Administrator

Administrator

የአፍሪካ ሞዛይክ የፋሽንና የባህል ትርኢት በሚቀጥለው አርብ ምሽት በሸራተን አዲስ የሚካሄድ ሲሆን በዝግጅቱ አለማቀፍ የፋሽን ሞዴሎችና ዲዛይነሮች ይሳተፋሉ፡፡ የአፍሪካን ሞዛይክ ዳይሬክተር አና ጌታነህ እንደገለፀችው፤ አስራ አምስት የውጪና የሀገር ውስጥ ዲዛይነሮች በሚሳተፉበት ትርኢት፤ እውቅ የዘርፉ  ባለሞያዎች ከኒውዮርክ፣ ከደቡብ አፍሪካና ከሴኔጋል ይመጣሉ፡፡ የኢትዮጵያ ምርጥ ሃያ ሞዴሎች የሚሳተፉበት የፋሽን ትርኢት ምሽት የመግቢያ ዋጋ 500 ብር ሲሆን ገቢው ከአዲስ አበባ 55 ኪ.ሜ ርቀት ላይ በምትገኘው አለልቱ ከተማ ለሚካሄደው የተቀናጀ ልማት ፕሮጀክት ይውላል ተብሏል፡፡ የአፍሪካ ሞዛይክ የፋሽንና የባህል ትርኢት በአዲስ አበባ ሲካሄድ የአሁኑ ለአስራ አራተኛ ጊዜ መሆኑ ታውቋል፡፡

በእናቱ ኢትዮጵያዊ፣ በአባቱ ሆላንዳዊ በሆነው ዳንኤል ጁፕሁክ የተፃፈውና በእውነተኛ ታሪክ ላይ የሚያጠነጥነው “አመፀኛው ክልስ” የተሰኘ መጽሐፍ ሰሞኑን በገበያ ላይ ዋለ፡፡ ደራሲው በ12 ዓመት የእስር ቤት ቆይታው ያሳለፈውን ህይወት ከወህኒ ቤት ከወጣ በኋላ በደች ቋንቋ እንደፃፈው፣ ከዚያም ወደ አማርኛ በመተርጎም እንዳሳተመው ታውቋል፡፡
በአማርኛ ቋንቋ የተተረጐመው መጽሐፍ፤ በአገር ውስጥ በ70 ብር እየተሸጠ ሲሆን በደች ቋንቋ የተዘጋጀው ደግሞ በደቡብ አፍሪካና በአውሮፓ በመሸጥ ላይ እንደሆነ ያገኘነው መረጃ ይጠቁማል፡፡

በአሚር ዩኒስ ረሐስ የተፃፈው “የምሥራቅ ፈርጦች” የተሰኘ ታላላቅ የሐረሪ ተወላጆችን ታሪክ የያዘ መፅሃፍ ባለፈው ሳምንት ለንባብ በቅቷል፡፡ ስምንት የሚደርሱ የሐረሪ ሊቃውንቶችና የታሪክ ምሁራንን የሚያስተዋውቀው መፅሃፉ፤ መታሰቢያነቱን የሥነ ጽሑፍ ባለሙያ ለነበሩት ለአብዱል ሐፊዝ ከሊፋ መሐመድ እና ለመሐመድ ኢብራሒም ሱሌይማን አድርጓል፡፡
በመጽሐፉ ታሪካቸው ከተካተቱት መካከል የሳይንስ ሊቁ ፕሮፌሰር ዘኪ አብዱላሒ፣ የታሪክ ምሁሩ አህመድ ዘካሪያ፣ የሐረር የነፃነት አባት በሚል የተገለፁት ሼህ ኢብራሂም ጋቱርና ሌሎች ለሐረሪ ህዝብና ለኢትዮጵያ እድገት አስተዋጽኦ ያበረከቱ ግለሰቦች ይገኙበታል፡፡ ግለሰቦችም ትውልድ ሊማርበት የሚችል  አኩሪ ታሪክ አላቸው የሚለው ደራሲው፤ በመፅሃፉ ታላላቅ ሥራዎችን የሰሩና የታሪክ ባለውለታ የሆኑ የጥቂት ሐረሪዎችን ታሪክ ለመዳሰስ መሞከሩን በመግቢያው ላይ ገልጿል፡፡ በ413 ገፆች የተቀነበበው መፅሃፉ፤ በ80 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡
በሌላ በኩል በገጣሚ አለማየሁ ነጋ የተፃፉ ግጥሞችን ያካተተ ‹‹የተመዘዙ ሰበዞች›› የተሰኘ የግጥም መድበል ታትሞ ባለፈው ሳምንት  ለገበያ ቀርቧል፡፡ በ72 ገፆች ሰባ ሁለት ግጥሞችን የያዘው የግጥም መፅሐፍ በ30 ብር እየተሸጠ ነው፡፡

የፌዴሬሽን ምክር ቤት በፓርላማ የወጣውን ህግ ሲያሻሽል አሁን የመጀመሪይው ነው፡፡ የቀድሞ መከላከያ ሚኒስትር አቶ ስዬ አብርሃ ተመሳሳይ ጥያቄ አቅርበው ውድቅ ተደርጐባቸው ነበር፡፡
“በሚኒስትር ማዕረግ የገቢዎችና ጉምሩክ ባስልጣን ዋና ዳሬክተር አቶ መላኩ ፈንታ ላይ የቀረበው የሙስና ክስ መታየት ያለበት በከፍተኛ ፍ/ቤት ነው ወይስ በጠቅላይ ፍ/ቤትን” በሚል ለተነሳው ጉዳይ ምላሽ ለመስጠት ለሰዓታት የተከራከሩ የፌደሬሽን ምክር ቤት አባላት፤ የሚኒስትሮች ክስ በጠቅላይ ፍ/ቤት እንዲታይ የሚደነግገው አንቀጽ ከፀረ ሙስና አዋጁ እንዲሰረዝ በ76 የድጋፍና በ8 የተቃውሞ ድምጽ ወሰኑ፡፡
የሙስና ክሶችን በቀዳሚነት የመዳኘት ስልጣን የከፍተኛ ፍ/ቤት እንደሆነ የሚገልፀው የፀረሙስና አዋጅ፣ ሚኒስትሮች ሊከሰሱ ግን በቀጥታ ወደ ጠቅላይ ፍ/ቤት እንደሚቀርብ ይገልፃል፡፡ በ1993 ዓ.ም ኢህአዴግ ውስጥ በተከሰተው ፀብ ከፓርቲው አመራርነት የተባረሩት የቀድሞ መከላከያ ሚኒስትር ስዬ አብርሃ፣ በወቅቱ በሙስና መከሰሳቸው የሚታወቅ ሊሆን፣  ጉዳያቸው በቀጥታ በጠቅላይ ፍ/ቤት እንዲታይ መደረጉን ተቃውመው እንደነበር ይታወሳል፡፡ እንደሌሎች ተከሳሾች የአቶ ስዬ ክስ በከፍተኛ ፍ/ቤት እንዲታይ መከራከሪያ ያቀረቡት ጠበቃ፤ አለበለዚያ ግን ይግባኝ የመጠየቅ የተከሳሽ ህገመንግስታዊ መብትን የሚጥስ ይሆናል ብለዋል፡፡  በፀረ ሙስና አዋጅ የተካተተው አንቀጽ ህገመንግስቱን ስለሚቃረን ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ቀርቦ ውሳኔ እንዲሰጥበት የአቶ ስዬ ጠበቃ ቢከራከሩም፤ ፍ/ቤቱ ጥያቄውን ውድቅ ማድረጉ ይታወሳል፡፡
ጥያቄው እንደገና ፍ/ቤት ውስጥ የተነሳው ከአስር አመታት በኋላ የገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን ከፍተኛ ሃላፊዎች ላይ ከተመሰረተው ክስ ጋር ተያይዞ ነው፡፡ በአንድ በኩል ዋና ዳሬክተሩ አቶ መላኩ ፈንታ በሚኒስትርነት ማዕረግ የተሾሙ በመሆናቸው፣ በፀረ ሙስና አዋጁ መሰረት ጉዳያቸው በጠቅላይ ፍ/ቤት መታየት ይገባዋል የሚል አስተያየት ቀርቧል፡፡ የፀረ ሙስና ኮሚሽን አቃቤ ህጐች፣ በበኩላቸው ሁሉም ሰው በህግ ፊት እኩል እንደሆነ በህገመንግስት ውስጥ በግልጽ ስለሰፈረ፣ የሁሉም ተከሳሾች ጉዳይ በከፍተኛ ፍ/ቤት መታየት አለበት በማለት ተከራክረዋል፡፡ ፍ/ቤቱም፤ የአዋጁ አንቀፆች ከህገመንግስቱ ጋር እንደሚጋጩ ወይም እንደማይጋይጩ የመወሰንና ለዚህ ክርክር እልባት የመስጠት ስልጣን እንደሌለው በመግለጽ ነው፣ ጉዳዩን ለፌዴሬሽን ም/ቤት ያስተላለፈው፡፡  
በፌደሬሽን ምክር ቤት ስር የተቋቋመው የህገመንግስት ጉዳዮች የአጣሪ ጉባኤ፣ ጉዳዩን ከመረመረ በኋላ የውሣኔ ሃሳብ ያዘጋጀ ሲሆን፣ የምክር ቤቱ አባላት ለበርካታ ሰዓታት ተከራክረውበታል፡፡
“በፀረ ሙስና አዋጅ የተካተተው አንቀጽ ህገ መንግስቱን ስለማይፃረር ባለበት ይቀጥል፤ እንዲያውም ህገመንግስቱን የሚያስከብር ነው” በማለት አስተያየት የሰነዘሩ አባላት፤  “ባለስልጣናት በሙስና ሲባልጉ አምነው የተቀበሉትን ህገመንግስት ስለሚጥሱ ይግባኝ በሌለበት ሁኔታ ፍርዳቸው መታየቱ ተገቢ ነው” ብለዋል፡፡ አንዳንድ የምክር ቤቱ አባላት በበኩላቸው  ጉዳዩ ክብደትና እና ጥልቀት ያለው መሆኑን በመጠቆም ጉዳዩን ለማጤን የተሰጠው ጊዜ አጭር ነው የሚል ሃሳብ አቅርበዋል፡፡
በሌላ በኩል፤ “የይግባኝ መብት የሚጣሰው የአቶ መላኩ ብቻ ሳይሆን የአቃቤ ህግም ነው” በማለት የተከራከሩ አባላት፣ ጉዳዩ በከፍተኛው ፍ/ቤት መታየቱ ሁለቱንም ይጠቅማል ብለዋል፡፡ ይግባኝ በሌለበት ሁኔታ ፍርዳቸው መታየት አለበት በሚል የተሰነዘረውን ሃሳብ በመቃወም  ምላሽ የሰጡት የአጣሪ ጉባኤው አባል አቶ ሚሊዮን አሰፋ “የሚኒስትሮች ክስ ከሌላው ሰው ተነጥሎ ይታይ” የሚል ሃሳብ በዜጐች መካከል የመደብ ልዩነት መኖሩን ከሚያመላክት ፊውዳላዊ አስተሳሰብ የሚመነጭ በመሆኑ ተገቢ አይደለም ብለዋል፡፡
በመጨረሻም፤ አከራካሪው አንቀጽ ህገመንግስቱን ስለሚቃረን ከፀረ ሙስና አዋጅ እንዲሰረዝ በ76 የድጋፍና በ8 የተቃውሞ ድምፅ የተወሰነ ሆን፣ እንዲህ ዓይነቱ ውሳኔ ለምክር ቤቱ የመጀመሪያው መሆኑን በመጠቆም ታሪካዊ ውሳኔ ነው በማለት አፈጉባኤው አቶ ካሳ ተክለብርሃን ተናግረዋል፡፡

Saturday, 28 December 2013 12:28

ሴትና ኪነት

እንደውሀ ሀሳብ እየወረድልኝ ድርሰት መፃፍ ህልም ሆኖብኛል፤በቃ መፃፍ አቅቶኛል! አንድ አመት. . . ሁለት አመት. . . ሶስት አመት. . አምስት አመት. . .  ሙሉ ጠበቅሁ፤  ምንም ነገር ብቅ አላለም- አንድ ገፅ ቃለ ተውኔት መፃፍ እንኳ አልቻልኩም!
ድርሰት መፃፍ አቅቶኝ ማዘኔ ሳያንስ የምወዳት ሚስቴ ሜላት መካሻ ጥላኝ ሔደች!
መለየት እንደዱብዳ ወረደብኝ፡፡ የመፃፍ ችሎታዬ ተሟጦ ከእንግዲህ  መፃፍ እንደማልችል በትያትር ቤት ገምጋሚዎች በተነገረኝ በሁለተኛው ወር ምሽት ላይ ወደቤቴ ስገባ ባለቤቴ ጥላኝ እንደሔደች ተነገረኝ፡፡ ኪነትና ሴት ተመካክረው እስኪመስል ከህይወቴ ሰተት ብለው ወጡ። ኪነትና ሴትን አንድ ላይ ማጣት ልቋቋመው የምችለው አልነበረም። መኖር ራሱ ከዚህ በኋላ ምን ያደርግልኛል? ሰው መኖር ያለበት በምክንያት ነው፡፡ የመኖር ምክንያቶቹ በሙሉ የተወሰዱበት ሰው መኖር ምን ያደርግለታል? ለኔ የመኖር ምክንያቶቼ የነበሩት ሴት እና ኪነት ናቸው. . .  ሁለቱን ከተነጠቅሁኝ በኋላ መኖር ከመተንፈስ የዘለለ አይሆንልኝም፡፡  
ሀያ ስምንት ተውኔት ከፃፍኩ በኋላ በድንገት የመፃፍ ኃይሌን ተቀማሁ፡፡ የመፃፍ ችሎታዬን እንደተነጠቅሁ የተረዳሁት ከግማሽ በላይ ቴአትሮቼን ላሳየሁበት ቴአትር ቤት ያስገባሁት የተውኔት ፅሁፍ በተደጋጋሚ ውድቅ ሲደረግ ነበር።  ለመጨረሻ ጊዜ ግምገማ ሲደረግ፤ ገምጋሚዎቹ የተውኔቱን ፅሁፍ ቀሽምነት የሚያሳዩ ነጥቦችን እያነሱ አስተያየት ሲሰጡ ተሸማቅቄ መግቢያ ሳጣ- በቃ መፃፍ እንደማልችል በግልፅ  ገብቶኝ ነበር።  “መፃፍ አለመቻል ማለት የህይወት መጨረሻ አይደለም!” ብዬ ነበር ለራሴ ደጋግሜ የነገርኩት፡፡
ተሳስቼ ነበር፡፡ መፃፍ ለኔ ህይወት ነበር፡፡ ቃላትን መደርደር የህይወት ምልልሴ ነበር፡፡ ድርሰት ከመፃፍ ውጪ ጫማ ማሰር እንኳ አልችልም፡፡ የተወለድኩት እንድፅፍ ነበር የሚመስለኝ፡፡ በድንገት ግን ብዕሬ አልታዘዝ አለኝ፤ቃላት እንደሰማይ ራቁኝ። ለማን አቤት እንደምል አላውቅም. . . . . .
የመጨረሻውን ቴያትሬን ለግምገማ ሳቀርብ የመሞት ያህል ነበር የተሰማኝ፡፡ ከተውኔት ግምገማው ቢሮ ስወጣ ውስጤ ጭር ብሎ ነበር። በቁሜ የተገነዝኩ ያህል፣የራሴን የቀብር ንፍሮ የቀመስኩ ያህል . . . ድንጋጤ አቅሌን ሰውሮ ጭልም እንዳለብኝ ----ምን ነበር የቴያትር ገምገሚው ያለኝ? የቴያትር ገምጋሚው ንግግር በአእምሮዬ ደጋግሞ ያቃጭልብኛል፡፡ እስከ ህልፈተ ህይወቴ ድረስ በህሊናዬ የሚቀመጥ ንግግር ነበር የተናገረው፡፡
“ህሩይ እርግጠኛ ነህ ይህንን ጽሁፍ አንተ ለመፃፍህ?” ነበር ያለኝ ባለማመን፡፡ በአንገቴ ንቅናቄ ማረጋገጫዬን እንዳገኘ ወደኔ አፍጥጦ እያየ. . .
“ህሩይ ይህ ግምገማ በሁለት አመት ውስጥ ስድስተኛ  ሥራህ ላይ ያደረግነው ነው፡፡ አይገባህም እንዴ? በቃ! የጥበብ አድባር ርቃሀለች! መክሊትህን ጨርሰሀል! እስካሁን በሰራኸቸው እና ተመልካችን አጀብ ባሰኙ ሥራዎችህ እየታወስክ ትኖራለህ፡፡ ከእንግዲህ ግን ሙያ ቀይር! ለወጣቶቹ እድል ስጥ!” ሲል  የራሴን መርዶ ለራሴ ነገረኝ፡፡ ሀያ ስምንት ተውኔቶች ተለምኜ በፃፍኩበት መድረክ ላይ አንድ የሚበቃ ሥራ ማቅረብ አቃተኝ! ኪነት ጨርቄን ማቄን ሳትል ጣጥላኝ ሔዳለች. . . . .እብስ!
እውነቱን ስላላመንኩት ነው እንጂ በቃ መጻፍ አልችልም! አልችልም! አልችልም! ቃላት ያጎርፍልኝ የነበረው ምናቤ ሞቷል!
ለሀያ ምናምን ዓመት ያለማቋረጥ የሰራሁት ሥራ መፃፍ ነው! መፃፍ! መፃፍ! በቃላት ነፍስ መዝራት፤ በቃላት ህይወት መዝራት፤ ከህይወት ህይወትን ቀድቼ ህይወት ላላቸው ህይወትን ማጠጣት፡፡ አሁን ግን የህይወት ምንጬ ደረቀ፡፡ የፈጣሪነት ሚናዬን ተቀምቻለሁ!  ሥራዬ መፍጠር ነበር፡፡ ህይወቴ መፍጠር ነበር፡፡ ነበር፣ነበር፣ነበር. . . . . !!! አንድ የሚረባ ፅሁፍ መፃፍ አቅቶኝ አምስት አመት ተቆጠረ፡፡ መፃፍ እችላለሁ የሚለውን እምነት ይዤ ለአምስት አመት ታገልኩ. . .በቃ መፃፍ አቅቶኛል!
አእምሮዬ ድንገት እንደ ሻተር ዝግት አለ! በፊት በፊት ድርሰት እንዴት ነው የሚመጣልህ? ብለው ሲጠይቁኝ እስቅ ነበር- የአለቃ ገብረሀናን አሽሙር እንደሰማሁ፣የቻርልስ ቻፕሊንን ድምፅ አልባ ቧልት እንዳየሁ ሁሉ በሳቅ ፍርስ እል ነበር፡፡ በምድር ላይ ቀላሉ ሥራ በቃላት ሰዎችን መፍጠር፣እንዲናገሩ ፣እንዲያዝኑ ማድረግ ይመስለኝ ነበር፡፡ ሀያ ስምንቱም ተውኔቶቼ የተዋጣላቸው የሚባሉ ነበሩ፡፡ አምስት አመቴ! ቃላት ከአእምሮዬ መፍለቅ ካቆሙ፣ ቢፈልቁም ጣዕም አልባ ደረቅ ቃላት ናቸው፤ታሪክ በጣቴ በኩል አይመጣም፣ ታሪክ ብዬ የምፅፈው ከተራ ዝብዘባ ያነሰ ነው፡፡ በቃ መፃፍ አልችልም!!
አንድ የማላውቀው ኃይል የድርሰት አቅሜን ነጥቆኛል፡፡ የት ሔጄ አቤት እላለሁ? የትኛው ፍርድ ቤት ይግባኜን ይሰማኛል?
ስለማያስችለኝ ከቴያትር ቤቱ ደጃፍ ላይ ሔጄ ቁጭ እላለሁ፡፡ ከየት መጣ ያላልኩት እንባ አይኔን እየበረቀሰው ወደ ጉንጬ ይንፎለፎላል፡፡ ሰዓሊ ብሩሹ ሲደርቅ፣ቀራፂ መዶሻው ሲወልቅ. . . ምን ይላል? . . . ዘፋኝ ድምፁ ሲጎረንን፣ዳንኪረኛ እግሩ ሲሰበር. . . .  ምን ይሆን የሚሰሩት? እኔ ግን ግራ ገብቶኛል! ህይወት ትርጉም አጥታብኛለች፡፡ ስፅፍ እንዴት ደስተኛ ነበርኩ! ስፅፍ እንዴት ሀሴት አደርግ ነበር!. . . . ንስር የሆንኩ ይመስለኝ ነበር፤ሰማየ ሰማያት በርሬ ቁልቁል ዓለምን ሙሉ የምቃኝ ይመስለኛል፡፡ ሥነ-ፅሁፍ ነፃነቴ ነበር፣ ሥነ-ጽሁፍ ቁልፌ ነበር ከተዘጋ የአስተሳሰብ ሳጥን የምከፈትበት. . . . ሥነ-ፅሁፍ ማዕረጌ ነበር የምጠራበት. . .
የመጨረሻ የተውኔት ፅሁፌ በግምገማ እንዲያልፍልኝ ክፉኛ እንደተመኘሁ ትዝ ይለኛል፡፡ እናቴ በጠና በመታመሟ  ገንዘብ ማግኘት ነበረብኝ። የቤት ኪራይ አለ፣ፋሲካ እየደረሰ ነው. . . ገንዘብ ግን የለኝም ነበር፡፡ ገንዘብ እንዳገኝ የተውኔት ፅሁፍ አዘጋጅቼ ለቴያትር ቤቱ አስገባሁ፡፡ በግምገማ ቅስሜን እንደእንስራ ሰበሩት. . . .ይህ ሁሉ ጫና ኖሮብኝ ከኪነት እና ከሴት አንደኛቸው አብረውኝ ካሉ ጭንቅ አጠገቤ አይደርስም ነበር፡፡ ኪነት እና ሴት በአንድነት ሲርቁኝ ግን. . . .የጨለማ ግድግዳ የከበበኝ ይመስለኛል፡፡
በአንድ ተውኔቴ ውስጥ “ማበድ ሲያንሰኝ ነው!” የሚል ገፀ ባህሪ አለ፡፡ የመፅሀፍ ቅዱሱ ኢዮብን አይነት መከራ የሚደርስበት ይኼ ገፀ ባህሪዬ፤ በመጨረሻ የዓለምን ስቃይ መቋቋም አቅቶት አቅሉን ይስታል-ያብዳል፡፡ ካበደ በኋላ ማበዱን የሚያሞካሽበት ቃለተውኔት አለ።  “ባላብድ ይገርመኝ ነበር! ማበድ ሲያንሰኝ ነው!” ይላል ይህ ገፀ ባህሪዬ፡፡ “እንኳን አበድኩ! በጤነኛ አእምሮዬ ይህንን ሁሉ መከራ አልችለውም ነበር!” ይላል። የራሴን ህይወት እየተነበይኩ ነበር ማለት ነው። አንዴት አንድ የተሳካ ተውኔት መፃፍ ያቅተኛል? ማበድ ሲያንሰኝ ነው! ባብድ ይሻል ይሆን? እብደትን ተመኘሁ. . . .
ከድርሰት ውጪ ሰርቼ ገንዘብ ያገኘሁበት ሥራ ኖሮ አያውቅም! ስለዚህ ዓለም ያለጀንበር መኖር የጀመረች መሰለኝ. . . . .ጨለማ!
የመጨረሻ ተውኔቴ በግምገማ ከወደቀ በኋላ መጠጥ መቀማመስ አዘውትሬ ነበር፡፡ አንድ ቀን ከሰዓት በኋላ የተለመደውን አድርሼ ወደ ቤቴ አቅጣጫ ጉዞ የጀመርኩት. . . . .
11፡00 ሰዓት አካባቢ ይሆናል፡፡ ተማሪዎች ከትምህርት ቤት የሚመለሱበት፣ ፀሀይዋ መስከን የምትጀምርበት፣ሠራተኞች ከሥራ ወደ ቤት የሚቻኮሉበት. . . ጓዳናው ላይ ሰው የሚፈስበት የምወደው ሰዓት ነበር፡፡ በዚህ ሰዓት ጎዳና ላይ መውጣት የድርሰት አምሮቴን ይቀሰቅሰው ነበር። ሰውን የማንበብ ሱስ ነበረብኝ፡፡ ብዙ አይነት ፊቶችን ማንበብ እወድ ነበር... የተከፋ፣ የደነገጠ፣ የተደሰተ፣ የተኮሳተረ፣ የፈገገ፣ የሚቸኩል፣ የተናደደ፣ ተስፋየቆረጠ፣ የተቆጣ፣ የተራበ፣ የተፀፀተ ፊት...፤ በፂም የተከበበ፣ በመነፅር የተጋረደ ፊት፤ ሾካካ፣ መልከቀና፣ የዋህ፣ ጅላጅል ፊት. . . .እነዚህን ፊቶች ማየት ነበር የቃላት ክምር፣ የዓረፍተ ነገር ቋጥኝ ወደ አእምሮዬ የሚያንደረድረው፡፡
ምን ሆኖ  ይሆን ያዘነው? ምን ሆና ይሆን የምትስቀው? ለምን ተፀፀተ?. . .እያልኩ የሰዎችን ፊት ካየሁ በኋላ. . . ወደ መመሰጤ እመጣለሁ --- የፈጠራ ሀሳቦች እየተንከባለሉ ወደ አእምሮዬ ዘው ይሉ ነበር፡፡ የሰው ፊት ነበር መጽሀፌ! የተገለጠ፣ያልተደበቀ፣በብራና ያልተለበጠ፣ነፍስ ያለው መፅሀፍ --- የሰው ልጅ ፊት! እነዚህ ሁሉ ትርጉም ከሰጡኝ አመታት ተቆጥረዋል፡፡ የሰው ፊት ሳይ አፍንጫ እና አይን፣ቅንድብና ጉንጭ፣ከንፈር እና ግንባር. . . ወዘተ ብቻ ናቸው የሚታዩኝ፡፡ ከዛ ውስጥ ያለው የሰው ልጅ ማንነት አይታየኝም. . .ምናቤን ተነጥቄያለሁና፡፡
መፃፍ አቅቶኛል! በዚህ ስሜት ውስጥ ሆኜ ወደ ቤቴ እየሄድኩ ነበር፡፡ በመንገዴ ሙሉ የማስበው ስለተለየችኝ  ኪነት ነበር፡፡ ሚስቴ ያኔ አብራኝ ስለነበረች የኪነትን እጦት መፅናኛዬ እሷ ነበረች፡፡ እሷ ጋ እስክደርስ ግን ስለኪነት አስብ ነበር. . . .
መፍጠር መቻል የሚያስገኘው ደስታን ምናልባት የወለደ ብቻ ያውቀው ይሆናል፡፡ መፃፍ ደግሞ ከዚያ ይበልጣል፡፡ የተወለደ ልጅ ነፍስ ካወቀ በኋላ የራሱን የህይወት ትልም እራሱ ነው የሚኖረው። አማልክቱ ናቸው የተወለደ ልጅን እጣ ፈንታ የሚወስኑት፡፡ በድርሰት ግን ከዚያ በላይ መብት አለ፡፡ ገጸ ባህሪን መውለድ ብቻ ሳይሆን ጥሩና መጥፎ እንዲሆን ማድረግ ይቻላል፡፡ ጥቁር አለያም ቀይ የፊት ቀለም መሥጠት ይቻላል፡፡ የፈጠሩትን ገጸባህሪ እንዲሳካለት ማድረግ ይቻላል፡፡ ደራሲነት የአማልክትን እጣ ፈንታ መጋራት ነው፡፡ እስካሁን ከነበሩ ወላድ እናቶች መካከል የልጁን አንድ ስንዝር አፍንጫ ቁመት የጨመረ የለም፡፡ በድርሰት ውስጥ ግን እነዚህ ሁሉ ይቻላሉ፡፡ የሳምሶን ኃይል ፀጉሩ ውስጥ ነበር፤ የጸሀፊ ደግሞ ምናቡ ውስጥ፡፡ ምናቤን ተቀምቻለሁ. . . በቃ ከእንግዲህ መጻፍ አልችልም!
ይኼን እያሰብኩ ቁልቁል ወደ አትክልት ተራ አቅጣጫ መጓዜን ቀጠልኩ፡፡ ከኋላዬ የሁለት ወጣት ልጃገረዶች ሹክሹክታ ይሰማኝ ነበር፡፡
“አየሽው! ህሩይ ማለት እኮ እሱ ነው፡፡ የዛሬ አምስት አመት በቴሌቪዥን ይታይ የነበረው የህልም ዓለም ሰዎች የሚለውን ድራማ አስታወስሽ? የሱ ደራሲ እኮ ነው፡፡” አለች ተለቅ የምትለው፡፡ የህልም ዓለም ሰዎች በሚል የፃፍኩት ድራማ በጣም ታዋቂ ነበር፡፡
“አረ እኔ አላውቀውም!” አለች አነስ የምትለው
“በተደጋጋሚ መፅሔት ላይ ይወጣ ነበር እኮ! ብዙ ቴያትር ፅፏል!. . .”ትልቅየው ልታስረዳት ሞከረች፡፡
ዞር ብዬ አየኋቸው፡፡ ትልቋ አስራ ስምንት፣ትንሷ ደግሞ አስራ ሁለት አመት ቢሆናቸው ነው፡፡ ትልቋ በአውቅሀለው ስሜት ፈገግ አለችልኝ. . . ትንሷ ደግሞ በእንግዳ ስሜት አየችኝ፡፡ ደነገጥኩ! ለአዲሱ ትውልድ የሚሆን ሥራ የለኝም! በቃ እኔ ታሪክ ነኝ!. .. መፃፍ አልችልም፡፡ ልጆቹን ትቼ ጉዞዬን ቀጠልኩ።
ከሸዋ ሱፐር ማርኬት በሶማሌ ተራ አድርጌ፣ ወደ ሰፈሬ ወደ አሜሪካን ግቢ እስክደርስ ድረስ የሚራመድ ግዑዝ አካል ሆኜ ነበር፡፡ ለወትሮው አሜሪካን ግቢ ስደርስ የሚሰማኝ ሰላም አብሮኝ አልነበረም። የአሜሪካን ግቢ ግርግር፣ልባሽ ጨርቅ የሚሸጡ ወጣቶች ውርውርታ፣በትንንሽ ፔርሙዝ ቡና የሚሸጡ ሴቶች፣የወደቀ የጫት ገረባ የሚበላ ፍየል፣ከመስጂድ የሚመለሱ አባት፣መኪና ላይ የሚጫን ካርቶን፣ ረጅም የብረት ቱቦ በትከሻው ተሸክሞ ”ዞር በሉ! ዞር በሉ!” እያለ የሚያስጠነቅቅ ወጣት፣የተደረደሩ የሊስትሮ ዕቃዎች፣የመስጅድ አዛን፣የራጉኤል ቅዳሴ. . . .አሜሪካን ግቢ የሰው እርሻ ነች፣ሰው ግጥግጥ ተደርጎ የተዘራባት የመርካቶ አዝመራ! አሜሪካን ግቢ የድርሰት ሀድራዬ ነበረች። ሰው ሰው የሚሸት ትንፋሽ የምታሸተኝ. . . ሰው ሰው የሚል ስሜት እንዲሰማኝ የምታደርግ. . . . ከቅርብ አመታት ወዲህ ግን አሜሪካን ግቢ እነዚህን ሁሉ አትሰጠኝም! የማየው ተራ ግርግር ነው! የሰዎች ትርምስ - ምክንያቱም ምናቤን ተቀምቻለሁ!
እንዲህ እያሰብኩ ስሔድ. . . . ከኋላዬ ድምፅ ሰማሁ.. .
“ህሩይ!” ወደ መንደራችን መግቢያ መንገድ ጫፍ ላይ ካለው ሱቅ የተሰማ ድምፅ ነበር-የበድሩ ድምፅ። በተረቡ፣በቀልዱ፣በጨዋታው ቀኔን የሚባርክልኝ በድሩ። መከፋቴን ላጋባበት አልፈለግሁም- ዝም ብዬ ወደ ቤቴ አቅጣጫ መጓዜን ቀጠልኩ፡፡
“ህሩይ ፈልጌህ ነው!” በድሩ ተከትሎኝ ነበር፡፡ አጠገቤ ደርሶ ሁኔታዬን ሲያየው ደስ አላለውም፡፡
“ምን ሆነሀል ህሩይ?” በተጨነቀ ስሜት አስተዋለኝ። ምን ሆንኩ እለዋለሁ? ተዘረፍኩ ልበለው? የመፃፍ አቅሜ ተሟጠጠ፣ቃላት አውላላ ሜዳ ላይ ጥለውኝ እብስ አሉ!.. .ሊገባው አይችልም። እንኳን እሱ የገዛ ጓደኞቼ ችግሬን አውቀውት ምን ፈየዱልኝ?  “ you know what has happened to you? It is a writer’s block. ” እያሉ ለገጠመኝ ጉድ ገለፃ ለመስጠት ነው የሚሞክሩት፡፡ “አሜሪካዊው ደራሲ ፍራንሲስ ስኮት በዚህ በሽታ ይሰቃይ ነበር..   The love of the last tycoon የሚል ድርሰት ጀምሮ እስከህይወቱ ፍፃሜ ሳይጨርሰው ነው የሞተው...” ምናምን እያሉ ነገር ያራቅቃሉ።  እኔ የማውቀው ደስታዬን መነጠቄን ነው! የፀሀፊ መዘጋት የሚባል በሽታ እንደያዘኝ ማወቁ ሳይሆን መድሀኒቱን ነበር የምፈልገው፡፡ ከቃላት የማገኘውን ደስታ ድጋሚ ማግኘት የምችልበትን መንገድ! “ሶደሬ ለሁለት ሳምንት ተዝናና! ወደ ውጪ ሀገር ለምን ቫኬሽን አትወጣም?. . .” የአንዳንድ ሰዎች ምክር ነበር፤በሽታዬ እንዲለቀኝ፡፡ እኔ ግን ደራሲ ነኝ. . . ሶደሬ ለሁለት ሳምንት የሚያስኬድ ገንዘብ ብይዝ እናቴን ነበር የማሳክምበት፡፡
“ባክህ ተወኝ በድሩ! ጥሩ ስሜት ላይ አይደለሁም!” አልኩት፡፡
አንድ ነገር  ሊነግረኝ እንደፈለገ ሲያመነታ ቆየና በእሺታ አንገቱን ነቅንቆ ትቶኝ ሔደ፡፡
ወደ ቤቴ ገባሁ፡፡ ቤት ውስጥ ማንም የለም ነበር፡፡
“ሜላት?” የባለቤቴን ስም ደጋግሜ ጠራሁ፡፡ ምላሽ የለም!
የት ሔደች? ሜላት ከሌለች ቤቱ ሊበላኝ ይደርሳል፡፡ ሜላት ባትኖር በነዚህ አምስት አመታት ውስጥ ምን ልሆን እችል እንደነበር ማሰብ ይከብዳል፡፡ የብዙ ነገር መፅናኛዬ ሜላት ናት! እና እሷን ፈለግሁ. .  የት ሔዳ ነው? በእቅፏ ውስጥ ሆኜ ተስፋ መቁረጤን መርሳት ሻትኩ፣በእቅፏ ውስጥ ሆኜ ዓለምን መርሳት፣በእቅፏ ውስጥ ሆኜ ነገን መርሳት. . .ሜላት የመድሀኒት ያህል ናት ለኔ። በጡቶቿ መካከል አስገብታ፣ በጭኖቿ ደግፋ፣ በተስፋ መቁረጥ የደረሰብኝን ሀዘን የምታስረሳኝ መድሀኒቴ፡፡ . . .እና ክፉኛ ፈለግኋት. . . .
ወደ ሞባይሏ ስደውል ተዘግቷል የሚል ምላሽ አሰማኝ፡፡ በድሩ ትዝ አለኝ፡፡ እሱ ጋ መልዕክት አስቀምጣ ይሆናል፡፡ ወደ በድሩ ሱቅ ፈጠን ብዬ ሔድኩ፡፡
“ህሩይ እንኳን መጣህ! ቤት ልመጣ እያሰብኩ ነበር --- ሜላት መልዕክት ነግራኝ ነበር. . .እዚህ ቆመን ከሚሆን ሻይ ቤት ምናምን ሔደን. . . !” አለኝ። በድሩ ከበድ ያለ ጉዳይ ሲጋጥመው “ሻይ ቤት ሔደን እናውራ” የሚል ልማድ አለው፡፡
“በጣም እቸኩላለሁ! የምን መልዕክት ነው አንተ ጋ ያስቀመጠችው?”  አልኩት ነገሩን ለመስማት ጓጉቼ፡፡
“ትንሽ ጥሩ ነገር አይመስለኝም!. . . . . .” አለና በድሩ አቀርቅሮ ሲያስብ ቆየ፡፡ የፊቱን ጭንቀት ሳይ አንድ ጥሩ ያልሆነ ነገር እንዳለ ገመትኩ፡፡
“ግዴለም ንገረኝ ምንድነው? ሜላት ደህና አይደለችም እንዴ?” አልኩት
“ሜላት ሔዳለች ህሩይ!” አለኝ አንገቱን እንዳቀረቀረ
“የት ነው የሔደችው?”
“የት እንደሄደች ባላውቅም ምናልባት ወደ ክፍለ ሀገር እንደሔደች እገምታለሁ!”
“ለምንድነው የሄደችው? አልነገረችኝም እኮ!. . ” በቁጣ ጠየቅሁት
“አልገባህም ማለት ነው ህሩይ! ጥላህ ሔዳለች እያልኩህ ነው! . . . ላትመለስ ሔዳለች እያልኩህ ነው...” በድሩ እንደእድር ጥሩንባ ነፊ ሞቴን ያወጀ መሰለኝ፤ ከዛ በኋላ ያለውን ንግግሩን አልሰማሁትም። ውስጤ የነበረው ባዶነት እንደጥቁር አዘቅት blackhole/ ጥልቅ ሲሆን ይታወቀኛል- ወሰን አልባ ባዶነት!  
እንደቀፎ ባዶ የሆነ አካሌን እየጎተትኩ ወደ ቤቴ ነበር የተመለስኩት፡፡
ሜላት የወትሮ ፉከራዋ ጥዬህ እሔዳለው የሚል ነበር፡፡ ጨክና ታደርገዋለች የሚል እምነት ግን አልነበረኝም! ፈፅሞ!
ለብዙ ዘመን ፅሁፌ ላይ አተኩሬ ለሴት ልጅ የሚሆን ጊዜ አልነበረኝም፡፡ ሜላትን ካየኋት በኋላ ግን የሴትን ልጅ ውበት ችላ ማለቴን መቀጠል አልቻልኩም፡፡ ውድድ! አደረኳት፡፡ ጓደኞቼ እንኳን “ለረጅም ጊዜ አንድም ሴት ሳታፈቅር የቆየህበትን ጊዜ ለማካካስ ይመስላል” እያሉ ለእሷ ባለኝ ፍቅር ላይ ይቀልዱ ነበር፡፡ እንዲህ እንደምወዳት እያወቀች እንዴት ጥላኝ ትሔዳለች?
“ጠብ የሚል ነገር ለሌለው ለምን ጊዜህን እና ጉልበትህን ታጠፋለህ? ሌላ ሥራ ሞክር! መቀየር አለብን፣መሻሻል አለብን. . . ” ከተጋባን ጀምሮ እንዲህ ነበር የምትለኝ ሜላት፡፡  የእኔ ትልቁ መለያ ደግሞ ለሥጋ ማሰብ አለመቻሌ ነው፡፡ ካልሲ እንኳን ገዝቼ መቀየር የሚከብደኝ አይነት ሰው ነበርኩ፡፡ ሜላት ደግሞ የኔ ተቃራኒ ነበረች። የሚታይ የሚዳሰስ ነገር ትወዳለች፡፡ አዲስ የቤት ዕቃ፣መኪና፣የራሳችን ቤት. . .ቢኖረን የደስታዋ ምንጭ ነው፡፡ ለሷ ስል የቲያትር ቤቶችን መድረክ የሚነቀንቅ ተውኔት ለመፃፍ ደጋግሜ ሞከርኩ. . .ግን አልሆነም! በትዳር በቆየንባቸው አምስት አመታት አብዛኛው የቤት ወጪ የሚሸፈነው ሜላት ሰርታ በምታመጣው ገንዘብ ነበር፡፡ አሁን ግን ሔዳለች . . . .
በቃ ተሸነፍኩ! ሴትንም ኪነትንም በተከታታይ ማጣት ይከብዳል፡፡ የሁለቱም ፍቅር ገላንም ነፍስንም የሚያነድ፣የሚያንገበግብ አቅም ነበረው... “ማበድ ሲያንሰኝ ነው!” የሚለው ገፀ ባህሪዬ እያሽካካ የሚያየኝ ይመስለኛል፡፡ ኪነትንም ሴትንም በተከታታይ እንዳጡ ማወቅ ከባድ ነው. . . .ሴትና ኪነት ኪነትና ሴት. . . . .
ሜላት ጥላኝ እንደሄደች ካወቅሁ በኋላ ነገር ዓለሙ ዞረብኝ፡፡
ጥላኝ በሔደች በሶስተኛው ሳምንት አንድ ተአምር ተፈጠረ፡፡ እስከ ውድቅት ድረስ የቤቴን በር ሳልዘጋ በጨለማ ውስጥ በተቀመጥኩበት፤ ተስፋ መቁረጥ፣ብቸኝነት፣ባዶነት፣መሸነፍ. . . ዙሪያዬን እንደጥንብ አንሳ ይዞሩኝ በጀመሩበት አንድ ተአምር ተከሰተ፡፡ ሴት ብቸኝነትን ማርካ የምትገድል ብርቱ ጦረኛ ኖራለች? እያልኩ ሜላትን ክፉኛ በምፈልግበት ወቅት ተአምሩ መጣ፡፡ ሜላት መሸነፌን የምደበቅባት፣ተስፋ መቁረጤን የምከልልባት ስጦታዬ ነበረች፡፡ ሜላት!ሜላት!ሜላት! ብቸኝነት እንደ ውርጭ ነፍሴን አቆረፈዳት. .  ተስፋ መቁረጤን ማስተንፈሻ ፈለግሁ. . . ሜላት ስላልነበረች ሌላ አማራጭ መፈለግ ነበረብኝ. . .
ለሰአታት ከተቀመጥኩበት ተነስቼ መብራቱን አበራሁ፡፡ ከአልጋው አጠገብ ካለች አነስተኛ ጠረጴዛ ላይ ልሙጥ ነጭ ወረቀት ተቀምጧል፡፡ መፃፊያ እርሳሴን አነሳሁ. . . .
“ባዶ ቤት! ” የሚል ርዕስ ከአእምሮዬ ተስፈንጥሮ ወጣ. . . . . . .
እስኪነጋ ድረስ ከተቀመጥኩበት አልተነሳሁም። ሀሳብ እንደ ጢስ አባይ ፏፏቴ እየተንዶሎዶለ ይጎርፍልኝ ጀመር፡፡ ሁሉን አጣሁ ባልኩበት ሰዓት ኪነት አለሁ ማለቷን ማመን አልቻልኩም፡፡ ለሊቱ ተገባዶ በንጋት ሲተካ በማያቋርጥ የምናብ ጉዞ ላይ ነበርኩ. . .እስከረፋዱ ድረስ ስፅፍ ቆየሁ፡፡ በሰው ተከቦ ብቸኝነት የሚሰማውን አንድ ገፀ ባህሪን መሰረት አድርጎ የሚሔድ የተውኔት ፅሁፍ ነበር፡፡  
እያንዳንዷ ቃል ውስጤን ጠርምሳ ስትወጣ ይታወቀኛል. . . . .በቃ! ከአምስት አመት በፊት እንደነበረው! . . . .የሚወጡት ቃላት እስኪገርሙኝ ድረስ፣የሚፈጠሩት ታሪኮች እስኪያስደምሙኝ ድረስ... .እየፃፍኩት የምጓጓለት ፍሰት ነበረው፡፡ የተሳካ ሥራ እንደሚሆን እርግጠኛ ነበርኩ፡፡ እራሴን በመጀመሪያ ያረካኝ ሥራ በግምገማ ፈፅሞ ወድቆ አያውቅም. . . አምስት አመት ሙሉ ያጣሁት ይኼንን ነበር፡፡ ሀያ ስምንት የመድረክ ጽሁፎቼን ስፅፍ የነበረኝ ስሜት እንደተመለሰ ገብቶኛል፡፡
“ተመልሻለሁ!” ብዬ መጮህ አማረኝ! ወይም እንደአርኬሜደስ “ዩሪካ! ተገኝቷል!” እያልኩ በአሜሪካን ግቢ ውስጣ ውስጥ ሰፈሮች፣በወለኔ ግቢ፣በወልደጋግሬ ግቢ፣በጎርዶሜ ወንዝ፣በጌሾ ጊቢ፣በአባኮራን ሰፈር... ብሮጥ በወደድኩ፡፡ መፃፍ፣መፃፍ. . በቃላት ዓለምን መበርበር. . .
ረፋዱ ላይ ትንሽ ድካም ተሰማኝ፡፡ ከድካሜ በላይ ግን የፃፍኩትን ሳይ ማመን አቃተኝ፡፡ ሀያ አምስት ገፅ ያለምንም ስርዝ ድልዝ ፅፌያለሁ፡፡ በዚሁ ፍጥነት ከሔድኩ በሁለት ቀን ውስጥ የተውኔቱን ፅሁፍ ልጨርስ እችላለሁ፡፡ የማይታመን ነገር ነው! ለእናቴ መታከሚያ ገንዘብ እንደማገኝ ሳስብ ደስታ ሰውነቴን ወረረው፡፡ ጽሁፉን አለፍ አለፍ እያልኩ አነበብኩት. . .አምስት አመት ሙሉ የቆየሁት እንዲህ አይነት ፅሁፍ ለመፃፍ ነበር!
አምስት አመት ሙሉ ግን የት ነበርኩ? እንደ ካዝና ቁልፍ የተዘጋብኝ የኪነት መንገድ እንዴት ሊከፈት ቻለ? እንቆቅልሹ ቅርፅ እየያዘልኝ ሲመጣ አንዳች አስደንጋጭ እውነት ውስጤ ዱብ አለ! ሜላትን ካገባሁ- አምስት አመቴ! የተውኔት ፅሁፍ መፃፍ ካቃተኝ አምስት አመት!
የመፃፍ አቅሜ ጥሎኝ የሔደው ሜላትን መከተል ስጀምር ነበር ማለት ነው! ከሜላት ጋር ከተጋባን ጀምሮ አንድ ተውኔትም ቢሆን መፃፍ አቅቶኛል! እውነቱ ይህ ነበር፡፡ ፈጽሞ ልረዳው ያልቻልኩት እውነት. . . ሜላትን ከማግባቴ በፊት ለረጅም አመት ብቻዬን ነበር የኖርኩት -በወንደላጤነት፡፡ ብሶቴን፣ንዴቴን፣ተስፋ መቁረጤን፣ጉጉቴን የምተነፍሰው በጽሁፍ ነበር፡፡ ኪነት መተንፈሻዬ ነበረች. . . ሜላትን ካገባሁ በኋላ ግን የኪነትን ቦታ ምህረት ወሰደች፡፡ ተስፋ ስቆርጥ በምህረት እቅፍ ውስጥ መግባትን እመርጣለሁ. . . . . ነፍሴ የምትተነፍሰው በሴት እና በኪነት በኩል ነው ማለት ነው. . . . አንደኛዋ ስትመጣ ሌላኛዋ ትሔዳለች. . .ሌላኛዋ ስትሔድ አንደኛዋ ትመጣለች. . . .እኩል መሔድ አይችሉም፡፡ ሁለቱም ሀሳብ ይፈልጋሉ፣ሁለቱም ውበት ይፈልጋሉ፣ሁለቱም ቀናተኞች ናቸው. . ሁለቱም ይናጠቃሉ!
ሜላት ስትሔድ ኪነት መጣች. . . . .
ሜላትን መቼም ማጣት የምፈልግ አይመስለኝም። እስከ ዓለም ዳርቻ ድረስ ሔጄም ቢሆን የምፈልጋት ይመስለኛል. . . ለጊዜው ግን ተውኔቱን መጨረስ አለብኝ። ለእናቴ መታከሚያ የሚሆን ገንዘብ ማግኘት ቅድሚያ የምሰጠው ተግባር ነበር፡፡ወደ ውጪ መውጣቴን ትቼ የተውኔት ጽሁፌን ቀጠልኩ፡፡ ለግማሽ ሰአት ያህል ሀሳቤ ሳይደናቀፍ ስጽፍ እንደቆየሁ የውጪው በር ሲከፈት ተሰማኝ፡፡ ማን እንደመጣ ለማየት ከተቀመጥኩበት ተነስቼ ወደ በሩ እየሄድኩ ሳለ አንድ ሰው ወደ ቤት ውስጥ ገባ- ሜላት መካሻ!
ክው ብዬ ቀረሁ! መፃፊያ ብዕሬ ከእጄ ወደቀ፡፡
ሜላት በቆመችበት እንባዋ በጉንጮቿ እየወረደ በሳግ በታፈነ ድምፅ “አልቻልኩም! ምንም ሳታደርገኝ ጨክኜ ጥዬህ ልሔድ አልቻልኩም!” አለችኝ፡፡ ሜላት ተመልሳ ነበር፡፡ ከሶስት ሳምንት በኋላ . . . .
ተሸክማው የነበረውን የልብስ ሻንጣ ተቀበልኳትና ወደ ጓዳ አስገባሁት፤በቆመችበት ጥምጥም አድርጌ አቀፍኳት፡፡ በከንፈሮቼ እንባዋን መጠጥኩት፤ በከንፈሮቿ ሳመችኝ፡፡ እጅግ አድርጋ ናፍቃኝ ነበር፡፡ ሰውነቴ እንደመንቀጥቀጥ እያደረገው ተንሰፈሰፈ፡፡ ወደ አልጋው ተሸክሚያት ሔድኩ. . . . ልብሷን እስክታወልቅ ትዕግስት አልነበረኝም፤በጭኖቿ ውስጥ ለመደበቅ ተቻኮልኩ፡፡
“እወድሀለው! እወድሀለው!” የሚል ለሆሳስ ቃል ሜላት ታሰማለች፡፡ከገላዋ ተጣብቄ “እኔም እወድሻለሁ!” እላለሁ. . . .የኔ ሴት ሆይ እወድሻለሁ! ላንቺ ያለኝ መውደድ በመስዋዕት የታጀበ ነው፡፡ እናቴን እና ኪነትን መስዋዕት የሚያደርግ መውደድ. . .
ከሴትና ከኪነት ሴትን መርጫለሁ! ሴትን ስመርጥ ደግሞ ሌላ ሴትን አጥቻለሁ. . . . . ሴትና ኪነት፣ ኪነትና ሴት. . . .

“ሰው ለማገልገል መፈጠር መታደል ነው”


ራስዎን ያስተዋውቁ …
ስሜ ጌታቸው ተድላ ይባላል፡፡ አሁን የምኖረው አዲስ አበባ ውስጥ ነው፡፡ ትምህርቴ በእርሻ ኢኮኖሚክስና በገጠር ልማት

ሲሆን የመጨረሻው ማዕረጌ PHD ነው፡፡ በዓለም ዙሪያ ብዙ አገሮች ላይ ሰርቻለሁ፡፡ ጡረታ ስወጣ አገሬ ላይ መጥቼ

መፃፍ የጀመርኩ ሲሆን እስካሁን  ወደ ስድስት ያህል መፃህፍትን ጽፌያለሁ፡፡
የመጽሐፍቱን ስም ቢዘረዝሩልኝ?
የመጀመሪያው መጽሀፌ የአባቴ የእርሻ ሥራ ላይ ያጠነጥናል፡፡ ሁለተኛው መጽሐፍ እኔ ሳልጽፈው ክቡር ፀሐፊ ትዕዛዝ

አክሊሉ ሃብተወልድ (በኃይለስላሴ ጊዜ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበሩ ናቸው) እስር ቤት ሆነው የፃፉትን ህዝብ ማወቅ

አለበት በሚል በአማርኛም በእንግሊዝኛም ተረጐምኩት። በመጨረሻም አዲስ አበባ ዩኒቨርስቲ ፕሬስ “የአክሊሉ

ማስታወሻ” በሚል አውጥቶት በርካታ ቅጂዎች ተሸጠዋል፡፡ ከዚያ በኋላ በራሴ ታሪክ ላይ የሚያጠነጥን “የህይወት

ጉዞዬና ትዝታዎቼ” የሚል መጽሐፍ ፃፍኩኝ። ይህን ከጨረስኩ በኋላ “ተስፋ የተወጠረች ህይወት” የሚል መጽሐፍ

ፃፍኩኝ። በደርግ ጊዜ ስድስት ልጆች ከዘመቻ ጠፍተው ወደ ጅቡቲ ሰባት ቀንና ሰባት ሌሊት የተጓዙበትን ታሪክ

ያሳያል፡፡ በመጨረሻም “ከትዝታ ጓዳ” እና “እንደወጡ የቀሩት ኢትዮጵያዊ” የሚል መጽሐፍ ለመፃፍ በቅቻለሁ፡፡
በተባበሩት መንግስታት ውስጥ ለረጅም ጊዜ መስራትዎ ይታወቃል፡፡ እስኪ የት የት እንደሰሩ ይንገሩኝ…
ከ20 አመት በላይ በተባበሩት መንግስታት የምግብና እርሻ ድርጅት (FAO) ነው የሰራሁት፡፡ በልዩ ልዩ አገሮች ለምሳሌ

በሌሴቶ፣ በታንዛኒያ እና በበርካታ አገሮች ሰርቻለሁ፡፡ ከዚያ በኋላ በአለም የስራ ድርጅት (ILO) ውስጥ ገባሁና

በናይጀሪያ ለአምስት አመት ሰራሁ፡፡ መጨረሻ ላይ በሰላም ማስከበር ሥራ በኢራቅ የሰሜኑ ክፍል (ኩርዶች በሚኖሩበት)

ሁለት አመት፣ ባግዳድ ደግሞ ሁለት አመት በአጠቃላይ ለአራት አመት አገልግያለሁ፡፡ ሳዳም ሁሴን በነበሩበት ዘመን

ማለት ነው።  
ጡረታ ከወጡ በኋላ ከመጽሐፍ ውጭ ምን እየሰሩ ነው?
ከመጽሐፍ ውጭ በአሁኑ ሰዓት በበጐ አድራጊ ድርጅቶች ውስጥ በበጐ ፈቃደኝነት ነው የምሰራው። በዋናነት ሜቄዶንያ

የአረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማን ማዕከል ውስጥ ብዙም ባይሆን የአቅሜን ለማድረግ እየጣርኩኝ እገኛለሁ፡፡
ኢትዮጵያ ውስጥ በወላጅ አልባ ህፃናት፣ በሴቶች ጥቃት፣ በትምህርትና የሴቶችን አቅም በመገንባት ዙሪያ የሚንቀሳቀሱ

የበጐ አድራጐት ድርጅቶች አሉ። እርስዎ ለምን ሜቄዶንያን መረጡ?
ሜቄዶንያን የመረጥኩበት ዋናው ምክንያት የአረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማን ማዕከል በመሆኑ ነው። ብዙ በጐ አድራጐት

ድርጅቶች የሚሰሩት በህፃናት፣ በጉዲፈቻ እና በመሳሰሉት ላይ ነው። ሜቄዶንያ የሚሰራው ስራ በጣም ቅዱስና የተለየ

ነው፡፡ ይህን ስልሽ የሌላው መጥፎ ነው፤ ጥቅም የለውም ለማለት አይደለም። ሜቄዶንያ በትንሽ ብር ብዙ ስራ

የሚሰራበት፣ በጐ ፈቃደኞች ያለ ክፍያና ያለ ደሞዝ፣ ደከመኝ ሰለቸኝ ሳይሉ፣ ሽንትና ሰገራ የማይቆጣጠሩትን ሳይጠየፉ

እያጠቡ እያገላበጡ የሚውሉ የሚያድሩበት ድርጅት ነው፡፡ ይህ በእውነት ልብ የሚነካ በመሆኑ የመረጥኩበት ዋነኛ

ምክንያቴ ነው፡፡ መስራቹ አቶ ቢኒያም በለጠን ውሰጅ… በጣም ወጣት ነው፤ ትልቅ ሰው ነው፤ የሚሰራውም ቅዱስ ስራ

ነው፡፡ ይህን የማይሞከር ስራ ሞክሮ ለዚህ የበቃ ፅኑ ልጅ ነው፤ ይህንን ልጅ ደግሞ ማገዝ አለብኝ በሚል ነው

የመረጥኩት፡፡
እንግዲህ በጐ ፈቃደኛ ሲኮን የግድ ገንዘብ ያለው መሆን አያስፈልግም፡፡ የሜቄዶንያ መስራች  የአቶ ቢኒያም መርህ

“ሰውን ለመርዳት ሰው መሆን በቂ ነው” የሚል ነው፡፡ እርስዎ በየትኛው ዘርፍ ነው እርዳታ የሚያደርጉት?   
እኔ እንግዲህ በተለያዩ ዘርፎች ነው የማገለግለው። በቻልኩት ሁሉ፡፡ ለምሳሌ በአስተዳደሩ በኩል እሰራለሁ። ከእኔ

መሰሎች ጋር ስድስት ሆነን “የአማካሪ ግሩፕ” በሚል ቡድን አቋቁመን የማማከር ስራ እንሰራለን። በገንዘብም በኩል

ቢሆን እውነት ለመናገር ያቅማችንን እያደረግን ነው፡፡ ለምሳሌ ታህሳስ 13 ቀን 2006 ዓ.ም በተደረገው የግሎባል ሆቴል

የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ላይ ለማሳተም 64ሺህ ብር ያወጣሁበትን “ከትዝታ ጓዳ” እና “እንደወጡ የቀሩት

ኢትዮጵያውያን” የተሰኙ ሁለት መፃህፍቶቼን 900 ያህል ቅጂዎች ለሽያጭ አቅርቤ ገቢ እንዲያገኙበት አድርጌያለሁ፡፡
እኔ ሁለቱን መፃህፍት በመቶ ብር እንዲሸጡ ነበር የተመንኩት፡፡ ነገር ግን እነሱ ሁለቱን በ150 ብር እንሸጣለን ብለው

በዚህ ዋጋ ሲሸጡ ነበር፡፡ ዘጠኝ መቶውም ካለቀ ወደ 135ሺህ ብር ገደማ ያገኙበታል ማለት ነው፡፡ ይህቺ የእኔ ትንሿ

አስተዋፅኦ ናት፡፡
በሜቄዶንያ ከሚገኙ 300 ያህል አረጋዊያንና የአዕምሮ ህሙማን መካከል አይቼው በጣም ስሜቴን ነክቶታል የሚሏቸው

አሉ?
በአጠቃላይ እዛ ያሉት ሁሉ ልብ ይነካሉ፡፡ ነገር ግን እኔም ሆንኩ ባለቤቴ በጣም ልባችንን የነካው አልጋ ላይ ተኝቶ

የሚገኘው ጌዲዮን የተባለው ወጣት ነው፡፡ 24 ሰዓት እዛው እየተገላበጠ ነው የሚውል የሚያድረው። ሰውነቱ ከወገቡ

በታች ፓራላይዝድ ነው፡፡ (በነገራችን ላይ ጌዲዮን በጣም ወጣት፣ ቀይ፣ እጅግ መልከ መልካም ሲሆን መናገር ባይችልም

መስማት ግን ይችላል፡፡ አጠገቡ ያለች በጣም ወጣት አስታማሚና ተንከባካቢው ብቻ የአፉን እንቅስቃሴ አይታ

ትተረጉማለች፡፡ ከዚህ በፊት የሀብታም ቤተሰብ ልጅ ነበር ተብሏል) ይህ ወጣት በጣም ቆንጆና የሚያሳዝን ነው፡፡
አዲስ አድማስ ላይ የወጡት ኮሎኔል ታሪክም ያሳዝናል፤ ነገር ግን አሁን እርሳቸው በጥሩ ሁኔታ ላይ ነው የሚገኙት፡፡

ከሁሉም ከሁሉም ግን ማን ልቤን እንደሚነካው ታውቂያለሽ? የአዕምሮ ህሙማኑ አረጋዊያን እላያቸው ላይ ሲፀዳዱ

ተሯሩጠው የሚያፀዱትና ንፁህ የሚያደርጓቸው አስታማሚዎች ልቤን ይነኩታል። እውነቱን ልንገርሽ እኔ አላደርገውም፡፡

በዚህ መጠን ሰውን ለማገልገል መፈጠር መታደል ነው፡፡ እና እነዚህ በጐ ፈቃደኞች ዝም ብዬ ሳስባቸው ፅናታቸው

ልቤን ይነካዋል፡፡ እግዚአብሔር ይባርካቸው፡፡
ከመፃህፍቱ በተጨማሪ አንድ ስዕል ለጨረታ አቅርበው ነበር አይደል…?
አዎ! “የቴዎድሮስ የመጨረሻው የመቅደላ ጉዞ” የተሰኘ ስዕል ነበረኝ፡፡ ያወጣላቸውን ያህል ያውጣላቸው ብዬ

ሰጠኋቸው፡፡ ከ10ሺህ ተነስቶ መቶ ሺህ ብር ተሸጠ፡፡ በጣም የምወደው እና ሳሎኔ ውስጥ ሰቅዬው የነበረ ስዕል ነው፡፡

ቴዎድሮስ በፈረስ ላይ ሆነው ሰው ከቧቸው ሲጓዙ የሚያሳይ በጣም ማራኪ ስዕል ነው፡፡
ባለፈው እሁድ በግሎባል ሆቴል የተካሄደው የገቢ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም አጠቃላይ ድባብ ምን እንደሚመስል

ቢገልፁልኝ…
እውነት ለመናገር … የእሁዱ ፕሮግራም ከጠበቅነው በላይ ነበር፡፡ አንደኛ ከ3500 በላይ ሰው ተገኝቷል። በሁለተኛ ደረጃ

ሁሉም እጁን ዘርግቷል፤ በርካታ ብር ለግሷል፡፡ ለምሳሌ አንድ ስዕል ነበር፡፡ የአንዲት ሴት ስዕል ነው፡፡ ዝም ብሎ ስዕል

ነው፤ አንድ 20ሺህ ብር ቢያወጣልን ብለን ነበር የገመትነው፡፡ ነገር ግን 200ሺህ ብር ተሸጠ። ሌላ ስዕል ደግሞ 50ሺህ

ብር ቢያወጣልን ብለን አስበን 300ሺህ ተሸጠ፡፡ ብቻ ሰው የሜቄዶንያ ስራ ገብቶታል፤ መርዳት አለብን ብሎ አምኗል

ማለት ነው፡፡ ሌላው ስለሜቄዶንያ መታወቅ ያለበት በቀን አንድን ሰው ለመመገብ 20 ብር ያስፈልጋል፤ ለቁርስ፣ ምሳና

እራት ማለት ነው፡፡ አሁን ላሉት 300 ሰዎች በቀን 6ሺህ ብር እናወጣለን፡፡ በወር 180ሺህ ሲሆን በአመት 2 ሚሊዮን

አንድ መቶ ሰማኒያ ሺህ ብር ይወጣል፡፡ ይህ እንግዲህ ለምግብ ብቻ ነው። መድሀኒት፣ ልብስ፣ የንፅህና መጠበቂያ፣ እና

ሌሎችንም ሳይጨምር ነው፡፡ የዛሬ አመት ደግሞ ተረጂዎችን አንድ ሺህ የማድረግ እቅድ አለው፡፡ የሜቄዶንያ ተረጂዎቹ

አንድ ሺህ ሲደርሱ ለምግብ ብቻ ወጭው 20ሺህ ብር በቀን ይሆናል፡፡ በወር 600ሺህ ብር ይመጣል፣ በአመት ደግሞ

ወደ 5.5 ሚሊዮን ይሆናል፡፡ ይሄ ልጅ በእናትና አባቱ ቤት ነው 300ውን እየተንከባከበ ያለው፡፡
ታዲያ ተጨማሪ ቤት ሳይኖር እንዴት አንድ ሺህ ሰዎችን መርዳት ይቻላል?  
ያው መንግስት ሊሰጥ ያሰበውን 20ሺህ ሄክታር መሬት ቶሎ ቢሰጥና እዚያ ትልቅ ቤት ተሰርቶ አረጋዊያን ለብቻ፣

ሴቶችና ወንዶች ለብቻ፣ የአዕምሮ ህሙማን ለብቻ ሆነው፤ ክሊኒካቸዉ እዛው፣ ማረፊያቸውም እንዲሁ ሆኖ የተሻለ ስራ

መስራት ቢቻል ደስ ይለኛል፡፡ ቦታው ይገኝ እንጂ ግንባታው ጊዜ አይወስድም፤ ምክንያቱም ህዝብ ይገነባዋል የሚል

እምነት አለኝ፡፡
በእሁድ ዕለቱ ፕሮግራም በአጠቃላይ ምን ያህል ገቢ አገኛችሁ?
እኔ እስከማውቀው ከሶስት ሚሊዮን ብር በላይ ገቢ ተገኝቷል፡፡ ዲኤክስ መኪናም አግኝተናል፡፡ እግዚአብሔር ይመስገን፡፡
ከጨረታውና ከመሰል ነገሮች እንኳን ከ600ሺህ ብር በላይ ነው የተገኘው። ነገር ግን ወጪው ብዙ ነው፡፡ ያውም

ተጠንቅቀው ነው ገንዘቡን የሚያስተዳድሩት፡፡ ይገርምሻል… ሰው ማኮሮኒ ይዞ ይመጣል፣ ዱቄት ይዞ ይመጣል። በረከቱ

ነው መሰለኝ ተረጂዎቹ ጦማቸውን አድረው አያውቁም፡፡ ቢሆንም አሁንም እርዳታዎቹ ተጠናክረው መቀጠል

አለባቸው፡፡
በመጨረሻ ስለሜቄዶንያና ስለ መስራቹ አቶ ቢኒያም ምን የሚሉት ነገር አለ?
ኦ…ህ ስለ ቢኒያም ለመናገር እቸገራለሁ፡፡ እሁድ ዕለት እንኳን ንግግር ሳደርግ ስሜታዊ ሆኜ ነው ያለቀስኩት፡፡
ቢኒያም የእግዚአብሔር ሰው ነው፡፡ ለእነዚህ የአገር ባለውለታዎችና የአዕምሮ ህሙማን እግዚአብሔር የላከው ሰው ነው፡፡
በእንዲህ አይነት ጊዜ እንዲህ አይነት የተቀደሰ ስራ ለመስራት መመረጥና መታደል ያስፈልጋል። እኛ በእርሱ ዕድሜ

በነበርንበት ጊዜ ድግሪያችንን ይዘን፣ ፔኤች ዲ ይዘን፣ ንብረት አፍርተን፣ ቤት ትዳር ይዘን እያልን ነበር የምናስበው፡፡

እርሱ ግን  እንዴት ጉድጓድ ውስጥ የወደቁትን አንስቼ ያገግሙ እያለ ነው የሚጨነቀው፡፡ ይሄ በእውነት መታደል ነው።

ይህን ወጣት ማንኛውም ሰው ተሯሩጦ ማገዝ አለበት። አቶ ቢንያም እንዳለው “ሰውን ለመርዳት ሰው መሆን በቂ

ነው”፡፡
አመሰግናለሁ።  

Saturday, 28 December 2013 11:10

የኢትዮ ቴሌኮም ማስተባበያ

           ጋዜጣችሁ ባለፈው ቅዳሜ ታህሳስ 12 ቀን 2006 ዓ.ም እትሙ ላይ፣ “ከዓመት በፊት ለተበላሸ ሲሚንቶ ማስቀመጫ ከ30ሺ ብር በላይ ወርሃዊ ኪራይ ይከፈላል” በሚል ርዕስ ለቀረበው ሚዛናዊ ያልሆነ ዘገባ የሚከተለውን ምላሽ አቅርበናል፡፡ በመጀመሪያ ደረጃ የዜና ዘገባው ሚዛናዊነት የጎደለው ከመሆኑም ባሻገር በሃቅ ላይ ያልተመሰረተ፣ አንባቢን የሚያሳስት እና የኩባንያችንን ገጽታ የሚያጎድፍ ነው፡፡ በዜና ዘገባው መነሻ “በሶማሌ ክልል በጅግጅጋ ከተማ ለቴሌ ታወሮችና የኔትወርክ ግንባታ ከጅቡቲ ተገዝቶ የገባው ሲሚንቶ ከአንድ ዓመት በፊት መበላሸቱ ቢታወቅም በየወሩ ከ30ሺ ብር በላይ ለግለሰቦች ኪራይ እየተከፈለ የህዝብና መንግስት ሀብት እየባከነ እንደሚገኝ---” ሲል የፈጠራ ሃተታውን ይጀምራል፡፡

ኢትዮ ቴሌኮም እንደ ሌሎች የሃገራችን ክልሎች ሁሉ በተለይ በኢትዮጵያ ሱማሌ ክልል በጅግጅጋ ከተማና በክልሉ ባሉ ወረዳዎች የሚያስፈልጉ ግብዓቶች እና ለሌሎች ንብረቶች ማስቀመጫ የሚያገለግል ግምጃ ቤት በከተማዋ ከሚገኝ የግል ድርጅት ተከራይቶ ሲጠቀም መቆየቱና አሁንም እየተጠቀመበት መሆኑ ይታወቃል፡፡ በዘገባው ተቋሙ መጋዘን መከራየቱ የተገለፀው ትክክል ቢሆንም መጋዘኑ የሚያገለግለው ግን ለሲሚንቶ ማስቀመጫ ብቻ ሳይሆን ለሌሎችም የቴሌኮም ማስፋፊያ ፕሮጀክቱ ግንባታ የሚያስፈልጉ ግብዓቶችና ቁሳቁሶች ለማስቀመጥ ጭምር ነው፡፡

ምንም እንኳን በዘገባው እንደተገለፀው፣ ከንብረቶቹ መካከል የተበላሹ ሲሚንቶዎች ቢኖሩም መጋዘኑ ግን ለፕሮጀክቶች ሥራ የሚያገለግሉ የተለያዩ ንብረቶች ማኖሪያነት እና ለሌሎች ግብዓቶች ማስቀመጫነት እያገለገለ በመሆኑ፣ በዜናው እንደተጠቆመው ያለ አገልግሎት ለመጋዘኑ በከንቱ ክፍያ እየተፈፀመ እንዳልሆነ ውድ አንባቢያን እንዲረዱልን እንፈልጋለን፡፡ ሌላው የዘገባው ስህተት ደግሞ የወርሃዊ ክፍያ መጠን ላይ ነው፡፡ በዜናው እንደተጠቀሰው፣ ለመጋዘን ኪራይ የሚከፈለው ወርሃዊ ክፍያ 30ሺ ብር ሳይሆን 12,360 ብር ነው፡፡ መጋዘኑ በአሁኑ ሰዓትም በእንቅስቃሴ ላይ ለሚገኘው ለቴሌኮም ማስፋፊያ ፕሮጀክቶችና ለሪጅኑ የኦፕሬሽን ስራ የሚሆኑ ንብረቶች የሚቀመጡበትና ለነዚህ ሥራዎች አገልግሎት እየሰጠ ያለ ሆኖ ሳለ “ጥቅም ላይ ለማይውሉ ሲሚንቶዎችና ብረቶች ያለ አግባብ ኪራይ እየተከፈለ ይገኛል” በሚል መዘገቡ ስህተት ከመሆኑም በላይ የአንድ ወገን መረጃን ብቻ በዋቢነት በመጠቀም ለአንባቢያን የቀረበ በመሆኑ የዘገባውን ሚዛናዊነት ጥያቄ ውስጥ ያስገባል፡፡ በጥቅሉ ዜናው ሲዘገብ መረጃውን ከሚመለከተው አካል ማጣራትና ሚዛናዊ ማድረግ እየተቻለ፣ፍትሃዊ ባልሆነ መልኩ የተሳሳተ መረጃ መቅረቡ አግባብ አይደለም፡፡ የኢትዮ ቴሌኮም ኮርፖሬት ኮሙኒኬሽን መምሪያ

•    የልማት ሥራዎች ለብዝሐ ሕይወት አስተዋፅኦ ሊኖራቸዋል ይገባል ተብሏል
•    የተከማቸውን አገልጋይ ለማቀፍ የሚያስችል መዋቅርና አደረጃጀት ተዘርግቷል

በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት አድባራትና ገዳማት ልማትን በማስፋፋት

ሐዋርያዊ አገልግሎትን በዘላቂነት ለማከናወን የሚያስችል ሀብትና ንብረት የሚያፈሩበት የልማት ፈንድ ሊያቋቁሙ መኾኑ

ተገለጸ፡፡ አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት በሰበካ ጉባኤ ከሚሰበስቡት አስተዋፅኦ ጋራ በልማት መስኮች ለሚያገኙት ገቢ

ትኩረት ሊሰጠው እንደሚገባ አቅጣጫ መቀመጡን ለአዲስ አድማስ ያስታወቁት የሀ/ስብከቱ ምንጮች÷ ገዳማትና

አድባራት በአንድ የበጀት ዓመት መጨረሻ ለመደበኛ አገልግሎት ከሚመደበው በጀትና መጠባበቂያው ከሚተርፈው

ገንዘብ ስድሳ በመቶውን (60%) የልማት ፈንድ እንዲያቋቁሙበት የሚያስችል ጥናት መቅረቡን ገልጸዋል፡፡  

ገዳማቱና አድባራቱ በልማት ሥራዎች የሚያገኙት ገቢ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያደገ መምጣቱን  ያስረዱት ምንጮቹ÷ በሒሳብ

አያያዝ ፖሊሲውና ዝርዝር የአፈጻጸሙ መመሪያው መሠረት የሚመሠርቱት የልማት ፈንድ የልማት ተቋማትን

በማቋቋምና በማስፋፋት አብያተ ክርስቲያናቱን ከልመና ለማውጣት፣ የካህናትንና ሊቃውንትን የኑሮ ኹኔታ ለማሻሻልና

የገጠር አብያተ ክርስቲያናትን በዘላቂነት ከመደገፍ ጀምሮ የምግባረ ሠናይ ተግባራትን በስፋት ለማከናወን

እንደሚያገለግል ተናግረዋል፡፡

በልማት ፈንዱ የሚቋቋሙና የሚስፋፋፉ ነባርና አዲስ የልማት ሥራዎችና የምግባረ ሠናይ ተግባራት የሚመሩበት

ፖሊሲና መመሪያም ስለመረቀቁ በምንጮቹ ገለጻ ተጠቁሟል፡፡ የልማት ተቋማቱ የቤተ ክርስቲያኒቱ ዋነኛ ተልእኮ

የኾነውን ሐዋርያዊ አገልግሎትዋን በከተማና በገጠር የማፋጠንና የመደገፍ፣ የምግባረ ሠናይ ድርጅቶቿን በቋሚ የገንዘብ

ምንጭነት የማገልገል አስፈላጊነት እንዳላቸው በፖሊሲው ተዘርዝሯል፡፡
ፖሊሲው ለልማት ተቋማቱ ባስቀመጣቸው መርሖዎች መሠረት÷ በምሥረታና ማስፋፋት ወቅት ለቤተ ክርስቲያን

ምስጢራዊ አገልግሎት እንደ ግብዓት የሚያገልግሉ ዕቃዎችን ለማምረትና ለማከፋፈል ቅድሚያ መስጠት የሚጠበቅባቸው

ሲኾን ተቋማቱ የሚያመርቷቸውና የሚያከፋፍሏቸው ንዋያተ ቅድሳት፣ የኅትመት ውጤቶች፣ የምስል ወድምፅ ሥራዎችና

የመሳሰሉት ከቤተ ክርስቲያኒቱ ዶግማና ሥርዐት፣ ከማኅበረሰቡ ኢትዮጵያዊ ማንነትና ትውፊት አንጻር ታሳቢ

መደረጋቸው መፈተሽና መረጋገጥ እንደሚኖርበት ተመልክቷል፡፡
ፖሊሲው የተፈቀዱ ናቸው የሚላቸው የልማት ተቋማት ለብዝኃ ሕይወት አዎንታዊ አስተዋፅኦ ሊኖራቸው እንደሚገባ፣

በዕውቀቱ የበለጸገ፣ በሥነ ምግባሩ የታነጸ ትውልድ ለማፍራት ትኩረት ሰጥተው መሥራት እንደሚያስፈልጋቸው

በመርሖው አስቀምጧል፡፡ ከተቋማቱ ዝርዝር ውስጥም ኮሌጆችና ማሠልጠኛዎች፣ ማተሚያ ቤቶች፣ የጉዞና አስጎብኚ

ድርጅት በማቋቋም የሆቴልና ቱሪዝም አገልግሎት መስጠት፣ ክሊኒኮችን፣ ሆስፒታሎችንና ፋርሚሲዎችን በማቋቋም

የሕክምና የሕክምና አገልግሎት መስጠትና መድኃኒቶችን ማከፋፈል፣ የግንባታ ቁሳቁሶችን ማቅረብ፣ ለአገልግሎትና ኪራይ

የሚውሉ ሕንጻዎችን መገንባትና ማከራየት፣ ከውጭ የሚገቡ ንዋያተ ቅድሳትን በመተካት የውጭ ምንዛሬ ማዳንና ወደ

ውጭ በመላክ የውጭ ምንዛሬ ማስገኘት፣ የግብርና ውጤቶችን ለሀገር ውስጥና ለውጭ ገበያ ማቅረብ፣ የፋይናንስ ተቋም

አክስዮን መግዛት፣ የመንግሥት የግምጃ ቤት ሰነድና ቦንድ መግዛት ይገኙበታል፡፡
ገዳማትና አድባራት በራሳቸው አልያም በመቀናጀት ተቋማቱን መመሥረት እንደሚችሉ በመርሖው የተገለጸ ሲኾን

ቅንጅቱም አጥቢያ አብያተ ክርስቲያኒቱ ከሌሎች አጥቢያዎች ጋራ፣ አጥቢያዎች ከአዲስ አበባ ሀ/ስብከት ጋራ እንዲሁም

ሀ/ስብከቱና አጥቢያዎቹ ከሌሎች አህጉረ ስብከትና አጥቢያዎቻቸው ጋራ ሊከናወን የሚችልበት የፕሮጀክት አጸዳደቅና

አተገባበር ሥርዐት ማካተቱ ተገልጧል፡፡
በልማት ፈንዱ የሚቋቋሙና የሚስፋፉ ተቋማት ካህናትና ሊቃውንት ከመደበኛ ተግባራቸው  በተጨማሪ

እንደየዝንባሌያቸው በተለያዩ ክሂሎቶች እየሠለጠኑ እንዲሠማሩ በማስቻል የሥራ ዕድል እንደሚፈጥሩላቸው፣

በአገልግሎታቸውም እንዲበረቱ ተገቢውን በማሟላት አስተዋፅኦ እንደሚያደርጉላቸው ታምኖባቸዋል፡፡ የልማት ተቋማቱ

ወደፊት በሀ/ስብከቱ እንደአስፈላጊነቱ ከሚተከሉት አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናት ጋራም ተነጻጻሪ መስፋፋት

እንደሚኖራቸው ተጠቁሟል፡፡

የአዲስ አበባ ሀ/ስብከት 169 በሚደርሱት አጥቢያ አብያተ ክርስቲያናቱ ባሰራጨው ቅጽ እየሰበሰበው የሚገኘው

የአገልጋዮች ጠቅላላ መረጃ፣ በአሁኑ ወቅት አድባራቱና ገዳማቱ ልዩ ልዩ ክህሎትና ልምድ ያላቸው አገልጋዮች

እንዳሉባቸው የሚያመላክቱ ናቸው ያሉት ምንጮቹ÷ ይህም ለልማት ተቋማቱ ከሚፈጥረው የሰው ኃይል አቅም ባሻገር

የቤተ ክርስቲያኒቱን ትምህርት ከዘመናዊው ሞያ ጋራ በአቻ ግመታ በማስቀመጥ በአምስቱ የአጥቢያ አብያተ ቤተ

ክርስቲያናት መዋቅርና አደረጃጀት ውስጥ በሚሠራው የሰው ኃይል ትመናና ምደባ በርካታ የአገልጋይ ቁጥር ለማስተናገድ

እንደሚያስችል ተመልክቷል፡፡

“ጋዜጠኞች ታስረዋል አልታሰሩም?”

      ከአዘጋጁ- ባለፈው ሳምንት በኒውዮርክ የሚገኘው የጋዜጠኞች መብት ተሟጋች ድርጅት (CPJ) ባወጣው ዓመታዊ ሪፖርቱ ጋዜጠኞችን በማሰርና በማሰቃየት ኤርትራን በቀዳሚነት በማስቀመጥ ኢትዮጵያንና ግብፅን በሁለተኛነትና በሦስተኛነት ደረጃ ላይ አስቀምጧቸዋል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት በተደጋጋሚ “ከጋዜጠኝነት ሙያው ጋር በተያያዘ ያሰርኩት አንድም ጋዜጠኛ የለም፤ በእስር ላይ ያሉት በሽብርተኝነት ተፈርዶባቸው የታሰሩ ናቸው” ቢልም ሲፒጄ ግን በሽብር ሽፋን ለእስር የተዳረጉ ጋዜጠኞች እንደሆኑ በሪፖርቱ ገልጿል፡፡ በአገሪቱ ያለውን የፕሬስ ነፃነት ሁኔታ አጥብቆ የሚተቸው የጋዜጠኞች መብት ተሟጋቹ ሲፒጄ፤ ከመንግስት በደረሰባቸው ማስፈራሪያና ወከባ በርካታ ጋዜጠኞች ለስደት እንደተዳረጉ ሲገልፅ ቆይቷል፡፡ ድርጅቱ ባለፈው ሳምንት ይፋ ያደረገውን ሪፖርት አስመልክቶ የመንግስት ባለሥልጣን፣ የጋዜጠኞች ማህበር አመራሮችና የተቃዋሚ ፓርቲ መሪ በማነጋገር የሰጡትን አስተያየት እንደሚከተለው አጠናቅረን አቅርበነዋል፡፡

“ሲፒጄ ፖለቲካዊ አጀንዳ ያለው ነው”

(አቶ ሽመልስ ከማል፤ የመንግስት ኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ፅ/ቤት ሚኒስትር ዴኤታ) በመጀመሪያ ሲፒጄ የኢትዮጵያ ጋዜጠኝነት እንዲያድግና እንዲስፋፋ አይፈልግም፡፡ ፖለቲካዊ አጀንዳ ያለው፣ መንግስት በኃይል ለመለወጥ ከሚንቀሳቀሱ ድርጅቶች ጋር የሚንቀሳቀስ፣ በጋዜጠኝነት ታፔላ ድጋፍ የሚሰጥ ድርጅት ነው። ሥራው ከጋዜጠኝነት ጋር ምንም ግንኙነት የለውም፤ ከእርሱ ጋር ከሚጠቃቀሱት አንዱ አምነስቲ ኢንተርናሽናል ነው፡፡ አምነስቲ ሲፒጄን፣ ሲፒጄ አምነስቲን --- እርስ በእርስ እየተጠቃቀሱ፣ አንዳቸው ያንዳቸውን የፈጠራ ውሸት እየያዙ፣ የአገራችንን ስም ሊያበላሹ የሚጮሁ፣ ስነምግባር የሌላቸው ተቋማት ናቸው፡፡ እናውቃለን… የፖለቲካ አጀንዳ እንዳላቸው። ሁለተኛ በኢትዮጵያ የትኛው ጋዜጠኛ ነው የታሰረው? እንግዲህ እናንተም የምትኖሩባት አገር ናት፤ እናንተ መቼ ታሰራችሁ? የማታውቁት ከማርስ የመጣ የታሰረ ጋዜጠኛ አለ እንዴ ? ከቁጥሩ ብዛት ኢትዮጵያን ከአለም ሁለተኛ ሊያስብላት የሚችል---? እንዲህ ነው--- እነ ዳንኤል በቀለ እየፈተፈቱ ሲሰጧችሁ የምትቀበሉት!! የሂውማን ራይትስዎች የአፍሪካ ዴስክ ሃላፊ ዳንኤል በቀለ፣ የቅንጅት መሪ ነበረ፡፡ በ97 በሰብአዊ መብት ድርጅት ስም መንግስት ለመገልበጥ ሲሰራ ተፈርዶበት በምህረት የወጣ ነው፡፡ ይሄ ግለሰብ መንግስት ለመገልበጥ አንዴ የጋዜጠኛ ማህበር አቋቁሙ እያለ ቅስቀሳ ያደርጋል፡፡ በየትም በየትም ብሎ ይህንን መንግስት በብረትድስት ከትቶ በምድጃው ላይ መጣድ ነው የሚፈልገው፡፡ ገለልተኛነት በሌላቸውና ችግር ላይ በወደቁ ግለሰቦች የሚፃፉ አስተያየቶችን በመፃፍ የእነሱ መሳሪያ አትሁኑ፡፡ ኢትዮጵያ በጋዜጠኝነት ያሰረችው አንድም ጋዜጠኛ የለም፤ ካለ ይምጣና “እኔ በጋዜጠኝነት ስራዬ ምክንያት ታስሬአለሁ” ይበል፡፡ ግን በጋዜጠኝነት ምክንያት የታሰረ የለም።

ቆይ የሚታመነው ማነው? የኢትዮጵያ ፍርድ ቤት ነው ወይስ ሲፒጄ? የኢትዮጵያ ፍርድቤት ርዕዮት አለሙ ላይ ፅፋ ነው የፈረድኩባት አላለም፡፡ በፃፈው ተፈርዶበት የታሰረ አለ ከተባለ ዶክመንቶችን ማገላበጥ ያስፈልጋል፡፡ ማንም ደግሞ አልታሰረም። ይህ አልሆነም፡፡ ከምላሴ ላይ ፀጉር ይነቀላል፡፡ ሲፒጄ ስላጨበጨበ፣ ዳንኤል ስለጮኸ እና ብሩን ስለበተነ፣ የግንቦት ሰባት መፅሄቶች ስለጮሁ እውነቱ ተገልብጦ ይቀርባል፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ያላችሁ ጋዜጠኞች ታያላችሁ፣ ትሰማላችሁ፣ ታገናዝባላችሁ፣ እስኪ በፃፈው ፅሁፍ ታሰርኩ የሚል ካለ አምጡ፡፡ የሲፒጄ ቃል የሙሴ ቃል አይደለም፤ ለምን እንደ ጣኦት ታመልኩታላችሁ? በጣም እምናዝነው---- እዚህ አገር ያሉ በሳል ጋዜጦች ላይ እንዲህ አይነት ነገሮች መፃፋቸው ነው፤ የዚህ ዘመቻ ሰለባዎች መሆናቸው ያሳዝነናል፡፡ ይሄ የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ነው፤ “መንግስት ከቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ህልፈት በኋላ አቋሙን ይቀይራል” ብለው ትንሽ ፋታ እንስጠው በማለት ለትንሽ ጊዜ ያቆሙት ነገር እንጂ ከዚህ በፊትም ሲያወሩት የነበረ ነው፡፡ ሲፒጄ እድሜውን ሁሉ መግለጫ ሲያወጣ፣እኛም መልስ ስንሰጥበት ነው የኖርነው፡፡ አዲስ አይደለም፡፡ ሲፒጄ መቼ ነው ስለኢትዮጵያ መልካም ነገር ተናግሮ የሚያውቀው? በፕሬስ ህጉ ላይ ሳይቀር “ኑ ና እንነጋገር” ብለናቸው ሽሽት ነው የመረጡት፡፡

ስለዚህ ሲፒጄ በኢትዮጵያ ጋዜጠኞች ላይ የተሰነዘረ ስድብ ነው፡፡ እንዲህ የሚያደርገው ኢትዮጵያ ውስጥ ጋዜጠኝነት የለም ብሎ ስለሚያምን ነው፡፡ እግራቸው ሸብረክ ሲል ወንበር የሚያቀርቡላቸው በጋዜጠኝነት ስም የሚነግዱ አሉ፡፡ እነሱን ስለለመደ ሌሎቹን እንደ ባለሙያ አይቆጥርም፤ ስለዚህ ኒውዮርክ ውስጥ ቁጭ ብሎ ኢትዮጵያ ጋዜጠኞችን በማሰቃየትና በማሰር ከአለም ሁለተኛ ነች ይላል - እናንተ አፍንጫው ስር ቁጭ ብላችሁ፡፡ ፈረንጅ የተናገረው ሁሉ ለምንድነው እንዳለ የሚወሰደው? ሁሌም አምኖ መቀበል ነው እንጂ ጉዳዩን ለማጣራት ሲሞከር አይታይም፡፡ “ሲፒጄ የወሮበሎች ቡድን ነው” (የኢብጋህ ፕሬዚዳንት፤አቶ አንተነህ አብርሃም) ሲፒጄ ኢትዮጵያን በተመለከተ ባወጣው ሪፖርት ላይ የማህበርዎም ሆነ የእርሶ አቋም ምንድነው? ሲፒጄ ያወጣው የተዛባ መረጃ ነው፡፡ ኢትዮጵያ በአለም በምንም ሁለተኛ አይደለችም፡፡ የሀገራችንን ስም ለማጥፋት ስለሚፈልግ ነው፤ ምክንያቱም ድርጅቱ ከኢትዮጵያ መንግስት ጋር ከፍተኛ የሆነ የጥቅም ችግር ያለበት ነው፡፡ የሦስት እስረኛ ጋዜጠኞችን ቁጥር ከፍ አድርጐ ማውራት ምንም አይጠቅምም፡፡ እነሱም የታሰሩት በአሸባሪነት ተጠርጥረው ነው እንጂ በጋዜጠኝነታቸው በፃፉት ፅሁፍ አይደለም፡፡ ሲፒጄ እውነተኛ ከሆነ ቱርክ ስለታሰሩት 64 ጋዜጠኞች ለምን አያወራም፡፡ ግን በማያገባው ነው የሚገባው፡፡ ሲፒጄ፤ በእስር ላይ ያሉት ጋዜጠኞች በአሸባሪነት ነው የታሰሩት የሚለውን እንደማይቀበል ይገልፃል። እርስዎ በታሰሩት ጋዜጠኞች ዙርያ አቋምዎ ምንድነው? የታሰሩ ጋዜጠኞች አሉ፤ ግን የታሰሩት በፃፉት ፅሁፍ አይደለም፡፡

ማህበራችሁ ለየትኞቹ ጋዜጠኞች መብት ነው የቆመው? እስካሁን የታሰሩ ጋዜጠኞችን ለማስፈታት ጥረት አድርጓል? እኛ የምንቆመው ከሙያ ጋር በተያያዘ ለታሰረ ጋዜጠኛ ነው፡፡ በፃፈው ፅሁፍ የተነሳ የሚታሰር ጋዜጠኛን ወዲያው እናስፈታለን፡፡ የማህበራችሁ አባላት የየትኛው ሚዲያ ጋዜጠኞች ናቸው ? ምን ያህል አባላትስ አላችሁ? የግልም የመንግስትም ጋዜጠኞች አባሎቻችን ናቸው፡፡ በአጠቃላይ 600 አባላት አሉን፡፡ ከአገር ውጪ የምስራቅ አፍሪካ ጋዜጠኞች ምክትል ፕሬዚዳንት ነን፡፡ እኛ በማውገዝ አናምንም፤ በውይይት እንጂ፡፡ በአሁኑ ሰአት የጋዜጠኞች እስር ቆሟል፤ ይህም የሆነው በኛ ጥረት ነው፡፡ የ“ኢትዮ ምህዳር” ጋዜጠኞች ከጥቂት ወራት በፊት ተከሰው አዋሳ በሄዱ ጊዜ አንደኛው ባልደረባቸው ላይ ከፍተኛ አደጋ ደርሶበታል፡፡ እነዚሁ ጋዜጠኞች ለገጣፎ ለሁለትና ለሶስት ቀናትም ታስረው ነበር፡፡ ነገር ግን የትኛውም የጋዜጠኞች ማህበር እንዳልጎበኛቸው ነግረውናል…ማህበራችሁ ለየትኞቹ ጋዜጠኞች መብት ነው የሚቆመው? መታሰራቸውንም መከሰሳቸውንም በጋዜጣቸው ላይ ሲፅፉ ነው የምንሰማው እንጂ ለኛ መጥቶ የነገረን የለም፡፡ አደጋ ደረሰበት ስላልሽው ልጅም ጓደኞቹ ወይም ቤተሰብ ከጠየቀን እንረዳለን፣ ካልጠየቀን ግን በስሙ እርዳታ አንለምንም፡፡ ማንም ጋዜጠኛ ታስሮ ወደ የትም ክልል እንዳይወሰድ ከመንግስት ባለስልጣናት ጋር ተነጋግረን መተማመን ላይ ደርሰናል፡፡ የጋዜጠኞች ማህበር እንደመሆናችሁ ከሲፒጄ ጋር ለመወያየት የሞከራችሁበት አጋጣሚ አለ? ሲፒጄ የወሮበሎች ቡድን ነው፤ የተወሰኑ ወሮበሎች ተሰብስበው ያቋቋሙት ነው፤ ጋዜጠኞችን እንወክላለን ብለው ገንዘብ ለመሰብሰብ የተቀመጡ ናቸው፡፡ ውብሸትን ለማስፈታት እንኳን እንቅፋት ሆነውብናል፡፡ ውብሸትን ለማስፈታት ሞክራችሁ ነበር ? አዎ! ይቅርታ ጠይቅ ብለነው ጠይቋል፤ በሱ ስም ግን ሲፔጂ መግለጫ እያወጣ ስራችንን አስተጓጉሎብናል፡፡ ሲፒጄ መግለጫ የሚያወጣው ለኢትዮጵያ ጋዜጠኞች አስቦ አይደለም፤ ኢትዮጵያን ለማጥቃት ነው፡፡

ብዙ በደል የሚደርስባቸውን የሌላ አገር ጋዜጠኞች ትቶ፣ ስለማያገባው ያወራል እንጂ እኛ በመወያየት ስራችንን እየሰራን ነው፡፡ የጋዜጠኞች መታሰርን አስቁመናል፤ ይህ የሆነው በኛ ጥረት ነው፡፡ “መንግስት ጋዜጠኞችን እንደሚያስር እስር ቤት ሄዶ ማየት ይቻላል” (ዶ/ር መረራ ጉዲና፤ የመድረክ አመራር አባል) ለመሆኑ እዚህ አገር የጋዜጠኞች ማህበር አለ እንዴ? መንግስት ጋዜጠኞችን እንደሚያስርና እንደሚያንገላታ ለማወቅ እስር ቤት ሄዶ ማየት ይቻላል፡፡ ጋዜጠኞቹ ራሣቸው ታስረው ፍርድ ቤት ሲቀርቡ ስለነበር፣ አይኔን የበሬ ግንባር ያድርገው ካልተባለ በስተቀር ነገሩ አከራካሪ አይደለም። መንግስት እንደተለመደው የታሠረ ፖለቲከኛም ጋዜጠኛም የለም የሚለው ቀልድ ካልሆነ በቀር እነ እስክንድር፣ ውብሸትና ርዕዮትን የመሣሠሉት ታስረው እኮ ነው ያሉት፡፡ እነዚህ ሠዎች እኮ ሽጉጥ ሲሠርቁ አልታሠሩም፡፡ መንግስት፤ ጋዜጠኞቹ የታሠሩት በፃፉት አይደለም በማለት የሚናገረው ነገር መራር ቀልድ ነው፤ ዝም ብሎ “የሌባ አይነ ደረቅ መልሶ ልብ ያደርቅ” አይነት ነገር ነው እንጂ ሠዎቹ ጋዜጠኞች መሆናቸውና የነፃ ጋዜጣ ባለቤትና አዘጋጅም እንደነበሩ በሚገባ ይታወቃል፡፡ ከ97 ዓ.ም በኋላ እኮ መንግስት በግልፅ ጋዜጠኞች ላይ ጫና እያሣረፈባቸው ነው፡፡ ነፃ ጋዜጦች የሚኖሩት የፖለቲካ ምህዳሩ ሲሠፋ ነው፤ የፖለቲካ ምህዳሩ ደግሞ ሙሉ ለሙሉ በሚባል ደረጃ የተዳፈነ ነው፡፡

“ሲፒጄ ሪፖርቱን ሲያወጣ የራሱ የሆነ ተልዕኮ አለው” (የኢነጋማ ሊቀመንበር፤ አቶ ወንደወሰን መኮንን) ባለፈው ሳምንት ሲፒጄ ባወጣው ሪፖርት፤ ኢትዮጵያ ጋዜጠኞችን በማሰር ከአስር ሃገራት መካከል ሁለተኛ እንደሆነች ገልጿል፡፡ የጋዜጠኞችን እስር በተመለከተ የማህበራችሁ አቋም ምንድነው? ጋዜጠኞች ይታሰሩ የሚል አቋም መቼም ቢሆን ሊኖረን አይችልም፡፡ የታሰሩ ጋዜጠኞች ካሉ ጉዳያቸው ታይቶ መንግስት መፍታት አለበት የሚል አቋም ነው ያለን፡፡ ሲፒጄ ግን ይሄንን ሪፖርት ሲያወጣ የራሱ የሆነ ተልዕኮ አለው፡፡ ኢትዮጵያ ጋዜጠኞችን በማሰር ሁለተኛ ናት ብሏል፡፡ ይሄ ከዚህ በፊትም ሆኖ የማያውቅ ግነት ነው፡፡ የታሰረ የለም። ለአፍሪካ ሚዲያ ፎረም ጉባኤ ወደ አዲስ አበባ በመጡ ጊዜ እንደ አዲስ ነው ዘመቻ የተከፈተው፡፡ በአጭሩ ግን የኢትዮጵያ መንግስት ለጉዳዩ ትኩረት ሰጥቶት … ሁኔታውን አጢኖ የታሰሩ ጋዜጠኞችን ቢፈታ በጣም ደስተኞች ነን፡፡ ማህበርዎ ኢነጋማ ስንት አባላት አሉት? ለጋዜጠኞች መብት መከበር ያደረጋችሁት እንቅስቃሴስ ምን ይመስላል ? እኛ ከዚህ በፊትም ትግል ስናደርግ ነው የኖርነው፣ አሁንም እያደረግን ነው ያለነው፡፡ አባላት አሁን አሉ ከሚባሉትም በላይ በዚህ ሂደት ውስጥ የሚታወቅና የተለየ ስፍራ አለን ብለን ነው የምናምነው፡፡ እንደ በፊቱ የመንግስትና የግል ጋዜጠኛ የሚባል ነገር የለም፤ ያንን አንኮታኩተን ጥለነዋል፡፡ ሙያው አንድ ነው፤ ይሄንን ልዩነት የፈጠሩት እርስ በርስ ሲያባሉ የነበሩና የተለየ የፖለቲካ ተልኮ ያላቸው ሃይሎች ናቸው፡፡ እነሱ ደግሞ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ከጨዋታ ውጪ ሆነዋል፡፡ ከጀርባቸው የተለየ ተልዕኮ ያላቸው ናቸው፡፡ ጋዜጠኛውን እርስ በርስ ሲያባሉ ቆይተዋል፤ አሁንም እያባሉት ይገኛሉ። ይሄንን እኔ አልቀበለውም፤ ጋዜጠኞች ሙያውን ከፖለቲካ ነፃ ሆነው መስራት አለባቸው፡፡ ጋዜጠኛው ተቀራርቦ በራሱ ጉዳይ መምከር አለበት፡፡ ጋዜጠኞች በነፃነት መስራት፣ ሃሳባቸውን መግለፅ፣ በተጨባጭ ማስረጃዎች ላይ ተመርኩዘው መተቸት አለባቸው። የሕዝብ ጥያቄ በሚመልሱበት ሰዓት በአግባቡ የመከላከል፣ የመከራከር፣ ድምፃቸውን የማሰማት መብት አላቸው፡፡

በእኛ በኩል በመንግስት፣ በግልና በኮሙዩኒኬሽን ቦታ ላይ ያሉ የሚዲያ አባላቶችን ይዘን፤ ከተወሰኑ ወራት በኋላ ጠቅላላ ጉባዔ እናደርጋለን፤ ለውጦችም ይኖራሉ፡፡ እኛ የፖለቲካ መጠቀሚያ አይደለንም፣ የትኛውንም የፖለቲካ አቋም አናስተጋባም፤ የመንግስትንም ሆነ የተቃዋሚውን። በነፃነት ሃሳባችንን በመግለፃችን ነው ውርጅብኝ ሲወርድብን የኖረው፡፡ ይሄንን ደግሞ እናውቀዋለን፡፡ ማህበራችሁ ከተቋቋመ ጊዜ አንስቶ ለመብቱ የተከራከራችሁለት ጋዜጠኛ አለ? ከተቋቋመ ጊዜ ጀምሮ ላልሽው ---- እንናገረው ብንል መፅሃፍ ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ ተሰሚነት የነበረው በአገር ውስጥም ሆነ በአለማቀፍ ደረጃ ኢነጋማ ነው፤ እሱ አከራካሪ አይደለም፡፡ ነገር ግን የቀድሞው አመራሮች በሚዲያው ውስጥ በነበረው የእርስ በርስ ትግል አዳክመው፣ ገለውት ነው የሄዱት። ዛሬም በአሜሪካና በአውሮፓ ሆነው “ኢነጋማ አለ” እያሉ መግለጫ እያወጡ ነው። ኢትዮጵያ ውስጥ ከሙያው ጋር በተያያዘ የታሰረ ጋዜጠኛ የለም። የታሰሩት በሌላ ጉዳይ ነው፤ ቢሆንም መፈታት አለባቸው ብለን እናምናለን፤ ነገር ግን መግለጫ አናወጣም፡፡ መግለጫ መስጠትም አይቻልም። ጋዜጠኛው ከሌላ አካል ከመጠበቅ ይልቅ በአንድ ላይ ሆኖ ለመብቱ መቆም አለበት፡፡ ለዚህ ደግሞ የሚያስፈልገው ተቀራርቦ በመነጋገር ችግሮችን መፍታት ብቻ ነው፡፡ በተለያየ ጎራ ሆኖ መተቻቸቱ ፋይዳ የለውም፡፡ በአሁኑ ጊዜ ሶስት “ነፃና ገለልተኛ ነን” የሚሉ የጋዜጠኞች ማህበራት አሉ፡፡ በቅርቡ ደግሞ አዲስ የጋዜጠኛ ማህበር ለማቋቋም እንቅስቃሴ የጀመሩ ወገኖች አሉ፡፡ አዲሱን ማህበር በተመለከተ የእርስዎ አስተያየት ምንድነው? ሊቋቋሙ ይችላሉ መብታቸው ነው፡፡ ነገር ግን እነማ ናቸው የሚያቋቁሙት፣ እንዴት ነው የሚቋቋሙት፣ ከጀርባ እነማን አሉ ---- ይሄን ጠንቅቀን እናውቀዋለን፡፡ ትልቅ ጉዳይ አይደለም፤ ኖረንበታል፡፡ ለእኛ አዲስ ነገር አይደለም፡፡

ከአዲሱ ጠ/ሚኒስትር አዲስ ራዕይ እንፈልጋለን

“የራበው ሥራ ፈልጐ ማግኘት የማይችልና ልጆቹን ለማስተማር አቅም ያጣ ሰው ከባርነት ነፃ ነው ማለት አይቻልም፡፡” የሚለው የአሜሪካዊው ፕሬዚዳንት ሊንደን ቢ. ጆንሰን ንግግር እውነትነት አሁን አሁን በጆሮዬ መደወሉ ራሴን እያስገረመኝ መጥቷል፡፡ የዛሬ አምስትና ስድስት ዓመት ገደማ ደራሲና ጋዜጠኛ አለማየሁ ገላጋይ፤ ስለኑሮ ውድነት ሲጽፍ ብዙዎቻችን እያነበብን ፈገግ ከማለት በቀር ብዙ ልባችን አልተነካም ነበር፡፡ ምናልባትም በጣም አልፎ አልፎ ከምናነባቸው መጣጥፎች ይልቅ መንግስት ስለ ልማት የሚነፋው ጥሩንባ አደናቁሮን ይሆናል፡፡ አሁን አሁን የመንግሥት መዝገበ ቃላት “ልማት” የሚለው ትርጓሜ ግራ እያጋባን መጥቶ ጭራሽ ወደ ብስጭት የተመነዘረብን ብዙ ነን ብዬ አስባለሁ፡፡ መንግስት ልማት የሚለው ከእኛ አፍ “ቫት” እያለ የሚነጥቃትን ገንዘብ ሰብስቦ ለሌቦች ካጠገበ በኋላ፣ በፍርፋሪዋ የሚሠራትን መንገድና ጤና ጣቢያ ወይም ትምህርት ቤት ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ “ኮንደሚኒየም”እየተባሉ የተሠሩት ቤቶች አካባቢ ያለውን ግድየለሽነት ተመልከቱ፡፡ የውሃ መፍሰሻ ቦዮቹ ገና ተሠርተው ሳያልቁ ይፈርሣሉ። ሕንፃው ውስጥ ያሉትን የግብር ይውጣ ሥራዎች ተውአቸው፡፡ ለመሆኑ ልማትና ዕድገት ምንድነው? ወረቀት ላይ የሃሰት ሪፖርቶችን ከምሮ መቀለድ ነው። ቀልድና ውሸትስ እስከ የት ያዘልቀናል? ከወር ወደ ወር ሰዎች በልተው የማደር አቅማቸውን እያጡ፣ ልጆቻቸውን ማስተማር ተራራ መቧጠጥ እየሆነባቸው ሲመጣ --- እንዴት ስለ ዕድገት ይወራል? ጋዜጠኛ መሳይ ካድሬዎች ስለልማትና እድገት ብዙ ቢለፈልፉም ከሕዝቡ የበለጠ ጓዳውን የሚያውቅ ማንም ሊኖር አይችልም፡፡ አለ ቢባልም ከተራ ቀልድነት አያልፍም፡፡ እርግጥ ነው፤ ባለፉት ሃያ ዓመታት ጥቂት ሰዎች በኑሯቸው አድገው ይሆናል፤ ለስላሳ መጠጣት የማይችሉ ዛሬ ቤታቸው ውስኪ ደርድረው የሚመርጡበት ዕድል ደርሷቸው ይሆናል፡፡ያ ግን ዕድገት አይደለም፡፡ የማሕበረሰብ ሳይንስ ምሁራን የዕድገትና ልማትን ዓላማዎች እንዲህ ያስቀምጡታል - የሕዝቡን የገቢ መጠን በፍጥነት ማሳደግ ለዜጐች የሥራ ዕድልን መፍጠር መሠረታዊ የሆኑ የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ፍላጐቶችን ማርካት፤ ማህበራዊ ፍትህን ማስፈን ሥራንና የቁጠባ ባህልን በሕብረተሰቡ ማስረጽ መልካም አስተዳደርና አሣታፊ የሆነ የፖለቲካ
ምህዳር መፍጠር ከላይ የተጠቀሱትና ሌሎችም ተጨማሪ ነጥቦች የአንዲት ሀገርንና ሕዝብን ዕድገት መንገድ የሚያሳዩ ናቸው፡፡ ይሁን እንጂ በሀገራችን ያለው ተጨባጭ ሁኔታ ከዚህ በተቃራኒ የቆመ ይመስላል፡፡ ምናልባት የማይካድ ለውጥ አምጥቷል ብለን የምንወስደው ሕብረተሰቡ በሥራ ላይ ያለውን አመለካከት በመጠኑ መቀየር መቻሉ ነው፡፡ ቁጠባውንም በውድም ሆነ በግድ በየሰበቡ ለማስለመድ የሚደረገው ጥረት የሚናቅ አይደለም፡፡ የፖለቲካው አሣታፊነት ጉዳይ የሕፃን ልጅ ዕቃ ዕቃን የመሰለ ቀልድ ስለሆነ ጉዳዩ ለሰለቸው አንባቢ ይህን አንስቶ እንዲህና እንዲያ ማለት እንደ ደንቆሮ መቁጠር ሊመስልብኝ ይችላል፡፡ ጠቃሚ ባህሎችን ማሳደግ በሚለውም መሥመር እያንዳንዱ ብሔር ብሔረሰብና ሕዝብ (በመንግስት መሠረት) ሥነ ጽሑፉንና ባህሉን ማሳደጉን እኔ በግሌ እደግፈዋለሁ፡፡ ልክ ነው ብዬም አምናለሁ፡፡ አንዱ በባህሉ እየኮራ፣ ሌላው እያፈረ የሚደበቅባት ሀገር አሁንም እኩልነት የጐደላት ስለሆነች ያንን ሕልም ማለም ጠባብነት ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ የሚያሣዝነው ግን በዚህ በጐሣ በተከፋፈለ ከለላና አስተዳደር ምክንያት የተፈጠሩት
ጥላቻዎች ማርከሻ መድሃኒት ማጣታቸው ነው፡፡ መሪዎቻችን በወጣትነት መንፈስ በስሜታዊነት ያደረጉትን ነገር ምራቅ ሲውጡ እንኳን ለማስተካከል ያለመቅናታቸው የሚገርም ነው፡፡ ለዚህ ሃሳብ ዋቢ የሚሆነኝን አንድ ሃሳብ ወደኋላ መለስ ብዬ ሕዳር 18 ቀን፣ አንድ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ተማሪ በዶክተር እሸቱ ጮሌ አዳራሽ፣ ለዶ/ር ፋሲል ናሆም (ለጠቅላይ ሚኒስትሩ አማካሪ) ያቀረበውን ጥያቄ ልጥቀስ፡፡ተማሪው የተወለደበትን ክልል ጠቅሶ፣ በክልሉ ዋና ከተማ የሚኖሩ የሌላ ብሔር ተወላጆች ሀገራቸው እስከማይመስላቸው ድረስ በደል እየተፈፀመባቸው እንደሆነ ገልፆ፣ መንግስት ለ “minority” ምን መፍትሔ አለው ሲል ጠይቆ ነበር፡፡ በሌላ አንፃር ደግሞ ያ ተማሪ እኖርበታለሁ ወይም ተወልጄበት ግን የዜግነት መብት አላገኘሁም የሚልበት ክልል ተወላጅ የሆነ ሌላ ተማሪ ተነስቶ፣ ችግሩ የሚታየው የቀደመው ተማሪ በጠየቀበት ክልል ብቻ ሣይሆን በሁሉም የሀገሪቱ ክልሎች መሆኑን ጠቅሶ፣ ሥራ ለመቀጠርም ሆነ ለሌላ ጉዳይ ዘር መቁጠር ግድ ስለሆነ፣ ችግሩን መፍታት ያለብን ሁላችንም ነን ብሎ ደመደመ፡፡ እኔ ግን በሁለተኛው ተማሪ ሃሳብ አልስማማም፤ ችግሩን ለመፍታት እኛ ድርሻ ቢኖረንም የአንበሳው ድርሻ ግን የመንግስት ነው፡፡ ስለዚህ መንግስት ለዚህ ነቀርሣ መፍትሔ መፈለግ አለበት፤ ሰው በገዛ ሀገሩ ባዕድ እየሆነና እየተገፋ መኖሩ የሚያመጣው ልማት ፈፅሞ ግልጽ አይደለም፡፡ ለመሆኑ መንግስት ማለትስ የሰዎች ስብስብ አይደለም እንዴ? እንዴት ይህንን ነገር ማሰብ ያቅተዋል? ባለሥልጣን ሲኮን ተከትሎ የሚመጣው አጃቢ ወታደር፣ ያበጠ ወንበር--- የነገን ጉዳይ ያዘናጋልና መሪዎቻችንም ሊያስቡበት የሚገባ ይመስለኛል። አብዛኛው ሕዝባችን ከእጅ ወደ አፍ እንኳን ኑሮ እያቃተው ከመጣ፤ የመኖር ዕድሉ እየጠበበ ከሄደ ሊፈጠር የሚችለው ነገር ምንድነው ብሎም ማሰብ ደግ ይመስለኛል፡፡ የኢሕአዴግ አማካሪዎች ምናልባት እውነት የማይናገሩ አሸርጋጆች እንዳይሆኑ እሠጋለሁ። ሕዝቡ እየተራበ

“ጠግቧል”፣ እየተማረረ “ደስተኛ ነው” እያሉ ከሆነ ፍፃሜው አያምርም። በርግጥ እኛ ሥልጣን የሌለን አስበን ምንም አናመጣም፣ ሥልጣን ያላቸው ናቸው ለችግሩ መቋጫ መፍትሄ ሊያበጁለት የሚገባቸው፡፡አዲሱም ጠቅላይ ሚኒስትር ቢሆኑ ሁልጊዜ የታላቁ መሪያችንን መዝሙር ከመዘመር ይልቅ አዲስ መዝሙርና ራዕይ ለመፍጠር መሞከር ይጠበቅባቸዋል፡፡ ቶማስ ጀፈርሰን፤ ሁሉም ሰው የየራሱ ዘመን አለው፣ በሕይወት የሌለ ሰው በሕያው ሰው ዘመን ሊወስን አይችልም እንደሚል፣ አሁን ያለውን ኑሮና ሕይወት የማያዩት የቀድሞው መሪያችን ራዕይ ሊያዘልቀን ይችላል ብሎ ማመን ያስቸግራል፡፡ ርግጥ ነው ያስጀመሩትን ግድብ ማጠናቀቅ፣ የባቡሩን ሥራ መፈፀም፣ ወዘተ ጥሩ ነው። ግን በጤፍ ዋጋ፣ በስኳርና በትራንስፖርት ጉዳይ ያለውን ጣጣ ዛሬ ቢያዩ፣ እሳቸውም ደንግጠው ጭንቅላታቸውን ይይዙ ነበር፡፡ በዓመት ውስጥ ለአንድ የሆቴል ተመጋቢ ቢያንስ ሦስቴና አራቴ ዋጋ ይጨምርበታል፡፡ ታዲያ ሆዱ ባልጠገበ ሲቪል ሠራተኛ ተሠርቶ፣ ሀገርን ማሳደግ ይቻላል እንዴ? ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትሩ አዲስ ሕልም ያልሙ እንጂ --- አዲስ ራዕይ ያምጡ! የስነ አመራር ምሁሩ

ጆን ሲ ማክስዌል እንደፃፉት፤ በየዓመቱ ዶሮዎቹን የክረምት ጐርፍ የሚወስድበት ዶሮ አርቢ፣ ሁልጊዜ በዶሮ ላይ የሙጢኝ ማለት የለበትም፤ ይልቅስ ጐርፉ ላይ ዋኝቶ አልፎ ሀብት የሚሆን ዳክዬ የማርባት ጥበብና ዘዴ ሊኖረው ይገባል። መቼም መንግስታችን ሁልጊዜ በሕይወት በሌሉት የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር ላይ መንጠልጠል ያለበት አይመስለኝም፤ እሳቸው በጊዜያቸው የሚሰሩትን ሰርተው አልፈዋል፡፡ አሁን ተራው የሥልጣን ወንበሩ የተሰየሙት ሰውዬ ነው፡፡ ፕሬዚዳንት ሊንደን ቢ. ጆንሰን እንዳሉት፤ ድሀና ሀብታም በጠብደል ግድግዳ ሲለይ ጥሩ አይደለም። ይልቅስ ግድግዳው የመስተዋት ነውና በኋላ የሚያመጣው መዘዝ መጥፎ ነው፡፡ ከፊሉ በሌብነት እየበለፀገ፣ ሌላው በጨዋነት እየተራበ - ለዘላለም - አይኖርምና መጠንቀቅ ያስፈልጋል፡፡ ዶክተር መረራ ጉዲና እንደሚሉት፤ የራበው ሕዝብ - መሪውን ለመብላት እንዳይነሣ - ካሁኑ ማሰብ የግድ ይላል፡፡ ጆንሰን - “There are two courses open to us. We can master the problem, or we can leave it to master us” ብለዋል - የኛም ምርጫ ይኸው ነው። አዲዮስ!