Administrator

Administrator

አስትራዜንካ  በመላው ዓለም የሚከበረውን ‹‹የዓለም የልብ ቀን›› ምክንያት በማድረግ ነፃ የደም ግፊት ምርመራዎች እና የምክር ድጋፎችን በትናንትናው እለት በአዲስ አበባ እና በሌሎች የክልል ከተሞች አከናወነ፡፡
‹‹ሄልዚ ሃርት  አፍሪካ” በተሰኘው ፕሮግራሙ   አስትራዜንካ ነፃ የደም ግፊት ምርመራዎች እና የምክር ድጋፎችን  ያከናወነው በአዲስ አበባ ከተማ በሜክሲኮ፤ በዋቢ ሸበሌ ሆቴል፣ በሾላ ገበያ እና ሩፋኤል ቤተ ክርስቲያን አካባቢ በሚገኙ አውራ ጎዳናዎች አደባባዮች እንዲሁም በክልሎች በጅማ፣ ሃዋሳ፣ ሆሳዕና ፤መቀሌ፣ ሃረር እና ድሬደዋ ከተሞች  በመሰማራት ነው፡፡ የዓለም ልብ ቀን ከ2012 እኤአ ጀምሮ በመላው ዓለም በተለያዩ ዘመቻዎች ሲከናወን የቆየ ሲሆን ከልብ ህመም ጋር በተያያዘ የሚከሰተውን የሞት አደጋ እስከ 2025 እኤአ በ25 በመቶ ለመቀነስ በተያዘ ዓላማ ዘንደሮ ተከብሯል፡፡ አስትራዜንካ የደም ግፊት ምርመራዎች በማከናወን የልብ ጤናን ለመጠበቅ  መደረግ ስለሚችሉ ቅድመ ጥንቃቄዎች ግንዛቤ ለመፍጠር ተንቀሳቅሷል፡፡  
“በደም ግፊት ማንም ሰው መሞት የለበትም” በሚል መርህ የሚንቀሳቀሰው አስትራዜንካ ከኢ.ፌ.ዲ.ሪ የጤና ጥበቃ ሚኒስተር ጋር በአጋርነት ለመስራት ስምምነት ያደረገው  ከዓመት በፊት ሲሆን፤ በሔልዚ ሃርት አፍሪካ ፕሮግራሙ የደም ግፊት በሽታን ለመዋጋት የሚደረገውን እንቅስቃሴ ማገዝ እንዲሁም በሽታውን ለመከላከል የሚያስችሉ የአሰራር መዋቅሮችን ከአገሪቱ የጤና አስተዳደር ጋር አጣጥሞ ለማከናወን ድጋፍ በመስጠት ኢትዮጵያውያን የነፃ ደም ግፊት ምርመራዎች እና የምክር አገልግሎቶችን እንዲያገኙ  እየተንቀሳቀሰ ነው፡፡
አስትራዜንካ  ባለፈው 1 ዓመት ለ900 የጤና ባለሙያዎች እና የህክምና ድጋፍ ሰጪዎች ስልጠና የሰጠ ሲሆን በሰባት የአገሪቱ ክልሎች በሚገኙ 12 ሆስፒታሎች እና 36 የጤና ማዕከላት የተቀናጀ የአሰራር መዋቅርን ዘርግቷል፡፡ የህክምና ተቋሙ ባለፈው 1 ዓመት ነፃ የደም ግፊት ምርመራዎችን ከ200ሺ በላይ ለሚገመቱ ኢትዮጵያውያን ያከናወነ ሲሆን ፤ በሄልዚ ሃርት አፍሪካ ፕሮግራሙ ከደም ግፊት ጋር በተያያዘ ደረጃውን የጠበቀ ህክምና፤ እንክብካቤ እና የተሟላ አገልግሎት የሚሰጥበትን ሁኔታ በመላው ኢትዮጵያ ለማስፋፋት በትኩረት እየሰራ ቆይቷል፡፡






   የላቲን አሜሪካው ጎሬላ መሪና አብዮታዊ ንድፈ - ሀሳብ ቀማሪ፣ ቼ ጉቬራ ዕውነተኛ ስሙ ኤርኔስቶ ጉቬራ ነው፡፡ የ1960ዎቹ አዲስ የግራ - ሥር - ነቀል ኃይሎች ጀግና ነው፡፡ በፊደል ካስትሮ በሚመራው የኩባ አብዮት ዋና ከሚባሉት ሰዎች አንዱ ነው፤ ቼ፡፡ ቼ ጉቬራ የአርጀንቲና ተወላጅ ይሁን እንጂ በየትም ሀገር ሄዶ፣ ትግል ለማገዝ ወደ ኋላ የማይል ዓለም - አቀፋዊ ታጋይ ነው፡፡ እንደ እሱ ዕምነት የላቲን አሜሪካን ድህነት፣ በሽታና ኢኮኖሚያዊም ሆነ ፖለቲካዊ ኢ-ፍትሃዊነት ለመላቀቅ፣ ብቸኛው መፍትሄ/መድሕን አብዮት ነው ብሎ ያምናል። የካስትሮ ዋንኛ አማካሪ የሆነ ሲሆን ካስትሮ ከኪውባው አምባገነንና ሙሰኛ መሪ ከፉልጄንቺዮ ባቲስታ ጋር ባደረገው የጎሬላ ውጊያ፤ ቼ ጉቬራ ቁልፍ ሚና ተጫውቷል፡፡ ቼ በኋላ የቦሊቪያን ወታደራዊ መንግስት ሲዋጋ ተገደለ፡፡ የተቀበረው ኪዩባ ውስጥ ነው።
ከላይ በተጠቀሰው የካስትሮና የቼ ጉቬራ ትግል ላይ በመመስረት፣ በወቅቱ ይጠቀስ የነበረ ቀልድ የሚመስል አንድ ታሪክ አለ፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን ቼ ጉቬራ፣ ካስትሮና አንድ ተራ ወታደር ኪውባ ውስጥ አምባገነኑን ወታደራዊ መሪ ባቲስታን እየተዋጉ ሳሉ አንድ ቃል ይገባባሉ፡፡
ካስትሮ ነው ነገሩን ያመጣው፡፡
“እንግዲህ” አለ ካስትሮ፤ “መቼም ሽምቅ ውጊያ ላይ ነንና ድንገት ጠላት እጅ ልንወድቅ እንችላለን፡፡ ጠላትም የሚሰጠን ቅጣት እኛ እሱ ላይ ባደረስንበት ጥቃት ያህል እንደሚሆን ጥርጥር የለውም”
ቼ፤ በጉዳዩ መስማማቱን ሲገልፅ፤
“ዕውነት ነው፤ ጠላታችን ብዙ ጉዳት ያደረሰበት ሰው ላይ የመጨረሻውን አሰቃቂ የቅጣት እርምጃ እንደሚወስድበት ከዓለም ታሪክ የተረዳነው ነገር ነው፡፡ አይመስልህም ወዳጄ?” አለው፤ ወደ ወታደሩ ዘወር ብሎ።
ወታደሩም፤
“የእኔም ዕምነት እንደዚያው ነው!” አለ፡፡
ቀጠለ ካስትሮ፤
“እንግዲያው ጓዶች እንዳንከዳዳ! ጠላት ላይ የጥቃት እርምጃ ስንወስድ አናወላውል፡፡ የማያዳግም ጥቃት እናድርስ!”
ቼ፤ “በትክክል! ወሳኝ ጥቃት ነው መሰንዘር ያለብን!” አለ፡፡
ወታደሩም፤
“በበኩሌ የተማርኩትን የጎሬላ ጥበብ ሁሉ ልጠቀም ቃል እገባለሁ!”
ካስትሮ፤
“እኔም ቃል እገባለሁ!”
ቼም፤
“እኔ ቅንጣት ጥርጣሬ የለኝም፤ ቃሌ ቃል ነው!” አለ፡፡ ሲዋጉ ከርመው የተባለው አልቀረም፣ ሶስቱም ጠላት እጅ ወደቁ! ይባላል! ቅጣታቸውም እንደየበደላቸው መጠን በቁማቸው መሬት መቀበር ሆነ፡፡
ያ ተራ ወታደር እስከ አንገቱ ድረስ መሬት ተቀብሯል፡፡ ካስትሮ ግን እጉልበቱ ድረስ ብቻ ነው መሬት የገባው፡፡
ይሄኔ ያ ወታደር፤
“ካስትሮ፤ የገባነው ቃል እንዲህ ነበር? ጠላት ላይ ምንም ጉዳት አላደረስክም ማለት’ኮ ነው አንተ?” አለው፡፡
ካስትሮም፤
“አይ፤ ቼ ጉቬራ ጭንቅላት ላይ አቁመውኝ እኮ ነው!” አለ፡፡ (I am just standing on the head of Che Guevara) ቼ ሙሉ ለሙሉ ከመሬት በታች ተቀብሯል ማለት ነው!
*            *            *
አንድም በቼ ጭንቅላት ነው እዚህ የደረስከው ማለት ነው፤ ነገሩ፡፡ ቼ ያልተገነዘበው፤ “የሰው ቤት የሰው ነው” የሚለውን አማርኛ ተረት ነው! ያም ሆኖ መኖሪያው ያልሆነ ኩባ፣ መቀበሪያው ሆነ! የእንቅስቃሴዎች ሁሉ መዘውር ዕምነትን መካድ፣ ማተብን መበጠስ፣ አድር - ባይነት፣ ፅናት፣ ቆራጥነት፣ አይበገሬነት ነበር፤ ነውም፡፡
ጠንካራ ሰው ጥንካሬን ለዘለዓለም ማቆየት አይችልም፡፡ ጉልበትን ወደ መብት፣ ታዛዥነትን ወደ ሥራ ግዴታ ካልለወጠ በስተቀር፤ ይላሉ ፀሐፍት፡፡
ቼ ማርክሲስት ነው፡፡ የ60ዎቹ ዘመን ኢትዮጵያውያንም ማርክሲስቶች ነበሩ፡፡ እስከ ዛሬም አባዜው ያልለቀቃቸው፤ ልክ ይሁኑም አይሁኑም፤ አሉ፡፡
“ማርክሲዝምን ማግኘት፤ ጫካ ውስጥ ካርታ እንደ ማግኘት ነው” የሚል ሰው ነበር፡፡ የዚያን ዘመኑ ማርክሲዝም የፖለቲከኝነት መገለጫ ነበር፡፡ በኢትዮጵያም እንደዚሁ የፖለቲካው መገለጫ የሶሻሊስቱ አካሄድ ሲሆን መጠንጠኛው ይኼው ማርክሲዝም ነበር፡፡ ዛሬ በገዢው ፓርቲም ሆነ በተቃዋሚ ጎራ የተሰለፉት ወገኖች የማርክሲዝም አቀንቃኞች ነበሩ፡፡ እስካሁን ያልለቀቃቸው አሉ ቢባል ስህተት አይሆንም፡፡
ቶማስ ፔይን፤ “አንድ ትክክለኛ ሰው፤ ዘውድ ካጠለቀ አጭበርባሪ ይልቅ ብዙ ከበሬታ ይገባዋል” ይለናል። ዘውድ ያጠለቀ እንግዲህ ባለስልጣን ሁሉ ማለት ነው፡፡ ሹመኛ ማለት ነው፡፡ ሊቀመንበር ማለት ነው፡፡ የማህበርም፣ የፓርቲም መሪ ነው፡፡ የቢሮ ኃላፊ ነው፡፡
ካስትሮ እንዲህ ይለናል፡-
“የሀገሪቱ የወደፊት ዕጣ፣ ለችግርቿም የሚሰጠው መፍትሔ በጥቂት ስግብግብ ነጋዴዎች ትከሻ ላይ አሊያም ከደርዘን የማይበልጡ፣ አየር-ማረጋጊያ በተገጠመለት ነፋሻ ቢሮ የተቀመጡ፣ ወሳኝ ሰዎች፤ ቀዝቃዛ የትርፍ ሂሳብ ስሌት ላይ የተመሠረተ ሆኖ ሊቀጥል አይችለም፡፡ … ችግራችን የሚፈታው አባቶቻችን ባወረሱን ኃይል፣ ታማኝነት/ለአገር መታመን፤ ጀግንነት… ራሳችንን አሳልፈን ከሰጠን ነው፡፡ “የኢንተርፕራይዞች ፍጹም ነፃነት”፣ “ካፒታላቸውን ለሚያፈሱ ኢንቨሰትሮች ዋስትና መስጠት”፣ “የአቅርቦትና ፍላጎት ሕግ” እያልን ያማሩ ቃላት በመደርደር አይደለም ችግራችን የሚፈታው! በሙስና የተዘፈቁ ተቋሞቻችንን ስናፀዳና በዘርፉ የተጨማለቁ ባለሥልጣናትን ስናስወግድ ነው! ትክክለኛ ያልሆኑ ህግጋትን ተቀብሎ የሚኖር፣ አገርን የሚጨፈልቅና የተወለደባትን አገር የሚበድል ሰው እያየ ዝም የሚል ግለሰብ፤ እሱ የተከበረ ሰው አይደለም፡፡… በዓለም ላይ የተወሰነ ብርሃን ያለውን ያህል፣ የተወሰነ የክብር ደረጃ መኖር አለበት፡፡ ክብረ-ቢስ የሆኑ ሰዎች በኖሩ ቁጥር፤ የብዙ ሰዎችን ክብር ይዘው የሚኖሩ ሌሎች ሰዎችም ይኖራሉ፡፡ እንደነዚህ ያሉ ሰዎች፤ የህዝቡን ነፃነት የሚሰርቁ ሰዎች ለማስወገድ በኃይል የሚነሱቱ ናቸው፡፡ ያም ማለት ክብርን ራሱን የሚዘርፉ ሰዎችን የሚቃወሙ ማለት ነው! በእንደዚህ ያሉ ሰዎች ልብ ውስጥ  በሺዎች የሚቆጠሩ ህዝቦች አሉ፡፡ የሰው ልጅ ክብር ታፍሮ ይኖራል!...” የሀገራችንን ነገር ከኩባ ጋር አነፃፅሮ ማየት እጅግ ጠቃሚ ነው፡፡
 ሼክስፒር በሎሬት ፀጋዬ ብዕር ውስጥ ይሄን ይለናል፡-
“ገንዘቤን የሰረቀ ሰው፣ ወሰደ እንበል ከንቱ ነገር
 ዋጋ አለው ግን ከንቱም ነው፣ የእኔም የእሱም የእሷም ነበር፤
ግና ስሜን የሰረቀኝ
የማያከብረውን ወስዶ፣ እኔን በግልፅ አደኸየኝ”
ጆን ሚልተን፤ “የፖለቲካ ሥልጣን ያለው ለንጉሦች ዘውድ መጫንም፣ ዘውድ መንጠቅም፣ ጨቋኞችን የመጣል ግዴታም ባለው ህዝብ እጅ ውስጥ ነው!” ይለናል፡፡ ችግሩ የሚከሰተው የተባለው ህዝብ ይሄንን ያላወቀ እንደሆነ ነው፡፡
እዚህ ላይ የካስትሮን “ታሪክ ነፃ ያደርገኛል” የሚለው የፍርድ ቤት መከላከያ ንግግር መጥቀስ ተገቢ ነው፡፡ “ህልመኛ ነው ብለው የሚያስቡ ካሉ የማርቲን ንግግር እጠቅሰላቸዋለሁ፡፡ “ዕውነተኛ ሰው ጥቅም ያለበትን ቦታ አይደለም የሚሻው፡፡ ይልቁንም ተግባር ያለበትን ቦታ እንጂ፡፡ ዕውነተኛ የተግባር ሰው ይሄ ነው- የዛሬ ህልሙ የነገ ህግ የሚሆን! ምክንያቱም፤ የታሪክን ሂደት ዞር ብሎ ለተመለከተና እንደ እሳት የሚንበለቦሉና በዘመናት ሰታቴ ድስት ውስጥ እየተፍለቀለቁ የደሙ ህዝቦችን ላየ፣ ነገ ሥራን በሚያከብሩ ሰዎች እጅ ውስጥ መሆኑን ይገነዘባል” ስለዚህ ዕውነተኛ ሰዎችን በዙሪያችን መያዝ ተገቢ ነው፡፡ የሰው ኃይል፣ የተደራጀ የሰው ኃይል፣ ራሱን የሚያውቅ የሰው ኃይል ማፍራት ዋና ነገር ነው፡፡ “ከእሾህ አጥር፣ የሰው አጥር ይጠነክራል” የሚለው የትግርኛ ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው፡፡

    ላለፉት 38 አመታት በጆሴ ኤድዋርዶ ዶስ ሳንቶስ ስትመራ የቆየቺውና ዜጎቿ የነዳጅ ሃብቷ ተጠቃሚ ሳይሆኑ የከፋ ኑሮን እንደሚገፉ የሚነገርላት አንጎላ፤ የቀድሞውን የመከላከያ ሚኒስትሯን ጃኦ ሎሬንኮን በሳምንቱ መጀመሪያ ቃለ መሃላ አስፈጽማ በፕሬዝዳንትነት ሾማለች፡፡አንጎላ ከአራት አስርት ዓመታት ገደማ በኋላ መሪዋን ብትቀይርም ይህ ነው የሚባል ለውጥ እንደማይጠበቅ የዘገበው ቢቢሲ፤ ለዚህ በምክንያትነት
ያስቀመጠውም፣አዲሱ ፕሬዚዳንት በእነዚህ አመታት በብቸኝነት ስልጣኑን ተቆናጥጦ የዘለቀው የገዢው ፓርቲ ኤምፒኤልኤ ቁልፍ ሰው መሆናቸውን ነው፡፡ፕሬዚዳንት ዶስ ሳንቶስ፣ የፕሬዚዳንትነቱን ቦታ ቢያስረክቡም፣ በፓርቲው ውስጥ ያላቸውን የአገሪቱን የፖሊስ አዛዥና የጦር ሃይል አዛዥ የመሾም ስልጣን ይዘው እንደሚቆዩ የጠቆመው ዘገባው፤ ይህም ሰውዬው ከወንበራቸው ቢነሱም አሁንም ቁልፍ ሚና እንዲጫወቱ እድሉን እንደሚሰጣቸው አመልክቷል፡፡በነዳጅ ሃብት በበለጸገቺው አንጎላ፣ የሃብት ክፍፍል ልዩነቱ እጅግ ከፍተኛ ሆኖ መዝለቁን የጠቆመው ዘገባው፤ አዲሱ ፕሬዚዳንት በነባሩ የፖለቲካ ስርዓት ላይ ለውጥ ለማምጣት ቢያቅዱም ብዙ ፈተና ይገጥማቸዋል ተብሎ እንደሚጠበቅም ገልጧል፡፡ አንጎላ ከፖርቹጋል ቅኝ አገዛዝ ነጻ ከወጣችበት ከ1975 አንስቶ በገዢ ፓርቲነት የዘለቀው የኤምፒኤልኤ ፓርቲ ሊቀመንበር በመሆን ለረጅም አመታት ስልጣንን የሙጥኝ ብለው የዘለቁት የቀድሞው የአገሪቱ ፕሬዚዳንት፣ ከፍተኛ ነቀፋ ሲሰነዘርባቸው እንደቆዩ ያስታወሰው ዘገባው፤
የአፍሪካ ቁጥር አንድ ሴት ቢሊየነር የሆነቺው ልጃቸው ኤልሳቤጥ ዶስ ሳንቶስም አባቷን መከታ በማድረግ፣ የአገሪቱን ኢኮኖሚ ተቆጣጥራዋለች በሚል እንደምትተች አስረድቷል፡፡

   በህፃናት አመጋገብ ዙሪያ በጥናት ላይ ተመስርቶ ያዘጋጃቸውን ማኑዋሎች ሰሞኑን ለባለድርሻ አካላት ይፋ ያደረገው  ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ፤ በስልጠና ማኑዋሎቹ አማካኝነት ሰፊ ለውጥ ይመጣል ተብሎ እንደሚጠበቅ አስታውቋል። በተለይ ህፃናት ተወልደው 1 ሺህ ቀናት ድረስ ባሉት ጊዜያት ያለው አመጋገባቸው ለእድገታቸው ወሳኝ መሆኑን በተመለከተ በኦሮሚያ ክልል ሁለት ወረዳዎች በወላጆችና ህፃናት ላይ ውጤታማነቱን ማረጋገጥ እንደተቻለ የጠቆመው ወርልድ ቪዥን፤ ለጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ተወካዮችና በህፃናት ላይ ለሚሰሩ መንግስታዊ ላልሆኑ ድርጅቶች፣ከትላንት በስቲያ በሳርማሪያ ሆቴል  ስልጠና ሰጥቷል፡፡
በስልጠናው ላይ በቀረበው ጥናታዊ ፅሁፍ፤ በሁለቱ ወረዳዎች በተለይ የህፃናት አመጋገብን አስመልክቶ በቤተሰብ ግንዛቤ ላይ በተሰራ ስራ፣ አመርቂ ውጤቶች መምጣታቸው የተገለጸ ሲሆን ይህንን የግንዛቤ ስራ ወደ አገር አቀፍ ደረጃ በማሳደግ፣ ህፃናትን ከመቀንጨር በመከላከል፣ በቂ ክብደት ኖሯቸው እንዲያድጉ በማድረግ፣ ምርታማ ዜጋን ለማፍራት አማራጭ የሌለው መፍትሄ ነው ብለዋል - በወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ፣ የፕሮግራም ውጤታማነትና የማስተማር ስትራቴጂ ዳይሬክተር አቶ በየነ ገለታ፡፡ አዲሱ የስልጠና ማንዋል በተለይ ለጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ግብአት በመሆን፣ በአገር አቀፍ ደረጃ አገልግሎት ላይ እንደሚውልም ዳይሬክተሩ አክለው ገልጸዋል፡፡
ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ በአሁኑ ወቅት ወደ 55 በሚጠጉ ወረዳዎች በአገር አቀፍ ደረጃ እንደሚሰራ የገለፁት ዳይሬክተሩ፤ ትኩረቱንም በጤና፤ በትምህርት፣ በማህበረሰብ ልማትና በምግብ ዋስትና ላይ እንደሚያደርግ ተናግረዋል፡፡
በወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ የኒዩትሪሽን ዲፓርትመንት ቴክኒካል ሀላፊ አቶ በኩረፅዮን አሳሳኸኝ በበኩላቸው፤ ይህንን የህፃናት አመጋገብ በማስተካክል በኩል ዋናው ተዋናይ መንግስት ቢሆንም ወርልድ ቪዥን የጥናት ውጤቶችን ለመንግስት በማቅረብ የበኩሉን እንደሚወጣ ገልፀዋል፡፡
በአንዳንድ አካባቢዎች በምግብ እጥረት፣በሌላ አካባቢ በግንዛቤ እጥረት፣ ልጆች ከህፃንነታቸው ጀምሮ ሁለት ዓመት እስኪሞላቸው ድረስ ባለው ጊዜ የተመጣጠነ ምግብ እንደማያገኙ ጥናቱ በተደረገባቸው ሁለት ወረዳዎች መረጋገጡን የጠቆሙት አቶ በኩረፅዮን፤ በጥናቱ ወቅት ግንዛቤ ያገኙ ወላጆች፣ አመጋገብ ላይ በሠሩት ስራ አመርቂ ውጤት መምጣቱንና በስልጠና ማኑዋሎቹ በስፋት ለውጥ ይመጣል ተብሎ እንደሚጠበቅ ተናግረዋል፡፡

ከእያንዳንዱ ጠርሙስ ውሃ፣ 1ሣንቲም፣ ለችግረኞች ድጋፍ ይውላል

ዋው የማዕድን ውሃ ፋብሪካ ምርት ከጀመረበት ቀን አንስቶ ከሸጣቸው ከእያንዳንዱ ጠርሙስ የማዕድን ውሃ ላይ አንድ ሳንቲም፣ ጧሪና ደጋፊ ለሌላቸው አረጋውያንና ወላጆቻቸውን ላጡ ህፃናት ድጋፍ አደረገ፡፡ ድርጅቱ ያደረገው የገንዘብ ድጋፍ፤ ቀጣይነት ያለውና ቋሚ
መሆኑን የፋብሪካው ባለቤትና ማኔጂንግ ዳይሬክተር አቶ ጠንክር በቀለ ገልፀዋል፡፡ ሰሞኑን በጉራጌ ዞን ቸአ ወረዳ ውስጥ በሚገኘው
የፋብሪካው ቅፅር ግቢ በተከናወነ ሥነሥርዓት፣ድርጅቱ 60 ለሚሆኑ አረጋውያንና ችግረኛ ህፃናት የገንዘብ ድጋፍ አድርጓል፡፡ በአረጋውያኑና በህፃናቱ ስም በንብ ኢንተርናሽናል ባንክ በተከፈተ የቁጠባ ሂሳብ፣ ለእያንዳንዳቸው 1500 ብር ገቢ የተደረገላቸው ሲሆን ችግረኞቹን በዘላቂነት ለመደገፍ ድርጅቱ ቃል ገብቷል። ማኔጂንግ ዳይሬክተሩ ባደረጉት ንግግርም፤የተደረገው የገንዘብ ድጋፍ፣ ድርጅቱ የገባውን ቃል
የሚያረጋግጥበትና ሃገራዊ ሃላፊነቱን በመወጣት ተግባራዊ እንቅስቃሴውን የሚያሳይበት ነው ብለዋል፡፡ ድጋፍ የተደረገላቸው አረጋውያንና ወላጅ
የሌላቸው ህፃናት በበኩላቸው፤ ባገኙት ድጋፍ ከፍተኛ ደስታ እንደተሰማቸው ገልጸው፣ ድርጅቱ በቀጣይነት በሚያደርግላቸው ድጋፍ፣ ህይወታቸውን ለማስተካከል የሚችሉበትን ሥራ ለመስራት እንደሚጥሩ ተናግረዋል። በዕለቱ በፋብሪካው ቅጥር ግቢ ውስጥ የተገኙ በርካታ
የአካባቢው ተወላጅ ባለሃብቶችም፣ለችግርኛ ህፃናቱና አረጋውያኑ የተለያዩ ድጋፎችን አድርገዋል፡፡ በ”የካብዲ አግሮፕሮሰሲንግ” ኃ.የተ.የግ.ማ ሥር
የተቋቋመው ዋው የማዕድን ውሃ ፋብሪካ፤ ለአካባቢው ወጣቶች የሥራ ዕድል በመፍጠርና ሌሎች አገር አቀፍ ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞችን በማስገኘት ሰፊ እንቅስቃሴ እያደረገ እንደሚገኝ የገለፁት የፋብሪካው ባለቤት፤ ከዚህ ባሻገር ችግረኛ የሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎችን በቋሚነት ለመደገፍ ዕቅድ ነድፎ በስፋት እንደሚንቀሳቀስ ተናግረዋል፡፡ ከ500 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ካፒታል የተቋቋመው ድርጅቱ፤ በቀጣይ በወተትና የወተት ተዋፅኦ፣ በፍራፍሬ ጭማቂዎችና በሌሎች የምግብና የመጠጥ አግሮፕሮሰሲንግ ሥራዎች ላይ በስፋት እንደሚሰማራ አቶ ጠንክር ገልፀዋል፡፡

“የተሻለ ኮንስትራክሽን፣ ለተሻለች ኢትዮጵያ”


የኢትዮጵያ ኮንስትራክሽን ሥራ ተቋራጮች ማህበር በየዓመቱ የሚያዘጋጀው “ኢትዮ ኮን” ዓለም አቀፍ የኮንስትራክሽን ኤግዚቢሽን ባለፈው ረቡዕ በአዲስ አበባ ኤግዚቢሽን ማዕከል የተከፈተ ሲሆን ነገ አመሻሽ ላይ ይጠናቀቃል ተብሏል። “የተሻለ ኮንስትራክሽን፣ ለተሻለች ኢትዮጵያ” በሚል መሪ ቃል በተከፈተው በዚህ ኤግዚቢሽን ላይ ከ100 በላይ የአገር ውስጥና የውጭ የኮንስትራክሽን ኩባንያዎች የተሳተፉ ሲሆን ከውጭዎቹ ሀገራት፡- ቻይና ቱርክ፣ ህንድ፣ ደቡብ ኮሪያና ሌሎችም ተሳታፊ መሆናቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡
በኤግዚቢሽኑ ላይ የኮንስትራክሽን እቃ አምራቾች፣ አቅራቢዎች፣ ዲዛይንና ስፔስፊኬሽን አዘጋጆች፣ ስራ ተቋራጮች፣ የሪል እስቴት አልሚዎች፣ ኤጀንቶች፣ የኮንስትራክሽን ማሽነሪ የአገር ውስጥ አምራቾች፣ አስመጭና አከፋፋዮች እንዲሁም ሌሎችም ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል፡፡
የኢትዮጵያ የኮንስትራክሽን ሥራ ተቋራጮች ማህበር ፕሬዚዳንት ኢ/ር አበራ በቀለ በመክፈቻው ላይ ባደረጉት ንግግር፤ በኢትዮጵያ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ የመጣው የኮንስትራክሽን ዘርፍ፣ እድገቱ ጤናማና ትክክለኛ እንዲሆን ለማድረግ፣ ሀላፊነቱ የዘርፉ ባለድርሻ አካላት ቢሆንም በዋናነት ከዘርፉ ባለቤት ከኮንስትራክሽን ሚኒስቴር ብዙ እንደሚጠበቅ ጠቁመው፣ አስፈላጊውን ድጋፍ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
ኤግዚቢሽኑ ምርትና አገልግሎትን ለጎብኚ በማቅረብ ብቻ ሳይወሰን የውይይት መድረክም አዘጋጅቷል፡፡ በዛሬው ዕለት ከጠዋቱ 2፡30 ጀምሮ በኢሲኤ አዳራሽ፤ “ወቅታዊ የኢትዮጵያ የኮንስትራክሽን ሥራ ተቋራጮች ተግዳሮቶችና የእድገት ማነቆዎች”፣ “የቴክኖሎጂ ሽግግር በካፒታል ኢንተንሲቭ፣ በኮንስትራክሽን ዘዴ”፣ “የኮንስትራክሽን ግዢና የኮንስትራክሽን አስተዳደር”፣ “ብክነትና ሊን ኮንስትራክሽን” በሚሉ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ ጥናታዊ ፅሁፎች ቀርበው  ውይይት እንደሚካሄድ ለማወቅ ተችሏል፡፡

አዲስ አበባ የጤናና የቢዝነስ ኮሌጅ፣ ለ13ኛ ጊዜ በዲግሪና በደረጃ አራት ያሰለጠናቸውን 429 ተማሪዎች ባለፈው ሳምንት በብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ አስመረቀ።ተመራቂዎቹ በነርሲንግ፣ በጤና መኮንን፣ በክሊኒካል ነርሲንግና በላብራቶሪ ቴክኒሺያን የትምህርት ዘርፍ
የሰለጠኑ እንደሆኑ ታውቋል፡፡ኮሌጁ ከተመሰረተበት ጊዜ አንስቶ እስካሁን ድረስ በሶማሌ ላንድ ሀርጌሳ የሚገኘውን ካምፓስ ጨምሮ
በአዲስ አበባና በተለያዩ ክልሎች ባሉት ካምፓሶቹ፣ከ47ሺህ በላይ የህክምና ባለሙያዎችን አሰልጥኖ በማስመረቅ በጤናው ዘርፍ ያለውን የባለሙያ ክፍተት ሲሞላ መቆየቱን የኮሌጁ ባለቤትና ፕሬዚዳንት ተናግረዋል፡፡ ከተመረቁ 47 ሺህ ባለሙያዎች መካከል
ከ10 ሺህ በላይ የሚሆኑት በኮሌጁ ነፃ የትምህርት እድል ተጠቃሚዎች እንደነበሩ ያስታወሱት ፕሬዚዳንቱ፤
በየካምፓሶቹ በዓመት ለ20 ተማሪዎች ነፃ የትምህርት እድል እንደሚሰጥና በተለይ መክፈል ባለመቻል መማር ላልቻሉ ሴት ልጆች ቅድሚያ በመስጠት ኃላፊነቱን ሲወጣ እንደቆዩ አክለው ገልፀዋል፡፡ተማሪዎች እዚህ ትምህርታቸውን አጠናቅቀው ለከፍተኛ ትምህርት አሜሪካ በሚሄዱበት ወቅት ተቀባይነት የሚያስገኝ፣ በአሜሪካ እውቅና ያለው ብቸኛ ኢትዮጵያዊ ኮሌጅ መሆኑን ፕሬዚዳንቱ በምርቃቱ ዕለት አስታውቀዋል

በብርሀኑ ደጀኔ የተሰናዳውና በእውነተኛ ታሪኮች ላይ ያጠነጥናል የተባለው፣ “በራስ እይታ የእማዬ ውለታ” መፅሀፍ ለንባብ በቃ።መፅሀፉ፤ የልጅነት፣ የስራ፣ የት/ቤትና ተለያዩ የህይወት አጋጣሚዎችን ያስቃኛል፤ ተብሏል። በ74 ገጽ የተመጠነው መፅሀፉ፣ በ70 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

Monday, 25 September 2017 11:56

የዒላማ ግርዶሽ

ርዕስ የለሽ ጽሕፈት
ውል አልባ ምዕራፍ
የምገርፈው በሬ
የሚጮኸው ጅራፍ
ያገር ደጅ ስጠና
ተከፈተ በራፍ፡፡
ክፋት ላይ ስተኩስ
ቅንነት ተመታች
ለተኩላ ባለምኩት
እርግብ በ’ራ ገባች
እርኩስ መቺ ቀስቴ
ደግ ላይ ተሰካች፡፡
ባላሚ ታላሚ
መሀል ስቶ ገብቶ
የዒላማ ግርዶሽ
ባገር ተንሰራፍቶ
አልሞ ለመምታት
አልተቻለም ከቶ፡፡
ከምሥጋና ጋር
ሳምሶን ጌታቸው ተ/ሥላሴ

* የቅዱስ ላሊበላ ደብርንና የደብረ ሊባኖስ ገዳምን ይጐበኛሉ
* ከፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ ጋር እንደሚነጋገሩ ይጠበቃል

     የሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ቅዱስ ባስልዮስ ማር ቶማ ጳውሎስ ዳግማዊ፣ የፊታችን ማክሰኞ በሚከበረው የመስቀል ደመራ በዓል ላይ ለመገኘት ከነገ በስቲያ ቀትር ላይ አዲስ አበባ የሚገቡ ሲሆን ከርእሰ ብሔሩ ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ ጋራ ተገናኝተው እንደሚነጋገሩ ተጠቁሟል፡፡
ቅዱስ ፓትርያርኩ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን አምስት ልኡካን በመምራትም፣ በኢትዮጵያ የአራት ቀናት ጉብኝት እንደሚያደርጉ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ቤተ ክህነት ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡
ለጉብኝቱ በወጣው መርሐ ግብር መሠረት፥ ሰኞ፣ ከቀትር በኋላ፣ የህንዱ ፓትርያርክ፣ በመንበረ ጸባኦት ቅድስት ሥላሴ ካቴድራል ኦፌሴላዊ አቀባበል ይደረግላቸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ የመንግሥት ባለሥልጣናት፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነቱና የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት አስተዳዳሪዎች፣ ሊቃውንት፣ የሰንበት ት/ቤት አባላትና ምእመናን በተገኙበት በሚደረገው አቀባበል፣ ፓትርያርኩ፣ ትምህርተ ወንጌል ይሰጣሉ፤ ተብሏል፡፡
በማግሥቱ ማክሰኞ፣ ከርእሰ ብሔሩ ፕሬዝዳንት ሙላቱ ተሾመ ጋራ ተገናኝተው እንደሚነጋገሩ የተጠቀሰ ሲሆን፤ ከቀትር በኋላም፣ ከብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ጋራ ወደ መስቀል ዐደባባይ በማምራት፣ የደመራን በዓል ያከብራሉ፡፡ ብዙ ሺሕ የሰንበት ት/ቤቶች ወጣቶች የሚያቀርቡትንና የሥነ በዓሉ ድምቀት የሆነውን ዐውደ ትርኢት የሚመለከቱት የህንዱ ፓትርያርክ፤ የሁለቱን አገሮችና አብያተ ክርስቲያናት ጥንታዊ ወዳጅነትና ቀጣይ ግንኙነት የተመለከተ ንግግር የሚያደርጉ ሲሆን ደመራውን፣ ከፓትርያርክ አቡነ ማትያስና ከአዲስ አበባ ከተማ ከንቲባ ድሪባ ኩማ ጋራ በአንድነት እንደሚለኩሱ ተጠቁሟል፡፡
በዕለተ ረቡዕ የመስቀል በዓልን፣ በላሊበላ ደብር ውቅር አብያተ ክርስቲያናት በመገኘት እንደሚያከብሩም የተገለጸ ሲሆን ከዚያም መልስ፣ የመንበረ ፓትርያርክ ጠቅላይ ጽ/ቤት ቤተ መጻሕፍት ወመዘክርን፣ የሰበታ ጌቴሰማኔ ቤተ ደናግል ሴቶች ገዳምንና የደብረ ሊባኖስ ገዳምን እንደሚጎበኙ መርሐ ግብሩ ያስረዳል። ከጉብኝታቸው ፍጻሜ በኋላ፣ በሁለቱ እኅትማማች አብያተ ክርስቲያናት አንድነትና ዓለም አቀፍ አገልግሎት ዙሪያ፣ በቅዱስ ሲኖዶስ ደረጃ የጋራ ምክክር እንደሚያካሒዱና መግለጫም እንደሚሰጡ ምንጮች ለአዲስ አድማስ ገልጸዋል፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፣ ባለፈው ዓመት ኅዳር ሕንድን በጎበኙበት ወቅት ባቀረቡላቸው ግብዣ መሠረት፣ መስቀል ደመራን በኢትዮጵያ የሚያከብሩት ቅዱስ ባስልዮስ ማር ቶማ ጳውሎስ ዳግማዊ፣ ለመጀመሪያ ጊዜ ከተገኙበት የካቲት ወር 2005 ዓ.ም. በዓለ ሢመት ወዲህ የአሁኑ ለሁለተኛ ጊዜ የሚያደርጉት ጉብኝት እንደሆነና የሁለቱን አብያተ ክርስቲያናት የተጠናከረ ግንኙነት እንደሚያሳይ ተጠቅሷል፡፡
ከቀድሞም ጀምሮ በአገራችን ዘመናዊ ትምህርት ቤቶች ጎልቶ የሚታየው የሕንዳውያን መምህራን አገልግሎት፣ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የሥነ መለኰት ኮሌጆችም መኖሩን ምንጮቹ አስገንዝበዋል፡፡ በአንጋፋው የቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ በማስተማር የሚታወቁ ዕውቅ የሥነ መለኰት ሊቃውንትን ያወሱት ምንጮቹ፤ ኮሌጁ በቀድሞው መንግሥት ተዘግቶ ዳግም ከተከፈተበት ከ1987 ዓ.ም. ወዲህም አገልግሎታቸው መቀጠሉንና ከመምህራኑም  መካከል ለማዕርገ ጵጵስና የበቁ እንዳሉ ጠቅሰዋል። ይህም፣ የቆየውን ግንኙነትና ትብብር ለማጠናከር ከፍተኛ ሚና መጫወቱን አስረድተዋል፡፡
ቅዱስ ባስልዮስ ማር ቶማ ጳውሎስ ዳግማዊ፣ እ.ኤ.አ ከኖቨምበር 2010 ጀምሮ፣ በሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን መንበረ ቶማስ የተሠየሙ 91ኛው የምሥራቅ ካቶሊኮስና የማላንካራ መጥሮጶሊጣን ናቸው፡፡ በኦፊሴላዊ ስያሜዋ፣ የማላንካራ ኦርቶዶክስ ሶርያ ቤተ ክርስቲያን ወይም የኦርቶዶክስ ሶርያዊ ምሥራቅ ቤተ ክርስቲያን ተብላ የምትጠራው የሕንድ ኦርቶዶክስ ቤተ ክርስቲያን፣ በሐዋርያው ቅዱስ ቶማስ በ52 ዓ.ም. የተመሠረተች ጥንታዊት ናት፡፡ በደቡብ ሕንድ የምትገኘው ኬሬላ ወይም ማላንካራ፣ የክርስትናው መሠረት የተጣለባት የመንበሩ መቀመጫ ስትሆን፤ ካቶሊኮስ የሚለው የርእሰ መንበሩ ሥያሜም የፓትርያርክ አቻ ተደርጎ ይወሰዳል፡፡ በአሁኑ ወቅት ቤተ ክርስቲያኒቱ፣ በሊቃነ ጳጳሳት የሚመሩ 25 የሀገር ውስጥና የውጭ አህጉረ ስብከትን እንዳቋቋመችና ከ2.5 ሚሊዮን በላይ ተከታዮች እንዳሏት መረጃዎች ያሳያሉ፡፡
በሌላ በኩል፣ ትውልደ ሕንዳውያንና የኦርቶዶክስ ክርስትና ተከታይ የሆኑ በርካታ ተሳላሚዎች፣ የሕንዱን ፓትርያርክ በመከተል በአዲስ አበባ የመስቀል ዐደባባይ ተገኝተው የደመራን በዓል እንደሚያከብሩ ታውቋል። ነዋሪነታቸውን በሕንድ፣ በአሜሪካና በእስራኤል ያደረጉ መነኰሳትን፣ ካህናትንና ምእመናንን ያካተተውና በአርባ አምስት ቡድን የተደራጀው ይኸው የተሳላሚዎቹ መንፈሳዊ ጉዞ፣ በአንጋፋው የሙምባዩ ሊቀ ጳጳስ ብፁዕ አቡነ ቄርሎስ የሚመራ እንደሆነ ተነግሯል፡፡ የጠቅላይ ጽ/ቤቱ ምንጮች እንደገለጹት፣ ተሳላሚዎቹ፣ “በኢትዮጵያ ገዳማት ሥርዓትና አኗኗር ዝና ተስበው የመጡ መንፈሳውያን ተጓዦች ናቸው፡፡” በኒውዴልሂ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ቢሮ አስተባባሪነት በተዘጋጀው ጉብኝት ፓኬጅ መሠረትም፣ የደመራን በዓል በመስቀል ዐደባባይ ተገኝተው ያከብራሉ፤ የላሊበላ ደብር ውቅር አብያተ ክርስቲያናትን፣ የጣና ገዳማትንና የጠቅላይ ጽ/ቤቱን ቤተ መጻሕፍት ወመዘክር ይጎበኛሉ፤ ብለዋል - ምንጮቹ፡፡