Administrator

Administrator

          የአፍሪካ ዋንጫ ለማዘጋጀት  ጊዜው የኢትዮጵያ እንደሆነ ሱፐር ስፖርት ዘገበ፡፡ የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ሊቢያን በመተካት በ2017 እ.ኤ.አ ላይ 31ኛው የአፍሪካ ዋንጫን ለማስተናገድ እንደሚፈልግ ያስታወቀው ከ2 ሳምንታት በፊት ሲሆን በኦፊሴላዊ ደረጃ ለካፍ ማመልከቻ ስለማስገባቱ ግን የታወቀ ነገር የለም፡፡ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን  ሊቢያን በመተካት  አዘጋጅነቱን ለሚያመለክቱ አገራት የሰጠው የግዜ ገደብ  3 ሳምንታት ይቀሩታል፡፡ ኢትዮጵያ አመልክታ ተቀባይነት ካገኘች ለ4ኛ ጊዜ የምታስተናግደው የአፍሪካ ዋንጫ ይሆናል፡፡
ከዚህ ጋር በተያያዘ በወጡ ዘገባዎች ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫ መስራች እንደነበረች በማስታወስና ባለፉት 3 ዓመታት ለ31 ዓመታት ከውድድሩ የራቀችበትን ሁኔታ በቀየረ የእግር ኳስ ለውጥ ላይ እንደምትገኝ በመግለፅ አዘጋጅነቱን ብታገኝ ይገባታል ብለዋል፡፡ ከሁለት ሳምንት በፊት በአፍሪካ የኢኮኖሚ፤ የፖለቲካ እና ዓለም አቀፍ ዲፕሎማሲ መናሀርያነት የምትጠቀሰው  ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫን ለማዘጋጀት ፍላጎት እንዳላት ገልፆ የዘገበው ቢቢሲ ነበር፡፡ በወቅቱ በአዲስ አበባና  በባህርዳር  ሁለት ዝግጁ ስታድዬሞች መኖራቸውን ለቢቢሲ የተናገሩት የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ፕሬዚዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ ሲሆኑ ፤ በሌሎች የአገሪቱ ክልሎች ደረጃቸውን የጠበቁ ስታድዬሞች ግንባታ እየተጠናቀቀ መሆኑን በመጥቀስ ውድድሩን ለማስተናገድ ዝግጁ ነን ብለዋል፡፡ ኢትዮጵያ የፊፋ እና የኦሎምፒክ ስታንዳርድን የሚያሟላ እና 60ሺ ተመልካች የሚያስተናግድ ብሄራዊ ስታድዬም በአዲስ አበባ ለመስራት እቅድ እንዳላት የገለፀው የሱፕር ስፖርት ዘገባ ሶስት አፍሪካ ዋንጫዎችን ያስተናገደው የአዲስ አበባው ብሄራዊ ስታድዬምም ከፍተኛ እድሳት ተደርጎለት ለመስተንግዶ ሊደርስ እንደሚችል ጠቅሷል፡፡
በ2017 እኤአ ላይ 31ኛውን አፍሪካ ዋንጫ እንድታዘጋጅ  ተመርጣ የነበረችው ሊቢያ  መስተንግዶውን የተወችው በአገሪቱ በቂ ሰላምና መረጋጋት አለመስፈኑ በፈጠረባት እክል እንደሆነ ያስታወቀችው ከሶስት ሳምንት በፊት ነበር፡፡ ይህን ተከትሎ የአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌዴሬሽን ካፍ ባወጣው መግለጫ  እንዳመለከተው ሊቢያ ለውድድሩ የሚያስፈልጉ ስታድዬሞችን በመገንባት እንደማይሳካላት እና በአስተማማኝ ፀጥታ ውድድሩን ለማካሄድ እንደማትችል አረጋግጫለሁ በማለት ለአባል ፌደሬሽኖቹ ምትክ አዘጋጅን ለማግኘት ጥሪ አቅርቧል፡፡
ሱፕር ስፖርት  ጊዜው ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫን የምታዘጋጅበት ነው በሚል ርእስ በሰራው ዘገባ በኢትዮጵያ ስፖርት ዙርያ ባሉ ባለድርሻ አካላት የተሰጡ አስተያየቶች የመስተንግዶውን ፍላጎት አድርገውታል፡፡ ለሱፕር ስፖርት በሰጡት አስተያየት አፍሪካ ዋንጫ ለማዘጋጀት ያለንን ፍላጎት መላው ኢትዮጵያዊያንና እና የአፍሪካ አገራት ከደገፉት ይሳካል ያሉት የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ  ናቸው፡፡
‹‹የአፍሪካ ዋንጫን ማዘጋጀት፤ በአህጉሪቱ እግር ኳስ ያለንበትን ከፍታ ለማሳየት እድል ይፈጥራል›› ብሎ የተናገረው ደግሞ ኤልሻዳይ ነጋሽ የተባለው ታዋቂ ጋዜጠኛ ነው፡፡ አዲስ አበባ በአፍሪካ የባቡር ሜትሮ ኔትዎርክ ካላቸው ጥቂት ከተሞች አንዷ መሆኗን፤ በመሰረተ ልማት እየተጠናከረች መምጣቷን ለሱፕር ስፖርት የገለፀው ኤልሻዳይ  ፤ የፓን አፍሪካኒዝም መዲና በሆነች ከተማ ውድድሩ መዘጋጀቱ ተገቢ ነው በማለት ድጋፉን ገልጿል፡፡ ‹‹የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ለውድድሩ አዘጋጅነት ፍላጎት ማሳየቱን ስሰማ በጣም ጉጉት ፈጥሮብኛል፡፡ ለእኛ ተጨዋቾች አፍሪካ ዋንጫን በሜዳችን በደጋፊችን ፊት መጫወት ከፍተኛ ሞራል እና መነቃቃትን የሚፈጥር ይሆናል፡፡ ሁሉም ኢትዮጵያውያን ፌደሬሽኑን እና መንግስትን በሙሉ አቅም መደገፍ አለባቸው፡፡  በዚህም አፍሪካ ዋንጫ የማዘጋጀት ህልምን ማሳካት ይቻላል፡፡›› በማለት ለሱፕር ስፖርት የድጋፍ አስተያየት ያቀበለው የብሄራዊ ቡድኑ ተጨዋች አበባው ቡጣቆ ነው፡፡ የብሄራዊ ቡድኑ ወሳኝ የአማካይ መስመር ተሰላፊ የሆነው ሽመልስ በቀለ በበኩሉ ‹‹አስደሳች  እና ታላቅ ዜና ነው፡፡ ኢትዮጵያ የአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅነት እንደሚሳካላት ተስፋ አደርጋለሁ፡፡   አዘጋጅ ሆነች የሚለውን ዜና በጉጉት እጠብቃለሁ፡፡›› በማለት ተናግሯል፡፡
ከ29 የአፍሪካ ዋንጫዎች በአስሩ ላይ መሳተፍ የቻለችው ኢትዮጵያ ለሶስት ጊዜያት የአፍሪካ ዋንጫ አዘጋጅ ነበረች፡፡ በ1962 ውድድሩን በማዘጋጀት ሻምፒዮን ስትሆን እንዲሁም በሌሎች ባዘጋጀቻቸው ሁለት የአፍሪካ ዋንጫዎች በ1968 እኤአ ላይ አራተኛ ደረጃ እና በ1976  እኤአ ደግሞ ከመጀመርያው ዙር ከውድድሩ ተሰናብታለች፡፡ ከኢትዮጵያ ሌላ የውድድሩን አዘጋጅነት ለመረከብ ፍላጎታቸውን የገለፁት አገራት አምስት ደርሰዋል፡፡ የመጀመርያዋ ኬንያ ስትሆን የአፍሪካ ዋንጫውን ከጐረቤቶቿ ታንዛንያ፣ ኡጋንዳ እና ሩዋንዳ ጋር በጣምራ የማዘጋጀት ጥያቄ አቀርባለሁ እያለች ነው፡፡ የምእራብ አፍሪካዋ ጋና እና የደቡብ አፍሪካዋ ዛምቢያም አዘጋጅነቱን እንደሚፈልጉ ሲያስታውቁ በመጨረሻም ለመስተንግዶ ፍላጎቷን እያሳየች የመጣችው አልጄርያ ናት፡፡ 16 ብሄራዊ ቡድኖች የሚሳተፉበትን የአፍሪካ ዋንጫ ለማዘጋጀት ዓለም አቀፍ ደረጃን የሚያሟሉ ስታድዬሞች፤ የሆቴል እና የትራንስፖርት መሰረተልማቶች እጅግ ወሳኝ ሲሆኑ እስከ 55 ሚሊዮን ዶላር በጀት እንደሚያስፈልግም ይገመታል፡፡

       በሳምንቱ መግቢያ ላይ በሮም ከተማ በሚገኘው ስታድዮ ኦሎምፒኮ በተዘጋጀው የዓለም ሃይማኖቶች ሁሉን አቀፍ የሰላም ግጥሚያ ላይ የዋልያዎቹ የቀድሞ ዋና አምበል ደጉ ደበበ ተሳተፈ፡፡ የእግር ኳስ ግጥሚያውን በክብር እንግድነት የታደሙት የቫቲካኑ ጳጳስ ፍራንሲስ ሲሆኑ፤ የሰው ልጆች በጭራሽ ሰይፍ የማይማዘዙበት ዘመን እንዲመጣ ሃይማኖት እና ስፖርት ከፍተኛ አስተዋፅኦ አላቸው ሲሉ ተናግረዋል፡፡
በዓለም እግር ኳስ የታዩ ከ50 በላይ የአሁን ዘመንና የቀድሞ እግር ኳስ ተጨዋቾች በሰላም ግጥሚያው ተሳታፊ ነበሩ፡፡ ለሁለቱ ቡድኖች ተሰላፊዎችን የመረጡት አዲሱ የአርጀንቲና ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ጌራርዶ ታታ ማርቲኖ እና የአርሰናሉ አሰልጣኝ አርሰን ቬንገር ናቸው፡፡ በሁለቱ ቡድን የተመረጡ ተጨዋቾች በግጥሚያው የሁለት ግብረሰናይ ተቋማትን የሚወክሉ ማልያዎችን ለብሰው ተሳትፈዋል፡፡ በሃቪዬር ዛኔቲ አምበልነት የሚመራው ፑፒስ እና  በጂያንሉጂ ቡፎን የሚመራው ስኮላስ ናቸው፡፡
በጨዋታው ተሳታፊ ከሆኑት የጊዜያችን ምርጥ ተጨዋቾች መካከል ሊዮኔል ሜሲ፤ ኤቶና ፒርሎ እንዲሁም ከአንጋፋዎች ዲያጐ ማራዶና፣ ዴልፒዬሮና ሮበርቶ ባጂዮ ይገኙበታል፡፡
 የዓለም ህዝቦችን አንድነት ለማጠናከር ጉልህ ሚና እንደሚኖርበት የታመነበት የሰላም ግጥሚያው በመላው ዓለም ሰላምን ለማስፋፋት ቅስቀሳ የተደረገበት ሲሆን በከፋ አደጋ ላይ ለሚገኙ የዓለም ህፃናት ድጋፍ የሚሆን ገቢም ተሰባስቦበታል፡፡  የሰላም ግጥሚያውን ስፖንሰር ካደረጉት መካከል ዓለም አቀፉ እግር ኳስ ማህበር ፊፋ፤ የዓለም ምግብ ፕሮግራም ፋኦ፤ የመኪና አምራቹ ኩባንያ ፊያት እና ሌሎች ትልልቅ ዓለም አቀፍ ኩባንያዎች ይጠቀሳሉ፡ በመላው ዓለም በአምስት አህጉራት በቴሌቭዥን የቀጥታ ስርጭት የነበረው ዝግጅቱ በጣሊያን፤ በኦስትርያ፤ በፈረንሳይ እና በጀርመን ልዩ  ትኩረት እንዳገኘም ታውቋል፡፡
በዓለም ሰላም እንዲሰፍን ለመቀስቀስ የተዘጋጀውን የእግር ኳስ ልዩ  ግጥሚያ በማስተባበር በቦነስ አይረስ የሚገኘውን ፑፒ ፋውንዴሽን መስራች የቀድሞው አርጀንቲናዊ ተጨዋች ሃቪዬር ዛኔቲ ጉልህ አስተዋፅኦ አበርክቷል፡፡
  ሃቪዬር ዛኔቲ  በአርጀንቲና ብሄራዊ ቡድን አምበልነት ያገለገለ፤ በሚላን ከተማው ክለብ ኢንተር ሚላን ለ19 ዓመታት የተጫወተ እና አሁን የክለቡ ምክትል ፕሬዝዳንት ሆኖ እየሰራ ነው፡፡

       በኢትዮጵያ እናቶች በአማካይ በሕይወት ዘመናቸው የሚወልዱት ልጅ መጠን በ2005 /5.4/ በ2011 /4.8/ (DHS)› ሲሆን በ2015 ይህን ቁጥር ወደ /4.4/ ዝቅ የማድረግ እቅድ ተይዞአል ፡፡ በዚህ ዙሪያ በተለይም ቋሚና የረዥም ጊዜን የመከላከያ ዘዴዎች ጠቀሜታን እና የጎንዮሽ ጉዳታቸውን ዶ/ር ነጋ ተስፋው የጽንስና ማህጸን ሕክምና እስፔሻሊስት አብራርተዋል፡፡ ዶ/ር ነጋ  በአሁኑ ወቅት በማሪስቶፕስ ኢንተርናሽናል ኢትዮጵያ የጥራትና የህክምና አገልግሎት ዳይሬክተር ሆነው ይሰራሉ፡፡
ጥ/ የረዥም ጊዜ የእርግዝና መከላከያዎች ሲባል ምን ማለት ነው?
መ/ የእርግዝና መከላከያዎች የተለያዩ ናቸው፡፡ በተወሰነ የጊዜ እርቀት ወይንም በየእለቱ ከሚወሰዱት በኪኒን መልክ እና በመርፌ ከተዘጋጁት ውጪ ለረዥም ጊዜ እንዲሁም በቋሚነት እርግዝናን ለመከላከል የሚያስችሉ ዘዴዎች አሉ፡፡ የረጅም ጊዜ የሚባሉት በማህጸን ውስጥ እስከ 12/ አመት ድረስ መቀመጥ የሚችል (IUD) ወይንም ሉፕ እና በክንድ ቆዳ ስር እስከ አምስት አመት ድረስ በመቆየት ያልተፈለገ እርግዝናን መከላከል የሚችያስችል የህክምና ዘዴ ነው፡፡ እነዚህ ሁለቱም መከላከያዎች 99 % ያህል አስተማማኝ የእርግዝና መከላከያዎች ሲሆኑ ሕክምናው የሚሰጠውም ለሴቶች ነው፡፡
ጥ/ (IUD)  ሉፕ የተባለው የረዥም ጊዜ የእርግዝና መከላከያ በማህጸን ውስጥ ለ12/አመት ያህል ሲቆይ ችግር አያመጣም?
መ/ (IUD)  ሉፕ ለረጅም ጊዜ አገልግሎት ላይ የሚውል በመሆኑ እንደመርፌ ወይንም እንክብል በየጊዜው ውሰዱኝ የማይል እና ጊዜውን በትክክል ባለመጠበቅ ምክንያት ችግር የሚያስከትል አይደለም፡፡ ምናልባትም ሕክምናው በተሰጠ ለመጀመሪያዎቹ የሶስት ወራት የወር አበባ መዛባት ሊያስከትል ቢችልም ይህም ጊዜ ሳይፈጅ የሚስተካከል በመሆኑ ምንም አያሳስብም፡፡ በማህጸን ውስጥ ለረጅም ጊዜ ወይንም እስከ 12/አመት ድረስ በመቆየቱም የመመረዝ ወይንም የመቆሸሽ እድል የማይገጥመው ሲሆን በየመሀሉ ማውጣት የሚያስፈልገው አይደለም፡፡ ተጠቃሚዋ በፈለገችው ጊዜ እንዲወጣ ከማድረግ በስተቀር እስከ12/ አመት ድረስ ካለምንም ችግር ሊቆይ የሚችል አስተማማኝ የመከላከያ ዘዴ ነው፡፡ ..ህ.... ሉፕ ቀላል የሆነ የመከላከያ ዘዴ ሲሆን ለተጠቃሚዎችም ምቹ የሆነ እና ከባድ የጤና ችግር የማያስከትል ተስማሚ የሆነ የህክምና ዘዴ ነው፡፡
ጥ/ (IUD)   ሉፕ የተባለው የእርግዝና መከላከያ አንዳንዴ እርግዝናን ሳይከላከል ከልጅ ጋር አብሮ ይወለዳል?
መ/ በመጀመሪያ ደረጃ የረጅም ጊዜ የእርግዝና መከላያ (IUD)   ሉፕ 99 % ያህል እርግዝናን የመከላከል አቅም ያለው ስለሆነ እርግዝናው ይከሰታል ተብሎ አይጠበቅም፡፡ አንዳንድ ጊዜ ግን ከኑሮ ሁኔታ ወይንም የግብረስጋ ግንኙነቱ ባህርይ በሚፈጥረው ተገቢ ያልሆነ እንቅስቃሴ እርግዝናው ቢከሰት እርግዝናው ጊዜው ሳይገፋ ክሩ የሚታይ ከሆነ ሉፑን በቀላሉ ስቦ ማውጣት ይቻላል፡፡ምናልባት ትኩሳት ወይንም የደም መፍሰስ ቢያጋጥም ግን ወደሐኪም በመሔድ መታየት ያስፈልጋል፡፡  ሳይታወቅ እርግዝናው የገፋ እና (IUD)    ሉፑም ክሩ የማይታይ ከሆነ ግን ከልጁ ጋር አብሮ ቢወለድ ምንም ጉዳት አያስከትልም፡፡ በአጠቃላይ ግን (IUD)    ሉፕ በማህጸን ውስጥ በሚቀመጥበት ጊዜ የሚሰጥ የህክምና ባለሙያዎች ምክር ስለሚኖር ያንን በትክክል ተግባራዊ ማድረግ ከተጠቃሚዎች ይጠበቃል፡፡
ጥ/ ቋሚ የእርግዝና መከላከያዎች ምን አይነት ናቸው?
መ/ ቋሚ የሚባለው የእርግዝና መከላከያ  በቀዶ ሕክምና ለሴቷም ሆነ ለወንዱ የሚሰጥ የመከላከያ ዘዴ ነው፡፡  ቋሚ የሚባለው የእርግዝና መከላከያ ዘዴ በተለያየ የጋብቻ ሁኔታ ፣የስራ መስክ ፣የእድሜ ክልልና የኑሮ ሁኔታ ላይ የሚገኙ ተጨማሪ ልጅ ለመውለድ የማይፈልጉ ሴቶችና ወንዶች የሚመርጡት ዘመናዊ ዘዴ ነው፡፡ ይህ የቤተሰብ እቅድ ዘዴ ለወንዶችም ሆነ ለሴቶች በቀላል የቀዶ ሕክምና የሚሰጥ ፣ ለሕይወት ዘመን በቋሚነት እርግዝናን የሚከላከል አስተማማኝና በጤና ላይ ምንም ጉዳት የማያስከትል ነው፡፡ ለሴቷ የሚደረገው ቋሚ የእርግዝና መከላከያ ዘዴ የዘር መተላለፊያውን ቱቦ በመቋጠር ሲሆን የወንዱ ቋሚ የእርግዝና መከላከያ ዘዴ የወንዱ የዘር ፈሳሽ መተላለፊያን በመቋጠር እርግዝናን በቋሚነት መከላከል የሚያስችል ዘዴ ነው፡፡
ጥ/ ከቀዶ ሕክምናው በሁዋላ ተጠቃሚዎች ምን ጥንቃቄ ሊያደርጉ ይገባል?
መ/ ቀዶ ሕክምናው በጣም ቀላል በመሆኑ ምክንያት ከጥቂት ቆይታ በሁዋላ አገልግሎቱን ያገኙ ሁሉ ወደቤታቸው ይሄዳሉ፡፡ በተለይም ሴቶች ከሆኑ ለሁለት ቀናት ያህል በቤታቸው ከባድ ስራን ከመስራት እንዲቆጠቡ እና በቂ እረፍት እንዲያደርጉ ይመከራል፡፡ ሴቶች ለአንድ ሳምንት ወይንም ቁስሉ እስኪድን ድረስ ከግብረስጋ ግንኙነት መታቀብ ይኖርባቸዋል፡፡ ወንዶችን በሚመለከት ከቀዶ ሕክምናው በሁዋላ እንደሴቶቹ ለሁለት ቀናት ያህል በቂ እረፍት ማድረግ የሚገባቸው ሲሆን የግብረስጋ ግንኙነትን በሚመለከት ግን ከቀዶ ሕክምናው በሁዋላ ለሶስት ወራት ያህል የማስረገዝ እድል ስለሚኖር  መታ ቀብ፣ ሚስትየዋ ሌላ ዘዴ እንድትጠቀም ማድረግ ወይንም ኮንዶም ሁልጊዜና በአግባቡ መጠቀም ያስፈልጋል፡፡
ጥ/    አገልግሎቱን ያገኙ ሴቶችም ሆኑ ወንዶች ተመልሰው ወደጤና ድርጅት መሄድ ያስፈልጋቸዋልን?  
ሴቶች
* ከፍተኛ ትኩሳት፣
* በታችኛው የሆድ ክፍል ከባድ ሕመም፣
* የቁስሉ እብጠት ቅላትና መመርቀዝ.. መምገልና መድማት..  የሚያዩ ከሆነ በፍጥነት ወደሕክምናው ተቋም መሄድ ያስፈልጋቸዋል፡፡
ወንዶች
* ቀዶ ሕክምናውን ካደረጉ ከጥቂት ቀናት በሁዋላ በቀዶ ሕክምናው ቦታ ላይ እብጠት ከተፈጠረ፣
* ቁስሉ ከመድረቅ ይልቅ የማመርቀዝ ፣የመድማት ወይም የመምገል ምልክት ካሳየ ወደ ሕክምና ተቋም መሔድ ይጠበቅባቸዋል፡፡
ጥ/ ቋሚ የእርግዝና መከላከያ ምን ያህል ተጠቃሚ አለው?
መ/በአለም አቀፍ ደረጃ ሁለቱም ማለትም ወንዶችም ይሁኑ ሴቶች በከፍተኛ ሁኔታ ተጠቃሚ  ሆነው ይታያሉ፡፡ በአገራችን ግን እስከአሁን በአለው ልምድ ተጠቃሚው በአብዛኛው መርፌውን የሚመርጥ የነበረ ቢሆንም አሁን ግንቋሚ የእርግዝና መከላከያ ዘዴው ከውሳኔ በደረሱ ሰዎች ዘንድ በስፋት እየተለመደ እና በስራ ላይ እየዋለ ያለ ነው፡፡ ይህ ያልተፈለገ የእርግዝና መከላከያ ዘዴ ሁለቱ ጥንዶች ተስማምተው ወይንም በግልም ቢሆን በእርግጠኝነት በቂ ልጅ ስለአለኝ ወደፊት ልጅ መውለድ አልፈልግም ከሚል ውሳኔ ላይ እስከደረሱ ድረስ ደስተኛ የሆነ ሕይወትን ለመምራት የሚያስችል የእርግዝና መከላከያ ዘዴ ነው፡፡
ጥ/ ቋሚ የእርግዝና መከላከያ ጉዳት አለውን?
 መ/ በሕክምናው ዘዴ የሚደርስ ምንም አይነት ጉዳት የለም፡፡ ወንድም ሆነ ሴት የቋሚ የእርግዝና መከላከያ እንዲወስዱ በሚወስኑበት ጊዜ ግን መጠንቀቅ ያለባቸው ነገር አለ፡፡
* በጊዜያዊ የኑሮ ሁኔታዎች ተገፋፍቶ፣
* በትዳር ጉዋደኛ አሳማኝነት ወይንም ግፊት ብቻ ተመርቶ፣
* ስሜትን ወይንም የእራስን ፍላጎት በደንብ ሳያዳምጡ፣
* ከሚመለከተው ቅርብ ከሆነው የትዳር ጉዋደኛ ጋር በትክክል ተወያይተው ሳይወስኑ፣
* በአጠቃላይም ሁኔታዎችን በትክክል ሳያመዛዝኑ ...ወዘተ
በዚህ መልክ እርምጃ በአካልዎ ላይ ከወሰዱ በእርግጥ ውጤቱ የሚጸጽት ሊሆን ይችላል፡፡ ከዚህ በተረፈ ግን በሁኔታው አምነው እርምጃ ከወሰዱ ሕክምናው ቀላል እና ከማንኛውም አይነት የኑሮ ሁኔታ ወይንም ከፍቅር ግንኙነት የማያግድ መሆኑን ባለሙያዎችም ሆኑ ተጠቃሚዎች የሚመሰክሩት ነው፡፡ ቋሚና የረዥም ጊዜ የእርግዝና መከላከያዎች አስተማማኝ እና ለተጠ ቃሚዎች ተስማሚ በመሆናቸው ህብረተሰቡ ይህንን ተረድቶ አስፈላጊ በሆነ ጊዜ  እንዲጠ ቀምበት ይመከራል፡፡

*    ጋዛን መልሶ ለመገንባት 6 ቢሊዮን ዶላር ያስፈልጋል
*    እስራኤል ለጦርነቱ 2. 3 ቢሊዮን ዶላር አውጥታለች

ለሰባት ሳምንታት ያህል ከወደ እስራኤል ቀን ከሌት ሲሰነዘርባት በቆየው አሰቃቂ ድብደባ አሳር መከራዋን ስታይ የቆየችው የፍልስጤሟ ጋዛ፣ ከቀናት በፊት በተደረሰው የተኩስ አቁም ስምምነት ለጥቂት ጊዜም ቢሆን እፎይ ብትልም፣ ድብደባው ያደረሰባት ጥፋት ግን እጅጉን የከፋና በቀላሉ የሚሽር አይደለም፡
በሁለቱ ሃይሎች መካከል የተፈጠረው ግጭት ለ70 እስራኤላውያን ሞት ምክንያት መሆኑ እንዳለ ሆኖ፣ ግጭቱ እጅግ የከፋ ሰብዓዊና ኢኮኖሚያዊ ጥፋት ያስከተለው ግን፣ በፍልስቴም ላይ መሆኑን የኣለማችን መገናኛ ብዙሃን እየመሰከሩ ይገኛሉ፡፡
ግጭቱ ለህልፈተ ህይወት ከዳረጋቸው 2ሺህ በላይ ፍልስጤማውያንን መካከል አብዛኞቹ ጨቅላ ህጻናት ሰለመሆናቸው የዘገበው ሲኤንኤን፣ ለሳምንታት ስትደበደብ የቆየችው ጋዛ እንዳታገግም ሆና መፈራረሷንና የደረሰባት ኢኮኖሚያዊ ቀውስም እጅግ የከፋ እንደሆነ ገልጧል፡፡
በእስራኤል ጥቃት የፈራረሰችዋን ጋዛ መልሶ ለመገንባት ከፍተኛ ገንዘብ እንደሚጠይቅ የጠቆመው ሲኤንኤን፣ መልሶ ግንባታውን በተገቢው መንገድ ለማከናወን እስከ 6 ቢሊዮን ዶላር የሚደርስ የገንዘብ  እንደሚያስፈልግ ገልጧል፡፡የተባበሩት መንግስታት ድርጅትና አጋሮቹ በጋዛ ለሚከናወኑ የሰብዓዊ መልሶ ማቋቋም ስራዎች ተጨማሪ 367 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስፈልግና፣ ከዚህ ገንዘብ ውስጥም ከግማሽ በላይ የሚሆነው የጥቃቱ ሰለባ የሆኑ ከ500ሺህ በላይ የጋዛ ነዋሪዎችን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ፤ የተቀረው ገንዘብም ለቤቶች ግንባታ፣ ለውሃና ንጽህናና ለትምህርት ተቋማት ግንባታ እንደሚውል ገልጠዋል፡፡
ኦክስፋም በበኩሉ በጋዛ ነዋሪዎች ላይ የደረሰው የመሰረተ ልማት አውታሮች ውድመት፣ በአለማችን ባለፉት 20 አመታት ከተከሰቱ መሰል ውድመቶች ሁሉ ባደረሰው ቀውስ ከፍተኛነት ወደር እንደማይገኝለት ገልጧል፡፡ ከ15 በላይ ሆስፒታሎች እና በጋዛ ብቸኛው የነበረው የሃይል ማመንጫ፣ ከእስራኤል በደረሰባቸው የድብደባ ጥቃት ሙሉ ለሙሉ መፈራረሳቸውንም ተናግሯል፡፡
በጋዛ እስካለፈው ነሃሴ 3 ቀን ድረስ ከ10    ሺህ 600 በላይ መኖሪያ ቤቶች መውደማቸውን የጠቆመው የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የልማት ፕሮግራም፣ የፈራረሱትን ቤቶች መልሶ የመገንባቱ ስራ እጅግ ፈታኝ እንደሚሆንና ምናልባትም አራት አመታትን ያህል ጊዜ ሊፈጅ እንደሚችል አስታውቋል፡፡
የእስራኤል የታክስ ባለስልጣን በበኩሉ፣ ከሃማስ በተሰነዘሩ ጥቃቶች የወደሙ የአገሪቱ ቤቶችን ቁጥር በተመለከተ ተጨባጭ መረጃ ባይኖርም፣ የመሰረተ ልማት አውታሮችን መልሶ ለመገንባት ግን 11 ሚሊዮን ዶላር ያህል ወጪ እንደሚጠይቅ አስታውቋል፡፡
የእስራኤል መንግስት የንብረት ውድመት ለደረሰባቸው ዜጎቹ ማካካሻ ገንዘብ እየሰጠ እንደሚገኝ የጠቆመው የሲኤንኤን ዘገባ፣ ከፍተኛ የመሰረተ ልማት አውታሮች ውድመት በደረሰባት የሰሜን እስራኤሏ ከተማ የአሽዶድ ነዋሪዎችን ጨምሮ፣ 3ሺህ 700 ያህል የአገሪቱ ዜጎች ለመንግስት የማካካሻ ገንዘብ ጥያቄ ማመልከቻ ማቅረባቸውንና ከግማሽ በላይ የሚሆኑትም ለመኖሪያ ቤት ውድመት ያመለከቱ መሆናቸውን ገልጧል፡፡
ግጭቱ በእስራኤል የቱሪዝም ገቢ ላይ ከፍተኛ ተጽዕኖ መፍጠሩን፣ ምርታማነት ላይ ቅናሽ እንዲፈጠር ማድረጉንና ይህም የሆነው በርካታ የአገሪቱ ሰራተኞች የሮኬት ጥቃትን በመፍራት ስራ አቋርጠው በመኖሪያ ቤቶቻቸው በመደበቃቸው እንደሆነም አስረድቷል፡፡
እስራኤል ለሰባት ሳምንታት ያህል በጋዛ ላይ በሰነዘረችው ጥቃት ያወጣችውን አጠቃላይ ወታደራዊ ወጪ በተመለከተ ይፋዊ መረጃ ባትሰጥም፣ የአገሪቱ መገናኛ ብዙሃን ግን ወጪው እስከ 2 ነጥብ 3 ቢሊዮን ዶላር ይደርሳል እያሉ ነው፡፡

በአመት 3.6 ሚ. ዜጎች በሙስና ሰበብ ለህልፈተ ህይወት ይዳረጋሉ

በድሃ ሃገራት በአመት 1 ትሪሊዮን ዶላር የሚገመት ገንዘብ በሙስና ተመዝብሮ ከአገር እንደሚወጣና በአንድ አመት ጊዜ ውስጥም በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች በሙስና ሰበብ ለህልፈተ ህይወት እንደሚዳረጉ አንታይፖቨርቲ ኦርጋናይዜሽን ዋን የተባለ ተቋም ያወጣውን ሪፖርት ጠቅሶ ቢቢሲ ዘገበ፡፡
በድሀ አገራት የሚታየውን የከፋ ድህነት ለመቅረፍ ባለፉት ሁለት አስርት አመታት ሲደረጉ የነበሩ አበረታች ጥረቶች በሙስና ሳቢያ እየተደናቀፉ እንደሚገኙ የጠቆመው ዘገባው፣ በአገራቱ በከፍተኛ ሁኔታ በመስፋፋት ላይ በሚገኘው ሙስና ሳቢያ በየአመቱ ከፍተኛ መጠን ያለው ገንዘብ ተመዝብሮ እንደሚወጣና ዜጎችም ለህልፈተ ህይወት እየተዳረጉ እንደሚገኙ ገልጧል፡፡
ሙስና በደሃ የዓለማችን አገራት ከበሽታዎችና ከተፈጥሮ አደጋዎች በበለጠ ሁኔታ የኢኮኖሚና የሰብዓዊ ቀውስ እየፈጠረ እንደሚገኝ የገለጸው የተቋሙ ሪፖርት፣ ድርጊቱ የግል ኢንቨስትመንትን የሚያደናቅፍ፣ የኢኮኖሚ እድገትን የሚገታና የንግድ እንቅስቃሴ ወጪዎችን ያለአግባብ የሚያንር ከመሆኑ በተጨማሪ ፖሌካዊ አለመረጋጋት እንዲፈጠር ያደርጋል ብሏል፡፡በማደግ ላይ ያሉ አገራት የገንዘብ ሃብት በሙስና እየተመዘበረ ከአገር እንዲወጣ መደረጉ፣ የአገራቱ መንግስታት ለጤና እንክብካቤ፣ ለምግብ ዋስትናና ለሌሎች መሰረታዊ መሰረተ ልማቶች ማስፋፊያ በቂ በጀት እንዳይመድቡ እንቅፋት ስለሚፈጥር፣ በአገራቱ በየአመቱ በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ ዜጎች፣ በተለይ ደግሞ በርካታ ቁጥር ያላቸው ህጻናት ለህልፈተ ህይወት እንደሚዳረጉ ሪፖርቱ ገልጧል፡፡ከሰሃራ በታች በሚገኙ የአፍሪካ አገራት ሙስናን ማጥፋት ቢቻል፣ በየአመቱ 10 ሚሊዮን ተጨማሪ ህጻናትን የትምህርት እድል ተጠቃሚ ማድረግ፣ ለተጨማሪ 500 ሺህ የአንደኛ ደረጃ መምህራን ደመወዝ መክፈል እንዲሁም ከ11 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑ ሰዎችም የጸረ ኤች ኤቪ ኤድስ መድሃኒት በአግባቡ ማዳረስ ይቻል እንደነበርም በሪፖርቱ መገለጹንም ዘገባው ጨምሮ ገልጧል፡፡

*ጦርነት፣በሽታ፣ድህነት-- ለድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻ መስፋፋት አስተዋጽኦ አበርክተዋል

“ድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻ”የሚለውን አጠራር የተባበሩት መንግስታት ዓለምአቀፍ የህፃናት ፈንድ(ዩኒሴፍ)፤ ልጆች ከትውልድ አገራቸው ድንበር ተሻግረው ወደ ሌላ አገር በመግባትበጉዲፈቻ የሌላ ቤተሰብ አባል የሚሆኑበት ሁኔታ ነው ሲል ይተረጉመዋል።
በተለያዩ አገራት ዜጐች መካከል የሚፈፀም ጉዲፈቻ እየጨመረ የመጣው ከሁለተኛው የዓለም ጦርነት ማብቂያ በኋላ ነው፡፡ በዚህ ጦርነት የተነሳ አያሌ ህፃናት ወላጆቻቸውን በማጣታቸው፤በማሳደጊያዎች ውስጥበአሰቃቂ ሁኔታ ተይዘው ለማደግ ይገደዱ ነበር፡፡ከዚያ የተሻለ ሌላ አማራጭም አልነበራቸውም፡፡
ድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻ የተጀመረው የተለያዩ አገራት ወታደሮች የጦርነት ቀጠና በሆኑ የዓለም አገራት መስፈራቸውን ተከትሎ እንደሆነ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ሁለተኛው የዓለም ጦርነት ካበቃ በኋላ በበርካታ የአለም ክፍሎች የተነሱ ግጭቶች ለወታደሮች በየአገሩ መስፈር ምክንያት ሆኗል፡፡ በተለይ የተባበሩት መንግስታት ወታደሮች በኮሪያ ጦርነት እንዲሁም የአሜሪካ ወታደሮች በቬትናም ውጊያ ወቅት በርካታ ልጆችን እንደወለዱ መረጃዎች ያመለክታሉ፡፡
በአብዛኛው ጉዲፈቻ የተደረገው ወደ አሜሪካ እና አውሮፓ አገራት ሲሆን የጉዲፈቻ ልጆች ምንጭ አገሮችም ደቡብ ኮሪያ፣ ቬትናም እና የመሳሰሉት ነበሩ፡፡ ከጦርነትና ግጭቶች በተጨማሪም ድርቅ፣ በሽታና ድህነትም ለድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻ መስፋፋት ምክንያት ሆነዋል፡፡
 ለዚህም ሩሲያ፣ ጉዋቲማላ፣ ቻይና እና የአፍሪካ አገራት ይጠቀሳሉ፡፡
በተለይ ከደቡብ ኮሪያ በርካታ ቁጥር ያላቸው ህፃናት በጉዲፈቻ የተወሰዱ ሲሆን ለዚህም ምክንያቱ በሰሜኑና ደቡብ መካከል በተደረገው በርካታ አገሮች የተሳተፉበት ጦርነት፣ ልጆች ቤተሰባቸውን በማጣታቸው ነው፡፡ ከዚህም ሌላ በወቅቱ በደቡብ ኮሪያ ሰፍረው ከነበሩ የአሜሪካ ወታደሮች የተወለዱ ህጻናት በመልክ ከአካባቢው ማህበረተሰብ የተለዩ ስለነበሩ፣ለማህበራዊና ስነልቦናዊ ችግሮች ተጋልጠዋል፡፡እነሱ ብቻ ሳይሆኑ እናቶቻቸውም በሕብረተሰቡ ዘንድ መገለል ይፈጸምባቸው ነበር፡፡በጦርነት ሰበብ የተወለዱ ህፃናት በአብዛኛው በጉዲፈቻ የሚወሰዱት ወደ አባቶቻቸው አገር ሲሆን ለዚህም ምክንያቱ በአባታቸው የዜግነት መብት ስላላቸው ነው፡፡ ይሔም ለድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻ መጨመር አስተዋጽኦ አድርጓል፡፡ ከዚህም ባሻገር“በጦርነት ምክንያት የተወለዱ ልጆች በመሆናቸው ልንታደጋቸው ይገባል”የሚለው አስተሳሰብ ድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻን ያስፋፋ ሲሆን “ጉዲፈቻ በአገሮች መካከል መልካም ግንኙነት ለመፍጠርም ይረዳል”የሚለው አመለካከት ስር መስደዱ ሌላው ምክንያት ነው ሊባል ይችላል፡፡
በአሜሪካ ድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻ ተቋማዊ በሆነ መልኩ የተጀመረው እ.ኤ.አ. በ1956 ዓ.ም ሆልት በሚባል በጎ አድራጊ ግለሰብ ሲሆን በአሁኑ ወቅት “ሆልት ችልድረንስ ሰርቪስ” በበርካታ አገራትየሚንቀሳቀስና ብዙ ቅርንጫፎች ያሉት የጉዲፈቻ አገልግሎት ኤጀንሲ ለመሆን በቅቷል፡፡ ኤጀንሲው ኢትዮጵያ ውስጥ መስራት ከጀመረም ከሰባት ዓመት በላይ አስቆጥሯል፡፡
በተለያዩ አገራት የተከሰቱ ማሕበራዊ፣ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ቀውሶችምለድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻ መስፋፋት አስተዋጽኦ አድርገዋል፡፡
በሮማኒያ የቻችስኩ መንግስት ፖሊሲ /Ceausescu’s Policy/ እያንዳንዷ ሩማንያዊት ሴት፣ቢያንስ አምስት ልጅ የመውለድ ግዴታ ተጥሎባት ነበር፡፡ አንዳንድ ቤተሰቦች ታዲያበድህነት የተነሳ የወለዷቸውን ልጆች ማሳደግ ስለማይችሉ ህጻናት ማሳደጊያ ውስጥ ለማስገባት ይገደዱ ነበር፡፡ የቻችስኩ መንግስት እ.ኤ.አ. በ1989 ዓ.ም በወደቀ ማግስት፣በአገሪቷ ውስጥ ከስድስት እስከ ስምንት መቶ የሚደርሱ የህፃናት ማሳደጊያዎች ነበሩ፡፡በእያንዳንዱ ማሳደጊያም ከ100ሺ እስከ 300ሺ የሚገመቱ ህፃናትእንደነበሩ መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ በማሳደጊያዎች ውስጥ ያሉ ህፃናት ሁኔታበመገናኛ ብዙሃንበሰፊውይነገር ስለነበር፣ አሁንም “ልጆችን ልንታደጋቸው ይገባል” በሚል ዓላማ፣የምእራቡ አለም ድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻን ማድረጉን ቀጠለበት። በተመሳሳይ ሁኔታ በሩሲያ በነበረው ከፍተኛ የሆነ ድህነት የተነሳም ከ300ሺ በላይ ህፃናት ማሳደጊያ ውስጥ እንዲገቡ ምክንያት ሆኖ ነበር፡፡ ይሄን ተከትሎም የድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻ ሊጨምር ችሏል፡፡
በቻይና አሁንም ድረስ የሚተገበረውና የህዝብ ብዛትን ለመቀነስ በመንግስት የወጣው አንድ ልጅ ብቻ የመውለድ ፖሊሲ፣ ዜጎች ጉዲፈቻ እንዳያደርጉ ከተቀመጠው ክልከላ እንዲሁም ህብረተሰቡ “ወንድ ልጅ ቤተሰቡን ይጦራል” በሚል ለሴት ህፃናት ባለው አሉታዊ አመለካከት የተነሳ፣ ብዙ ልጆች በተለይም ሴት ልጆች ማሳደጊያ ውስጥ እንዲገቡ ተገደዋል፡፡
የኤችአይቪ/ ኤድስ መስፋፋትምለድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻ መጨመር ትልቅ አስተዋፅኦ እያደረገ ይገኛል፡፡ ከሰሃራ በታች ባሉ የምስራቅ አፍሪካ አገራት 12.3 ሚሊዮን ህፃናት በኤድስ ምክንያት ወላጆቻቸውን እንዳጡ ይገመታል፡፡ ሆኖም በአፍሪካ ድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻ እንደሌሎች የዓለም አገራት በብዛት አልተለመደም፡፡ ለዚህ ምክንያቱ ደግሞ በአህጉሪቱ ልጆችን በቤተዘመድ የማሳደግባህል መኖሩ ሳይሆን እንደማይቀር ይገመታል፡፡ አሁን ባለው ተጨባጭ የአህጉሪቱ የኢኮኖሚ ሁኔታ ግንወላጆቻቸውን ያጡ ህፃናት በቤተዘመድ የማሳደግ ሁኔታ መቀጠሉ በእጅጉ የሚያጠራጥር ነው፡፡ እናም በአፍሪካ ድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻ እየተስፋፋ እንደሚመጣ ጥናቶች ይጠቁማሉ፡፡
ድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻ፤ ዝምድና በሌላቸው ሰዎች መካከል የሚደረግ የጉዲፈቻ ዓይነት በሚለው ዘርፍ የሚመደብ ነው፡፡ የዚህ ዓይነት ጉዲፈቻ ልጁ የተፈጥሮ ልጅ አለመሆኑ ብቻ ሳይሆን በጉዲፈቻ አድራጊዎችናበጉዲፈቻ ተደራጊ መካከል የድንበር፤ የቀለም፣ የባህል፣ የዘር፣የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልዩነትምየሚስተዋልበት መሆኑ ነው፡፡
የድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻ፤ መንግስት ወላጅ ለሌላቸው ህጻናት ከሚያቀርበው አማራጭ የእንክብካቤ መንገዶችአንዱ ሲሆን ጉዲፈቻው ፐብሊክ /public adoption/ በሚለው ዘርፍ ይመደባል፡፡ ይህም ለጉዲፈቻ የሚቀርቡት ልጆች ዕጣ ፈንታየሚወሰነው በሚመለከተው የመንግስት አካል መሆኑንያመላክታል።

በአሜሪካኖች ዘንድ የሚነገር አንድ ቀልድ መሳይ ተረት እንዲህ ይላል:-
ከዕለታት በአንደኛው አዲስ ዓመት ዕለት አምላክ ሶስት ታዋቂ ሰዎችን ጠራ
1ኛ/ ቢል ጌትስን
2ኛ/ ቦሪስ ዬልሲንን
3ኛ/ ቢል ክሊንተንን
ከዚያም “የጠራኋችሁ አንድ አስቸኳይ መልዕክት ስላለኝ ነው” አለ፡፡
ሁሉም በችኮላና በጉጉት “ምንድን ነው?” “ምንድን ነው?” “ፈጥነህ ንገረን” አሉት፡፡
አምላክም፤
“ይሄንን መልዕክት እንደ አዲስ ዓመት መልዕክት ቁጠሩት፡፡ ምክንያቱም በመልዕክቱ በመጠቀም ብዙ ህዝብ ታድኑበታላችሁ” አለና፤
“በመጀመሪያ፤ ዬልሲንን፤
‘ጠጋ በል ዬልሲን፡፡ ከሚቀጥለው ሳምንት ጀምሮ ዓለም ትጠፋለች፡፡ ስለዚህ ወደሩሲያ ህዝብ ሄደህ ይህንኑ አሳውቅ” አለው፡፡
ዬልሲን ወደ አገሩ በረረ፡፡ ቀጥሎ ክሊኒተንን “ጠጋ በል፡፡ ለአሜሪካን ህዝብ መንገር ያለብህ መልዕክት አለ፡፡ በአንድ ሣምንት ጊዜ ውስጥ ዓለም ልትጠፋ ነውና የአሜሪካ ህዝብ እንዲዘጋጅና እንዲጠብቅ ንገር!” አለው፡፡
ክሊንተንም አፍታም ሳይቆይ ወደ አገሩ በረረ፡፡
በመጨረሻም አምላክ ቢልጌትስን “ና ወደ ኔ፡፡ እንደሌሎቹ ሰዎች ለአንተም መልዕክት አለኝ፡፡ በቴክኖሎጂው ማህበረሰብ ውስጥ እጅግ ታዋቂ እንደመሆንህ ለኮምፒዩተር ሠሪውና ተገልጋዩ ህዝብ፤ በሚቀጥለው ሳምንት ዓለም እንደምትጠፋ ደጋግመህ አሳውቅ” አለው፡፡
ቢልጌትስም፤ “አሁኑኑ ባለኝ ፈጣን የቴክኖሎጂ ዘዴ በፍጥነት እገልፃለሁ” ብሎ ፈጥኖ ሄደ፡፡
ሦስቱም መልዕክቱን ያስተላለፉት እንደሚከተለው ነበር፡፡
ዬልሲን ለሩሲያ ህዝብ እንዲህ አለ:-
“አንድ መጥፎ ዜናና አንድ አስደንጋጭ ዜና ልነግራችሁ ነውና አዳምጡ:-
መጥፎው ዜና - በዕውነት አምላክ መኖሩ መረጋገጡ ነው፡፡
አስደንጋጩ ዜና - ከእንግዲህ ምንም ዓይነት የጦር መሣሪያ አናመርትም፡፡ የአገሮችን ዕዳም ምረናቸዋል፡፡ ምክንያቱም ዓለም በሚቀጥለው ሣምንት ትጠፋለች” አለ፡፡
ክሊንተን ዋሺንግተን ዲሲ ውስጥ ጋዜጣዊ መግለጫ ሊሰጥ ስብሰባ ጠራ፡፡
ከዚያም፤
“አንድ ጥሩ ዜናና አንድ መጥፎ ዜና ስላለኝ የአሜሪካን ህዝብ ስማ፡፡
ጥሩው ዜና - አምላክ በዕውነት መኖሩ መረጋገጡ ነው፡፡ In God we Trust (በአንድ አምላክ እናምናለን) ብለን ዶላራችን ላይ መፃፋችን አኩርቶናል፡፡
መጥፎው ዜና - በሚቀጥለው ዓመት ከማንኛውም አገር ጋር ተኩስ አቁም ስምምነት እናደርጋለን፡፡ ምክንያቱም ዓለም በሚቀጥለው ሣምንት ትጠፋለች” አለ፡፡
ቢልጌትስ በበኩሉ ወደ ሬድሞንድ ሄደ፡፡ ጋዜጣዊ መግለጫ ስለሚሰጥ በጣም ሰፊ ስብሰባ እንዲጠራ አዘዘ፡፡ ከዚያም፤
“አንድ ጥሩ ዜናና አንድ አስደናቂ ዜና አለኝ፡፡
የመጀመሪያው - አምላክ እኔ ምን ዓይነት አስፈላጊና ትልቅ ሰው መሆኔን ማወቁ ነው!
ሁለተኛውና አስደናቂው ዜና - በሚቀጥለው ዓመት የኮምፒዩተር ጥገና ሥራ የለብንም” አለ፡፡
***
መጪውን ጊዜ ሁሉም እንደየቁቡ፤ ሁሉም እንደየፍጥርጥሩ ነው የሚተረጉመው፡፡ ሁሉም እንደየኪሱ ነው የሚመነዝረው፡፡  
“ዛሬ ባይልልን ነው እንጂ ይቺ አገር፤ ምርቃት መሬት የማይወድቅባት ነበረች”፤ ይላሉ አበው፡፡ አዲሱ ዓመት ከብዙ ችግሮች ይሠውረን ዘንድ እንመኝ፡፡ ልባችንንም ይከፍትልን ዘንድ ተስፋ እናድርግ፡፡
የፍቅር፣ የዕርቅ፣ የይቅር ባይነት ዘመን እንዲሆንልን እንደምናስብ ሁሉ ሀቀኛ ትግል፣ ሀቀኛ ፖለቲካዊ ውይይት፣ የእርስ በርስም፤ ከራስ ውጪም ተቻችሎ የመነጋገር፤ የሀቀኛ ምርጫም ዘመን ያደርግልን ዘንድ መተሳሰብን ያስርፅብን፡፡ ያነሰ ምሬት፣ የበዛ አዝመራ፣ ከቂም በቀል የፀዳ ዓመት ያድርግልን!!
አንድ ገጣሚ፤
“ነብሩን እየጋለበ፣ ሰውዬው እጫካ ገባ
ኋላ ቆይቶ ቆይቶ፣ ነብሩ መጣ ብቻውን
ላዩ የነበረው ሰውዬም፣ ሆዱ ውስጥ ነው አሁን፤
ሰው ማለት ይህ ነው በቃ
ከላይ ሲጋልብ ቆይቶ፣ ሆድ ውስጥ ነው ’ሚያበቃ!”
ይላል፡፡ በዚህ ዓመት ከዚህም ይሠውረን፡፡
በዚህ ዓመት፤ ነፃ የሀሳብ ገበያ እንደልብ የሚኖርባትና መብት የማይገደብባት ኢትዮጵያን ለማኖር ከባድ ርብርብ እንደሚጠበቅ የሚያውቅ የሠለጠነ ዜጋ እንዲኖረን እንፀልይ!
በዚህ ዓመት ውዳሴና ሙገሣን እንደምንቀበል ሁሉ ትቺንና ነቀፋንም ለመቀበል ልብና ልቦና ይስጠን፡፡
የህትመት ውጤቶች የህዝብ ዐይንና ጆሮ ይሆኑ ዘንድ፣ የጠባቂነት ሚናቸውንም በወጉ ይጫወቱ ዘንድ፤ ነፃነታቸው መጠበቅም፣ መከበርም ይገባዋል፡፡ ለእነሱም የዕውነትን፣ የመረጃን ትክክለኛነትና የሚዛናዊነትን ሥነምግባር የሚጐናፀፉበት ዓመት ያድርግላቸው፡፡
አንድ የአገራችን ፀሐፊ፣    
“በንጉሡ ዘመን (ሠራተኛው) ደሞዙ ትንሽ ስለሆነ ተብሎ የቢሮውን ጠረጴዛ እንደገቢ ምንጭ ቢጠቀምበት ከወንጀል እንደማይቆጠርበት፣ ዛሬ ደግሞ የ “ኑሮ ውድነት” ወይም አልፎ አልፎ አምልጦ የሚሰማው “ተዋጊ ስለነበር” መቋቋማያ ያሻዋል የሚሉት እየገነኑ ነው” ይላል፡፡ “የአገዛዙን አውታሮች ተገን አድርገው በተቋራጭነት፣ በዕቃዎችና አገልግሎቶች አቅራቢነት እንዲሁም በሌሎች ተግባራት ሳቢያ ጥቅሞችን ለተወሰኑ ክፍሎች ማርከፍከፍ የተለመደ አሠራር መሆኑን ሁሉም ያውቃል…” ይላል፡፡ በዚህ ዓመት ከዚህም ያውጣን፡፡ ቢያንስ ዐይን ካወጣ ሙስና ይሰውረን፡፡ ከነናይጄሪያ ዓይነት ምዝበራና ዘረፋ እንዳንጠጋ ያድርገን፡፡
ወጣቱ አገሩን ከልቡ ይወድ ዘንድ፣ ምንም ዓይነት ካፒታሊስታዊ ማማለያ እንዳይበግረው ከልብ እንመኝ!!
አስማተኛ ካልሆነ በቀር አገርን ብቻውን የሚገነባ ማንም አይኖርም፡፡ አንዱ የሌላውን አቅም ይፈልጋል፡፡ ከሌላ ጋር ካልመከሩ፣ ከሌላ ጋር ካልተረዳዱና ሁሉን ብቻዬን ልወጣ ካሉ አንድ ልሙጥ አገር ናት የምትኖረን፡፡ የተለያየ ቀለሟ ይጠፋል፡፡ ልዩነት ከሌለ ዕድገት ይጠፋል፡፡ VIVE La difference - ልዩነት ለዘላለም ይኑር ማለት አለብን፡፡ እየተራረሙ መሄድ እንጂ እየኮረኮሙ መሄድ የትም አያደርሰን፡፡ አንዱ ኮርኳሚ ብዙሃኑ ተኮርኳሚ ከሆነ እጅም ይዝላል፡፡ ራሳችን ባወጣነው ህግ ራሳችን አጥፊ ሆነን ከተገኘን፣ ለጥቂቶች ብቻ የሚሠራ ደንብ አውጥተን ብዙሃኑን የምንበድል ከሆነ፣ ራሳችን ሠርተን እራሳችን የምናፈርስ ከሆነ፣ ራሳችን አሳዳጅ ራሳችን ተሳዳጅ ከሆንን፣ ከዓመት ዓመት “የዕውነት ዳኛ ከወዴት አለ?” የምንባባል ከሆነ፤ ምን ዓይነት ለውጥ፣ ምን ዓይነት ዕድገት እየጠበቅን ነው? “ብቻውን የሚሮጥ የሚቀድመው የለ፣ ብቻውን የሚሟገት የሚረታው የለ” ነውና በርካቶችን የሚያሳትፍ ሥርዓት ይበረክታል ብለን የምናስብበት ዘመን ይሁንልን፡፡ አለበለዚያ፤ “ራሷ ከትፋው ታነቀች፤ ራሷ ጠጥታው ትን አላት፡፡ ራሷ ሰቅላው ራቀ፡፡ ራሷ ነክታው ወደቀ” የሚል ህዝብ ብቻ ነው የሚኖረን፡፡ ያለ ህዝብ የት ይደርሳል? አዲሱን ዘመን አሳታፊ ያድርግልን!!
መልካም አዲስ ዓመት  


                በዓመቱ መጀመሪያ በመስከረም ወር 2006 ዓ.ም ለ12 ዓመታት የአገሪቱ ፕሬዚዳንት በመሆን ያገለገሉት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ፤ ከስልጣናቸው የወረዱ ሲሆን በቦታቸውም ዶ/ር ሙላቱ ተሾመ ተተክተዋል፡፡ በአምባሳደርነት ዘመናቸው የውጭ አገር ኢንቨስተሮችን ወደ ኢትዮጵያ በማምጣትና አገር ውስጥ መዋዕለ ንዋያቸውን እንዲያፈሱ በማግባባት ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማበርከታቸው የሚነገርላቸው ዶ/ር ሙላቱ፤ የፕሬዚዳንትነት ስልጣናቸውን ከተረከቡ በኋላም ሥራቸው በቤተመንግስት አካባቢ የተገደበ አልሆነም፡፡ በተለያዩ አገራት እየዞሩ የውጭ ኢንቨስተሮችን የማግባባት ሥራቸውን ቀጥለውበታል፡፡
በዓመቱ ከተከናወኑ አነጋጋሪ ጉዳዮች መካከል አንድነት ፓርቲ ከሰላማዊ ሰልፍ ጋር በተገናኘ የመብት ጥሰትና መጉላላት ተፈጽሞብኛል በማለት የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ከንቲባንና የከተማዋን ፖሊስ ኮሚሽን በፍ/ቤት መክሰሱ ተጠቃሽ ነው፡፡
ፍ/ቤቱም ጉዳዩን ከመረመረ በኋላ “ክሱ ለክስ የሚያበቃ ምክንያት የለውም፣ አስተዳደራዊ ውሣኔ ያገኝ የሚል ውሣኔ የሰጠ ሲሆን ፓርቲውም በጊዜው ይግባኝ እንደሚጠይቅ ገልፆ ይግባኝ ለመጠየቅ በሂደት ላይ ይገኛል፡፡  
የቀድሞ የአንድነት ፓርቲ ሊቀመንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ፣ እንዲሁም የኢዴፓ መስራችና ሊ/መንበር የነበሩት አቶ ሙሼ ሰሙ ራሳቸውን ከፖለቲካ ፓርቲ ያገለሉት በዚሁ ባሳለፍነው ዓመት ነው፡፡ ዶ/ር ነጋሶ ከጤና ጋር በተያያዘ፣ አቶ ሙሼ ደግሞ “የጥሞና ጊዜ እፈልጋለሁ” በሚል የፓርቲ ፖለቲካ በቃን ብለዋል፡
ሹመትና ህልፈት
የአማራ ክልልን ለ8 ዓመታት በርዕሰ መስተዳደርነት የመሩት አቶ አያሌው ጎበዜ፣ የደቡብ ክልል ርዕሰ መስተዳደር የነበሩት አቶ ሽፈራው ሽጉጤ በአምባሳደርነትና በትምህርት ሚኒስትርነት የተመደቡት ባሳለፍነው ዓመት ሲሆን የኦሮሚያ ክልል ርዕሰ መስተዳደር የነበሩት አቶ አለማየሁ አቶምሳ ባደረባቸው ህመም ህክምና ሲከታተሉ ቆይተው ህይወታቸው ማለፉ ይታወሳል፡፡ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የህዝብ ተሳትፎና ንቅናቄ ክላስተር አስተባባሪና የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትር የነበሩት አቶ ሙክታር ከድርም የክልሉ ፕሬዚዳንት በመሆን የተሾሙ ሲሆን  በሳቸው ቦታ ወ/ሮ አስቴር ማሞ ተተክተዋል፡፡
የሳኡዲ ስደተኞችን ማባረር
የሳኡዲ አረቢያ መንግስት የመኖሪያ ህጋዊ ፍቃድ የላቸውም በሚል ኢትዮጵያዊያንን ጨምሮ የበርካታ ሃገር ዜጎችን ከሃገሩ በኃይል ማስወጣት የጀመረው ባሳለፍነው ዓመት ጥቅምት ወር  መጨረሻ ገደማ ነበር፡፡ የሳኡዲ አረቢያ መንግስት ህገወጥ ስደተኞች ባላቸው ላይ በወሰደው የማባረር እርምጃ ከ150ሺ በላይ ኢትዮጵያውያን ወደ ሃገር ቤት መመለሳቸው የሚታወስ ሲሆን የዓለም አቀፍ ሚዲያዎችን ትኩረት በሳበው በዚህ ክስተት፣ በተለያዩ የዓለም ክፍሎች የሚገኙ ኢትዮጵያውያን በሳኡዲ ኤምባሲዎች በር ላይ ሰላማዊ ሰልፍ በማድረግ ተቃውሞአቸውን ገልፀዋል፡፡ በአዲስ አበባ ለተመሳሳይ ዓላማ ሰማያዊ ፓርቲ የጠራው ሰላማዊ ሰልፍ ግን በፖሊስ በመበተኑ ሳይደረግ ቀርቷል፡፡
የኢትዮጵያ መንግስት በየአረብ ሃገራቱ ለስራ የሚጓዙ ዜጎች ጉዳይ አሳስቦኛል በማለት ወደ የትኛውም የአረብ ሃገራት ለጉልበት ስራ የሚደረግን ጉዞ ለ6 ወር ያህል ማገዱ የሚታወስ ሲሆን እገዳው 9ኛ ወሩን ቢይዝም እስካሁን አልተነሳም፡፡
“የረዳት አብራሪው የአውሮፕላን ጠለፋ”
በኢትዮጵያ አየር መንገድ ለ5 ዓመታት በረዳት አብራሪነት ያገለገለው ሃይለመድህን አበራ፤ በጥር ወር አጋማሽ ላይ ከአዲስ አበባ ወደ ጣሊያን ሲበር የነበረውን የኢትዮጵያ አየር መንገድ አውሮፕላን  ጠልፎ ስዊዘርላንድ ማሳረፉ ከዓመቱ አነጋጋሪና ትኩረት ሳቢ ጉዳዮች አንዱ ነበር፡፡
ረዳት አብራሪው አውሮፕላኑን ለምን እንደጠለፈ እስካሁንም ይሄ ነው የሚባል አሳማኝ ምክንያት አልተገኘለትም፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት ጠላፊው ተላልፎ እንዲሰጠው የጠየቀ ቢሆንም አዎንታዊ ምላሽ አላገኘም፡፡ ጠላፊው የስዊዘርላንድን መንግስት ጥገኝነት ጠይቆ እንደተፈቀደለትና አሁን እዚያው በእስር ላይ እንደሚገኝ ይታወቃል፡፡ ፍትህ ሚኒስቴር በበኩሉ፤ በጠላፊው ላይ  ክስ መስርቶ ፍ/ቤት የአቃቤ ህጎችን ምስክርነት በመስማት  ላይ ይገኛል፡፡
መፍትሔ ያልተበጀለት “የሙስሊሞች ጉዳይ”
“ከሁለት ዓመት በፊት የታሰሩት ሙስሊም መሪዎቻችን ይፈቱ፣ ድምፃችን ይሰማ” የሚሉ ንቅናቄዎች እየተካሄዱ ነው ዓመቱ ያለፈው፡፡ ሐምሌ 11 ቀን 2006 ዓ.ም አርብ በታላቁ አንዋር መስጊድ የተቀሰቀሰውን ተቃውሞ  ተከትሎ ፖሊስ በወሰደው እርምጃ በሰዎች ላይ ድብደባና ጉዳት መድረሱ ይታወሳል፡፡ ቁጥራቸው በውል ያልታወቀ ሰዎች ታስረው የነበረ ሲሆን በነሐሴ ወር መጀመሪያ ላይ በዋስ ተለቀዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል የቀድሞው “አዲስ ጉዳይ” መፅሄት የፎቶግራፍ ባለሙያ አዚዛ አህመድ እና የሰማያዊ ፓርቲ አመራር አባል ወይንሸት ሞላ ይገኙበታል፡፡
የታሰሩት ሙስሊሞች ጉዳይ በፍ/ቤት መታየቱን የቀጠለ ሲሆን ተጠርጣሪዎቹ የመከላከያ ምስክሮቻቸውን በማሰማት ሂደት ላይ እንደሆኑ ይታወቃል፡፡
አዲሱ ማስተር ፕላን የቀሰቀሰው ተቃውሞ
ሌላው የዓመቱ አብይ ክስተት የአዲስ አበባና በኦሮሚያ ልዩ ዞን ስር የሚተዳደሩ ከተሞች የጋራ ማስተር ፕላን የተነሳ የተቀሰቀሰው ተቃውሞና ረብሻ ሲሆን የሰው ህይወትን ጨምሮ በርካታ ጉዳትና ውድመት ደርሷል፡፡
በአገሪቱ የተለያዩ ዩኒቨርሲቲዎች የሚማሩ የኦሮሚያ ተወላጅ ተማሪዎች በሚያዚያ ወር አጋማሽ ላይ ባስነሱት ተቃውሞ ሳቢያ ከፖሊስ ጋር ግጭት መፈጠሩ ይታወሳል፡፡
ዓለም አቀፍ ሚዲያዎች በአምቦ ከተማ በተፈጠረው ግጭት 30 የሚደርሱ ሰዎች መሞታቸውን ሲዘግቡ፣ የሃገር ውስጥ መገናኛ ብዙሃን በበኩላቸው፤ በአጠቃላይ የ11 ሰዎች ህይወት ማለፉን ዘግበዋል፡፡
ተቃውሞውን ለማስቆም በፀጥታ ሃይሎች ከተወሰደው እርምጃ ባሻገር ከፍተኛ የመንግስት አመራሮች ውዝግብ ባስነሳው የጋራ ማስተር ፕላን ዙሪያ ከተማሪዎችና ከህብረተሰቡ ጋር ለበርካታ ሳምንታት ውይይት እንዳደረጉም አይዘነጋም፡፡
“አስደንጋጩ” የጋዜጠኞችና ጦማሪያን እስር
መንግስት በሽብርተኝነት ጠርጥሬያቸዋለሁ በማለት  3 ጋዜጠኞችና 6 ጦማሪያን ማሰሩ የዓለም አቀፍ ሚዲያዎችን ትኩረት የሳበ ሌላው የዓመቱ ጉልህ ክስተት ነበር፡፡ አብዛኞቹ ዓለምአቀፍ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማትም እስሩን ከመጪው አገራዊ ምርጫ ጋር በማያያዝ የመንግስት ፍርሃት የፈጠረው ጉዳይ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡
በሚያዚያ ወር አጋማሽ ላይ ጋዜጠኛ ተስፋለም ወልደየስ፣ ኤዶም ካሳዬ፣ አስማማው ሃይለጊዮርጊስ እንዲሁም “ዞን 9” በተሰኘ ድረገጽ ፀሐፊነታቸው የሚታወቁት አጥናፉ ብርሃኔ፣ ማህሌት ፋንታሁን፣ ዘላለም ክብረት፣ ናትናኤል ፈለቀ፣ በፈቃዱ ሃይሉና አቤል ዋበላ ተይዘው መታሰራቸው የሚታወስ ነው፡
መንግስት በተጠርጣሪዎቹ ላይ በሽብርተኝነት ከተፈረጁ ድርጅቶችና ተቋማት ጋር በመተሳሰር እንደሚሰሩ ደርሼበታለሁ በሚል ክስ የመሰረተባቸው ሲሆን ጉዳያቸው በፍ/ቤት በመታየት ላይ ይገኛል፡፡
የአቶ አንዳርጋቸው መያዝና የተቃዋሚ አመራሮች እስር
በህዝብ ተወካዮች ም/ቤት በአሸባሪነት ከተፈረጁት አምስት የፖለቲካ ድርጅቶች አንዱ የሆነው የ“ግንቦት 7” ዋና ፀሐፊ የነበሩት አቶ አንዳርጋቸው ጽጌ፣ በሰኔ ወር መጨረሻ ላይ በየመን መያዝና ለኢትዮጵያ መንግስት ተላልፎ መሰጠት የተጠናቀቀው አመት ያልተጠበቀ ክስተት ነበር፡፡ የእንግሊዝ ዜግነት ያላቸው አቶ አንዳርጋቸው፤ ቀደም ሲል በሌሉበት በተመሰረተባቸው የአሸባሪነት ክስ የሞት ፍርድ እንደተወሰነባቸው ይታወሳል፡፡
እኚህ የግንቦት 7 ከፍተኛ አመራር በኢትዮጵያ መታሰራቸውን ተከትሎ በተለያዩ የአሜሪካና አውሮፓ አገራት የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በእንግሊዝ ኢምባሲዎች ደጃፍ ላይ በመሰባሰብ ተቃውሞ ማሰማታቸውን ቀጥለዋል - እንግሊዝ ዜግነት ለሰጠችው ሰው ተገቢውን ጥበቃና ከለላ አልሰጠችም በሚል፡፡
አንዳንዶች እንደሚሉት፤ የአቶ አንዳርጋቸው ጦስ ለአገር ውስጥ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮችም ተርፏቸዋል፡፡ እሳቸው በታሰሩ ማግስት በሐምሌ ወር መጀመሪያ ላይ የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ሃብታሙ አያሌውና የፓርቲው የድርጅት ጉዳይ ም/ኃላፊ አቶ ዳንኤል ሺበሺ፣ የሰማያዊ ፓርቲ ብሄራዊ ም/ቤት ም/ሰብሳቢ አቶ የሽዋስ አሰፋ እንዲሁም የአረና ፓርቲ አመራር አባል አቶ አብርሃ ደስታ በሽብር ተጠርጥረው የታሰሩ ሲሆን ጉዳያቸውም በፍ/ቤት እየታየ ነው፡፡
የግል የሚዲያ ተቋማት ክስ፤ የአሳታሚዎችና ጋዜጠኞች ስደት
መንግስት በ“ፋክት” ፣ “ሎሚ” ፣ “አዲስ ጉዳይ”፣ “እንቁ”፣ “ጃኖ” መፅሄት እና “አፍሮ ታይምስ” ጋዜጣ አሳታሚዎችና ባለቤቶች ላይ የወንጀል ክስ መመስረቱን በቴሌቪዥን የገለፀው  በሐምሌ ወር መጨረሻ ነበር፡፡ ከመግለጫው ጥቂት ሳምንት በኋላ ለፍ/ቤት የቀረበው የአሳታሚዎችና የስራ አስኪያጆቹ ክስ ጠቅለል ብሎ ሲታይ በተለያዩ የህትመት ውጤቶቻቸው በፃፏቸው ፅሁፎች በህገ-መንግስታዊ ስርአቱ ላይ አመፅ ቀስቅሰዋል፣ በሃሰት ወሬ ህዝብን በመንግስት ላይ የሚያነሳሱ ፅሁፎችን አትመዋል የሚል ሲሆን የፍ/ቤት ሂደቱም ቀጥሏል፡፡
የመንግስትን ክስ ተከትሎ ከ “ፋክት” መፅሄት አሳታሚ በስተቀር የሁሉም ተከሳሽ የሚዲያ ተቋማት ባለቤቶች ሃገር ለቀው የወጡ ሲሆን በአጠቃላይ 16 ያህል የግል ፕሬሱ አባላት አገር ለቀው ተሰደዋል፡፡ መንግስት በበኩሉ፤ በጋዜጠኞች ላይ የተመሰረተ ክስ ስለሌለ የተሰደደ አንድም ጋዜጠኛ የለም ብሏል፤ ጋዜጠኞቹ ለተሻለ ኢኮኖሚያዊ ጥቅም ከአገር መውጣታቸውን በመጠቆም፡፡
“ብዙ የተባለለት የደሞዝ ጭማሪ”
ብዙ የተነገረለትና በጉጉት የተጠበቀው የመንግስት ሰራተኞች የደሞዝ ጭማሪም የተደረገው በዚህ ዓመት ሐምሌ ወር ጀምሮ ነው፡፡ ጭማሪው ከፍተኛ ይሆናል በሚል ግምት ከፍተኛ የመነጋገሪ አጀንዳ ሆኖ የቆየው የደሞዝ ጭማሪው ብዙዎች እንደጠበቁት ግን አልሆነም፡፡ ጭማሪው ከ33 እስከ 46 በመቶ ብቻ ነበር፡፡ ጭማሪውን ተከትሎም ነጋዴው በመሰረታዊ ሸቀጦች ዋጋ ላይ ጭማሪ እንዳያደርግ መንግስት ተደጋጋሚ ማስጠንቀቂያ ሲሰጥ ቆይቷል፤ ማስጠንቀቂያውን የጣሱ “ህገወጥ” ነጋዴዎች ላይም እርምጃ መወሰዱን መንግስት አስታውቋል፡፡
“ዓለምን ያስደነገጠው ኢቦላ”
በምዕራብ አፍሪካ አገራት ተከስቶ ወደሌሎች የአፍሪካ አገራት የተስፋፋው ኢቦላ፤ መላውን ዓለም ድንጋጤ ውስጥ የከተተው በዚሁ ዓመት ላይ መገባደጃ ላይ ሲሆን አሁንም ስጋት እንደሆነ ቀጥሏል፡፡  
ዓለም አቀፉ የጤና ድርጅት (WHO) ከትላንት በስቲያ ይፋ ባደረገው መረጃ፤ ቫይረሱ በተከሰተባቸው የአፍሪካ አገራት 2ሺ ገደማ ሰዎች ለህልፈት መዳረጋቸውን አስታውቋል፡፡
 ኢትዮጵያም የዚህ ቫይረስ ተጠቂ እንዳትሆን ከወዲሁ ለመከላከል የተለያዩ የቅድመ ጥንቃቄ እርምጃዎች እየተወሰዱ መሆኑን መንግስት አስታውቋል፡፡ ቦሌ አየር መንገድን ጨምሮ በተለያዩ የድንበር አካባቢዎች ጊዜያዊ የምርመራ ጣቢያዎች የተቋቋሙ ሲሆን በአዲስ አበባም 50 አልጋዎች ያሉት ልዩ ሆስፒታል መዘጋጀቱን የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር አስታውቋል፡፡


ዋዜማውን የት ለማሳለፍ አስበዋል?

በዘንድሮ የአዲስ ዓመት ዋዜማ ከቀድሞ ዓመታት በተለየ በርካታ የሙዚቃ ድግሶች እንደተዘጋጁ ያሰባሰብናቸው መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡ ጃኪ ጎሲና አንጋፋው ድምፃዊ ቴዎድሮስ ታደሰ ረቡዕ ምሽት በዋዜማው ታዳሚውን በሚሊኒየም አዳራሽ እንደሚያዝናኑ ይጠበቃል፡፡ አንጋፋው ድምፃዊ አለማየሁ እሸቴም በምሽቱ ዝግጅት ላይ የሚያቀነቅን ሲሆን “የተመስገን ልጆች” የባህል ውዝዋዜ ቡድን የኮንሰርቱ አካል እንደሆኑ ታውቋል፡፡ ኮንሰርቱን ለመታደም ቀደም ብለው ትኬት ለሚገዙ 500 ብር፣ በእለቱ በር ላይ በእለቱ ለመግዛት 600 ብር ነው ተብሏል፡፡ የቪአይፒ ትኬት 1500 ብር ሲሆን እራትን ይጨምራል፡፡
ሃርመኒ ሆቴል
ከኤድናሞል ዝቅ ብሎ በሚገኘው ሃርመኒ ኢንተርናሽናል ሆቴልም ለአዲስ ዓመት ዋዜማ ትልቅ የሙዚቃ ድግስ ተዘጋጅቷል፡፡ በዚህ ድግስ ላይ ዋዜማውን የሚያደምቁት የጃኖ ባንድ አባላት ናቸው ተብሏል፡፡ በዚህ ድግስ ላይ ለመታደም ብቻዎን ከሄዱ በሰባት መቶ ብር የፍቅር ወይም የትዳር አጋርዎን ከያዙ ደሞ በ1200 ብር ይዝናናሉ፡፡
ሒልተን ሆቴል
በቅርቡ ስሙን ከኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ድርጅት ወደ ኢትዮጵያ ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬሽን የቀየረው EBC፤ በዋዜማው ዕለት ከሒልተን በቀጥታ የሚያስተላልፈው የመዝናኛ ዝግጅት እንዳለው ታውቋል፡፡ በዋዜማ ዝግጅቱ ላይ እነማዲንጎ አፈወርቅ፣ ሃመልማል አባተ፣ ኤፍሬም ታምሩ፣ ንዋይ ደበበ፣ ማህሌት ገ/ጊዮርጊስ፣ ዘውዱ በቀለ፣ ሃይሉ ፈረጃና ሌሎች በርካታ አንጋፋና ወጣት ድምፃዊያን ይሳተፉበታል ተብሏል፡፡ በዚህ የዋዜማ ፕሮግራም የመግቢያ ክፍያ እንደሌለና እንግዶች በጥሪ ካርድ እንደሚገቡ ታውቋል፡፡  
ካፒታል ሆቴል
ከኡራኤል ወደ 22 በሚወስደው መንገድ ላይ የሚገኘው ካፒታል ሆቴልና ስፓ እንዲሁ ትልቅ የዋዜማ የሙዚቃ ድግስ ያዘጋጀ ሲሆን ምሽቱ በመሃሪ ብራዘርስ ባንድ ይደምቃል ተብሏል፡፡ በዚህ ምሽት አንጋፋው ድምፃዊ አለማየሁ እሸቴ ሥራዎቹን የሚያቀርብ ሲሆን መግቢያ 1300 ብር ነው፡፡
ሳሬም ኢንተርናሽናል ሆቴል
ሰሜን ማዘጋጃ አካባቢ የሚገኘውና በዓመቱ መጀመሪያ ላይ አካባቢ ስራ የጀመረው ባለ አራት ኮከቡ ሳሬም ኢንተርናሽናል ሆቴልም ለአዲሱ ዓመት ዋዜማ የሙዚቃ ድግስ አዘጋጅቷል፡፡ በዚህ ምሽት ገነነ ሃይሌ፣ የባህል ዘፋኙ ግዛቸው እሸቱ፣ ፀጋዬ ስሜ (ሆሴ ባሳ) እና ሌሎችም የትግርኛና ጉራጊኛ ዘፋኞች የበዓል ዋዜማውን አድምቀውት ያመሻሉ፡፡ መግቢያው 380 ብር እንደሆነ ታውቋል፡፡
ጨጨሆ የባህል ምግብ አዳራሽ
በአዲስ አበባ ከኢምፔሪያል አደባባይ ወደ 17 ጤና ጣቢያ በሚወስደው መንገድ የተገነባውና ባለፈው ቅዳሜ የተመረቀው አዲሱ “ጨጨሆ የባህል ምግብ አዳራሽ” ደግሞ የፊታችን ሐሙስ የአዲስ ዓመት ልዩ የሙዚቃና የባህል ዝግጅቶችን እንደሚያቀርብ ታውቋል፡፡

            አንድነት ለዴሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ በአዲሱ ዓመት ሃገራዊ ኃላፊነትን ለመሸከም መዘጋጀቱን ገለፀ፡፡ ፓርቲው ከትናንት በስቲያ ረፋድ ላይ በጽ/ቤቱ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ፤ “የገዢውን ፓርቲ ምርጫ መጣ ነፃ ፕሬስ ውጣ” አይነት አካሄድ አጥብቆ እንደሚቃወም አስታውቋል፡፡
እንደነ አንዷለም አራጌ፣ ናትናኤል መኮንን፣ አንዱዓለም አያሌው፣ ሻምበል የሺዋስ፣ ሃብታሙ አያሌው እና ዳንኤል ሺበሺ ያሉ ወጣት የፓርቲው አመራሮች በፖለቲካ አመለካከታቸው ብቻ ወህኒ ተወርውረው የግፍ ፅዋ እየተጋቱ ነው” ያለው ፓርቲው፤  “አፈናና ስደት በአምባገነን መሪዎች አገር የተለመደና የሚታወቅ ቢሆንም አምባገነንነት በኢህአዴግ እንዲያበቃ ቆርጠን እንታገላለን” ብሏል፡፡
ፓርቲው ከ2003 ዓ.ም እስከ 2007 ዓ.ም ያለውን ጊዜ “የኢትዮጵያ ፖለቲካ ትግል እድሳትና ማንሰራራት ዘመን” ብሎ በመሰየም ባለፉት አመታት በከፍተኛ ህዝባዊ ንቅናቄ የኢትዮጵያን ህዝብ ችግሮች አደባባይ እንዳወጣ አስታውቋል፡፡
“የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” እና “የእሪታ ቀን” በሚል ያካሄዳቸውን እንቅስቃሴዎች በመጥቀስ፡፡
የፓርቲው ሊቀመንበር ኢ/ር ግዛቸው ሽፈራው በመግለጫው ላይ እንደተናገሩት፤ “አፈናና እስራት ቢበዛብንም ትግሉ ከዚህም የባሰና የከፋ ችግር እንደሚያስከትል እያወቅን ስለገባንበት በሰላማዊ ትግላችን እንቀጥላን“ ብለዋል፡፡
ፓርቲው በ2007 “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነትና ፍትሃዊ ምርጫ “በሚል አመቱን ሙሉ የሚቆይ ንቅናቄ እንደሚያካሂድ ገልፆ፣ በዚሁ ዓመት በሚደረገው ሃገራዊ ምርጫ ላይ የምርጫ ቦርድ፣ የመገናኛ ብዙሃን፣ የፍትህ ስርዓቱና ሌሎች የዴሞክራሲ ተቋማት በህገ-መንግስቱ የተደነገገውን መሰረት በማድረግ ገለልተኝነታቸውን በአንፃራዊ ደረጃ በማረጋገጥ፣ በምርጫው እንደሚሳተፍና የህዝብን የስልጣን ባለቤትት ለህዝብ እንደሚያበስር አመራሮቹ ተናግረዋል፡፡
 የፓርቲውን ስትራቴጂና የአምስት ዓመት እቅድ መሰረት በማድረግ፣ በአብዛኛው የአገሪቱ ክልል ምርጫ ተኮር አደረጃጀት ለመዘርጋት እንቅስቃሴ መጀመሩንም ፓርቲው አስታውቋል፡፡ “መንግስት ለ2007 ዓ.ም ምርጫ ፍጆታ ሲል ለሰራተኛው ደሞዝ ጨመርኩ ቢልም ህዝቡ ጀኑሮ ውድነት የተሰቃየበትና አሁንም እየተሰቃየ ያለበት ዓመት ሆኗል፡፡” ያሉት አመራሮቹ፣ መንግስት ገበያውን በአስቸኳይ በማረጋጋት የህዝቡን ጫና እንዲቀንስ ጠይቀዋል፡፡
 መንግስት የአዲስ አበባን ይዞታ ለማስፋፋት ሲል የሚመለከታቸውን የህብረተሰብ ክፍሎች ሳያወያይ ባደረገው አከላለል በተነሳ የህዝብ ቁጣ በርካታ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎች ለሞት፣ ለአካል ጉዳት፣ ለእስራትና ለተያያዥ ጉዳዮች ያጋለጠ በመሆኑ ከምንግዜውም በላይ ዓመቱን መራራ አድርጎት ማለፉን የተናገሩት የአንድነት አመራሮች በ2007 ዓ.ም ይህ ሁሉ ግፍ ተወግዶ ህዝቡ እፎይታ የሚያገኝበት ዓመት እንዲሆን ፓርቲው ከምንጊዜውም በላይ የሃገርን ኃላፊነት ለመሸከም መዘጋጀቱን ገልፀዋል፡፡ፓርቲው ለኢትዮጵያ ህዝብ ባስተላፈው መልእክት፤ በመጪው አገራዊ ምርጫ ከህዝቡ ጋር በመሆን ሰላማዊ ትግሉን በምርጫ ለማሳካት በአራቱም ማዕዘናት የፖለቲካ ፕሮግራሙን እንደሚተገብርና መጪው ዘመን የኢትዮጵያ ህዝብ ነፃነት በእጁ የሚገባበት በመሆኑ ህዝቡ ከትግሉ ከጎኑ እንዲቆም ጥሪውን አቅርቧል፡፡