Administrator

Administrator

በዓለም ላይ “የመርፊ ህግ” በመባል የሚታወቅ ህግ አለ፡፡ የምንሠራው ሥራ ሁሉ ስህተት ይሆናል ብሎ የማመን አዝማሚያ ነው፡፡ ስለዚህ ጉዳይ የሚተረክ አንድ ተረት አለ፡፡
ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ሰው፤ በአንድ በጣም በራበው ጠዋት፤ ቁርስ አስቀርቦ መብላት ጀመረ፡፡ ዳቦውን ሁለት ላይ ከፈለና አንዱን ግማሽ ቅቤ ቀባው፡፡ ጥሩ አድርጐ ግማሹን ክብ ዳር እስከዳር አሳምሮ ነው በቅቤው ያዳረሰው፡፡ ከዚያ ሻዩን ለማወራረጃ ስለሚፈልገው ስኳሩን አስቀድሞ ከቶ ሻዩን ብርጭቆው ውስጥ ቀድቶ እያዘጋጀ ሳለ፤ ሳያስበው ያን የተቀባ ግማሽ ዳቦ ከጠረጴዛው ገፋና ጣለው፡፡
ዳቦው ወለሉ ላይ ወደቀ፡፡
ደንግጦ ወደ ወለሉ ሲያይ በጣም አስገራሚ ነገር ገጠመው፡፡ የዳቦው ያልተቀባው ወገን ወደመሬት፤ የተቀባው ወገን ወደላይ መሆኑን አየ፡፡ አንዳች ተዓምር እንዳየ ሆኖ ተሰማው፡፡ ተደነቀ፡፡
ወደ ጓደኛዬ ሄደና፤
“ዛሬ ጉድ ነው ያየሁት!” አለ፡፡
“ምን አየህ?”
“ብታምኑም ባታምኑም - ተዓምር ነው ያየሁት!”
“እኮ ምን አየህ? ንገረና!?”
“ቁርስ ስበላ ድንገት ግማሹ ቅቤ የቀባሁት ዳቦ መሬት ወደቀ፡፡ የሚገርመው ያልተቀባው ወገን ወደታች የተቀባው ወደላይ ሆኖ ተገኘ!”
“እረ ባክህ? ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል? የተቀባ ዳቦ ሲወድቅኮ፤ ብዙ ጊዜ የተቀባው ወደ መሬት፣ ያልተቀባው ወደላይ ነው የሚሆነው፡፡ አንተ ያጋጠመህ ተዓምር ካልሆነ በስተቀር ወደላይ ሊሆን አይችልም። ምናልባት ለእኛ አልታወቀን ይሆናል እንጂ አንተ ቅዱስ ሳትሆን አትቀርም፡፡ አምላክ ምልክት ሲሰጥህ ነው” አለ
አንደኛው ጓደኛው፡፡
ከዚህ በኋላ በአንድ ጊዜ ወሬው በመንደሩ ተነዛ፡፡ ሁሉ ሰው ጆሮ ደረሰ፡፡
ሁሉ ሰው መጠያየቅ ጀመረ፡፡
“ይሄ እንዴት ሊሆን ቻለ? ማንም ሰው ያልተቀባው ወገን ወደታች ይሆናል ብሎ አይጠረጥርም፡፡ ዳቦው በተሳሳተ ወገንኮ ነው የወደቀው?” ተባለ፡፡
ማንም መልስ ሊሰጥበት ያልቻለ ትልቅ ጥያቄ ሆነ፡፡
በመጨረሻው “ለሰፈሩ ሊቅ ጥያቄውን እናቅርብለትና እሱ ይመልስልን” ተባለ፡፡
ወደመምህሩ ሊቅ ሄደው የሆነውን ተዓምር ነግረው እንዲያብራራላቸው ጠየቁት፡፡
አዋቂው፤ “በዚህ ጉዳይ ላይ፤ ለመፀለይ፣ ሃሳቡን ለማብላላትና መለኮታዊ ምጥቀት ለማግኘት፤ አንድ ማታ ያስፈልገኛል” አለ፡፡
ጊዜው ተሰጠው፡፡
በነጋታው በጉጉት ህዝቡ እየጠበቀው ሳለ መምህሩ መጥቶ፤
“ነገሩ እንኳን በጣም ቀላል ነው፡፡ ያ ዳቦ የወደቀው በትክክል መውደቅ ባለበት በኩል ነው፡፡ ቅቤው የተቀባው ግን በተሳሳተው ወገን ነው!!” አለ፡፡
                                                            *   *   *
እርግጥ በሀገራችን አንፃር ስናየው፤ ዳቦው ከሌለ ግማሹም ሆነ ሙሉው ተቀባ አልተቀባ ማለት አስቂኝ ይሆን ይሆናል፡፡ የተረቱ ምልኪ ግን፤ ስለወደቀውም ዳቦ አሉታዊ አስተሳሰብ ሊኖረን አይገባም ነው፡፡ ከዚያ ቀጥሎ ዳቦው የዳነው በተሳሳተ ወገን ስለተቀባ ነው የሚለው ሌላው አሉታዊ ምላሽ ነው፡፡ ከዚህ ይሰውረን። ህዝቡም መምህሩም አፍራሽ ይሆኑብናልና!
አንዳንዴ አንዳንድ ምናባዊ ፅንሰ-ሀሳብ ምድር ላይ ቢሆን ምናለበት ያሰኛል፡፡ የዳንቴ ፍልስፍና ለዚህ ይበጀናል፡፡
ሰይጣንን ከማግኘታችን በፊት የወንጀለኞች መቀጫ፤ አውቀው ኃጢአት የሰሩ የሚቃጠሉበት፤ ቦታ አንድ ህግ አለው ይባላል፡- የወሸሙና የከጀሉ፤ በዲያብሎስ ይገረፋሉ፡፡ ሸፋጮች አወናባጆች፣ አይነ ምድር ውስጥ ይደፈቃሉ አጨናባሪ አትራፊዎች እግር-ወደላይ-ራስ ወደ ታች ሆነው አዛባ ውስጥ ይዘፈቃሉ። ጠንቋዮች፣ ጠጠር ጣዮች፣ ዛጎል ወርዋሪዎች፤ አንገታቸው ወደ ጀርባ የሚዞርበት ምስል ይኖራቸዋል። አወናባጅ ፖለቲከኞች የአፈር-ውሃ ጥልቅ ጉድጓድ ውስጥ ይጣላሉ፡፡ አስመሳዮች መሸከም የማይችሉት ካፖርት ይጫንባቸዋል፡፡ ሌቦች በእባብ አለንጋ ይገረፋሉ፡፡ አጭበርባሪ የፖለቲካ አማካሪዎች በእሳት ይዋጣሉ የማይሆን ወሬ የሚነዙ ፍም ውስጥ ይቀበራሉ፣ ይለናል፡፡
ከዚህ ሁሉ ይሰውረን ዘንድ መንገዱን ያብጅልን! ይሄ የገባው እራሱን ይጠብቅ፡፡
የሃገራችን ውሃ፣ የመብራት፣ የስልክ… የባንክ፣፣ የቀረጥ ወዘተ የማይነጣጠሉ ችግሮች፤ የዘንድሮ ጉዴስ እኔም ገረመኝ፡፡
አንዱን ስለው አንዱ አንዱ ባሰብኝ!
የሚለውን የዱሮ የኦርኬስትራ ኢትዮጵያን ዘፈን ያስታውሰናል፡፡ በዚያው ዘመን ስለ ሎተሪ አዟሪ በሚዘፈን ዜማ፤
“እስኪ ተመልከቱት፣ ይሄንን ፈሊጥ
እሱ እድል የሌለው፣ ዕድልን ሲሸጥ!” የሚልም ነበር፡፡ ከሁሉም ይሰውረን፡፡
ዛሬ “የባሰ አታምጣ!” ብሎ መፅናናትም አስቸጋሪ ሆኗል፡፡ እንደዕውነቱ ከሆነ የዕውቀትና የሙያ ክህሎታችን ምን ዓይነት ለውጥ ያመጣል ማለት እንጂ “ፓርቲዬ ከመደበኝ የትም ቦታ እሰራለሁ” ብቻውን መፍትሄ አያመጣም፡፡ ችግሩ የተፈጠረው በፓርቲ ምደባ ምክንያት ከሆነስ? ብሎ መጠየቅም ያባት ነው፡፡ ህዝባችን ፓርቲን እንዲያልም ሳይሆን አገር እንዲያልም ብናስብ መልካም ሳይሆን አይቀርም፡፡
የሀገራችን አካሄድ ዕውን፣ በዳቦ የተሳሳተ ወገን መቀባት? ቅቤውን አፈር አይነካውም በማለት? ዓበው እንደሚሉት ከተምኔታዊ (utopian) ገጠመኝ ይልቅ ሌላውን ግማሽ ምን እናርገው? የትኛው ይበጃል? የሚለውን በቅጡ ማጤን ዛሬም ወሳኝ ነው! በወደቀው ላይ ከመፈላሰፍ እንዴት ቀጣዩን በወጉ እንያዘው? ማለት አንገብጋቢ ጉዳይ ነው፡፡
ከቶውንም በግሎባላይዜሽን (ትርጉሙ እኳኋን በእርግጥ ባልተረጋገጠው ፅንሰ ሀሳብ ተንተርሶ) አገርን ማሰብ የተሳሳተ ድምዳሜ ላይ እንዳያደርሰን ከልብ ማውጠንጠን ይኖርብናል፡፡ ምዕራባውያን አገሮች እስከዛሬ ያልታየ የፋይናንስ ድንገተኛ አደጋ (Financial Calamity) እየገጠማቸው መሆኑን በዋዛ አንየው! ታይቶ በማይታወቅ ደረጃ እየተንኮታኮተ ያለውን የኢኮኖሚ የበላይነት በተምታታ ብዥታ እንደሚመለከተው መታየት ፀሐይ የሞቀው ሀቅ ነው፡፡ ይሄን የውስጥ ድንግርግር በዓለም ዙሪያ በተለይም በአዳጊ አገሮች ላይ በመጫን የንግድ፣ የሽብርተኝነት፣ “የዲሞክራሲን አስፋፋለሁ” መርህ ምህዋር ለማስቀየር መጣጣራቸውን ከመፍራት ይልቅ ማወቅ፣ እጅ ከመስጠት ይልቅ ሉዓላዊነትን ጠንክሮ ማሰብ፤ ደግ መሆኑን የዘመኑ የፖለቲካ ጠበብት እንደሚመክሩ ልብ እንበል፡፡ ዘይት፣ ነዳጅ፣ ማዕድን… ያላቸው አገሮች የሚያስነሱትን ብጥብጥ ያስታውሷል፡፡ የራሳችንን ህዝብ ኢኮኖሚያዊ አሳር ቸል አንበል፡፡ የራሳችንን ህዝብ ፖለቲካዊ ምሬት የራሱ ጉዳይ አንበል፡፡ የራሳችንን ህዝብ አስተዳደራዊ በደል ለሌላ ለማንም ብለን ሳይሆን ለነገ የራሳችን ሰናይ ማንነት ስንል ከጉዳይ እንፃፈው፡፡ የራሳችንን ህዝብ የሞራልና የስነ-ምግባር ምንነት በትምህርት በንቃት፣ በአስተዳደጋዎ አስምህሮት ስራዬ ብለን እንደግፈው፡፡ እነዚህን ከላይ የጠቀስናቸውን ፍሬ - ጉዳዮች በቅጡ አስበንባቸው ችግሮቻችንን በየደረጃውና በወቅቱ ካልፈታን ለጎረቤት አገሮች እያሳየን ነው የምንለውን የመፍትሄ - አሽነት ሚና የለበለጠ ያስመስልብናል!  ትላንት ሩዋንዳ፣ ሱማሌ፣ ጅቡቲ ወዘተ… በሞፈር - ዘመትነት መሄዳችንን የአንገት - በላይ ያረግብናል፡፡ “የራሷ ሲያርባት የሰው ታማስላለች” እንዳይሆን እንጠንቀቅ፡፡  


“በሁሉም ማዕከላት አገልግሎቱ ያለእንከን እየተሰጠ ነው”

በአዲስ አበባ ተግባራዊ በተደረገው የቅድመ ክፍያ የመብራት አገልግሎት አሰጣጥ ደንበኞች መማረራቸውን እየገለፁ ሲሆን መብራት ሃይል በበኩሉ፤ በሁሉም ማዕከላት አገልግሎቱ ያለእንከን እየተሰጠ ነው ብሏል፡፡
ካዛንቺስ በሚገኘው የቅድመ ክፍያ አገልግሎት ማዕከል፣በክፍያ አሰባሰብ ላይ ቅሬታ ሲያቀርቡ ያገኘናቸው አንዳንድ ተገልጋዮች፤ ክፍያው የሚሰበሰበው በአንድ ሠራተኛ ብቻ በመሆኑ ወረፋ በመጠበቅ የስራ ጊዜያቸውን እያባከኑ እንደሆነ በምሬት ገልፀዋል፡፡ ረጅም ወረፋ ሲጠብቁ ቆይተው  የምሣ ሰአት አሊያም የስራ መውጫ ደርሷል እየተባሉ ወደ ቤታቸው የሚመለሱ በርካታ ደንበኞች እንዳሉ የታዘበ አንድ ወጣት የቅድመ ክፍያ አገልግሎት ደንበኛ፤ እሱም ራሱ በተመሳሳይ ምክንያት ለሶስት ተከታታይ ቀናት ወደ ማዕከሉ መመላለሱን ገልጿል።
ከሃያት አካባቢ የአገልግሎት ካርዳቸውን ለማስሞላት ካዛንቺስ ድረስ መምጣታቸውን የገለፁት አንድ ጎልማሳ በበኩላቸው፤ ድርጀቱ በከተማዋ አንድ ማዕከል ብቻ በመክፈቱ እሳቸውን ጨምሮ በርካታ ተገልጋዮች ለእንግልት መዳረጋቸውን ተናግረዋል። የአገልግሎቱ መጀመር በተለይ የመብራት አጠቃቀምን በዘመናዊ መልኩ ለመቆጣጠር ከፍተኛ ፋይዳ እንዳለው የሚገልፁት ደንበኞች፤ መብራት ሃይል በከተማዋ የተለያዩ አካባቢዎች የቅድመ ክፍያ አገልግሎት ማዕከላትን በስፋት በመክፈት፣ አገልግሎቱን በተደራጀ የሰው ሃይል በመስጠት ደንበኞችን ከእንግልትና ከምሬት መገላገል ይችላል  ብለዋል፡፡
የደንበኞችን ቅሬታና በአጠቃላይ አገልግሎቱን በተመለከተ ያነጋገርናቸው የኢትዮጵያ መብራት ሃይል ኮርፖሬሽን የውጭና ህዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ምስክር ነጋሽ፤አገልግሎቱ ከሁለት አመት በፊት እንደተጀመረና የደንበኞችን ወጪና ጊዜ ለመቆጠብ ታስቦ ተግባራዊ መደረጉን አስታውሰው፤ በከተማዋ አገልግሎቱን የሚሰጡ 29 ማዕከላት እንዳሉ፣ ሁሉም አገልግሎቱን በተቀላጠፈ መልኩ ለ174ሺ35 ደንበኞች ያህል እየሰጡ እንደሆነም ገልፀዋል፡፡ ከአዲስ አበባ በተጨማሪ በአዳማ ያሉት 3 ማዕከላት እና በቢሾፍቱ ያሉት 2 ማዕከላት፣ በአጠቃላይ ለ26ሺ39 ደንበኞች የተቀላጠፈ አገልግሎት እየሰጡ እንደሆነም ነው ኃላፊው የተናገሩት፡፡ የቢል ህትመት ወጪን እንዲሁም የቆጣሪ አንባቢንና የገንዘብ ሰብሳቢን ድካም በማስቀረት ረገድ አዎንታዊ ሚና እንዳለው የሚነገርለት የቅድመ ክፍያ ቆጣሪ አገልግሎት ተግባራዊ በተደረጉባቸው ሶስቱ ከተሞች ለ200ሺ104 ደንበኞች አገልግሎት እየተሰጠ እንደሆነም አክለው  ገልፀዋል፡፡
በከተማዋ አንድ የአገልግሎት ማዕከል ብቻ በመኖሩ ተቸግረናል የሚለውን የደንበኞች ቅሬታ አስመልክቶ  የተጠየቁት አቶ ምስክር ሲመልሱ “ካዛንቺስና ሜክሲኮ ያሉት እንደ ዋና ማዕከል እሁድን ጨምሮ አገልግሎት የሚሰጥባቸው እንጂ ብቸኛ ማዕከላት አይደሉም፤ በከተማዋ ያሉት 29 ማዕከላት በቂ ሙያተኛ ተመድቦላቸው አገልግሎቱን በተቀላጠፈ መልኩ እየሰጡ ነው” ብለዋል፡፡ በቅርቡም የሃይል ብክነትን  ለመቆጣጠር የሚያስችሉ ሌሎች ዘመናዊ ቆጣሪዎችን ተግባራዊ ለማድረግ መስሪያ ቤቱ እቅድ መያዙን አቶ ምስክር ጠቁመዋል፡፡  

ጊዜው ቢከፋም ለጋሾች እጃቸው አልታጠፈም
50 በጎ አድራጊዎች 7.7 ቢሊዮን ዶላር ለግሰዋል
ከሴቶች ለጋሾች ይልቅ ወንድ ለጋሾች በርክተዋል

በተጠናቀቀው የፈረንጆች አመት 2013 ለተለያዩ የበጎ አድራጎት ስራዎች ገንዘባቸውን ከለገሱ አሜሪካውያን መካከል፣ የፌስቡክ መስራቹ  ማርክ ዙከርበርግና ባለቤቱ ፒሪሲላ ቻን ቀዳሚዎቹ መሆናቸውን ክሮኒክል ኦፍ ፌላንትሮፒ የተባለው ተቋም ይፋ አደረገ፡፡
ጥንዶቹ የአመቱን የወደር የለሽ የቸርነት ክብር የተጎናጸፉት፣ ሲሊከን ቫሊ ፋውንዴሽን ለተሰኘው የበጎ አድራጎት ድርጅት 990 ሚሊዮን  ዶላር ዋጋ ያለው የፌስቡክ የአክሲዮን ድርሻ በመለገሳቸው ነው፡፡ ይህ በአመቱ በአሜሪካ ምድር የተሰጠ ከፍተኛ ልግስና፣ ፋውንዴሽኑን ከአገሪቱ ታላላቅ የበጎ አድራጎት ድርጅቶች ተርታ ያሰልፈዋል ተብሏል፡፡
ዙከርበርግና ሚስቱ በአመቱ የአገሪቱ 50 አባ መስጠቶች ዝርዝር ውስጥ ከተካተቱት አሜሪካውያን በእድሜ ለጋዎቹ ሲሆኑ በሰላሳ አመት እድሜ ላይ የሚገኙት ጥንዶቹ፣ ባለፉት ሁለት አመታትም ለዚሁ የበጎ አድራጎት ድርጅት 1 ነጥብ 5 ቢሊዮን ዶላር የሚያወጣ የአክሲዮን ድርሻ በልግስና አበርክተዋል።
ጥንዶቹ የለገሱት ገንዘብ በትምህርትና በጤና ዘርፎች ለሚከናወኑ ስራዎች ይውላል ተብሏል፡፡
ክሮኒክል ኦፍ ፌላንትሮፒ የአመቱ ለጋስ ብሎ በሁለተኛነት ያስቀመጣቸው፣ ቴክሳስ ኢነርጂ የተባለው ኩባንያ የቀድሞ ስራ አስኪያጅ ጆርጅ ሚሼል ናቸው፡፡ ባለፈው ሃምሌ ከዚህ አለም በሞት የተለዩት እኒህ ባለጠጋ፣ቤተሰባቸው ለበጎ አድራጎት ድርጅት እንዲሰጥላቸው አደራ ብለው በሄዱት 750 ሚሊዮን  ዶላር ነው ለዚህ ክብር የበቁት፡፡
ከናይኪ ኩባንያ መስራቾች አንዱ የሆኑት ፊል ናይት እና ባለቤታቸው ፔኔሎፔም፣ ለኦሪገን ሄልዝ ኤንድ ሳይንስ ዩኒቨርሲቲ ፋውንዴሽን የካንሰር ምርምር እንዲውል መዥረጥ አድርገው በሰጡት 500 ሚሊዮን  ዶላር ከአገሪቱ የአመቱ ቀዳሚ ለጋሶች ሶስተኛ ሆነዋል፡፡ የአሜሪካን የወደር የለሽ ቸሮች ዝርዝር በቀዳሚነት ሲመሩ የቆዩት የማይክሮ ሶፍቱ መስራች ቢል ጌትስና ባለቤታቸው ሚሊንዳ ጌትስ፣ በ2013 ክብራቸውን ማስጠበቅ ባይችሉም በአመቱ ከ181 ሚሊዮን  ዶላር በላይ ለግሰዋል ተብሏል፡፡ ጥንዶቹ በ2004 ለበጎ አድራጎት ተግባር ለመስጠት ቃል የገቡትን 3 ነጥብ 3 ቢሊዮን  ዶላር ቀስበቀስ መክፈል መቀጠላቸው ተነግሯል፡፡
በክሮኒክል ኦፍ ፌላንትሮፒ የ2013 ወደር የለሽ ለጋሶች ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት 50 አሜሪካውያን፣ ለተለያዩ የበጎ አድራጎት ስራዎች በድምሩ 7 ነጥብ 7 ቢሊዮን ዶላር ሰጥተዋል - በ2014፡፡
በአመቱ 296 ሚሊዬን ዶላር በመስጠት በለጋሾች ዝርዝር ውስጥ የአምስተኛነትን ደረጃ የያዙት ጆን አርኖልድ እና ባለቤቱ ላውራ፣ ድጋፍ የሚሹ ወገኖቻቸውን ብቻም ሳይሆን መንግስታቸውንም በመርዳት የሚታወቁ ጥንዶች ናቸው፡፡ ባልና ሚስቱ ባለፈው ጥቅምት ወር የአሜሪካ መንግስት መዘጋቱን ተከትሎ በተከሰተ የአቅም ማጣት ችግር ላይ ፈጥነው ደርሰዋል፡፡ መንግስት በወቅቱ ትምህርት ቤቶቻቸው ተዘግተው ቤት ሊውሉ የነበሩ 7ሺህ ያህል አሜሪካውያን ህጻናትን ትምህርት ማስቀጠል የቻለው፣ እነዚህ ጥንዶች ባበደሩት 10 ሚሊዮን  ዶላር ነው፡፡
በአመቱ የለጋሾች ዝርዝር ውስጥ ዙከርበርግን ጨምሮ በቴክኖሎጂው ዘርፍ የተሰማሩ ሌሎች አምስት ታዋቂ ግለሰቦችም ተካተዋል፡፡ ከእነዚህም መካከል የኢቤይ መስራች ፔሪ ኦሚድያር፣ የጎግል መስራች ሰርጌይ ብሪንና ከማይክሮሶፍት መስራቾች አንዱ የሆኑት ፖል አለንና ሚስቶቻቸው ይጠቀሳሉ።
ወንዶች በሚበዙበት በዚህ ዝርዝር ውስጥ የተካተቱት ለጋሾች፣ የአገሪቱ ኢኮኖሚ እየተንገራገጨ ባለበት ወቅት ሳይሰስቱ በሚሊዮን የሚቆጠር ዶላር ለበጎ አድራጎት ስራ መለገሳቸው ያስደንቃቸዋል ተብሏል፡፡
ለጋሾቹ በአመቱ ከሰጡት ገንዘብ አንድ ሚሊዮን ዶላር ያህሉን የወሰዱት የእርዳታ ድርጅቶች፣ ሆስፒታሎችና ኮሌጆች ሲሆኑ፤ የተቀረውም በህክምና ምርምር፣ ሰብአዊ አገልግሎቶች፣ በአካባቢ ጥበቃ፣ በህጻናትና ወጣቶች ወዘተ ዙሪያ ለሚሰሩ ድርጅቶችና ተቋማት እንደሚውል ተነግሯል፡፡


Monday, 10 February 2014 07:47

‘ድፍረት’ ፊልም ተሸለመ

በኢትዮጰያዊው ፊልም ባለሙያ ዘረሰናይ ብርሃኔ ተጽፎ የተዘጋጀው ድፍረት ፊልም፣ በ2014 ሰንዳንስ አለማቀፍ የፊልም ፌስቲቫል በ‘ወርልድ ሲኒማ ድራማቲክ ኦዲየንስ’ ዘርፍ ተሸላሚ ሆነ፡፡
ታዲያስ መጽሄት ከኒዮርክ እንደዘገበው፣ በእውነተኛ ታሪክ ላይ ተመስርቶ የተሰራውና የ99 ደቂቃ ርዝማኔ ያለው የዚህ ፊልም ዳይሬክተር ዘረሰናይ ብርሃኔና ፕሮዲዩሰሯ ምህረት ማንደፍሮ ባለፈው ቅዳሜ በተከናወነው የፌስቲቫሉ የመዝጊያ ስነስርዓት ላይ ተገኝተው ሽልማቱን ተቀብለዋል፡፡
በሰንዳንስ አለማቀፍ የፊልም ፌስቲቫል ላይ በመካፈል የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊ ፊልም የሆነውና በተለያዩ የአሜሪካ ሲኒማ ቤቶች ተዘዋውሮ ሲታይ የሰነበተው ድፍረት፣ በተመልካቾች ዘንድ ከፍተኛ ተወዳጅነት በማግኘቱ ነው በዘርፉ ተሸላሚ ለመሆን የበቃው፡፡
ከፊልሙ ኤክስኪዩቲቭ ፕሮዲዩሰሮች አንዷ የሆነችው ታዋቂዋ የሆሊውድ የፊልም ተዋናይት አንጀሊና ጆሊ፣ ከሳምንታት በፊት ድፍረት በኢትዮጵያ የፊልምና የኪነጥበብ ዘርፍ ላይ የራሱን አሻራ ያሳረፈ ስራ ነው ስትል አድናቆቷን መግለጧ ይታወሳል፡፡

        በአፍሪካ ፖለቲካዊና የውጭ ግንኙነት ጉዳዮች ላይ በርካታ መፅሃፍትን በመፃፍ የሚታወቁት የፖለቲካ ተመራማሪው ዶ/ር ዴቪድ ሆይሌ “አለም አቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት፤ የአውሮፓ ጓንታናሞ ቤይ?” የተሰኘ መፅሃፍ ለንባብ አበቁ።
ዓለም አቀፍ ፍርድ ቤቱ አፍሪካን ዳግም በቅኝ ግዛት ለመያዝ ታልሞ የተቋቋመ አውሮፓዊ ፍ/ቤት ነው የሚሉት ዶ/ር ዴቪድ፤ አውሮፓ ከ120 ዓመታት በኋላም በተቋሙ አማካይነት አፍሪካውያንን ለመዝረፍ እየሞከረች ነው ብለዋል።
“አውሮፓውያን፤አፍሪካንና ሌሎች ታዳጊ ሃገራትን በዘመናዊ ባርነት ለመግዛት እንዲሁም  ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ሉዓላዊነታቸውን ለማሳጣት የሚጠቀሙበት መሳሪያ ነው” በማለት መፅሃፉ ዓለም አቀፉን የወንጀለኞች ፍ/ቤት ያብጠለጥላል።
ባለፈው ሳምንት  በመዲናችን በተካሄደው 22ኛው የአፍሪካ መሪዎች ጉባዔ ላይ የተመረቀውን የዶ/ር ዴቪድ መፅሃፍ ያሳተመው የአፍሪካ የጥናትና ምርምር ማዕከል እንደሆነ ታውቋል። የመጽሐፉ ዋጋ  14.99 ዶላር  ነው፡፡ ዶ/ር ዴቪድ ከዚህ ቀደም በአፍሪካ ጉዳዮች ላይ የሚያጠነጥኑ አምስት መፅሃፍትን ያሳተሙ ሲሆን በቅርቡም የአሁኑ መፅሃፍ ተከታይ ለንባብ እንደሚበቃ ለማወቅ ተችሏል፡፡

በኢትዮጵያ የኢራን ኢምባሲ የባህል ክፍል የሚዘጋጀው አመታዊው የኢራን የፊልም ፌስቲቫል ካለፈው ሰኞ ጀምሮ በብሄራዊ ትያትር ተካሄደ፡፡
የኢራንን እስላማዊ አብዮት 35ኛ ዓመት ምክንያት በማድረግ የተከናወነው ይህ የፊልም ፌስቲቫል፣ የሁለቱን አገራት ባህላዊ ግንኙነት የማጠናከርና የኢራን የፊልም ኢንዱስትሪ የደረሰበትን ደረጃ የማስተዋወቅ አላማ እንዳለው በኢትዮጵያ የኢራን አምባሳደር አሊ ባህሪኒ በፌስቲቫሉ መክፈቻ ላይ ተናግረዋል፡፡ የኢራን ኢምባሲ የባህል ክፍል፣ በሁለቱ አገራት መካከል የተፈረመውን የባህል፣ የትምህርትና የሳይንስ ትብብር መሰረት በማድረግ የኢትዮጵያን ፊልም ለማሳደግ የሚያግዙ ስራዎችን እንደሚያከናውንም ገልጸዋል፡፡
ለሶስት ተከታታይ ቀናት በተካሄደው በዚህ የፊልም ፌስቲቫል ላይ፣ ‘ኤም ፎር ማዘር’፣ ‘ዘ ሶንግስ ኦፍ ስፓሮውስ’ እና ‘ኦን ፉት’ የተሰኙ፣ በአለማቀፍ ደረጃ ተቀባይነት ያገኙ ስኬታማ የኢራን ፊልሞች ለእይታ በቅተዋል፡፡

          በኢትዮጵያ እግር ኳስ የሰሞኑ አበይት መነጋገርያ አጀንዳ የ62 ዓመቱ ሰውነት ቢሻው ከኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝነት መነሳታቸው ነበር፡፡ ሰውነት ከሃላፊነታቸው ከተነሱ በኋላ ለሱፕር ስፖርት አስተያየት ሲሰጡ ለስንብታቸው በፌደሬሽን ላይ ያቀረቡት ቅሬታ የለም፡፡ በስንብታቸው ማግስት ከዋልያዎቹ በኋላ ዋንኛው ትኩረታቸው ከቤተሰባቸው ጋር ማሳለፍ እንደሆነ የተናገሩት ሰውነት ቢሻው አሰልጣኝነት የማይተውት ሙያቸው እንደሆነ በመግለፅ በአገር ውስጥ የሚወዳደሩ ክለቦችን ወይንም በአፍሪካ ደረጃ ብሄራዊ ቡድኖችን ለማሰልጠን ፍላጎት እንዳላቸው ገልፀዋል፡፡
‹‹የአሰልጣኝነት ስራ አስቸጋሪ እና ምስጋና የሚያሳጣ ነው፡፡ የምትወደደው በከፍተኛ ደረጃ ውጤታማ ስትሆን ብቻ ነው፡፡ በህይወት ውስጥ በተለያዩ  ሁኔታዎች ሊያጋጥሙ የሚችሉ ውጣውረዶችን በፀጋ መቀበል ያስፈልጋል፡፡ መባረሬ ድንገተኛ ዜና አልሆነብኝም። በደቡብ አፍሪካ ከተደረገው የቻን ውድድር ስንመለስ ከመቅፅበት ሁኔታዎች ሲቀየሩ አስተውያለሁ፡፡ ከስንብቱ በፊት ተዘጋጅቶ በነበረው የግምገማ መድረክ፤ በብሄራዊ ቡድኑ የነበሩ ችግሮችን አስረድቼ ነበር፡፡ ይሁንና ቡድኑ በቻን ተሳትፎው ለገጠመው ውጤት ማጣት እኔ ምክንያት እንደሆንኩ አስቀድሞ የተወሰነ ነበር፡፡ በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በነበረኝ ሃላፊነት ባስመዘገብኳቸው ውጤቶች እኮራለሁ፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ላገኛቸው ስኬቶች 100 ፐርሰንት ብቃቴን በመስጠት አገልግያለሁ፡፡ ›› በማለት አሰልጣኝ ሰውነት ለሱፕር ስፖርት የስንብት ቃላቸውን ሰጥተዋል፡፡
ከኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከተሰናበቱ በኋላ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው  የት ይሄዳሉ የሚል ጥያቄ መነሳት ጀምሯል፡፡ አሰልጣኙ በዓለም ዋንጫ የመጨረሻ የደርሶ መልስ ትንቅንቅ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በናይጄርያ ከተሸነፈ በኋላ በማግስቱ ወደ ጊኒ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት ሊሄዱ ነው ተብሎ ተወርቶ ነበር። በዚሁ ጊዜም አሰልጣኙ አገሬን ትቼ የትም አልሄድም፤ በብዙ ሺ ዶላሮች እንድሰራላቸው የጠየቁኝ ነበር ግን አልተቀበልኳቸውም፤ ፍላጎቴ በኢትዮጵያ መቀጠል ነው ብለው አስተባብለው ነበር፡፡ ከሳምንቱ አጋማሽ ስንብታቸው በኋላ ደግሞ ከቦትስዋና እግር ኳስ ፌደሬሽን ጋር ለአዲስ ስራ ግንኙነት ፈጥረዋል እየተባለ ነው፡፡
የዛሬ ሳምንት ቅዳሜ እለት በኤሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል ከተደረገው የግምገማና የምክክር መድረክ ከሁለት ቀናት በኋላ የእግር ኳስ ፌደሬሽን ስራ አስፈፃሚ  ከቀኑ 9 ሰዓት እስከ ምሽቱ 4 ሰዓት ልዩ ስብሰባ አድርጓል። ስብሰባው በአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና በረዳት አሰልጣኞቻቸው  ቀጣይ ሁኔታ ላይ ያተኮረ ነበር፡፡ ከዚሁ የስራአስፈፃሚ ስብሰባ በኋላ በማግስቱ ረቡዕ ካሳንቺስ በሚገኘው የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ፅህፈት ቤት ስራ አስፈፃሚው አስቸኳይ ጋዜጣዊ መግለጫ ጠርቷል። ከቀኑ 10 ሰዓት የነበረው ጋዜጣዊ መግለጫ በጣም በተጣበበ ጊዜ ቢጠራም በርካታ የስፖርት ጋዜጠኞች መገኘታቸውን ያደነቁት የፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ፤ መግለጫው በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኞች  ስንብት ላይ ያተኮረ መሆኑን በይፋ ገልፀዋል። ከኤሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል የግምገማ እና የምክክር መድረክ፤ ከማክሰኞው የስራ አስፈፃሚ ስብሰባ እስከ ረቡዕ ጋዜጣዊ መግለጫ የነበሩትን ሁኔታዎች ከዚህ በታች እንደቀረበው ተዳስሰዋል፡፡
ሰውነትና ዋልያዎቹ በባለድርሻ አካላት ሲገመገሙ
ከሳምንት በፊት በኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን በተዘጋጀው የግምገማ እና የምክክር መድረክ ላይ ከ59 በላይ የስፖርት ጋዜጠኞች መገኘታቸው ያለምክንያት አልነበረም፡፡ በእለቱ  በአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና በብሄራዊ ቡድናቸው ላይ የሚደረገው ግምገማ የመጨረሻ ውጤት የሚዲያውን ትኩረት የሳበው ጉዳይ ነበር፡፡ በሙሉ ቀን በተካሄደው የግምገማ እና የምክክር መድረክ ላይ የስፖርት ኮሚሽን ተወካዮች፤ የሙያ ማህበራት ተወካዮች፤ የክለብ አመራሮች፤ የእግር ኳስ ፌደሬሽን ስራ አስፈፃሚ አባላትና  ባለሙያዎችና በስፖርቱ ላይ ያገባኛል የሚሉ ሁሉም ባለድርሻ አካላት ተሳትፈዋል፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ በመክፈቻ ንግግር ባስጀመሩት በዚህ ስብሰባ ላይ በጠዋት ፕሮግራም የፌደሬሽኑ ዋና ፀሃፊ የአስተዳደር ዘርፍ ካቀረቡት ሪፖርት በኋላ በቴክኒኪ ኮሚቴ ሰብሳቢው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በቻን የነበረውን ተሳትፎ በቁጥሮች የመዘነ ግምገማ ተሰጥቷል፡፡ በመቀጠል የቀረበው ደግሞ የቻን ተሳትፎ እንዴት እንደነበር የሚያብራራ የሰውነት ቢሻው መግለጫ ነበር፡፡ በእለቱ የነበሩ ጋዜጠኞች እነዚህ መግለጫዎች ሲቀርቡ ተከታትለዋል፡፡ የአስተዳደር ዘርፉ ሪፖርት የ2 ዓመት ተኩል ስራን በአጭሩ የተነተነ ነበር፡፡ ሪፖርቱ በሰውነት ቢሻው ዘመን የነበረው  ብሄራዊ ቡድን አጠቃላይ የአስተዳደር እና የፋይናንስ ሂደት በአጭሩ መግለፁን የታዘቡ አንዳንድ ጋዜጠኞች የአሰልጣኙ መሰናበት ፍንጭ ነው ብለው ነበር፡፡ በአንፃሩ የሚዲያ ባለሙያዎች በቴክኒክ ኮሚቴው ግምገማ ብሄራዊ ቡድኑን በመዘኑ በቁጥሮች መወሳሰብ ግራ ተጋብተዋል፡፡ የቴክኒክ ኮሚቴው አሰልጣኙን ከውድድር በኋላ ከመተቸት ከውድድሩ በፊት በቂ መረጃ  በመስጠት ለምን አልሰራም በሚል ቁጭት ብዙዎች ግምገማውን አልተማረኩበትም፡፡ ከዚያ በኋላ ግን የዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው አስገራሚ ማብራርያን ሁሉም ባለድርሻ አካል በትኩረት አዳምጦታል፡፡ ሰውነት በግምገማው መድረክ ያቀቡትን መግለጫቸውን ሲጨርሱ ከብሄራዊ ቡድን ጋር በመስራት ለመቀጠል ያላቸውን ፍላጎት በመግለፅ ነበር፡፡ ለጋዜጠኞች ከአሰልጣኙ ማብራርያ ቀልባቸውን የወሰደው በብሄራዊ ቡድኑ ውጤት ማጣት ተጠያቂ ነኝ ብለው በልበሙሉነት መናገራቸው ነበር፡፡  ይሁንና ዓላማቸው የነበሩትን ልጆች በመያዝ እና አዳዲስ ተተኪዎችን በመፈለግ ብሄራዊ ቡድኑን ለቀጣዩ የሞሮኮው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ ማሳለፍ እንደሆነ ሲናገሩ ግን ማጉረምረም ነበር፡፡  ፌደሬሽኑ የግምገማ እና የምክክር  መድረኩን ያዘጋጀው በቅርቡ ይፋ ለሚያደርገው የ5 ዓመት መሪ ስትራቴጂክ እቅድ ግብዓት የሚሆኑ ሃሳቦችን ለማግኘት አስቦ መሆኑን በመግለፅ ሚዲያዎች በቡድን ለሚደረገው ምክክር እንዲሳተፉ ጋብዞ ነበር። ጋዜጠኞች በመድረኩ መሳተፋቸው ተገቢ አለመሆኑን አምነውበት ሳይሳተፉ ቀርተዋል፡፡
በእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ዋና ፀሃፊ አቶ ይግዛው በቀረበው የአስተዳደር ዘርፍ ሪፖርት መንግስት በስፖርቱ እየተጫወተ ያለውን ወሳኝ ሚና ጎልቶ ወጥቷል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ባለፉት ሁለት ዓመታት ተኩል በአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ እና ዋና ውድድር፤ በዓለም ዋንጫ 3 ዙር የማጣርያ ምእራፎች፤ በሴካፋ እና በቻን ውድድሮች በነበረው ጉዞ ፌደሬሽኑ በአስተዳደራዊ ዘርፉ ካከናወናቸው ተግባራት የትጥቅ ድጋፎች እና ማበረታቻ ሽልማቶች ዋናዎቹ ነበሩ፡፡ ዋና ፀሃፊው አቶ ይግዛው ለአሰልጣኞች፤ ለተጨዋቾች፤ ለቡድን መሪዎች፤ ለልዑካኖች እና ልዩ ልዩ አስተዋፅኦ ላደረጉ ሰዎች በድምሩ 14 ሚሊዮን 875ሺ ብር ወጭ መደረጉን አስታውቀዋል፡፡ ዋና ፀሃፊው አልገለፁትም እንጂ ብሄራዊ ቡድኑ በነበረው ስኬት በስፖንሰርሺፕ፤ በገቢ ማሰባሰብ እና በተለያዩ እንቅስቃሴዎች የተገኘው ብር ከ80 ሚሊዮን ብር በላይ ነበር፡፡ ባለፈው ሁለት ዓመት ተኩል ብሄራዊ ቡድኑን በስፖርት ትጥቆች አቅርቦት አለመቸገሩን  የገለፁት ዋና ፀሃፊው ፤ ለብሄራዊ ቡድኑ ከፌደራል ስፖርት ከ1060 በላይ የተለያዩ ትጥቆችን፤ ከኦሎምፒክ ኮሚቴ 236 ቱታዎች መገኘቱን በመጥቀስ መንግስት በፌዴራል ስፖርት ኮሚሽን በኩል   ለብሄራዊ ቡድኑ የማበረታቻ እና የምስጋና  ድጋፎችን በመስጠት የነበረው ትኩረት የሚመሰገን ነውም ብለዋል፡፡ በብሄራዊ ቡድኑ ስኬት የገቢ ምንጮቹን ያሰፋው ፌደሬሽኑ 1116 የስፖርት ቱታዎች ከ886ሺ በላይ በማውጣት ገዝቷል ፤ ብሄራዊ ቡድኑ በልምምድ ስፍራ እንዳይቸገር፤ በመኝታ እና በምግብ  ደረጃውን የጠበቀ አገልግሎት ሲያገኝ እንደነበርም  ዋና ፀሃፊው አቶ ይግዛው ገልፀዋል፡፡ በአስተዳደራዊ ዘርፍ የተፈጠረው ችግር የቡድን መሪዎች በየጊዜው እና በዘፈቀድ ሲቀያየሩ ከመቆየታቸው በተያያዘ እንደነበር ዋና ፀሃፊው አቶ ይግዛው በሪፖርታቸው አንስተዋል፡፡  ይሄው ዝርክርክ የፌደሬሽን አሰራር ታሪካዊ ቀውስ አስከትሏል፡፡ በዓለም ዋንጫ ማጣርያ ብሄራዊ ቡድኑ  በቢጫ ካርድ ቅጣት መሰለፍ ያልነበረበት ተጨዋች አጫውቶ በሰራው ጥፋት ለ3 ነጥብ መቀነስና ለገንዘብ ቅጣት መብቃቱ በአስተዳደር ዘርፉ የታየ የአሰራር ችግር  ነበር ብለዋል፡፡
“በቻን ውድድር ኢትዮጵያን ወክሎ የቀረበው የሰውነት ቡድን ፋውል የሚያበዛ፤ የግብ እድሉን የማይጠቀም፤ የአካል ብቃት ችግር የታየበት፤ በስነልቦና ያልጠነከረ፤ በደንብ ያልተዘጋጀ ነበር”  በማለት አሰልጣኙን በመተቸት የቴክኒክ ኮሚቴው ሰብሳቢ በግምገማው መድረክ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በቻን የነበረውን ተሳትፎ በቁጥሮች ላይ በተመሰረተ ሪፖርት ፈትሸዋል ፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ በቻን ተሳትፎው በመብቃቱና በአህጉራዊ መድረክ ያለበትን ደረጃ በማሳየቱ ተጠቃሽ ውጤት መሆኑን የገለፁት ባለሙያው ለወጣቶች መነቃቃት የነበረው አስተዋፅኦ ትልቅ ጥንካሬ እንደሆነና የዜጎች መነጋጋርያ አጀንዳ መሆኑ ይደነቃል ብለዋል፡፡ የብሄራዊ ቡድኑ ድክመቶች በሁለት ነጥቦች እንደሚጠቃለሉ የቴክኒክ ኮሚቴው ሰብሳቢ ሲያስረዱ፤ የመጀመርያው በቻን ተሳትፎ ዋና አሰልጣኙ እና ረዳቶቻቸው ለወጣት እና ተተኪ ተጨዋቾች እድል አለመስጠታቸው በብሄራዊ ቀጣይ እድገት ተፅእኖ የሚፈጥር መሆኑን ባለመረዳት ነው ብለው፤  በሌላ በኩል የብሄራዊ ቡድኑ የተፎካካሪነት ብቃት በውጤት የታጀበ አለመሆኑ በግልፅ ከብዙ ችግሮች ጋር ታይቷል ብለዋል፡፡
የቴክኒክ ኮሚቴው ግምገማ  የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በቻን ተሳትፎው ከሊቢያ፤ ከኮንጎ እና ከጋና ጋር ባደረጋቸው ጨዋታዎች ከ3ቱ ቡድኖች በድምር የሚበልጥ ፋውል እንደሰራ፤ የግብ እድሎችን መጠቀም እንዳልቻለ፤ በኳስ ቅብብል ረገድ ውጤታማ ያልሆኑ እንቅስቃሴዎችን እንዳበዛ፤ በአጨዋወቱ ኳስ ወደ ኋላ በመመለስ መጥፎ አዝማሚያ እንዳሳየ፤ በመከላከል ላይ የጥንቃቄ ጉድለት እና ድክመት እንዳለበት፤ ኳስን በጭንቅላት መግጨት እና የተቃራኒ ቡድን ኳሶችን ከአደጋ ነፃ እንደማያወጣ፤ በመስመር ብዙም እንደማይጫወት አመልክቷል። የቴክኒክ ኮሚቴው ሰብሳቢ በአጠቃላይ አሰልጣኞች ለብሄራዊ ቡድን በመረጧቸው ተጨዋቾች መሄድ የሚገባቸውን እድል ነፍገው የማይገባቸውን ማሰለፋቸው ዋና ስህተት እንደነበር ሲገልፁ፤ የተጨዋቾች የአካል ብቃት  አለመሟላትና ለስነልቦና ችግሮች መጋለጥ የቡድኑን አቅም ያቃወሱ ምክንያቶችእንደነበሩም ተረድተናል ብለዋል፡፡ አሰልጣኞች ቡድኑን በብቃት እንዳላዘጋጁ፤ ለዝግጅታቸውም ከክለቦች ጋር በቅንጅት ስለማይሰራ በቡድኑ ብቃት ላይ ተፅእኖ መፍጠራቸውንም የቴክኒክ ኮሚቴው ግምገማ አብራርቷል፡፡
ለሰውነት ምስጋና ይግባቸው
የፌደሬሽን ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ እንደገለፁት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና ረዳቶቻቸው ቡድኑን ተረክበው ባገለገሉበት ባለፈው ሁለት ዓመት ተኩል እግር ኳሱን ያነቃቁ በርካታ ውጤቶች እና ለውጦች ተመዝግበዋል፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ከ31 ዓመታት በኋላ ለአፍሪካ ዋንጫ መብቃቱ  የመጀመርያው ድንቅ ስኬት እና አበይት የታሪክ ምእራፍ ነበር፡፡ ለ20ኛው የዓለም ዋንጫ ለማለፍ እስከመጨረሻው የማጣርያ ምዕራፍ በመጓዝ ብሄራዊ ቡድኑ ከአፍሪካ 10 ምርጥ ቡድኖች ተርታ መግባቱም ይታወሳል፡፡  በአፍሪካ አገራት የእግር ኳስ ሻምፒዮንሺፕ ቻን ውድድር ኢትዮጵያ ለመጀመርያ ጊዜ መሳተፏም ተጠቃሽ ስኬት ነበር፡፡ ብሄራዊ ቡድኑ ባለፈው ሁለት ዓመት ከመንፈቅ ባስመዘገበው ውጤት በ2015 የአፍሪካ ዋንጫ ያለቅድመ ማጣርያ በቀጥታ ለምድብ ማጣርያ የመወዳደር እድልም አግኝቷል፡፡  
አቶ ጁነዲን ባሻ ባለፈው ሁለት ዓመት ተኩል የተገኘውን ስኬት ባጠቃለለ ንግግራቸው ‹‹ ለብዙ ዘመናት ብሄራዊ ቡድኑ ብዙ ጎል የሚገባበት፤ ተከታታይ ሽንፈቶችን የሚያስተናግድ፤ እናሸንፋለን ብለን በአዕምሯችን እንዳናስብ ያደረገን ነበር፡፡ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻውና መላው ቡድናቸው ይህን የቀየረ ውጤት አስመዝግበዋል፡፡ የኢትዮጵያን ህዝብ የእግር ኳስ ስሜት አነቃቃትዋል፤ ወደ ስታድዬም  እንዲመጣ አድርገዋል፤ ኢትዮጵያ ታሸንፋለች ተብሎ መታሰብ እንዲጀምር አስችለዋል፡፡  የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ማልያ ከዳር እስከዳር እንዲለበስም ምክንያት ሆነዋል፡፡›› በማለት  ምስጋና አቅርበዋል፡፡
የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በኢትዮጵያ እግር ኳስ በፈጠሩት መነቃቃት እንደ ብሄራዊ ጀግና የሚታዩ ታላቅ ሰው መሆናቸውን በድፍረት መናገር ይቻላል፡፡ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ ከፍተኛውጤት አላቸው። በ50ሺህ ብር ወርሃዊ ደሞዛቸው ከፍተኛው ተከፋይ ነበሩ።
በሰውነት የስራ ዘመን በኢትዮጵያ እግር ኳስ ታሪክ ትልቁ ስኬት ከመመዝገቡም በላይ የአገሪቱ የእግር ኳስ ደረጃ ተሻሽሏል፤ ከዋልያዎቹ መካከል አንዳንዶቹ ወደ 6 የተለያዩ አገራት ወደ የሚገኙ ክለቦች በመሰማራት በዝውውር ገበያው ተፈላጊነታቸው ጨምሯል፡፡
የሰውነት መሰናበቻ ምክንያቶች
ስራ አስፈፃሚው በዋና አሰልጣኙ ሰውነት ቢሻው እና በረዳቶቻቸው ለተገኙ ውጤቶች ክብርና ምስጋና እንደሚገባ ቢገልፅም በብሄራዊ ቡድኑ ቀጣይ ጉዞ ላይ ባደረገው ልዩ ስብሰባ የተገኘውን ውጤት ለማስቀጠል እንቅፋት የነበሩ ድክመቶችን መርምሯል፡፡ በአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የሚመራው ብሄራዊ ቡድን ከናይጄርያ ጋር ለዓለም ዋንጫ ለማለፍ ባደረጋቸው ሁለት ጨዋታዎች የባከኑ እድሎች ነበሩ፡፡ ከዚያም ኬንያ ባዘጋጀችው የሴካፋ ሻምፒዮና የኢትዮጵያ ቡድን ለዋንጫ ተጠብቆ ከምድቡ በጊዜ የተሰናበተበት ሁኔታም ብዙ ጥያቄዎችን ፈጥሯል። በመጨረሻም  በደቡብ አፍሪካው የቻን ውድድር ቡድኑ በነበረው ተሳትፎ ደካማ አቋም ማሳየቱ እና የፉክክር ደረጃው ኋላቀር መሆኑ መረጋገጡ ሁሉንም ያሳሰበ ነበር።  ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ብሄራዊ ቡድን ዳግም ወደሽንፈት መመለሱን የፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ ሲታዘብ ቆም ብሎ ማሰብ እንዳስፈለገው የተናገሩት አቶ ጁነዲን ባሻ፤ የኢትዮጵያ እግር ኳስ በቀጣይ ወዴት ያመራል፤ መንግስት እና ህዝብ ከስፖርቱ ምን ለውጥ ይፈልጋሉ የሚለውን መክረንበት ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና ረዳቶቻቸው በብሄራዊ ቡድኑ ያላቸው ቆይታ ማብቃት እንዳለበት ከውሳኔ ላይ ደርሰናል ብለዋል፡፡
አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ ከስራ እንደተሰናበቱ የተገለፀላቸው   በኤሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ሃላፊዎች፤ የሚዲያ ባለሙያዎች እና ባለድርሻ አካላት በተገኙበት የግምገማ መድረክ ላይ በሃላፊነታቸው ስለመቀጠል ፍላጎታቸው ከተናገሩ 3 ቀናት በኋላ ነበር፡፡ አሰልጣኞቹ መሰናበታቸውን ካወቁ በኋላ ውይይት ተደርጎ በተሰራው ሁሉም መደሰቱን፤ ግንኙነታቸው እንደሚቀጥል፤ ከስፖርቱ ጎን በመሆን እንደሚቀጥሉ ቃል መግባታቸው ተነግሯል፡፡
‹‹ሰዎች ጥሩ ይሰራሉ፡፡ ጊዜዎች ይቀያየራሉ፡፡ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና ረዳቶቻቸው በዓለም ዋንጫ የመጨረሻ ደርሶ መልስ ፍልሚያ ከናይጄርያ ጋር፤ በሴካፋ እና በቻን ውድድሮች ይዘው በቀረቡት  የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የማሸነፍ ስሜት ቀነሰ፤ የውጤት ማጣት ተከታታለ፤ በእርግጥ ተጨዋቾችም አሰልጣኞችም በጨዋታዎቹ የተቻላቸውን ሁሉ አድርገዋል፡፡ በክለቦች መካከል ያለው ውድድር አለማደጉ፤ በታዳጊዎች ላይ የሚሰሩ ተግባራት ያልጠነከሩ መሆናቸው፤ እና የአደረጃጀት እና የአሰለጣጠን ብቃት አለማደግ ለብሄራዊ ቡድኑ ድክመት የሚጠቀሱ ምክንያቶች ናቸው፡፡ የውጤት ማጣቱ አዝማሚያ የመጣው ባለንበት ልክ እና ደረጃ ነው። እግር ኳስ ያለበትን ደረጃ ቆም ብለን ማሰብ ነበረብን ›› በማለት ለታሪካዊው ውሳኔ ያደረሱ ዝርዝር ሁኔታዎችን አቶ ጁነዲን ባሻ ገልፀዋል፡፡
 በፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ በኩል ብሄራዊ ቡድኑ በመቀጠል በ2015 በሞሮኮ ለሚዘጋጀው የአፍሪካ ዋንጫ እንዲያልፍ ይፈለጋል፡፡  በታዳጊ እና ወጣት  ቡድኖች አህጉራዊ ውድድሮች ንቁ ተሳታፊ የመሆን ፍላጎትም አለ። የስፖርቱ ባለድርሻ አካላት ለለውጥ ተነሳስተው በዘላቂ ልማትና የእድገት ሂደት  እንዲሰሩ የማስተባበር እቅድም አለ፡፡ በአጠቃላይ የአሰልጣኝ ሰውነት ስንብት ስራውን ከጀመረ 4 ወራት የሆነው የፌዴሬሽን አመራር አዲስ የለውጥ ምእራፍ መክፈቱን ያበሰረበት ነበር፡፡
የአሰልጣኞቹ የኮንትራት ውል መቋረጡ ትልቅ ውሳኔ በመሆኑ በግልፅ መታወቅ አለበት ያሉት ጁነዲን ባሻ፤ አሰልጣኞች ስራቸውን ራሳቸው አልለቀቁም ወይም በክፉ ስሜት አልተሰናበቱም ብለዋል፡፡ ዋና አሰልጣኙና ረዳቶቻቸው በማንኛውም የሰራተኛ ህግ መሰረት ስንብታቸው እንደሚከናወን የገለፁት የፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት በክብር እና በምስጋና ይሸኛሉ እንጂ የካሳ ክፍያ የላቸውም ብለዋል፡፡ የስራ አስፈፃሚው አሰልጣኞቹን ለመቀየር መወሰኑን በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ሲገልፅ ሌላው የፌደሬሽን ዝርክርክ አሰራርም ተጋልጧል፡፡ የአሰልጣኞቹ የቅጥር ኮንትራት ጉዳይ ነው፡፡ የአንዱ በጥቅምት፤ የሌላው በህዳር የሌላው በታህሳስ ውል የሚያበቃበት ነበር ያሉት አቶ ጁነዲን ባሻ፤ የቅጥር ኮንትራት በግልፅ የሚታወቅ መሆን ቢኖርበትም አሰልጣኞቹ ኮንትራታችሁ አልቋል ብለንና ኮንትራታቸውን አቋርጠን ለማሰናበት ያልፈለግነው፤ የቡድኑን የስራ ስሜት ላለማመሳቀል እና ላለመረበሽ በመወሰናችን ነበር ብለዋል፡፡ አሁን በስልጣን ላይ ያለው ፌደሬሽን ሃላፊነቱን ከተረከበ ከ3 ቀናት በኋላ ብሄራዊ ቡድኑ ወደ ዓለም ዋንጫ ለማለፍ የደርሶ መልስ ማጣርያውን ከናይጄርያ ጋር በአዲስ አበባ ይጀምር ነበር። በሴካፋና በቻን ውድድሮች ከዚያ በኋላ  በአንድ ወር ጊዜ ውስጥ መደረጋቸውን በማገናዘብ ይሆናል፡፡ ሆኖም ግን  በተለይ የአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው የቅጥር ኮንትራት ውል ጥቅምት 28 አብቅቶ በይፋ ኮንትራራታቸው እንደተራዘመ ሳይገለፅ እስከ ታህሳስ 28 እየሰሩ እንዲቀጥሉ መደረጉ ፌደሬሽኑን ያስተቸዋል፡፡  
አሰልጣኞቹ እንዲሰናበቱ የተደረገው በሴካፋ እና በቻን ውድድሮች ላይ ባሳዩት ድክመት ብቻ እንዳልሆነ በመግለጫው የተናገሩት ሌላው የፌደሬሽኑ  የስራ አስፈፃሚ አባል እና ምክትል ፕሬዝዳንት የሆኑት  አቶ ተክለወይኒ ናቸው፡፡ በቻን ውድድር የኢትዮጵያ ቡድን ለዋንጫው ትልቅ ግምት ተሰጥቶት እንደነበር ከናይጄርያ እና ጋና ተርታ ይጠቀስ እንደነበር ያስታወሱት አቶ ተክለወይኒ፤ ይህን በመንተራስ የፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ ከአሰልጣኞቹ፤ ከረዳቶቻቸው እና ከተጨዋቾች ጋር ሲመካከር በቻን ያለው ግብ ዋንጫ ማምጣት ወይም ግማሽ ፍፃሜ መድረስ እንደሆነ ገልፆላቸዋል፡፡  የቡድኑ አባላት ይህን ግብ ለማሳካት ስንት ሽልማት ይጠብቀናል ብለው ሲደራደሩ ደህና ሽልማት ታገኛላችሁ ብለን ተማምነን ነበር ብለዋል፡፡  ከቻን ጉዞ በፊት በነበረው ጋዜጣዊ መግለጫ ዋና አሰልጣኙ ዋንጫ ለማምጣት ወይም ግማሽ ፍፃሜ ለመድረስ ቃል የገቡትን ካልሆነ ተሸንፎ መመለስ የሚለውን ጨመሩበት፡፡ ተገቢ አልነበረም፡፡ ‹‹በቻን ውጤት ላይ ያደረግነው  የውስጥ ግምገማ ብሄራዊ ቡድኑ ለተሰጠው ግምት በቂ ጥረት አላደረገም ነው፡፡ አህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ የእግር ኳስ አካላት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በአፍሪካ ደረጃ በተሳተፈባቸው ውድድሮች ጥሩ መጫወቱን ገልፀውልናል፡፡ ጎንለጎን ግን የቡድኑ ደረጃ ደካማ እንደሆነና የተፎካካሪነት ብቃቱም መሻሻል እንደሚያስፈልገው መክረውናል፡፡ ስለሆነም የአሰልጣኞቹ መቀየር አስፈልጓል›› በማለት አቶ ተክለወይኒ ማብራርያ ሰጥተዋል፡፡  የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በየጨዋታው ብዙ የግብ እድሎች አምልጦታል፤ ተጨዋቾቹ ጥሩ ቢጫወቱም ውጤት ግን አላገኙም፤ ለውድድሮቹ በአሰልጣኞቹ የተደረገው ዝግጅት በፕሮፌሽናል መንገድ አልነበረም። ይህ ሁሉ ዝርዝር ምክንያት የፌደሬሽኑ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ተክለወይኒ ትልቅ ክፍተት ብለውታል። ‹‹ያሉብን ክፍተቶች የማይስተካከሉ ከሆነ የኢትዮጵያ ህዝብ የሚፈልገው ውጤት መቼም ሊሳካ አይችልም ስለዚህም ስርነቀል ለውጥ ያስፈልጋል በሚል ከመግባባት ላይ ደርሰናል ››ሲሉም ተጨማሪ አስተያየት ሰጥተዋል፡፡ በኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ወቅታዊ ብቃት ላይ የፊፋ ባለሙያዎች ያደረጉትን ትንተና ለአሰልጣኞቹ መቀየር ተጨማሪ ምክንያት እንደነበር በመግለፅም  ለእግር ኳሱ ጠቅላላ ህዳሴ የሚያመጣ ስትራቴጂ እንደሚያስፈልግ ለታመነበት አቅጣጫ ውሳኔው አስፈላጊ ነበር ብለው ተናግረዋል፡፡
የሰውነት  ተተኪ ከየት? ከአገር ውስጥ ከባህር ማዶ
የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌደሬሽን ስራ አስፋፃሚ የብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት ቀላል ስራ አለመሆኑን ትልቅ ሃላፊነት እንደሆነ መገንዘቡን ሰሞኑን ገልጿል፡፡ የአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እና የረዳቶቻቸውን ስንብት የወሰነው ግን በአጣብቂኝ ውስጥ ሆኖ ይመስላል፡፡ ስራ አስፈፃሚው በፕሬዝዳንቱ በኩል አሰልጣኞቹን ያሰናበትነው ሌላ አሰልጣኝ ለመቅጠር በመጓጓት ማለቱም ተስፋ ሰጪ አይመስልም፡፡ በአዲስ አሰልጣኝ ቅጥር ለኢትዮጵያ እግር ኳስ እድገት የሚመች አደረጃጀት ለመፍጠር መታሰቡን የገለፁት ፕሬዝዳንቱ ፤ ቦታውን ክፍት ማድረግ የመጀመርያው ተግባር እንደሆነ መታወቅ እንዳለበት በማስረዳት የህዝብ ጉዳይ ስለሆነ በግልፅ፤ ያለወከባ እና በጥንቃቄ ተገቢው መስፈርት ወጥቶ በሚደረግ ውድድር መሰረት የሚፈፀም እንደሚሆን ቃል ገብተዋል፡፡
የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ስራ አስፈፃሚ በአዲሱ አሰልጣኝ ቅጥር የመጀመርያ ሙከራ በአገር ውስጥ ያሉ ባለሙያዎችን ማሰስ እንደሆነ ተገልጿል፡፡ ከሰውነት ቢሻው ስንብት በኋላ ብሄራዊ ቡድኑ ጋር ስማቸው እየተያያዘ ካሉ የአገር ውስጥ አሰልጣኞች መካከል ስዩም ከበደ፤ ፀጋዬ ኪዳነማርያም እና ገብረመድህን ሃይሌ እና ሌሎችም ይጠቀሳሉ፡፡ የፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት ለአሰልጣኙ ቅጥር ወደውጭ የምንወጣበት ሁኔታ ካለ የገንዘብ ምንጮቻችን በመፈተሽ የምናደርገው ይሆናል ሲሉም አስረድተዋል፡፡ የቀድሞው የጊዮርጊስ ክለብ አሰልጣኝ የነበረው፤ በሱዳኑ አልሂላል ክለብ የሰራውና በምስራቅ አፍሪካ ክለቦች ካለው ልምድ ባሻገር የሩዋንዳ እና የኡጋንዳ ብሄራዊ ቡድንን ያሰለጠነው ሰርቢያዊ ሰርዶጆቪች ሚሉቲን ሚቾ ከውጭ አሰልጣኞችቀድሞ ስሙ ተጠርቷል፡፡
በቀድሞው ፌደሬሽን የተገባላቸውቃል ሳይፈፀምላቸው ቅር ተሰኝተው የነበሩት ቤልጅማዊው ቶም ሴንትፌንትም እየተጠቀሱ ናቸው፡፡ ቶም ሴንትፌይት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን ሃላፊነት ለመረከብ በይፋ ጥሪ በማክበር የመጀመርያ የውጭ አሰልጣኝ ናቸው።  ከቤልጅዬም ለሱፕር ስፖርት በሰጡት ማብራርያ ‹‹ሰውነት ቢሻው ለብሄራዊ ቡድን ባስገኘው ስኬት ምስጋና ይገባዋል። ረዳቴ ሆኖ አብረን ስንሰራ በነበረበት ወቅት እንደ አስራት መገርሳ እና ጌታነህ ከበደን የመሳሳሉ ተጨዋቾች ለቡድኑ በመምረጥ አስተዋፅኦ ነበረኝ። በእርግጥ አገሪቱን ለቅቄ የወጣሁት ከፌደሬሽኑ ጋር በተፈጠሩ አለመግባባቶች ነበር፡፡ ተመልሼ ብሄራዊ ቡድኑን የማሰልጠን እድል ባገኝ ብዙ ልሰጠው የምችለው ነገር አለ፡፡ በተለይ ዋልያዎቹ በትልልቅ ግጥሚያዎች የሚገጥማቸውን ፈተና የሚወጡበትን አቅም ማስተካከል እችላለሁ፡፡ የኢትዮጵያ ቡድን በፈጠራ እና በቴክኒክ የዳበረ ጥሩ አሰልጣኝ ካገኘ ምርጥ መሆን የሚችል ነው።›› በማለት ቶም ሴንትፌይት ለሱፕር ስፖርት ተናግረዋል፡፡
ፌደሬሽኑ የአሰልጣኙ ቅጥር በቀና መንገድ፤ አሳማኝ መመዘኛ እና መስፈርት ተዘጋጅቶ የሚከናወን እንደሆነ ሲያስታውቅ፤ ፍለጋውን በጋዜጦች ማስታወቂያዎችን በማውጣት፤ የተለያዩ ጥቆማዎችን ከባለድርሻ አካላት እና ከሙያተኞች በመቀበል፤ በብሮድካስት ሚዲያዎች በማስተዋወቅ ይሰራበታል ብሏል፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት አቶ ጁነዲን ባሻ እንደገለፁት በአሰልጣኝ አዲስ ቅጥር የማፈላለግ ተግባር ላይ  የቴክኒክ ኮሚቴ ሃላፊነት ተሰጥቶታል፡፡ ኮሚቴው በአንድ ሳምንት ጊዜ  ለሃላፊነቱ ብቁ የሆኑ ሰዎችን ዝርዝር እንዲያቀርብ ይጠበቃል፡፡
ቀጣዩን የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ለመቅጠር ፌደሬሽኑ ያሰበው የህዝብ ፍላጎት አድጓል፤  ዓለም አቀፍ ደረጃ ይዘን ተፎካካሪ ሆነን እንቅረብ ከሚል አቅጣጫ በመነሳት ነው፡፡ ከአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው መሰናበት  በኋላ ግን ለብሄራዊ ቡድኑ የሚመጥን አሰልጣኝ ፍለጋው ፈታኝ እንደሚሆን  መገመቱ  ስጋትን የጋረጠ ሆኗል፡፡
በአገር ውስጥ የአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻውን ተተኪ ለማግኘት አሁን ጊዜው የሚያስቸግር ይመስላል፡፡ ብቁ ናቸው የሚባሉ አሰልጣኞች በአመዛኙ  በብሄራዊ ቡድን ደረጃ ብዙም ልምድ የሌላቸው፤ የሙያ ብቃታቸው ያን ያህል የማያስመካ፤ አንዳንዶቹ በክለብ አሰልጣኝነት ሃላፊነታቸውን ለመልቀቅ የሚቸገሩ ናቸው፡፡ እነዚህ እና ሌሎችም ምክንያቶች ተተኪ አሰልጣኝ ከአገር ውስጥ የማግኘቱን እድሉን ያጠብበዋል፡፡ ከአገር ውጭ አሰልጣኝ ለመቅጠር ደግሞ ከዚህ በፊት ያሉ ተመክሮዎች የሁኔታውን አስቸጋሪነት በይበልጥ ያጎሉታል፡፡ ከአሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በፊት ሁለት የውጭ አገር አሰልጣኞች ነበሩ፡፡  በትውልድ ናይጄርያዊ ሆነው ስኮትላንዳዊ ዜግነት ያላቸው አሰልጣኝ ኢፌም ኦኑራ እና ቤልጅማዊው ቶም ሴንትፌንት ናቸው፡፡
ሁለቱም አሰልጣኞች ከብሄራዊ ቡድን ጋር የነበራቸው ቆይታ አወዛግቧል፡፡ ከዚያ በፊት የነበሩትን ፈረንሳዊ አሰልጣኝ ዲያጎ ጋርዚዬቶ እና የፌደሬሽኑ እሰጥ አገባም በማስታወስ  ብዙ ልምድ መቅሰም ይቻላል፡፡ በአጠቃላይ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን ለማሰልጠን ብቁ ናቸው ተብለው ከውጭ የመጡ አሰልጣኞች ያለው መጥፎ አመላከት ካልተወገደ የሚያሳስብ ይሆናል፡፡ የውጭ አሰልጣኞች የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የማሰልጠን ሃላፊነቱ በምቹ ሁኔታ በነፃነት እንዲሰሩበት  የተሰጣቸው አልነበሩም፡፡ በቂ የስራ ጊዜ በኮንትራት ውላቸው አያገኙም ነበር፡፡  
ከአገር ውስጥ ባሉ አሰልጣኞች ምንም አይነት ክብር አይሰጣቸውም፤ ተባብሮ ከመስራት ይልቅ እንደውም ለውጥ አያመጡም በሚል አስተሳሰብ ዘመቻ ሲደረግባቸው አጋጥሟል፡፡ በሌላ በኩል ለአሰልጣኞቹ የሚከፈለው ደሞዝ እና ሌሎች ጥቅማ ጥቅሞች ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ መጠየቁም ይፈትናል፡፡  ብዙውን ጊዜ የውጭ አገር አሰልጣኞች ቅጥር  ለማከናወንና ክፍያ በመፈፀም ፌደሬሽኑ እቅዱን  እውን የሚያደርገው ክቡር ሼህ አላሙዲ ድጋፍ ላይ በመተማመን ነበር። ክቡር ሼህ አላሙዲ ይህን አይነቱን ድጋፍ መስጠት ካቆሙ ዓመታት ተቆጥረዋል፡፡ አስቀድመው የነበሩ ድጋፎችም በተለያዩ መንገዶች ሲመዘበሩ እና ሲባክኑ ማጋጠሙም ጥሩ ታሪክ አይደለም፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞ በአሰልጣኞቹ የቅጥር ሁኔታ ላይ ፌደሬሽኑ ከየትኛው አካል ጋር ተመካክሮ እንደሚሰራ፤ በምን አይነት መስፈርት አወዳድሮ እንደሚቀጥር እና ለምን እንደቀጠረ በግልፅ ሁኔታ ያልተሰራበት ሆኖ መቆየቱን ማስታወስ ይቻላል። ሌላው ዋና አደጋ የውጭ አገር አሰልጣኞች ከተቀጠሩ በኋላ የሃላፊነት ቆይታቸው በአላስፈላጊ ጫናዎች ሲያጥር፤ በአሰለጣጠን ፍልስፍናቸው እና በቋንቋቸው ከብሄራዊ ቡድን ጋር መግባባት ሲያዳግታቸው፤ ከአገሪቱ ሚዲያዎች ጋር ተቀራርበው ለመስራት ሲቸገሩ እና ከፌደሬሽኑ አካላት ጋር መግባባት ሲሳናቸው እንደነበር ማስታወሱ ተስፋ ያስቆርጣል፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በአህጉራዊ እና በዓለም አቀፍ ውድደሮች በብቁ ተፎካካሪነት እንዲሳተፍ የሚያበቃውን ፕሮፌሽናል አሰልጣኝ  እንዴት ሊያገኝ ይችላል ብቻ ሳይሆን ከተገኘስ የሚጠይቀውን ውድ ክፍያ ማን ይችላል የሚሉ ጥያቄዎች ስጋት ይፈጥራሉ። የሊቢያን ብሄራዊ ቡድን በማሰልጠን በቻን ውድድር ዋንጫ ለማንሳት የቻሉት ፈረንሳዊው ሃቪዬር ክሌሜንቴ ደሞዛቸው እስከ 20 ሺ ዶላር ነው፡፡ በአጠቃላይ አንድ የውጭ አገር አሰልጣኝ ለመቅጠር በወቅቱ የገበያ ሁኔታ ኢትዮጵያ ከ15 እስከ 20 ሺ ዶላር በወር መክፈል ሊኖርባት ይችላል፡፡ ይህ ገንዘብ ታድያ ከየት ይመጣል፤ ከሼህ አላሙዲ ወይንስ ከመንግስት መልስ የሚያስፈልገው ጥያቄ ነው፡፡
ከሰውነት በኋላ ፌደሬሽኑ እና የህዳሴ ስትራቴጂው
በኤሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል በተካሄደው የግምገማ እና የምክክር መድረክ ላይ ከፌደሬሽኑ ፕሬዝዳንት በመቀጠል የመክፈቻ ንግግር ያሰሙት የፌዴራል ስፖርት ኮሚሽን ምክትል ኮሚሽነር አቶ አንበሴ እንየው ነበሩ። ኮሚሽኑ እንደመንግስት የእግር ኳሱ ከፍተኛ ባለድርሻ አካል መሆኑን የጠቀሱት ምክትል ኮሚሽነሩ አቶ አንበሴ፤  እግር ኳስ አንጋፋ እና ፈርቀዳጅ ስፖርት እንደሆነ በመግለፅ የህዝብ አጀንዳና አንድ የልማት ጉዳይ ስለሆነ የግምገማ እና የምክክር መድረኩ በስፖርቱ ህዝብን የሚያስደስት እና የሚያረካ ውጤት ላይ ለሚደረስበት የለውጥ እንቅስቃሴ መነሻ መሆን አለበት ሲሉ ተናግረዋል፡፡
በቀድሞው ፌደሬሽን አማካኝነት ከ2004 እሰከ 2007 በሚል የ3 ዓመት ስትራቴጂክ እቅድ ተዘጋጅቶ እንደነበር ያስታወሱት ምክትል ኮሚሽነሩ፤ በአህጉራዊ እና ዓለም አቀፍ ውድድሮች ለመሳተፍ በሚል ትኩረት ተሰጥቶ በመሰራቱ በተወሰነ መልኩ እቅዱን ማሳካት መቻሉን አመልክተዋል፡፡ ወደፊትም በተሻለ ሁኔታ መሰራት ስላለበት  በአሁኑ ፌደሬሽንም በስትራቴጂክ እቅድ መመራት ያስፈልገዋል ብለዋል፡፡ አቶ አንበሴ እንየው እግር ኳስ የእድገታችን ልዩ መገለጫ መሆን አለበት የሚል ማሳሰቢያቸው  መንግስት ለስፖርቱ ከፍተኛ ትኩረት መስጠቱን ያረጋገጠ ነበር፡፡ በየክልሉ በርካታ ስታድዬሞች እየተገነቡ ናቸው፡፡ አካዳሚዎችም ተመስርተዋል፤ እየተሰሩም ናቸው፡፡  መንግስት በስፖርቱ ሊገኝ የሚችለውን ኢኮኖሚያዊ ጥቅም እና የአገር መልካም ገፅታ ገብቶታል፡፡ የእግር ኳሱ ባለድርሻ አካላት በመንግስት በኩል ለስፖርቱ  የተሰጠውን ትኩረት ያህል ብዙ መስራት እንዳለባቸው መረዳት ይገባል፡፡
በእግር ኳስ ኢትዮጵያ አሸንፋ እንድትወጣ ሁሉም ይፈልጋል ያሉት አቶ ጁነዲን ባሻ፤ በስፖርቱ ኢንቨስትመንት እስከዛሬ ከተደረገው የበለጠ ማሳደግ አለብን ይላሉ፡፡ እንደ ጋና አይነት አገራት በርካታ ታዳጊ ፕሮፌሽናሎችን በማፍራት በአሁኑ ጊዜ ከ354 በላይ ተጨዋቾች በላይ በመላው ዓለም በማሰማራት ከፍተኛ ተጠቃሚ መሆናቸውን ማጥናት እንደሚያስፈልግ ያስረዱት ፕሬዝዳንቱ ፤ ኢትዮጵያ ወጣት ፕሮፌሽናሎችን ለማውጣት ምን መስራት እንዳለባት፤ ስንት አካዳሚዎች ይበቁናል ስንት አካዳሚዎች አሉን እንዴት እንስራባቸው በሚል መንቀሳቀስ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
የስራ አስፈፃሚው እንደሚያስበው በኢትዮጵያ እግር ኳስ የወደፊት ጉዞ ላይ አሰልጣኝ መቀየር ብቻ ለውጥ አያመጣም፡፡ በእርግጥ የዋና ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝነት ቁልፍ ሃላፊነት ቢሆንም ጎን ለጎን በስፋት ለውጥ የሚያስፈልጋቸውም ሁኔታዎችም አሉ፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽን የማስፈፀም ብቃት እና አደረጃጀት ለውጥ እንደሚያስፈልግ ታምኖበታል፡፡ በወጣቶች አና ታዳጊዎች ላይ ባተኮረ ስትራቴጂ ከስርመሰረቱ ካልተሰራ አሰልጣኝ ተጨዋች ሊያገኝ አይችልም በሚል አስተሳሰብም ለውጥ ለመፍጠር ታስቧል፡፡ የስራ አስፈፃሚው አባላት እንደገለፁት በኢትዮጵያ እግር ኳስ ላይ ስርነቀል ለውጥ ለማምጣት ለሚያስችለው ስትራቴጂክ እቅድ የባለሙያ ቡድን ተቋቁሞ ሰነዱ እየተዘጋጀ ነው፡፡  በየካቲት ወር ሰነዱ ሙሉ ተዘጋጅቶ የሚያልቀው ይህ የስትራቴጂ እቅድ በአምስት አመት መርሃ ግብር የተነደፈ መሆኑ ተገልፆ አሁን ያለው ፌደሬሽን በስልጣን ላይ በሚቆይባቸው ቀሪዎቹ 3 ዓመታት በስፋት እንደሚሰራበት፤ ለሚቀጥለው የፌደሬሽን አመራር የሚያወርሰው እንደሚሆንም ተስፋ ተደርጓል፡፡ የፌደሬሽኑ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ተክለወይኒ እንደገለፁት በዚሁ የስትራቴጂ ሰነድ ላይ ከ300 እስከ 400 የሚደርሱ ባለድርሻ አካላትን በማሰባሰብ ውይይት ለማድረግ ፍላጎት እንዳለ ጠቁመው በስትራቴጂክ እቅዱ መሰረት የብሄራዊ ቡድኑ አጠቃላይ አደረጃጀት እና መዋቅር፤ አሰራሩ፤ የሰው ሃይል አደረጃጀቱ በአጠቃላይ እንደሚገመገም እና በተገቢው  መንገድ ከተሰራበት ለውጥ መፍጠር እንደሚቻል ፅኑ እምነት አለን ብለዋል፡፡ በስትራቴጂክ እቅዱ የኢትዮጵያን እግር ኳስ ፕሮፌሽናላይዝድ ማድረግ ወሳኝ መሆኑን ስራ አስፈፃሚው ተስማምቶበታል፡፡
በዚህ የፕሮፌሽናሊዝም አቅጣጫ መሰረት የፕሪሚዬር ሊግ፤ የብሄራዊ ሊግ እና ሌሎች የወጣት እና ታዳጊ ውድድሮች ፕሮፌሽናላይዝድ ማድረግ እነደሚያስፈልግ፤ የክለቦችን አቅም እና አደረጃጀት በማሳደግ ፕሮፌሽናላይዝድ ሆነው እንዲንቀሳቀሱ ማስቻል እንደሚገባ እና የኢትዮጵያ ህዝብ ብዛት እንደከፍተኛ የሰው ሃይል በመጠቀም እግር ኳሱ እንደኢኮኖሚው አድጎ እንዲታይ መሰራት አለበት በሚል ነው፡፡ በወጣት እና በታዳጊ ፕሮጀክቶች፤ መንግስት፤ ክለቦች እና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በስፋት እንዲንቀሳቀሱም ይደረጋል፡፡
የፌደሬሽኑ ምክትል ፕሬዝዳንት አቶ ተክለወይኒ ሃጎስ እንደሚናገሩት የኢትዮጵያ እግር ኳስ ወደፊት በዓለም አቀፍ ደረጃ ተፎካካሪ ሆኖ ለመቀጠል የሚችለው በእውቀት እና በስትራቴጂ እቅድ ሲሰራበት፤ የፕሮፌሽናሊዝም አቅጣጫዎችን ሲከተል ነው ፡፡ በዚህ ረገድ አሁን በስልጣን ላይ የሚገኘው የፌደሬሽን ስራ አመራር ብዙ ጥረት ማድረግ እንደሚጠበቅበትና ኢትዮጵያ ዛሬ በከፍተኛ ደረጃ የሚያፎካክረውን ስፖርት የሚመጥን ደረጃ አግኝታ እንደ ብራዚል ፤ እንደ ስፔን እና እንግሊዝ ተጠቃሚነት እንዲኖራት በመመኘት መስራት ያስፈልጋል በማለት ጥሪ አስተላልፈዋል፡፡

የፍ/ቤቱን ሸፍጥ ያጋለጡት አውሮፓዊ በአፍሪካ መሪዎች ተደንቀዋል
አፍሪካን ቅኝ ለመግዛት የሚደረግ አዲስ ኩሸት ነው ተብሏል
“አውሮፓ የሚሏት እርም የለሽ አህጉር፣ እነሆ ከአንድ መቶ ሃያ አመታት በኋላም አፍሪካንና አፍሪካውያንን ለመዝረፍ እየሞከረች ነው!” አሉ እንግሊዛዊው የፖለቲካ ተመራማሪ ዶክተር ዴቪድ ሆይሌ፡፡
“አውሮፓውያን ያቋቋሙትን ‘አለማቀፍ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት’ የተባለ መላ ተጠቅመው አፍሪካውያንን ባህር አሻግረው እያጋዙ፣ ሆነ ብለው በሰየሙት የይስሙላ ችሎት ላይ እያቆሙ ነው” ሲሉ ደገሙ ዶክተር ዴቪድ ሆይሌ፡፡
ይህም በአዳራሹ ውስጥ የነበሩ በርካቶችን በደስታ አፍለቀለቀ፡፡ ዙሪያ ገባውንም በጭብጨባ አደበላለቀ፡፡ እርግጥም የሰውዬው ንግግር ብዙዎችን ማስደሰቱ ሳይታለም የተፈታ ነው፡፡ ምክንያቱም በዚህ አዳራሽ ውስጥ ከታደሙት የተለያዩ የአፍሪካ አገራት መሪዎች አብዛኞቹ፣ ከአለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድቤት ጋር ቂም የተያያዙና በባላንጣነት የሚተያዩ ናቸው፡፡
በአፍሪካ ፖለቲካዊና የውጭ ግንኙነት ጉዳዮች ላይ በርካታ መጽሃፍትን ለንባብ በማብቃት የሚታወቁት የፖለቲካ ተመራማሪው ዶክተር ዴቪድ ሆይሌ፣ ባሳለፍነው ሳምንት በዚሁ በአዲስ አበባ በተካሄደው 22ኛው የአፍሪካ ህብረት ጉባኤ ላይ ነበር፣ የአገራቱ መሪዎች በተገኙበት ሁለት መጽሃፍቶቻቸውን በይፋ ያስተዋወቁት፡፡
በአፍሪካውያን መሪዎች ተጨብጭቦላቸው ከተመረቁት የዶ/ር ዴቪድ ሆይሌ መጽሃፍት አንዱ፣ ‘የአለማቀፉ ወንጀለኞች ፍርድ ቤት፤ የአውሮፓ ጓንታናሞ ቤይ?’ የሚል ርዕስ አለው፡፡ መሪዎቹ ያጨበጨቡት ለርዕሱ ብቻ አይደለም፡፡
“አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት፣ ለአውሮፓውያን አፍሪካን እንዳትረጋጋ በማድረግ፣ ፖለቲካዊ የበላይነቷን የማሳጣትና የማዕድን ሃብቷን በገፍ የመዝረፍ ድብቅ አጀንዳቸው ማስፈጸሚያ ሆኖ ከርሟል!... ተቀማጭነቱ በሄግ የሆነው ፍርድ ቤቱ፣ አፍሪካን እንደገና ቅኝ ለመግዛት የሚደረግ አዲስ አውሮፓዊ ኩሸት መገለጫ ነው!...” ለሚለው መደምደሚያው ጭምር እንጂ፡፡
ዶክተር ዴቪድ እንደሚሉት፣ ፍርድ ቤቱ በአለም ዙሪያ በሚገኙ 130 በላይ አገራት ተፈጸሙ በተባሉ ኢ-ሰብአዊ ድርጊቶችና ወንጀሎች ዙሪያ ከ8ሺህ 300 በላይ የክስ ማመልከቻዎች ቢደርሱትም፣ እስካለፈው የፈረንጆች አመት 2013 መጨረሻ ድረስ የወንጀል ምርመራ የጀመረው በ8 አገራት ላይ ብቻ ነው፡፡ ይሄም ብቻ አይደለም፡፡ ሰውዬው እንደገለጹት፣ የፍርድ ቤቱን ተልዕኮ ጥያቄ ውስጥ የሚከተው ሌላው አስገራሚ ነገር፣ እነዚሁ ስምንት አገራትም ሁሉም አፍሪካዊ መሆናቸው ነው - ኡጋንዳ፣ ዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ፣ የመካከላዊ አፍሪካ ሪፐብሊክ፣ ሱዳን፣ ኬንያ፣ ኮትዲቯር፣ ማሊና ሊቢያ፡፡
“አንድ እንኳን አፍሪካዊ ያልሆነ አገር፣ በፍርድ ቤቱ የወንጀል ምርመራ እየተደረገበት አይደለም። ራሱን አለማቀፍ የፍትህ ተቋም አድርጎ የሰየመው ይህ የይስሙላ ፍርድ ቤት፣ በአፍጋኒስታንና በኢራቅ የሰሯቸውን የጦርነት ወንጀሎች በተመለከተ በቂ ማስረጃ ከያዘባቸው የተለያዩ አውሮፓ አገራት መንግስታት፣ አንዱን እንኳን ለፍርድ ለማቅረብ አልደፈረም!... ይህም የተቋሙን አድሏዊነት ቁልጭ አድርጎ ያሳያል” ብለዋል ዶ/ር ዴቪድ፡፡
የአውሮፓን ‘ሸፍጥ’ ባጋለጠው አውሮፓዊ የባዳ ዘመዳቸው፣ ዶ/ር ዴቪድ ልባቸው ቅቤ የጠጣ የአፍሪካ መሪዎችም፣ “እኛም ሰሚ አጥተን ነው እንጂ፣ ለፍትህ ቆሜያለሁ እያለ ፍትህን ስለሚገድለው ስለዚህ ወገኛ ተቋም ቀድመን ተናግረናል” ሲሉ በኩራት ተናግረዋል፡፡
አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት፤ እ.ኤ.አ በ2013 በኬኒያው ፕሬዚዳንት ኡሁሩ ኬኒያታና በምክትላቸው ዊሊያም ሩቶ ላይ ክስ መመስረቱን ተከትሎ፣ የፍርድ ቤቱ ጉዳይ ከአፍሪካ ህብረት ቀዳሚ የመነጋገሪያ አጀንዳዎች አንዱ እንደነበር ይታወሳል፡፡ ህብረቱ በዚህ ተቋም ላይ እምነት እንደሌለውና አካሄዱም አህጉሪቱን ክፉኛ የሚጎዳ ህገወጥ ተግባር እንደሆነ በይፋ ከመናገር አልፎ፣ በአህጉሪቱ መንግስታት ላይ የሚሰነዝረውን ውንጀላም መሰረተ ቢስ ሲል አጣጥሎታል፡፡
ህብረቱ በጥቅምት 2013 በጠራው የመሪዎች ልዩ ጉባኤ ላይ የአለማቀፉን የወንጀለኞች ፍርድ ቤት እውቅና የሚነሳ ውሳኔ አሳልፏል፡፡ ተሰሚነት ያላቸው የአህጉሪቱ ቁልፍ መሪዎችም፣ በተቋሙ ላይ ያላቸውን ተቃውሞ በተለያዩ አህጉራዊና አለማቀፋዊ መድረኮች ላይ ማስተጋባታቸውን ቀጥለዋል፡፡
የኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር ሃይለማርያም ደሳለኝ “አፍሪካ ላይ ወዳነጣጠረ የፖለቲካ መሳሪያነት ዘቅጧል” ሲሉ በይፋ የተቹትን ይሄን ፍርድ ቤት፤ የኡጋንዳው ፕሬዚደንት ዮሪ ሙሴቬኒም እንዳይሞት እንዳይድን አድርገው ዘልፈውታል፡፡
የመፅሃፉ ደራሲ ዶ/ር ዴቪድም የአፍሪካ መሪዎች ባገኙት አጋጣሚ ሁሉ በተቋሙ ላይ የሚሰነዝሯቸውን ትችቶች የሚደግፍ ንግግር ነው በህብረቱ ጉባኤ ላይ ያሰሙት፡፡ “ራሱን አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት እያለ የሚጠራው የውሸት ፍርድ ቤት ከተቋቋመበት ጊዜ አንስቶ ያከናወናቸውን ተግባራት ተመልከቱ፡፡ እጅግ ብዙ የመሰሪነት ስራዎችና ተንኮሎችን ሲጎነጉን፣ የአፍሪካ አገራትን በማስፈራራት አልያም መደለያ በማቅረብ በግዳጅ የፍርድ ቤቱ አባል ሆነው እንዲቀጥሉ ሲሞክር እኮ ነው የኖረው!” በማለት፡፡
በህብረቱና በአለማቀፉ ወንጀለኞች ፍርድ ቤት መካከል የተፈጠረው የጠላትነት ስሜት ከጊዜ ወደ ጊዜ ማደጉን ተከትሎ፣ የአፍሪካዊ መንግስታት አለማቀፍ ወንጀሎችን የሚዳኝ የራሳቸውን ክልላዊ የፍትህ ተቋም ወደመፍጠር እንዲገቡ አስገድዷል፡፡
ዶ/ር ዴቪድ እንደሚሉት፤ አውሮፓውያን ይሄንን የአፍሪካ ህብረት አማራጭ ለማሰናከል በቢሊዮን የሚቆጠር ዶላር መድበው እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ፡፡ እ.ኤ.አ በ1998 በአለም ዙሪያ የሚገኙ 122 አገራትን በአባልነት ይዞ በተመሰረተው አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት፣ 34 አገራትን የፍርድ ቤቱ አባላት በማድረግ ከሁሉም አህጉራት ቀዳሚ የሆነችው አፍሪካ ናት፡፡ “ፍርድ ቤቱ 18 የእስያ ፓሲፊክ፣ 18 የምስራቅ አውሮፓ፣ 27 የካረቢያንና 25 የምዕራብ አውሮፓ አገራትን በአባልነት ቢይዝም፤ ጣቱን የቀሰረው ግን በፈረደባት አፍሪካ ላይ ብቻ ነው፡፡ ይህ ነው ፍርድ ቤቱን ፍትሃዊነት በጎደለው ሁኔታ ፍትህን አስከብራለሁ ብሎ የሚዳክር የይምሰል ተቋም የሚያደርገው” ብለዋል ዶክተር ዴቪድ፡፡
በአፍሪካ ጉዳይ ላይ ጥልቅ ጥናት በማድረግ የሚታወቁት ዶ/ር ዴቪድ፤ ስለ አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት ጸረ - አፍሪካ ተቋምነት ሲናገሩ ቅንጣት ታህል ማመንታት አይታይባቸውም።
“አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት አውሮፓዊ ተቋም ነው፡፡ አፍሪካን እዳኛለሁ ብሎ የተነሳ አውሮፓዊ ፍርድ ቤት ነው፡፡ እውነታው ይሄና ይሄ ብቻ ነው!!” በማለት ነው፣ ዶ/ር ዴቪድ በህብረቱ 22ኛ ጉባኤ ላይ ተገኝተው በሙሉ ልብ የተናገሩት፡፡ ይህ የዶክተሩ ንግግር፣ አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት፤ ለፍርድ ይቅረቡ ብሎ በወሰነባቸውና ከችሎት ፊት ሊገትራቸው በሚፈልጋቸው በእነኡሁሩ ኬንያታና ኦማር ሃሰን አል በሽር ልብ ውስጥ ትልቅ ደስታ ፈጥሯል፡፡
ዶ/ር ዴቪድ ሆይሌ ለንባብ ያበቁት አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት፤ የአውሮፓ ጓንታናሞ ቤይ?’ የተሰኘና 345 ገጾች ያሉት መጽሃፍ፤ አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት አጠቃላይ ዓላማና የመጨረሻ ግብ፣ አፍሪካን መልሶ በአውሮፓውያን ቅኝ ግዛት ስር ማድረግ እንደሆነ ያትታል፡፡ ፍርድ ቤቱ ራሱን እንደገለልተኛና ከአድልኦ የጸዳ ተቋም አድርጎ ለማሳየት ቢጥርም እውነታው ግን ከዚህ የራቀ ነው ባይ ናቸው ዶክተሩ፡፡
ፍርድ ቤቱ 60 በመቶ የሚሆነውን በጀቱን የሚያገኘው ከአውሮፓ ህብረት እንደመሆኑ፣ በአውሮፓ አገራት የሚፈጸሙ ወንጀሎችን በድፍረት ለማጋለጥና ወንጀል ፈጻሚዎችን ለፍርድ ለማቅረብ ሞክሮ እንደማያውቅ ገልጸዋል፡፡ ይልቁንም ፍርድ ቤቱ፣ እጅ ያጠራቸውንና ከአጋሮቹ ጋር የፖለቲካ ንክኪ ያላቸውን የአፍሪካ አገራት እየመረጠ በመወንጀል፣ እድሜ ዘመኑን የገፋ የአውሮፓውያን ተላላኪ ነው ይላሉ፤ ዶክተሩ በመጽሃፋቸው፡፡
“አፍሪካ ከቅኝ አገዛዝ ቀንበር ለመውጣትና ነጻነቷን ለመጎናጸፍ ለዘመናት ታግላለች፡፡ ትልቅ መስዋዕትነትም ከፍላለች፡፡ አሁን ደግሞ ከወደ አውሮፓ ዘመን የወለደው ሌላ ‘ህጋዊ’ የቅኝ ግዛት ሙከራ እየተሰነዘረባት ይገኛል፡፡ እዚህ ላይ ዝም ማለት የለባትም፡፡ መክታ መመለስ እንጂ!” ብለዋል ጸሃፊው፡፡
ዶ/ር ዴቪድ በመጪው መጋቢት ወር በይፋ ለንባብ ያበቁታል ተብሎ የሚጠበቀውና ‘ጀስቲስ ዲናይድ፣ ዘ ሪያሊቲ ኦፍ ዘ ኢንተርናሽናል ክሪሚናል ኮርት’ የሚል ርዕስ በሰጡት ሁለተኛው መጽሃፋቸውም፣ ፍርድ ቤቱ በአፍሪካ አህጉር ላይ አነጣጥሮ እየሰራ ያለውንና ለወደፊትም ሊሰራ ያሰባቸውን ኢ-ፍትሃዊ ተግባራት በዝርዝር ይዳስሳል ተብሏል፡፡

ጥንት ዱሮ አያ ቋቴ የሚባሉ ብልህ ሰው ነበሩ ይባላል፡፡ የአያ ቋቴ መታወቂያ ሰው እህል ለመዝራት ገና መሬቱን ሳያለሰልስ እሳቸው እርሻ መጀመራቸው ነው፡፡
“አያ ቋቴ?” ይላቸዋል አንዱ፡፡
“አቤት” ይላሉ
“ምነው እንዲህ ተጣደፉ? በጊዜ እርሻ ጀመሩ?”
“በጊዜ ቋቴን (የዱቄት እቃዬን) ልሞላ ነዋ” ይላሉ፡፡
“መሬቱ የት ይሄድቦታል? ቀስ ብለው አያርሱትም ታዲያ?”
“አርሼውስ የት ይሄድብኛል? ብዘራበትስ መች እምቢ ይላል?”
አያ ቋቴ በጊዜ በማለዳ እየተጣደፉ ሄደው አዝመራቸውን ሲሰበስቡ፤ ገና ያልዘሩ ሰዎች፤
    “አያ ቋቴ?”
    “አቤት”
“አሁን አዝመራው የት ይሄድብዎታል? እንዲህ ሰማይ ዐይኑን ሳይገልጥ እየሮጡ የሚሄዱት?”
“ፈጥኖ የደረሰ እህል አንድም ለወፍ አንድም ለወናፍ ነው፡፡ በጊዜ እጅ የገባ ነገር ጥሩ ነው፡፡ ቋቴ በጊዜ ሞልቶ ቢገኝ ምን ይጎዳኛል?” ይላሉ፡፡  
ቆይተው እየተጣደፉ ሊያስፈጩ እህል በአህያ ጭነው ሲሄዱ ሰዎች ያገኙዋቸዋል፡፡
    “አያ ቋቴ?”
    “አቤት”
    “ወዴት ነው እንዲህ እየተጣደፉ የሚሄዱት?”
    “ወደ ወፍጮ ቤት”
    “እንዲህ በጠዋት፣ እንዲህ እየሮጡ?”
    “አዎን እንዲህ በጠዋት፣ እንዲህ እየሮጥሁ”
    “ምነው ጦር መጣ እንዴ? ፀሐይ ሞቅ ሲል ቀስ ብለው አይሄዱም?”
    “ለቋቴ፡፡ ቋቴ በጊዜ እንዲሞላ ነዋ!”
አያ ቋቴ እህላቸውን አስፈጭተው ማጠራቀሚያ ቋታቸው ውስጥ ከትተው እያስጋገሩ ሲበሉ፣ ሰዉ ገና እርሻ ላይ ወዲያ ወዲህ ይላል፤ በማህል አንዱ ይመጣና
    “አያ ቋቴ?”
    “አቤት”
    “የምንበላው አጣን እባክዎ ዱ    ቄት ያበድሩን”
ሌላው አዛውንት ይመጡና፤
    “የእገሌ ቤተሰብ በረሀብ ሊያልቅ ነው እባክዎ ትንሽ ዱቄት ካለዎት?”
ቀጥሎ የእድሩ ዳኛ ይመጡና፤
“አያ ቋቴ”
    “አቤት”
“እባክዎ የእገሌ ልጅ ሞቶ ለቀስተኛውን እምናበላው አጣን፤ እንደሚያውቁት እህል አልደረሰልንም?”
አያ ቋቴም አይ ያገሬ ሰዎች፤ “ለልመና ሲሆን ሰው ሳይቀድማችሁ ትነሳላችሁ፡፡ እኔ ለቋቴ ማለዳ ስነሳ ታሾፋላችሁ! መቼ ነው ጊዜ ቋት መሆኑ የሚገባችሁ?” አሉ ይባላል፡፡
    *     *     *
ከአያ ቋቴ የምንማረው ለዓላማችን ስንል በጠዋት መነሳትን ነው፡፡ አስቀድሞ መዘጋጀትን ነው፡፡ በጊዜ መሰነቅን ነው፡፡ በጊዜ መክተትን ነው፡፡ ጊዜ የትግል ቋት ነው፡፡ “ጊዜ የስልጣን እጅ ነው” ይላሉ አበው፡፡ ሰው ሳይቀድመን ለልመና ከመነሳት ይሰውረን፡፡
ገጣሚው ራልፍ ኤመርሰን “አልኮል፣ ሐሺሽ፣ ፕሩሲክ አሲድ፣ ካናየን ደካማ ሱሶች ናቸው፡፡ ዋና መርዘኛ ዕፅ ጊዜ ነው” ይለናል፡፡
“የሰዓቱ እጀታ ከምናስበው በላይ እየተንቀረፈፈ ነው፡፡ ረፍዶብናል!” የሚሉት መዝሙር አላቸው ቦሄማውያን፡፡ መርፈዱን መገንዘቢያችን ደቂቃ ወይም ሰከንድ ላይ ነን፡፡ በወሬ የምንፈታው ጦር የለም። በወሬ የምንፈታው ዳገት የለም፡፡ ሁሉ ነገር ሥራ ይፈልጋል፡፡ ነገን ዛሬ እንሻማው፡፡ “ዛሬ ላይ ሆነን ከነገ መስረቅ ነው (Plagiarizing the future)” እንደተባለው ነው፡፡
ዛሬ፤ የለመድነውን ይዘን ከመቀጠል ሌላ የአስተሳሰብ ለውጥ ሽታው ጠፍቷል፡፡ ዕውቅናና ገንዘብ የማሰባሰቢያውን ማሺን እጁ ያስገባ ሰው የሚነግስበት ዘመን ሆኗል! ይሄንን ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ብለን እየተጓዝን ነው፡፡ ሆኖም ፓርቲ እየዘቀጠ ሲሄድ ባለፀጋ መሆን (Fattening) ይበረክታል፡፡ ዝነኛ መሆን ግብ ይሆናል፡፡ ቲፎዞ በመሰብሰብ የሚመራ መሪ ባዶ ገረወይና ነው፤ እንደሚባለው ዓይነት ነገር ይዘወተራል፡፡ ይለመዳል፡፡ ዲሞክራሲ ይህ ከሆነ ዲሞክራሲ ራሱ ገና ዲሞክራሲያዊ መሆን ያስፈልገዋል። (Let’s Democratize Democracy-Fareed Zekaria)
ለማስመሰል በማይሆን ተስፋ መፅናናት ብዙዎቻችንን ላልተጨበጠ መንገድ ይዳርገናል፡፡ አስተሳሰባችን አሜሪካዊው ድራማቲስት ብሩክ አትኪንሰን “አንድ ቀን በፀሐይ ዙሪያ” በሚለው ፅሑፍ ተስፈኝነትን ሲገልፅ፤ ካለው ጋር የሚሄድ ነው፡፡ “አንዳች ተዓምራዊ-ሚሥጥራዊ መንገድ ፍቅር ሁሉንም ድል ይመታል፣ መልካሙ ነገር መጥፎውን በሁለንተናዊው ዓለም ሚዛን መሰረት ይረታል፤ እናም በ11ኛው ሰዓት ክፉ ነገር በእኛ ላይ ከመምጣቱ በፊት አንዳች ገናናና ታላቅ ኃይል ያቆመዋል፤ ይከለክልልናል!” ከዚህ ቢሰውረንና ለመስራት ብንነሳ፣ ለመደራጀት ብንዘጋጅ፣ ውጣ ውረዳችንን ከወዲሁ በተጨባጭ ልንበግረው ብንጣጣር ይሻላል፡፡ ልባችን ዘውድ ለመጫን ያስብ እንጂ እጃችን አፈር አልጨበጠም፡፡
የተለመደ መፈክር፣ የተለመደ የአፍ ወረርሺኝ፣ የተለመደ ከላይ ወደታች ትዕዛዝ፣ የተለመደ ዝቅጠት፣ የተለመደ በሙስና ወደ ሀብት ጉዞ፤ ተፈጥሮ የሰጠን ይመስል ተቀብለነው የምንኖር ልማድ ሆኗል። መብራት ሲጠፋ ለመድነው፡፡ ውሃ ሲጠፋ ለመድን፡፡ ስልክ መስመር ሲጠፋ ለመድን፡፡ ኑሮ ሲከፋ ለመድን፡፡ ይሄንኑ ማማረርንም ለመድን… በመልመድ ተሞላን፡፡
ዛሬ በአገራችን ኢ-ሜይል ሳይሆን “ስኔይል” ተሽሏል እየተባለ ነው፡፡ ከኢሜይል ይልቅ የቀንድ-አውጣ ጉዞ ይሻላል እንደ ማለት ነው፡፡ በአጠቃላይ አነጋገር እየተንቀረፈፍን ነው፡፡ የቴሌ ሥርዓት ዋናው አንቀርፋፊያችን ነው እተባለ ነው፡፡ በእንሰቅርት ላይ ጆሮ ደግፋችን መዓት ነው!
Death and taxes and childbirth! There’s never any convenient time for any of them!
የ “ነገም ሌላ ቀን ነው” ደራሲ ማርጋሬት ሚሼል “ሞት፣ ቀረጥ እና ልጅ-መውለድ ምኔም ምቹ ጊዜ ኖሮት አያውቅም” ትላለች፡፡ ምጡ ከደረሰ ማሰቃየቱ አይቀርም ነው፡፡ ሦስቱ አንድ ላይ ሲመጣማ የመርገምት ሁሉ መርገምት ነው፡፡
በ11ኛው ሰዓት ይላሉ ፈረንጆች፡፡ አዬ፤ አማርኛ ቢያውቁ “ሰርገኛ መጣ በርበሬ ቀንጥሱ” ይሉ ነበረ። ይሄንን ክፉኛ ለምደናል፡፡ ዕዳ የምንከፍለው በ11ኛው ሰዓት ነው፡፡ ስልክ የምንከፍለው በ11ኛው ሰዓት ነው። (ስልክ ባይኖርም)!! መብራት የምንከፍለው በ11ኛው ሰዓት (ውሃው ባይኖርም)!! ለፈተና የምናጠናው በ11ኛው ሰዓት (ትምህርት ቢደክምም ባይደክምም)!! ወደ ሐኪም የምንሄደው በ11ኛው ሰዓት!! (ቢጭበረበርም ባይጭበረበርም)!! ይሄን ልማድ ካልተውን መቼም ህይወትን አንረታም፤ ባላንጣችንንም ተፎካካሪያችንንም አናሸንፍም!!
ሼክስፒር በፀጋዬ ገ/መድህን ብዕር፤
“ዛሬ ለወግ ያደረግሺው፣ ወይ ለነገ ይለምድብሻል
ልማድ ፊት እንዳሳዩት ነው፣ ወይ ይጠፋል ወይ ያጠፋል
ከርሞም የሰለጠነ እንደሁ፣ ተፈጥሮ ይሆናል ይባላል”፡፡ የሚለን ለዚህ ነው፡፡”    

እንዴት ሰነበታችሁሳ!
ስሙኝማ…ተቀምጠን እየሰቀልን እኮ ቆመን ማውረድ አቃተንሳ! ልክ ነዋ…ይኸው በምኑም፣ በምናምኑም በአጋጣሚም ቢሆን ‘ወደ ላይ’ ያወጣናቸው “አይ፣ በቃችሁ…” ምናምን ስንል የሚሰማን አጣን፡፡
እኔ የምለው… መቼም ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… “የተሸነፍነው ስፖርት ጋዜጠኞቹ ግራ አጋብተውን ነው…” ምናምን ተባለ የተባለው…በቃ እንደዚህ የ‘ቻርሊ ቻፕሊን ወራሾች’ ምናምን ሆነን እንቅር! ጭራሽ ታክቲክና ስትራቴጂ በጋዜጠኞች ሆነና አረፈው!
ችግሩ ምን መሰላችሁ…በዛ መያዣ መጨበጫ ባጣን ሰሞን ጋዜጠኞች የኳስ ሰዎቻችንን አወጣን አወጣንና እላይ ‘ጉብ’ ማድረግ! ነገሩ ሲረጋጋና ጎል እያቃሙንና ውራ እያደረጉን ሲልኩን “ለነገሩ እኮ ብዙ ይቀራችኋል…” ሲባል ማን ይስማ! እናላችሁ… እንዲሁ “ከዚህ ያክል ቡድኖች መካከል ምርጥ ተባልን…” “ዓለም በጉጉት የሚጠብቀው የናይጄሪያና የኢትዮጵያ ጨዋታ…” እያልን ነገር ስናሳምር ከረምንና ጭራሽ ቤተክርስትያን የገባች እንትን ጋዜጠኞች ሆነው አረፉት!
(ለነገሩ እንግዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ…አንዳንዶቻችን ጋዜጠኞችም እኮ አለ አይደል…ስናደንቅ ‘ቃላት አመራረጥ’ አልቻልንበትም ነበር፡፡ ቀስ ብለን በምትንቃቃ መሰላል በጥንቃቄ እየተረገጠ እንዲወጣ ከማድረግ ይልቅ መንኮራኩር ውስጥ ከተን እንተኩስና ከዛ ማውረዱ መከራ፡፡
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
ደግሞላችሁ…በስነ ጥበባችን አካባቢ መኮፈስ፣ ‘ማበጥ’፣ ምናምን በሽ እንደሆነ ነው የሚወራው። እናላችሁ…አንድ ፊልም ሲወጣ ለስፖንሰርሺፕ እንዲመችም፣ ለፈረንካውም “መቼም ግሩም የሆነ ፊልም” “ግሩም ትወና” ይባልና ሰዉ ሆዬ ያለክሬንና ያለክንፍ ላይ ወጥቶ ቁብ!
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
እናላችሁ… ያስቸገረን ነገር ኖር ከተሰቀሉበት ማማ ለመውረድ ፈቃደኛ አለመሆን ነው፡፡ አንድ ሰሞን እግር ኳሳችንን  ጄኔቭ ድረስ ሲያሯሩጥ የነበረው… ውረድ እንውረድ ብሎ ነገር የለም፡፡
ደግሞላችሁ…አንዳንድ ምሁራን ዘንድ ብትሄዱ…አለ አይደል… በቤተሰብ ጉባኤ፣ የቢራውን ሂሳብ እንዴት ‘እንደሚያዘጋ’ ዘዴው የገባው… የዓይን መነጽር የሚሰካና የኮቱን ኮሌታ ገደድ የሚያደርግ ሁሉ የአሪስቶትል ደቀ መዝሙር የሚያደርግ ምስኪን ተማሪ… ላይ አውጥተው ያስቀምጧቸውና እንዴት ይውረዱ! “ኧረ እንደ እሱ አይነት ችሎታ ያላቸው መአት አሉ፣ እነሱ እንኳን ላይ ሄደው ሊሰቀሉ አጠገባቸው መሰላልም አሳንሰርም የለም…” ሲባሉ ማን ሰምቶ! ነገርዬው… “እኔን ውረድ የምትሉኝ ማናችሁና ነው…” አይነት ነገር ነው፡፡
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
ሙዚቃ አካባቢ ብትሄዱ… አለ አይደል… አንዱ ዕድለኛ አንድ ሲንግል ይለቅና ምን አለፋችሁ፣ እዚህም እዛም የእሱ ዘፈን ከተማውን ሰቅዞ ይይዘዋል፡፡ ዕድሜ ለኤፍ ኤሞች ምን ችግር አለ! (እኔ እንደውም ከዕለታት አንድ ቀን “ኤፍ ኤም ላይ ‘እንዲህ ተደብቆ የከረመው ድምፀ መረዋ…’ ምናምን የሚሉኝ ከሆነ ሲንግል የማልለቅሳ!” ማለቴ አይቀርም፡፡
እናላችሁ…አንዳንድ ፕሮግራሞች ላይ ስለሆነ ሙዚቃ ወይም ስለ ፊልም ሲወራ ግርም ይላችሁና… “እንደው የሥራው ባለቤቶች የዚሀ አይነት ከመሬት እጅግ ከፍ ብሎ ከመንግሥተ ሰማያት ትንሽ መለስ የሚል አደናቆት ለራሳቸው ይሰጣሉ?” ያሰኛችኋል፡፡
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
አንድ የሆነ የማስቲካም ይሁን የመኪና ማስታወቂያ ላይ ሁለት ቀን ብልጭ ብላ የጠፋች እንትናዬ…በቃ ላይ ወጥታ ጉብ! “ኧረ ቀስ ብለሽ ተራመጅ፣ እንደ ሞዴል ‘ለመነስነስ’ ትደርሽበታለሽ…” ቢባል ማን ሰምቶ! በዚህ ላይ ደግሞ ዙሪያዋን ከበው “አንቺ እኮ የሀበሻ ክሌኦፓትራ ማለት ነሽ…” ምናምን የሚላት አሟሟቂ መአት ስለሆነ ኮከቦቹን ልትነካ ደርሳ ‘ማን፣ ኧረ ማን’ ነው ውረጂ የሚላት!”
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
እናላችሁ… የእልፍኝ አስከልካይ ረዳት እንኳን ሳንሆን እንደ ናፖሊዮንነት የሚቃጣን…አለ አይደል… ላይ አውጥተው ሲሰቅሉን ነው፡፡ ስሙኝማ…ምን ይገርመኛል መሰላችሁ…ሰዋችን ከደግነትም ይሁን፣ “ቲራቲር እንሥራበት …” ከማለት ሲያመሰግንና ሲክብ ምን አለፋችሁ…“አሞራ በሰማይ ሲያይሽ ዋለ…” አይነት ነገር ነው፡፡
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
እናላችሁ፣ ነገርዬው እኮ… አለ አይደል… ሰውን የማይሆን ቦታ አውጥቶ ጉብ ማደረግ፣ ልክ ለራሰ በራ ሰው ለልደቱ የማበጠሪያ ስጦታ እንደመስጠት ነው። አሃ፣ ምን ያደርግለታል… አንደኛውን ጭንቄውን ሊነቀስበት ካልሆነ፡፡ ቂ…ቂ…ቂ…
(“ኧረ የራስህ ጭንቄ! ሁለተኛ፣ አይደለም ክትፎና አሮስቶ ዲቢቴሎ ጮርናቄ እንኳን አታገኛትም። ማበጠሪያህን ብላ…” ምናምን የምትሉ ወዳጆቼ ብስጭታችሁ ስለገባኝ ደብዳቤ ሳታስገቡ፣ ኮሚቴ ሳይቋቋም ይቅርታ አድርጌላችኋለሁ፡፡ የቮድካው ተረኛ ማን ነበር!)
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
ስሙኝማ… እግረ መንገዴን… እንደ ድሮ ቢሆን ኖሮ “ጥር የልጃገረድ ጠር…” አበቃ ማለት ነበር! ለነገሩ ጥያቄ አለን… ለጥር ብቻ የተሰጠው ‘የልጃገረድ ጠርነት ለአሥራ ሦስቱም ወራት ይሰጥልንማ! እኔ የምለው…በዛ ሰሞን፣ ‘ያልተነካ’ ምናምን ነገሩ አሥር ሺህ ብር ያወጣል ነው የተባለው! እኔ የምለው…እሱም እንደ ‘ክትፎ’… አለ አይደል… ‘ኖርማልና ስፔሻል’ ነገር አለው እንዴ! አሀ..ማወቅ አለብና! ነገ ድንገት ዲታ ከሆንን ምድረ ሀብታም ሲያደርግ የነበረውን ነገር ሁሉ “ምን የተለየ ነገር  ቢኖረው ነው! ብለን መሞከራችን አይቀርማ!
እግረ መንገዴን…በቀደም አንድ ድረ ገጽ ላይ “ባልና ሚስት መናጠቅ ብሶበታል” ምናምን የሚል ነገር አንብበን ነበር፡፡ አንድ ተረት አለች…
“አገባሻለሁ ያለ ላያገባሽ ከባልሽ ሆድ አትባባሽ”
ይሄ እንግዲህ ያኔ መነጠቅ እንግዲህ የሚያስፎክር ባልነበረበት ጊዜ ይባል የነበረ ነው፡፡
ዘንድሮ ግን ነገርዬው ተሻሽሎ ምን ሊባል ይችላል መሰላችሁ…
“ባልሽ ነኝ ያለሽ መወሸሙ ላይቀር፣ የማንን ጎፈሬ ታበጥሪ ነበር”
ቂ…ቂ…ቂ… ‘ግጥም ተገጠመ’ ይሏችኋል እንዲህ ነው!
እኔ የምለው…እንገዲህ ጨዋታን ጨዋታ ያነሳው የለ… ማስታወቂያው ሁሉ ‘ግጥም፣ በግጥም’ የሆነው…የግጥም ምሽት ስለበዛ ነው እንዴ! ግራ ገባና…አንዳንዱ የማስታወቂያ ‘ግጥም ድርደራ’ እኮ…የድንጋይ ዘመን ትውስታ ነገር ይመስላል። ይሄኔ እኮ የእኔ ቢጤ አሟሟቂ “ፐ! የሠራኸውን ማስታወቂያ ስሰማ እኮ…ምን አልኩ መሰለህ…ይሄ ሰውዬ ኢትዮጵያ ውስጥ መወለድ አልነበረበትም ነው ያልኩት!” እያለ ‘እዛ ላይ’ ሰቅሏቸዋል!
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
ስሙኝማ…ቦተሊከኞችማ አንዴ ካወጧቸው… አለቀ በሉት! ማን ‘እናቱ የወለደችው’ ነው እነሱን ካሉበት ዙፋን ዝቅ ለማድረግ የሚሞክረውስ…አይደለም መሞከር ማንው የሚያስበውስ! ታዲያላችሁ… የአገራችንን መሽቶ ሲነጋ ‘ጠርቶ የማይጠራ’ ቦተሊካችንን ነገሬ ስትሉ የሚያባላን ስር የሰደደ እምነት ምናምን ሳይሆን ይቺ የ‘ውረድ እንውጣ’ ነገር አትመስላችሁም! “በሦስተኛው ዓለም ቦተሊካ ወጣህ ማለት በቃ ወጣህ ማለት ነው!” ብሎ እቅጩን የሚነግረን ሰው እየጠበቅን ነው፡፡ እናላችሁ…ዘላለም “ማን ባሞቀው ወንበር ማን ይቀመጣል፣ ሰማይ ከምድር ይደባለቃል! ” እየተባለ…የምንጨፍረው “ሠላሳ አንድ ዓመት…” ጠብቀን በምንገባባት የኳስ ውድድር ብቻ ሆኗል፡፡
እናማ… ቁጭ ብለን የሰቀልነውን ቆመን ማውረድ እያቃታን ነው፡፡   
ደህና ሰንብቱልኝማ!