
Administrator
“መንግስት ከገለልተኝነት ባሻገር ወደ ህጋዊው አካል ማዘንበል አለበት”
“ትልልቅ የመንግስት ሚዲያዎች አለመዘገብ ምንም ችግር እንዳልተፈጠረ ማስመሰል ነው”
ጋዜጠኛና ደራሲ በኩረ ትጉሃን ጥበቡ በለጠ)
ከአንድ ሳምንት በፊት በቀድሞው አቡነ ሳዊሮስ የሚመራው አካል የኦሮሞያና የብሄር ብሄረሰቦች ሲኖዶስ መሰርቻለሁ ማለቱን ተከትሎ ቅዱስ ሲኖዶስ እነዚህን አካላት ማውገዙ ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ እነዚህ አካላት በተለያዩ አካባቢዎች ቤተክርስቲያናትን እያስገደዱ በመግባታቸውና ይህን ድርጊት በመቃዎማቸው ምዕመናን በመንግስት ታጣቂዎች እየተገደሉ መሆናቸውን ተከትሎ በሀገር ውስጥም ሆነ በመላው ዓለም መንግስትንና የተወገዙትን አካላት በሰላማዊ ሰልፍ እየተቃወሙ ይገኛሉ፡፡ ይህንን ተከትሎ በኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንና በመንግስት መካከል ውጥረት ነግሶ ይገኛል፡፡ ይሄ ጉዳይ መንስኤው በትክክል ምንድን ነው?መፍትሄውስ ምን መሆን አለበት? ከመንግስትስ ምን ይጠበቃል ከቤተክርስቲያን በኩልስ? በሚሉና በተያያዥ ጉዳዮች የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ከአንጋፋው ጋዜጠኛና ደራሲ በኩረ ትጉሃን ጥበቡ በሰጠና የቤተክርስቲያንን በደል ለፍርድ ቤት ከወሰዱት የህግ ባለሙያዎች መካከል አንዱ ከሆነው አንዱ አለም በውቀቱ ገዳ ጋር ተከታዩን ቃለ ምልልስ አድርጋለች እንድታነቡት እንጋብዛለን፡
የቤተክርስቲያኗን ጉዳይና ወቅታዊ ሁኔታውን እንዴት ታየዋለህ በትክክል ችግሩ የቋንቋ ነው ወይ ላልሽው እውነት ለመናገር በኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተ ክርስቲያን ውስጥ የቋንቋ ጉዳይ ከዚህ ቀደም ይነሳ ነበር፡፡ ጥያቄው ረጅም አመታት አስቆጥሯል፡፡
በኦሮምኛ ቋንቋ ብቻ ሳይሆን በሁሉም የብሄር ብሄረሰቦች ቋንቋ እናስተምር በየገጠሩ ገብተን ዜጎች በሚገለገሉበት ቋንቋ ካህናትን እናፍራ የሚል ትልቅ ፕሮጀክት እንደነበር በጋዜጠኝነት ህይወቴ ውስጥ አውቀዋለሁ፡፡ ፕሮጀክት ተቀርፆ ሲሰራበትም አውቃለሁ፡፡ ይህ እንግዲህ ከአስር ዓመታት በፊት ነው፡፡ ምክንያቱም የቋንቋው ፖለቲካም በሀይማኖቱ ላይ ጫና እያሳደረ ስለነበረ እንዲሁም የአንድ ወይም የሁለት ብሄር ሀይማኖት ነው የሚል ትርክትም መጥቶ ስለነበር የዛን ጊዜ በስፋት ተሰርቶበት በጣም ብዙ ከተለያዩ ቋንቋ ተናጋሪዎች ለክህነት የበቁ ካህናት እንዳሉ አውቃለሁ፡፡
ከዚያ በኋላ እንዲያውም ትንሽ ወጣ ባለ መልኩ ጳጳሳትም ከተለያዩ ብሄሮች እንደተሾሙም አውቃለሁ፡፡ አሁን ተገንጥለው ያሉትም እኮ በቋንቋና በብሄራቸው ተሹመው የነበሩ ናቸው፡፡ ስለዚህ የቋንቋ ጉዳይን ካነሳን የቀድሞው አቡነ ሳዊሮስ የተሾሙት በቋንቋቸውና በብሄራቸውም ጭምር ነው፡፡
ይህንን ካልን በኋላ ከእሳቸውና እሳቸውን መሰል ሹሞች የሚጠበቀው ደግሞ በሀገረ ስብከታቸው ውስጥ የበለጠ መምህራንንና ዲያቆናትን በቋንቋቸው ማፍራት ነው፡፡ እነሱ ሀላፊዎች ስለሆኑ ወንጌለ ስብከትን፣ አገልጋዮችን በራሳቸው ቋንቋ ማስፋፋትና ማሳደግ ያለባቸው ራሳቸው ናቸው የቋንቋ ጥያቄም ካለ ተጠያቂዎቹ እነሱ ናቸው፡፡
ሌላው ግን በቋንቋዬ አልተማርኩም ብሎ ያመፀ ምዕመን አለ ወይ? ምዕመኑ መቼ ጠየቀ? መቼስ ቅሬታ አቀረበ? የሚለው ነው የኔ ጥያቄ፡፡ ምዕመኑ መቼ ነው የጠየቀው በየትኛው ጉባኤ? በየትኛው ደብዳቤ? ማንስ ነው የከለከለው? ተከልክሎ ያውቃል ወይ? የሚሉ ነገሮች አላየናቸውም፡፡ ነገሩን በአጠቃላይ ስናየው ሐይማኖት የቋንቋ ጉዳይ ብቻም አይደለም፡፡ ለምሳሌ እስልምና በአረብኛ ቋንቋ ነው በብዙ መልኩ የሚሰበከው ፖፕ ፍራንሲስ የሁሉንም አገር ቋንቋ አይችሉም፡፡ ምናልባት ሁለት ሶስት ቋንቋ ቢችሉ ነው፡፡
እዚህ አሁን እኛ ጋር የመጣው ነገር የሚመስለኝ ሀገራችን ኢትዮጵያ ላለፉት 30 ምናምን ዓመታት የሄደችበት ብሄርን መሰረት ያደረገ የፖለቲካ አስተሳሰብ እንዳለ ወደ ሀይማኖት ውስጥ በመግባቱ ነው፡፡ ሀይማኖቱ ደግሞ ይህን በብሄር በጎሳ መደራጀቱን አያውቀውም፡፡ የተለያየ ቋንቋ ተናጋሪ ልትሆኚ ትችያለሽ፣ የሀይማኖቱን ቀኖና እና ዶግማ ተከትለሽ መሄድ ብቻ ነው የሚጠበቀው። እናም ሀይማኖት የትኛውንም የፖለቲካ አደረጃጀት አያውቅም፡፡ እስልምናውም ያንን የሚያውቅ አይመስለኝም፡፡ እናም ያ አስተሳሰብ ሀይማኖቱ ውስጥ ገብቶ ነው ቤተክርስቲያኒቱን እንዲህ እየበጠበጣት ያለው፡፡ ስለዚህ ህጋዊ የሆነው ሲኖዶስ አለ፡፡ ከእሱ ውጪ ያሉ ሲኖዶሶች፣ ህጋዊ ናቸው ማለት አይደለም በፍፁም ትክክልም አይደለም፡፡ ቅዱስ ሲኖዶስ የወሰናቸውን ውሳኔዎች ህጋዊ በሆነ መንገድ የማስፈፀም ሀላፊነት ደግሞ የመንግስት ነው፡፡
መንግስት ደግሞ ይህንን ማድረግና የቅዱስ ሲኖዶስን ውሳኔ ማስፈፀም ብሎም እንዲህ አይነት ስህተቶች እንዳይደገሙ ማድረግም አለበት፡፡ የተገነጠሉ አባቶችም ደግሞ ለክህነትና ለመሰል ማዕረግ የደረሱ ሰዎች ናቸውና በእነሱ ምክንያት የኔ ናት የሚሏት ቤተክርስቲያን በልዩ ልዩ መልክ ስትፈርስ ማየት፣ ምዕመኖቿ ሲገደሉና ሲሰቃዩ ሲመለከቱ ምንድን ነው የሚሰማቸው? ምንስ አይነት ክህነት ነው የሚልም ነገር ያሳስበኛል፡፡
ከሁሉም በላይ ሀገር ትቀድማለት፣ ሐይማኖት ትቀድማለች እና ለሀገርና ለሀይማኖታቸው ሲሉ ለምን ይህን ነገር አልተውም? ይህን ያህል ፅንፍ የተወጣውስ ለምንድን ነው? ይሄ ሁሉ መከራ፣ ይሄ ሁሉ በደል፣ ይሄ ሁሉ ሀዘንና ማቅመልበት ድረስ አምንበታለሁ፣ ተክኜበታለሁ፣ ቦታ ይዤበታለሁ፣ ደሞዝ አገኝበታለሁ፣ ከምንም በላይ ደግሞ መንፈሳዊ ፀጋ አለኝ አስተምርበታለሁ የሚሉ ሰዎች ይሄ ሁሉ ሞት ይሄ ሁሉ ደም መፋሰስ ይሄ ሁሉ ከፊት የተደቀነ አስፈሪ ነገር ሁሉ አልታይ ያላቸው ለምንድን ነው የሚለው ጉዳይ ሁሉ መታየት አለበት፡፡ ይህም ለተወሰኑ ሰዎች ብቻ የሚተው አይደለም፡፡ እንደ ሀገር ሁሉም ሊያሳስበው ይገባል ምክንያቱም መጪው ጊዜ አሳሳቢ ስለሆነ፡፡
ዛሬ አንዱ አካል አሸናፊ ሆኖ ነገ አንዱ ተሸናፊ ሆኖ ዝም ሊል ይችል ይሆናል፤ ነገር ግን ያ ነገር ደግሞ ሌላ ነገር ቆስቁሶት ሊነሳ ይችላል ስለሆነም ይሄ ነገር ዘላቂ እልባት ሊበጅለት ይገባል፡፡
ከሁሉም በላይ ግን ህግና ሥርዓት መከበር አለበት፡፡ ህጋዊ የሆነውን አካል ህጋዊነቱን ማፅናት ብቻ ነው የመጀመሪያውና ትክክለኛው አማራጭ፡፡ እዚህ ላይ ቢሰራ ትክክል ነው ብዬ ነው የማስበው፡፡
እንዳልሽው ቤተ ክርስቲያን ለነገ (እሁድ) ምዕመኑ ታቦታቱን ከየደብሩ እያወጣ ወደየ ባህረ ጥምቀቱና መስቀል አደባባዩ እንዲወሰድ በዚያውም ያለውን ችግር ለአለም አቀፍ ማህበረሰብ እንዲያሰማ ትዕዛዝ ሰጥታለች፣ በተወገዘው አካል በኩል ያለውም ሰልፍ እንወጣለን የሚል መግለጫ አውጥቷል የጋራ ግብረሀይሉም ሁለት ሰልፍ አይሆንም ከልክያለሁ ብሏል፡፡ በዚህ ላይ ምን ይታይሃል ላልሽኝ እኔ የሚያየኝ ችግሩ እየከረረ ሁኔታው እየተወጠረ በቀላሉ ለሌላ ግጭትና ደም መፋሰስ አገራዊ ችግር ሊከሰት እንደሚችል ነው፡፡ ስለዚህ ለሚያልፍ ነገር ብዙ ዜጎቻችን ባያልፉብን እመርጣለሁ፡፡ ከሁሉም በላይ እነዚህ ተቋማት ትልልቅ ናቸው መንግስትም ቤተክርስቲያኒቱም ማለቴ ነው፡፡ መንግስት የፀጥታና የሀገር ደህንነት የመጠበቅ ሀላፊነት ያለበት ተቋም ነው፡፡ ቤተክርስቲያንም ደግሞ መንፈሳዊ የሆነውን ነገር በማስተማር ዜጎችን በሀይማኖታዊ ዕሴቶች የመጠበቅ ሀላፊነት አለባት ፣ ስለሆነም በሁለቱ መካከል መቀራረብ በእጅጉ ያስፈልጋል። መንፈሳዊና ሥጋዊ መቀራረብ ማለቴ ነው። አሁን ችግሩ በሁለቱም መካከል መራራቅ መፈጠሩ ነው፡፡ መሃል ላይ ደግሞ ትልልቅ የሀገር ሽማግሌ ካለን ይህን ውጥረት ለማርገብ መግባት አለባቸው ብየ አምናለሁ፡፡ እንደገና ደግሞ ሰልፎች በተመሳሳይ ጊዜ ባይጠሩ ጥሩ ነው፡፡ ሁልጊዜ እከሌ እኔ እወጣለሁ ሲል ሌላው ያንን ተከትሎ እኔም በዚያውቀን እወጣለሁ ሲባል ለሌላም ጊዜ ይሄ ጥሩ ልምድ አይደለምና መታረም አለበት፡፡
እንዲህ አይነት ነገር ሲፈጠር በሌላ ጊዜ መርጦ የሚወጣበትን መንገድ መፈለግ ነው የሚበጀው፡፡ ምክንያቱም አደባባይ መውጣት፣ መቃዎም ህገ መንግስታዊ መብት ነውና። ነገር ግን ወደ ግጭት ሊያመሩ የሚችሉ ሌላ ደም አፋሳሽ ነገሮችን የሚያሳዩ ነገሮች ካሉ መንግስት እንደመንግስት አቋም መውሰዱ የሚኮነን አይደለም፡፡ ምክንያቱም መጪው ነገር ለሀገርም ለህዝብም ጎጂ ነው ብሎ እስካመነ ድረስ የመንግስትንም ነገር መጠበቅ አለብን፡፡ መንግስት ይህንን ሲያደርግ እከሌ በዚህ ቀን አድርግ እከሌ ደግሞ ይሄኛውን ቀን ጠብቀህ አድርግ የሚል ጠበቅ ያለ ውሳኔ ማሳለፍ አለበት እንጂ ሙሉ ለሙሉ ከልክያለሁ ማለትም የመብት መንፈግ ጥያቄ ስለሚያመጣ ሊያስብበት ይገባል፡፡ እኔ በአጠቃላይ የማየው እልህ መያያዝና የነገሮችን ውጥረት ነው፡፡ ይሄ መርገብ አለበት ባይ ነኝ፡፡
ከቤተክርስቲያን ዶግማና ቀኖና ውጪ የተገነጠሉትን አካላት መንግስት ለምን አደብ ማስገዛት አልቻለም ብለሽ ላነሳሽው ጥያቄ መልስ መስጠት የሚችለው እራሱ መንግስት ብቻ ነው። ይህንን መገመት አልችልም፡፡ የተገነጠሉትን መንግስት እየደገፋቸው ነው ይባላል ያልሽውን ነገር በተመለከተ በሲኖዶስ የተወገዙት አካላት በመንግስት ድጋፍና ጥበቃ ነው ወደ የቤተ ክርስቲያናቱ እየገቡ ያሉትና ይሄ ፈፅሞ ትክክል አይደለም፡፡
መንግስት በዚህ ጉዳይ ላይ ኒውትራል ነው መሆን ያለበት፡፡ ከገለልተኝነትም ባሻገር ህጋዊ ወደ ሆነው ተቋም ማዘንበል አለበት የሚል እምነት አለኝ፡፡ ህጋዊነት ያለውን ተቋም እስካላከበርነው ድረስ ሁከቶች እየተባባሱ ለሌላ ደም መፍሰስና ግጭት ብሎም አላስፈላጊ ለሆነ ተግባር ይዳርጋሉና የመጀመሪያው ነገር ህጋዊ ለሆነው ተቋም ህጋዊነቱን ማፅናት ያስፈልጋል፡፡ በሌላ ወገን ጥያቄዎች አሉ ከተባለም ጥያቄ አቅራቢዎቹ ህጋዊ በሆነው በቤተ ከርስቲያኒቱ ዶግማና ቀኖና መሰረት እንዲሄዱ ማድረግ ወይም አሁን በተጀመረው በፍርድ ቤት ሂደት ጉዳዩ ስለተያዘ ፍርድ ቤት ውሳኔና ብይን እስኪሰጥ ድረስ ሁሉም ባለበት እንዲቆም መደረግ አለበት፡፡ ይህ ማለት ቤተ ክርስቲያኒቱም በያዘችው እነዛኞቹም ባሉበት እንዲፀኑ አድርጎ የፍርድ ቤቱን ውሳኔ መጠባበቁ የተሸለ ይመስለኛል፡፡ እኔ ይሄ ነው የሚታየኝ፡፡
ታዋቂ አትሌቶችና ባለሀብቶች ያሉበት የሽምግልና ቡድን ተቋቁሟል ከእነሱስ ምን ይጠበቃል?
ለተባለው ጉዳይ እንዲህ አይነት ነገሮች ሲከሰቱ የሽማግሌዎች ሚናም ትልቅ መሆን አለበት የሚል እምነት አለኝ፡፡ የእነሱ እንቅስቃሴ መጀመሩም ጥሩ ነው፡፡ ምክንያቱም የሽማግሌዎቹ እንቅስቃሴ ምንን መሰረት ያደረገ ነው ለሚለው ቅዱስ ሲኖዶሱ በሰጠው መግለጫ የቤተ ክርስቲያኒቱን ህግና ቀኖና ጠብቀው እነ አትሌት ኮ/ል ደራርቱ ቱሉ እየሰሩ መሆኑን ገልጿል፡፡ ይሄ ጥሩና ተስፋ ሰጪ ነው፡፡ በዚህ ነገር መሃል ያሉት እነሱ ናቸውና ይሄንን ውጥረት አርግበው ሀገር ወደ ሰላም የምትመጣበትን መንገድ ቢሰሩና ለሀገራቸውም ለህዝባቸውም ታሪካዊ አሻራ ቢያስቀምጡ ደስ ይለኛል፡፡ የማንም ሰው ደም መፍሰስ የለበትም፡፡ በዚህች አገር ላይ ግጭት ደም መፋሰስ፣ መፈናቀል ጦርነት ሁሉም ይበቃል፡፡ ምክንያቱም በሰሜኑ ጦርነት ብዙ ወገን አጥተን ፣ ብዙ ንብረት ወድሞ ህዝቡ ከቀየው ተፈናቅሎ ለረሀብና ለችጋር ተጋልጦ ያ ችግር ተቋጨ እፎይ አልን ስንል ነው ይሄ ውጥረት የመጣው፡፡ አሁን ላይ አዛውንት ህፃናት ጎልማሳው ሁሉም ጭንቀት ላይ ነው፣ ሀገር ከሀዘኗ ብዛት ማቅ የለበሰችበት ጊዜ ነውና ይህ እንዳይከሰት፣ ዳግም ደም እንዳይፈስ፣ አገር እንዳትፈርስ የሚጨነቁና የሚቆረቆሩ አካላት ያስፈልጋሉ፡፡ እነዚህ ሰዎች በርትተው ሌሎችንም ሰዎች ከጎናቸው ይዘው አልቅሰውም ሆነ ተንበርክከው ህንን ጉዳይ ቢያስቆሙ ምኞቴ ነው፡፡
ከሜይኒስትሪም ሚዲያውም ሆነ ከማህበራዊ ሚዲያው ምን ይጠበቃል ለተባለው ትልቁ ጉዳይ እዚህ ላይ ትኩረት ማድረግ ነው፡፡ ዞሮ ዞሮ የሚዲያው ሚና ትልቅ ነው ለበጎ ነገሩም ሆነ ለግጭት መባባስ፡፡ እናም እዚያ ላይ ትልቅ ሀላፊነት ያላቸው የሚዲያ አካላት ያስፈልጋሉ። ሀላፊነት ሲባል ሁሉ ነገር ተዘርግፎ አይነገርም አደጋ ሊያመጣ ይችላልና፡፡ በህዝቦች መካከል መቃቃርና ግጭት፣ ለሀገርና ለህዝብ የማይበጁ ነገሮች ላይ ጥንቃቄ መውሰድ ያስፈልጋል፡፡ ሀላፊነት ማለት ይሄ ነው፡፡
የአንድ ሚዲያና የባለሙያ ብቃት የሚለካው ለሀገርና ለህዝብ ደህንነትና ሰላም በሚወስደው ጥንቃቄ ነው፡፡ ነገር ግን አለመዘገብና ዝም ማለት ደግሞ በራሱ ሌላ ችግር ነው፡፡ በዚህ ወቅት ዝም ያሉ ትልልቅ ሚዲያዎች አሉ፡፡ ይሄ ማለት በሀገሪቱ ውስጥ ምንም አይነት ችግር እንዳልተፈጠረ ለማስመሰል እየሞከሩ መሆኑ ነው፡፡ ይሄ ጉዳይ በታሪክም የሚወቀሱበት እንዳይሆን የጋዜጠኝነት ሙያቸው በሚፈቅደው የሙያ ስነምግባር ላይ ተመስርተው ዘገባ የመስራት ግዴታ አለባቸው፡፡ ዝምታው ግን የሚያዋጣ አይደለም፡፡
በሌላ በኩል የማህበራዊ ትስስር ገፆች ላይ እያንዳንዱ ሰው በምግባሩም በምኑም የተማረ ነው ማለት አይደለም፡፡ ከወዲያኛው ከወዲህኛው ሆኖ ሀይማኖት የሚዘልፍ፣ በቃላት በምን የሚወራወረው ብዙ ነው፡፡ ህዝቡ ደግሞ ይህን እየተመለከተ እንዳይታበይ መደረግ አለበት፡፡ አንዳንዴ እኛ ኢትዮጵያዊያን ብዙ ሳናነብ ብዙ ሳናውቅ ገና ብዙ ሳንመራመር ቴክኖሎጂው እየቀደመን ነው ማህበራዊ ሚዲያ ውስጥ የገባነው፡፡ አንድ መፅሀፍ ያላነበበ ሁሉ ነው ሶሻል ሚዲያ ላይ እንደልቡ የሚፅፈውና የሚናገረው፡፡ ስለዚህ ትራንስፎርሜሽኑ (ሽግግሩ) በእውቀት ላይ የተመረኮዘ ባለመሆኑ እዛ ማህበራዊ ሚዲያ ላይ የምናየው መበጣበጥ ሀገሪቱ የፈጠረችው የብሄርተኝነት ፖለቲካና ሳናውቅ ሳንመራመር የገባንበት ስለሆነ ይሄም በራሱ ችግር ፈጣሪ ነውና አንዳንድ ጊዜ ይሄንንም የመቆጣጠር ሂደት ሀላፊነት በሚሰጣቸው አካላት ቢደረግ መልካም ነው፡፡
ስለሆነም የጥላቻ ንግግሮች፣ ህዝብን ከህዝብ ፣ሀይማኖትን ከሀይማኖት የሚያጋጩ ንግግሮችና ቪዲዮዎች የሚተላለፉባቸውን የማህበራዊ ሚዲያ ፕላትፎርሞች ወዲያውኑ እያጠፉ መቆጣጠር ያስፈልጋል የሚል እምነት አለኝ፡፡ ከሁሉም በላይ ግን ችግሩ ያለ ደም መፋሰስ የሚቋጭበትን መንገድ በጋራ መፈለግ አለብን ብዬ አምናለሁ፡፡
መዶሻ ያለው ሰው፤ እያንዳንዱ ችግር፣ ሚስማር ይመስለዋል
ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንድ እናት ቢምቢ ትንኝና ልጅ ቢንቢ ትንኝ ነበሩ፡፡ ልጅዬዋ ቢምቢ፤ በአገሩ እየተዘዋወረች ዙሪያ ገባው ውስጥ ነዋሪ - የሆኑትን እንስሳት፣ አዕዋፍና ነብሳት ልትጠይቃቸው ጎራ ልትል አሰበች፡፡ ይህንን ያወቀችው እናት፤
“መሄዱንስ ሂጂ፡፡ ዘመድ ማግኘትና መጠየቅ በጣም ጥሩ ነው፡፡ ነገር ግን ወዳጅና ጠላትሽን መለየት ይኖርብሻል፡፡ ጠላት የመሰለሽ ወዳጅ ሆኖ ይገኛል፡፡ ወዳጅ ያልሺው ደግሞ፣ ጠላት ሆኖ ተለውጦ ታገኚዋለሽ። ለማንኛውም ማጣራትን የመሰለ ነገር የለም፡፡”
ልጅዬዋ ቢምቢም፤
“እሺ እማማ፣ ቀስ ብዬ እያጣራሁ ለማየት እሞክራለሁ” ብላ አካባቢዋን ልታጠና መንገድ ቀጠለች፡፡
መጀመሪያ ቢራቢሮን አገኘች፡፡ “ቢራቢሮ እንደምነሽ?”
ቢራቢሮ፤
“ደህና ነኝ” አለች፡፡
“በአካባቢው ያሉ ነብሳት ተስማምተውሽ ይኖራሉ?”
“አዎን፡፡ ግን ክረምትም በጋም ሳልቸገር ለመኖር በመቻሌ፣ ወረተኛ ነሽ እያሉ ይወቅሱኛል”
“እነሱ ምን ፈልገው ነው?”
“ወይ የበጋ ሁኚ ወይ የክረምት ሁኚ ነው የሚሉኝ”
“ቆይ፤ ስለዚህ ጉዳይ እናቴን ጠይቄ ምን እንደምትል እነግርሻለሁ” ብላት ቢምቢ ሄደች፡፡
ቀጥላ ጦጣን አገኘቻት፡፡
“ጦጢት እንደምንድነሽ?”
“ደህና ነኝ”
“ከእንስሳቱ ጋር ስትኖሪ ምን ችግር ገጥሞሽ ያውቃል?”
“ምንም ችግር አልገጠመኝም፡፡ ግን ሁሉም በአንድነት በእኔ ላይ ፈርደው ብልጣ - ብልጥ ብትሆኚ ምን አለበት ታዲያ?”
“ታታልይኛለሽ፡፡ ታሞኚኛለሽ እያሉ ነው፡፡”
“የራሳቸው ጅልነት ነው ተያቸው” ብላ ቢምቢ መንገድ ትቀጥላለች፡፡
ብዙም ሳትሄድ አንበሳን አገኘችው፡፡
ቢምቢ፤
“ደህና ዋልክ አያ አንበሶ?”
“ደህና ነኝ፤ ቢምቢ”
“እንስሳት አብረውህ ሲኖሩ ምን ይሉሃል?”
“ጉልበተኛ ነህ፡፡ አምባገነን ነህ፤ ነው የሚሉኝ” አለ እየተጎማለለ፡፡
“አቅም ስላነሳቸው ነው እነሱ፡፡ ተዋቸው፡፡” ብላው መንገዷን ቀጠለች፡፡
በመጨረሻ የተሰበሰቡ ሰዎች አግኝታ፣ እነሱን አዳመጠችና፣ እየመሸ ስለመጣ ወደ እናቷ ተመለሰች፡፡
የሆነችውን ሁሉ ነገረቻት፡፡
“ሰዎችስ ምን አሉሽ?” አለቻት እናት ቢምቢ፡፡
ልጅየዋ ቢምቢም፤
“ይገርምሻል፤ ሰዎችማ ሲያጨበጭቡልኝ ዋሉ” አለቻት፡፡
እናት ቢምቢም፤
“ልጄ ሁለተኛ እንዳትሳሳቺ! እንደ፣ሰዎች ክፉ የለም፡፡ ያጨበጨቡልሽ የመሰለሽም በመዳፍና መዳፋቸው ጨፍልቀው ሊገድሉሽ ሲሞክሩ ነው፡፡ ስለዚህ ዳግመኛ እንዳትታለይላቸው!” አለችና መከረቻት፡- “ማጨብጨብ የሰው ልጆች ኃይለኛ መሳሪያ ነው፤ ተጠንቀቂ!”
***
አክራሪ መሆን መጥፎ የመሆኑን ያህል አድር - ባይና ወላዋይ መሆንም ያንኑ ያህል አስቸጋሪ ጠባይ ነው! ብልጣ ብልጥ መሆን የራሱ ችግር እንዳለው ሁሉ፣ ሞኛ - ሞኝ መሆንም ለማንም ብልጥ - ነኝ - ባይ የማታለል ተግባር ሰለባ ስለሚያደርግ፤ መጠንቀቅ ተገቢ ነው! አምባገነንነት ሁልጊዜ አያበላም፡፡ በእርግጥም የተገፉ፣ የተበደሉ፣ ፍትሕ - ያጡ፣ የተመረሩ ህዝቦች በተነሱ ጊዜ ማናቸውም ፈላጭ - ቆራጭ አገዛዝ አሳሩን ያያል፡፡ በዓለም ላይ ስንት አምባገነኖች ተሰባብረው እንደወደቁ ማሰላሰል ነው! የደገፉ መስለው ጧት ማታ ሲያጨበጭቡልን ጤነኛ መስለውን፤ “አሁን ነው ራስን ማሳየት” ብሎ ብቅ ማለት አደጋ አለው! ለመውረድ ብዙ ሽቅብ መውጣትም ክፉ ባህሪ ነው፡፡ ሁሉን፣ ሁልጊዜ አገኛለሁ ማለትም ግብዝነት ነው፡፡ እያጨበጨቡ ጎል ከሚከቱን ይሰውረን!
ዛሬ የትምህርት ጊዜ ነውና ትምህርታችንን ይግለጥልን፡፡ እንደ እስያ፤ “ዕውቀት እያለ የሚማር ጠፋብን” የሚል ትራጀዲ ውስጥ እንዳንገባ አምላክ ይጠብቀን!
“ምዕራቡ ዓለም ሲያስነጥስ ሌላው ክፍለ ዓለም ኒሞኒያ ይይዘዋል” የሚለውን በማሰብ፤ እንዳይምታታብን ራሳችንን እንቻል! የራስን የመሰለ ምንም ነገር የለም፡፡
የመጨረሻው እንግሊዛዊ የህንድ ገዢ ሎርድ ሉዊ፣ ለማህታማ ጋንዲ እንዲህ አለው “እኛ ከወጣን በህንድ አገር ቀውስ ይፈጠራል!”
ይሄኔ ማህታማ ጋንዲ፤
“አዎን ቀውስ ይፈጠራል - ቀውሱ ግን የራሳችን ነው!” አለና፤ ኩም አደረገው፡፡
“የራሳችንን ቀውስ ‘ራሳችን እንፈታዋለን!”
አንድ ፀሐፊ ካነበብናቸው በርካታ መጣጥፎች አንዱ ላይ፤ “የአዕምሯችን ማዕከል፣ እና ደጃፉም ሆነ ግንባሩ በጣም ሩቅ ለሩቅ ናቸው! ግን ተቀናጅተው ሥራ ይሰራሉ” ይላል፡፡ የእኛም ተግባር እንደዚሁ የተቀናጀ መሆን ይኖርበታል! ከተሳሰብንና ከተናበብን የስሌት ስህተት አንሰራም፡፡ የፍርድ ማዛባት ስህተት አንሰራም፡፡ የመረዳዳት ማቃት ስህተት አንሰራም፡፡
ዛሬ “ነፃ ኢኮኖሚ”፣ “ዲሞክራሲ”፣ “መልካም አስተዳደር” አስፈላጊ ነው ብለን ተፈጥመናል፡፡ ያም ሆኖ የፌደራሊዝምን ስርዓት፣ በተለይ የብሔር ብሔረሰብን ፌደራሊዝም ጨርሶ ካላደገው ካፒታሊዝማችን ጋር አብረን ለማስኬድ ብዙ እንቅፋት ሲፈጠርብን ይታያል፡፡ ኦሊቨር ጎልድስሚዝ የተባለው ገጣሚ፤ “ሀብት ይከማቻል ሰው ይበሰብሳል” ወደ ውስጥ እያየን፣ ራሳችንን እንፈትሽ፡፡ ነፃ ኢኮኖሚ ስንል በምን የዕድገት ደረጃ ላይ ላለ ኢኮኖሚ ነው ያጨነው? ብለን እንጠይቅ፡፡ ዲሞክራሲ ስንል በምን ደረጃ ላለ አገር ነው ያስቀደድነውና ስፌቱን የምንመርጠው? እንበል፡፡ ከፊውዶ ቡርዥዋ ሥርዓት ገና ሙሉ ለሙሉ ባልተላቀቀ ፖለቲካል-ኢኮኖሚ ላይ መልካም አስተዳደርን መጋለብ ቀርቶ መፈናጠጥስ ይቻላል ወይ? ብለን እንጠይቅ! ታላቅ ኃይል ያዘለውን ካፒታሊዝም፤ ከማህበረሰባዊ ኮንሰርቫቲዝም ጋር ማጋባትስ አማራጭ ይሆናል ወይ? (ምናልባት የቻይናን፣ የህንድን ስነልቦና ቢሰጠን) ብለን እንመርምር፡፡
የንድፈ-ሀሳብ መንገዳችን ከረኮንች ነው፡፡ እንኳንስ አስፋልት ኮብል-ስቶኑም ገና እያንገዳገደን ነው፡፡ ቆም ብሎ የሚያስብ አስተዋይ አዕምሮ አሁንም ያስፈልገናል! ከዕለታት አንድ ቀን የያዝነው ቲዎሪ ስህተት ሆኖ ቢሆንስ? ብለን መጠያየቅ አይከፋም፡፡ ለሁሉም ህመም አንድ መድኃኒት በመስጠት (ፓናሲያ እንዲሉ) ፈውስ እናገኛለን ብሎ ማሰብ ቀቢፀ- ተስፋ ነው፡፡ ማርክ ትዌይን፤ “መዶሻ ያለው ሰው፣ እያንዳንዱ ችግር ሚሥማር ይመስለዋል!” የሚለው በእኛ ዓይነቱ ላይ ሲሳለቅ ነው፡፡ ከዚህም ይሰውረን፡፡
በአሜሪካ የኢትዮጵያ ህዝብ ጉዳይ ኮሚቴ ለጠ/ሚ ዐቢይ ጥሪ አቀረበ
ኮሚቴው በኢትዮጵያውያን ላይ እየተፈጸመ ያለው ግፍና መከራ በአስቸኳይ ይቁም ሲል ጠይቋል።
- በሚሊዮን የሚቆጠር የኢትዮጵያ ህዝብ በመንግስት ላይ ያለው እምነት እየተሸረሸረ መሆኑን ኮሚቴው አመልክቷል። - ችግሩ በአፋጣኝ ካልተፈታ አገሪቷ በታሪኳ አጋጥሟት የማያውቅ ቀውስ ውስጥ ትገባለች ብሏል።
በአሜሪካ የኢትዮጵያውያ ጉዳይ ኮሚቴ (ኢፓክ) ከዓለም አብያተክርስቲያናት፣ ከኢትዮጵያ ሃይማኖት ካውንስል፣ ከኢትዮጵያ ሰብአዊ መብቶች ካውንስል፣ ከምስራቅና ኦረየንታል ኦርቶዶክስ አብያተ ክርስቲያናት እና ከበርካታ ታዋቂ የኢትዮጵያ ዲያስፖራ ማህበራትና ድርጅቶች እንዲሁም ግለሰቦች ጋር በመሆን በኢትዮጵያውያን ላይ እየተፈጸመ ያለውን ግፍና የሰብአዊ መብቶች ጥሰት በአስቸኳይ እንዲያስቆሙና አገሪቱን ከቁልቁለት ጉዞ እንዲመልሱ ለጠቅላይ ሚኒስትር ዶ/ር ዐቢይ አህመድ ጥሪ አቀረቡ።
በኢትዮጵያ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ለተፈጠረው ቀውስ መነሻ ምክንያቶቹ በህገ-ወጥ መንገድ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ያፈነገጡት ቡድኖች መሆናቸው በግልጽ እየታወቀ የኦሮሚያ ክልል የፀጥታ ሃይሎች የበርካታ ንፁሃንን ህይወት ሲቀጥፉ ቤተክርስቲያኒቱ ክብሯ ሲዋረድና ከባድ ውድመት ሲደርስባት መንግሰት ሁኔታውን በዝምታ መመልከቱ በእጅጉ አስገርሞናል ያለው ኮሚቴው ይህም መንግስት የዜጎቹን ደህንነት መጠበቅ ሃላፊነቱን በአግባቡ አለመወጣቱን አመላካች ነው ብለዋል።
በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን እና ዲያስፖራው በመንግስት ላይ ያለው እምነት በፍጥነት እየተሸረሸረ ሄዷል ያለው ኮሚቴው መንግስት ቀውሱን ለመፍታት ያለው ፍላጎት አነስተኛ መሆኑ ቀውሱን እራሱ አውቆ የፈጠረውና የሚደግፈው ነው ብሎ ለማመን የሚያስገድድ ሁኔታ ላይ እንዲደረስ ማድረጉን አመልክቷል።
በአገሪቱ የተፈጠረውን ቀውስ እና የህግ ጥሰት አስመልክቶ የኢትዮጵያ ሃይማኖቶች ካውንስል ለፌደራል መንግስትና ለተለያዩ ፖለቲካ ፓርቲዎችና ለመገናኛ ብዙሃን አካላት ያስተላፈውን መልዕክት በመደገፍ ተቋማቱ ሃላፊነት የሞላበትንና ህጋዊ አካሄድ በተከተለ መንገድ መፍትሄ ለመሻት የበኩላቸውን አስተዋፅኦ እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርቧል።
በኦሮሚያ ክልል የፀጥታ አካላት በቤተክርስቲኗ ላይ እየተፈጸመ ያለውን ግፍና በደል አጥብቆ እንደሚቃወም የገለጸው ኮሚቴው በቅዱስ ሲኖዶሱ የተመደቡ የሃይማኖት መሪዋችን ማሰር መደብደብና ማጉላላት፣ ወደሀገረ ስብከታቸው እንዳይገቡ መከልከል፣ ምዕመናንን በጭካኔ መግደል፣ ያፈነገጡትንና በቅዱስ ሲኖዶሱ የተወገዙትን ሊቃነጳጳሳት በመደገፍ ህግ በመጣስ የአብያተክርስቲናትን በር እየሰበሩ ማስገባት፣ የቤተክርስቲኒቱን ክብር ማጉደፍና ሀብትና ንብረቷን የማዘረፍ ወንጀል አጥብቀን እንቃወማለን ብሏል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ ለህገ-መንግስቱና ለሀገሪቱ ህግ የበላይ ጠባቂ መሆናቸውን በመገንዘብ ሃላፊነት ተሰምቷቸው አቅጣጫቸውን እንዲያስተካክሉና አገሪቱን ከከፋ መቅሰፍት እንዲያድኑ ጥሪ ያቀረበው ኮሚቴው ችግሩ በቶሎ ካልተፈታና እየተባባሰ ከሄደ ሀገሪቷ ከዚህ ቀደም በታሪኳ ካጋጠሟት ሁሉ የከፋ ቀውስ እንደሚያጋጥማትና መውጫ የማይገኝለት አዙሪት ውስጥ እንደምትገባ አበክሮ አሳስቧል።
ጠቅላይ ሚኒስትሩ አገሪቱ በድንገት ከገባችበት ቀውስ ውስጥ ለማዳን የሚያስችል ትክክለኛና ቆራጥ አመራር እንዲሰጡም ጥሪ አቅርበዋል።
በወቅታዊ ጉዳዮች ከመንግሥት ኮሙኒኬሽን የተሰጠ መግለጫ
በወቅታዊ ጉዳዮች ከመንግሥት ኮሙኒኬሽን የተሰጠ መግለጫ
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ አባቶች መካከል የተፈጠረው መለያየት በሰላማዊ መንገድ በውይይትና በውስጥ አሠራር እንዲፈታ መንግሥት አቋም መያዙ ይታወቃል። ለዚህምም የሀገር ሽማግሌዎችና የሚመለከታቸዉ ሁሉ ጥረት እያደረጉ ይገኛሉ፡፡
በሕገ መንግሥታችን መንግሥታዊ ሃይማኖትም ሆነ ሃይማኖታዊ መንግሥት ሊኖር እንደማይችል ተደንግጓል። በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን አባቶች መካከል የተፈጠረው ልዩነትም በቤተ ክርስቲያኒቱ ዉስጣዊ አሠራርና ከዚያም ካለፈ በፍትሐ ብሔር ዳኝነት የሚታይ ነው። አስፈጻሚው አካልም በፍርድ ቤት ሲወሰን ብቻ የማስፈጸም ኃላፊነቱን እንደሚወጣ ይታወቃል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ አጋጣሚዉን ለእኩይ የፖለቲካ ዓላማ ለመጠቀም የሚንቀሳቀሱ አካላት እየተገለጡ መሆኑን መንግሥት በልዩ ልዩ መንገዶች አረጋግጧል።
"የመሥዋዕትነት ሰልፍ አዘጋጅ " በሚል ከባለ ሀብቶች፣ ከፖለቲከኞች እና ከ"መንፈሳውያን የወጣት አደረጃጀቶች" የተውጣጣ ቡድን ከማዕከል እስከ ታች መዋቀሩን መንግሥት ደርሶበታል። አጋጣሚዉን በትጥቅ በተደገፈ ሁከት መንግሥትን የመነቅነቅ ፍላጎት ያለው ይህ ቡድን ወጣቶችን እየመለመለ ማሠማራት መጀመሩን፣ ለዓላማዉ በልዩ ልዩ መንገዶች ገንዘብ በመሰብሰብ እያሠራጨ መሆኑንና በሕገ ወጥ መንገድ ከታጠቁ ኃይሎች ጋርም ግንኙነት እየፈጠረ መሆኑን መንግሥት አረጋግጧል። ለዚሁ እኩይ ዓላማ አስቀድሞ አስቦበት ያደራጁት የሚዲያ ቡድን ሥራዉን መጀመሩም ተረጋግጧል፡፡
በዚህ የክትትል ሂደት ድምጽ ያላቸውና የሌላቸው መሣሪያዎች ይዘው ሁከት የሚፈጥሩ አካላት በሥምሪት ላይ እያሉ ተይዘዋል። የቤተ ክርስቲያንን ደወል ላልተገባ ዓላማ በመጠቀምሕዝብን ለብጥብጥ የሚዳርጉ ቡድኖችም ታይተዋል። በየአካባቢው ወጣቶችን ለግጭት የሚመለምሉና የሚያሠማሩ አካላት ተደርሶባቸዋል። የፖለቲካ ዓላማቸውን በሃይማኖት ሽፋን ለማስፈጸም የሚሞክሩ ኃይሎች በቁጥጥር ሥር ውለዋል። የተሰጣቸውን ኃላፊነት በመጠቀም የሰዎችንና የእምነት ተቋማትን መብቶች በመጣስ የመንግሥትን መልካም ስም ለማጥፋት የሚፈልጉ ሥውር እጆች እንዳሉም ታዉቋል።
በአጠቃላይ የተፈጠረውን ችግር ከመፍታት ይልቅ ችግሩን ለግልፅ የፖለቲካ ዓላማ ማሳኪያ አድርገዉ ወደ መጠቀም ተሸጋግሯል። ይህ ደግሞ የሀገርን ሰላም፣ ደኅንነት እና ልማት የሚጎዳ ነው። በመሆኑም በዚህ ተግባር ሆን ብለው የተሠማሩትን በቁጥጥር ሥር አውሎ ለሕግ የማቅረብ ተግባር ተጀምሯል። ይህም ተጠናክሮ ይቀጥላል። ከዚህ በኋላ መንግሥት ቀደም ሲል ሲገልፅ እንደ ነበረዉ ጉዳዩ ቀይ መሥመር ያለፈ ሆኖ በማግኘቱ፣ “የመሥዋዕትነት ሰልፍ” ብሎ ሰላማዊ ሰልፍ የሌለ በመሆኑ ሀገራዊ መረጋጋትን ለመፍጠርና የዜጎችን ደኅንነት ለማረጋገጥ ሲባል መንግሥት ጠንካራ የሕግ ማስከበር ሥራ ዉስጥ የሚገባ መሆኑን ከወዲሁ ያሳዉቃል። በዚህ አጋጣሚ ባለማወቅና በቅንነት የጥፋት ኃይሎችን የምትከተሉ ሁሉ መንገዱ ወደ ከፋ ጥፋት እንደሚወስዳችሁ ተረድታችሁ ከድርጊታችሁ እንድትቆጠቡ መንግሥት ያሳስባል።
መላዉ ህዝባችንም እንደቀደመዉ ሁሉ ከፀጥታ አካላት ጋር በመተባበር አካባቢዉንና ሰላሙን እንዲጠብቅ መንግስት ጥሪ ያቀርባል፡፡ ሕጋዊና ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓቱን በመናድ፣ በአቋራጭ በማንኛውም ዓይነት ጉልበትና ሁከት እኩይ የፖለቲካ ፍላጎትን መሳካት አይቻልም።
የካቲት 2 ቀን 2015 ዓ/ም
የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት
አዲስ አበባ
ለ ፫ ተከታታይ ቀናት በመላው ዓለም የታወጀው የነነዌ ፆም እና ምሕላ መጠናቀቅን አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ::
በስመ አብ፤ ወወልድ፤ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን!!
ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ቅዱስ ሲኖዶስ ከጥር ፳፱ እስከ የካቲት ፩ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ለ ፫ ተከታታይ ቀናት በመላው ዓለም የታወጀው የነነዌ ፆም እና ምሕላ መጠናቀቅን አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ::
++++++++++++++++++++++++++++++++++++++++
በትንቢተ ዮናስ በሰፊው እንደተጠቀሰው የነነዌ ሰዎች በእግዚአብሔር ፊት ላይ ስለአመጹ እና ግብራቸውም በእግዚአብሔር ፊት አጸያፊ በሆነ ጊዜ እግዚአብሔር ዮናስን “ተነስተህ ወደዚያች ወደ ታላቂቱ ከተማ ወደ ነነዌ ሂድ፤ ክፋታቸውም ወደ ፊቴ ወጥቷልና በእርስዋ ላይ ስበክ” በማለት አዘዘው፡፡ ትንቢተ ዮናስ ምዕ ፩ ቁጥር ፪ ዮናስም ድምፁን ከፍ አድርጎ ለነነዌ ሰዎች የእግዚአብሔርን ቃል ሲሰብክ “የነነዌ ሰዎች እግዚአብሔርን አመኑ፤ ለጾም አዋጅ ነገሩ፤ ከታላቁም ጀምሮ እስከ ታናሹ ድረስ ማቅ ለበሱ፡፡ ወሬውም ወደ ነነዌ ንጉሥ ደረሰ፤ እርሱም ከዙፋኑ ተነስቶ መጎናጸፊያውን አወለቀ ማቅም ለበሰ፤ በአመድም ላይ ተቀመጠ፡፡ አዋጅም አስነገረ፤ በነነዌ ውስጥ የንጉሡንና የመኳንንቱን ትእዛዝ አሳወጀ፤ እንዲህም አለ ሰዎችና እንስሶች፤ ላሞችና በጎች አንዳችን አይቅመሱ፣ አይሰማሩ፣ ውኃንም አይጠጡ፤ ሰዎችና እንስሶችም በማቅ ይከደኑ፣ ወደ እግዚአብሔርም በብርቱ ጩኸት ይጩኹ፤ ሰዎችም ሁሉ ከክፉ መንገዳቸውና በእጃቸው ካለው ግፍ ይመለሱ፡፡ እኛ እንዳንጠፋ እግዚአብሔር ተመልሶ ይጸጸት እንደሆነ ማን ያውቃል፡፡ እግዚአብሔርም ከክፉ መንገዳቸው እንደተመለሱ ሥራቸውንም አየ፤ እግዚአብሔርም ያደርግባቸው ዘንድ በተናገረው ክፉ ነገር ተጸጽቶ አላደረገውም” ትንቢተ ዮናስ ፫፡ ፭-፲
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም ይህን የነነዌ ሰዎች ፆም መነሻ በማድረግ የነነዌ ሰዎችን በምሕረቱ የጎበኘ አምላክ እኛንም በምሕረቱ ይቅር ይለን ዘንድ በየዓመቱ በአዋጅ በመፆም አምላካችንን ስንማጸንበት ኖረናል፡፡ የቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባዔ በጥር ፳፮ ቀን ፳፻፲፭ዓ.ም ባደረገው ስብሰባ በወሰነው መሠረት የካቲት ፩ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም የተጠናቀቀው የነነዌ ፆምና ምሕላ ልዩ በሆነ በመንፈሳዊ የንስሐ ጸሎት በሰላም ተጠናቋል፡፡
በምሕላውም ከብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ ጀምሮ ብፁዓን አበው ሊቃነ ጳጳሳት፤ ካህናት፤ ሊቃውንተ ቤተ ክርስቲያን፤ አገልጋዮች እና ምእመናን እንደነነዌ ሰዎች ጥቁር ለብሰን ጠዋትና ማታ በጸሎት ፤ በምሕላ፤ ቀን በቅዳሴ እንዲሁም በሰባቱ የጸሎት ጊዜያት ፈጣሪያችንን ስንለምን እና ስንማጸን የቆየንበት ምክንያት በቤተክርስቲያናችን ላይ የመጣው ፈተና እጅግ በጣም ከባድ በመሆኑ ነው፡፡
በዚህ የጾምና የንስሐ ወቅት ምእመናን ልጆቻችን የአባቶቻችሁን ጥሪ ሰምታችሁ፤ የሹመኞችን ማዋክብና እስር ሳትፈሩ ጥቁር ለብሳችሁ ጠዋትና ማታ በጾምና በምሕላ፣ ቀን በቅዳሴ በቤተክርስቲያን ቅጥር እየተገኛችሁ ለአምላካችን ያቀረባችሁትን ጸሎት እና ምሕላ እግዚአብሔር ሰምቶ ለችግራችን መፍትሄ፣ ለሀገራችን ሰላምን እንደሚሰጠን እምነታችን ጽኑ ነው፡፡ እናንተም ምእመናን የቤተ ክርስቲያንን ጥሪ ሰምታችሁ ለሃይማኖታችሁ፣ ለሀገራችሁ አንድነትና ሰላም ያላችሁን ጥልቅ ፍቅር ስለገለፃችሁም ያገኘነው መንፈሳዊ ብርታት ሳንገልፅላችሁ አናልፍም፡፡
በእግዚአብሔር ቸርነት፣ በእናታችን በቅድስት ድንግል ማርያም እና በቅዱሳን አማላጅነት፣ በመላእክት ተራዳኢነት በፍፁም ፍቅርና አንድነት የያዝነውን ጸሎት እና ምሕላ አጠናቀናል፡፡ ችግራችንን ለአምላካችን በለቅሶ እና በጩኸት ነግረናል፡፡ ከዚህ በኋላ መከራው ቢጸና፣ የመከራው ጊዜ እንኳን ቢረዝም እግዚአብሔር በመከራ ውስጥ ሊያፀናን እና ሊያበረታታን አስቦ በመሆኑ በፍፁም አንናወጽም፡፡ ከእነኚህ መከራዎች በኃላም ታሪክን ጽፈን ሃይማኖታችንን ጠብቀን እና አስጠብቀን በመንፈሳዊ ጽናት እና ተጋድሎ እንሻገራለን፡፡
ጥቃቱ የቤተ ክርስቲያንን እውነት በካዱና በእውነተኛዋ ቤተ ክርስቲያን መካከል ነው፡፡ ይህም የቅድስት ቤተ ክርስቲያንን ሃይማኖት፤ ቀኖና እና አስተዳደራዊ ሕግጋትን ጥሰው ሕገወጥ የጳጳሳት ሢመት በመደረጉ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ቅዱስ ሲኖዶስ በሕገ ቤተ ክርስቲያንና በቀኖና ቤተ ክርስቲያን መሠረት በጥር ፲፰ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ይህን ጥሰት የፈፀሙትን ግለሰቦች አውግዛ ከቤተ ክርስቲያን ኅብረት የለየቻቸው ቢሆንም ጉዳዩ ከግለሰቦቹ በላይ በመንግሥት ስልጣን ላይ ባሉና ጽንፈኛ በሆኑ ፖለቲከኞች እንዲሁም የሌላ እምነት ተከታዮች ጭምር የሚደገፍ በመሆኑ ቤተ ክርስቲያንን ከፍተኛ ዋጋ እያስከፈላት ይገኛል፡፡
እየተፈጸመ ያለው ድርጊት በሰማያዊ መንፈሳዊ ዓለምና በምድራዊ ሥጋዊ ዓለም መካከል ስለሆነ በዚህ አጭር ጊዜ ውስጥም የቤተ ክርስቲያን ክብርና ተቋማዊ ልዕልና ተደፍሯል፡፡ የቤተክርስቲያን ቅጥሮች መሣሪያ በያዙ አካላትና በመንግሥት የጸጥታ መዋቅር በኃይልና በጉልበት ተወሯል፡፡ ሊቃነ ጳጳሳት አባቶች ለብዙ ዓመታት ከኖሩበት አህጉረ ስብከት ያለአንዳች የሕግ መሠረት በጸጥታ መዋቅሮች ተባረዋል፡፡ በነጻነት የመንቀሳቀስ መብቶቻቸው ተገድቦም በግዞት ወደ አዲስ አበባ እንዲመለሱ ተደርገዋል፡፡ ወደ አህጉረ ስብከታቸውም ተመልሰው መግባት እንዳይችሉ እቀባ ተደርጎባቸዋል፡፡ ካህናት አባቶች እና ምእመናንም ያለአንዳች የሕግ መሠረት በየእስር ቤቱ ያለበቂ ምክንያት በሕገወጥ መንገድ ታጉረዋል፡፡ በጸጥታ ኃይል ከመጠን በላይ ከመደብደባቸው የተነሳ የሞት፣ የከባድ እና ቀላል አካል ጉዳት እንዲደርስባቸው ምክንያት ሆኗል፡፡ በአጠቃላይም በመንግሥት ኃይሎች ከፍተኛ የሰብዓዊ መብት ጥሰት ተፈፅሞባቸዋል፡፡
ቤተ ክርስቲያን ይህ ሁሉ በደል ቢፈጸምባትም ናዛዜ ሕዙናን የሆነው አምላካችን ለቤተ ክርስቲያናችን እና ለሀገራችን መፍትሔ እንዲያመጣልን፣ መንግሥትም ወደ ልቡ ተመልሶ ቤተክርስቲያንን እንዲያከብርና እንዲጠብቅ በሚል ሰላማዊ በሆነ ሁኔታ ይህን ጾም የነነዌ ሰዎች እንዳደረጉት ጥቁር ለብሰን በፍፁም ኃዘን ወደ አምላካችን እንድንጮህ ቅዱስ ሲኖዶስ ትእዛዝ ባስተላለፈበት ማግስት በሻሸመኔ ደብረ ስብሐት ቅዱስ ሚካኤል ቤተክርስቲያን ሕገወጡን ቡድን በኃይል ለማስገባት በመንግሥት የጸጥታ መዋቅሮች በተወሰደ አሰቃቂ እርምጃ እስከ አሁን በደረሰን መረጃ ቁጥራቸው ከ፴ በላይ የሚሆኑ ካህናትን እና አገልጋዮችን ጨምሮ የቤተ ክርስቲያናችን ልጆች ቅጥሯ አይደፈርም፣ ቤተክርስቲያን በተወገዙ ግለሰቦች አትረክስም በሚል ለሃይማኖታቸው ሰማእትነትን ተቀብለዋል፡፡ ቁጥራቸው ከፍተኛ የሆኑ ልጆቿም በደረሰባቸው ከባድ እና ቀላል የአካል ጉዳት ምክንያት በሕክምና ላይ ይገኛሉ፡፡ ከዚህ ሁሉ በደል በኋላም እስከ አሁን ድረስ የሞቱትን በአግባቡ መቅበርና የተጎዱትን በበቂ ሁኔታ ማሳከም ሳንችል ቀርተናል፡፡ እነዚህ ሰማዕታት በዚህ ኃጢያት በበዛበት ዘመን ለቤተክርስቲያን እስከሞት ድረስ በመታመን ለቤተ ክርስቲያንና ለምእመናን የጽናት ተምሳሌት በመሆናቸው ቤተክርስቲያን ስትዘክራቸው ትኖራለች፡፡ እንዲሁም ቤተ ክርስቲያን በልጆቿ ላይ እየደረሰ ባለው ሞት፤ እርዛት፤ እስራት እና መልከ ብዙ በሆነው መከራ ብታዝንም ለክርስትና እውነተኛነት ምስክሮች የሆኑ አዳዲስ ቅዱሳን ሰማእታትን በማግኘቷም እጅግ ደስ ትሰኛለች፡፡
ጾሙ ከተጀመረም በኋላ ሕዝቡ ወደ አምላኩ እንዳይጮህ እና እንዳይጸልይ ለማወክ የሕዝብ አስተዳዳሪ ሆነው የተሾሙ የመንግሥት ሹማምንት ሊያገለግሉት ኃላፊነት የተቀበሉበትን የሀገሪቱን ሕግ ጥሰው ምእመናን ልጆቻችን ጥቁር ለብሰው ወደ መሥሪያ ቤት እንዳይገቡና በመንግሥት ቢሮዎችም አገልግሎት እንዳያገኙ በተለይም በኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት እና አንዳንድ በፌዴራል እና በከተማ መስተዳድር ቢሮዎች ጥቁር የለበሱ እና በሀዘን ላይ ያሉ ልጆቻችንን በማሠር ሲያንገላቱ በዓይናቸው ያዩ ምስክሮች አረጋግጠውልናል፡፡ በዚህም ሹማምንት ስልጣናቸውን ቤተ ክርስቲያንን ለማጥቃት እየተጠቀሙበት መሆኑን እና ለቤተ ክርስቲያናችንም ሆነ ለሕዝበ ክርስቲያኑ ከፍተኛ ንቀት እና ጥላቻ ያላቸው መሆኑን ተረድተናል፡፡
ይህ በቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ እየደረሰ ያለው መከራና በደል በዚህ ዘመን በጉልህ የሚጠቀስ የቤተ ክርስቲያን የስደትና የመከራ ጊዜ ነው፡፡ ይህ የቤተ ክርስቲያን የስደትና የመከራ ጊዜ በቤተ ክርስቲያኒቱ የታሪክ መዝገብ እና በመጽሐፈ ስንክሳር ተመዝግቦ ይቀመጣል፡፡ ለትውልድም ይተላለፋል፡፡ ይህ የፈተና ዘመን ያልፋል፤ ነገር ግን በዚህ ታሪክ ውስጥ ከእውነት ጎን የቆማችሁ ስማችሁ በታሪክ እና በወርቅ ቀለም ሲፃፍ በቤተክርስቲያን ላይ መከራ ያበዛችሁ ክፉ ታሪካችሁን ዛሬ በእጃችሁ ጽፋችሁ አልፋችኋል፡፡
በዚህ አጋጣሚ ከኦሮሚያ ክልላዊ መንግሥት እና ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ውጭ ሌሎች የክልል ርዕሳን መስተዳድሮችና ከተሞች በተለይም የድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር፤ የደቡብ ብሔር ብሔረሰቦች እና ሕዝቦች ክልላዊ መንግሥት፤ የሲዳማ ክልላዊ መንግስት፣ የደቡብ ምዕራብ ኢትዮጵያ ክልላዊ መንግሥት፤ የሱማሌ ክልላዊ መንግሥት፤ የቤንሻንጉል ክልላዊ መንግሥት፣ የሐረሪ ክልላዊ መንግሥት፣ የአፋርና ጋምቤላ ሕዝቦች ክልላዊ መንግሥት፤ በጎፋ ዞን የሳውላ ከተማ እና ሌሎች ስማቸውን ያልጠቀስናቸው መንግሥታዊ ተቋማት የቤተ ክርስቲያናችንን ጥሪ በመከተል በአግባቡ ሕግና ሥርዓትን ለማስከበር የወሰዳችሁ ፍትሐዊ እና ሕጋዊ መፍትሔዎችን እናደንቃለን፣ በቤተ ክርስቲያንም ስም እናመሰግናለን፡፡ እንዲሁም ሀዘናችሁ ሀዘናችን ነው ብላችሁ ከጎናችን የተሰለፋችሁ አኃት አብያተ ክርስቲያናት፤ የሃይማኖት ተቋማት፣ ድርጅቶች እና ጉባኤያት፤ የእስልምና እምነት ተከታዮች፤ በእምነት የማትመስሉን ወንድሞቻችን እና እህቶቻችን ስላደረጋችሁልንና ስለምታደርጉልን እርዳታና ትብብር በቅድስት ቤተ ክርስቲያን ስም እናመሰግናለን፡፡
ጸሎተ ምሕላውን ስናውጅ መንግሥት ሕግ አክብሮ እንዲያስከብር፣ የቤተክርስቲያኒቱን ክብር እና ልዕልና እንዲያከብር፣ በሃይማኖታችን የውስጥ ጉዳይ ጣልቃ መግባቱን እንዲያቆምና ወደ ውስጡ ማየት እንዲችል ነበር:: ይህ ድርጊት እስከ አሁን ድረስ ግን መንግሥት ለዘመናት ሕጋዊ ተቋም እና የሀገር ባለውለታ የሆነችውን ቤተ ክርስቲያንን ከመስማት እና ችግሯን ከመቅረፍ ይልቅ የማዋከቡን ሥራ አጠናክሮ ቀጥሎበታል፡፡ በዚህም መንግሥት ችግሮችን ኃላፊነት ተሰምቶት እንዲፈታ ያደርገዋል የሚል እምነት ቢኖረንም አገዛዙ ግን ከጊዜ ወደ ጊዜ ልቡ መደንደኑን መመልከታችን በእጅጉ ልባችንን ሰብሮታል፡፡
በተለይም ቤተ ክርስቲያናችን ያወጀችው የ፫ ቀናት ጸሎትና ምህላ በአግባቡ እንኳን ሳይጠናቀቅ ከመንግሥት ደኅንነት የጋራ ግብረ-ኃይል ወቅታዊ የፀጥታ ጉዳይን አስመልክቶ በየካቲት ፩ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም የተሰጠው የሰልፍ ክልከላ መግለጫ መንግሥት አሁንም ችግሩን ለመፍታት ሳይሆን ቤተክርስቲያኒቱን ለአንዴና ለመጨረሻ ለማውደምና ቤተ ክርስቲያኒቱን ለማጥፋት የታወጀ አዋጅ መሆኑን በጽኑ እንድናምን አድርጎናል፡፡
በመግለጫውም፡-
፩ኛ. በእምነቱ አባቶች በተመሳሳይ መልኩ ሰልፍ ተጠርቷል በማለት መጥቀሱ የቤተክርስቲያን የመጨረሻው አካል የሆነው ቅዱስ ሲኖዶስ አውግዞ የለያቸውን አካላት የእምነቱ ተከታይ ማድረግ ብቻ ሳይሆን መብት ያላቸው ሕጋዊ አካላትና የቤተ ክርስቲያን አባቶች አድርጎ መጥራቱ አሁንም ላይ ማብራርያ ለመስጠት መሞከሩ የቤተ ክርስቲያኒቱን ክብር የሚነካ እና የሚያጠለሽ እንዲሁም ሕግና ሥርዓትን ከማስከበር ይልቅ ለሕገ ወጦች ጠበቃ ሆኖ የሚከራከረው መንግሥት መሆኑን ጭምር ለመረዳት ችለናል፡፡ በመሆኑም ቤተክርስቲያን በመንግሥት የደህንነት የጋራ ግብረ ኃይል ተሰጠ የተባለው መግለጫ የቤተ ክርስቲያናችንን ሕጋዊ መብት የገፈፈ እና ሕገ ወጥ መግለጫ በመሆኑ ቤተ ክርስቲያን አትቀበለውም፡፡
፪ኛ. ጉዳዩን የውጪ እና የውስጥ ጠላቶች የፈጠሩት ነው በማለት የተለመደውን ፖለቲካዊ ቅርፅ ለማስያዝ መሞከርም ቤተክርስቲንያንም ሆነ ሕዝብን መናቅ በመሆኑ የምንቀበለው አይሆንም፡፡ ቤተ ክርስቲያን በተለይ ላለፉት ፬ ዓመታት በሀሰተኛ ትርክት ልጆቿ በተለያዩ የሀገሪቱ ክፍል መከራን ሲቀበሉ ችግሮችን በሆደ ሰፊነት ችላ ያለፈችው የሀገር መሠረት እንዳይናጋ፣ ቅጥሯ እንዳይደፈር በማሰብና በሀገር አንድነት ላይ ባላት የማይናወጽ ጽኑ አቋም ምክንያት መሆኑን መንገር ለቀባሪው ማርዳት ነው፡፡ ጉዳዩ ግልፅ የሆነ የመንግሥት ጣልቃ ገብነት ሆኖ እያለና መፍትሄውም በመንግሥት እጅ የሚገኝ ብቻ መሆኑ እየታወቀ የፖለቲካ ቅርፅ ለማስያዝ መሞከር ችግሩን ያባብሰው እንደሆን እንጂ አይፈታውም፡፡
በሰሞኑም ቤተ ክርስቲያናችን በመዋቅር የምትመራ እና ልጆቿም ድምጽዋን አውቀው በአግባቡ የሚሰሟት መሆኑ እየታወቀ ሆነ ተብሎ ቃላት አጠቃቀሙ እንኳን ኦርቶዶክሳዊ ያልሆነ የሀሰት እና ጸብ አጫሪ የሆኑ መልእክቶችን በአደባባይ የተለጠፉ መሆናቸውን ሲታይ ምን ያህል ጉዳዩን ላልተገባ ፖለቲካዊ ጥቅም እንደተፈለገ ለመረዳት ችለናል፡፡ ይህ ተለጠፈ የተባለውም ሕገ ወጥ ጽሑፍ የቅድስት ቤተ ክርስቲያናችን ያልሆነና ፈጽሞም ሊሆን የማይችል መሆኑን ጭምር ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡
፫ኛ. የትኛውም ሰልፍ በየትኛውም የሀገሪቱ ክፍል ማድረግ አይቻልም በማለት የተደረገው ክልከላን በተመለከተም ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ ከዓለም አቀፍ የሰብዓዊ መብቶች ውስጥ መሠረታዊ መብት ሆኖ የተጠቀሰ እና በሕገ መንግሥቱም አንቀፅ ፴ ላይ በግልጽ የተደነገገ በመሆኑ መንግሥት ራሱ የሚመራበትን ሕገ መንግሥት ማክበርና ማስከበር ይኖርበታል፡፡ ቤተ ክርስቲያን ላይ ከላይ የተጠቀሰው ከፍተኛ መከራና በደል ምክንያት ከብዙ ሺህ ዓመታት በላይ ጸንታ የመጣችን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን በእኛ በልጆቿ ዘመን ስትፈርስ ዝም ብሎ መመልከት በጭራሽ የሚታሰብ አይሆንም፡፡
ይህን በደላችንን ለዓለም አቀፉ ማሕበረሰብ ለማሳወቅ እና መንግሥትም ከሚያደርገው ጣልቃ ገብነትና አፈና ወጥቶ ሕግ እንዲያከብር እና እንዲያስከብር የጠራነው የየካቲት ፭ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ሰላማዊ ሰልፍም መንግሥት ተገቢውን ጥበቃ በማድረግ እንድናከናውን መፍቀድ አሊያም የጠየቅናቸውን ሕገ መንግሥታዊ ጥያቄዎቻችንን በአግባቡ እና አንድ በአንድ መመለስ አማራጭ የሌለው መፍትሔ መሆኑን ደግመን ደጋግመን ለማሳሰብ እንወዳለን፡፡
በዚህ ሂደት ውስጥም የሚደርስብንን ሞት፣ መከራና ስደት እኛ አባቶች ከመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን ጋር ደስ ብሎን የምንቀበለው እንጂ ቤተ ክርስቲያናችን እና ሀገራችን ስትፈርስ ቆመን የምንመለከት፣ ዝም የሚል አንደበትና የሚሸከም ኀሊና የማይኖረን መሆኑን በአጽንዖት እናሳስባለን፡፡
መንግስት ከአጉል እልከኝነቱ ወጥቶ ከሕገ ወጦቹ ግለሰቦች ጋር በመተባበር በአደባባይ እየፈጸመ ያለውን የሕግ ጥሰት ዛሬን ጨምሮ በቀጣዮቹ ፪/ሁለት/ ቀናት ውስጥ እንዲያቆም እና ሕግ እና ሥርዓትን እንዲያስከብር፣ በኃይል የወረራቸውን መንበረ ጵጵስና እና አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ለቆ ለቤተክርስቲያኒቱ ሕጋዊ መዋቅር እንዲያስረክብ፣ ያለአግባብ ያሠራቸውን ካህናት እና ምእመናን ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንዲለቅ፣ ቤተ ክርስቲያኒቱ ላይ ለፈፀመው በደል በአደባባይ ይቅርታ እንዲጠይቅ፤ በካህናት እና ምእመናን ላይ ለደረሰው ሞት እና የአካል ጉዳት ተገቢውን ካሳ እንዲክስ እና የወደሙ ንብረቶቿን እንዲጠግን በጥብቅ እንጠይቃለን ፡፡
መንግሥት በዚሁ አካሄድ ሕግ እየጣሰ እና የቤተ ክርስቲያኒቱን ክብር እና ልእልና እያዋረደ የሚቀጥል ከሆነ ቤተ ክርስቲያን መንግሥት የጣሰውን ሕግ መሠረት በማድረግ መብቷን ለማስከበር እስከአሁን ድረስ ፍጹም ሰላማዊ የሆነውን እንቅስቃሴዋን አድማሱን በማስፋት በየካቲት ፭ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም ለማድረግ ያቀደችውንና ያሳወቀችውን ሀገር አቀፍ እና ዓለም አቀፍ ሰላማዊ ሰልፍ ያለማንም ከልካይነት በራሷ አደባባይ የምታከናውን መሆኑን እያሳወቅን መንግሥትም ድርሻው ሰልፉ ሰላማዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ መንግሥታዊ ኃላፊነቱን በአግባቡ መወጣት ብቻ መሆኑን እያሳሰብን ዛሬም ቢሆን መንግሥት ቆም ብሎ በማሰብ ከእኛ ከአባቶች ጋር ሃይማኖታዊ፣ ቀኖናዊና መንፈሳዊ የአስተዳደር ሥርዓታችንን ባልጣሰ መልኩ ለመነጋገር እና ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት ጥረት ካደረገ በውይይት ለመፍታት መንፈሳዊ በራችን ክፍት መሆኑንም እናሳውቃለን፡፡
ከዚህ ውጭ ግን በሁለቱ አባቶች መካከል የተፈጠረ ችግር እየተባለ የሚነገረው ፖለቲካዊ ጨዋታ የመንግሥት እንጂ በሀገሪቱ ሕጋዊ ሰውነት የሌላቸውና ከቤተ ክርስቲያን የተለዩ ግለሰቦች ጋር ማነጻጸር ሕገ መንግሥታዊም ሆነ ሞራላዊ የሕግ መሠረት የለውም፡፡
ስለዚህ ቤተ ክርስቲያናችን የጠራችውን ሰላማዊ እና ሕጋዊ የሆነ የመብት ጥያቄ የማፈን ሂደትን በጥብቅ እንቃወማለን፡፡
የተወደዳችሁ የመንፈስ ቅዱስ ልጆቻችን እስከአሁን ባደረጋችሁት ጽናትና ተጋድሎ ሃይማኖታችሁንና ቅድስት ቤተ ክርስቲያንችሁን እንዳላሳፈራችሁ ሁሉ አሁንም ከስሜታዊነት በወጣ ሁኔታ በከፍተኛ ጽናት እና ጥንካሬ የአባቶቻችሁን ድምጽ ብቻ እንድትሰሙ፣ ቤተ ክርስቲያንን በየአጥቢያችሁ ተደራጅታችሁ እንድትጠብቁ፤ ለአባቶቻችሁ መንፈሳዊ ጥሪ ፈጣን ምላሽ እንድትሰጡ፣ እየመጣው ላለ መከራና ስደት ለመንፈሳዊ ተጋድሎ እንድትዘጋጁና በፍፁም መንፈሳዊ ጨዋነት በአንድነት የመጣብንን ፈተና እንድትወጡ አደራ እያልን አባታዊ መልእክታችንን እያስተላለፍን ሰላማዊ ሰልፉን በተመለከተም በአጭር ጊዜ ውስጥ ዝርዝር መግለጫ የምንሰጥ መሆኑን እያሳውቅን በዚህ ጥቃት መስዋእትነት የከፈሉ እና ያረፉ ልጆቻችንን ነፍሳቸውን በአጸደ ገነት በክብር ያሳርፍልን እያልን ጸሎተ ፍትሐትም በየደረጃው የሚከናወን መሆኑን እያሳወቅን በተለያዬ ጊዜ ዛሬን ጨምሮ በወለቴ እና በሰበታ ከተሞች የደረሰውን የአካል ጉዳት እና ሞት እግዚአብሔር ምህረት እና መጽናናቱን ያድልልን፡፡ እግዚአብሔርም ገድላችሁን፣ ጽናታችሁንና ጸሎታችሁን ይቀበል፤ የቅዱሳን አምላክ ከሁላችን ጋር ይሁን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
“እግዚአብሔር ሀገራችንን ይባርክ”
የካቲት ፪ ቀን ፳፻፲፭ ዓ.ም.
አዲስ አበባ ኢትዮጵያ
ታዳጊው ሥራ ፈጣሪ
“--ቬስትልን ከገዛ በኋላ እስከ ሩቅ ምስራቅ ድረስ በመሄድ በወቅቱ የነበረውን የገበያ ፉክክር አጥንቷል፡፡ ሲመለስም በአንድ ዓመት ውስጥ የቴሌቪዥን ምርት አቅሙን ከ360 ሺ ወደ 600 ሺ ለማሳደግ ወሰነ - የውጭ ገበያውን አቅም ለማስፋፋት በማቀድ፡፡--”
አህመት ዞርሉ ከቱርክ ጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪ ዘርፍ ጋር የተዋወቀው ገና በ15 ዓመቱ ነበር፡፡ በትውልድ ቀዬው በአቅራቢያው የሚገኘው ት/ቤት በ20 ኪ.ሜ ርቀት ላይ እንደነበር የሚያስታውሰው ዞርሉ፤ በርቀቱ ሰበብ ትምህርት አቋርጦ ወደ ሙሉ ሰዓት ሥራ እንደገባ ይናገራል፡፡
በልጃቸው ሥራ ፈጣሪነት እምነት ያደረባቸው አባቱ፣ በወቅቱ የራሷ የጨርቃጨርቅ ኢንዱስትሪ ወዳልነበራት ትራብዞን የተሰኘች የቱርክ ግዛት ላኩት - ንግድ እንዲጀምር፡፡
ሱቅ ተከራይቼ በትውልድ አካባቢዬ የሚመረቱ ጨርቃጨርቆችን እሸጥ ነበር የሚለው ዞርሉ፤ እስከ 1961 ዓ.ም መፈንቅለ መንግስት ድረስ ጥሩ እንደነገደ ይናገራል፡፡
የፖለቲካው አለመረጋጋት የፈጠረው የንግድ መቀዛቀዝ በወቅቱ ከነበረው ሃይለኛ የገበያ ፉክክር ጋር ተዳምሮ ታዳጊው ነጋዴ ከቢዝነስ ሊያስወጣው ምንም አልቀረውም ነበር፡፡ ሆኖም በወቅቱ ጠቀም ያለ ትርፍ አግኝቶ ስለነበር በቢዝነሱ መቀጠል ቻለ፡፡
“አዲስ ሱቅ ኢስታንቡል ውስጥ በመክፈት አዳዲስ ምርቶችን መሸጥ ጀመርኩ፡፡ በርካታ አንሶላዎችን በመግዛት የተለያዩ ዲዛይኖች እያሳተምኩ በቱርክ የመጀመሪያውን ባለ ህትመት አንሶላ ለገበያ ማቅረብ ጀመርኩ። የአንሶላዎቹ ገበያ ሲደራልን ወደ ጠረጴዛ ልብሶች ሽያጭ ገባን፤ በሱም ቀናን፡፡ በ1973 ዓ.ም የራሳችንን የመጀመሪያ የሽመና ፋብሪካ ከፈትን፡፡”
ፋብሪካው ከፍተኛ ስኬት እንዳስመዘገበ የሚያስታውሰው ታዳጊው፤ በ1970ዎቹ ዓመታት በስኬት ለመቀጠል ወደ አዳዲስ ዘርፎች መግባት እንደሚያስፈልግ መገንዘቡን ይናገራል፡፡
“ማምረትና ችርቻሮ ሽያጭ በቂ እንዳልሆነ ተገነዘብኩ፤ አዳዲስ ብራንዶች ያስፈልጉን ነበር። እናም በ1975 ዓ.ም የራሳችንን “ታች” የተሰኘ የአገር ውስጥ የጨርቃ ጨርቅ ምርት ፈጠርኩ ሲል ያስረዳል፡፡ “ታች” በአገር ውስጥ ገበያ የመሪነቱን ሥፍራ ሲይዝና ትልቁ ጨርቃጨርቅ ላኪ ኩባንያ እየሆነ ሲመጣ የቱርክ የፖለቲካ ችግሮች እንደገና ቢዝነሱን አወኩት፡፡ በወቅቱ የበለጠ መስፋፋት እንፈልግ ነበር የሚለው ዞርሉ፤ ሆኖም በፖለቲካው ምስቅልቅልና ሁከት የተነሳ እንቅስቃሴያችንን ገታን ይላል፡፡
ከ1980 ዓ.ም መፈንቅለ መንግስት በኋላ የፖለቲካ አየሩ ተረጋግቶ ሰዎች እንደገና ኢንቨስት ማድረግ ጀመሩ፡፡ ይሄን ጊዜ ነው “ኮርቴክስ” የተባለ የመጋረጃ አምራች ኩባንያ የገዙት፡፡ ኩባንያውን በማስፋፋትም በስድስት ዓመት ውስጥ በወቅቱ በዓለም ላይ ከነበሩ ትላልቅ የጨርቃ ጨርቅ ፋብሪካዎች አንዱ እንዲሆን አስችለውታል፡፡
የገበያ ተንታኞች እንደምንከስር ይናገሩ ነበር፤ እኛ ግን ከፍተኛ የገበያ ፍላጎት እንዳለ እናውቅ ነበር ይላል- ዞርሉ፡፡
“በ1980 ዓ.ም አስተማማኝ የፖሊስተር ጨርቅ ያስፈልገን ነበር ፤ ስለዚህም የራሳችንን ፋብሪካ ተከልን፡፡ በሌሎች ላይ ከመተማመን የራሳችንን ማምረት ተመራጭ ነበር” ብሏል፡፡
በጥቂት ዓመታት ውስጥ ዞርሉ አቅሙን በአራት እጥፍ ማሳደግ የቻለ ሲሆን በመላው ዓለም ትልቁ የፖሊስተር አምራች ለመሆን በቅቷል፡፡ ሆኖም የቱርክ የአገር ውስጥ ገበያ እየተጣበበ ከመሄዱም በተጨማሪ የዓለም የጨርቃጨርቅ ገበያ ተለዋዋጭ ስለነበር ዞርሉ ቢዝነሱን በተለያዩ ዘርፎች ማስፋፋት ነበረበት፡፡
“በ1992 ዓ.ም በጨርቃጨርቅ ብቻ የምንፈልግበት ደረጃ ላይ እንደደረስን ተገነዘብን እናም አዲስ ዘርፍ ማፈላለግ ጀመርኩ” ይላል- የቱርኩ ኢንቨስተር፡፡
ከሁለት ዓመት በኋላ የኤሌክትሮኒክስ እቃዎች አምራች ኩባንያ የሆነው ቬስትል በኪሳራ ሊሸጥ መሆኑን የሰማው ዞርሉ፤ ኩባንያውን እንዴት እንደገዛው ሲናገር፡-
“ቬስትልን በደንብ ተመለከትኩትና የገንዘብ እጥረት እንዳለበት ተገነዘብኩ፡፡ ፋብሪካው ዘመናዊና በደንብ የተደራጀ ሲሆን ከአገር ውስጥ ብቃቱ በተጨማሪ በዓመት ከውጭ ገበያ 100 ሚ. ዶላር የማስገባት አቅም አለው፡፡ ከሁሉም በላይ ግን በክልሉ ቲቪ የሚያመርት ሌላ ፋብሪካ የለም” ብሏል፡፡
ቬስትልን ከገዛ በኋላ እስከ ሩቅ ምስራቅ ድረስ በመሄድ በወቅቱ የነበረውን የገበያ ፉክክር አጥንቷል፡፡ ሲመለስም በአንድ ዓመት ውስጥ የቴሌቪዥን ምርት አቅሙን ከ360 ሺ ወደ 600 ሺ ለማሳደግ ወሰነ - የውጭ ገበያውን አቅም ለማስፋፋት በማቀድ፡፡
ቬስትል 103 ለሚደርሱ የዓለም አገራት የቲቪ ምርቶችን መላክ ችሏል- በዓመት 17 ሚ. ቲቪዎች፤ 12 ሚ. ዲጂታል መሳሪያዎች (ዲቪዲ፣ ሳተላይት መቀበያ እና ተያያዥ መሳሪያዎች) ይልክ ነበር፡፡
ቢዝነሱ የዚህን ያህል ቢጧጧፍም ዞርሉ ስለስኬቱ ብዙም አያወራም፡፡ ሲጠየቅም ገበያውን የማንበብ ችሎታና ጠንክሮ የመስራት ውጤት ነው ሲል ይመልሳል፡፡
“ገበያውን ማንበብ ሁሉም ነገር ማለት ነው፡፡ በ60ዎቹና 70ዎቹ ቱርክ የገበያውን ፍላጎት የሚያሟላ በቂ የጨርቃጨርቅ ምርት አልነበራትም፡፡ ያንን ፍላጎት አሟላንና ከገበያው ጋር አደግን፡፡ በኤሌክትሮኒክሱም ተመሳሳይ ነው፡፡ የገበያው አዋቂዎች ትከስራላችሁ ብለውን ነበር፡፡ በጥናታችን መሰረት ብዙ ፍላጎት እንደነበር ተገነዘብን፡፡ አልተሳሳትንም አድገናል” ይላል፡፡
በተመሳሳይ እሳቤ ነው ዞርሉ ወደ ተለያዩ የቢዝነስ ዘርፎች የገባው - የገበያውን ፍላጎት በማሟላት አብሮ ለማደግ፡፡ በዚህም መሰረት በባንክ በፋይናንሽያል አገልግሎትና ኢነርጂ ዘርፎች ተሰማርቶ በስኬት እየገሰገሰ ይገኛል፡፡
በቅርብ ዓመታት 20 የቱርክ ትላልቅ ባንኮች ለኪሳራ መዳረጋቸው ይታወቃል፡፡ ዞርሉ በ1996 ዓ.ም ከመንግስት ይዞታ ላይ የገዛው ዴኒዝ ባንክ ከተፎካካሪዎቹ የሚፈለገውን ዋስትና ለደንበኞች በመስጠቱ ስኬታማ ሊሆን በቅቷል፡፡ በአገሪቱ ሰባተኛው ትልቁ የፋይናንስ አገልግሎት ሰጪ ቡድን የሆነው የዞርሉ ተቋም፤ 200 ቅርንጫፎች ያሉት ሲሆን ዓለም አቀፍ ደረጃውም ጥሩ እንደሆነ ይነገርለታል፡፡
ቱርክ ነዳጅ ባይኖራትም ወጣቶችና በደንብ የሰለጠኑ የሥራ አመራሮች አሉን የሚለው ዞርሉ፤ በኢነርጂ ክንፉም አስደናቂ ዕድገት እያስመዘገበ ነው - በአውሮፓ 98ኛው ፈጣን ዕድገት እያሳየ ያለ ኩባንያ ተብሎለታል፡፡
የዞርሉ የቢዝነስ ቡድን ወደ ኤሌክትሪክና ሃይል ማመንጨት ሥራ የገባው በቱርክ ትላልቅ ኢንዱስትሪዎች የራሳቸውን የኤሌክትሪክ ሃይል እንዲያመነጩ ዘርፉ ወደ ግል ይዞታ ከተቀየረ በኋላ ነው፡፡ ዞርሉ ግን ለራሱ ፋብሪካ ሃይል በማመንጨት ብቻ አልተወሰነም፡፡ በቱርክ የመጀመሪያው የኤሌክትሪከ ሃይል አምራች ለመሆን በቅቷል፡፡ ከታዳጊነት እስከ ጎልማሳነት በስኬት መዝለቅ ይሏል ይሄ ነው፡፡
(“ታላላቅ ህልሞች” ከሚለው መጽሐፍ የተወሰደ)
መንግሥትና የህብረተሰብ አስተዳደር
“--እንሆ ነፍስና ውሃ እንኳ ሳይቀሩ እንዲያገለግሏቸው አድርገው ድካማቸውን ከቀድሞው ያቃልላሉ፡፡ በነፍስየሚዘወር ወፍጮና በውሃ የሚዘወር የዕንጨት መቁረጫ መጋዝ ያበጃሉ፡፡--”
የሚበልጥ ብዙ ነገር ይገኛል፡፡ ነገር ግን እንደዚህ የሆነበት ምክንያት ምን እንደ ሆነ በዘመናት ብዛት ተረስቶ ኑሮ ሊቃውንት እየመረመሩ፣ የመሬቱ መልክ ልዩ ልዩ የሆነበትን የያንዳንዱ አገር አየር ለብቻው የሆነበቱ ሁሉ በምን ምክንያት እንደ ሆነ ራሳቸው መርምረው ተረድተው ደግሞ ለዓለም ሕዝቦች ለማስረዳት ይጣጣራሉ፡፡
እውነትም የኤውሮፓ ሊቃውንት ስለዚሁም ነገር ብዙ ደክመዋል፡፡ ድካማቸው ግን ከንቱ አልሆነም፡፡ ታሪክ ሳይፃፍ የነበሩ ሰዎችና ሕዝቦች ምንስ ስማቸውና ሞያቸው በርግጥ ባይታወቅ ኑሯቸውም እንዴት እንደነበረ በዘመናቸውም የሆነው የአየርና የመሬት መለዋወጥ በምርምር ተለይቶ ታውቋል፡፡
የኤሮፓም ሊቃውንት በሚነግሩን መንገድ ከሄድን ዘንድ ሰው የዛሬውን ዕውቀትና የኑሮ ምቹነት ያገኘ ካንዱ ደረጃ ወዳንዱ ደረጃ እየወጣ ነው እንጂ ባንድ ጊዜ አይደለም፡፡
የሰውም አስተዳደር ከጥንት ከመሰረት እንዴት እንደ ነበረና እንዴትስ እየተለዋወጠ እንደ ሄደ በፍፁም እንድንረዳው ትልቁ ያሜሪካ ሊቅ ካሬ እንደ ፃፈው፤ ለምሳሌ አንድ ሰው ከነሚስቱ ለብቻው ተለይቶ ሌላ አጋዥ ሳይኖረው መሣሪያም አልባ ሆኖ ወዳንድ የባህር ደሴት መሰደዱን እናስብ፡፡
በመካከልም መሰናክል ነገር ካላገኘው የሱና የልጆቹ፤ የልጅ ልጆቹም ኑሮ በዘመናት ብዛት እንዴት እየተለዋወጡና እየሰፋም እንዲሄድ በተራ አስተውለን እናስብ፡፡
ይህ የምናስበው ሰው ከነሚስቱ ባንድ ሰፊ አገር ውስጥ ብቻውን ሲሆን መሣሪያም ሳይኖረው ትዳሩ በመጀመሪያ እንዴት ያለ ኑሮ ኑሮት ይሆን። መቼም ደሴቱ ሰፊ ነውና እሱ ግን ሁለት ራሱን ብቻ ነውና የሄደ የሚመቸውን አይቶ ለትዳሩ የሚሆነውን ቦታና መሬት ሳይመርጥ አይቀርም፡፡ ፍሬያማውን መሬት እንዳያቀና ግን ትልልቅ ዛፎችና ቁጥቋጦ መልተውበታል፡፡ ወይም ደግሞ ትልልቅ ረግረግ ይሆንበታል፡፡ ዛፎቹንም ለመቁረጥ ቡቃዮቹንም ለመንቀል ረግረጎቹንም ለማድረቅ ጉልበትና መሣሪያ ያጣል፡፡
ደግሞም የደኑና የረግረጉ አየር ከነከታቴውም ለጤናው የማይመቸው ይሆናል፡፡ በእጁም የሚነቅለው ቁጥቋጦ ወዲያው እንደ ነቀለው ተመልሶ እንዳይበቅልበት ያስፈራዋል፡፡ ስለዚህም በተራራው አግድመት ያለው ገላጣ መሬት ዛፍና ብዙ ቁጥቋጦ የለበትም፡፡ ውሃም አይቆምበትም፤ ረግረግም አይሆንምና፤ ከዚያው ላይ የሚበቃውን መሬት አይቶ መሬቱንም ባንድ በትር ምሶ ፍሬ ይተክልበታል፡፡ ይህም የተከለው ፍሬ በመከር ጊዜ ዕጥፍ ሆኖ ይገባለታል፡፡
ይህንንም ፍሬ በሁለት ደንጊያ መካከል አድርጎ ይፈጨዋል፡፡ ባንድ ደንጊያም ላይ እንደ ቂጣ ዓይነት አድርጎ ጋግሮ ይበላዋል፡፡ የተከለው ፍሬ እስኪበቅልለት ድረስ ግን ሥራ ፈቶ ዝም ብሎ አይቀመጥም ይሆናል፡፡ ዐውቆ የበቀለውን የደን ፍሬ ለመሰብሰብ አውሬውንም ለመያዝ ወይም ለመግደል ወዲያና ወዲህ ሲመላለስ ይቆያል፡፡ እንዲህና እንዲህም ሲል ለራሱና ለሚስቱ የሚሆን የዕለት ምግብ ያገኛል። ይህም ሲሆንለት ኑሮው እየተሳለ ይሄዳል፡፡ የሚመቸውንም አንድ ደንጊያ አይቶ መጥረቢያ እንዲሆንለት በሌላ ደንጊያ ይስለዋል፡፡ በብዙ ድካምም ዛፎቹን ይጥልበታል፡፡ ነገር ግን በጊዜ ብዛት የመዳብን ዐፈር ያገኛል፤ አቀላለጡንም እሱው ራሱ አስቦ ይማራል፡፡ በዚሁም ባዲስ ዕውቀቱ በጥቂት ድካም የተሳለ መጥረጊያ ለማበጀት ይችላል፤ ከመዳብም አንደኛ መናኛ ዶማ ያበጃል፡፡
በዶማውም መሬቱን አጥብቆ ወደ ውስጥ ዘለቃ ይቆፍረዋል፤ መሬቱም ደህና ሁኖ ስለ ተቆፈረ የሚዘራውንም ፍሬ ፀሐይ ያደርቀዋል፤ ጎርፍም ይወስደዋል ተብሎ እንደ ዱሮው አያስፈራም፡፡
መከሩም የተዘራውን ሦስት እጅ አኽሎ ሳይገባ አይቀርም፡፡ ከዚያም ቀጥሎ ዚን ያለበትን ዐፈር ያገኛል፡፡ ዚኑንና መዳቡንም ባንድነት አጋጥሞ ቢያቀልጠው ብሮንስ ይሆንለታል። ከብሮንስም ከዱሮ የበለጠ መሣሪያ ያበጃል። ሥራውም በዚሁ ምክንያት ከዱሮው ይልቅ በጣም ይቀልለታል፡፡
ያንን በፊት በማይገባ መሣሪያ ሲቆፍረው የነበረውንም መሬት ከእንግዲህ ወዲህ አጥብቆ ሊቆፍረው ይችላል፡፡ ከፍሬያማውም መሬት ቡቃያ ከነበረበቱ ጥቂቱን በዚሁ ባዲሱ መሣሪያ ያቀናዋል፤ መሬቱንም በደህና ይቆፍረዋል። ቡቃያው እንደ ገና በቅሎ የዘራውን ፍሬ እንዳይውጥበት አያስፈራውም፤ በዚሁ መካከል መቼም ልጆች ይወልዳል፤ ልጆቹም ለሥራ ይደርሳሉ፡፡ የሱ ጉልበትና የልጆቹ ጉልበት ይተባበራል፡፡ ከመተባበራቸውም የተነሣ የበለጠ ሀይል ያገኛሉ፡፡ የሚያስፈልጋቸውንም ነገር ሁሉ፡፡ መሬት በሆዷ እንደ ያዘች ተረድተውታል፡፡ ለመሣሪያም የሚሆናቸውን ነገር ከመዳብና ከዚን የበለጠ ሌላ ነገር እንዲያገኙ ይመረምራሉ፡፡ እንሆም የብረት ዐፈር ያገኛሉ፤ ያቀልጡታልም፡፡ እንዲሁም ሆኖ ከሚወጣው ብረት ምንም እንኳ ጨርሶ ለጊዜው ባያምር እውነተኛ ብረት ያገኛሉ፡፡ ወዲያው ዶማና መጥረጊያ ያበጁና ሥራቸውን ከዱሮ ይልቅ በበለጠ ይሰሩበታል፡፡
እንግዲህም ይህ መጀመሪያ ስደተኛው ሰውዬ ከልጆቹ ጋር በተራራው አግድመት የነበረውን ትልቁን ጥድ ጥሎ እርሻውን ያሰፋል። በብረቱም ዶማ መሬቱን በጣም እስከ ውስጡ ድረስ ዘልቆ ይቆፍረዋል፡፡ የላይኛውንም ዐፈር ከታችኛው ዐፈር ጋር ያደባልቀዋል፡፡
ልጆቹም ልጆች ይወልዳሉ፤ የልጅ ልጆቹም ያድጉለታል፤ ከዚያም በኋላ ከልጆቹና ከልጅ ልጆቹ ጋር ሁኖ ብቻውን ሳለ ለመሥራት ያልቻለውን አሁን ግን ቤተ ሰቦቹን ይዞ ብዙ ሥራ ለመሥራት ይችላል፡፡
ቤተ ሰቡም እየበዛ ሲሄድ እያንዳንዱ ሰው የሚያገኘው ምግብ እየበዛ የያንዳንዱም ድካም እያነሰ ይሄዳል፡፡ ቤተ ሰቦቹም ከበዙ ዘንድ ሥራውን ይከፋፍሉታል፡፡ እኩሌቶቹ የእርሻን ሥራ ይሠራሉ፤ እኩሌቶቹም ደግሞ ብረትና መዳብ ዚንም የሚገኝበትን ዐፈር እያቀለጡ ልዩ ልዩ የሆነ ደህና ደህና መሣሪያ ይሰራሉ፡፡ እኩሌቶቹ ግን ደግሞ የተበላሹትን መሣሪያዎች እያሻሻሉ ያድሳሉ፡፡
ለእንክርዳድ መንቀያ የሚሆናቸውንም ራሳቸው መርምረው አንድ አዲስ ዐይነት ዶማ ይሰራሉ፡፡ ይህንንም አዲስ መሣሪያ ይዘው ትንንሾቹም ልጆች ቢሆኑ እንክርዳዱን በመንቀላቸው ማለፊያ አድርገው ሥራውን ይረዳሉ፡፡ ሰዎቹ እንደዚህም በመተባበራቸው ትዳራቸው እየሰፋ፤ እነሱም እየበረቱና እየተጠቀሙ ይሄዳሉ፡፡
እንግዲህም በሥራና ባሳብ እየተረዳዱ የጠነከረ መሣሪያ አብጅተዋልና ከተራራው አግድመት በታች ወዳለው ቁጥቋጦ ወደ በዛበት መሬት እርሻቸውን ለማስፋት ይወርዳሉ፡፡ ወርደውም ቁጥቋጦውን በእሳት ያቃጥሉታል። ከዚያም በኋላ ትልልቆቹን ዛፎች በመጥረቢያ ይጥላሉ፡፡ በጊዜም ብዛት ራሳቸው መርምረው በሬውን ለማሰራት ያስባሉ። በሬውም በጉልበቱ እንዲረዳቸው የሚረዳበትን መሣሪያ አስበው ያወጣሉ፤ ይህነንም መሣሪያ በጠረፍ አጋጥመው ከበሬው አንገት በእንጨትና በጠፍር ያስሩታል፤ ከዚያም በኋላ ያርሱበታል፡፡ እንሆ እንደዚህ ያለው መሣሪያ ባልሰለጠኑት ሕዝቦች እስከ ዛሬ ድረስ ይኖራል፡፡
እንሆም ዱሮ በዶማ ዐስር ሰዎች ሲቆፍሩ ይውሉበት የነበረውን የእርሻ መሬት ኋላ ግን አንድ ሰው በሁለት በሬ አርሶት ይውል ጀመር። እንደዚህም ሲሆን እርሻቸው ከድሮው በጣም የተሻለ እኽል የሰፋም ይሆናል። የሰዎቹም ቁጥር እየበዛ ይሄዳል፡፡ በመሣሪያና በእኽል በልብስም ሀብታቸው ይበዛል፡፡ የሚኖሩበትም ቤት በጊዜ ብዛት የተሻለ ይሆናል፡፡
ያ በደሴት የገባው የመጀመሪያው ሰው ከነሚስቱ እንደ አውሬ በጉድጓድ ወይም በዋሻ ውስጥ ይኖር ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ ግን ዐውቆ የወደቀውን ዕንጨት ሰባስቦ አንዲት ጎጆ ሰራ። የመጀመሪያው ቤት መቼም መስኮትና የጢስ መውጫ አልነበረውምና ሰውዬው በብርድ እንዳልሞት ሲል በጢስ ውስጥ ታፍኖ ይኖር ነበር፡፡
ነፍሱም ሲበረታበት መዝጊያውንም ለመዝጋት የግድ እየሆነበት በጢሱ ውስጥ በጨለማ ሥራ እየፈታ ሲቀመጥ ነበር፡፡ ይህ ኑሮ ግን ለጤናው እጅግ የሚስማማው አልነበረም። ልጆቹና የልጅ ልጆቹ ካደጉና ለሥራ ከደረሱ በኋላ ከእነሱ ጋር በህብረት ተጋግዞ ደህና መሳሪያ አውጥቶ ሃይሉ ሲሰፋለት አይቶ፣ ጥዱንና ዝግባውን ቆርጦ ፈልጦ የተሻለ ቤት ሰራ፡፡ የሚኖርበትም ቤት እየተሻለ ስለ ሄደ ቤተ ሰቦቹ እየተመቻቸው ይበዛሉ፡፡
ከመብዛታቸውም የተነሳ ባህሪያቸውና ሞያቸውም ይለያያል። እኩሌቶቹ በእርሻ የሰለጠኑ ይሆናሉ። ያውሬንና የከብትን ቆዳ እየፋቁ ልብስ ያበጃሉ። እኩሌቶቹም መሳሪያውን በማበጀት ይሰለጥናሉ። ከዚህም ስራ መከፋፈል የተነሳ የያንዳንዱ ሰው ድካም እየተቃለለ ይሄዳል፡፡ በዚህ ሥራ ብዛት ገንዘብ እየተረፋቸው ስለ ሄደ ለክፉ ቀን እንዲሆነን እያሉ ትርፉን ያከማቻሉ፡፡
እርሻቸውም ብዙ ፍሬ ከማይሰጠው አግድመት ወደ ፍሬያማው ሜዳና የወንዝ ዳር እየሰፋ ሲሄድ ሰዎቹም ደኑን መንጥረው ረግረጉንም አድርቀው እየዘሩ ከድሮው በጣም የተሻለ መከር ያገኛሉ፡፡ ለከብትም መሰማሪያ የሚሆን አይተው ደህና ግጦሽ ይለያሉ፡፡
እንሆም በጥቂት ድካም ከድሮው የበለጠ ስጋና ወተት፤ ቅቤም ቆዳም ለማግኘት ይሆንላቸዋል፡፡
በበታቹ ያለው ሜዳ የተሻለ የእርሻ መሬት ስለ ተገኘበት ያ ድሮ ሲታረስ የነበረው የተራራው አግድመት የእርሻ መሬት ለፍየልና ለበግ መሰማሪያ እንዲሆን ይለቀቅና ወደ አዲሱ የእርሻ መሬት ይወረዳል፡፡
ይህም ሁሉ ነገር እስኪሆን ድረስ ብዙ ትውልዶች አልፈዋል፡፡
አዲሶቹ ትውልዶች አባቶቻቸውና አያቶቻቸው ባከማቹት ሀብትና ዕውቀት ተጠቅመው ነበርና ለወደፊት የበለጠ ጥቅም እንዲያገኙ ራሳቸው መርምረው ለማግኘት በመጣጣር ይሆንላቸዋል፡፡
እንሆ ነፍስና ውሃ እንኳ ሳይቀሩ እንዲያገለግሏቸው አድርገው ድካማቸውን ከቀድሞው ያቃልላሉ፡፡ በነፍስ የሚዘወር ወፍጮና በውሃ የሚዘወር የዕንጨት መቁረጫ መጋዝ ያበጃሉ፡፡ የዕንጨት ከሰልም የሚነድበትን የብረት ማቅለጫ ሸክላ ያበጃሉ፡፡
እንሆም ድሮ ብዙ ቀን የሚደከምበትን ጥቅም ባንድ ቀን ለማግኘት ይቻላቸዋል፡፡ ሕዝቡም በዝቶ የደሴቱን ተራራና ሜዳ ሁሉ እያቀና ይመላዋል፡፡
የሰዎቹም ቁጥር ሲበዛ ሥራቸውና ሞያቸው ዐይነቱ በጣም የተለያየ ይሆናል፤ አራሾች ሰፊዎች፤ ቤት ሰሪዎች፤ ብረት ሰሪዎች፤ የተባሉ ሞያ ሞያቸውን ይይዛሉ። ረግረጎች በሰው ብልኃት ይደርቃሉ፡፡
“ኦርቶዶክስን ማፍረስ ሀገርን ማፍረስ በመሆኑ መጠንቀቅ ያስፈልጋል” በኢትዮጵያ የሩሲያ አምባሳደር
በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የተፈጠረው ድርጊት እንዳስጨነቃቸውና በቤተ ክርስቲያኒቱ የተፈጠረው ችግር በቤተ ክርስቲያኗ የውስጥ ሕግና ስርዓት ብቻ ሊፈታ እንደሚገባ በኢትዮጵያ የሩሲያ አምባሳደር ኢቭጌኒ ተርኪሂን ገለጹ::
አምባሳደሩ ከማኅበረ ቅዱሳን ቴሌቪዥን ጋር ባደረጉት ቆይታ እንደተናገሩት፤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ለኢትዮጵያ ሕዝብ ታሪክ ባህልና አንድነት መሠረት የሆነችና የሀገሪቱን ታሪክ ሰንዳ ያቆየች ባለውለታ ናት ብለዋል።
ሩሲያ እና ኢትዮጵያ የረጅም ዓመታት የቆየ ግንኙነትና ትስስር እንዳላቸው ያስታወሱት አምባሳደሩ፤ ለዚህም ጥንካሬ መንፈሳዊ ትስስሩ ከፍተኛ ሚና እንዳለው ተናግረዋል።
ከአየር ንብረት ለውጥ ጋር ተያይዞ በአሁኑ ሰዓት የሀገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሳይቀር እውቅና ያገኙበት እንቅስቃሴ ቢኖርም፣ በኢትዮጵያ ታሪክ ግን በቤተ ክርስቲያኗ ለዘመናት የተሠራው የአካባቢ ጥበቃ ሥራ ቤተ ክርስቲያኗን “የአረንጓዴ አሻራ እምብርት” ያደርጋታል ብለዋል።
በአሁኑ ሰዓት ቤተ ክርስቲያኒቱ ያለችበት ሁኔታ እጅግ እንዳሳዘናቸውና እንደ ኦርቶዶክስ ሃይማኖት ተከታይነታቸውም ጉዳዩ በጣም እንዳስጨንቃቸው የተናገሩት አምባሳደር ኢቭጌኒ ተርኪሂን፤ ይህቺን ቤተ ክርስቲያን ማፍረስ ማለት ሀገር ማፍረስ ማለት በመሆኑ ከፍተኛ ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል ብለዋል።
በሁለቱ አብያተ ክርስቲያናት ታሪክ በርካታ የፈተና ጊዜያት አልፈዋል ያሉት አምባሳደር ኢቭጌኒ ተርኪሂን፤ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያንም ይህንን ከባድ ጊዜ እንደምታልፈው እምነታቸው የፀና መሆኑን ተናግረዋል።
አምባሳደሩ በቆይታቸውም ጥያቄ ያነሳው አካልም “አጥቂ” እርምጃ ከመውሰድና ከመገንጠል ይልቅ ቅሬታውን በቀጥታ ለአባቶችና ለምእመናን ማሳወቅና በቤተ ክርስቲያኗ ሕግና ስርአት መሄድ ይገባው ነበር ብለዋል። በቀጣይም ጉዳዩ በራሷ በቤተ ክርስቲያኗ ሕግ መሰረት በውይይት እንዲፈታ ፍላጎታቸው መሆኑን ተናግረዋል።
ከዚህ ቀደም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አስቸጋሪ ጊዜ ላይ በሆነችበት ሰዓት የሩሲያ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን በቅዱስ ፓትርያርኳ በኩል ሀዘኗን በመግለጽ አጋርነታቸውን ማሳየታቸውን ያስታወሱት አምባሣደሩ፤ ሁለቱ አብያተ ክርስቲያናትም እንደቀደመው ጊዜ በመተባበር እንደሚቀጥሉም አስታውቀዋል።
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን አባቶችና ምእመናንን ከቀድሞው በበለጠ ሁኔታ አንድነታቸውን ማስጠበቅና በጽናት መቆም ይኖርባቸዋል ያሉት አምባሳደር ኢቭጌኒ፤ ይህ ሳይሆን ከቀረ ግን በቀጣይ ትውልድ ሁሉ የሚያስጠይቅ ይሆናል፤ ብለዋል። “በዚሁ ሂደትም ከጎናችሁ እንደምንቆም ላረጋግጥላችሁ እወዳለሁ” ሲሉም መልእክት አስተላልፈዋል።
ግብርን በቴሌ ብር ለመክፈል የሚያስችል ስምምነት ተደረገ
ከትላንት በስቲያ ጥር 25 በኢትዮ ቴሌኮም እና በገቢዎች ሚኒስቴር መካከል የግብር ክፍያዎችን በቴሌብር ለመሰብሰብ የሚያስችል ስምምነት ተደረገ፡፡
በዚህም ስምምነት፣ የሚኒስቴር መሥሪያ ቤቱ ደንበኞች የተለያዩ የግብር ክፍያዎችን በቴሌብር የዲጂታል ክፍያ ሥርዓት ተጠቅመው በኦንላይን አገልግሎት ክፍያቸውን እንዲፈፀሙ ያስችላቸዋል ተብሏል፡፡
ይህ የአጋርነት ስምምነት በዋናነት ለገቢዎች ሚኒስቴር የገቢ ግብርን እና የግል ሰራተኞች የጡረታ መዋጮ ፤እንዲሁም የፌዴራል ታክስ ክፍያዎችን ለመሰብሰብና ለማሳለጥ ጉልህ ሚና ያለው ሲሆን፤ ከዚህም ባሻገር በየጊዜው እያደገ የመጣውን የግብር ከፋዮች የክፍያ አማራጭ ፍላጎት ቀላልና አስተማማኝ በማድረግ፣ የቴሌብር ተጠቃሚዎች ከግል ወይም ከድርጅት የቴሌብር አካውንታቸው በቴሌብር የሞባይል መተግበሪያ ወይም በአጭር ቁጥር *127# በመጠቀም የግብር ክፍያቸውን ባሉበት ሆነው በቀላሉ ለመክፈል የሚያስችላቸው እንደሆነ ተገልጿል፡፡ በተጨማሪም በቴሌብር ግብይት የሚፈፅሙ ነጋዴዎች ከሚፈፅሟቸው ግብይቶች ከሰበሰቡት ገንዘብ ላይ ለግብር ክፍያ በቀጥታ መክፈል የሚችሉበት ሁኔታም ተመቻችቶላቸዋል ተብሏል፡፡
አገልግሎቱን ለማግኘት የሚኒስቴር መ/ቤቱ ደንበኞች ወደ www.mor.gov.et በመግባትና የኤሌክትሮኒክስ ታክስ አገልግሎት የሚለውን በመምረጥ፣ አስፈላጊውን ሂደት ሲጨርሱ፣ ከገቢዎች ሚኒስቴር የሚሰጣቸውን የሰነድ ቁጥር በመጠቀም በቀላሉ ክፍያቸውን በቴሌብር አፕሊኬሽን መፈፀም እንደሚችሉ ተጠቁሟል፡፡
በሌላ በኩል፤ ኢትዮ ቴሌኮም የክላውድ፣ የሙዚቃ ስትሪሚንግ እና የቴሌድራይቭ የሞባይል መረጃ ቋት አገልግሎቶችን ባለፈው ሰኞ ጥር 22 ቀን 2015 ዓ.ም ከአጋሮች ጋር ስምምነት በመፈፀም በይፋ አስጀምሯል፡፡
በዕለቱ ይፋ ከተደረጉት አገልግሎቶች መካከል ከቨድሊ ትሬዲንግ ኃ/የተ/የግ/ማህበር ጋር የተፈፀመው ስምምነት አንዱ ሲሆን በዚህ አገልግሎት ደንበኞች በሞባይል ስልኮቻቸው የሚገኙ እንደ ፎቶ፣ ቪዲዮና የመሳሰሉ ከፍ ያለ መጠን ያላቸውን ፋይሎች አስተማማኝ በሆነ የክላውድ መረጃ ቋት በማስቀመጥ በፈለጉ ጊዜ ሁሉ ማግኘትና መጠቀም የሚችሉበት መፍትሄ ነው ተብሏል፡፡
የዚህ አገልግሎት ተጠቃሚዎች የሞባይል ስልኮቻቸው ቢጠፋ ወይም ቢበላሽ ፋይሎቻቸውን ያለ ሃሳብ መልሰው ማግኘት እንደሚያስችላቸው ተነግሯል፡፡
ሌላው ይፋ የተደረገው አገልግሎት ከኩሉ ኔትወርክ ኃ/የተ/የግ/ማህበር ጋር የተፈፀመው ስምምነት ሲሆን ይህም የእልፍ ሙዚቃ መተግበሪያ ነው፡፡ ይኸው አገልግሎትም ሙዚቃዎችን በመተግበሪያው በመግዛት የሞባይል ዳታ ሳይጠቀሙ በፈለጉ ጊዜ ማዳመጥ እንዲችሉ እንዲሁም በአምስት ቋንቋዎች የሚተላለፍ የቀጥታ ሥርጭት ሬዲዮ ፕሮግራም ያለውና አገልግሎቱ በተመጣጣኝ ዋጋ የቀረበበት መሆኑ ተገልጿል፡፡
በአገራችን ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ የመጣውን የግልና የመንግስት ተቋማት ከፍተኛ የመረጃ ክምችትና አጠቃቀም እንዲሁም ተዛማች የክላውድ አገልግሎት ፍላጎትን መሰረት በማድረግ፣ እጅግ አስተማማኝ የክላውድ ማዕከላት መሰረተ ልማትንና አስፈላጊ ግብአቶችን ሁሉ በማሟላት ቴሌክላውድ አገልግሎትን በይፋ ለደንበኞቹ ማቅረቡን ያስታወሰው ኢትዮቴሌኮም፣ ከዚህ በተጨማሪም ከዘረጋው የኢንተርኔት አገልግሎት አቅራቢ ጋር በመተባበር የክላውድ ሶሉሽን አገልግሎቶችን በተለያዩ አማራጮች ማቅረቡን ይፋ አድርጓል፡፡
“አገባሽ ያለሽ ላያገባሽ ከባልሽ ሆድ አትባባሽ!”
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ መንገደኛ በፈረስ እየገሠገሠ ሳለ፣ አንድ ምስኪን አንድ እግሩ ጉዳተኛ ሰው ዳገቱን በእንፉቅቅ ሊወጣ አበሳ ፍዳውን ሲያይ ያገኛል። ያ ጉዳተኛ ሰው፤ “ወዳጄ እባክህ አፈናጥጠኝና እቺን አቀበት እንኳ ልገላገል” ይለዋል።
ፈረሰኛውም ከፈረሱ ወርዶ ያን እግረ- ጉዳተኛ ሰው ተሸክሞ ፈረሱ ላይ ያፈናጥጠውና መንገድ ይቀጥላሉ። ብዙም ሳይሄዱ ተፈናጣጩ፤
“ወዳጄ ካዘንክልኝ አይቀር እባክህ በተራ በተራ እንንዳ፤ ጉዳተኛው እግሬ ተቆልምሞ ስቃዬ ጭራሽ በረታብኝ” አለው።
ፈረሰኛውም አዝኖ፤
“ግዴለም! አንተ በፈረስ ዳገቱን ውጣ። እኔ በፍጥነት እርምጃ እየሮጥኩም ቢሆን እደርስብሃለሁ” ብሎ ወርዶ ፈረሱን ሙሉ በሙሉ ለቀቀለት።
በተባባሉት መሰረት ጥቂት ርቀታቸውን ጠብቀው ከተጓዙ በኋላ፣ ፈረስ የተዋሰው ሰው ፈረሱን ኮልኩሎ እንደ ሽምጥ ጋለበ።
ባለፈረሱ በማዘን በሩጫ እየተከተለው፤
“ወዳጄ ግዴለም ፈረሱን ውሰደው። ግን አንድ ነገር ብቻ ስማኝ?” ይለዋል።
ያኛው ተንኮለኛ ነውና እየጋለበ ባለፈረሱ ሮጦ የማይደርስበት ርቀት ጋ ሲደርስ፤
“እሺ፣ አሁን ልትለኝ የፈለግኸውን ነገር ንገረኝ” አለው።
ባለፈረሱም፤
“ወዳጄ ሆይ! ሌላ ምንም ነገር ልልህ አይደለም። አንድ ነገር ግን እለምንሃለሁ። ይኸውም፡-
“ይሄንን ዛሬ እኔን ያደረግኸኝን ነገር፣ አደራ ለማንም አትንገር። አለዛ ደግ የሚሰራ ይጠፋል” አለው ይባላል!!
* * *
ዱሮ በየሰው ቤት ግድግዳ ላይ በስክርቢቶም በፓርከርም በከረርም ተፅፋ የምትለጠፍ ጥቅስ ነበረች፡
“ጽድቅና ኩነኔ፣ ቢኖርም ባይኖርም
ከክፋት ደግነት ሳይሻል አይቀርም!”
ዛሬም ውሃ የምታነሳ ጥቅስ ናት!
በሌላ አቅጣጫና ገጽታውን ስናየው ደግሞ የፖለቲካ ክፋትና ደህንነት፤ የኢኮኖሚ ክፋትና ደህንነት፤ እንዲሁም የማህበራዊ ክፋትና ደህንነት የሚል ትርጓሜን እናገኝበታለን ማለት ይሆናል። በፖለቲካው ረገድ የጭካኔያችንን፣ የጦርነታችንን፣ የደም መፋሰሳችንን መጠን እንለካበታለን። በተቃራኒው ደግሞ የልግስናችንን፣ የሰብዕናችንን ስፋት እናመዛዝንበታለን፡፡ የሰብዓዊ እርዳታ ወደ ህዝብ እንዳይደርስ “አገቱ” የሚባለውን አይነቱን ዜና መመርመር ነው። ለማን ነው የሚታገሉት? ለምን አገቱት? ምን ይጠቀማሉ? ወዘተ እያሉ መጠየቅ ነው። የተቃውሞ እንቅስቃሴ በአጠቃላይ የኢኮኖሚ መስኩ ላይ የሚያደርሰውን ጉዳት ለማስተዋል መቼም ጭንቅላትን ይዞ ማሰብን አይጠይቅም። በባህሉም ረገድ እንደዚያው ነው። አብያተ ክርስቲያናቱ እንደምሽግ እንዳገለገሉ አይተናል።
አያሌ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የባሕል ፍጭቶችንና ደም-መፋሰሶችን በምስክርነት አይተን ስናበቃ፣ የተለመደው የሰላምና የድርድር ወቅት ሲከሰትም ማየታችን የማይታበል ሀቅ ነው! ድግግሞሹ አቋም እስከምናጣ ድረስ ለቋሳ አደረገን እንጂ ክስተቱንስ እንደ ፀሀይ መውጣትና መግባት ተዋህደነዋል። “ጣሊያን ሊማሊሞን በመድፍ ሲደበድበው አደረ” ቢለው፤ “ተወው ይበለው፣ እሱም መገተሩን አብዝቶት ነበር” አለው እያልን የምንሸሙር ሰዎች ያለንባት አገር ናት! መንግሥቱ ፀጥታውንና ሰላሙን ማስከበሩ ግዴታውና የሚያስጠይቀውም መሆኑ እንደተጠበቀ ሆኖ፤ በሌላ በኩል ግን ሌላው የህብረተሰብ ወገን ተገቢውን እገዛና ተሳትፎ ሊያደርግለት ይገባል የሚለውን እሳቤ በአግባቡ ማጤን የማንኛውም ወገንና ዜጋ ኃላፊነት መሆኑንም ማስተዋል ያባት ነው።
በሌላ መልኩ የሀገራችንን ሁኔታ ስናስተውል አሳሳቢውና አላባራ ያለው ሙስና ነው። በየመንግሥት መዋቅሩ ታማኝ ሰው መጥፋቱን የተሻለ ተብሎ የሚመደበው ሹም፤ “የምበላው ሳጣ፣ ልጄ ጥርስ አወጣ” እያሰኘን መምጣት ነጋ ጠባ እየመሰከርን ነው። የቀድሞው ቀድሞ ጠ/ሚኒስትር መለስ ዜናዊ፤ “እኛን ያስቸገረን የአማራ ተረትና የሶማሌ ባጀት ነው” ብለው ነበር ይባላል። አይ ዛሬ ባዩ!... የኢትዮጵያ ጠቅላላ ባጀት ራስ የሚያዞር መሆኑን በይፋ ይነግሩን ነበር። በጀቱ በራሱ ወንጀል የለበትም። ወንጀለኛው በጀት ያዡና ተቆጣጣሪው ነው። ገንዘብ ሚኒስቴር፣ ፋይናንስ ቢሮ፣ አገር ውስጥ ገቢ፣ የፖሊስ ጣቢያዎችና ፍትሕ አካላት… ማን ከማን ይመረጣል። በጠቅላላ ሽንፍላ ማጠብ ነው! አሁንም ሰው መቀያየሩ፣ ሹም- ሽሩ፣ እርምጃና እሥሩ፣ ተግባራዊ መፈክር ነው። እስኪጠራ ድረስ ሂደቱ መቋረጥ አይችልም። ዛሬም፡-
“… አገርህ ናት በቃ
አብረህ እንቀላፋ፣ ወይ አብረሃት ንቃ!” እንላለን።
የውጪ አገር መንግስታት በእኛ ጉዳይ ውስጥ እጃቸውን ከማስገባት መቼም ቦዝነው አያውቁም- በቀጥታም በተዘዋዋሪም። “ብርድ ወዴት ትሄዳለህ?” ቢሉት “ወደለበሱት።” “የተራቆቱትስ?” ቢሉት፣ “እነሱማ የኔው ናቸው!” አለ አሉ። የምዕራብ አገሮች ብድር ራሳችንን እስክንችል ድረስ አይፋታንም። ስለዚህ ከገዛ ሕዝባችን ጋር በጽንዓት መቆም፣ በራስ መተማመንና መታገል ቁጥር አንድ ተግባራችን ነው - “አገባሽ ያለ ላያገባሽ፣ ከባልሽ ሆድ አትባባሽ!” የምንለው ለዚህ ነው።