦችን ተሸክመን እዚህ ደርሰናል፡፡ አንዳንድ ተቋማት አይነኬ በመሆናቸው “እናውቃለን፤ ብንናገር እናልቃለን” በሚል

የፍርሃት መርህ፤ ስንበዘበዝ ከርመናል፡፡ መከላከያ አይነካም፡፡
ደህንነት አይጠቀስም፡፡ እገሌ የጠቅላይ ሚኒስትሩ ወንድም ስለሆነ አይደፈርም፡፡ እገሌ የእነ እገሌ ዘር ስለሆነ ባናስቀይመው ይሻላል ወዘተ እያልን፣ እያየናቸው በህዝብ ገንዘብና ንብረት

ሲላሲሎ ሲጫወቱ በዝምታ ተቀበልናቸው፡፡ አሁን መሸባቸው፡፡ እኛ ግን ዛሬም ገና አልነጋልንም፡፡ ቀጥለን ምን እናድርግ? አልተባባልንም፡፡ ነገን እንደፈራን፣ ነገን እንደሰጋን ነን፡፡ ይሄን

መሻር አለብን፡፡ አሁንም እየተለሳለሱ፣መፈክር እያሰገሩ የሚኖሩ ብዙ ጨዋ መሳይ “ታጋዮች” አሉ፡፡
“እባብ ቆዳው ለሰለሰ ብለህ ቀበቶ አድርገህ አትታጠቀውም” የሚባለው እኒህን እኩያን ዐይናችንን ገልጠን እንድናይና እነሱ ላይ ማነጣጠር እንድንችል ነው፡፡ እናነጣጥር፤ ግን ሳናልም

አንተኩስ!


    ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ጡረታ የወጣች አህያና አንድ ከቤት የተባረረ ውሻ አገር ለቀን እንሂድ ተባብለው ሲጓዙ፤
አህያዋ፤
“የማንታወቅበት አገር ሄደን አዲስ ሥራ ብንጀምር ጥሩ ነው” አለች፡፡
ውሻው፤
“መልካም ሃሳብ ነው፡፡ ዕድሜያችንን እንቀንስና እንቀጠር፡፡ ‘በአዲስ መልክ ሥራ ጀምረናል’ ማለት ብቻ እኮ ነው የሚያስፈልገው፡፡”
አህያዋም፤
“በጣም ጥሩ፡፡ ግን እግረመንገዳችንን አንድ ጊዜ ላናፋ ፍቀድልኝ” አለ፡፡
ውሻም፤
“ግዴለሽም እንጠንቀቅ፡፡ አያ ጅቦን ትቀሰቅሺዋለሽ”
አህያም፤
“በጣም ብዙ ስለጋጥኩኝ ነፋኝ ቀበተተኝ”
ውሻ፤
“እኔ የለሁበትም- እንዳሻሽ አድርጊ”
አህያ አንድ ጊዜ በከባዱ አናፋችና መንገዳቸውን ቀጠሉ፡፡
ጥቂት እንደሄዱም፤ አህያ
“አሁን አንዴ ልጩህ?”
ውሻም፤
“ተይ አህያ፣ የቅድሙ መቀስቀሻ የአሁኑ መቅረቢያ ነው”
አህያ፤
“እንደዚህ ሆዴን ነፍቶኝ፣ ቀብትቶኝ መንገድ መሄድ አልችልም”
ውሻም፤
“እኔ ተናግሬያለሁ፡፡ እንዳሻሽ!”
አህያ አንድ ጊዜ በረዥሙ አናፋች፡፡
ደግሞ ጥቂት እንደሄዱ “እንግዲህ አንድ ብቻ ነው የቀረኝ - አንድ የመጨረሻ ልጩህ” አለች አህያ፡፡
ውሻም፤
“ይሄውልሽ አህይት
የመጀመሪያው መቀስቀሻ፤ ነው፡፡
ሁለተኛው ማቅረቢያ ነው፡፡
ሦስተኛው መበያ ነው፡፡”
አህያም፤
“በምንም ዓይነት ካልጮህኩ አይወጣልኝም” አለችና የመጨረሻ ጮክ ብላ ጮኸች፡፡
ውሻ እንዳለው አያ ጅቦ መጣ፡፡ ውሻ ሮጦ አመለጠ፡፡ አህያን አያ ጅቦ ዘርግፎ ጣላት፡፡ ወዳጆቹን ጠርቶ ተቀራመቷት፡፡
***
የምንጨህበትን ሰዓት እንለይ፡፡ ጥጋባችንን ጋብ እናድርግ፡፡ ለምን ሊዳርገን እንደሚችል እናጢን፡፡ የታገልንለት፣ የሞትንለትና የተሰቃየንለት ነፃነት፣ ዲሞክራሲ፣ ፍትሕና እኩልነት ትርጉም ባለው መንገድ ፍሬ የሚያፈራው፣ ሰዓትና ጊዜ የለየ ዕቅድና አተገባበር ሲኖረን ነው፡፡
ነፃነት ከልኩ በላይ ሊያስፈነድቀንም ሆነ ከልኩ በታች ሊያደናብረን አይገባም፡፡ አዲስ ነገርን በሆይሆይታ ሳይሆን በጥሞናና በአበክሮ ማየት ብልህነት ነው፡፡ ስለ ጊዜ ያለን ግንዛቤ አጋጣሚዎችን በትክክል መጠቀምንም ሆነ ታግሶ ማለፍን ሊያስተምረን አስፈላጊ ነው፡፡ በ1966 ዓ.ም የተፈጠረውን አብዮታዊ ንፋስ በአግባቡ አልተጠቀምንበትም፡፡ የ1967 -68 ዓ.ም የዕድገት በህብረት የዕውቀትና የሥራ ዘመቻን ወቅትም ከፈጣን ተምኔታዊ ጉዞ ያለፈ ፋይዳ ላይ አላዋልነውም፡፡
በ1997 ዓ.ም ለውጫዊ ሁኔታ በጥድፊያ እንጂ በሰከነና በተደራጀ መልክ የተቃኘ፣ ጊዜን ከጉዳይ የጣፈ ቅኝት ያልነበረው ነበረና አጋጣሚው እንደ ዘበት አመለጠ፡፡ የአሁኑ ሌላ አጋጣሚ ነው፡፡ ከግርግር ይልቅ የተባና የረባ ድርጅትን መሠረት ያደረገ ቢሆን መልካም ነው፡፡ ከአቋራጭ ይልቅ የረዥም ጊዜ ዕቅድ ማቀድን እንልመድ! እንከን ፍለጋ ከመሮጥ ደግ ደጉን እናስተውል፡፡
አፋችን ቅቤ ልባችን ጩቤ ከሆነ፣ የምናመራው ወደ እብሪት ነው፡፡ ወደ ትምክህት ነው። እኔ ያልኩት ብቻ ነው ትክክል፤ የኔ አበባ ብቻ ናት ዕንቡጥ ማለት አያዋጣንም፡፡ የቆየውንና የተደበቀውን አጀንዳ በሆዳችን ይዘን፣ አዲስ ወይን እየጠመቅን ነው ብንል የለበጣ ጉዞ ነው፡፡ ተስፋችንን አጨላሚ ነው፡፡ ቀና ፉክክር እንጂ ድርጅታዊ የበላይነቴን ያለ ምርጫ አሸንፌያለሁ እንደ ማለት ያለ ጭፍን ግብዝነት የለም፡፡ በርትቶ በዲሞክራሲያዊው መንገድ ማሸነፍንና መሸነፍን እንልመድ እንጂ ብቆጣም እመታሻለሁ፣ ብትቆጪም እመታሻለሁ እንዳለው አባወራ መሆን ወንዝ አያሻግርም!

 አንጋፋው አርቲስት ፍቃዱ ተክለማሪያም ለኩላሊቱ ጉዳት መጋለጡ ከታወቀ በኋላ ህይወቱን  ለማትረፍ አድናቂዎቹ፣ የሙያ አጋሮቹና መላው የኢትዮጵያ ህዝብ በገንዘብ፣ በፀሎትና ኩላሊት ለመስጠት በመዘጋጀት አለኝታቸውን አሳይተዋል፡፡ ህዝቡ ለእሱ ያለውን ፍቅርና አክብሮት በህይወት እያለ የማየት ዕድልም ገጥሞታል፡፡
ሆኖም “እኔን ለማሳከም ልመና አትውጡ፤ከእነ ክብሬ ልሙት” በማለት ለህክምናው ወጪ የተጀመረውን ገንዘብ የማሰባሰብ ዘመቻ አርቲስት ፍቃዱ ቢቃወምም፣ “አይናችን እያየ አትሞትም” በሚል የሙያ አጋሮቹ ዘመቻውን ቀጠሉበት፡፡ የፍቃዱ የቅርብ ወዳጅ አርቲስት ፈለቀ አበበም፤ በወቅቱ በእስር ላይ ለነበሩት የኬኬ ኩባንያ ባለቤት አቶ ከተማ ከበደ፣ ጉዳዩን በመንገር፣ የ1.ሚ ብር ድጋፍ ለማግኘት ተችሏል፡፡   
ይሁንና አርቲስት ፍቃዱ ከዘመናዊ ህክምና ይልቅ መንፈሳዊውን በመምረጡ ወሎ ወልዲያ አቅራቢያ በምትገኘው ሲሪንቃ አርሴማ፣ ፀበል ሲጠመቅ ቆይቶ ህይወቱ አልፏል፡፡ ነገር ግን በሁለት ፈርጅ  ለህክምናው ተብሎ ከተሰበሰበው ገንዘብ ጋር በተያያዘ፣ባለፈው ሳምንት በኮሚቴዎች አለመግባባት የተፈጠረው ውዝግብ ብዙዎችን አሳዝኗል፡፡ “አርቲስት ፍቃዱ ለምን ከነክብሩ እንዳላረፈ ለእኔ እንቆቅልሽ ነው” የሚለው አርቲስት ፈለቀ አበበ፤በሰሞኑ ውዝግብ ቅሬታ እንደተሰማው ተናግሯል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፣ በጉዳዩ ዙሪያ ከአርቲስት ፈለቀ አበበ ጋር ተከታዩን ቃለ ምልልስ  አድርጋለች፡፡

   የአርቲስት ፍቃዱ ተ/ማርያምን የጤና መታወክ በቅርበት ታውቅ ነበር?
ጤናው መታወኩን የማውቀው ከኩላሊት ህመሙ በፊት በነበረበት የስኳር ህመም ነው፡፡ በብሔራዊ ቴአትር መድረክ ላይ አብረን ስንሰራ፣ ክብርት ባለቤቱ ለመቅሰስ በምትቋጥርለት የምሳ እቃ መነሻ፣ ስለ ስኳር ህመሙ አውርተን እናውቃለን፡፡ ኩላሊቱን እንደታመመ ስሰማ፣ በጣም ነበር የደነገጥኩት፤ በጣምም አዘንኩ። እርግጥ እኔ ብቻ ሳልሆን መላው የኢትዮጵያ ህዝብ ደንግጧል፤ አዝኗልም፡፡ ከእኔ ጋር አብረን  ለመስራት ብዙ አቅድ ነበር፡፡ እንደምታውቂው፤ ጋሽ ፍቄ ተአምረኛ ተዋናይ ነበር፤ አጣነው እንጂ!
በአንድ ወቅት በኢቴቪ “አርሂቡ” ፕሮግራም ላይ በእንግዳነት ቀርበህ፣ ጋሽ ፍቄ ስላንተ ችሎታ ሲመሰክርና እንደሚሳሳልህ ሲናገር ሰምቻለሁ፡፡ ትክክል --- ነኝ?
ትክክል ነሽ! እኔም በጣም እሳሳለት ነበር። ከአንጀቴ ነበር የምወደው፡፡ ሁላችንም እንወደዋለን፤ እናደንቀዋለን፡፡ እሱም የሙያ ተከታዮቹንና አዳዲስ ወጣት አርቲስቶችን ይወድና ያበረታታ ነበር፡፡ የ”አርሂቡ” እንግዳነቴን ካነሳሽው አይቀር፣ እኔም ከእርሱ ጋር መድረክ ላይ ስቆም፣ ሀሴት እንደማደርግ በዚያው ፕሮግራም ላይ ተናግሬ ነበር፡፡
በዚህ ቅርበታችሁ ይመስለኛል በታመመ ጊዜ፣ ድጋፍ እንዲያገኝ የታተርከው?
እውነት ነው፡፡ ነገር ግን ባለሀብቱ ቀድመው ሊረዱት ተዘጋጅተው ነበር፡፡ እኔ እንደ ቧንቧ ነው ያገለገልኩት ማለት ትችያለሽ፡፡
እንዴት?
ነገሩ እንዲህ ነው፡፡ የኩላሊት ህሙማን ማህበር፤ አቶ ከተማ ከበደን (የኬኬ ኩባንያ ባለቤት) የክብር አምባሳደር አድርጓቸው ነበር። አቶ ከተማ ከአምባሳደርነታቸውም በተጨማሪ ከቤተሰባቸው በኩላሊት ህመም የተጐዱ ስለነበሩ፣ የችግሩን ጥልቀትና ስፋት በውል ያውቁት ነበር፡፡ ወህኒ ቤትም ሳሉ ስለ ህሙማኑ ይብሰለሰሉ ነበር።
በዘውዲቱ መታሰቢያ ሆስፒታል ለተቋቋመው “የኩላሊት ህሙማን በጐ አድራጐት ማህበር” 5 ሚሊዮን ብር መለገሳቸውም በአዲስ አድማስ ተዘግቧል ---
ትክክል ነው፡፡ እናም አንድ ቀን ልጠይቃቸው የታሰሩበት ወህኒ ቤት ሄጄ፣ ብዙ ከተጨዋወትን በኋላ በኩላሊት ህሙማን አምባሳደርነታቸው ምን ሊሰሩ እንዳሰቡ ጠየኳቸውና፣ እግረመንገዴንም አንዲት እርዳታ የሚያሻት ታዳጊ ወጣት እንዳለች ነገርኳቸው፡፡ እሳቸውም “ዛሬ እንኳን መጣህ፤ ማታ በቴሌቪዥን አይቻት ነበር፤ ሜላት አሰፋ አይደል የምትባለው” አሉኝ፡፡ አክለውም፤” በል ቶሎ አግኛትና ለጊዜው የዲያሊሲስ ህክምና እንዳታቋርጥ እንርዳት፤ ቀጣዩን ከቤተሰቧ ጋር ተነጋግረን እንወስናለን” አሉ፡፡
ጋሽ ፍቄ ከተለገሰው 1 ሚሊዮን ብር ላይ 200 ሺህ ብር ያካፈላት ታዳጊ ናት አይደል?
ትክክል፡፡ ከጋሽ ፍቃዱ እገዛ  በፊት አቶ ከተማ  ሊረዷት መሞከራቸውን አስታውሳለሁ። በኔ ግምት አቶ ከተማ ከበደ፤ እያንዳንዱን የሚያደርጉትን ድጋፍ ሰው እንዲያውቀው የሚፈልጉ አይመስለኝም እንጂ ለሌሎችም በርካታ በኩላሊት ህመም ለተጠቁም ሆነ የተለያየ እገዛ ለሚያስፈልጋቸው ሰዎች፣ ተገቢ ሆኖ ሲያገኙት፣ የልግስና እጃቸውን ከመዘርጋት ወደ ኋላ አይሉም። ይህንን ደራሽነታቸውን ደግሞ ሁሉም የሚያውቅ ይመስለኛል፡፡
ለአርቲስት ፈቃዱ ተ/ማርያም ወዳደረጉት ድጋፍ  እንመለስ---
የጋሽ ፍቄን መታመምና የቤተሰቡንና የህዝቡን ድንጋጤ ስመለከት፣ ተነስቼ ወደ እሳቸው ሄድኩኝ - ወህኒ ቤት፡፡ ገና ስንገናኝ “ምነው ፊትህን እንዲህ ክረምት አስመሰልከው?” አሉኝ፡፡ እኔም “የሙያ አባቴ ኩላሊቱን በጠና ታሟል፤ ፊቴን ያጨፈገገው ምክንያት ይሄው ነው፤ እባክዎ አፋጣኝ ህክምና ያስፈልገዋል” ብዬ ሳልጨርስ፤ “እኔም ዜናውን በቴሌቪዥን አይቼ፣ እንደው ምን ባደርግለት ይሻላል እያልኩ ነበር፤ በጣም ያስደነግጣል” አሉኝና፤ “ለመሆኑ ኩላሊትስ የሚሰጠው ያገኝ ይሆን?” ሲሉ ጠየቁኝ፡፡ ወዲያው፤ “ቶሎ እንዲታከም 1 ሚ. ብር በአስቸኳይ ይሰጠው፡፡ ያን የሚያህል ትልቅ ያገር ሀብት በጭራሽ የሰው ፊት ማየት የለበትም” ብለው እዚያው በቆምኩበት ወሰኑ፡፡ “ይሄ ብር ለህክምናው ይዋል፤ ከዚህ በኋላም የሚያስፈልገውን የትኛውንም ወጪ ለመሸፈን ዝግጁ ነኝ” በማለት ቃል ገብተውልኝ ተለያየን፡፡
ከዚያስ?
በመጀመሪያ ለጋሽ ፍቄ፤ 1 ሚ. ብር የለገሰው ሰው እንዳለ ነገርኩትና በጣም ተደሰተ፡፡ ያው ጋሽ ፍቄ ማንም ሰው እንደሚያውቀው ትሁት ነው፡፡ በትህትና አመስግኖ፣ የኮሚቴው ሰብሳቢ ሃይሉ ከበደ መሆኑን ነገረኝና እኔም ደውዬ፣ ሁኔታውን አሳውቅሁት፡፡ ሃይሉ ከበደም በምሳ ሰዓት ከኮሚቴው አባላት ጋር አገናኘኝ፡፡  
አንድ ያልገባኝ ነገር አለ፡፡ አቶ ከተማ ከ1 ሚ. ብሩም በኋላም ተጨማሪ እገዛ እንደሚያደርጉለት ቃል መግባታቸውን ነግረኸኛል፡፡ ለህክምናውም የሚበቃውን ገንዘብ ፈቅደዋል፡፡ ነገሩ እንዲህ ከሆነ ጋሽ ፍቄ፤ “ልመና አትውጡ፤ ከነክብሬ ልሙት” እያለ ለምንድን ነው የኮሚቴ አባላቱ ገንዘብ ማሰባሰባቸውን የቀጠሉት?
ጋሽ ፍቃዱ ራሱ እንደፈለገው፣ ከእነ ክብሩ እንዳይሞት የሆነበት ምክንያት፣አሁንም ድረስ ለእኔ እንቆቅልሽ ነው፡፡ በትክክል ለኮሚቴው አሳውቄያለሁ፡፡ ለራሱ ለጋሽ ፍቃዱም ሁሉን ነገር ነግሬው ነበር፡፡ አቶ ከበደ ሁሉንም ወጪ ለመሸፈን ዝግጁ መሆናቸውን ነግሬው፤ ልመናው እንዲቆም አማክሬው ነበር፡፡ በበኩሌ፤ ያ መልካም አጋጣሚ፣ በአደባባይ እርዳታ ከመጠየቅ የተሻለ አማራጭ ነበር ብዬ አምናለሁ፡፡
ታዲያ ጋሽ ፍቄ፤ ስታማክረው ምን አለህ?
“እኔም’ኮ ከእነ ክብሬ ልሙት ብዬ ነበር ፈለቀ” አለኝ፤ በሀዘንና በብስጭት እየተወራጨ፡፡
እንደፈለገው “ከእነ ክብሩ እንዳይሞት” እንቅፋት የሆነበትን ነገር ለማወቅ አልሞከርክም?
ልጠይቀው ፈልጌ ነበር፡፡ ግን ደግሞ በወቅቱ በነበረበት ስሜት ውስጥ ሆኖ፣ መገዳደርና ገፍቼ መጠየቅ አልቻልኩም፡፡ አሁን ታዲያ ፀፀቱ በውስጤ አለ፤ ምነው ደፍሬ እንቅፋት የሆነበትን ጉዳይ በጠየቅኩት ነበር እላለሁ፡፡ መኖሪያ ቤቱ ግቢ ውስጥ ብቻችንን ስንቀር ነበር የነገርኩት፡፡ በነገራችን ላይ ቼኩ የተፃፈው በጋሽ ፍቃዱ ስም ነበር፡፡ ለራሱ ለጋሽ ፍቃዱ ነው መኖሪያ ቤቱ ወስደን የሰጠነው፡፡
ከማን ጋር ሆናችሁ ነበር ቼኩን ያስረከባችሁት?
እኔ የአቶ ከተማ ከበደ ጓደኛ የሆነው አቶ ሲራክ በትዕዛዙ፣ ወኪሉ አቶ ቴዎድሮስ ቦጋለና አርቲስት አበበ ባልቻ ሆነን ነው ሄደን የሰጠነው። ጋሽ ፍቄም “ሁሉንም ጉዳዬን ለያዘልኝና ለእኔ መስዋዕት እየከፈለ ላለው ኮሚቴ” ብሎ ቼኩን ለኮሚቴው አስረከበ፡፡
ሰሞኑን ለአርቲስቱ መታከሚያ በተሰበሰበው ገንዘብ ዙሪያ በኮሚቴውና በአርቲስት ቴዎድሮስ ተሾመ መካከል ውዝግብ መነሳቱ ይታወቃል፡፡ ነገሩን  ስትሰማ ምን አልክ?
እንግዲህ እኔ የማውቀው ቴዎድሮስ ተሾመ፤ ለጋሽ ፍቃዱ መኪና በስጦታ ማበርከቱን ነው። ይልቅ ሰሞኑን  በኮሚቴዎቹ ከተሰባሰበው ገንዘብ ውጭ አስገራሚ መረጃ ሰምቼአለሁ፡፡ የእርሻ በሬያቸውን ሸጠው ጋሽ ፍቄን ለመርዳት የወሰኑ እንዲሁም  ኩላሊት ለመገለስ የተመዘገቡ፣ ባልሳሳት ከ30 በላይ የግለሰቦች ሥም ዝርዝር፣ የጋሽ ፍቄ ወንድም ግርማ ተክለማርያም አሳይቶኛል፡፡ ይሄ በመላው ኢትዮጵያ አድናቂዎቹ፣ ለጋሽ ፍቄ ያላቸውን ፍቅርና አክብሮት የሚመሰክር ነው፡፡  
አቶ ከተማ  ከአርቲስት ፍቃዱ ጋር የመገናኘት እድል ገጥሟቸዋል?
አንድ ጊዜ አቶ ከተማን ለማመስገን፣ ጋሽ ፍቄ ወህኒ ቤት ሄዶ ነበር፡፡ በወቅቱ አቶ ከተማም፤ “አንተም ታክመህ ድነህ፣ እኔም ከእስር ወጥቼ፣ ቁጭ ብለን እንጫወታለን” ብለውታል፡፡ ጋሽ ፍቃዱም በምስጋና ንግግሩ መሀል፤ “እሳቸው (አቶ ከተማ) ከሚገኙበት ጭንቅ በላይ ለኔ በማሰባቸው ሆድ ይመርቅ” ብሎ ነበር፡፡
በመጨረሻስ የምትለው አለህ----?
እኔ ከዚህ በላይ ብዙ ማለት አልፈልግም። በውስጤ የምፀፀትበትን ነገር ነግሬሻለሁ፡፡ አሁን አደባባይ የወጣው ውዝግብ ደስ አይልም፡፡ የጋሽ ፍቃዱን ነፍስ ይማር፡፡ ለኮሚቴዎቹ ፈጣሪ ብድራቸውን ይክፈላቸው። እንደ አቶ ከተማ ከበደ አይነት ያላቸውን የሚያካፍሉ ለጋሶችንና ባለፀጐችን ያብዛልን እላለሁ፡፡ በደበበ ሰይፉ ስንኝ ብናሳርግስ---
ከሜዳ ከአውድማ አንድ ፍሬ ብትጠፋ
የፍቅር ድምጽ ከፋ እምነት በአፍጢሙ ተደፋ።

በአሜሪካ አንድ ፕሬዚዳንት ወደ ስልጣን በመጣ በ2 አመቱ ወይም በስልጣን ዘመኑ እኩሌታ ላይ የሚካሄደውና የአጋማሽ ዘመን ምርጫ በመባል የሚታወቀው የኮንግረስ  ምርጫ በሳምንቱ መጀመሪያ ተከናውኗል፡፡
በየአራት አመቱ በወርሃ ህዳር በሚካሄደውና ባለፈው ማክሰኞ በተካሄደው የአሜሪካ የአጋማሽ ዘመን ምርጫ፤ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዴሞክራቶች 219 ወንበሮችን በማግኘት ሲያሸንፉ፣ ሪፐብሊካኑ ደግሞ በሴኔት ምርጫ ድል ቀንቷቸዋል፡፡
ከአሜሪካ የአጋማሽ ዘመን ምርጫ ጋር በተያያዘ አለማቀፍ የመገናኛ ብዙሃን ከዘገቧቸው ጉዳዮች መካከል ጎላ ያሉትን መራርጠን እንዲህ አቅርበናል፡፡
***

ሴቶች ታሪክ ሰርተዋል
በአሜሪካ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ ታሪክ እንዳሁኑ በርካታ ቁጥር ያላቸው ሴቶች ለምክር ቤቶች ተወዳድረውም አሸንፈውም አያውቁም፡፡ ለሁለቱም ምክር ቤቶች በዕጩ ተወዳዳሪነት የቀረቡት ዲሞክራትና ሪፐብሊካን ሴቶች ድምር ቁጥር 3 ሺህ 379 ሲሆን ይህም በምርጫው ታሪክ ከፍተኛው ቁጥር እንደሆነ ሎሳንጀለስ ታይምስ ዘግቧል፡፡
በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ 99 ያህል ሴቶች ያሸነፉ ሲሆን፣ ሁሉም ማለት ይቻላል ዲሞክራቶች መሆናቸው ተነግሯል፡፡ በሴኔት አሸናፊ የሆኑት ሴቶች ቁጥርም 22 ነው ተብሏል፡፡
የ29 አመት ዕድሜ ያላቸው አሌክሳንድራ ኮርቴዝና አቢ ፊንከኖር በአሜሪካ ታሪክ በለጋ ዕድሜያቸው የምክር ቤት አባል በመሆን ተመዝግበዋል፡፡
ሶማሌ-አሜሪካዊቷ ስደተኛ ኢሃን ኡመር እና ትውልደ ፍልስጤማዊቷ ራሺዳ ጠይባ፤ በአሜሪካ ምክር ቤት አባል በመሆን የመጀመሪያዎቹ የሙስሊም እምነት ተከታይ ሴቶች ሆነው በታሪክ ተመዝግበዋል፡፡
እጅግ ከፍተኛ ገንዘብ የወጣበት ምርጫ
የማክሰኞው የአሜሪካ የአጋማሽ ዘመን ምርጫ በአገሪቱ ታሪክ እጅግ ከፍተኛው የምርጫ ቅስቀሳና ዝግጅት ወጪ የተደረገበት መሆኑ ተነግሯል። ሴንተር ፎር ሪስፖንሲቭ ፖለቲክስ የተባለው ተቋም ባወጣው መረጃ እንዳለው፤ የአጋማሽ ዘመን ምርጫው በአጠቃላይ 5.2 ቢሊዮን ዶላር ያህል ወጪ እንደተደረገበት ይገመታል፡፡
ለሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ምርጫ ቅስቀሳና ዝግጅት ዲሞክራቶች 624.7 ሚሊዮን ዶላር፣ ሪፐብሊካኖች ደግሞ 471.6 ሚሊዮን ዶላር ያህል ወጪ አድርገዋል፡፡ ለሴኔት ምርጫ በአንጻሩ ዲሞክራቶች 368.6 ሚሊዮን ዶላር፣ ሪፐብሊካኖች ደግሞ 233.9 ሚሊዮን ዶላር ያህል ገንዘብ ማውጣታቸው ተዘግቧል።
113 ሚሊዮን ድምጾች
በዘንድሮው የአሜሪካ የአጋማሽ ዘመን ምርጫ፤ 113 ሚሊዮን ያህል መራጮች ድምጻቸውን እንደሰጡ ይገመታል ሲል ሲቢኤስ ኒውስ ዘግቧል፡፡ በምርጫው ድምጻቸውን ለመስጠት ከሚችሉት ዜጎች መካከል 48 በመቶው መብታቸውን ተጠቅመው ድምጻቸውን መስጠታቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ በ2014 በተደረገው ምርጫ መብታቸውን የተጠቀሙ ዜጎች 39 በመቶ ያህሉ ብቻ እንደነበሩ አስታውሷል፡፡
36 ሚሊዮን የቴሌቪዥን ተመልካቾች
የአጋማሽ ዘመን ምርጫውን የድምጽ አሰጣጥና የምርጫ ውጤት ገለጻ አጠቃላይ ሂደት በርካታ አለማቀፍ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች በመላው አለም ያሰራጩ ሲሆን፣ በታላላቆቹ የአሜሪካ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ብቻ የምርጫ ሂደቱን የተከታተሉት ተመልካቾች ቁጥር 36.1 ሚሊዮን ያህል እንደሚደርስ ተዘግቧል፡፡
ፎክስ ኒውስ፣ ኤንቢሲ፣ አቢሲ፣ ሲኤንኤን፣ ኤምኤስኤንቢሲ እና ሲቢኤስ በበርካታ ተመልካቾች በመታየት እንደ ቅደም ተከተላቸው ከአንደኛ እስከ አምስተኛ ደረጃን የያዙት የአሜሪካ የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ናቸው፡፡
የመጀመሪያው ትውልደ ኤርትራዊ  
ከስደተኛ ኤርትራውያን ወላጆች በአሜሪካ የተወለደው ጆ ንጉሴ፤ በአሜሪካ የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባል በመሆን የመጀመሪያው ትውልደ ኤርትራዊ ሆኖ ተመዝግቧል፡፡
በኮሎራዶ ዲሞክራቶችን ወክሎ የተወዳደረው የ34 አመቱ ትውልደ ኤርትራዊ ጆ ንጉሴ፤ 60 በመቶ ድምጽ በማግኘት ያሸነፈ ሲሆን፣ በኮሎራዶ የመጀመሪያው ጥቁር የኮንግረስ አባልና ግዛቱን ከወከሉ ዘጠኝ ተወካዮች መካከልም በእድሜ ትንሹ እንደሆነ ቢቢሲ ዘግቧል፡፡

 በማክሰኞው የአሜሪካ የአጋማሽ ዘመን ምርጫ በማሸነፍ፣ ታሪክ ከሰሩት ሁለቱ ሙስሊም ስደተኛ ሴቶች አንዷ ናት - ትውልደ ሶማሊያዊቷ ኢልሃን ኡመር፡፡ የሶማሊያ የእርስ በእርስ ጦርነት በተፋፋመበት ወቅት፣ እናትና አባቷ ነፍሳቸውን ለማዳን ማቄን ጨርቄን ሳይሉ የ8 አመቷን ልጃቸውን ኢልሃንን አዝለው፣ ከቤትና ከአገራቸው ርቀው ተሰደዱ፡፡
ከወላጆቿ ጋር አገሯን ጥላ የተሰደደቺው ኢልሃን ማረፊያዋ በአፍሪካ ግዙፉ የኬንያው ዳባብ የስደተኞች መጠለያ ካምፕ ነበር፡፡ በአስከፊው ዳባብ የስደተኞች የመጠለያ ካምፕ አራት አመታትን የገፋቺው ኢልሃም፣ የ10 አመት ህጻን ሳለች ነበር ወደ አሜሪካ የተጓዘቺው፡፡ በወቅቱ የእንግሊዝኛ ቋንቋ ባለማወቋ ለመግባባትና ለመማር ተቸግራ እንደነበር ይነገራል፡፡
በሚኒያፖሊስ የማህበራዊ ንቅናቄ ስራዎችን በመስራት የምትታወቀው የ36 አመቷ ትውልደ ሶማሊያዊት ኢልሃም፤ በአፍሪካን አሜሪካን የሲቭል መብቶች ቡድን ውስጥም ንቁ ተሳትፎ ታደርግ ነበር፡፡ የትራምፕን የስደተኞች ፖሊሲ አጥብቃ በመቃወም የምትታወቀው ኢልሃም በዘንድሮው የአጋማሽ ዘመን ምርጫ፣ ሚኒሶታ ላይ ዲሞክራቶችን ወክላ በመወዳደር፣ ታሪካዊ ድልን የተቀዳጀቺው ኢልሃን፤ በአሜሪካ ታሪክ የመጀመሪያዋ ሴት የእስልምና እምነት ተከታይ፣ ጥቁር ስደተኛ የምክር ቤት አባል ሆና ስሟን በደማቅ ቀለም አስጽፋለች፡፡
“በዚህች ምሽት እነሆ ወኪላችሁ ሆኜ ከፊታችሁ ቆሜያለሁ!... ከስሜ ጀርባ የተሸከምኩት ብዙ ኃይል አለኝ። ግዛታችንን ወክላ የምክር ቤት አባል የሆነች የመጀመሪያዋ ጥቁር ሴት፤ ሂጃብ ለብሰው በኩራት በምክር ቤት ውስጥ ለመሰየም ከታደሉት የመጀመሪዎቹ ሁለት ሴት ሙስሊም ስደተኞች አንዷ ነኝ!” ብላለች፤ ኢልሃም ታሪካዊውን ድል መጎናጸፏን ተከትሎ ለደጋፊዎቿ ባደረገቺው ንግግር፡፡

 አፍሪካ 1 ትሪሊዮን ዶላር ከሚደርሰው የአፍሪካ አመታዊ አለማቀፍ ንግድ ውስጥ የአህጉሪቱ አገራት ያላቸው ድርሻ 15 በመቶ ብቻ መሆኑን ኦልአፍሪካን ኒውስ ዘግቧል፡፡ የአፍሪካ ኤክስፖርት ኢምፖርት ባንክ ሰሞኑን ያወጣውን መረጃ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ አፍሪካ አገራት በአመታዊው የአህጉሪቱ አለማቀፍ ንግድ ውስጥ ያላቸው ድርሻ 150 ቢሊዮን ዶላር ያህል ብቻ ነው፡፡
የአገራቱ የንግድ ድርሻ አነስተኛ ሊሆን የቻለው አገራቱ በቂ የአለማቀፍ ንግድ ገበያ መረጃ ስለሌላቸውና ንግዱን የሚደግፍ በቂ መሰረተ ልማት ለመገንባት ባለመቻላቸው ነው ብሏል ተቋሙ፡፡ አንዳንድ አገራት የአፍሪካ የንግድ ስምምነትን አለመፈረማቸው የንግድ ተሳትፎ ድርሻቸውን ዝቅ እንዳደረገባቸውም ተቋሙ ኣስታውቋል፡፡

ጥቁርና ነጭ ቴሌቪዥን ፋሽኑ ካለፈበትና ባለቀለም ቴሌቪዥን ከመጣ ከ50 አመታት በላይ ቢሆነውም፣ በእንግሊዝ ከ7 ሺህ በላይ ቤተሰቦች አሁንም ጥቁርና ነጭ ቴሌቪዥን እንደሚያዩ ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
በእንግሊዝ ባለቀለም ቴሌቪዥን ገበያ ላይ የዋለው እ.ኤ.አ በ1967 እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ በአገሪቱ 7 ሺህ 161 ያህል ቤተሰቦች አሁንም ድረስ ቴሌቪዥናቸውን እንዳልቀየሩ አመልክቷል፡፡ ባለቀለም ቴሌቪዥን ከመጣ በኋላ ጥቁርና ነጭ ቴሌቪዥን የሚገዙ የአገሪቱ ዜጎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ ቢሆንም አንዳንዶች ግን ለመቀየር አለመፈለጋቸውን ዘገባው አስረድቷል፡፡

 በፈረንጆች አመት 2018 ያለፉት ወራት ጊዜ ውስጥ ብቻ ሜዲትራኒያን ባህርን አቋርጠው ወደ አውሮፓ ለመግባት በጉዞ ላይ ሳሉ በባህር ውስጥ ሰጥመው የሞቱ የተለያዩ አገራት ስደተኞች ቁጥር፣ ከ2ሺህ በላይ መሆኑን ተመድ አስታውቋል፡፡የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ተቋም ያወጣው ሪፖርት እንደሚለው፤ በሜዲትራኒያን ባህር በአስቸጋሪ ጉዞ ውስጥ አልፈው ወደ አውሮፓ ለመግባት ሲሞክሩ ለተለያዩ አሰቃቂ አደጋዎችና ለሞት የሚዳረጉ ስደተኞች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ ይገኛል፡፡
ህገ ወጥ የሰዎች አዘዋዋሪዎች ስደተኞችን በአደገኛ ሁኔታ ውስጥ ማጓጓዛቸው መበራከቱን የጠቆመው ሪፖርቱ፣ አደጋዎች በሚከሰቱበት ጊዜ ፈጥነው የሚደርሱና የነፍስ አድን ስራ የሚሰሩ መንግስታዊ ያልሆኑና አለማቀፍ ተቋማት ስራቸውን እንዳይሰሩ መታገዳቸው ለሟቾች ቁጥር መጨመር አንዱ ምክንያት መሆኑንም አመልክቷል፡፡

Saturday, 10 November 2018 13:16

ጀግንነት በየፈርጁ!

 በአሜሪካ ሚኔሶታ ግዛት ነው፡፡   
ለአሜሪካዊው የእሳት አደጋ ሠራተኛ ጀሬሚ ቦሮሳ ልዩ ቀን ነበረች፡፡ ከወደፊት የህይወት አጋሩ ክሪስታ ቦላንድ ጋር ትዳር የሚመሰርቱበት የጋብቻ  ዕለት፡፡ ሙሽሮቹና ጥቂት ዘመድ ወዳጆቻቸው፣ የማስታወሻ ፎቶግራፍ ለመነሳት፣ የእሳት አደጋ መከላከያ ጣቢያው ጋ ተሰባስበው ነበር፡፡ ይሄን ጊዜ ነው  ቦሮሳ  ከሥራ ባልደረቦቹ  ያልጠበቀው የስልክ ጥሪ የደረሰው፡፡ በአቅራቢያ በሚገኝ የመኖሪያ ቤት ላይ  የእሳት ቃጠሎ ደርሶ፣ የሰው ሃይል ስላነሳቸው ነበር  የደወሉለት፡፡ ጀሬሚ ቦሮሳ  እረፍት ላይ  ቢሆንም፣ ለባልደረቦቹ ድንገተኛ የእርዳታ ጥያቄ ጆሮ ዳባ ልበስ አላለም፡፡ ከመቅጽበት የሠርግ ሥነስርዓቱን አቋርጦ ሄደ እንጂ፡፡ በደቂቃዎች ውስጥም ዩኒፎርሙን ለብሶ  ባልደረቦቹን ተቀላቀለ፡፡   
ከሁለት ሰዓት በኋላ  ግዳጁን ተወጥቶ፣ ወደ ሠርግ ሥነሥርዓቱ ሲመለስ፤ “እንግዶች በሙሉ ቆመው  በጭብጨባ ተቀብለውታል” ብላለች፤ውድ ባለቤቱ  ክሪስታ ቦላንድ፡፡ ከዚህ በኋላ ነበር ሠርጋቸውን በዳንስ ያደመቁት፡፡ በጀግንነት ተግባር የታጀበ፣ አይረሴ  ሠርግ  ይሏል ይኼ ነው፡፡      
*   *   *
የአየርላንድ ተወላጇ ካይትሮይና ላሊ፤ ከዱብሊን  ትሪንቲ ኮሌጅ የተመረቀችው የዛሬ 14 ዓመት ነበር፡፡ በ2015  ወደ ኮሌጁ የተመለሰችው ትምህርቷን ለመቀጠል አልነበረም፡፡ በጽዳት ሠራተኛነት ተቀጥራ ለመሥራት እንጂ፡፡ ይሄኔ ነበር “Eggshells”  የተሰኘው የበኩር  ረዥም ልብወለዷ ለንባብ የበቃው፡፡  ይሄን ልብወለዷን የጻፈችው  ከሥራ ውጭ በቆየችባቸው  ዓመታት ነበር፡፡     
 ባለፈው ሳምንት ታዲያ ልታምነው ያዳገታትን  ዜና ሰማች፡፡ “Eggshells”  የተሰኘው  መጽሐፏ የኮሌጁን ከፍተኛ የሥነጽሁፍ ሽልማት አሸነፈ፡፡ ሩኔይ የአየርላንድ ሥነጽሁፍ ሽልማት፤ “የላቀ ተስፋ” ለሚጣልባቸው፣ ዕድሜያቸው  ከ40 ዓመት በታች ለሆኑ ጸሐፍት የሚሰጥ ዓመታዊ ሽልማት ነው፡፡ የሥነጽሁፍ ሽልማቱ 11 ሺ 500 ዶላርም (300 ሺ ብር ገደማ) ይጨምራል፡፡  ሽልማቱን ማሸነፏ “ፍጹም ተዓምር ነው” ያለችው  ላሊ፤ በአሁኑ ወቅት ሁለተኛ ልብወለዷን በመጻፍ ላይ እንደምትገኝ ታውቋል፡፡ ማን ያውቃል፣ ለሁለተኛ  ሽልማት ትበቃ ይሆናል፡፡      
ምንጭ፡- (THE WEEK October 12,2018)