Administrator

Administrator

*ከ2500 በላይ ህፃናት ይሳተፋሉ
የፊታችን አርብ የሚከበረውን “የአውሮፓ ቀን” ምክንያት በማድረግ የህፃናት የሩጫ ውድድር ነገ በጃንሜዳ ይካሄዳል፡፡ የአውሮፓ ህብረት የኢትዮጵያ ልዑክ ጽ/ቤት ከታላቁ ሩጫ በኢትዮጵያ ጋር በመተባበር ባዘጋጀው በዚህ ውድድር፤ አዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ከሚገኙ የአንደኛ ደረጃ ት/ቤቶች የተውጣጡ ከ2500 በላይ እድሜአቸው ከ14 አመት በታች የሆኑ ህፃናት ተካፋይ ይሆናሉ፡፡
ለዘጠነኛ ጊዜ በሚካሄደው በዚህ ውድድር ተካፋይ የሚሆኑት ህፃናት፤ በአራት የእድሜ ክልል ተመድበው ከአንድ እስከ ሁለት ኪሎሜትር ርቀት የሚሸፍን የሩጫ ውድድር ያካሂዳሉ፡፡ ከዚህ ውድድር ቀደም ብሎ በአለም አቀፍ ት/ቤት ህፃናት ተማሪዎች መካከል የሁለት ኪሎ ሜትር የዱላ ቅብብል ውድድር ይካሄዳል፡፡
የአውሮፓ ህብረት የኢትዮጵያ ልዑክ ጽ/ቤት ይህን የህፃናት የሩጫ ውድድር የአውሮፓ ቀንን ምክንያት በማድረግ በየአመቱ የሚያዘጋጀው፤ ስፖርት ለአንድ ሀገር እድገት የሚያበረክተውን ከፍተኛ ጠቀሜታ ከግምት ውስጥ በማስገባትና ኢትዮጵያ በአለም አቀፉ መድረክ ወደር የለሽ ክብርና ዝና በተጐናፀፈችበት የአትሌቲክስ ስፖርት ተተኪ ስፖርተኞችን ለማፍራት የምታደርገውን ጥረት በመደገፍ የበኩሉን አስተዋጽኦ ለማበርከት መሆኑን የአውሮፓ ህብረት የኢትዮጵያ ልዑክ ጽ/ቤት የፕሬስና ኢንፎርሜሽን ኦፊሰር አቶ ሰሎሞን ከበደ ለአዲስ አድማስ ተናግረዋል፡፡

የስነ ጥበብ ስራዎችን ለህብረተሰቡ በማቅረብ አማራጭ መድረክ የመፍጠርና ለጥበብ አፍቃሪያን በተለያዩ አጋጣሚዎችና ስፍራዎች የስነ ጥበብ ስራዎችን የመመልከት፣ የማድነቅና ቁምነገር የመቅሰም ዕድል የመፍጠር አላማ ይዞ የተቋቋመው ጉራማይሌ የስነ ጥበብ ማዕከል፣ ትናንት ምሽት ተመርቆ ተከፈተ፡፡
የማዕከሉ መስራችና ዳይሬክተር አቶ ሚፍታ ዘለቀ እንደተናገሩት፤ ጉራማይሌ የስነ ጥበብ ማዕከል፣ ስነጥበባዊ ዋጋው ከፍ ያለ ማህበረሰብ የመፍጠር፣ የስነ ጥበቡን ማህበረሰብ ከሰፊው ህብረተሰብ ጋር የማቀራረብ፣ ስነ ጥበብን መሰረት ያደረገ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ እንዲሁም መንፈሳዊ ብልጽግናን የመፍጠር ግብ ይዞ ነው የተቋቋመው፡፡
ትናንት ምሽት በተከናወነው የማዕከሉ የምረቃ ስነ ስርዓት ላይ፤ ታደሰ መስፍን፣ ደረጀ ደምሴ፣ ዘላለም ግዛው፣ ዳዊት አድነውና ሌሎች አንጋፋና ወጣት ሰኣሊያን የተሳተፉበት “ጉራማይሌ - አንድ” የተሰኘ የስዕል ትርዒት ለእይታ በቅቷል፡፡

በርካታ የሀገሪቱን ተዋንያን መፍለቂያ የሆነው እና ፈረንሳይ ለጋሲዮን አካባቢ የሚገኘው “ሚያዚያ 23” አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የተመሰረተበትን 50ኛ ዓመት እያከበረ ነው፡፡  በ1956 ዓ.ም “አስፋወሰን ካሳ” በሚል መጠሪያ ሥራ የጀመረው “ሚያዚያ 23” በመጪው ሐሙስ ከጧቱ ሦስት ሰዓት በሚከናወን ደማቅ ሥነ-ሥርአት የቀድሞ ተማሪዎቹ እና ያሁኖቹ የሀገሪቱ አንጋፋና ታዋቂ ከያንያንና ጋዜጠኞች በትምህርት ቤቱ እንደሚገኙ የተናገሩት የትምህርት ቤቱ ርእሰ መምህር አቶ ጌታቸው አዋሽ፤ እነዚሁ ከያንያን ልምድና ተሞክሮአቸውን እንዲሁም ትዝታቸውን ለአሁን ተማሪዎችና ተጋባዥ እንግዶች እንደሚያቀርቡ ጠቁመዋል፡፡ በተጨማሪም የተለያዩ ኪነጥበባዊ ዝግጅቶች የሚቀርቤ ሲሆን 50ኛ ዓመቱን አስመልክቶ እየተካሄደ ያለው የእግር ኳስ ውድድርም ይጠናቀቃል፡፡ ሥራ ሲጀምር ከ120 በታች ተማሪዎች የነበሩት ትምህርት ቤቱ፤ አሁን 1560 ያሕል ተማሪዎች ያሉት ሲሆን ከቀድሞ ተማሪዎቹ መካከል አርቲስት ጥላሁን ዘውገ፣ ጋዜጠኛ አለምነህ ዋሴ፣ የቶክሾው አቅራቢው ሰለሞን ሹምዬ፣ አርቲስት ግርማ ተፈራ፣ አርቲስት አለልኝ መኳንንት እና ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት የኤፍኤም ጣቢያዎች ዳይሬክተር የነበረው ጋዜጠኛ ሳሙዔል እንዳለ ይገኙበታል፡፡

     በሽመልስ ይፍሩ (ጤርጢዮስ ከቫቲካን) የተዘጋጀው “የተመለሱና ያልተመለሱ ጥያቄዎቼ” የተሰኘው መፅሃፍ ታትሞ እየተሸጠ ነው፡፡
መጽሃፉ፤ አንዱን ቅዱስ መጽሐፍ እያነበቡ በተለያየ ስም የተጠሩበትንና የተለያየ አቋም የያዙበትን ዐብይ ምክንያት እንደሚፈትሽ የገለፀው አዘጋጁ፤ ርዕሰ ጉዳዩም ስለ እግዚአብሔር፣ ስለ ሰውና ስለ ክርስቶስ ባላቸው የእምነት ግንዛቤ ላይ ብቻ የሚያተኩር ነው ብሏል፡፡
በመፅሃፉ ውስጥ የኦርቶዶክስ፣ የካቶሊክ፣ የፕሮቴስታንት፣ የሐዋርያዊት (በተለምዶ Only Jesus የሚባሉቱ) ቤተክርስቲያናት እና የይሖዋ ምስክሮች አገልጋዮች ተሳታፊ ሆነዋል፡፡ መጽሐፉ በ50 ብር እየተሸጠ ሲሆን በጃፋር የመጽሀፍት መደብር እየተከፋፈለ ይገኛል፡፡

  በቴዎድሮስ ኃይሉ ተፅፎ በሰለሞን ሙሄ የተዘጋጀው “አንላቀቅም” የተሰኘ ሮማንስ ኮሜዲ ፊልም፤ የፊታችን ሰኞ ከቀኑ በ11 ሰዓት በአቤል ሲኒማ ይመረቃል፡፡ በቴዎድሮስ ፊልም ፕሮዳክሽን በቀረበው በዚህ ፊልም ላይ ማህደር አሰፋ፣ ሰለሞን ሙሄ፣ ሙሉዓለም ጌታቸው፣ ነብዩ ኤርሚያስ፣ ሄኖክ አለማየሁና ሌሎች አንጋፋ ባለሙያዎች እንደተሳተፉበት ታውቋል፡፡

    የተለያዩ የቢዝነስ፣ የሞቲቬሽን እና መሰል መፅሀፍት በማዘጋጀት የሚታወቁት ዶ/ር አቡሽ አያሌው፤ ያዘጋጁት “ካይዘን” የተሰኘ መፅሀፍ በትላንትናው እለት በግራንድ ዮርዳኖስ ሆቴል ተመርቋል፡፡ ሩቅ ምስራቃዊያን ሳይንሳዊ እውነታውን ቀድመው በመረዳት ካይዘንን ተለውጠውበታል የሚሉት ዶ/ር አቡሽ፤ ሀገራችንም ካይዘንን ተግባራዊ ካላደረገች ያሰበችው ለውጥ ላይ እንደማትደርስ በማሰብ፣ የካይዘንን ግንዛቤ በህብረተሰቡ ውስጥ ለማስረፅ እንደተዘጋጀ ተናግረዋል በመፅሀፉ ምረቃ ላይ የተለያዩ እንግዶች የተገኙ ሲሆን በመፅሀፉ ዙሪያም ውይይት ተካሂዷል፡፡

    ነዋሪነታቸውን በለንደን ባደረጉት ኢ/ር ወንድሙ ነጋሽ ተፅፈው የተዘጋጁት “የአዕምሮ አስተዳደር ሞዴል” እና “ፍቅር ምንድን ነው” መፃህፍት ዛሬ ረፋድ ላይ በብሄራዊ ቴአትር አዳራሽ ይመረቃሉ፡፡
መፃህፍቶቹ ስሜትን ስለመቆጣጠር፣ በራስ ስለመተማመን፣ በአላማ ስለመፅናት፣ ስለ ደስታና የፍቅር ያለንን ግንዛቤ የሚያሰፉ ሲሆን “ፍቅር ምንድነው?” በሚለው መፅሀፍ ውስጥ ፍቅር ምንነትና መሰል ጉዳዮች ተዳስሰውበታል፡፡ መፃህፍቱ በብሔራዊ ቴአትር አዳራሽ ዛሬ ሲመረቁ ውይይት ይደረጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡
ፀሐፊው ኢንጂነር ወንድሙ ነጋሽ ላለፉት 15 ዓመታት በእንግሊዝ የጦር መርከቦችን ከአደን የመከላከል ሲስተም መሀንዲስ በመሆን ከመስራታቸውም በተጨማሪ በስነ-ልቦና ላይ የተመሰረቱ ተከታታይነት ያላቸው ጥናታዊ መፃህፍት በመፃፍ ላይ እንደሚገኙ ታውቋል፡፡

የተለያዩ የኢትዮጵያ ታሪክ፣ ቅርሶችና የብሔር ብሄረሰቦችን ባህልና ትውፊት በአንድ ላይ በማሰባሰብ ለማስጎብኘት የሚያስችል ነው የተባለ የባህል ማዕከል የፊታችን ሐሙስ ሊከፈት ነው፡፡
“ብርሃን ኢትዮጵያ የባህል ማዕከል” የሚል ስያሜ የተሰጠው የባህል ማዕከል፤ ኢትዮጵያን ቀደምት ታሪኮች የሚያወሱ ቅርሶች፣ ለአገሪቱ ታሪካዊ ቦታዎች ምሳሌ የሚሆኑ ስራዎች፣ ከአፄ ቴዎድሮስ እስከ አሁን ድረስ ያሉ የአገሪቱ መሪዎች ምስሎችና አጫጭር ታሪኮችና ብሔር ብሔረሰቦች ባህላዊ ቤቶችን አካቶ የያዙ መሆኑ ታውቋል፡፡
የማዕከሉ ዋና ስራ አስኪያጅ ወ/ሮ ሳቤላ በላይነሽ አባይ ለአዲስ አድማስ እንደገለፁት፤ ማዕከሉ ህብረተሰቡ ባህሉን በአግባቡ ለማወቅና ጎጂውን ለማስቀረት፣ ጠቃሚውን ደግሞ ለመያዝ እንዲችል የሚያግዝ መሆኑን ጠቅሰው፣ ቱሪስቶች በአንድ ጊዜ ሁሉንም አካባቢዎች ለመጎብኘት እንዲችሉ እድሉን ያመቻቸ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
በአዲስ አበባ ቄራ ቡልጋሪያ ማዞሪያ አካባቢ የተሰራው የባህል ማዕከል፣ የፊታችን ሐሙስ በይፋ ተመርቆ እንደሚከፈትም ታውቋል፡፡  

Saturday, 26 April 2014 13:02

የግጥም ጥግ

ዝም ብንል ብናደባ
ዘመን ስንቱን አሸክሞን፤
የጅልነት እኮ አይደለም
እንድንቻቻል ነው ገብቶን፡፡
 ባለቅኔ ሎሬት ጸጋዬ ገ/መድኅን
ቅልስልሱ ይሁዳ
ይሁዳማ ቅልስልስ ነው
አቅፎና ደግፎ
ክርስቶስን ሰጠ
ለሞት አሳልፎ፤
የኛ ዘመን ሰው ግን
ሰቅሏችሁ ሲያበቃ
በፈገግታ ክቦ፤
አቅፎ ይስማችኋል
አይኑን በጨው አጥቦ፡፡
                                       አማኑኤል  መሀሪ
ስሙነኛ ስንኝ
የህዝቦች ልቦና
በታሪክ አንደበት፤
‹‹ንጉሥ ነህ!!›› ባለ አፉ
የሆሳዕና ለት፤
‹‹ስቀለው!!!›› ይልሀል
ውሎ አድሮ እንደ ዘበት፡፡
                                        ፈለቀ  አበበ                           


        በየመን በረሃ የአልቃይዳ ድብቅ ካምፕ ውስጥ የነበሩ 55 የቡድኑ መሪዎችና ታጣቂዎች ሰሞኑን መገደላቸውን የዘገበው አሶሼትድ ፕሬስ፣ ጥቃቱ የተፈፀመው በአሜሪካ ሰው አልባ አውሮፕላን (ድሮን) እንደሆነ ገልጿል፡፡
የአሜሪካ ሰው አልባ አውሮፕላኖች ከነባር የስለላ ቅኝት በተጨማሪ የሚሳኤል ጥቃት መፈፀም የጀመሩት በቀድሞው ፕሬዚዳንት ጆርጅ ቡሽ ትዕዛዝ ቢሆንም፤ የአውሮፕላኖቹ ስምሪት እጥፍ ድርብ የተበራከተው በፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ ዘመን ነው - በአፍጋኒስታን፣ በኢራቅ፣ በፓኪስታን፣ በየመን፣ በሶማሊያ፣ በሊቢያ ወዘተ፡፡
የሰው አልባ አውሮፕላኖች ስምሪት ለማበርከትም ነው፤ አውሮፕላኖቹን የሚቆጣጠሩ አብራሪዎችም በብዛት እየሰለጠኑ ሲመረቁ የቆዩት፡፡ ዛሬ ወደ 10ሺ ከሚጠጉ የአሜሪካ የጦር አውሮፕላን አብራሪዎች መካከል 5ሺ ያህሎቹ ሰው አልባ አውሮፕላኖችን ለመቆጣጠር የሰለጠኑ ፓይለቶች ናቸው፡፡
አሜሪካ የጦር ካምፕ ውስጥ በኮምፒዩተሮች ቁሳቁሶችና ስክሪኖች ያሸበረቀ ቢሮ ውስጥ በስራ የተጠመዱት የድሮን ፓይለቶች፤ ጌም የሚጫወቱ ነው የሚመስሉት፡፡ ግን የምር ጦርነት ውስጥ ናቸው፡፡ በየመን ሰማይ የስለላ ካሜራዎችንና ሚሳዬሎችን የተሸከመ ሰው አልባ አውሮፕላን አልቃይዳ ካምፕ ላይ ጥቃት እንዲሰነዝር ትዕዛዝ እየሰጡት ነው፡፡
ከአስር ሺ ኪሎ ሜትር ርቀት ሆነው ይዋጋሉ፡፡ ምን አለፋችሁ? የአልቃይዳ ዋና መሪዎችና ወታደራዊ መሪዎች በአብዛኛው የተገደሉት በድሮን ሚሳዬል ነው፡፡ ውጤታማነታቸውን በማየትም፤ የአሜሪካ ኮንግረስ፣ ለውጤታማ ድሮን አብራሪዎች የጦር ሜዳ ኒሻን ለመስጠት የሚያስችል ህግ አዘጋጅቷል፡፡ በአካል የጦር ሜዳን ባይረግጡም፤ ለውጊያ አደጋዎች ባይጋለጡም፤ በውጊያ የጦርነት ድል ሲያስመዘግቡ የጀብድ ኒሻን ሊበረከትላቸው እንደሚገባ ይገልፃል - አዲሱ ህግ፡፡ ግን በዚሁ የሚያበቃ አይመስልም፡፡ የዛሬዎቹ ሰው አልባ የጦር አውሮፕላኖች፣ የርቀት ተቆጣጣሪ ፓይለት ያስፈልጋቸዋል፡፡
አሁን እየተሰሩ የሚገኙ አዳዲስ የጦር አውሮፕላኖች ግን የርቀት ተቆጣጣሪ ፓይለት አያስፈልጋቸውም፡፡ ራሳቸው ችለውታል እኮ! ሃላፊነት እየተቀበሉ የመሰማራትና ወታደራዊ እርምጃ የመውሰድ አቅም አላቸው፡፡ ያኔስ የጀብድ ኒሻንና ወታደራዊ ማዕረግ ለማን ይበረከታል? ለአውሮፕላኖቹ፡፡