Administrator

Administrator

የእንግሊዙ ጠቅላይ ሚኒስትር ዴቪድ ካሜሩን፤ አገሬን ብላክቤሪ በተባለው ዘመናዊ ስማርት ፎን የሞባይል ቀፎዬ ብቻ በወጉ ማስተዳደር እችላለሁ ማለታቸውን ዘ ጋርዲያን ዘገበ፡፡ ዴቪድ ካሜሩን ባሉበት ቦታ ሆነው አገሪቱን የማስተዳደር ስራቸውን በሞባይላቸው አማካይነት በአግባቡ ማከናወን እንደሚችሉ መናገራቸውን የገለጸው ዘገባው፤ በየትኛውም የአለም ጫፍ ላይ ብሆን ብላክቤሪ ሞባይሌን ከእጄ ስለማላወጣት፣ በእሷ አማካይነት ከአስተዳደር ጋር በተያያዘ መስራት የሚገባኝን ነገር ሁሉ ሳላጓድል ማከናወን አያቅተኝም ማለታቸውን አስረድቷል፡፡ ብላክቤሪ ስማርት ፎን መረጃን በማስተላለፍ ረገድ ደህንነቱ የተረጋገጠ ነው ተብሎ ስለሚታሰብ፣ የሞባይል ቀፎው የዴቪድ ካሜሩን ቀዳሚ ምርጫ መሆኑን የጠቆመው ዘ ጋርዲያን፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ የብላክቤሪ የረጅም ጊዜ ተጠቃሚ መሆናቸውን ገልጽዋል፡፡ “ካለፉት ጥቂት አመታት አንስቼ፣ የበአል ቀናትን በመሳሰሉ ስራ ላይ በማልገኝባቸው ጊዜያት አገር የማስተዳደር ስራዬን ሳከናውን የቆየሁት በዚህች ዘመናዊ ብላክቤሪ የሞባይል ቀፎዬ ነው” በማለት በግልጽ ተናግረዋል ብሏል ዘገባው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሁለት አመታት በፊት በአፕል አይፓዶች ላይ በሚጫኑ አፕሊኬሽኖች በመጠቀም የአገሪቱን የኢኮኖሚ መረጃ ለማወቅ ሙከራ ማድረጋቸውንና በዚህም፣ አጠቃላይ የአገር ውስጥ ምርት፣ የባንኮችን የብድር አሰጣጥ አሰራር፣ የስራ ዕድሎችን፣ የንብረት ዋጋ ተመኖችን፣ የምርጫ ውጤቶችን የመሳሰሉ መረጃዎችን በፍጥነት ማግኘት እንደቻሉ፤ ከዚያ ጊዜ ጀምሮም ቴክኖሎጂ ያለውን እገዛ ማጤናቸውን ዘገባው አስታውሷል፡፡

“አትሌት የሆንኩት ባለማወቅ ካዳበርኩት አቅም ነው” አትሌት ወርቁ ቢቂላ ወርቁ ቢቂላ በጣም ታዋቂና አይረሴ የሚያሰኙ በርካታ የአትሌቲክስ ገጠመኞች ያሉት ታዋቂ አትሌት ነው፡፡ በኢትዮጵያ የዘመን ቀመር ከ1976 ጀምሮ እስከ ፈረንጆቹ 2002 ድረስ በተለያዩ ዓለም አቀፍ የውድድር መድረኮች የአገሩን ባንዲራ በድል አውለብልቧል፡፡ ከጀግናው አትሌት ሻለቃ ሃይሌ ገ/ስላሴ ጋር በተለያዩ የአለም የሩጫ ትራኮች ላይ ጥሩ የቡድን ስራ በመስራት ለድል በቅተዋል፡፡ በአርሲ ክ/ሀገር ሰሬ ወረዳ አርብ ገበያ የተወለደው አትሌት ወርቁ ቢቂላ፣ የጐልደን ሊግ አሸናፊም ነበር፡፡ በጐልደን ሊግ ካስመዘገበው ስኬት በኋላ አዲዳስ ኩባንያ ጋር የማስታወቂያ ውል በመፈራረም ለሶስት አመታት ማስታወቂያ ሰርቷል፡፡ በግምት 48 ዓመት እንደሆነው የሚናገረው አትሌት ወርቁ በአሁኑ ሰዓት በዱከም ከተማ ትልቅ ሆቴልና ትልቅ የአሽከርካሪዎች ማሰልጠኛ ት/ቤት ከፍቶ ኢንቨስትመንት ላይ ተሰማርቷል፡፡

ለህንፃ ግንባታ በዝግጅት ላይ እንደሆነም ተናግሯል፡፡ ከሩጫ አጀማመሩ፣ ከስኬቶቹ፣ ከቢዝነስ ስራውና ከግል ህይወቱ ጋር በተገናኘ ዱከም በሚገኘው ሆቴሉ ከአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ጋር ቆይታ አድርጓል፡፡ እስኪ ስለአስተዳደግህ አጫውተኝ… እኔ እንግዲህ ገጠር ነው የተወለድኩት፤ የአርሶ አደር ልጅ ነኝ፡፡ እንደማንኛውም የገጠር ልጅ በእርሻ በከብት ጥበቃ ቤተሰቤን እያገለገልኩ፣ ከዚያው ጎን ለጎን ትምህርት እየተማርኩ ነው ያደግሁት፡፡ ያው ገጠር ውስጥ ስትኖሪ በግብርና ህይወት ውስጥ ብዙ ውጣ ውረዶች አሉ፡፡ እነዚያን ውጣ ውረዶች በፅናት ማለፌ አሁን ላለሁበት ህይወት መሰረት ጥሎልኛል፡፡ ብዙ ጊዜ ስለአትሌቶች ሲነሳ አርሲ ትጠቀሳለች፡፡ ብዙዎቹ ሩጫ ለመድን የሚሉት የመኖሪያ ቤታቸውና ት/ቤታቸው ሩቅ በመሆኑ እየሮጡ ስለሚሄዱ ነው፡፡ የአንተ ሯጭነት መነሻው ከዚህ ይለያል? በእርግጥ እኔ የተማርኩበት ት/ቤት ከቤቴ ብዙ አይርቅም ነበር፡፡

ግፋ ቢል በእግር የ20 ደቂቃ መንገድ ነው፡፡ እሷን በሩጫ በአምስት ደቂቃ ፉት ነው የምላት፡፡ ከቤቴ ሲደወል ተነስቼ እንኳን ሮጬ እደርሳለሁ፡፡ ትልቁ እኔን ለሯጭነት ያበቃኝ ጉዳይ ከብት እረኝነት ላይ እያለሁ አንድ አመፀኛ ወይፈን ነበረኝ፡፡ ይህ ወይፈን አውድማ ላይ እህል ሲወቃ በጄ ብሎ አይወቃም፡፡ ጥጋበኛ ነው፡፡ ሳሩ ለምለም ነው፤ እንደልቡ ይበላል፡፡ ውቂያ ውስጥ ግባ ስትይው ይፈረጥጣል፡፡ በዚህን ጊዜ ጭራውን ይዤ አብረን እንሮጣለን፡፡ ይገርምሻል እኛ የምንኖርበት አካባቢ ሜዳማ ነው፤ ያንን ሁሉ ሜዳ ጭራውን ይዤ አብሬው እሮጣለሁ፡፡ ለምን አብረኸው ትሮጣለህ? አሃ! ወይፈኑ ሮጦ ሮጦ ሲደክምና ሲያለከልክ ይዤው እመለስና ወደ ውቂያው እከተዋለሁ፡፡ ይሄን በየጊዜው ስለማደርግ ለካ ሳላውቀው አቅም አዳብሬ ኖሯል፡፡ በሌላ በኩል እህል እነግድ ነበር፡፡ እህል ለመሸመት የምንሄድበት ገበያ የአራት ሰዓት መንገድ ሲሆን ስንመለስ አራት ሰዓት በድምሩ በቀን የስምንት ሰዓት መንገድ እጓዛለሁ ማለት ነው፡፡ በዚህ በዚህ የአካል ብቃቴ እየዳበረ መጣ፡፡ ይህ የሆነው ሳላውቀው ነው፡፡ ስራዬ ብለህ ሩጫ የጀመርከው እንዴትና መቼ ነበር? ሩጫ የጀመርኩት ት/ቤት እያለሁ ነው፡፡ በስፖርት ክፍለ ጊዜ እንሮጣለን፡፡ እንዳልኩሽ እኔ ከዚያ በሬ ጋር ስሮጥ፣ ገበያ በቀን ስምንት ሰዓት ስጓዝ፣ ሳላውቀው ሯጭ ሆኛለሁ፡፡ በማወቅና ባለማወቅ ነው ስፖርት የሚሰራው ብሏል ኃይልሻ (ኃይሌ ገ/ሥላሴ ለማለት ነው) ከዚያ በስፖርት ክፍለ ጊዜ ሩጫ ስንወዳደር ማን ይቻለኝ! 1500 ሜትርና 800 ሜትር አንደኛ፣ ከት/ቤቶች ጋር ስወዳደር አንደኛ፤ በአርሲ ክ/ሃገር በ1500 እና 800 ሜትር አንደኛ እየሆንኩ ማንም ሊደርስብኝ አልቻለም፡፡

በዚያን ጊዜ የሙዚቃ ክፍለጊዜም ነበረን፤ ሙዚቃም ስፖርትም ማርክ ነበረው፡፡ ዘፈን በድምፄ ስለማልችል ማርክ ሊያመልጠኝ ሆነ፡፡ ዋሽንት መፈለግ አለብኝ ብዬ ተነሳሁ፡፡ በሸምበቆ እሰራለሁ፤ እበሳለሁ፣ አልተሳካም፡፡ ብዙ ስቃይ አየሁ፡፡ የዋሽንት አሰራሩ ችግር ለካስ የራሴው ነው፡፡ በኋላ አንድ የብረት ዋሽንት በአንድ ብር ገዛሁ፡፡ ድምፅ ማውጣት ጀመረች፡፡ በእሷ ቀስ በቀስ ስለማመድ ዋሽንት መንፋት ቻልኩ፡፡ የሙዚቃ ማርኬን ማግኘት ቻልኩኝ ማለት ነው፡፡ በሁለቱም መስኮች ተሳትፎዬ አደገ፡፡ ያኔ ወረዳችን ስፌ ወረዳ ይባል ነበር፤ አሁን ጦሳ ወረዳ ተብሎ ተቀይሯል፡፡ ያኔ በወረዳችን መጥተው ሲያወዳድሩ አንደኛ እወጣ ጀመር፡፡ ልጁ በሙዚቃውም በስፖርቱም ጠንካራ ነው በማለት ካምፕ አስገቡኝ፡፡ መቼ ነው ይህ የሆነው? በ1976 ዓ.ም አካባቢ ነው፡፡ ካምፕ ከገባን በኋላ መማር፣ መሰልጠን ጀመርን፡፡ እዚያም ማሸነፍ ሆነ ስራዬ፡፡ መጨረሻ ላይ ፍስሃ የሚባል ሰው “ጐበዝ አትሌት ስለሆንክ ኢንስፔክተር ትዕዛዙ ውብሸት ከሚባል አሰልጣኝ ጋር ላስተውዋቅህ” አለኝ፡፡ በትልቅ ደረጃ ላይ የሚገኝ ሰው ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊም መሬት ሸልመውታል፡፡ በወቅቱ የወጣቶችና ስፖርት ክፍል ኃላፊ ነበር፡፡ እኔ ደግሞ ፈርቼ እምቢ አልኩኝ፡፡ በኋላ ትዕዛዙ ራሱ ተዋወቀኝና “ምን መሆን ትፈልጋለህ?” ብሎ ጠየቀኝ “እኔ በህይወቴ መሆን የምመኘው ፖሊስ ነው፤ ፖሊሶችን በጣም እወዳለሁ” አልኩት፡፡ ለምን ነበር የምትወዳቸው? ይሄ ጃምቦ የሚመስል ትልቅ ኮፍያቸውን ሲያደርጉ በጣም ደስ ይሉኛል፡፡ እናም በወር 30 ብር ደሞዝ ላግኝ እንጂ ምንም አልፈልግም አልኩኝ፡፡

ለካስ ቤት ኪራይ አለ፣ ምግብ አለ፣ መታመም አለ፤ ያንን 30 ብር ምን ላደርገው ነበር እያልኩ አሁን ሳስብ ያስቀኛል፡፡ በቃ ትዕዛዙ “በቃ በርታ፤ ስፖርትህን አታቋርጥ፤ በደንብ ስራ” አለኝ፡፡ ከዚያስ? ከዚያማ በ1979 የሰራዊቱ የስፖርት በዓል በአዲስ አበባ ይካሄድ ነበር፡፡ ትዕዛዙ ያኔ ተመልምሎ አርሲ ሄዷል፡፡ እኔ ገና ሰሬ ወረዳ ውስጥ ነበርኩኝ፤ እድሜዬም ገና ነበር፤ በዚህ በአገር አቀፍ የስፖርት በዓል ላይ እሱ አርሲን ወክሎ ሄዶ ነበር፡፡ ስድስት ወር ያህል ቀድሞ አዲስ አበባ ገብቷል፡፡ በስፖርቱ ለመሳተፍ ግዳጃቸውን ፈፅመው የተመለሱ አንድ ሺህ ሰራዊት፣ እንደገና ከዚያው አካባቢ የተመለሱ ስድስት መቶ ተሳታፊዎች ነበሩ፡፡ “ከ1600 ሰራዊት የሚበልጥ፣ ከእነሱ ሁሉ አንደኛ የሚወጣ ወርቁ ቢቂላ የሚባል አትሌት አመጣለሁ” አለ፡፡ “እንዲህ የምትለው ከስልጠና ለመሸሽ ነው፤ እሱ ከተሸነፈ አንተ ትባረራለህ” አሉት፡፡ “ግዴላችሁም ልባረር” አለና እኔ ጋ መምጫ ብር አጥቶ፣ ከጓደኞቹ አንድ አንድ ብር ለቃቅሞ በ10 ብር እኔ ጋ መጣ፡፡ ካምፕ መጥቶ “ወርቁን ፈልጉልኝ” አለ፤ ገና እንዳገኘሁት “በል ልብስህን ያዝና ተነሳ” አለኝ፤ “ለምን?” ስለው “ፖሊስ ላደርግህ ነው” አለኝ፡፡ ያኔ ምን እንደተሰማህ ታስታውሳለህ? በደንብ እንጂ! ቀላል አስታውሳለሁ! ማመን አቃተኝ፤ የምይዝ የምጨብጠውን አጣሁ፡፡ ካምፕ ውስጥ መንግስት የሰጠኝን ልብስ በሙሉ ፀጋዬ ለሚባል ጓደኛዬ “ከመጣሁ መጣሁ፣ ካልመጣሁ የት እንደሄደ አላውቅም ብለህ ልብሱን ብቻ አስረክብልኝ” አልኩት፡፡

ተመልሰህ ወደ ካምፕ የመምጣት ሃሳብ ነበረህ እንዴ? አይ… ምናልባት በጤና ምርመራ ወይም ሌሎች መስፈርቶችን ላላሟላና ልመለስ እችላለሁ በሚል ጥርጣሬ ነው፡፡ ከዚያ ወደ አዲስ አበባ መምጫ ብር ከየት ይምጣ! በሌሊት ዶሮ ሲጮህ ተነሳንና እናቴ ቤት ጅማታ ሎዴ ጉዞ ጀመርን፡፡ ምክንያቱም 20 ብር ያስፈልገናል፡፡ መንገዱ አራት ሰዓት ያስኬዳል፤ ገደላገደል አለው፤ አስቸጋሪ መንገድ ነው፡፡ አንዲት ሸራ ጫማ ነበረችኝ፡፡ እሱ ደግሞ መንግስት የሰጠው ቆዳ ጫማ ነበረው፡፡ ያ ፖሊስ ቤት የተሰጠው ጫማ እንዳይቆሽሽና በአስቸጋሪ መንገድ እንዳይቀደድ አወለቀና የእኔን ሸራ ሰጥቼው፣ እኔ በእግሬ ሆኜ ጉዟችንን ቀጠልን፡፡ እሾሁ፣ ድንጋዩ እግሬን እየጋጠኝ፣ አይደረስ የለም ጠዋት አንድ ሰዓት አካባቢ ደረስን፡፡ ብሩን አገኘህ? እህቴ በወቅቱ ቡና ትነግድ ነበር፡፡ ከእሷ ወሰድኩ፡፡ ትንሽ አረፍንና በሁሩታ በኢተያ አድርገን አዲስ አበባ ገባን፡፡ ከዚያ ማሰልጠኛ ገባሁ፤ ጥቂት እንደቆየን ማጣሪያ ውድድር ተባለ፡፡ ኢንስፔክተር ትዕዛዙ እንደነገርኩሽ፣ ቀልጣፋና ተግባቢ በመሆኑ፣ ምልመላ ፖሊሶችም ሆኑ ኃላፊዎቹ ይወዱታል፡፡ ማጣሪያ ሲባል ተጠራጠረኝ፤ ምክንያቱም “እሱ ከተሸነፈ ትባረራለህ” ተብሏል፡፡ ያኔ ፖሊስ ቤት የመግባት እድል ጠባብና ከባድ ነበር፡፡ እኔ ላይ ጥርጣሬ ሲያድርበት ለማጣሪያ የሚወዳደሩትን ጠዋት ከባድ ልምምድ ሰጥቶ አደከማቸው፡፡ ከሰዓት ማጣሪያው ሆነ፡፡ ባለስልጣኑ ሁሉ ወጣ፣ ሰራዊቱ ተደረደረ፣ ሜዳዋ ጠባብ ስለነበረች ለ1500 ሜትር ስምንት ዙር ነው የምትሮጪው፡፡ ሲጀመር ፈትለክ ብዬ ወጣሁና ደርቤ ደርቤ አንደኛ ወጣሁ፡፡ ጭብጨባው ቀለጠ፤ ያኔ ትዕዛዙን “ሼባው” ነው የሚሉት፣ “የሼባው ልጅ አንደኛ” እያሉ ጮሁ፡፡ አሸነፍኩ፡፡ የመጣንበት የትራንስፖርት ታስቦ ተሰጠን፡፡ ደስታ በደስታ ሆንን እልሻለሁ፡፡ አንተ ግን ያን ጊዜ ያሸነፍከው በሙስና ነው ማለት? እንዴት? ምክንያቱም ከሰዓት በኋላ ማጣሪያው እንደሚካሄድ ሲያውቅ ትዕዛዙ ስልጣኑን ተጠቅሞ ተፎካካሪዎችህን በልምምድ ስላደከማቸው ነው ያሸነፍከው (ሳ…ቅ) በእውነት እልሻለሁ፤ በልምምድ ባይደክሙም እምቅ ጉልበት ስለነበረኝ አሸንፋቸው ነበር፡፡ በእርግጠኝነት ነው የምነግርሽ በዚያን ወቅት እንደ ንፋስ ነበር የምበረው፡፡ እሺ ከማጣሪያው በኋላ ምን ሆነ? ከዚያማ ኦሜድላ ስፖርት ገባን፡፡

የጤና ምርመራ አደረግን፡፡ በምርመራው ወቅት ሲያዩኝ “ስፖርተኛ ነህ አይደል?” አሉኝ፤ “አዎ” አልኳቸው፡፡ “በቃ አንተ የሰራዊታችንን ስም ታስጠራለህ፤ ሰራዊታችንን ብቻ ሳይሆን ለአገራችንም ትልቅ ነገር ታደርጋለህ፤ በርታ ውጤት እንጠብቃለን” አሉኝ፡፡ በቃ ፖሊስ ሰራዊት ውስጥ መግባቴን አረጋገጥኩኝ፡፡ በፕሮፌሽናል ደረጃ ለመጀመሪያ ጊዜ የሮጥክበትን መድረክ እስኪ አስታውሰኝ ከዚያ በፊት ልነግርሽ የምፈልገው ትዕዛዙ ቀድሞ ስድስት ወር ስልጠና ገብቶ ስለነበር ስልጠናውን ጨርሶ ወጣ፤ እኛ ገና ስድስት ወር ይቀረናል፡፡ ስለዚሀ አርሲ ሆኖ በመደወል “አትሌት ወርቁ ቢቂላ ጎበዝ እና ጠቃሚ በመሆኑ ወደ አርሲ እንዲዛወርልን” በማለት ጥያቄ አቀረበ፡፡ ወዲያው ስልጠናው እንደተጠናቀቀ ሃላፊው “ወደ አርሲ ይዛወር” ብለው ፈቀዱ፡፡ የዚያኔ የደርግ ዘመን ጦርነት ስለነበረ ወይ ወደ አንዱ ግንባር ዘምቼ ሞቼና ተረስቼ እቀር ነበር፤ አሊያም አካል ጉዳተኛም ሆኜ ልኖር እችል ነበር፡፡ በትዕዛዙ ምክንያት ወደ አርሲ ሄጄ የፖሊስ አትሌት ሆኜ ቀጠልኩኝ፡፡ የትምህርትህስ ጉዳይ? ትምህርት እስከ 8ኛ ነበር የተማርኩት፡፡ አርሲ ፖሊስ ስገባ ትዕዛዙ የማታ ተማር አለኝ፡፡ እኔ ደግሞ “እንዴት አድርጌ እማራለሁ” አልኩት፤ ምክንያቱም ገና ከፖሊስ ስልጠና ስትወጪ ጥበቃ ነው የምትሰሪው፡፡ “ጥበቃ ሰርቼ፣ ሩጫ ሮጬ እንዴት ትምህርት ማታ እማራለሁ” አልኩት፡፡ “ጥበቃውን ከእኔ ጋር አንድ ሽፍት እናደርግና የአንተንም አደር እየጠበቅሁ እረዳሃለሁ፤ አንተ ብቻ ትምህርትህን ቀጥል” አለኝ፡፡ አሰላ ጭላሎ ት/ቤት እስከ 11ኛ ክፍል ትምህርቴን ተከታተልኩኝ፡፡ አግደው ወልዴ የሚባል የጥበቃ ኃላፊ ነበር “አይዞህ አንተን አሳድገን አንድ ነገር ላይ እናደርስሃለን ይለኝ” ነበር፡፡ ብቻ ድጋፋቸው በጣም አበረታታኝ፡፡ ትዕዛዙ ደግሞ አሰላ ቤተሰብ ስለነበረው ወንድሙ ቤት እንድቀመጥ አድርጐ ከምግብ ጀምሮ በእንክብካቤ ያኖረኝ ጀመር፡፡ ሁሉን ነገር ትቼ ሩጫዬ ላይ አተኮርኩኝ፤ ከዚያ የኢትዮጵያ አየር መንገድ ፕሮጀክት ስለነበረ፤ እዛ ገባሁ፡፡ እዚያ በሶስት ወር ሶስት መቶ ብር ይሰጡናል፡፡

የፖሊስ ደሞዝ ደግሞ 137 ብር ነበረ፡፡ በቃ ሃብታም ሆንን፡፡ ሶስት መቶ ብር ብዙ ነው ያን ጊዜ፡፡ እኔ፤ ሃይሌ ገ/ሥላሴና ሌሎች አትሌቶች ከዚህ ፕሮጀክት ነው የወጣነው፡፡ የፖሊስ አትሌቶችም ሆነን በአየር መንገድም ታቅፈን ነበር፡፡ በዚህ መልኩ ስንሰለጥን ከቆየን በኋላ በ1983 ዓ.ም ኢህአዴግ ገባ፡፡ በወቅቱ ስፖርቱም ሁሉም ብትንትኑ ወጣ፡፡ የለውጡ ሂደት ሲረጋጋ የስፖርቱ ሂደት መቀጠል አለበት ብለው ኢህአዴጎች ስፖርቱን መልሰው አቋቋሙት፡፡ ተበትናችሁ በነበረበት ሰዓት ምን እየሰራህ አሳለፍክ? ይገርምሻል፤ ተበትነንም እኔ ስፖርት መስራቴንና ሩጫ መሮጤን አላቆምኩም፡፡ እናቴም በሶና የተለያዩ ምግቦች እየላከችልኝ፣ ትእዛዙ ውብሸትም እየረዳኝ ልምምዴን ቀጥዬ ነበር፡፡ ከለውጡ በኋላ የመጀመሪያ ፕሮፌሽናል ውድድሬን ያደረግሁት ሃዋሳ ላይ ነበር፡፡ ውድድሩ የ21 ኪ.ሜትር (ግማሽ ማራቶን) ነበረ፡፡ በመሰረቱ የእኔ የሩጫ ዘርፍ አጭር ርቀት ነበር፤ 800፣1500 እና 5000 ሜትር ላይ ነው የምሮጠው፡፡ ሃዋሳ ላይ ስሄድ ትእዛዙ “ታሸንፋላችሁ አይዟችሁ” አለንና ተወዳደርን፡፡ ፊሽካ ተነፋ፡፡ እኔ 21 ኪ.ሜትር ርቀት ተወዳድሬ አላውቅም፤ ግን ሸክሽኬ ሸክሽኬ አፈትልኬ ስወጣ፣ ትዕዛዙ ሳይክል ተከራይቶ ይከተለን ነበር፡፡ በምልክት “አይዞህ” አልኩት፡፡ ይገርምሻል ትዕዛዙ ሰው ሲሞት እንኳን አያለቅስም፡፡ በቁም እያለ መርዳት ያለበትን ይረዳል፣ ያስታምማል፤ ያንን አልፎ ከሞተ “ምንም ማድረግ አይቻልም” ባይ ነው፡፡ “አይዞህ አሸንፋለሁ” የሚለውን ምልክት ስሰጠው አለቀሰ፡፡ አንደኛ ወጥቼ አሸነፍኩኝ፡፡ ከዚያ ፖሊስ ኦሜድላ መግባት አለብህ አለ፡፡ አሰላ ፖሊስ ደግሞ አንለቀውም አሉ፡፡ “ከኦሜድላ ሁለት ወታደር እንሰጣችኋለን፤ ወርቁን ስጡን” አሉ፤ ከዚያ በሁለት ፖሊስ ተቀይሬ ኦሜድላ ገባሁ እልሻለሁ፡፡ የኦሜድላ ፖሊስ ቆይታህ ምን ይመስል ነበር? ኦሜድላ ደግሞ ሃይለኛ ሃይለኛ ልጆች ነበሩ፡፡ ያኔ ሃይልሻ (ኃይሌ ገ/ሥላሴ) ብሄራዊ ቡድን ገብቶ ነበር፡፡

“እባክህ ብቻዬን ሆኛለሁ፤ ቶሎ ወደ ብሄራዊ መጥተህ ተረዳድተን እንስራ” ይለኝ ነበር፡፡ ኦሜድላ እያለሁ ብሄራዊ ቡድን እንድገባ ትዕዛዙ በጎን ጥረት ጀመረ፡፡ እሱ ይጥራል፤ እኔ በውጤት እያሸነፍኩ እደግፈዋለሁ፡፡ ከዚያ ኢትዮጵያ ሻምፒዮን ውድድር ተደረገ፡፡ በአምስት ሺህ አንደኛ ወጣሁ፤ በ10 ሺህ ሁለተኛ ወጣሁ፡፡ 10ሺውን አሸንፌያለሁ ስል አንዱ አንገቱ ብቻ ቀድሞኝ ሁለተኛ አልወጣ መሰለሽ፡፡ ተበሳጭቼ ልሞት! እንደ ኃይሌና ፖልቴርጋት አገባብ ማለት ነው? ትክክል፡፡ እንደዚያ አይነት መሸነፍ ነው የተሸነፍኩት፡፡ ገርባ በትቻ የሚባል የአምቦ ውሃ ልጅ ነው ያሸነፈኝ፡፡ ከዚያ ብሄራዊ ቡድን ገባሁ፤ ይህ እንግዲህ በ1984 ዓ.ም መሆኑ ነው፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ ውጭ አገር የተወዳደርከው የት ነው? ውጤትህስ? ቦስተን የዓለም አገር አቋራጭ (Cross Country) ውድድር ላይ ተሳተፍኩና በጣም የሚያስቅ ውጤት አመጣሁ፡፡ 90ኛ ወጣሁ (በጣም እየሳቀ…) በረዶው እስከ ቅልጥምሽ ይደርሳል፡፡ እኔ በእንደዚህ አይነት አየር ላይ ተወዳድሬም እንዲህ አይነት የአየር ንብረት አይቼም አላውቅም፡፡ ሃይልሻም አልቀናውም፡፡ ወደኔው አካባቢ ነው ውጤቱ፡፡ ያኔጥሩ የነበረው ፊጣ ባይሳ ነው፡፡ ደራርቱም ጥሩ ነበረች፡፡ ሃይሌ ገ/ሥላሴ 100 ሺህ ብር እንደ ሸለመህ ሰምቻለሁ፡፡ ለምን ነበር የሸለመህ? በፈረንጆቹ 1994 አካባቢ ይመስለኛል፡፡ ከሃይልሻ ጋር አብረን ሮጠናል፤ ማናጀራችንም አንድ ነበር፡፡ በወቅቱ በነበረው ውድድር ሃይሌ ሪከርድ መስበር አላሰበም፡፡ እኔ አፌ ላይ መጣብኝና “ሃይልሻ አብሬህ ልሂድና ልወዳደር ሪከርድ እንሰብራከን አልኩት፡፡ ውድድሩ ሆላንድ ሄንግሎ ውስጥ ነበር፡፡

“ያንተ ውድድር ጣሊያን ሮም ውስጥ ነው፤ ሄንግሎ ውስጥ ሆቴልም የለህም አልተያዘልህም” አሉኝ፡፡ “እኔ ምንም አልፈልግም፤ ሆቴል ብቻ ያዙልኝ፤ ገንዘብም ምንም አልፈልግም፤ ግን ሪከርድ እንሰብራለን” አልኩት፡፡ ተሳካ ታዲያ? ሃይሌ ያኔ እንዳሁኑ ፈረንጅ አልሆነም፤ እንግሊዝኛ ትንሽ ትንሽ ይችል ነበር፤ ለማናጀሩ ሃሳቤን ነገረው፤ እኛ እንግሊዝኛ “Yes” እና “No” ብቻ ነበር የምንችለው፤ እርግጥ የሚናገሩት ይገባናል፤ መመለስ ላይ ነው ችግሩ (ሳ…ቅ) ሄድን ተወዳደርን፤ አሪፍ የቡድን ስራ ሰራን፤ ሪከርድ ሰበርን፡፡ ውድድሩ የ10 ሺህ ሜትር ነበር፤ ሃይሌ ሪከርድ ሰበረ፡፡ ብር የለም የተባልኩት ሰውዬ ማናጀሩ ተደስቶ 5ሺህ ዶላር ለቀቀብኝ፡፡ መቶ ሺህ ብር ተሰጠኝ ማለት ነው፡፡ የሚገርምሽ በሶስተኛው ቀን ሮም ላይ ውድድር አለኝ አላልኩሽም፡፡ ሮም ላይ እሱ ሆላንድ ሄንግሎ ያስመዘገበው ሪከርድ ተሰበረበት፤ ተናደድኩ፤ አበድኩ በቃ ምን ልበልሽ … ሪከርዱ ስለተሰበረ ነው? አዎ … እኔ ባለሁበት እንዴት ይሰበራል ብዬ ነዋ! እኔ ሶስተኛ ወጣሁ፤ የእኔ ውጤት በእለቱ በአምስት ሺህ ሜትር ከዓለም አራተኛ ሆኖ ተመዘገበ ሃይሌ በሩጫው አልተሳተፈም፡፡ እዚያው ሆላንድ ቀረ፤ ግን በቴሌቪዥን ውድድሩን ይመለከት ነበር፡፡ በጣም ተደሰተ፤ ሆላንድ ስገባ “ዝነኛ ሆንክ ኮንግራ” አለኝ፡፡ “በቃ ሌላ ጊዜ ሪከርዱን እንሰብራለን” አለኝ “እሺ እንሰብራለን” ተባብለን ወዲያው ስዊዘርላንድ ዙሪክ ላይ ሪከርድ ሰበርን፡፡ ተዓምር ሰራን፡፡ ከዚህ ሁሉ ድል በኋላ ነው ሃይልሽ 100ሺህ ብር የሰጠኝ፡፡ ጎልደን ሊግ ላይም ተወዳድረሃል ሲባል ሰምቻለሁ … በዚሁ በ1994 ዓ.ም ለአትላንታ ኦሎምፒክ ሚኒማ ለማምጣት ልሞክር ብዬ ነበር የገባሁት፡፡ እኔ፤ ዳንኤል ከመን፤ ፖልቱርጋርና ሌሎችም ነበሩ፡፡ እነዚህ ሰዎች ትልቅ ደረጃ ላይ ያሉ ሯጮች ናቸው፤ በ10ሺህ ሜትር ነው፡፡

እኔ ለሚኒማ ነው የሮጥኩት፡፡ ሩጫው ተጀመረ፤ እጅብ ብለን እንሮጣለን፤ የሚመራውን እግር እግር ስከተል ስምንት መቶ ሜትር ላይ ስደርስ ተለይቼው ወጣሁ፡፡ ጎልደን ሊግ ትልቅ ውድድር ነው፤ ወርቅ ከሚያስገኙ ሰባት ውድድሮች አንዱ ጀርመን ስቱትጋርት ውስጥ አንዱን ማርቼሊስ ከሃይሌ ጋር የበላው እስማኤል ኩሪ የተባለ ሯጭም አለ፡፡ ዳንኤል ኮመንን ደረብኩት እና በዚህ ጎልደን ሊግ አንደኛ ወጣሁ፤ ጩኽት ቀጠለ… ምን ልበልሽ… በዚህ ውድድር አሸናፊነትህ የተነሳ በጥሩ ብር ከአዲዳስ ኩባንያም ጋር ለማስታወቂያ መፈራረምህን ሰምቻለሁ እውነት ነው? እውነት ነው፤ ከውድድሩም ከማናጀሬም ጥሩ ገንዘብ አግኝቼያለሁ፡፡ በተጨማሪም ከአዲዳስ ኩባንያ ጋር ለሶስት ዓመት ማስታወቂያ ተፈራርሜ ነበር፡፡ ጫማ ብትይ ልብስ እስካሁን የምለብሰው የአዲዳስን ምርቶች ነው፡፡ ምን ያህል ዶላር ነበር በዓመት የተፈራረምከው? እነሱ ምን ያህል እንክፈልህ አሉኝ፤ 25 ሺህ ዶላር በዓመት አልኳቸው፤ የኩባንያው ኃላፊ “Is it enough?” አለኝ “Yes it is enough” አልኩት በኋላ “It is no not enough” አለኝ “so how much” አልኩት “60 ሺህ ዶላር እንከፍላለን” አለኝ፡፡ “በሶስት ዓመት 180 ሺህ ዶላር ታገኛለህ፤ በዚህ ተስማምተህ ፈርም” አሉኝ፤ ፈረምኩ፡፡

ፈረንጅ አሪፍ ነው፤ ሌላው ቢሆን እኛ ምን አገባን ብለው በ25 ሺህ ያስፈርሙኝ ነበር፡፡ የሩጫ ጫማህን የሰቀልከው መቼ ነው? ማራቶን ፓሪስ ላይ ከሮጥኩ በኋላ 8ኛ ወጣሁ፡፡ በእርግጥ የመጀመሪዬ እንደመሆኑ በዚያው መቀጠል ነበረብኝ ግን ብዙ ዓመት ስለሮጥኩ ከአገር ቤት ጀምሮ ቆይ ትንሽ ልረፍ አልኩኝ፡፡ በቃ በዛው አቆምኩኝ፤ ወቅቱ በፈረንጅ 2002 ዓ.ም አካባቢ ይመስለኛል፡፡ ብዙ አትሌቶች እና ታዋቂ ሰዎች ስኬት ላይ ሲደርሱ ህንፃም ሆቴልም የሚሰሩት በትውልድ አካባቢያቸው ነው፡፡ አንተ ሆቴል የከፈትከው ዱከም ከተማ ነው እንዴት ነው? አንድ ጓደኛ አለኝ ብርሃኔ ሚደቅሳ ይባላል፤ የሆለታ ልጅ ነው፤ ብዙ ነገሮችን የሚያማክረኝ እሱ ነበር፤ ከውድድር ስመለስ ላዝናናህ አየር ቀይር ብሎኝ ዱከም ይዞኝ መጣ፡፡ ድሮም አካባቢውን እወደው ነበር፡፡ ነገር ግን እኔ ሃሳቤ አዲስ አበባ ውስጥ ክትፎ ቤት ለመክፈት ነበር፡፡ ብርሃኑ ያልኩሽ ጓደኛዬ ለምን እዚህ (ዱከም) ሆቴል አትከፍትም አለኝ፡፡ በል ቶሎ ደላላ ፈልግና ቦታ ይፈለግ አልኩት፤ መጀመሪያ ቤት ሂድና ከባለቤትህ ጋር ተማከር አለኝ፤ ግዴለም አሳውቃታለሁ ትስማማለች አልኩት፡፡ በኋላ አሁን ሆቴሉ ያረፈበትን ቦታ ገዛሁ፡፡ ለካ ያኔ በነፃ ሁሉ ማግኘት እችል ነበር፤ ቦታ እየገዛሁ እየገዛሁ አስፋፋሁ እስኪ ስለቤተሰብህ ንገረኝ? ጥሩ ትዳርና ቤተሰብ አለኝ፡፡ አራት ልጆች አሉኝ፡፡ የመጀመሪያው ልጄ የ17 ዓመት ልጅና የ10ኛ ክፍል ተማሪ ነው፡፡ አንደኛው ወደ ስምንት አልፏል፤ ሴትም ልጅ አለችኝ፤ የመጨረሻው ህፃን የሁለት ዓመት ነው፤ ልጆቼ ጥሩና ጨዋ ናቸው፡፡

አሁን ጤናህ እንዴት ነው? ጤናዬ ጥሩ ነው፤ ደስተኛ ሆኜ ነው የምኖረው፡፡ ለስፖርት ፍቅር ላላቸው የአቅሜን እደጉማለሁ፡፡ መርዳት ያለብኝን እረዳለሁ፡፡ ቢዝነስ ላይ ነኝ፤ በጣም በጥሩ ሁኔታ ነው የምኖረው፡፡ የእሬቻ በዓል ከደብረዘይት ቀጥሎ አንተ ሆቴል ውስጥ በድምቀት ይከበራል ይባላል፡፡ እውነት ነው? የእሬቻ በዓል ጊዜ መጥተሸ ብታይ ጉድ ነው የምትይው፡፡ አካባቢው በሰው ይሞላል፤ የሙዚቃ ባንድ አለ፤ የከተማው ሰው ይመጣል፤ የአገር ሽማግሌዎች፣ የገዳ ስርዓት መሪዎች ሳይቀሩ ይታደማሉ፡፡ በልዩ ድምቀት ይከበራል፡፡ በቀጣይም የመስቀል በዓል በዋለ በቀጣዩ እሁድ ይካሄዳል፤ በጣም አስደሳች በዓል ነው፡፡ አባ ገዳ ሆነህ ልትሾም ነው ሲባል ሰምቻለሁ ሰምተሽ ይሆናል፡፡ እሱን ከአካባቢው የአገር ሽማግሌዎችና ከስርዓቱ መሪዎች ብትጠይቂ ይሻላል፡፡ አሁን እሱን ለመናገር ጊዜው አይደለም፤ የሚሆነውን አብረን እናየዋለን፡፡ በተረፈ በሁሉ ነገር ደግፎ አይዞህ ብሎ መንገዱን ምቹና ቀና ላደረገልኝ ኢንስፔክተር ትዕዛዙ ውብሸት ታላቅ አክብሮትና ፍቅር አለኝ፤ ዘመኑ ይባረክ እላለሁ፡፡ ሻለቃ ሃይሌ ገ/ሥላሴንም አመሰግናለሁ፤ ሃይልሻ ጠንካራና ምሳሌ የሚሆን ሰው ነው፡፡ በተረፈ ለሁላችንም እድሜና ጤና ይስጠን፡፡ አገራችንን ከክፉ ይጠብቅልን እላለሁ፤ አመሰግናለሁ፡፡

          ለአመታት ያላቋረጠው የአገራችን የፖለቲካ ድራማ፣ ዛሬም ከአዙሪት የመላቀቅ ምልክት አይታይበትም። ሰሞኑን በስፋት የተሰራጩ ሁለት ወሬዎችን ብቻ እንመልከት። አንደኛው ወሬ፣ በኢህአዴግ ባለስልጣናት ላይ ያተኮረ ነው። ሌላኛው ደግሞ በግል ጋዜጦችና መፅሔቶች ላይ ያነጣጠረ።
በእርግጥ ወሬዎቹ እንደ ትኩስ “ዜና” ቢሰራጩም፣ አዲስ “መረጃ” አይደሉም። ከነጭራሹ የመረጃ ሽራፊ እንኳ የላቸውም። “የግል ጋዜጦችና መፅሔቶች፣ ከተለያዩ የውጭ ሃይሎች ወይም ከተቃዋሚ ፓርቲዎች የገንዘብ ድጋፍ ያገኛሉ” እየተባለ በመንግስት ሚዲያ ሲነገር ሰምታችሁ አታውቁም? በተደጋጋሚ ተወርቷል። ከሰሞኑም እንደገና ተከልሶ እንደ አዲስ ሲወራ ሰንብቷል። ግን፣ የትኛው ጋዜጣና መፅሔት መቼ፣ ምን ያህል ገንዘብ ከማን እንደተቀበለ በግልፅ አይልተጠቀሰም። ተጠቅሶም አያውቅም። ተጨባጭና ግልፅ መረጃ ይቅርና፣ ጠቋሚ መረጃ እንኳ ለማቅረብ አልተሞከረም። ጭፍን ውንጀላ ብቻ!
ሁሉም የግል ጋዜጦችና መፅሔቶች ከነውር ንፁህ ናቸው ማለቴ አይደለም። አንዳንዶቹ ንፁህ ላይሆኑ ይችላሉ። ነገር ግን፣ “ነውር ይፈፅማሉ፣ የተቃዋሚ ፓርቲ ልሳን ናቸው” በማለት ያለ አንዳች መረጃ በተደጋጋሚ ወሬ ማሰራጨት ግን፣ ከተራ የስም ማጥፋት ወይም የስም ማጉደፍ ዘመቻ አይለይም። ታዲያ ለምን የመንግስት ሚዲያና የኢህአዴግ ደጋፊዎች ይህን መረጃ አልባ ወሬ ያሰራጫሉ? ያው... ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ለማሳጣትና ለማብጠልጠል፣ እንዲሁም ዜጎችንና ጋዜጠኞችን ለማስፈራራት እስካገለገለ ድረስ፣ የሃሰት ወሬ ማሰራጨት ችግር የለውም - ለጭፍን የገዢ ፓርቲ ደጋፊዎች።
ሁለተኛው ወሬም እንዲሁ ያለ ምንም ተጨባጭ መረጃ ነው የተሰራጨው - በጭፍን ተቃዋሚዎች። “በርካታ የኢህአዴግ መሪዎችና ባለስልጣናት በአለማቀፍ የወንጀል ፍርድ ቤት (አይሲሲ) ተከሰሱ” የሚለው ወሬ እንደካሁን በፊቱ ባለፉት ቀናትም በብዛት ተሰራጭቷል። ወሬው ሲሰራጭ፣ “እስቲ በፍርድ ቤቱ (በአይሲሲ) ድረገፅ ላይ መረጃ ካለ ለማየት እንሞክር” የሚል ሰው አልተገኘም።
በፍርድ ቤቱ አሰራር፣ ከክስ በፊት መደበኛ ምርመራ ይካሄዳል። ከመደበኛ ምርመራ በፊት ደግሞ መነሻ ፍተሻ አለ። በተለያዩ አገራት፣ በርካታ መንግስታትና ባለስልጣናትን እንዲሁም ታጣቂ ድርጅቶችንና እንደ ኢራቅ አሸባሪዎች የመሳሰሉ ቡድኖችን በተመለከተ ምርመራና ፍተሻ እያካሄደ እንደሆነ አይሲስ በድረ ገፁ ይዘረዝራል። ግን፣ በአገራቱ ዝርዝር ውስጥ የኢትዮጵያ ስም አልተጠቀሰም። እና ለምን፣ ወሬው ያለ መረጃ ተሰራጨ? ያው... ገዢውን ፓርቲ ለማጥላላት፣ ለማንቋሸሽ እስካገለገለ ድረስ ችግር የለውም።
በየጎራው የተቧደኑት ጭፍን ፊታውራሪዎችና ቲፎዞዎች፤ በየፊናቸው የሚያሰራጩት የወሬ አይነት ይለያያል። ነገር ግን፣ በባሕሪያቸው በጣም ተመሳሳይ ናቸው። “ተቀናቃኝ ወገንን ለመወንጀል የሚያገለግል እስከሆነ ድረስ፤ ተጨባጭ መረጃ ሳያስፈልግ ማንኛውንም ወሬ ማሰራጨት ይቻላል” በሚለው ሃሳብ ይስማማሉ። ዛሬ የሚያሰራጩት ወሬ፣ ውሎ አድሮ ሃሰት እንደሆነ ቢታወቅ እንኳ፣ ያን ያህልም አያሳስባቸውም። “የሃሰት ወሬ የተሰራጨው ለበጎ አላማ ስለሆነ አያስነውርም” ብለው ያስባሉ። ምን አይነት በጎ አላማ? “ለአገር እድገትና ልማት፣ የአገርን ክብር ለመጠበቅና የአገርን ገፅታ ለማሳመር፣ የድሃውና የሰፊውን ሕዝብ ጥቅም ለማስከበር” ሲባል ነው ወሬው የተሰራጨው በማለት ማመካኛ ያቀርባሉ። “ለብሔር ብሔረሰብና ለባህል በመቆርቆር፣ ለሃይማኖት ቀናኢነትን ለማሳየትና የአምላክን ትዕዛዝ ለማስፈፀም በማሰብ ነው ወሬው የተሰራጨው” በማለትም ራሳቸውን ያሳምናሉ።

በነሱ ቤት፣ ለበጎ አላማ የሃሰት ወሬ ማሰራጨት መደበኛ የሕይወት ዘይቤ ነው።
በአሳዛኙ ነገር ምን መሰላችሁ? የበጎ ነገሮች ሁሉ ምንጭ የሆነውን ነገር እየናዱት ነው - ማለትም እውነትን ዋጋ እያሳጡ የእውነትን ክብር እያረከሱ ናቸው። በፖለቲካ ጉዳይ ውስጥ ስለ “እውነት” መነጋገር፣ ከንቱ “ቲዎሪ” ሊመስል ይችላል። ስለሚመስልም ነው፣ ከአመት አመት እየተደናበርን ከአዙሪት መውጣት ያቃተን። ዋናውን ቁልፍ ችላ ብለን ከተውነው፣ እንዴት ብለን መንገዳችንና መድረሻችን እናውቃለን። ለ“እውነት” ታላቅ ክብር የማይሰጥ ባህል ውስጥ፣ መቼም ቢሆን በጎ ለውጥ ሊፈጠር አይችልም። ለእውነት ክብር ከሌለን እንዴት ልንግባባ እንችላለን? ተቀናቃኛችን፣ የቱንም ያህል አስተማማኝ መረጃ ቢያቀርብ፣ ከመጤፍ አንቆጥረውም። በተቃራኒው፣ ምንም መረጃ ሳይኖረን ተቀናቃኛችንን የሚያሳጣ ወሬ እናወራለን - በዙሪያችን የተሰባሰቡ ቲፎዞዎች በጭፍን እንደሚያጨበጭቡልንና ወሬውን እንደሚያራግቡልን እርግጠኛ ነን። ለነገሩ፣ ትክክለኛ መረጃ ሰብስበን ብናቀርብን፣ ተቀናቃኛችንና ቲፎዞዎች፣ ለሴኮንድ ያህል የመስማት ፈቃደኛ አይሆኑም። አልቧልታ እየነዙና እየተቀባበሉ ያስተጋባሉ እንጂ።

“መውጪያ የሌለው አዙሪት” ይሉሃል ይሄ ነው። ታዲያ ይሄ በጎ ነው? በየጎራችን “ለበጎ አላማ” በማሰብ የምናሰራጨው አሉባልታ፣ እንደምታዩት የመጨረሻ ግቡ “ፋታ የለሽ መናቆር” እንደሆነ ተመልከቱ።
ለዚህም ነው፤ በአገራችንም ስለ ኢትዮጵያና ስለ ኢትዮጵያውያን ቀን ከሌት እያወራን መወዛገባችን፣ ክረምት ከበጋ እየተናቆርን መጠማመዳችን፣ መሻኮታችንና መጠላለፋችን ሊያስገርመን የማይገባው። በእርግጥ፣ አብዛኞቹ ፓርቲዎችና ፖለቲከኞች ስለ ኢትዮጵያ እየተናገሩ የሚወዛገቡትና የሚናቆሩት ለምን እንደሆነ ብትጠይቋቸው፣ መልሳቸው ተመሳሳይ ነው። በየጎራቸው ለአገሪቱ በጎ ለውጥ ለማምጣት እየተጣጣሩ እንደሆነ ይነግሯችኋል። አብዛኞቹ ምሁራንና ዜጎች ስለ አገራቸው እየፃፉ የሚከራከሩት ወይም የሚሰዳደቡትስ? በየፊናቸው “በቀና መንፈስ መልካም ለውጥን ስለምንመኝ ነው” ይሏችኋል። ምን ዋጋ አለው? ለእውነት ክብር ባለመስጠት፣ የ“በጎ” ነገሮች ጠላት ሆነን እናርፈዋለን።
በፖለቲካ ጉዳዮች ውስጥ መጠቀስ ከሚገባቸው በጎ አላማዎች መካከል አንዱ፣ “ነፃነት” የሚባለው ነገር ነው - በራስህ አእምሮ የመጠቀም፣ የራስህን ኑሮ የመምራት፣ የራስህን ሕይወት የማጣጣም ነፃነት። በጥንታዊው የግሪክና የሮም የስልጣኔ ዘመናት፤ እንዲሁም በሬነሰንስ እና በኢንላይትመንት ዘመናት፣ የፖለቲካ ነፃነትና ብልፅግና ከሳይንስና ከእውቀት ጋር በጣምራ የተስፋፉት አለምክንያት አይደለም - እነዚህ ሁሉ የሚመነጩት “እውነት”ን ከማክበር ነው። የነፃነት ተቃራኒ ምንድነው ቢባል፣ በቅድሚያ የሚጠቀሱት፣ አፈናና ጭፍን ፕሮፓጋንዳ ናቸው። አሃ፣ ከመነሻው አፈናና ጭፍንነት የሚስፋፋው ለምን ሆነና? ሰዎች፣ “እውነት”ን እንዳያውቁ ወይም “ሃሰትን” እንዲቀበሉ ማድረግ ነው። በሌላ አነጋገር፣ ለእውነት ከፍተኛ ክብር የሌለው ሰውም ሆነ ፖለቲከኛ፣ ገዢም ፓርቲ ሆነ ተቃዋሚ፣ ለነፃነትም ትልቅ ክብር ሊኖረው አይችልም። እንዲያውም፤ የአቅሙን ያህል አፈናንና ጭፍንነትን የማስፈን ዝንባሌ ይኖረዋል። የትኛውም ወገን ቢያሸንፍ ለውጥ የለውም። ለምሳሌ፣ የሙስሊም ወንድማማቾችና ሆስኒ ሙባረክ፣ የሶሪያ አክራሪዎች እና በሽር አልአሳድ፣ ... የሚጣሉት አንዱ አምባገነን አፋኝ ሌላኛው የነፃነት ታጋይ ስለሆነ አይደለም። የሰዎችን ሃሳብና ንግግር ሙሉ ለሙሉ ለመቆጣጠር፣ ማለትም ተቀናቃኝ የሌለው አፋኝ ለመሆን ነው። ጉልበት ያለውና ስልጣን የያዘ አፋኝ ፓርቲ፣ ግድያ፣ እስር፣ ወከባ፣ ፕሮፓጋንዳ ይፈፅማል። ለጊዜው ስልጣን ያልያዘና ጉልበት የሌለው ፓርቲ ደግሞ ቢያንስ ቢያንስ በአልቧልታ የማሸማቀቅ፣ ስም የማጥፋት፣ በጭፍን የመፈረጅ ዘመቻ ያካሂዳል። ማለቂያ የለሹ አዙሪት የዚህ ውጤት ነው።    
በአገራችን ኢህአዴግና ተቃዋሚዎች በሁለት ጎራ ስለ ኢኮኖሚ እድገትና ስለ ድህነት የሚያካሂዱትን ውዝግብ በምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል።  “የኢትዮጵያ ዋነኛ መገለጫ... የሞት አፋፍ ላይ መሆኗ ነው” በማለት ጠ/ሚ መለስ ዜናዊ የተናገሩ ጊዜ የተፈጠረውን ውዝግብ ታስታውሱ ይሆናል። ኢትዮጵያ በድህነት ተዳክማ በልመና የምትንገታገትና የሕልውና አደጋ የተጋረጠባት መሆኗን ጠቅሰው፤ “እርዳታ ባይገኝ ስንት ሚሊዮን ሕዝብ ያልቃል? እርዳታ እንደልብ ቢገኝ እንኳ፣ ረሃብተኛው እጅግ ብዙ ሲሆን እርዳታ ማጓጓዝ ራሱ ትልቅ ፈተና ይሆናል። ከጥፋት ለመዳን መሮጥ አለብን። መፍጠን አለብን፤ ሴንስ ኦፍ ኧርጀንሲ ያስፈልጋል” የሚል ሃሳብ ነው የተናገሩት ጠ/ሚ መለስ። ይሄ ለብዙ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የሚዋጥላቸው አልነበረም።
የዜጎች ድህነት እጅግ አስከፊ ከመሆኑ የተነሳ አገሪቱ የገደል አፋፍ ላይ መድረሷ እውነት ቢሆንም፤ ብዙዎቹ ተቃዋሚ ፓርቲዎች “እውነት ብለሃል” በማለት ስምምነታቸውን አልገለፁም። “አዎ አገሬው አደጋ ላይ ነው። ግን፣ መልካም ለውጥ ለማምጣት ገዢው ፓርቲ በብቃት አልሰራም። አገሪቱን ለማሳደግ የሃሳብና የተግባር ብቃት የለህም” ብለው መከራከር ይችሉ ነበር። ግን፤ አላደረጉም። እንዲያውም፤ “ምንም አዲስ የተፈጠረ ነገር ሳይኖር መዓት ማውራት ምንድነው? ኢህአዴግ የአገርን ክብር ደፈረ፤ የአገርን ስም አጠፋ...” በማለት ገዢውን ፓርቲ አብጠልጥለውታል።
አሁን ነገሩ የተገላቢጦሽ ሆኗል። በገዢው ፓርቲ ዘንድ፣ ስለ ድህነት ማውራት፣ የአገርን ገፅታ እንደማበላሸት እየተቆጠረ መጥቷል። ተቃዋሚዎች ስለ ድህነት ሲያወሩ... ገዢው ፓርቲ “አዎ ትክክል ነው። አገራችን ድሃ ነች። ባለፉት አስር አመታት ኢኮኖሚው ከእጥፍ በላይ ቢያድግም፤ አሁንም እጅግ ድሃ ነን። ለዚህም ነው በፈጣን የኢኮኖሚ እድገት መቀጠል አለብን የምንለው” ብሎ ማስረዳት ይችላል። ግን አያደርገውም። አገሪቱ እጅጉን የበለፀገች ያስመስላል፤ ስለ ድህነት የሚያወሩትንም “ፀለምተኛ፣ ፅንፈኛ፣ ከሃዲ” በሚል እየፈረጀ ይሳደባል፤ ያስፈራራል።
ተቃዋሚዎችም፤ “አዎ፣ የኢኮኖሚ እድገት እየታየ ነው። ነገር ግን፤ አሁንም ከ13 ሚሊዮን በላይ ተረጂዎች አሉ። በማምረቻ ኢንዱስትሪ መስክ ለውጥ እየታየ አይደለም። በቂ የስራ እድል እየተፈጠረ አይደለም። መንግስት እየገነነና የግል ኢንቨስትመንት ወደ ኋላ እየቀረ ነው። የያዝከው አቅጣጫ አያዛልቅም” ብለው ማስረዳት ይችላሉ። ግን አያደርጉትም። ገዢውን ፓርቲ ለማንቋሸሽ፣ ለመሳደብ፣ በጭፍን ለመፈረጅ ይቸኩላሉ።
እናማ ሁለቱም ጎራዎች፤ ገዢው ፓርም ተቃዋሚ ፓርቲዎችም በጭፍን ስሜታዊነት ይቀጥላሉ - አንዱ ሌላውን ለማሳጣት።
ግን በጋራ የሚጠሉት ደግሞ አለ - ሚዛናዊ የሆኑ ሰዎችን። እርስ በርስ ለመናቆር ችግር የለባቸውም - ቁንፅል እውነትና ያገጠጠ ሰበብ አለላቸው። ኢህአዴግ የኢኮኖሚ እድገት እየተመዘገበ ነው ሲል እውነት ነው - የአሪቱን ድህነት እየሸፋፈነ። ተቃዋሚዎች፣ ስለ ድህነትና ችግር የሚናገሩት ነገር እውነት ነው - ስለ ኢኮኖሚ እድገት እየዘነጉ። “እንዴት የህዝቡን ድህነት ትክዳለህ?”፣ “እንዴት የኢኮኖሚ እድገቱን ትክዳለህ?” እየተባባሉ ይናቆራሉ።
“ድህነትም አለ፤ የኢኮኖሚ እድገትም አለ” ብሎ እውነት የሚናገር ሲመጣ ለሁለቱም አይጥማቸውም። ኢህአዴግ የመንግስት ስልጣን ስለያዘ፤ ማስፈራራት፣ ማዋከብና ማሰር ይችላል።
 ተቃዋሚዎች ደግሞ፣ ስልጣን እስኪይዙ ድረስ፣ ስም ማጥፋት፣ ማንቋሸሽና መሳደብ ይችላሉ። ጨዋታው በዚሁ የሚቀጥል ከሆነ፤ የትኛውም ወገን ቢያሸንፍ ብዙም ለውጥ አያመጣም።

በመኩሪያ መሸሻ የተዘጋጀው “ከቤተ መንግስት ደሴ የብላታ    ወ/ማሪያም መዘክር” የሚል መፅሀፍ ሰሞኑን ለንባብ በቃ።
ማመልከቻና ደብዳቤ በአይነቱ ይገለጥበታል የተባለው መፅሀፉ፤ ብላቴን ጌታ ወ/ማሪያም አየለ ከ1912 ዓ.ም እስከ 1925 ድረስ በቁም እጅ ፅሁፋቸው በማስታወሻነት የከተቡት እንደሆነና ስለማዕድን፣ ስለፀጥታ፣ ስለ አውሮፕላን ግዢ፣ ስለ ጋምቤላ ወሰን፣ ስለ ጣና ባህር ልኬትና ግደባ፣ ስለ ጉምሩክ እቃዎችና መሰል ጉዳዮችን የያዘ መሆኑን አዘጋጁ በመፅሀፉ መግቢያ ላይ ገልጸዋል፡፡ 200 ገጾች ያሉት መፅሀፉ፤ በ35.50 ለሽያጭ ቀርቧል፡፡

በወጣት ገጣምያን የተጠነሰሰው “ግጥምን በጃዝ” ባለፈው ረቡዕ ምሽት የ3ኛ ዓመት ክብረ በዓሉን  በብሄራዊ ቴአትር አዳራሽ በተለያዩ የጥበብ ዝግጅቶች አከበረ፡፡ በክብረ በዓሉ ምሽት ግጥሞች፣ ሙዚቃዊ ተውኔት፣ዲስኩሮችና የእውቅና የሽልማት ስነስርአቶች ተካሂደዋል፡፡
በዋቢ ሸበሌ ሆቴል ተጀምሮ ወደ ራስ ሆቴል የተዛወረው “ግጥምን በጃዝ”፤ በኪነ-ጥበብ አፍቃሪያን ዘንድ ከፍተኛ ተወዳጅነትን ያተረፈ ፕሮግራም ነው፡፡ በምሽቱ የጥበብ ዝግጅት ላይ ጸሀፌ ተውኔትና ገጣሚ ጌትነት እንየው፣ ገጣሚ ነቢይ መኮንን፣ አርቲስት ግሩም ዘነበ፣ ገጣሚ አበባው መላኩ፣ ምህረት ደበበ፣ በረከት በላይነህ፣ ምስራቅ ተረፈና ሌሎችም የጥበብ ስራዎቻቸውን ለታዳሚው ያቀረቡ ሲሆን አዳራሹ ገና በጊዜ ጢም ብሎ ሞልቶ ነበር፡፡

          ባለፉት አስርት ዓመታት በልብ በሽታ ሳቢያ የሚጠፋው የሰዎች ህይወት በከፍተኛ መጠን እየቀነሰ መምጣቱ ተገለፀ፡፡ በከፊል አውሮፓ በቀዳሚ ገዳይነቱ ይታወቅ የነበረው የልብ በሽታ በሰዎች ህይወት ላይ ሲያደርስ የቆየው የሞት አደጋ በከፍተኛ ደረጃ እንደቀነሰ በቅርቡ የወጣ ጥናት ጠቆመ፡፡ በምስራቅ አውሮፓ አገራት ግን የልብ በሽታ በግንባር ቀደም ገዳይነቱ እንደቀጠለ ጥናቱ አመልክቷል፡፡
“European Heart Journal” ላይ የወጣ ሪፖርት እንደሚጠቁመው ደግሞ ዴንማርክን በመሳሰሉ አንዳንድ አገሮች በአሁኑ ሰዓት የልብ በሽታን ተክቶ ካንሰር ትልቁ ገዳይ በሽታ እየሆነ መጥቷል ተብሏል፡፡
በከፊል አውሮፓ የልብ ህመም ገዳይነት የቀነሰው ከአኗኗር ዘይቤ መሻሻል ጋር ተያይዞ ነው ያለው ጥናቱ፤ በዋናነት የሲጋራ ማጨስ መቀነስና የተሻሻሉ ህክምናዎች ተጠቅሰዋል፡፡
የኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ የጥናት ትንተና እንደሚያሳየው፤ በአስር አውሮፓ አገራት ወንዶችን በከፍተኛ ደረጃ ለሞት እየዳረገ ያለው ከልብ ህመም ይልቅ ካንሰር ነው፡፡ በዴንማርክ ደግሞ ካንሰር የልብ ህመምን ቦታ ተክቶ በከፍተኛ ደረጃ ህልፈት እያስከተለ የሚገኘው በሴቶች ህይወት ላይ ነው ይላል፤ የጥናት ውጤቱ፡፡
ምስራቅ አውሮፓውያን ግን ከአቻዎቻቸው በእጅጉ ወደ ኋላ እንደቀሩ የጠቆመው ጥናቱ፤ በአንዳንድ የምስራቅ አውሮፓ አገሮች የልብ በሽታ አሁንም ከፍተኛ የሞት አደጋ እያስከተለ ነው ብሏል።
ከተመራማሪዎቹ አንዱ የሆኑት ዶ/ር ማይክ ራይነር ለቢቢሲ ሲናገሩ፤ “በልብ በሽታ የሚከሰተው አጠቃላይ የሞት መጠን እየቀነሰ ነው፤ በአንዳንድ አገራት ከሌሎች አገራት ፈጣን ነው፤ አሁንም ግን በአውሮፓ ትልቁ ገዳይ ነው” ብለዋል፡፡
የብሪቲሽ ኸርት ፋውንዴሽን ዋና ሥራ አስፈፃሚ ሲመን ጊሌስፒ በበኩላቸው፤ “በልብ ህመም በአጭር ጊዜ ውስጥ ይሞቱ የነበሩ በርካታ ሰዎች ቁጥር በመላው አውሮፓ መቀነሱ መልካም ዜና ነው” ሲሉ ተናግረዋል፡፡

የስዕል ተሰጥኦ ከዘረመል ጋር ግንኙነት አለው ተብሏል

ህጻናት በአራት አመት እድሜያቸው ላይ ሆነው የሚስሏቸው ስዕሎች አጠቃላይ ሁኔታና የስዕል ችሎታቸው፣ በቀጣይ የህይወት ዘመናቸው የሚኖራቸውን አእምሯዊ ብቃት በተወሰነ መልኩ የሚያመላክት እንደሆነ በጥናት መረጋገጡን ቢቢሲ ዘገበ፡፡
ለንደን ውስጥ በሚገኘው ኪንግስ ኮሌጅ የሥነ አዕምሮ ተቋም ተመራማሪዎች በጥናታቸው ያካተቷቸውን 7ሺህ 752 ጥንድ መንታ ህጻናት፣ የአንዲትን ህጻን ፎቶግራፍ በወረቀት ላይ እንዲስሉ በማድረግ የህጻናቱን የስዕል ችሎታ የገመገሙ ሲሆን የስዕሎቹ ውጤትም ህጻናቱ ከአስር አመታት በኋላ የሚኖራቸውን አእምሯዊ ብቃት እንደሚያመላክት ማረጋገጣቸውን ተናግረዋል፡፡
በአይን የተመለከቱትን ነገር በወረቀት ላይ በስዕል መልክ ማስፈር መቻል ለሰው ልጆች የተሰጠ ልዩ ክህሎት ነው ያሉት የተመራማሪዎች ቡድኑ መሪ ዶ/ር ሮዚላንድ አርደን፤ የስዕል ችሎታ የሰዎችን መረጃን በአእምሮ የማቆርና በተፈለገው ጊዜ የማውጣትና የማሰብ ብቃት የሚያመለክት እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
የስዕል ችሎታ ህጻናት ሲያድጉ የሚኖራቸውን አእምሯዊ ብቃት የሚያመለክት ቢሆንም፣ ይህ ችሎታ አእምሯዊ ብቃትን የሚወስን አለመሆኑን የገለጹት ዶ/ር አርደን፤ አእምሯዊ ብቃትን የሚወስኑ ሌሎች ተፈጥሯዊና አካባቢያዊ ምክንያቶች እንደሆኑም ተናግረዋል፡፡
“በስዕል ችሎታና በአእምሯዊ ብቃት መካከል ያለው ግንኙነት የተወሰነ በመሆኑ፣ ወላጆች የልጆቻቸው የስዕል ችሎታ አነስተኛ በመሆኑ ሊሰጉ አይገባም” ሲሉም መልዕክታቸውን አስተላልፈዋል።
ተመራማሪዎቹ ከዚህ በተጨማሪም፣ ጥናት ያደረጉባቸው መንታ ህጻናት የሳሏቸውን ስዕሎች በመገምገም፣ የስዕል ችሎታ በዘር የሚተላለፍ መሆን አለመሆኑን ለማጥናት የሞከሩ ሲሆን፣ በዚህም የስዕል ችሎታ ከዘረመል ጋር ግንኙነት እንዳለው ድምዳሜ ላይ ደርሰዋል፡፡

ጉዲፈቻ የሚለው ቃል ከኦሮምኛ ቋንቋ በቀጥታ ወደ አማርኛ የተወሰደ ሲሆን ፍቺውም ከሌላ አብራክ የተገኘን ልጅ ከሌላ ሰው የተወለደ መሆኑን አምኖና ተቀብሎ፣ ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ መብቱን ጠብቆ እንደ ገዛ ልጅ አድርጎ ማሳደግ ማለት ነው፡፡
ጉዲፈቻ ለሚለው ቃል የእንግሊዝኛ አቻው “adoption” ሲሆን አመጣጡም ‘ad-optare’ ከሚል የላቲን ቃል ነው፡፡ ትርጉሙም “መምረጥ” የሚል ነው፡፡ ይህም ጉዲፈቻ በጉዲፈቻ አድራጊው ምርጫ ብቻ የሚከናወን መሆኑን አመላካች ነው፡፡ ጉዲፈቻ አድራጊው በነጻ ፈቃዱ ከሌላ አብራክ የተገኘን ልጅ ለማሳደግና ለመጠበቅ እንዲሁም ለእድገቱ አስፈላጊ የሆኑትን ማናቸውም እንክብካቤዎች ለማድረግ ወስኖ የሚወስደው እርምጃ ሲሆን ይሄም ልጁ የጉዲፈቻ አድራጊውን ቤተሰብ ስም፣ ንብረትና ህይወት እንዲካፈል የሚያደርግ መብት ያጐናጽፈዋል፡፡ ከአብራኩ ክፋይ የተገኘው ልጅ ያለው ማንኛውም መብት ይኖረዋል፡፡
በአጠቃላይ ጉዲፈቻ አንድ ሰው ቀደም ሲል የነበረውን ቤተሰባዊ የደም ትስስር በከፊልም ሆነ ሙሉ በሙሉ በአዲስ ቤተሰባዊ ትስስር የሚተካ ወይም የሚለውጥ ማህበራዊ ተቋም ነው ሊባል ይችላል፡፡
ጉዲፈቻ ከጥንት ጀምሮ በተለያዩ የዓለም ማህበረሰቦች ዘንድ በአንድ ወይም በሌላ መልኩ ሲከናወን የቆየ ሥርዓት ነው፡፡ ለዚህም በአይሁድና በክርስትና ሃይማኖቶች ታሪክ ውስጥ የሚጠቀሰው የነቢዩ ሙሴ ጉዲፈቻ እንደ አብነት ሊነሳ ይችላል፡፡ በህንድ፣ በግብፅና በሮማውያን ዘንድ የዘር ግንዳቸው መቀጠል ባልቻለበት ሁኔታ የቤተሰብ ስም እንዲቀጥል ጉዲፈቻን እንደመሳሪያ ይጠቀሙበት ነበር፡፡ በእስልምና ህግ የሚተዳደሩ አገሮች የሚጠቀሙበት “የጉዲፈቻ” ሥርዓት ከዚህ በመጠኑ ለየት ይላል፡፡ ካፍላህ በመባል የሚታወቀው ይሄ የጉዲፈቻ ሥርዓት ከኢንዶኔዥያና ቱኒዚያ በስተቀር በእስልምና ሃይማኖት ተከታይ አገራት በሙሉ  በስፋት ይተገበራል፡፡ ካፍላህ የተፈጥሮ ወላጆቻቸው ወይም ቤተሰቦቻቸው ሊያሳድጓቸው ላልቻሉ ልጆች የተፈጠረ አማራጭ የእንክብካቤ መንገድ ሲሆን በህጉ መሰረት ካፍላህ አድራጊዎች ልጆቹን ለዘለቄታው ወስደው እንደራሳቸው ልጆች የማሳደግ ግዴታ አለባቸው፡፡ ሆኖም ልጆቹ ማንነታቸውን ይዘው ማደግ አለባቸው ተብሎ ስለሚታመን የካፍላህ አድራጊዎችን የቤተሰብ ስም እንዲጠቀሙ የማይፈቀድ ሲሆን ንብረት የመውረስ መብትም የላቸውም፡፡
በጥንቱ ዘመን ጉዲፈቻ የልጆችን ሳይሆን የጉዲፈቻ አድራጊዎችን ጥቅም መሰረት በማድረግ ነበር የሚከናወነው፡፡ ጉዲፈቻ የዘር ሀረግን በቀጣይነት ለማረጋገጥ፣ በወንድ ጉዲፈቻ ተደራጊ ልጅ አማካይነት ፖለቲካዊ፣ ሃይማኖታዊና ኢኮኖሚያዊ ጥቅሞችን ለማስጠበቅ እንዲሁም በገበሬዎች አካባቢ ተጨማሪ አጋዥ ሐይል ለማግኘት ጭምር ሲተገበር ቆይቷል፡፡ የጉዲፈቻ ተደራጊዎች የእድሜ ክልልም በአብዛኛው ከ10 ዓመት በላይ ነበር፡፡
በአብዛኛው የዓለም ክፍል ሲተገበር የቆየው የጉዲፈቻ ሥርዓት በመካከለኛው ዘመን ላይ በተለይ በአውሮፓ አገራት ወደ መጥፋት ደረጃ ደርሶ ነበር፡፡ ለዚህም ምክንያቱ ደግሞ ከክርስትና ሃይማኖት መስፋፋት ጋር ተያይዞ የቤተሰብ ተቋም የደም ትስስር መለያ ባህሪ ስለተሰጠው ነው፡፡
ጉዲፈቻ ዳግም እንደ ሥርዓት ያንሰራራው በፈረንሳይ ቡርዥዋ አብዮት ማግስት በነገሰው ነፃ አስተሳሰብና ዘመናዊ ፍልስፍና ተፅዕኖ ሲሆን እ.ኤ.አ በ1804 በወጣው የፈረንሳይ ፍትሀብሔር ህግ ላይ ጉዲፈቻ በተወሰኑ ሁኔታዎች እንዲደረግ ተፈቅዶ ነበር፡፡
ይህን የፈረንሳይ ተሞክሮ ተከትሎ በ19ኛው ክፍለ ዘመን ማብቂያ ላይ ጉዲፈቻ በአውሮፓ አገራት እንደ አዲስ የህግ ማዕቀፍ እውቅና አግኝቷል፡፡ በእንግሊዝ ጉዲፈቻ ለመጀመሪያ ጊዜ ሕጋዊ ማዕቀፍ ያገኘው እ.ኤ.አ በ1926 “Children Act of 1926” (የ1926 የህፃናት ድንጋጌ) በሚል ሕግ ሲሆን በአሜሪካ በማሳቹስቴት ግዛት ደግሞ “The Massachusetts Adoption of Children Act” (የማሳቹሴትስ የህፃናት ጉዲፈቻ ድንጋጌ) በሚል በወጣው የጉዲፈቻ ህግ ዕውቅና አግኝቷል፡፡ በወቅቱ ህግ ጉዲፈቻ ተደራጊው ከሁለቱም ቤተሰቡ ማለትም ከቀድሞ ቤተሰቡና ከጉዲፈቻ አድራጊዎቹ ዝምድናውን ይዞ የሚቆይ ሲሆን ከሁለቱም የመውረስ መብት ነበረው፡፡ እነዚህ በአሜሪካና በእንግሊዝ የወጡት የጉዲፈቻ ድንጋጌዎች የመጀመሪያዎቹ ዘመናዊ የጉዲፈቻ ህጎች ተብለው ይታወቃሉ፡፡
የአሜሪካው የማሳቹሴትስ የጉዲፈቻ ድንጋጌ፣ ለቀጣዩ የጉዲፈቻ ህግ መበልጸግ የማእዘን ድንጋይ የጣለ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ ህጉ ለመጀመሪያ ጊዜ የጉዲፈቻ ውል በፍርድ ቤት እንዲጸድቅ የደነገገ ሲሆን ፍ/ቤቱም ውሳኔውን ከማስተላለፉ በፊት የሚመለከታቸው አካላት ለጉዲፈቻው ፈቃድ መስጠታቸውንና ውሳኔው የልጁን ደህንነት የሚያስጠብቅ መሆኑን ማረጋገጥ እንዳለበት ይገልፃል፡፡ ፍ/ቤቱ ጉዲፈቻ  አድራጊዎቹ ለህፃኑ ተስማሚ መሆናቸውን በቅድሚያ ማረጋገጥ እንዳለበትም ህጉ ያስቀምጣል፡፡
በሃያኛው ክፍለ ዘመን መግቢያ ላይ ከአዳዲስ የጉዲፈቻ ህጐች መውጣት ጋር ተያይዞ የጉዲፈቻ አላማና ግብ ከጉዲፈቻ አድራጊው ጥቅሞች ተላቅቆ የህፃናትን ደህንነትና ጥቅም የሚያስጠብቅ እየሆነ መጣ፡፡ ጉዲፈቻ መንግስታት የተጣሉ፣ ቤተሰብ የሌላቸው/የማይንከባከባቸው ወይም ከጋብቻ ውጭ የተወለዱ ልጆችን የሚንከባከቡበትና ደህንነታቸውን የሚያስጠብቁበት ተቋም ለመሆንም በቃ። ይሄን ተከትሎም የጉዲፈቻ ተቋም የሚያስከትለው ህጋዊ ውጤትም ተቀይሯል፡፡ በፊት ጉዲፈቻ ተደራጊው ከቀድሞ ቤተሰቡ ጋር ያለውን ግንኙነት ሙሉ ለሙሉ የማያቋርጥ ሲሆን ይህም ከፊል ጉዲፈቻ /weak or simple adoption/ በመባል ይታወቃል፡፡ አሁን በተሻሻለው የጉዲፈቻ ህጋዊ ሥርዓት ግን ጉዲፈቻ ተደራጊው ከቀድሞ ቤተሰብ ጋር ያለውን ግንኙነት ሙሉ በሙሉ ያቋርጣል፡፡ ይህም ሙሉ ጉዲፈቻ / ‘strong’ or ‘full’ adoption/ በሚል የሚታወቅ ሲሆን የህፃናትን ደህንነት ከማስጠበቅ አንፃር ተቀባይነቱ እየጨመረ መጥቷል፡፡
በአውሮፓና በአሜሪካ የጉዲፈቻ መርህ “የህፃናትን ደህንነት ማስጠበቅ ነው” የሚለው አስተሳሰብ እየጠነከረ የመጣው ከመጀመሪያው የዓለም ጦርነት በኋላ ሲሆን ለዚህም ምክንያቱ በርካታ ልጆች ያለቤተሰብና አሳዳጊ በመቅረታቸውና ከጋብቻ ውጪ የሚወለዱ ልጆች በመበራከታቸው ነበር፡፡ ጉዲፈቻ አድራጊዎች በአብዛኛው ባለትዳር ጥንዶች ቢሆኑም በርካታ ያላገቡ (ወንደላጤ ወይም ሴተላጤ) ግለሰቦችም ልጆችን በጉዲፈቻ ወስደው ያሳድጋሉ፡፡
ሰዎች በተለያዩ ምክንያቶች የጉዲፈቻ ልጅ ሊፈልጉ ይችላሉ፡፡ ብዙዎች የአብራካቸውን ክፋይ ማግኘት ባለመቻላቸው (የማይወልዱ በመሆናቸው) የጉዲፈቻ ልጅ ሲያሳድጉ፣ ሌሎች ደግሞ አዲስ አባል ቤተሰባቸው ውስጥ ለመጨመር ሲሉ የጉዲፈቻ ልጅ ይወስዳሉ፡፡ አሳዳጊ ለሌለው ልጅ መኖሪያ ቤት ለመስጠትና ቤተሰብ እንዲኖረው ለማድረግም የጉዲፈቻ ልጅ የሚወስዱ ቁጥራቸው ቀላል አይደለም፡፡
ህፃናቱም በተለያዩ ምክንያቶች በጉዲፈቻ የሚያሳድጓቸው ቤተሰቦች የሚፈልጉበት ሁኔታ አለ። አንዳንዶቹ ወላጆቻቸውን በሞት በማጣታቸው ሊሆን ይችላል፡፡ ወላጆች ቢኖሩም በህመም ወይም በሌላ የግል ችግር ማሳደግ አቅቷቸው በጉዲፈቻ የሚሰጡበት ሁኔታም አለ፡፡ ሌሎች ደግሞ ተፈጥሯዊ ወላጆቻቸው ጥለዋቸው በጉዲፈቻ የሚሳድጋቸው ቤተሰብ ሊፈልጉ ይችላሉ፡፡
ፍላጐት ሳይኖራቸው የወለዱ ወላጆችን ማንነትን የሚያጋልጥ አለመሆኑ እንዲሁም የልጆችን ደህንነት የሚያስጠብቅ መሆኑ በህፃናት ሥነልቦናና ዕድገት ላይ በተደረጉ ጥናቶች መደገፉ ለጉዲፈቻ ከፍተኛ ተቀባይነት ማግኘት ምክንያት ሆኗል፡፡
በአሜሪካ “የጉዲፈቻና አስተማማኝ ቤተሰቦች ድንጋጌ” (Adoption and Safe Families Act 1997) መውጣት ጋር ተያይዞ የህፃናትን ጥቅም ይበልጥ ሊያስጠብቅ የሚችለው ዘላቂ የሆነ አያያዝ ነው የሚለው ይበልጥ እየታመነበት መጥቷል፡፡ ቀደም ሲል ልጆችን በተቻለ መጠን “ከቤተሰብ ጋር መቀላቀል” የሚለው መርህ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶት የቆየ ሲሆን በዚህም ሳቢያ ልጆች ለረዥም ጊዜ በማሳደጊያ (ፎስተር ኬር) ውስጥ እንዲቆዩ ይደረግ ነበር - አሳዳጊ ቤተሰብ እስኪመጣ፡፡ ይሄ ደግሞ መንግስትን ለከፍተኛ ወጪ የሚዳርግ ከመሆኑም በላይ ልጆችን ከቤተሰብ ለመቀላቀል የሚደረገው ሙከራ በአብዛኛው እንደማይሳካ ተሞክሮዎች ያሳያሉ፡፡ አሁንም ቢሆን ልጆችን ከቤተሰብ ጋር መቀላቀል የሚለው መፍትሄ ቅድምያ የሚሰጠው ቢሆንም ህፃናት በማሳደጊያ ውስጥ ለረዥም ጊዜ መቆየታቸው በደህንነታቸው ላይ  አሉታዊ ተፅዕኖ እንዳለው ጥናቶች ይጠቆማሉ፡፡
የአሜሪካ የጉዲፈቻ ህግ ይሄን ለማስታረቅ የጊዜ ገደብ አስቀምጧል፡፡ ልጁ በተወሰነ የጊዜ ገደብ ውስጥ ከቤተሰቡ ጋር መቀላቀል ካልቻለ የወላጅነት መብት እንዲቋረጥ በቤተሰብ ላይ ክስ ተመስርቶ፣ ልጁ በጉዲፈቻ ሊመደብ እንደሚችል ህጉ ይደነግጋል፡፡ አሁን በአሜሪካ ተመራጩ የህፃናት እንክብካቤ መንገድ ጉዲፈቻ ሲሆን ለልጆች ዘላቂ መፍትሄ የሚሰጥ አማራጭ የእንክብካቤ መንገድ መሆኑ ይበልጥ እየታመነበት መጥቷል፡፡    
በኢትዮጵያ ጉዲፈቻ በትክክል መቼ እንደተጀመረ የሚጠቁም ጥናት ባይገኝም ከ1800 ክፍለ ዘመን መጀመርያ አንስቶ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች በባህላዊ መንገድ ይካሄድ እንደነበር ይገመታል፡፡ በተለይ በኦሮሞ ብሄረሰብ ዘንድ ይተገበር እንደነበርም ይነገራል፡፡ ለመጀመሪያ ጊዜ የህግ ማዕቀፍ የተበጀለት በ1952 ዓ.ም በወጣው የፍትሐብሄር ህግ ሲሆን በዚህ ህግ ስለ ድንበር ተሻጋሪ ጉዲፈቻ በግልፅ የተቀመጠ ነገር ባለመኖሩ፣ በፍትሐብሄር ህግ ውስጥ ያለውን የቤተሰብ ህግ ክፍል ከኢ.ፌ.ዲ.ሪ ህገ-መንግስት ጋር አጣጥሞ ማሻሻል አስፈልጓል፡፡ በዚህም መሰረት የተሻሻለ የቤተሰብ ህግ በአዋጅ ቁ፣ 213/92 ከ1992 ዓ.ም ጀምሮ ፀንቶ በስራ ላይ ውሏል፡፡   
ምንጭ - የጉዲፈቻ አሠራር በኢትዮጵያ
በወ/ሮ ረሂላ አባስ

ወጪው የኮሌጅ ክፍያን አያካትትም

በአሜሪካ ወላጆች አንድን ልጅ ከተወለደበት ጊዜ አንስቶ 18 አመት እስኪሞላው ድረስ በወጉ ተንከባክቦ ለማሳደግ የኮሌጅ ክፍያን ሳይጨምር ግማሽ ሚሊዮን  ዶላር ያህል ወጪ እንደሚጠይቃቸው ሲኤንኤን ዘገበ፡፡
አሜሪካውያን ወላጆች አንድን ልጅ ለማሳደግ ወጪ የሚያደርጉት ገንዘብ እንደገቢያቸው መጠን የሚለያይ መሆኑን የጠቆመው ዘገባው፤ አነስተኛ ገቢ ያላቸው የአገሪቱ ወላጆች ከ145 ሺህ በላይ፣ መካከለኛ ገቢ ያላቸው ከ245 ሺህ በላይ፣ ከፍተኛ ገቢ ያላቸው ደግሞ 455 ሺህ ያህል ዶላር ወጪ እንደሚያደርጉ ገልጿል፡፡
ወጪዎቹ የተሰሉት ወላጆች ለቤት፣ ለምግብ፣ ለትራንስፖርት፣ ለአልባሳት፣ ለጤና፣ ለትምህርትና ለሌሎች ጥቃቅን ጉዳዮች የሚከፈሉ ገንዘቦችን መሰረት በማድረግ ሲሆን ባለፉት አመታት ለጤናና ለልጆች እንክብካቤ የሚወጣው ወጪ በከፍተኛ ሁኔታ እያደገ መምጣቱን ዘገባው አስረድቷል፡፡
በአገሪቱ እየናረ የመጣው የትራንስፖርትና የምግብ ዋጋ ለአሜሪካውያን ወላጆች ከፍተኛ ጫና እየፈጠረ እንደሚገኝ የጠቆመው ዘገባው፤ ባለፉት አስር አመታት የነዳጅ ዋጋ በእጥፍ መጨመሩንና የምግብ ዋጋም ባለፉት ስድስት አመታት ከ13 በመቶ በላይ ጭማሪ ማሳየቱን አመልክቷል፡፡

ከ162 አገራት ‘ከግጭት ነጻ’ የሆኑት 11 ብቻ ናቸው ተባለ

ግጭት ባሉባቸው የዓለም አካባቢዎች ጦርነትን የማስቆምና ዓለምን ሁሉም ሰው ያለስቃይና ያለጦርነት ፍርሃት የሚኖርባት ሰላማዊ ስፍራ የማድረግ ዓላማ ያለው ዓለምአቀፍ የሰላም ጉባኤ በመጪው መስከረም መጀመሪያ በደቡብ ኮሪያ ሴኡል ከተማ እንደሚካሄድ አዘጋጆቹ ለአዲስ አድማስ አስታወቁ፡፡
የኡራጋይ፣ የኖርዌይና የኮስታ ሪካን ፕሬዚዳንቶች ጨምሮ የተለያዩ የአለም አገራት መሪዎችና የሃይማኖት ተቋማት መሪዎች እንደሚሳተፉበት የሚጠበቀውን ይህን አለማቀፍ የሰላም ጉባኤ የሚያዘጋጀው፣ “ሄቨንሊ ካልቸር፣ ዎርልድ ፒስ፣ ሪስቶሬሽን ኦፍ ላይት” (HWPL) የተባለ የሰላም ባህልን በማህበረሰቦችና በዓለም አቀፍ ደረጃ በማጎልበት ጦርነትን ለማስቆም የሚሰራ መንግስታዊ ያልሆነ ዓለም አቀፍ ተቋም ነው፡፡
በመላው ዓለም በሃይማኖቶች መካከል ያሉ አለመግባባቶች ትላልቅ ግጭቶችን እንዳስከተሉ ለዝግጅት ክፍላችን በላከው መግለጫ የጠቆመው ተቋሙ፤ ሰላምን ለመፍጠር አስቀድሞ በሃይማኖቶች መካከል ሰላምና መግባባት ማስፈን የሚል ተልዕኮ እንዳለው አስታውቋል። ከመላው ዓለም ከ40 አገራት የተወከሉ ተሳታፊዎች በሚገኙበት የሴኡሉ ታሪካዊ የሰላም ጉባኤ ግጭቶችን በማስቆም ላይ ያተኮሩ ውይይቶች፣ ባህላዊ ትርኢቶችና የሰላም የእግር ጉዞ እንደሚደረጉ ይጠበቃል፡፡
ይህ በዚህ እንዳለ በፊሊፒንስ በሃይማኖት ልዩነቶች በግጭት በምትታመሰው ዛምቦዋንጋ ከተማ ተጨባጭ የሰላም መፍትሄ ለማምጣት ያለመ ዓለም አቀፍ የሰላም ጉዞ ማካሄዱን ተቋሙ አክሎ ገልጿል። ባለፈው ነሐሴ 5 ለ3 ቀናት ተጀምሮ በተካሄደው 13ኛው የሰላም ጉዞ በዛምቦአኛ ከተማ በሚንዳናኦ ደሴት የፊሊፕንስ መንግስት ከፍተኛ አመራሮችና የሃይማኖት መሪዎችን ጨምሮ 12ሺ የሚገመት ህዝብ የተሳተፈበት የሰላም የእግር ጉዞ የተካሄደ ሲሆን 300 የፊሊፒንስ ፖሊሶች የተካፈሉበት የሰላም ፎረም መካሄዱን ተቋሙ በመግለጫው ጠቁሟል። የተቋሙ ፕሬዚዳንት ሚ/ር ሊ፤ 3ሺ ለሚደርሱ ተማሪዎች ሰላም ላይ ያተኮረ ትምህርት እንደሰጡም ለማወቅ ተችሏል፡፡ የሰላም ልኡኩ ከዚህ ቀደምም ወደ ፊሊፒንስ ተጉዞ እንደነበር ያስታወሰው ተቋሙ፤ የካቶሊክና የሙስሊም ሃይማኖት ተወካዮችን አገናኝቶ የወንድማማችነት ስምምነት በማፈራረም በሚንዳናኦ ከ40 ዓመት በላይ የዘለቀውን የሁለቱን ሃይማኖቶች ግጭት እንዳስቆመ ጠቁሟል፡፡ የሰላም  ተቋሙ በመላው ዓለም ከሚገኙ 81 አገራትና ከ321 ከወጣቶች ጋር ትስስር ካላቸው ድርጅቶች ጋር በትብብር እንደሚሰራ ታውቋል፡፡
በሌላ በኩል፣ ‘ኢንስቲቲዩት ፎር ኢኮኖሚክስ ኤንድ ፒስ” የተባለ ዓለማቀፍ ተቋም በሰራው ጥናት፣ ባለፈው የፈረንጆች አመት በአለም ዙሪያ ከሚገኙ 162 አገራት ‘ከግጭት ነጻ’ የሆኑት 11 ብቻ እንደነበሩ በጥናት ማረጋገጡን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል፡፡በዘንድሮው የፈረንጆች አመት ከተለያዩ የአገር ውስጥም ሆነ የውጭ ግጭቶች የጸዱ ተብለው በጥናቱ የተለዩት አገራት ስዊዘርላንድ፣ ጃፓን፣ ኳታር፣ ሞሪሺየስ፣ ኡራጓይ፣ ቺሊ፣ ቦትስዋና፣ ኮስታ ሪካ፣ ቬትናም፣ ፓናማ እና ብራዚል ናቸው፡፡
እ.ኤ.አ ከ2007 ጀምሮ ባሉት አመታት የዓለማችን ሰላም ከጊዜ ወደጊዜ እየከፋ መምጣቱን የጠቆመው ዘገባው፣ ጥናቱ ከተሰራባቸው 162 አገራት ግጭት የሌለባቸው 11 ብቻ ሆነው መገኘታቸውም ለዚህ አለማቀፍ ችግር ማሳያ ነው ብሏል፡፡
ምንም እንኳን አስራ አንዱ አገራት በ2013 ከግጭት ነጻ እንደሆኑ በጥናቱ ቢረጋገጥም፣ አገራቱ ለግጭት ሊዳርጓቸው ከሚችሉ ሌሎች ችግሮች ነጻ አይደሉም ያለው ዘገባው፣ ለአብነትም በብራዚልና በኮስታ ሪካ የአገር ውስጥ ግጭቶች ችግር እጅግ በጣም አነስተኛ ቢሆንም፣ የአገራቱ ዜጎች አነስተኛ የጦር መሳሪያዎችን የማግኘት እድላቸው ከፍተኛ በመሆኑ ሃይል የተቀላቀለባቸው ተቃውሞዎች የመካሄዳቸው እድል በአሳሳቢ ሁኔታ እየጨመረ መምጣቱን አስረድቷል፡፡
ጥናቱ በተሰራበት ወቅት ሰላማዊ የነበረችው ብራዚል ከወራት በፊት ባስተናገደችው የዓለም የእግር ኳስ ዋንጫ ውድድር ሳቢያ በተቀሰቀሰባት የህዝብ አመጽ የተነሳ በቀጣዩ አመት ይወጣል ተብሎ በሚጠበቀው የ2014 ከግጭት ነጻ አገራት ዝርዝር ውስጥ እንደማትኖር ዘገባው ገልጿል፡፡
አንድ አገር ከግጭት ነጻ ለመባል፣ ተቋሙ ያወጣቸውን የግጭት መለኪያ መስፈርቶችን በሙሉ ማሟላት እንደሚገባውና በአገሩ የግዛት ክልል ውስጥ በሁለት የታጠቁ ሃይሎች መካከል (ቢያንስ አንዱ መንግስት መሆን አለበት) በተፈጠረ ግጭት በአመት ውስጥ ከ25 በላይ የሞት አደጋ ያልተከሰተበት መሆን አለበት፡፡ በድንበር አካባቢም ግጭት መኖር የለበትም፡፡
አሜሪካ ተቋሙ ባወጣው የሰላማዊነት ደረጃ 101ኛ ደረጃ ላይ እንደምትገኝ ዘገባው ጨምሮ ገልጿል፡፡