Administrator

Administrator

• የችግሮች ዋነኛ መንሥኤ፥ የሕግና የሥርዓት መጣስና ዘመኑን የዋጀ አለመሆን ነው፤ ተብሏል
• ቅዱስ ሲኖዶስ፥ ለውጡን የሚያስተባብርና የሚያስፈጽም አካል እንደሚሠይም ይጠበቃል
• ምልአተ ጉባኤው፣ በይደር በተያዘው የአዲስ ኤጲስ ቆጶሳት ሹመትም እንደሚነጋገር ተጠቁሟል
  ላለፉት ሁለት ሺሕ ዓመታት አያሌ ፈተናዎችን በመቋቋም ሐዋርያዊና ሀገራዊ ተልእኮዋን ስትወጣ የቆየችው የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ወቅታዊ ችግሮች ዋነኛ መንሥኤ፥ “የሕግና የሥርዓት መጣስና ዘመኑን የዋጀ አለመሆን ነው፤” ያለው አንድ ጥናት፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን ህልውና በማስጠበቅና ቀጣይነቷን በማረጋገጥ ለትውልድ ለማሸጋገር፣ መዋቅሯን መልሶ ማደራጀት፤ ሕጎቿን፣ ደንቦቿንና መመሪያዎቿን በፍጥነት በማስተካከል የለውጥ ሥራ ማካሔድ እንደሚኖርባት አሳሰበ፡፡
ጥናቱን ያቀረበው፥ በተመረጡ ሊቃነ ጳጳሳት፣ ሊቃውንትና ምእመናን ስብጥር የተቋቋመውና ባለፈው ዓመት ጥቅምት ላይ በቅዱስ ሲኖዶስ የተሠየመው ከፍተኛ ኮሚቴ ሲሆን፤ ችግሮችን ከሥር መሠረታቸው ለማረምና ለማስተካከል የሚያስችል አዲስ መዋቅርና አደረጃጀት እንዲሁም መሠረታዊ የሆኑ ሕጎችን፣ ደንቦችንና የአሠራር ሥርዓቶችን በመቅረጽና መልክ በማስያዝ የለውጥ ሥራውን የሚያካሒድ፣ ራሱን የቻለ የባለሞያ አካል መሠየምና በአስቸኳይ መተግበር እንደሚያስፈልግ አሳስቧል፡፡
ከላይ ወደ ታች፣ ከቅዱስ ሲኖዶስ ምልአተ ጉባኤ እስከ አጥቢያ ቤተ ክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ የሚደርሰውን መዋቅር፣ ተግባርና ሓላፊነት፥ ከተጠሪነት፣ የሰው ኃይል አደረጃጀትና የማስፈጸም አቅም ጋራ በማዛመድ የገመገመው ጥናቱ፥ መዋቅራዊ አደረጃጀቱ በአግባቡ አለመዘርጋቱን፤ የዕዝ ሰንሰለቱ፥ የላላ፣ የተንዛዛ፣ ለሓላፊነትና ለተጠያቂነት የማያመች መሆኑ፣ ለቤተ ክርስቲያኒቱ ዋነኛ ችግሮች በመሠረታዊ መንሥኤነት አስቀምጧል፡፡
የቋሚ ሲኖዶሱን መዋቅርና አደረጃጀት በቀዳሚነት ያነሣው ጥናቱ፣ የቅዱስ ሲኖዶሱን የዕለት ተዕለት ሥራዎች ለማከናወን በምልአተ ጉባኤ ቢወከልም፣ አባላቱ በየሦስት ወሩ መቀያየራቸው፣ ጉዳዮችን በስፋትና በጥልቀት አጥንቶ በመወሰን በኩል የአሠራር ችግር ማስከተሉን አመልክቷል፡፡
የፓትርያርኩ ልዩ ጽ/ቤት፣ ለፓትርያርኩ የአስተዳደር አገልግሎት ድጋፍና ለጽሕፈት ነክ ሥራዎች ቢታሰብም፣ ያለአግባብ ራሱን የቻለ ከፍተኛ የመዋቅርና የሥልጣን አካል አድርጎ እንደሚሠራ ጠቅሶ፥ “ለሕግና ሥርዓት መዛባት፣ ለመልካም አስተዳደር ዕጦትና ለመሳሰሉ ችግሮች ቀዳዳ የከፈተ አሠራር ሆኖ ታይቷል፤” ብሏል፡፡ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ዋና ሥራ አስኪያጅ፣ የቤተ ክርስያኒቱ ዋና ሥራ አስፈጻሚ አካልና የሥራ መሪ ኾነው ሳለ፣ የቋሚ ሲኖዶሱ አባል ሆነው መሥራታቸውም ለቁጥጥር እንደማያመችና ፍትሕ ሊያዛባ እንደሚችል ጠቁሟል፡፡
የቁጥጥርና ምርምራ አገልግሎት፣ የሥርዓትና ሥነ ምግባር ኮሚሽን፣ የመንፈሳዊ ፍርድ ቤት፣ የሊቃውንት ጉባኤና የውጭ ጉዳይ መምሪያዎች፣ የልማትና ክርስቲያናዊ ተራድኦ ኮሚሽን፣ የመንፈሳውያን ኮሌጆች፣ የጠቅላይ ቤተ ክህነት ጽ/ቤትና መመሪያዎች፣ የአህጉረ ስብከት ጽ/ቤቶችና የሥራ ዘርፎች እንዲሁም የአጥቢያ ሰበካ ጉባኤ መዋቅራዊ አደረጃጀት፣ ሓላፊነትና ተጠሪነት፥ ከውጤታማ የአሠራር ሥርዓት፣ ከመፈጸም ብቃት፣ ከሥራ ቅልጥፍናና የውሳኔ አሰጣጥ አኳያ ያሉባቸው ችግሮች በጥናቱ ከተዳሰሱት መካከል ይገኙበታል፡፡
የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አወቃቀር፣ እንደሌሎች አህጉረ ተመሳሳይ ሆኖ አለመደራጀቱንና “የቅዱስ ፓትርያርኩ ልዩ ሀገረ ስብከት ነው” የሚለው ድንጋጌም ግልጽ ባለመሆኑ ለበርካታ ውዝግቦች መነሻ መሆኑን ጥናቱ አስረድቷል፡፡ ይህን በመጠቀም፣ አንዳንድ የሀገረ ስብከቱ የሥራ ክፍሎችና የአዲስ አበባ ገዳማትና አድባራት፣ “ተጠሪነታችን ለፓትርያርኩ ነው” በሚል ከሕግና ሥርዓት ውጭ በመሆን፣ በጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የሚሰጠውን አመራር ያለመቀበል አዝማሚያ እንደሚያሳዩና ይህም ለመልካም አስተዳደር ችግር፣ ለምዝበራና ለሌሎችም አግባብ ለሌላቸው ተግባሮች በር መክፈቱን ዘርዝሯል፡፡
በአጠቃላይ መዋቅርና አደረጃጀቱ፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን ተልእኮ የሚያሳካና ዓላማዎችንና ግቦችን ለማስፈጸም የሚያስችል እንዳልሆነ፤ በተለይም፣ ሥልጣን ሁሉ ተጠቃሎ በአንድ ቦታ ተከማችቶ መገኘትና የሥራና የሓላፊነት ክፍፍል አለመኖሩን፤ የሥራ አስፈጻሚው ተግባርና የዳኝነቱ ሥራ ተቀላቅሎ እንደሚሠራና ለአሠራር ሥርዓት ክፍተትና ለፍትሕ መዛባት ምክንያት እንደሆነ ያስረዳው ጥናቱ፤ ሕግን የማውጣት፣ ሕግን የማስፈጸምና ሕግን የመተርጎም የሥልጣን መርሖዎች፣ ከቋሚ ሲኖዶሱ ጀምሮ በየደረጃው ተለያይተውና ተመጣጥነው በአጥጋቢ ሁኔታ የሚዘረጉበት ተቋማዊ ሁኔታ ሊኖር እንደሚገባ ጠቁሟል፡፡ መዋቅሩንና አደረጃጀቱን ከላይ እስከ ታች መልሶ የማደራጀቱና የማስተካከሉ ተግባር፣ ስትራቴጂያዊና መሠረታዊ በሆነ መልክ መፈጸም እንዳለበትና በጉዳዩ ላይ ቁርጠኛ አቋም ሊያዝ እንደሚገባ ጥናቱ አስገንዝቧል፡፡
ሕጎች፣ ደንቦችና መመሪያዎች ተሟልቶ አለመገኘትና ያሉትንም እንደየወቅቱ ሁኔታ እየታየ ማሻሻያ አለማድረግ፥ ለክፋትና ለተንኮል፣ ለግል ጥቅም ለተሰለፉ ወገኖች የተመቻቸ ሁኔታ እንደፈጠረላቸው ጥናቱ ጠቅሶ፤ የአሠራር ሥርዓቱን በአግባቡ ለማከናወን የሚያስችሉ ሕጎችና ደንቦች ያለመኖራቸውን በተጨማሪ መሠረታዊ መንሥኤነት አስቀምጧል፡፡
የበላይና ዋነኛ የሆነውና በሥራ ላይ የሚገኘው የ2007 ዓ.ም. ሕገ ቤተ ክርስቲያን፣ እጥር ምጥር ብሎ በግልጽ አቀራረብ፣ ጠቅላላ ድንጋጌዎችን፣ መሠረታዊ መርሖዎችንና ፖሊሲዎችን ይዞ በኮንስቲቱሽን መልክ እንደገና ተስተካክሎ እንዲጻፍና በየጊዜው ሳይቀያየር ቋሚና ዘላቂ እንዲሆን፤ ቃለ ዓዋዲው፣ የሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ደንብ በመሆኑ እንደገና ተሻሽሎ ሕጉን መሠረት በማድረግ፣ ሰበካ ጉባኤ ነክ የሆነው ተግባር ብቻ በሚገለጽበት ሁኔታ ተስተካክሎ እንዲጻፍ ማድረግ እንደሚያስፈልግ በመፍትሔነት የጠቆመው ጥናቱ፣ በአዲሱ መዋቅር የሚደራጀው የሥራ አስፈጻሚው አካል ተግባርና ሓላፊነቱን በብቃት ለመወጣትና ተጠያቂነትን ለማስፈን የሚያስችሉ የተለያዩ የሥራ ማስፈጸሚያ ሕጎችና ደንቦች(ቃለ ዐዋዲዎች) ሕገ ቤተ ክርስቲያኑን እያጣቀሱ መውጣት እንደሚኖርባቸው አመልክቷል፡፡
ከፍተኛ ኮሚቴው፣ የቤተ ክርስቲያኒቱን መዋቅር በሁለንተናዊ መልኩ መልሶ ለማደራጀትና ለማሻሻል ያስችላሉ ያላቸውን ሦስት የመዋቅር ለውጥ አማራጮችን ከማብራሪያዎቻቸው ጋራ በጥናቱ በማካተት ያቀረበ ሲሆን፤ ሕገ ቤተ ክርስቲያኑ፣ ቃለ ዓዋዲውና የሠራተኛ አስተዳደር ደንቡ፥ የመልካም አስተዳደርና የሥነ ምግባር ችግሮችን በመቅረፍ፣ ወጥ የሆነ የአሠራር ሥርዓት በመዘርጋት ዋነኛ ተልእኮዋን በብቃት ለመወጣት በሚያስችላት አኳኋን የሚሻሻሉበትን ይዘትና ሊይዟቸው የሚገቡ ዋና ዋና ሐሳቦችንም አመልክቷል፡፡
የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግር እጅግ አሳሳቢና የለውጥ ሥራውም የሁሉንም ትብብርና ድጋፍ እንደሚጠይቅ ያስገነዘበው ከፍተኛ ኮሚቴው፣ ቅዱስ ሲኖዶሱ ችግሩን ለመፍታት ያሳየው ተነሣሽነትና ቁርጠኝነት ተገቢና ወቅታዊ መሆኑን ገልጿል፡፡
የአሁኑ የጥምር ኮሚቴው ጥናታዊ ሪፖርት፣ ቀደም ሲል በተለያዩ አካላት በቀረቡ ሰነዶች የተጠቆሙ የቤተ ክርስቲያኒቱ ችግሮችና መፍትሔዎች አሳሳቢነት በድጋሚ የተረጋገጡበት እንደሆነ የተናገሩ የቅዱስ ሲኖዶሱ ምንጮች፤ የርክበ ካህናት ምልአተ ጉባኤው፣ በመጪው ሳምንት ረቡዕ በሚጀመረው ስብሰባው፣ በዋነኛ አጀንዳነት በመያዝ የለውጥ ሥራውን በባለቤትነት በማስተባበር መልክና ቅርጽ የሚያሲዝ የባለሞያ አካል ሊሠይም እንደሚችል ጠቁመዋል፡፡
በሌላ በኩል፣ ምልአተ ጉባኤው፣ ከባለፈው የጥቅምት መደበኛ ስብሰባው የተላለፈውንና የአዲስ ኤጲስ ቆጶሳት ሹመት በሚመለከተው አጀንዳ ዙሪያ ተነጋግሮ ውሳኔ ያሳልፋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡


 ቅዱስ ጊዮርጊስ በኢትዮጵያ የክለቦች ታሪክ ፈርቀዳጅነቱ በተለያዩ ሁኔታዎች ይጠቀሳል፡፡ 80ኛ ዓመቱን በማክበር ላይ የሚገኘው ክለቡን በብሄራዊና አህጉራዊ ደረጃ አዳዲስ ምእራፎችን እየከፈተ ጉዞውን ቀጥሏል፡፡ በአፍሪካ የክለቦች ውድድር ተሳትፎ 50ኛ ዓመቱን ሲይዝ  በ2017 ቶታል የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የምድብ ድልድል ገብቷል፡፡ ከደቡብ ፤ ከመካከለኛው እና ከሰሜን አፍሪካ ምርጥና የቀድሞ ሻምፒዮን ክለቦች ጋር የሚፋለምበት ደረጃ ላይ ነው፡፡
በ2017 ቶታል የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ 16 ክለቦች መሳተፋቸው በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ ሲሆን የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን ይህን ለውጥ በመፍጠሩ አድናቆት አግኝቷል፡፡ በተለይ በክለቦች ደረጃ ጠንካራ የሊግ ውድድር ያላቸው እነ አልጄርያ፤ ዛምቢያ፤ ሱዳን፤ ኬንያና የመሳሰሉት፤ እንዲሁም በምስራቅ፤ በደቡብ እና በመካከለኛው አፍሪካ ዞኖች ያሉ ክለቦች በምድብ ፉክክር ተሳታፊ የሚሆኑበትን እድል ፈጥሯል፡፡ በሌላ በኩል ባለፉት የውድድር ዘመናት በምድብ ፉክክሩ የሚገቡት ክለቦች 5 አገራትን ብቻ በተደጋጋሚ የሚወከሉበትን ሁኔታም ቀይሮታል፡፡ ዘንድሮ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ የ13 አገራት ክለቦች ተሳታፊ ናቸው፡፡ በአጠቃላይ ሊጉ የምድብ ፉክክር አዳዲስ ክለቦች ከተለያዩ አገራት በብዛት ያሳተፈ በመሆኑ በአፍሪካ ደረጃ  የሚያገኘውን ትኩረት ያሳድገዋል፡፡
በሳምንቱ አጋማሽ ላይ በካይሮ ከተማ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን ለ2017 የካፍ ቶታል ሻምፒዮንስ ሊግ እና ኮንፌደሬሽን ካፕ የምድብ ድልድሎችን  አውጥቷል፡፡ ኢትዮጵያን በመወከል የምድብ ፉክክር ውስጥ የገባው ቅዱስ ጊዮርጊስ በምድብ 3 ከደቡብ አፍሪካው ሜመሎዲ ሰንዳውንስ፤ ከዲ.ሪ ኮንጎው ኤኤስ ቪታ ክለብ እና ከቱኒዚያው ኤስፔራንስ ዴቱኒስ ጋር ተመድቧል፡፡ የምድብ የመጀመርያ ጨዋታዎች ከ2 ሳምንት በኋላ የሚጀምሩ ሲሆን ቅዱስ ጊዮርጊስ ከሜዳው ውጭ ከደቡብ አፍሪካው ሜመሎዲ ሰንዳውንስ ጋር ይገኛል፡፡
በሌሎቹ ሶስት ምድቦች ከ1 ጊዜ በላይ የሻምፒዮናነት ድሎችን ያስመዘገቡት የሰሜን አፍሪካ ክለቦች ቀለል ያሉ ታጋጣሚዎችን አግኝተዋል፡፡ በምድብ 1 በ2007 እኤአ ላይ ሻምፒዮን የሆነው የቱኒዚያ ኤትዋል ደሳህል፤ የሱዳኖቹ አልሂላል እና አልሜሪክ እንዲሁም በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ በምድብ ማጣርያው ተሳታፊ የሚሆነው የሞዛምቢኩ ፌዮቬራዬ ዴማፑቶ ይገኛሉ፡፡ በምድብ 2 የአምስት ጊዜ ሻምፒዮኑ የግብፁ ዛማሌክ፤ በቅድመ ማጣርያ ሃያሉን ቲፒ ማዜምቤ ጥሎ ማለፍ የቻለው የዚምባቡዌው ካፕስ ዩናይትድ፤ የአልጄርያው ዩኤስኤም አልጀር እና በሜዳው የሚያደርጋቸውን ጨዋታዎች በቱኒዚያ የሚያደርገው የሊቢያው አልሃሊ ትሪፖሊ ተደልድለዋል፡፡ በምድብ 4 ደግሞ ለስምንት ጊዜያት የአፍሪካ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው የግብፁ ክለብ አልአሃሊ፤ ከሞሮኮው ዋይዳድ ካዛብላንካ፤ የካሜሮኑ ኮተን ስፖርት እንዲሁም የዛምቢያ ዛናኮ ዩናይትድ ተመድበዋል፡፡
ብራዚላውያኖቹ ከደቡብ አፍሪካ
ሜመሎዲ ሰንዳውንስ የአምናው የሻምፒዮንስ ሊግ አሸናፊ ነው፡፡ በ2016 የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው በሚያስገርም አጋጣሚ ነበር፡፡ የዲ.ሪ ኮንጎው ክለብ ኤኤስ ቪታ ክለብ ተገቢ ያልሆነ ተጨዋች በማሰለፉ በቅጣት ከውድድሩ ውጭ ሲሆን ሜሞሎዲ ተክቶ በመግባት እስከ ዋንጫው ድል ተጉዟል፡፡ ሜሞሎዲ ሰንዳውንስን ማልያቸው ከብራዚል ብሄራዊ ቡድን ጋር ስለሚመሳሰል ብራዚላዊያኖቹ እያሉ ይጠሯቸዋል፡፡ ባፋና ባ ስታይል የሚሏቸውም አሉ፡፡ ከተመሰረተ 47 ዓመት የሆነው ክለቡ ስታድዬሙ በፕሪቶርያ የሚገኘውና 28ሺ ተመልካች የሚያስተናግደው ሎፍተስ ቬርስፊልድ ነው፡፡ ከ2016 ጀምሮ ማሊያው በናይኪ ስፖንሰር የሆነለትና፤ 3 የደቡብ አፍሪካ ግዙፍ ኩባንያዎች በአበይት ስፖንሰርነት የሚደግፉት ክለቡን በባለቤትነት የሚያስተዳድሩት ፓትሪስ ሞቴስፔ የተባሉ ባለሃብት ናቸው፡፡ ዋና አሰልጣኝ ደግሞ የደቡብ አፍሪካ ብሄራዊ ቡድንን ሲያሰለጥኑ የነበሩት ፒትሶ ሞስማኔ ናቸው፡፡በ2016 የዓመቱ የካፍ ምርጥ ክለብ የተባለው ሜሞሎዲ የ2017 የአፍሪካ ሱፕር ካፕንም ተቀዳጅቷል፡፡ በሌላ በኩል ከ1996 እኤአ ወዲህ የደቡብ አፍሪካ አብሳ ሊግን 7 ጊዜ ያሸነፈ ሲሆን በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ባለፉት 10 ዓመታ 37 ጨዋታዎች አድርጎ በ37 ድል፤ በ16 አቻ እንዲሁም በ15 ሽንፈት ገጥሞታል፡፡
ጥቁር ዶልፊኖች ከመካከለኛው አፍሪካ
የዲሪ ኮንጎው ክለብ ኤኤስ ቪታ ክለብ በ1973 እኤአ ላይ የአፍሪካ ሻምፒዮን ለመሆን የበቃ ሲሆን  በቅፅል ስም ጥቁር ዶልፊኖች ብለው ይጠሯቸዋል፡፡ ከተመሰረተ 92 ዓመታትን ያስቆጠረው ይህ ክለብ 80ሺ ተመልካች የሚያስተናግደውን ስታድ ዴ ማርታየርስ በሜዳነት የሚጠቀም ሲሆን የክለቡ ፕሬዝዳንት ጋብሬል አሲሚ ይባላሉ፡፡
ደምና ወርቅ ከሰሜን አፍሪካ
የቱኒዚያው ምርጥ ክለብ በሙሉ ስሙ ኤስፔራንሴ ስፖርቲቭ ዴ ቱኒዝ ተብሎ ቢታወቅም ቅፅል ስማቸው ደምና ወርቅ የሚል ነው፡፡ ከተመሰረተ 98ኛ ዓመቱን የያዘው ክለቡ በቱኒስ ከተማ የሚገኘውና 60ሺ ተመልካች የሚያተናግደውን ኦሎምፒክ ዴ ራዴስ ስታድዬም ይጠቀማል፡፡ የእግር ኳስ ብቻ ሳይሆን፤ እጅ ኳስ፤ ቅርጫት ኳስ፤ መረብ ኳስ እና የራግቢ ቡድኖችን የሚያተዳድረው ክለቡን በሊቀመንበርነት የሚመሩት ሃመዲ ማዴስ ናቸው፡፡ ኤስፔራንስ የቱኒዚያን ሊግ ለ21 ጊዜ የቱኒዚያ ካፕን 15 ጊዜ ያሸነፈ ሲሆን የአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግን በ1994 እና በ2011 እኤአ ከማሸነፉም በላይ ለ4 ጊዜያት በ2ኛ ደረጃ ጨርሷል፡፡ በ1998 እ.ኤ.አ ደግሞ የአፍሪካ ሱፕር ካፕን አሸንፎ ነበር፡፡
ፈረሰኞቹ ከምስራቅ አፍሪካ
የ2009 ዓ.ም የኢትዮጵያ ፕሪሚዬር ሊግን እየመራ የሚገኘው ቅዱስ ጊዮርጊስ  ዓመታዊ በጀቱ እስከ 20 ሚሊዮን ብር ይደርሳል፡፡   ከደጋፊዎች መዋጮ፤ ከስፖንሰሮች እና ከአጋር ድርጅቶች ፤ ከሜዳ፤ ከስፖርት ማህበሩ ክበብ፤ ከልዩ ልዩ የስፖርት ቁሶች ሽያጭ ከሚሰበስባቸው ገቢዎች የሚገኝ ነው፡፡ በማልያው ስፖንሰርሺፕ በየዓመቱ እስከ 6 ሚሊዮን ብር እየተከፈለውም ነው፡፡ በክለቡ ዘንድሮ   የአባልነት መዋጮ የሚከፍሉ ደጋፊዎች ብዛት ከ14ሺ 700 በላይ ሲሆን በተለያዩ የጥራት ደረጃዎች የተሸጡት ማልያዎች ከ10ሺ በላይ ናቸው፡፡  
ጊዮርጊስ በአገር ውስጥ የክለብ ውድድሮች ከ80 በላይ ዋንጫዎች የሰበሰበ ሲሆን፤ የፕሪሚዬር ሊግ 30፤ የጥሎ ማለፍ 13፤ የአሸናፊዎች አሸናፊ 10 ዋንጫዎች ይገኙበታል፡፡ በሀገር ውስጥ ውድድር ባስመዘገባቸው ተደጋጋሚ ድሎች ምክንያት ከኢትዮጵያ ክለቦች በአህጉራዊ ውድድሮች ተሳትፎው ከ50 ዓመታት በላይ ሆኖታል፡፡ ከዘንድሮ በፊት በአህጉራዊ ውድድሮች የተሻለ ውጤት ያስመዘገበው በ1959 ዓ.ም በአፍሪካ ክለቦች ዋንጫ ግማሽ ፍጻሜ የገባበት እና በ2005 ዓ.ም በኮንፌዴሬሽን ዋንጫ ስምንት ውስጥ የገባበት ዋናዎቹ ናቸው፡፡ በአጠቃላይ ከ1967 እኤአ ጀምሮ በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን ስር በሚካሄዱ ውድድሮች፤ ለ12 ጊዜያት በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ፤ለ10 ጊዜያት በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ካፕ፤ 1 ጊዜ በአፍሪካ ክለቦች ኮንፌደሬሽን ካፕ፤ 1 ጊዜ በካፍ ካፕ እንዲሁም ለ3 ጊዜያት በካፍ የአሸናፊዎች አሸናፊ ውድድሮች  ነው፡፡ በአፍሪካ ክለቦች ሻምፒዮንስ ሊግ ማጣርያዎች ላይ (ውድድሩ በካፍ አዲስ መዋቅር መካሄድ ከጀመረበት ከ1997 እኤአ ወዲህ  ማለት ነው፡፡) ከዘንድሮ በፊት ለ12 ጊዜያት በነበረው ተሳትፎ  በአጠቃላይ ውጤቱ 61ኛ ደረጃ ላይ ነበር፡፡ ለ8 ጊዜያት ቅድመ ማጣርያውን በማለፍ ለመጀመርያ ዙር ሲበቃ ለ4 ጊዜያት ከውድድሩ የተሰናበተው በቅድመ ማጣርያ ነበር፡፡
የአቶ አብነት ተስፋ እና የአቶ አርሰናል ማነቃቂያ
በሙሉ ስማቸው ዴቪድ ባሪ ዲን ተብለው ይጠራሉ፡፡ የ73 ዓመት አንጋፋ የእግር ኳስ ባለሙያ ሲሆኑ በሊድስ ዩኒቨርስቲ ኢኮኖሚክስ አጥንተዋል፡፡ በ1983 እኤአ ላይ ወደ አርሰናል ሲቀላቀሉ በክለቡ እስከ 292ሺ ፓውንድ ኢንቨስት በማድረግ  16 በመቶ የአክሲዮን ድርሻ ገዝተው ነበር፡፡ ከዚያ በኋላ  በአርሰናል ክለብና በእንግሊዝ እግር ኳስ ማህበር ምክትል ሊቀመንበርነት ከ20 ዓመታት በላይ አገልግለዋል፡፡  በአርሰናል ክለብ ከፍተኛ ባለስልጣን ሆነው በቆዩባቸው ዓመታት በክለቡ በነበራቸው የአክሲዮን ባለድርሻነት ፤ የአሰልጣኝ ቅጥር እና የተጨዋቾች ግዢ፤ የስታድዬም ግንባታ እና ሌሎች እንቅስቃሴዎች  ጉልህ ሚናዎች በመጫወታቸው አቶ አርሰናል (Mr· Arsenal) እስከመባልም ደርሰዋል፡፡ በተለይም በአርሰናል ክለብ ዋና አሰልጣኝነት ሲሰሩ 21ኛ  ዓመታቸውን የያዙትን ፈረንሳዊ አርሴን ዌንገር በመቅጠር በክለቡ ታሪክ ጉልህ አስተዋፅኦ ለማበርከት መቻላቸው ይጠቀስላቸዋል፡፡  በ2007 ክለቡ የለቀቁት የነበራቸውን  የአክሲዮን ድርሻ በ25 ሚሊዮን ፓውንድ በመሸጥ ነበር፡፡    በሌላ በኩል በ1992 እኤአ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ በአዲስ መልክ ተዋቅሮ፤ በትርፋማ አቅጣጫዎች እንዲንቀሳቀስ ካስቻሉ ባለሙያዎች ግንባር ቀደም ተጠቃሽ  ናቸው፡፡ከወር በፊት  የቅዱስ ጊዮርጊስ የስፖርት ማህበር ፕሬዝዳንት አቶ አብነት ገብረመስቀል ባደረጉት ልዩ ጥረት በሸራተን አዲስ በተዘጋጀ የግማሽ ቀን ሲምፖዚዬም ላይ በኢትዮጵያ እግር ኳስ ለሚንቀሳቀሱ ባለድርሻ አካላት የማነቃቂያ ንግግር አቅርበው ነበር፡፡  በዓመት እስከ 4.8 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ስለሚሆንበት የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ መዋቅራዊ አደራጃጀትና የእድገት ሂደት ፤ የክለቦችና የደጋፊዎች እንቅስቃሴ፤ በቴሌቭዥን የስርጭት መብት፤ በፕሮፌሽናል ተጨዋቾች የዝውውር ገበያ ያሉትን ጠቃሚ ተመክሮዎች  አጭር መግለጫ የሰጡበት መድረክ ነበር፡፡ በኢትዮጵያም የክለብ እግር ኳስ የእንግሊዝ ፕሪሚዬር ሊግ ተመክሮ እንዴት መተግበር እንደሚቻል  ያነቃቁበት መድረክ ነበር፡፡ የቅዱስ ጊዮርጊስ ስፖርት ማህበር ፕሬዚዳንት የሆኑት አቶ አብነት ገ/መስቀል በ2017 የካፍ የክብር ሽልማት አግኝተዋል፡፡ ዴቪድ ባሪ ዲንን ወደ አዲስ አበባ የጋበዙት እሳቸው ነበሩ፡፡ በኢትዮጵያ የክለብ እግር ኳስ ለውጥ የሚፈጥሩ ተመሳሳይ መድረኮችን ወደፊትም በመፍጠር ለመስራት እንደሚፈልጉ ተናግረው ነበር፡፡ በሚቀጥሉት 5 ዓመታት የኢትዮጵያ የክለቦች ውድድር በስፖንሰርሽፕ፣ በፕሮፌሽናል አደረጃጀት ትርፋማ እንዲሆን የሚያስችሉ የውይይት መድረኮችን ለመፍጠር ቃል ገብተው ነበር፡፡   

የቱርክ መንግስት ከከሸፈው የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ ጋር ንክኪ አላቸው ያላቸውን 1 ሺህ ፖሊሶች ያሰረ ሲሆን ከ9 ሺህ 100 በላይ የሚሆኑ ተጨማሪ ፖሊሶችን ደግሞ ከስራ ገበታቸው ማባረሩን አጃንስ ፍራንስ ፕሬስ ዘግቧል፡፡
ፕሬዚዳንት ጠይብ ኤርዶጋን ከሳምንታት በፊት በተከናወነው ህዝበ ውሳኔ ተጨማሪ ሃይል የሚሰጣቸውን ድል መቀዳጀታቸውንና መንግስትም የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁን ማራዘሙን ተከትሎ፣ በአገሪቱ ተቃውሞ እንደገና መቀስቀሱን የጠቆመው ዘገባው፤ ከስልጣን ሊያስወግዱኝ እያሴሩ ነው ካሏቸው ቡድኖች ጋር ንክኪ አላቸው ያሏቸውን ፖሊሶች ባለፈው ረቡዕ ታድነው እንዲታሰሩ ማድረጋቸውን ገልጧል፡፡ 8 ሺህ 500 ያህል የመንግስቱ ታማኝ ፖሊሶች በተሳተፉበትና መላ ቱርክን ባዳረሰው አሰሳ፣ 1 ሺህ 120 ያህል ፖሊሶች መታሰራቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ ለቱርክ ብሄራዊ ደህንነት አደጋ ናቸው የተባሉ 9 ሺህ 103 ፖሊሶችም ከስራ ገበታቸው እንዲባረሩ ተደርጓል ብሏል፡፡
ተቀማጭነታቸው በአሜሪካ የሆነው ፈቱላህ ጉሌን ያቋቋሙት ቡድን ያቀናበረው ነው የተባለውና ባለፈው ሃምሌ ወር በኤርዶጋን ላይ የተቃጣው የመፈንቅለ መንግስት ሙከራ መክሸፉን ተከትሎ፣ የአገሪቱ መንግስት ከመፈንቅለ መንግስቱ ጋር ንክኪ አላቸው በሚል ለእስር የዳረጋቸው ዜጎች ብዛት 47 ሺህ፣ ከስራ የተባረሩት ደግሞ 120 ሺህ ያህል መድረሱንም ዘገባው ገልጧል፡፡
የቱርክ መንግስት ከከሸፈው መፈንቅለ መንግስት ጋር በተያያዘ የሚያስራቸውና ከስራ ገበታቸው የሚያፈናቅላቸው ዜጎች ቁጥር በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መምጣቱ አለማቀፍ ትችት እንደገጠመው የዘገበው ቢቢሲ በበኩሉ፣ አገሪቱ የአውሮፓ ህብረት አባል ለመሆን የጀመረቺውን ጥረት እያጓተተው እንደሚገኝም አመልክቷል፡፡

  በየመን በየ10 ደቂቃው አንድ ህጻን ይሞታል

      በጦርነት በፈራረሰችዋና የዓለማችን የከፋው ርሃብ ሰለባ በሆነቺው የመን የሚኖሩ 19 ሚሊዮን ያህል የአገሪቱ ዜጎች 1.1 ቢሊዮን ዶላር የሚገመት የአስቸኳይ ጊዜ ድጋፍ እንደሚያስፈልጋቸው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ሰሞኑን አስታውቋል፡፡
በዘንድሮው የፈረንጆች አመት 2017 የመናውያንን ከከፋ ጥፋት ለመታደግ የሚያስፈልገው የገንዘብ ድጋፍ 2.1 ቢሊዮን ዶላር ያህል እንደሆነ ያስታወሰው ተመድ፣ ከዚህ ገንዘብ ውስጥ ከአለማቀፉ ማህበረሰብ ማሰባሰብ የተቻለው 15 በመቶውን ያህል ብቻ መሆኑን ጠቅሶ፣ ዋና ጸሃፊው አንቶኒዮ ጉቴሬስም የመናውያንን ለመታደግ አለማቀፉ ማህበረሰብ ርብርብ እንዲያደርግ መጠየቃቸውን አመልክቷል፡፡
የዛሬይቱ የመን ሙሉ ትውልድ በአለማችን እጅግ የከፋው ርሃብ እየተጠቃ ነው ያሉት ጉቴሬስ፤3 ሚሊዮን ዜጎቿ ቤታቸውን ጥለው በተሰደዱባትና በጦርነት በፈራረሰቺው የመን የሚታየው ሰብዓዊ ቀውስ እየከፋ መሄዱን ገልጸዋል፡፡
በየመን በየአስር ደቂቃው ዕድሜው ከአምስት አመት በታች የሆነ አንድ ህጻን በመከላከል ሊድኑ በሚችሉ ምክንያቶች ሳቢያ ለህልፈተ ህይወት እንደሚዳረግ የጠቆሙት አንቶኒዮ ጉቴሬስ፤ አለማቀፉ ማህበረሰብና የሰብዓዊ ድጋፍ ተቋማት በተለይም ለየመናውያን ህጻናት ትኩረት መስጠት እንደሚገባቸው አመልክተዋል፡፡

 ካለፉት 3 አመታት ትርፉ ከፍተኛው ነው ተብሏል

      ያለፉትን ወራት በእሳት ፈጣሪው ምርቱ በጋላክሲ ኖት 7 ሳቢያ ቀውስ ውስጥ ተዘፍቆ የገፋው ታዋቂው የኤሌክትሮኒክስ አምራች ኩባንያ ሳምሰንግ፤ ባለፉት ሶስት አመታት ታሪኩ ከፍተኛው የተባለውን የ8.8 ቢሊዮን ዶላር የሩብ አመት ትርፍ ማስመዝገቡን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
የደቡብ ኮርያው ሳምሰንግ እስካለፈው መጋቢት ወር ባለው ያለፈው ሩብ አመት ከፍተኛ የተባለውን ትርፍ ሊያስመዘግብ የቻለው፣ የሚሞሪ ቺፕስ፣ የቴሌቪዥን ፍላት ስክሪን እና የሞባይል ስልክ ምርቶቹ በተጠቃሚዎች ዘንድ ያላቸው ተፈላጊነት በመጨመሩ ነው ተብሏል፡፡
ኩባንያው በቀጣይም ትርፋማነቱን ከፍ አድርጎ እንደሚዘልቅ ይጠበቃል ያለው ዘገባው፣ ለዚህም በምክንያትነት የተጠቀሰው ከሰሞኑ ለገበያ ያቀረባቸው የጋላክሲ ኤስ 8 እና ኤስ 8 ፕላስ የሞባይል ምርቶቹ በገበያው ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነት እያገኙ መምጣታቸው ነው መባሉን ገልጧል፡፡
ሳምሰንግ ባለፈው ጥቅምት ወር ላይ ለገበያ ያቀረበው የጋላክሲ ኖት 7 ምርቱ፣ ባትሪው ከፍተኛ ሙቀትና እሳት እየፈጠረ አደጋ ማስከተሉን ተከትሎ ህልውናውን ስጋት ላይ የሚጥል ፈተና ውስጥ ገብቶ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ ለደምበኞቹ ሽጧቸው የነበሩ 2.5 ሚሊዮን ያህል ምርቶቹን መልሶ መረከቡ ከፍተኛ ኪሳራ እንዳስከተለበትም አስታውሷል፡፡

የታጂኪስታን የመንግስት መገናኛ ብዙሃን ጋዜጠኞች፣ የአገሪቱን ፕሬዚዳንት ኢሞማሊ ራህሞንን የተመለከቱ ዘገባዎችን በሚሰሩበት ወቅት፣ ከስማቸው በፊት በእንግሊዝኛ 19 ቃላት ያሉትን ረጅም ማዕረጋቸውን አሟልተው እንዲጠሩ የሚያስገድድና ቅጣትን የሚያስከትል አዲስ ህግ መውጣቱ ተዘግቧል፡፡
የሰላምና የብሄራዊ አንድነት መስራች፣ የሃገሪቷ መሪ፣ የታጂኪስታን ሪፐብሊክ ፕሬዚዳንት፣ የተከበሩ ኢሞማሊ ራህሞን የሚል አማርኛ አቻ ያለውን የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሙሉ ማዕረግ ሳይጠራ ዘገባ የሚሰራ ጋዜጠኛ ህገወጥ ድርጊት እንደፈጸመ ተቆጥሮ ቅጣት እንዲጣልበት የሚደነግገው ህግ፣ ካለፈው ሳምንት ጀምሮ ተግባራዊ መደረጉን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ዋናው የአገሪቱ የቴሌቪዥን ጣቢያ ዜናዎችን በሚሰራበት ወቅት ይህንን ህግ ተግባራዊ ማድረግ መጀመሩን የጠቆመው ዘገባው፣ የፕሬዚዳንቱ ስም ከእነ ሙሉ ማዕረጋቸው በቴሌቪዥኑ ግርጌ በተንቀሳቃሽ ጽሁፍ መልክ ታይቶ ለማለቅ 15 ሰከንድ ያህል እንደወሰደም አመልክቷል፡፡
አስቂኙ ህግ ተግባራዊ መደረጉን ተከትሎ በማህበራዊ ድረገጾች መሳለቂያ ሆኖ መዝለቁን የጠቆመው ዘገባው፣ አንዳንድ አስተያየት ሰጪ የአገሪቱ ወጣቶችም፣ የፕሬዚዳንቱ ማዕረግ በጣም አጥሯልና ሊጨመርበት ይገባል ሲሉ መሳለቃቸው ተነግሯል፡፡
በሰብዓዊ መብቶች ጥሰት፣ በፕሬስ አፈና እና በመናገር ነጻነት አልቦነት ስሟ የሚጠራውን ታጂኪስታንን እ.ኤ.አ ከ1992 አንስቶ በማስተዳደር ላይ በሚገኙት የፕሬዚዳንቱ ዘልዛላ ማዕረግ ላይ ሊጨመሩ ይገባል በሚል በፌስቡክ ተጠቃሚዎች ከተሰነዘሩት አዳዲስ ማዕረጎች መካከልም፣ “የጨረቃው ሰው” እና “የአለሙ ሁሉ ፈጣሪ” የሚሉት ይገኙበታል፡፡

  የአሜሪካና የሰሜን ኮርያ ፍጥጫ ተባብሷል

      አለማቀፍ ውግዘት፣ ተደራራቢ ማዕቀብ፣ የማያባራ ዛቻና ማስጠንቀቂያ የኒውክሌርና የሚሳኤል ፕሮግራሟን ከማስፋፋትና ከማሳደግ በፍጹም እንደማይገታት በይፋ ስታውጅ የዘለቀቺው ሰሜን ኮርያ፣ በየሁለት ወሩ አንድ የኒውክሌር መሳሪያ ማምረት የምትችልበት አቅም ላይ መድረሷ ተዘግቧል፡፡
የአሜሪካ መንግስት የሰሜን ኮርያን የኒውክሌር ፕሮግራም አቅምና የደረሰበትን ደረጃ በተመለከተ በስውር ያስጠናውን ጥናት ጠቅሶ ኒውዮርክ ታይምስ እንደዘገበው፣ ሰሜን ኮርያ የኒውክሌር አቅሟን በተፋጠነ ሁኔታ በማሳደግ በየስድስት ሳምንቱ አንድ የኒውክሌር የጦር መሳሪያ ማምረት የምትችልበት ደረጃ ላይ ደርሳለች፡፡
የሰሜን ኮርያ እና የአሜሪካ ፍጥጫ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በከፍተኛ ሁኔታ እየተባባሰ መምጣቱን የጠቆመው ዘገባው፣ አሜሪካ በደቡብ ኮርያ ጦር ማስፈሯንና በምስራቃዊ የአገሪቱ ክፍል በመጪዎቹ ቀናት ውስጥ ስራ የሚጀምርና ታድ የሚል ስያሜ የተሰጠው የተራቀቀ ጸረ-ባላስቲክ ሚሳኤል መከላከያ ሲስተም ባለፈው ረቡዕ መትከል መጀመሯንም ገልጧል፡፡
ሰሜን ኮርያ በ11 አመታት ውስጥ ስድስተኛውን የኒውክሌር ሙከራ እንደምታደርግ ከሰሞኑ መዛቷን የጠቆመው ዘገባው፣ ይህን ተከትሎም ቻይና ሰሜን ኮርያ የኒውክሌር ሙከራውን እንዳታደርግ ያስጠነቀቀች ሲሆን፣ አሜሪካ በደቡብ ኮርያ በመትከል ላይ የምትገኘውን የሚሳኤል መከላከያም የአካባቢውን ውጥረተ ክፉኛ የሚያባብስ ስለሆነ በአፋጣኝ እንዲቆም ጠይቃለች፡፡

    የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር ከአማራ ብሔራዊ ክልል መንግስትና ከባህርዳር ዩኒቨርሲቲ ጋር በመተባበር ያዘጋጃቸውን ትልቅ የጉዞ መርሀ ግብር ምክንያት በማድረግ የግጥም ውድድር ጥሪ አቀረበ፡፡ የመወዳደሪያ ግጥሞቹ ይዘት በጥቅሉ የአባይን ወንዝና የአካባቢውን ስነ - ምህዳር፣ የጣና ሀይቅንና የገደማቱን ሁለንተናዊ ገፅታ፣ የክልሉን አጠቃላይ ማህበረሰብ ባህል እሴትና የመሳሰሉ ጉዳዮች ሊዳስሱ እንደሚገባ ማህበሩ ገልጿል፡፡ ግጥሞቹ በተጨማሪም የአካባቢ ጥበቃ ባህላችንን እንድናጤን እንዲሁም የመንከባከብ ባህላችንን የሚያጎለብቱ መልዕክቶችን የያዙ ቢሆኑ ይመረጣል ተብሏል፡፡ ለጥናቱ ዘርፍም አቅጣጫ ጠቋሚና በይዘታቸው ላቅ ያሉ እንዲሆኑ ለገጣሚያን ጥሪ ተላልፏል፡፡
ለውድድር የሚቀርቡ ግጥሞች፤ወጥና በሌሎች የህትመትና ተያያዥ ሚዲያዎች ያልታተሙና ያልቀረቡ መሆን እንዳለባቸው ታውቋል፡፡ ለንባብ እንዲመቹ በደንብ መተየብና ከሁለት ገፅ መብለጥ እንደሌለባቸው ያሳሰበው ማህበሩ፤ ከ1-3 ለወጡ አሸናፊዎች የገንዘብና የምስክር ወረቀት ሽልማት እንደሚኖር አስታውቋል። የሶስቱ አሸናፊዎች ግጥሞች፣ በጉዞ መርሃ ግብሩ በተለያዩ መድረኮች የሚቀርቡ ሲሆን አሸናፊዎች በነዚሁ መድረኮች በአካል ተገኝተው ሽልማቶቻቸውን እንደሚቀበሉ ተጠቁሟል፡፡ የግጥሞቹ ማስረከቢያ ጊዜም ከሚያዚያ 18 እስከ ሚያዚያ 28 ቀን 2009 ሲሆን ቦታውም በማህበሩ ዋና ፅ/ቤት እንደሆነ ታውቋል፡፡ 

 የእውቁ ደራሲና የግብርና ባለሙያ ዶ/ር ጌታቸው ተድላ “የህይወት ጉዞዬና ትዝታዎቼ በአገር ቤት” ክፍል ሁለት እና እቅድ 27፣ ሁለት መፅሐፎች በዛሬው ዕለት አምስት ኪሎ በሚገኘው የቅርስና ጥናት ጥበቃ ባለስልጣን ከረፋዱ 3፡30 ጀምሮ ይመረቃሉ፡፡ ከምረቃው ጎን ለጎንም በመጽሐፎቹ ዙሪያ ውይይቶችና ሃሳቦች ይንሸራሸራሉ ተብሏል፡፡
በተለይ “የህይወት ጉዞዬና ትዝታዎቼ በአገር ቤት” የተሰኘው መጽሐፋቸው ደራሲው ለስራ በተዘዋወሩባቸው በርካታ የአለም ክፍሎች ያዩዋቸውንና ያጋጠሟቸውን፣ እንዲሁም የኖሯቸውን የህይወት ተመክሮዎች በማራኪ ቋንቋ የተረኩበት ነው ተብሏል፡፡

  የዛሬና የመጪው ዘመን ወጣቶች በርካታ ጥራዝ መጻሕፍት ከመሸከም ይልቅ በአንድ ፍላሽ  (መረጃ መያዣ) በርካታ መጻሕፍትና መረጃ መያዝ ስለሚመርጡ ለዚህ የጊዜው አስገዳጅ ሁኔታ ዝግጁ መሆን አለብን ሲሉ በምክትል አስተዳደር ማዕረግ የኦሮሚያ የከተማ ልማትና ቤቶች ቢሮ ኃላፊ አቶ አቢይ አህመድ አሳሰቡ፡፡
ስፕሪንግ ኔቸር አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲና (አአዩ) አብረውት በጋራ የሚሠሩትን ተቋማት ለማመስገን ከትንት በስቲያ በሸራተን አዲስ ባዘጋጀው ስብሰባ ላይ በክብር እንግድነት የተገኙት አቶ አቢይ፣ በአሁኑ ወቅት በከፍተኛ ትምህርትና በምርምር ተቋማት የመጻሕፍት መደርደሪ ማሰስ ቀርቶ  በኢንተርኔት የኤሌክተሮኒክስ (ዲጂታል) መረጃ እየተተካ ስለሆነ ወደፊት ለዚህ ጊዜው ለጠየቀው ኢ-መጻሕፍት፣ ኢ-ጆርናልና ኢ-ዳታ ቤዝ መገኘት ተቋማት ምቹ ሁኔታ መፍጠር አለባቸው ብለዋል፡፡
ከ85 የከፍተኛ ትምህርትና ምርምር ተቋማት ለተገኙ ተሳታፊዎች ስፕሪንንገር ኔቸር በዚህ ዓመት የተመሠረተበትን 175ኛ ዓመት ለማክበር እየተዘጋጀ መሆኑን የጠቀሱት፤ ኢትዮጵያ ተወካይ  ሚ/ር ፓቫን ራመራካዛ፣ ደርጅታቸው፣ በኤሌክትሮኒክ (ዲጂታል) በኢ-ሪሶርስ፣ በዳታ ቤዝ፣ በኢ-መጻሕፍት፣ በኢ-ጆርናል ስለሚሰጠው  አገልግሎት ገለጻ አድርገዋል፡፡
ከአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ጋር የጠበቀ ትብብርና ግንኙነት እንዳላቸው የጠቀሱት ሚ/ር ራመራካሃ፣ ድርጅታቸው፣ ለአአዩ የአቅም ማጎልበቻ ሥልጠናዎች እንደሚሰጥና ድጋፍ እንደሚያደርግ ተናግረዋል፡፡
ስፕሪንገር ኔቸር፣ በቴክኖሎጂ፣ በሕክምና፣ በማህበራዊ ልማዶች፣ በሂማኒቲ፣… የተገኙ የምርምር ውጤቶችን ያዘጋጃል፣ ያትማል ያሉት ሚ/ር ራመራካሃ፣ ከኢትዮጵያ ጋር ብቻ ሳይሆን ከደቡብ አፍሪካ፣ ኬንያ፣ ናይጄሪያና ጋና የተገኙ የምርምር ግኝቶች የሚይዘጋጅና የሚያትም፣ እንዲሁም ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ መድረኮች በምርምር እንድትታውቅ ማድረግ የወደፊት ዕቅዳቸው መሆኑን ገልጸዋል፡፡
በዓለም ላይ ካሉ የታወቁ ለትምህርትና ለምርምር አገልግሎት የሚውሉ ሀብቶችና የኤሌክትሮኒክ ሪሶርሶችን ከሚያዘጋጀውና ከሚያትመው ስፕሪንገር ኔቸር ጋር የጠበቀ ግንኙነት እንዳላቸው የጠቀሱት በአአዩ ዋና የቤተመጻሕፍት ኃላፊ አቶ መስፍን ገዛኸኝ፣ አብረውት የሚሠሩት ድርጅቶች፤ ከሌሎች ተመሳሳይ ድርጅቶች ጋር በዋጋና በአቅርቦት ተወዳድሮ ተመራጭ ሲሆን፣ በዲፓርትመንቶችና በትምህርት ክፍሎች የተመረጡ ዲጂታል ሪሶርሶች ይገዛሉ ብለዋል፡፡  በአሁኑ ወቅት ለሚጠቀሙባቸው ጆርናሎች የአገልግሎት ክፍያ (ሰብስክራይብ) እንደሚያደርጉ የጠቀሱት አቶ መስፍን፣ ለ50 ያህል ዳታ ቤዞች እንደሚከፍሉ፣ ወደፊት ከስፕሪንገር ኔቸር ኢ-መጻሕፍት ለመግዛት ጥናት እያደረጉ መሆኑንና አአዩ ለትምህርት ማቴሪያሎች አንድ ሚሊዮን ዶላር ያህል እንደሚያወጣ ተናግረዋል፡፡
ለኢ- ሪሶርስ አጠቃቀም ያስፈልጋል፡፡ የአገሪቱ የኢንተርኔት አገልግሎት ደግሞ በጣም ደከማ ስለሆነ እንዴት ነው መጠም የሚቻለው ተብለው የተጠየቁት አቶ መስፍን፣ የኢንተርኔት አገልግሎት ደካማ መሆኑን አምነው፣ ተማሪዎች፣ ኢንተርኔት ባለጊዜ የተጠራቀሙ ሪሶርሶችን እንዲሚጠቀሙ ይደረጋል፡፡ ተማሪዎች መደርደሪያ ላይ መጻሕፍት እንደሚፈልግት ሁሉ፣ ከኢንተርኔት ውጪ፣ ማከማቻ ሰርቨሮች ላይ በተቀመጡ መጻሕፍት እንዲጠቀሙ ይደረጋል ብለዋል፡፡
ኃላፊው፣ ከግል ዩኒቨርሲቲዎች ጋር ስላላቸው ግንኙነት ተጠይቀው፣ እኛ የምናየው ተቋማትን ሳይሆን ተማሪዎች በሚማሩበት ጊዜ ሊያገኗቸው ስለሚገቡ ነገሮች ነው፡፡ የአስተዳደር ችግር ካልሆነ በስተቀር፣ ተማሪዎችም  ሆኑ በየተቋማቱ ያሉ ኃላፊዎች አሠራሩን ለመዘርገት ችግር የለባቸውም፡፡ አአዩ፣ ከቅድስት ማርያም፣ ከዩኒቲ፣ ከካሪፍት ቫሊ ዩኒቨርሲቲዎች ጋር እየሠራ ነው፡፡ ከሌሎችም ጋር የመግባቢያ ሰነድ ተፈራርመናል፡፡ ብዙዎቹ ዩኒቨርስቲዎች፣  አአዩ አገልግሎት ስለሚሰጣቸው ነው የድህረ ምረቃ ፕሮግራሞቻቸውን የጀመሩት በማለት አስረድተዋል፡፡