Administrator

Administrator

  • የፕሬዚዳንቱ ስልጣን፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩን፣ ፓርላማውን፣ እንዲሁም የፌደሬሽን ምክርቤትን ሁሉ ይነካል።
  • ፕሬዚዳንቱ ሳይፈቅድ፣ ጠ/ሚሩ ከፍተኛ ወታደራዊ ማዕረጎችን መስጠትና አምባሳደሮችን መሾም አይችልም።
  • ብዙዎች ቢያናንቁትም የፕሬዚዳንቱ ስልጣን ቀላል አይደለም። “ስልጣኑ ተሠርቶበታል ወይ?” ነው ጥያቄው።

ኢህአዴግ በተለመደው የምስጢራዊነት ባሕርይው፣ ለፕሬዚዳንትነት ማንን በእጩነት እንደሚያቀርብ ሳይነግረን ይሄውና የምርጫው ቀን ደረሰ። ባዕድ መሰልነው እንዴ የሚደብቀን? ዜችን ከመናቅ ይሁን ከመፍራት፣ ሕግን ባለማክበር ይሁን በቸልተኝነት… ምንም ሆነ ምን፣ ዜጎች በሰኞው የፕሬዚዳንት ምርጫና በእጩዎች ላይ ሃሳባቸውን እንዳያቀርቡና እንዳይወያዩ እድል ተነፍጓቸዋል - በኢህአዴግና በፓርላማው። ታዲያ የዜጎች ድርሻ ምንድነው? … ያው እንደተለመደው፣ “ተመልካች” መሆን ብቻ! በቃ፤ ሰኞ እለት ቴሌቪዥን ከፍተው፣ አንድ ሰው ፕሬዚዳንት ሆኖ ሲሾም መመልከት ብቻ! ለነገሩ፣ የአገራችን ችግር የገዢው ፓርቲ ብቻ አይደለም። ብዙዎቹ ተቃዋሚ ፓርቲዎችም ያው ናቸው። አንዳንዶቹም የባሱ! “ለፕሬዚዳንትነት በእጩነት የሚቀርበው ሰው ማን እንደሆነ ለዜጎች ተገልጾ ውይይት መካሄድ አለበት” ብሎ የኢህአዴግንና የፓርላማውን ድብቅነት የተቸ አንድም የተቃዋሚ ፓርቲና ፖለቲከኛ የለም። 
ኢህአዴግ ከዜጎች ጋር በአደባባይ ከመወያየት ይልቅ የጓዳ ምስጢራዊነትን፣ ፓርላማውም በግልፅነት ዜጎችን ከማገልገል ይልቅ የጓሮ ድብቅነትን መምረጣቸው ሳያንስ፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎችና ፖለቲከኞች እንዲህ መሆናቸው አይገርምም? ድብቅነትን በመተቸት ግልፅነት እንዲሰፍንና የዜጎች የሃሳብ ነፃነት እንዲሰፍን ሲጠይቁ የማናያቸው፣ ኢህአዴግን ወይም መንግስትን በመፍራት አይደለም። በፕሬዚዳንቱ ምርጫ ዙሪያብዙ ትችቶችን ለመደርደር አልሰነፉም - በተለይ ደግሞ የፕሬዚዳንቱን ስልጣን በማናናቅ።
በአላዋቂነት ይሁን በደንታቢስነት… ምክንያቱ ባይታወቅም፣ የፕሬዚዳንቱን ስልጣን ማጣጣል በኛ አገር በጣም የተለመደ ነገር ነው። ለነገሩ፣ በአገራችን ኋላ ቀር ባህል ውስጥ፣ የመንግስት ስልጣን… “ሕግ የማያግደው አድራጊ ፈጣሪና ፈላጭ ቆራጭ” ካልሆነ፤ ብዙዎቻችን ያን ያህል አናከብረውም፤ እውነተኛ ስልጣን ሆኖ አይታየንም። ለዚህ ይመስለኛል፣ የፕሬዚዳንቱን ስልጣን ማናናቅ እንደ አዋቂነት የሚቆጠረው - በሕግ የተገደበ ስልጣን ስለሆነ!

የኢህአዴግ የድብቅነት ባህል
ኢህአዴግና አጋሮቹ በ99.5% በላይ የተቆጣጠሩት ፓርላማ፣ ባለፈው ሰኔ ወር ላይ የሚኒስትሮች ሹም ሽርና ሽግሽግ እንዴት እንደተካሄደ ታስታውሱ ይሆናል። ባታስታውሱትም ችግር የለውም። እንደተለመደው ነው… አንድ የፓርላማ ስብሰባ ላይ፣ የአገሪቱ ጠቅላይ ሚኒስትር መጥተው፣ ለሹመት የታጩ ሰዎችን በስም ይዘረዝራሉ። “እገሌ፣ ይህንንና ያንን ተምሯል፤ እዚህና እዚያ ሰርቷል” የሚል፣ “የአጭር አጭር የመተዋወቂያ ገለፃ ይነበባል - ከሦስት ዓረፍተ ነገር ያልበለጠ። ከዚያ አንድ ሁለት ጥቅል አስተያየቶች በአጭሩ ይቀርቡና የፓርላማ አባላት ድምፅ ይሰጣሉ። የሚኒስትሮቹ ሹመት ይፀድቃል። እስከዚያች የስብሰባ ሰዓት ድረስ፣ ለሚኒስትርነት የታጩት ሰዎች እነማን እንደሆኑ አይታወቅም፤ በምስጢር ተደብቆ ይቆያል። የፓርላማ አባላት እንኳ፣ “ማን በእጩነት ይቀርባል?” ተብለው ቢጠየቁ፣ ከስብሰባው በፊት እንደማያውቁ ነው የሚናገሩት።
ለሚኒስትሮች ሹመት የሚሰጠው አቅምና ብቃታቸው እየታየ መሆን እንዳለበት ሕገመንግስቱ በግልፅ ይደነግጋል። የእጩ ተሿሚዎችን አቅምና ብቃት የመመዘን ስልጣንና ሃላፊነት የፓርላማው የመሆኑን ያህል፤ በእጩዎቹ አቅምና ብቃት ላይ መረጃ መስጠትና ሃሳብ መግለፅ ደግሞ የእያንዳንዱ ዜጋ ነፃነትና መብት ነው። መንግስት፣ የግልፅነት አሰራርን በመከተል እቅዶቹን በይፋ የማስታወቅ ግዴታ በህግ የተጣለበት በሌላ ምክንያት አይደለም። በእቅዶቹ ላይ ዜጎች ሃሳባቸውን የመግለፅና የመወያየት ነፃነት ስላላቸው ነው። “መንግስት እና ፓርላማው የህግ የበላይነትን በማክበር ሃላፊነታቸውን ለማሟላት፣ የዜጎችንም መብትና ነፃነት ለማክበር ፈቃደኛ ቢሆኑ”… ብለን እናስብ። ያን ያህልም ውስብስብ አይደለም።
ለሚኒስትርነት ወይም ለፕሬዚዳንትነት የሚታጩ ሰዎች እነማን እንደሆኑ፣ ከሳምንታት አስቀድሞ የፓርላማ አባላት እንዲያውቁት ይደረግና፣ ለዜጎችም በይፋ ይገለፃል። ያኔ፣ የእጩዎቹን ማንነት በማጥናትና መረጃ በመሰብሰብ፣ ብቃታቸውንና የስነምግባር ደረጃቸውን የመመዘን እድል ይፈጠራል። ዜጎችና የፓርላማ አባላት፣ ሃሳብ ለመለዋወጥና ለመወያየት ጊዜ ያገኛሉ። በእጩዎቹ ብቃትና ድክመት ወይም የስነምግባር ፅናትና ብልሹነት ላይ፣ የሚያስመሰግን ወይም የሚያስወቅስ ተጨባጭ መረጃ ያላቸው ሰዎች፣ ማስረጃቸውን ለፓርላማ አባላት በማካፈል ይተባበራሉ - ሃሳባቸውን የመግለፅ ነፃነታቸውን በመጠቀም። እንዲህ፣ በስልጣኔ ደህና የተራመዱ አገራት ውስጥ እንደሚደረገው፣ ግልፅነትና ጨዋነትን የተላበሰ፣ የህግ የበላይነትና የዜጎች ነፃነትን ያከበረ አሰራር ቢፈጠር፣ በሙስናና በብቃት ጉድለት የሚፈጠሩ ግርግሮች በቀነሱ ነበር። ይሄ ግን አልሆነም።
መንግስት በህግ የተጣለበትን የግልፅነት አሰራርን ወደ ጎን ብሎ፣ ለፕሬዚዳንትም ሆነ ለሚኒስትር ሹመት በእጩነት የሚያቀርባቸውን ሰዎች በምስጢር ደብቆ ይይዛል። የተሿሚዎችን ብቃትና ስነምግባር ፈትሸው እየመመዘን ህገመንግስታዊ ሃላፊነት የተጣለባቸው የፓርላማ አባላትም፣ ሃላፊነታቸውን መወጣት ያቅታቸዋል። በአንድ ስብሰባ ላይ የእጩ ሚኒስትሮች ወይም የእጩ ፕሬዚዳንት ስም ዝርዝር የሚቀርብላቸው የፓርላማ አባላት፤ እዚያው ስብሰባ ላይ የእጩዎችን የቀድሞ የሥራ ትጋትና ስንፍና፣ ስኬትና ውድቀት መርምረው፣ የወደፊት አላማቸውንና ሃሳባቸውን ፈትሸው፣ ብቃትና አቅማቸውንም ሁሉ በአምስት ደቂቃ ውስጥ መዝነው፣ በአምስት ደቂቃ ውስጥ የሁሉንም ሹመት ማፅደቅ የሚችሉት እንዴት ነው? አንድ ሾፌር፣ አንድ ነርስ ወይም አንድ የመዝገብ ቤት ሰራተኛ ለመቅጠር እንኳ ከዚህ የበለጠ ጊዜ ያስፈልጋል። የብቃትና የስነምግባር ጉዳዮችን ለመመርመርና ለመመዘን ይቅርና፣ የሚኒስትሮችን ስም በወጉ ለማወቅ እንኳ በቂ ጊዜ አያገኙም። በብልሹ ምግባር ከስልጣን የሚባረሩ ባለሥልጣናትን፣ በብቃት ጉድለት ሳቢያ የሚሰናበቱ ተሿሚዎችን በየጊዜው የምናየው፣ ከመነሻው ያለበቂ ፍተሻና ምዘና ሹመት ስለሚሰጥ ሊሆን ይችላል።
መንግስትስ የዜጎችን ሃሳቦች ለማሰባሰብና ለመወያየት መሞከር የለበትም? የፓርላማ ተመራጮች፣ በየቀበሌውና በየወረዳው ከመራጮች ጋር መወያየት የለባቸውም? ፓርቲዎችና ፖለቲከኞችስ?
ለዚህ የውስጥ ለውስጥ አሰራር መነሻ ሊሆኑ የሚችሉ ሦስት ምክንያቶች ይታዩኛል። አንደኛው ምክንያት፣ ሕጉ ምንም ይበል ምን፣ እስከ ዛሬ በተለመደው አሰራር በደመነፍስ የመጓዝ ልማድ ነው። ለመንግስት መሪዎችና ለፓርላማ አባላት፣ ለፓርቲዎችና ለፖለቲከኞች፣ ለምሁራንና ለዜጎች ሁሉ… ያን ያህልም ስህተት ሆኖ አይሰማቸውም። ድብቅነት፣ በአገራችን ፖለቲካ ውስጥ ለዘመናት የቆየ ባህልና የተለመደ አሰራር ነዋ። የጎጂ ልማድና የመጥፎ አመል ጉዳይ ነው።
ሁለተኛ፤ መንግስትን እንደ ቁጡ አባት፣ ዜጎችን እንደ ደካማ ሕፃን አድርገን የምናስብ መሆናችን ነው። እንዲህ መንግስትን እንደ ቁጡ አባት ወይም እንደ ጣኦት የማምለክ ኋላቀር ባህልና አስተሳሰብ ስለተጠናወተን፣ መንግስት ምንም ነገር ቢያደርግ፣ የዜጎችን ነፃነት ቢያፍን እንኳ፣ “መልካም ነገር አስቦ ይሆናል” እንላለን። ቁጡ አባት ምንም ቢያደርግ፣ “ለልጆቹ መልካም ነገር አስቦ ይሆናል” እንደምንለው አይነት ነው። ቁጡ አባት ምንም ነገር ሲያቅድ፣ ወደ ውሳኔ ከመሄዱ በፊት እቅዶቹን ለልጆቹ ማማከርና ሃሳባቸውን እንዲገልፁ የማድረግ ግዴታ አለበት? እሺ፣ ቢያማክራቸውና ሃሳባቸውን እንዲገልፁ ቢፈቅድላቸው ጥሩ ነው እንበል። ግን፣ ይህንን ባያደርግ እንደ ወንጀል ወይም እንደ ክፋት አንቆጥርበትም። “ዞሮ ዞሮ ለልጆቹ መልካም ነገር ማሰቡ አይቀርም። ለልጆቹ ምን እንደሚበጃቸው እሱ ያውቃል” እንላለን። እንደ ቁጡ አባት የምንቆጥረው መንግስትም፣ እቅዱን ባያሳውቀን፣ ዜጎችም ሃሳባቸውን እንዲገልፁ ባይፈቅድ፣ ህገመንግስቱን እየጣሰ ቢሆንም እንኳ ትልቅ ጥፋትና ወንጀል ሆኖ አይታየንም። መንግስትን እንደ ቁጡ አባት የመቁጠርና፣ “የሚበጀንን እሱ ያውቅልናል” የሚል ኋላቀር አስተሳሰብ አልለቀቀንማ።
ሦስተኛ፣ የመንግስት ባለስልጣናት እቅዳቸውን በማሳወቅ ከዜጎች አስተያየት ከጠየቁ፣ አላዋቂና ደካማ የሆኑ ይመስላቸዋል። እኛም፣ አላዋቂና ደካማ እንደሆኑ በመቁጠር፣ ከፍ ዝቅ እናደርጋቸዋለን። እንፈታተናቸዋለን። እነሱ ህጋዊውን መንገድ ጥሰው ያሰኛቸውን ነገር ከመፈፀም ይልቅ ዜጎችን ለማማከር ከሞከሩ፤ በእነሱ ፋንታ አዛዥ ናዛዥ ለመሆንና ዙፋን ላይ ቂብ ለማለት ይቃጣናል። እዚያ ድረስ ባንሄድ እንኳ፣ በንቀት መረን ለቀን፣ ጨዋነትን ጥሰን መሳደብ፣ ማንጓጠጥ፣ ሥም ማጉደፍ ያምረናል። ስድቡና ዘለፋው እየተግለበለበ ወደ ውግዘትና ውንጀላ ይሸጋገርና ምስቅልቅል ይፈጠራል። የማዘዝና የመታዘዝ፣ የመርገጥና የመረገጥ ባህል እንጂ፣ ተከባብሮ የመነጋገር ባህል የለማ። እናስ፣ መንግስትና ባለስልጣት ምን ያደርጋሉ? ስልጡን ባህል ለመፍጠር ከመጣጣር ይልቅ፣ አቋራጩን መንገድ ይመርጣሉ - በምስጢር ደብቆ ማቆየትና የእጩ ፕሬዚዳንቱን ወይም የእጩ ሚኒስትሮችን ስም በመዘርዘር በአምስት ደቂቃ ውስጥ ሹመታቸው እንዲፀድቅ ማድረግ! ይሄ ስንፍና ነው። መንግስት፣ በስልጣኔ እንደተራመዱት አገራት ባይሆን እንኳ፣ የእጩ ተሿሚዎችን ስም ከሁለት ከሦስት ቀን በፊት በማሳወቅ፣ የለውጥ ጅምር ማሳየት ይችላል። ለከርሞ ደግሞ የእጩ ተሿሚዎቹን ከሳምንት በፊት በይፋ ማሳወቅ… ቀስ በቀስ ስልጡን የግልፅነት አሰራርን መጀመር ይችላል። ከመርገጥና መረገጥ አባዜ የመላቀቅ ፍላጎት ካለው ማለቴ ነው።

የተቃዋሚዎች ዝርክርክነት
ከላይ እንደገለፅኩት፣ መንግስት በድብቅነት አባዜው፣ የዜጎች ሃሳብን የመግለፅ ነፃነት መጣሱ ሳያንስ፣ ተቃዋሚ ፓርቲዎች የመንግስትን ድብቅነት በዝምታ በማለፍ የፕሬዚዳንቱን ስልጣን ለማናናቅ መረባረባቸው ያሳዝናል። ፕ/ር መስፍን ወልደማሪያም የሰጡትን አስተያየት ልጥቀስላችሁ።
“የፕሬዚዳንቱ ስራ ዝም ብሎ ቁጭ ማለት ነው፡፡ ወደ 12 ዓመት ገደማ ቁጭ ብሏል፤ ይወጣል፤ በቃ አለቀ፡፡ … ህጉ ራሱ ምንም ሀላፊነት እና ሥራ አይሰጠውም፡፡ በህጉ ላይ የተወሰኑ ነገሮች አሉ፡፡ ሰዎችን መቀበል፣ እንግዶችን ማስተናገድ፣ አምባሳደሮችን መቀበልና መሸኘት፣ ይቅርታ መስጠት… የመሳሰሉትን ያከናውናል”
የፕ/ር መስፍን አስተያየት በጣም አስገራሚ ነው። አንደኛ ነገር፣ በህገመንግስቱ ላይ የሰፈሩት የፕሬዚዳንቱ ዋና ዋና ሥራዎች፣ በፕ/ር መስፍን የተጠቀሱት ነገሮች አይደሉም። ሁለተኛ ነገር፣ የፕሬዚዳንቱ ስልጣን የውጭ አገራት አምባሳደሮችን መቀበልና መሸኘት እንዲሁም ለእስረኞች ይቅርታ መስጠት ቢሆን እንኳ፣ ትንሽ ስልጣን አይደለም። በሁለት አገራት ግንኙነት ውስጥ፣ ከውጭ የተላከ አምባሳደርን ወዲያወኑ አስተናግዶ የሹመት ደብዳቤውን በመቀበል ወዲያውኑ ሥራውን እንዲጀምር ማድረግ፣ ትልቅ የወዳጅነት ምልክት ተደርጎ ይቆጠራል። ፕሬዚዳንቱ ከአሜሪካ ወይም ከአውሮፓ የመጣውን አምባሳደር ባያስተናግዱትና ለረዥም ጊዜ የሹመት ደብዳቤውን ሳይቀበሉ ቢያጉላሉትስ? ይሄም የቅሬታና የጠላትነት ስሜት የሚገለፅበት የዲፕሎማሲ መሳሪያ እንደሆነ ይታሰባል። ፕሬዚዳንቱ ይህንን የመጠቀም ስልጣን አላቸው። የፕሬዚዳንቱ ዋና ዋና ስልጣኖች ግን፣ ከዚህም በእግጁ የገዘፉ ናቸው።
ከጠቅላይ ሚኒስትሩ ስልጣኖች መካከል ሁለቱን ልጥቀስ - የውጭ አገር ግንኙነት እና የመከላከያ ሃይል ፖሊሲዎችን መምራት! በእነዚህ ቁልፍ ስልጣኖች ውስጥ፣ ፕሬዚዳንቱም የማይናቅ ድርሻ አላቸው። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ወደ ተለያዩ አገራት አምባሳደሮችን ሳይልክ የውጭ ግንኙነቶችን መምራት አይችልም። ለከፍተኛ የጦር መኮንኖች የማዕረግ ሹመት ሳይሰጥም፣ የመከላከያ ሃይል ፖሊሲውን ተግባራዊ ማድረግ አይችልም። ነገር ግን፣ ያለ ፕሬዚዳንቱ ይሁንታ፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ አምባሳደሮችን መሾም ወይም ለጦር መኮንኖች ከፍተኛ ማዕረግ መስጠት አይችልም። ፕሬዚዳንቱ የእጩ አምባሳደሮችን ሹመት ወይም የጦር መኮንኖቹን የማዕረግ እድገት፣ የማፅደቅ ወይም ውድቅ የማድረግ ስልጣን አላቸው። ይሄ ቀላል ስልጣን ነው? በውጭ ጉዳይ እና በመከላከያ ሃይል ፖሊሲዎች ላይ ተሰሚነትና ተፅእኖ እንዲኖረው የሚያደርግ ከፍተኛ ስልጣን ነው።
በእርግጥ፣ የእስካሁኖቹ ፕሬዚዳንቶች፣ ይህንን ከፍተኛ ስልጣን በአግባቡ አልሰሩበትም ይባል ይሆናል። ይሄ ግን ሌላ ጥያቄ ነው። በጣም ሰፊ ስልጣን በህገመንግስት የተሰጠው ፓርላማስ፣ ስልጣኑን በአግባቡ ሰርቶበታል እንዴ? ግን ስልጣኑ አለው፤ ሊሰራበትም ይችላል። ፓርላማው ካለፈው አመት ወዲህ፣ ሚኒስትሮችን የመቆጣጠር ስልጣኑን በመጠቀም ደህና እንቅስቃሴ ሲያደርግ አይተን የለ? ልክ እንደዚያው፣ ፕሬዚዳንቱም፣ እስካሁን በጉልህ ተግባራዊ ሲደረጉ ያልታዩትን ስልጣኖች ስራ ላይ ማዋል ይችላል። የሆነ ሆኖ፣ የፕሬዚዳንቱ ስልጣን፣ ፕ/ር መስፍን እንዳሉት እንግዶችን መቀበልና በመሳሰሉ መለስተኛ ሃላፊነቶች የታጠረ አይደለም።
ዶ/ር ያዕቆብ ኃይለማርያም፣ ስለ ፕሬዚዳንቱ የስልጣን ቦታና ስለ ሥራ ሃላፊነቱ ወደሰጡት አስተያየት ልሻገር። “ቦታው ለምልክትነት ካልሆነ ብዙ የሚሰራበት አይደለም በሚለውም አልስማማም” የሚሉት ዶ/ር ያዕቆብ፤ “ፕሬዚዳንቱ ሊያከናውኗቸው የሚችሏቸው የተለያዩ ተግባራት አሉ” በማለት የሰጡት አስተያየት ከፕ/ር መስፍን አስተያየት የተለየ ይመስላል። ግን አይደለም። ዶ/ር ያዕቆብም ቢሆኑ፣ በሕግ የተቀመጠው የፕሬዚዳንቱ ስልጣን፣ እንግዳ ከመቀበልና በአመት አንዴ በፓርላማ ስብሰባ የመክፈቻ ንግግር ከማድረግ የዘለለ እንዳልሆነ ያምናሉ። “በግልፅ የተቀመጡትን እንግዳ መቀበል፣ ፓርላማ መክፈት እና የመሳሰሉትን ትተን፣ በርካታ ስራዎችን መከወን ይችሉ ነበር” ያሉት ዶ/ር ያዕቆብ፣ ፕሬዚዳንቱ የበጐ አድራጐት ስራዎችን መምራት፣ ማህበራትን ማጠናከር፣ ህዝቡን ለስራ ማደፋፈር፣ እስረኞችንና ህሙማንንን እየጎበኙ መከታተልና የመሳሰሉትን ሊሰሩ ይችሉ ነበር ብለዋል።
የኢዴፓ ፕሬዚዳንት ሙሼ ሰሙ የሰጡት አስተያየትም ተመሳሳይ ነው። “ፕሬዚዳንት ግርማን የማውቃቸው በአገር ምልክትነታቸውና መገለጫነታቸው ብቻ ነው” ያሉት አቶሙሼ ሰሙ፣ “ፕሬዚዳንቱ ህገመንግስቱ ሰፍሮ ከሰጣቸው ስልጣን ባለፈ ሊሰሯቸው የሚችሏቸው ሥራዎች ሞልተዋል፡፡ ለምሳሌ የፕሬዚዳንቱ ቦታ የዲፕሎማቲክ ስራዎችን እንዲሰሩ ያደርጋቸዋል፡፡ ብዙ ማህበራዊ እንቅስቃሴዎችም አሉ” ብለዋል። የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ዘለቀ፣ የፕሬዚዳንቱ ቦታ እዚህ ግባ የሚባል ስልጣን በህገመንግስቱ እንዳልተሰጠውና የፖለቲካ ቁምነገር የሌለው ቦታ እንደሆነ ጠቅሰው፣ ህገመንግስቱ ላይ ባይቀመጥም ፕሬዚዳንቱ ብዙ ሊሰሯቸው የሚገቡ በጎና ማህበራዊ ነገሮች መኖራቸውን ገልፀዋል።
የአገላለፅ ልዩነት ቢኖራቸውም፣ ዶ/ር መስፍን፣ ዶ/ር ያዕቆብ፣ ኦቶ ሙሼ እና አቶ ዘለቀ የሰነዘሯቸው አስተያየቶች፣ ፕሬዚዳንቱ እንግዳ ከመቀበልና ከመሸኘት ያለፈ ስልጣን በህገመንግስት አልተሰጣቸውም፤ ነገር ግን ፖለቲካዊ ያልሆኑ ስራዎችን ማከናወን ይችላሉ የሚል ሃሳብ ያዘሉ ናቸው።
በእርግጥም፣ ፕሬዚዳንቱ በአገሪቱ ውስጥ ያላቸውን ተሰሚነት በመጠቀም በርካታ በጎ ነገሮችን ማበረታታት ይችላሉ። ነገር ግን፣ በህገመንግስት የተዘረዘረው የፕሬዚዳንቱ ስልጣን፣ እንግዳ መቀበል፣ አመታዊ የፓርላማ ስብሰባ መክፈትና የመሳሰሉት ብቻ አይደለም። በተለይ ዶ/ር ያዕቆብ፣ የሕግ ባለሙያ እንደመሆናቸው፣ እንዲህ አይነቱን ስህተት መስራታቸው ያስገርማል። ለነገሩ፣ ፕሬዚዳንቱን በማሞገስ አስተያየት የሰጡት የፓርላማ አባል ዶ/ር አሸብር ወልደ ጊዮርጊስ እና የፕሬዚዳንቱ ረዳትና የሕግ ባለሙያው አቶ አሰፋ ከሲቶም፣ ተመሳሳይ የተሳሳተ አስተሳሰብ አስተጋብተዋል።
የፕሬዚዳንቱን ስልጣን ለማናናቅ በተደጋጋሚ የሚጠቀስ አንድ አንቀፅ አለ። በፓርላማ የፀደቀ አዋጅ፣ ስራ ላይ የሚውለው ፕሬዚዳንቱ በፊርማ ሲያሳልፉት እንደሆነ የሚገልፀው የአገሪቱ ሕገመንግስት፣ ፕሬዚዳንቱ ፈቃደኛ ባይሆኑ እንኳ ህጉ ስራ ላይ እንዳይወል ማድረግ የሚችሉት ለ15 ቀን ያህል ብቻ ነው። በእርግጥ፣ አንድን ህግ ወዲያውኑ ስራ ላይ እንዲውል ማድረግ ወይም ለ15 ቀን ማዘግየት፣ ሰፊ ስልጣን አይደለም። እንዲያም ሆኖ፣ በተለይ አጣዳፊና አወዛጋቢ በሆኑ ህጎች ላይ፣ ለምሳሌ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ እና የጦርነት አዋጅ በመሳሰሉ ውሳኔዎች ላይ፣ ለ15 ቀናት አዋጁ ታግዶ እንዲቆይ የማድረግ ስልጣን ቀላል ስልጣን አይደለም።
ፕሬዚዳንቱ፣ በፓርላማ የሚወጡ ህጎችም ሆኑ በሚኒስትሮች ምክር ቤት የሚወጡ ደንቦች ላይ ተጨማሪ ተፅእኖ የማሳረፍ እድል አላቸው። ህጎችና ደንቦች፣ ከህገመንግስት ጋር የሚጋጩ መሆን አለመሆናቸውን በመመርመር የውሳኔ ሃሳብ የማቅረብ ስልጣን በተሰጠው ለህገመንግስት ጉዳዮች አጣሪ ጉባኤ እንደሆነ ይታወቃል። 11 አባላትን ባካተተው አጣሪ ጉባኤ ውስጥ፣ የስድስቱ አባላት ሹመት የሚፀድቀው በፕሬዚዳንቱ ይሁንታ ነው። በቀነ ገደብ የታጠረ ስልጣንም አይደለም። በቃ! ፕሬዚዳንቱ ካልተስማሙበት ሹመቱ አይፀድቅም። የአምባሳደሮች ሹመትና የጦር መኮንኖች ማዕረግም፣ ያለ ፕሬዚዳንቱ ይሁንታ ተግባራዊ ሊሆን አይችልም።
ይሄ፣ ቀላል ስልጣን ነው? በጭራሽ አይደለም። ይልቅስ፣ ይሄ የፕሬዚዳንቱ ከፍተኛ ስልጣን በአግባቡ ተግባራዊ ሳይደረግ ቆይቷል ከተባለ፣ አዎ አልተደረገም። ለምሳሌ፣ ፕሬዚዳንቱ የተሿሚ አምባሳደሮችንና ከፍተኛ ማዕረግ የሚሰጣቸው የጦር መኮንኖችን ጉዳይ የሚመረምር፣ መረጃ የሚያሰባስብ የባለሙያዎች ቡድን የላቸው።

“የአሜሪካ መንግስት ተዘጋ፤ የመንግስት መሥሪያ ቤቶች በር ተከረቸመ” የሚለው ሰሞነኛ የውዝግብ ዜና፣ እውነት ቢሆንም የተጋነነ ነገር አለው። አዎ፤ አብዛኞቹ መሥሪያ ቤቶች ተዘግተዋል። ነገር ግን ሁሉም አልተዘጉም። እንደ ኤፍቢአይ የመሳሰሉ የፍትህ አካላት፣ እንደ ሲአይኤ የመሳሰሉ የስለላ ተቋማት በከፊል እንጂ ሙሉ ለሙሉ አልተዘጉም። የመከላከያ ሃይል ተቋማትም ስራቸውን አላቋረጡም። በርካታ የሚኒስቴር መስሪያ ቤቶች ከሞላ ጎደል ተከርችመዋል። ከዚሁ ጋርም፣ 800 ሺ ገደማ የሚሆኑ የመንግስት ሰራተኞች፣ ደሞዝ የማይከፈልበት እረፍት እንዲወስዱ ተነግሯቸው ስራ ፈትተዋል፤ ወደ ስራ ተጠርተው እስኪመለሱም ድረስ የመተዳደሪያ ገቢ አይኖራቸውም። በእርግጥ “የመንግስት ሠራተኛ ድሮስ መቼ ሠርቶ ያውቃል?” ብለው በቢሮክረሲው ዝርክርክነት የሚያሾፉ ሰዎች ደግሞ፣ “ሳይሰራ ደሞዝ ይከፈለው ነበር፤ አሁን ግን ሳይሰራ ገንዘብ አለማግኘትን ደግሞ ይሞክረው!” ማለታቸው አልቀረም። በእርግጥም፤ የመሥሪያ ቤቶቹ ሰሞኑን የተዘጉበት የውዝግብ መነሻ፤ ከገንዘብ ጋር የተያያዘ ነው - ከመንግስት ወጪና ባጀት ጋር።

ዋናዎቹ አወዛጋቢ ጉዳዮች ሶስት ናቸው፣ ከአመት አመት የሚያብጠው የመንግስት በጀት፣ በጊዜ ወደ ጊዜ የሚቆለለው የመንግስት እዳ እና “ኦባማኬር” የተሰኘው አስገዳጅ የጤና ኢንሹራንስ። ተወዛጋቢዎቹስ እነማን ናቸው? በአንድ ወገን፣ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ እና መቶ መቀመጫዎች ባሉት ሰኔት ውስጥ አብላጫውን ወንበር የተቆጣጠሩ የዲሞክራቲክ ፓርቲ ተመራጮች አሉ። በሌላኛው ወገን ደግሞ፣ 435 መቀመጫዎች ባሉት ኮንግረስ ውስጥ፣ አብላጫውን ወንበር የተቆጣጠሩ የሪፐብሊካን ፓርቲ ተመራጮች አሉ። በእነዚህ ሁለት ወገኖች መካከል ላለፉት ሶስት አመታት እየተካረረ የመጣው ውዝግብ፣ ሰሞኑን መፈናፈኛ ወዳልተገኘለት አጣብቂኝ ስለተሸጋገረና በበጀት ጉዳይ ላይ ሊስማሙ ባለመቻላቸው ነው የመንግስት መስሪያ ቤቶች የተዘጉት።

ታላቋ የነፃነት አገር አሜሪካ፣ ባለፉት መቶ አመታት ነገረ ስራዋ እየተበላሸ መምጣቱን ከሚመሰክሩ ነገሮች መካከል፣ የሰሞኑ አጣብቂኝ እንደ አንድ ምልክት ሊታይ ይችላል። ውዝግብና አጣብቂኝ መፈጠሩ፣ አልያም የመንግስት መሥሪያ ቤቶች መዘጋታቸውና ሠራተኞች እረፍት እንዲወጡ መደረጋቸው አይደለም ችግሩ። እነዚህ ነገሮችማ፣ አሜሪካ ገና ከሁሉም አገራት የተሻለች የነፃነትና የሕግ አገር መሆኗን የሚጠቁሙ የጤንነት ምልክቶች ናቸው። ይልቅስ፣ ከጊዜ ወደ ጊዜ የመንግስት ወጪ እየተለጠጠና በጀቱ እያበጠ መምጣቱ ነው፣ ትልቁ የበሽታ ምልክት። በጀት ማሳበጥ፣ መዘዞች አሉት። ወጪውን የሚሸፍን በቂ ገንዘብ እንደ ልብ አይገኝማ። እናም መንግስት ወጪውን ለመቀነስ ከመጣጣር ይልቅ፣ በየአመቱ እየገዘፈ የሚመጣውን የበጀት ጉድለት ለመሸፈን፣ በቦንድ ሽያጭ ገንዘብ ይበደራል። ለምሳሌ ባለፉት መንግስት ሶስት አመታት ከ3 ትሪሊዮን ዶላር በላይ ስለተበደረ፣ በድምሩ የመንግስት እዳ ከ16 ትሪሊዮን ዶላር አልፏል።

በእርግጥ፣ የመንግስት ወጪዎችንና በጀቶችን ለመቀነስ መጠነኛ ማሻሻያዎች ተደርገዋል። ከዚህም ጋር የብድር ጣሪያን የሚገድቡ ህጎች በተደጋጋሚ ታውጀዋል። ነገር ግን፣ የብድርና የእዳ አዙሪቱ አልተበጠሰም። እንዲያውም በአዳዲስ ተጨማሪ ወጪዎች፣ ነገሩ ሁሉ እንደ አውሮፓውያኑ የግሪክ እና የስፔን አይነት ተስፋ ቢስነት እንዳያመራ የሚሰጉ አሉ። ለምሳሌ ከውዝግብ ጋር ተገጣጥሞ፣ ማክሰኞ እለት ስራ ላይ የዋለው አስገዳጁ የጤና ኢንሹራንስ ህግ (ኦባማኬር)፣ በየአመቱ በመቶ ቢሊዮን ዶላር የሚገመት ተጨማሪ ወጪዎችን የሚያስከትል ነው። በዚያው መጠንም የበጀት ጉድለቱና የእዳ ክምሩ ይባባሳል። የዘንድሮውን የበጀት ጉድለት ለመሸፈን ብቻ መንግስት፣ ከ700 ቢሊዮን ዶላር በላይ ተጨማሪ ብድር ያስፈልገዋል።

ነገር ግን፣ ፕሬዚዳንት ኦባማ በገንዘብ ሚኒስትራቸው በኩል ለ“ኦባማኬር” እና ለሌሎች የመንግስት ወጪዎች ያሰኛቸውን ያህል በጀት የመመደብና የበጀት ጉድለቱን ለመሸፈን ያሻቸውን ያህል ገንዘብ የመበደር ስልጣን የላቸውም - ከኮንግረስ ይሁንታ ካላገኙ በስተቀር። የአሜሪካ ውበት ያለው እዚህ ላይ ነው። የመንግስት ስልጣን በሕግ የተገደበ ነው። የመንግስት ወጪ በግማሽ ትሪሊዮን ዶላር ለመቀነስና “ኦባማኬር”ን ለማስወገድ ከመሞከር ያልቦዘኑት ሪፐብሊካኖች በበኩላቸው፣ ህጉን ለመሻር 40 ያህል አዋጆችን አርቅቀው ቢያፀድቁም፣ በፕሬዚዳንቱና በሰኔቱ ተቀባይነት ስላላገኙ ውድቅ ተደርጎባቸዋል። አንዱ የመንግስት አካል፣ ለሌላኛው የመንግስት አካል ልጓም ይሆንለታል። እንግዲህ፤ በአንድ በኩል ኮንግረሱ፣ በሌላ በኩል ደግሞ ሰኔቱና ፕሬዚዳንቱ ለበርካታ ወራት እንደተፋጠጡ፣ “መስከረም ጠባ”። የዘንድሮው መስከረም እንደሌላው ጊዜ የበጀት ውዝግብን ብቻ አስከትሎ አልመጣም፣ ሌሎች ሁለት ውዝግቦችንም ጨምሮበታል። እንደተለመደው፣ መስከረም 21 ቀን (ኦክቶበር 1 ቀን)፣ አዲስ የበጀት አመት የሚጀመርበት ቀን ስለሆነ፣ የበጀት ውዝግብ መፈጠሩ አይገርምም።

ውዝግቡ መካረሩና በቀላሉ ስምምነት ላይ አለመደረሱ ነው፣ የዘንድሮውን ለየት የሚያደርገው። አዲስ በጀት ካልፀደቀ የመንግስት መስሪያ ቤቶች በራቸውን ይዘጋሉ። አወዛጋቢውና በሪፐብሊካኖች ዘንድ የማይወደደው “ኦባማኬር” የተሰኘው አስገዳጅ የጤና ኢንሹራንስ፣ በይፋ ተግባራዊ መሆን የሚጀምረውም በዚሁ እለት መሆኑ፣ የሁለቱን ወገኖች ውዝግብ አወሳስቦታል። ከሁለት ሳምንት በኋላ (ኦክቶበር 17) ደግሞ፣ የመንግስት የእዳ ክምር በህግ የተቀመጠለትን ጣሪያ ይነካል ተብሎ ይጠበቃል። እናም የብድር ጣሪያ ለመገደብ ከሁለት አመት በፊት የፀደቀው ህግ ካልተከለሰ፣ መንግስት ወጪዎቹን ለመሸፈን ተጨማሪ ብድር ማግኘት አይችልም። የመንግስት አማካይ የሳምንት ወጪ 60 ቢሊዮን ዶላር ገደማ ቢሆንም፣ አማካይ ገቢው ግን 45 ቢ. ዶላር ገደማ ነው። በየሳምንቱ በአማካይ 15 ቢሊዮን ዶላር ብድር ካላገኘ አመቱን ሊዘልቅ አይችልም። ተንገራግጮ ይቆማል።

እናም፣ በተጨማሪ ብድር አመቱን ለመዝለቅ፣ የእዳ ጣሪያው ከ16.7 ትሪሊዮን ወደ 17.5 ትሪሊዮን ገደማ መስተካከል ይኖርበታል። ግን እስከመቼ እዳ እየተቆለ ይቀጥላል? እንደምታዩት፣ የፍጥጫው አስኳሎች እነዚሁ የበጀት፣ የእዳ እና የ“ኦባማኬር” ውዝግቦች ናቸው ማለት ይቻላል። ፕሬዚዳንት ኦባማ እና አብላጫውን የሰኔት ወንበር የያዙ የዲሞክራቲክ ፓርቲ ተመራጮች፣ የሚያጨቃጭቅ ነገር የለም ባይ ናቸው … “የመንግስት መስሪያ ቤቶች መዘጋት ስለሌለባቸው እንደ አምናው በጀት ሊመደብላቸው ይገባል፤ የበጀት ጉድለቱን ለመሸፈንም የእዳ ጣሪያው መስተካከል አለበት። ይሄ አከራካሪ ሊሆን አይገባውም። ወጪዎችን ለመቀነስ፣ የበጀት ጉድለትን ለማስወገድና የእዳ ክምችትን ለማቃለል፣ መወያየትና መደራደር እንችላለን። ነገር ግን፣ የመንግስት ስራዎች መቋረጥ አይኖርባቸውም” ይላሉ። በኮንግረስ ውስጥ አብላጫውን ወንበር የያዙ የሪፐብሊካን ፓርቲ ተመራጮች ግን በዚህ አይስማሙም። አምርረው ይቃወሙታል እንጂ። “የመንግስት ወጪ እየተለጠጠ፣ የበጀት ጉድለት እየሰፋና የእዳ ክምችት እየተቆለለ መምጣቱ ሳያንስ፣ ‘በኦባማኬር’ ሳቢያ ችግሩን ይበልጥ የሚያባብስ ግዙፍ ወጪ ሊጨመርበት አይገባም። የእዳ ጣሪያውን በማንሳት ለተጨማሪ ብድር በር ከመክፈታችን በፊት አሁኑኑ የረዥም ጊዜ መፍትሄ ማበጀት ይገባናል። ቢያንስ ቢያንስ፣ ኦባማኬር ሙሉ ለሙሉ ወይም በከፊል ለአንድ አመት ስራ ላይ እንዳይውል ማዘግየት ያስፈልጋል” ይላሉ። በዚህ አቋም ላይ በመመስረት፣ በኮንግረስ የሪፐብሊካኖች መሪ የሆኑት አፈጉባኤ ጆን በይነር ምን አደረጉ? ለአስር ሳምንታት ገደማ የሚያገለግል ጊዜያዊ የበጀት አዋጅ ያዘጋጁትበይነር፣ “ለኦባማኬር ምንም በጀት አይመደብለትም” የሚል ተጎታች ከአዋጁ ጋር በማዳበል የኮንግረስ አባላት ድምፅ እንዲሰጡበት አቀረቡት። አሜሪካ የነፃነት አገር ነውና፣ የፓርቲ መሪዎችን ተከትለው ድምፅ የማይሰጡ የኮንግረስ አባላት መኖራቸው አይገርምም። አብዛኞቹ ሪፐብሊካኖችና 20 ያህል አፈንጋጭ ዲሞክራቶች፣ ባለተጎታቹን የበጀት አዋጅ በመደገፍ ድምፅ ሰጥተዋል።

አብዛኞቹ ዲሞክራቶችና ጥቂት አፈንጋጭ ሪፐብሊካኖች ደግሞ ተቃውመውታል። በድምሩ በ230 ድጋፍ አዋጁ በአብላጫ ድምፅ ፀድቆ ወደ ሰኔት ተላከ። ሰኔቱ ይህንን ባለ ተጎታች የበጀት አዋጅ ቢያፀድቀው፣ ወደ ፕሬዚዳንቱ ነበር የሚሄደው። ነገር ግን፣ እዚያ አልደረሰም። በሴኔት ውስጥ አብላጫውን ወንበር የያዙት ዲሞክራቶች፣ የመጣላቸውን ባለተጎታች አዋጅ ተቀብለው፣ “ለኦባማኬር በጀት አይመደብለትም” የሚለውን አንቀፅ በመሰረዝ ሌጣውን ካስቀሩት በኋላ ሴናተሮች እንዲከራከሩበት አቀረቡት። ድምፅ ይሰጥበት ከተባለ ሌጣው አዋጅ እንደሚፀድቅ አያጠራጥርም - በ54 ዲሞክራት ሴናተሮች ድጋፍና በ46 ሪፐብሊካን ሴናተሮች ተቃውሞ። ነገር ግን፣ ዲሞክራቶች፣ በሰኔት ውስጥ አብዛኛውን ወንበር ስለያዙ ብቻ፣ በቀላሉ አዋጁን ማፅደቅ ይችላሉ ማለት አይደለም። አንድ እንቅፋት ማለፍ አለባቸው - በቅድሚያ የሰኔት ውስጥ የሚደረገውን ክርክር መቋጨት ይኖርባቸዋል።

ምክንያቱም በሰኔት ውስጥ፣ ነገ አራት ሰዓት ላይ ድምፅ ይሰጥበታል ተብሎ የተጀመረው ክርክር፣ በተባለው ሰዓት ላያበቃ ይችላል። ለምን? ሴናተሮች ልዩ መብት አላቸዋ። ተራው ደርሶ መናገር የጀመረ ሴናተር፣ ያለማቋረጥ የቻለውን ያህል ሰዓት ንግግሩን መቀጠል ይችላል። ባለፈው ሳምንት ማክሰኞ እለት፣ ‘ኦባማኬር’ እንዲወገድ የሚፈልጉ ቴዲ ክሩዝ የተባሉ ሪፐብሊካን ሴናተር፣ ሌጣውን አዋጅ በመቃወም ለ21 ሰዓታት ያለማቋረጥ የሴኔቱን መድረክ ይዘው ነበር። በአዋጁ ላይ ድምፅ ይሰጥበታል የተባለው ሰዓት ካለፈ፣ ማሸጋሸግ ብሎ ነገር የለም። እንደገና እንደ አዲስ የውይይትና የድምፅ አሰጣጥ ፕሮግራም ይወጣል። ነገር ግን አሁንም፣ ያለ ገደብ ለበርካታ ሰዓታት የሚቀጥል አንድ ሴናተር፣ እንደገና የድምፅ አሰጣጥ ፕሮግራሙን በማዛባት ያስተጓጉለዋል።

በዚህ መንገድ፣ አዋጅ እንዳይፀድቅ ማሰናከል፣ ‘ፍሊበስተር’ ተብሎ ይታወቃል። የሴናተር ንግግርና ክርክር ሊቋረጥ የሚችለው፣ 60 ሴናተሮች የሰዓት ገደብ ለመጣል ከተስማሙ ነው። በሌላ አነጋገር፣ በሰኔቱ ውስጥ 54 ወንበር ያላቸው ሴናተሮች፣ ብቻቸውን የውይይት ሰዓት ገደብ እንዲበጅለት መወሰን አይችሉም። ቢሆንም፣ በአሜሪካ ፖለቲካ ውስጥ “በፓርቲ ትዕዛዝ ሰጥ ለጥ ብሎ መመራት” ብሎ ነገር ስለሌለ፣ ዲሞክራቶቹ ከሪፐብሊካን ሴናተሮች መካከል የተወሰነ ድጋፍ ማግኘት ይችላሉ። በመጨረሻም የሪፐብሊካኑ ሴናተር የቴድ ክሩዝ ረዥም ንግግር እንዲያበቃ የሚፈልጉ ሴናተሮች ቁጥር 60 ስለደረሰ፣ ሲናገሩ ውለው ያደሩት ቴዲ ክሩዝ ከ21 ሰዓት ተኩል ገደማ በኋላ ንግግራቸው ለመቋጨት ተገደዋል።

ከዚያማ ሌጣው ሕግ ላይ ድምፅ ተሰጥቶ 54 ለ46 በሆነ ድምፅ ፀደቀና ወደ ኮንግረስ ተመልሶ ተላከ። በኮንግረሱ ውስጥ የሪፐብሊካኖች መሪ ሆነው በአፈጉባኤነት የሚሰሩትበይነር፣ በሰኔት ለከልሶ የመጣውን አዋጅ በኮንግረስ አባላት ድምፅ እንዲሰጥበት አላደረጉም - “ለኦባማኬር በጀት አይመደብለትም” የሚለው ተጎታች ስለተሰረዘ። በዚያ ምትክ ሌላ አዋጅ አርቅቀው አቀረቡ - ለ10 ሳምንታት ገደማ የሚያገለግል ጊዜያዊ በጀትና ኦባማኬር በከፊል ለአንድ አመት እንዲዘገይ የሚደነግግ አዋጅ። አዋጁ ፀድቆ ወደ ሰኔት ሲሄድ ግን፣ ተመሳሳይ እጣ ገጠመው። “ኦባማኬር፣ በከፊል ለአንድ አመት ይዘገያል” የሚለው አንቀፅ ተሰርዞ 54 ለ46 በሆነ ድምፅ ወደ ኮንግረስ ተመለሰ። እንዲህ እንዲህ እያለ፣ በጀት ሳይፀድቅ የበጀት መዝያ እለት ደረሰ - ሰኞ ሴፕተምበር 30። በማግስቱም በጀት አልፀደቀም። ያለበጀት መስራት ስለማይችሉ ለጊዜው እንዲዘጉ የመንግስት መስሪያ ቤቶች መቼ እንደሚከፈቱ አይታወቅም። ለምን? ውዝግቡ መቼ እልባት እንደሚያገኝና መቼ በጀት እንደሚፀድቅ ስለማይታወቅ! ሁለት ሶስት ሳምንት ሊቆይ እንደሚችል ነው የሚገመተው።

(ላታ ኤኬና ሾሮይ ብት ዎሬስ) - የወላይታ ተረት

        ከዕለታት አንድ ቀን፣ ከአንድ እርሻ አጠገብ፣ አንድ ኮሳሳ ውሻ ተኝቶ ፀሐይ እየሞቀ ሳለ፤ አንድ የተራበ ተኩላ ድንገት ከተፍ ይልበታል፡፡ ከዚያም ያንን ውሻ ለመብላት አሰፍስፎ፤ “እንዳትነቃነቅ! የዛሬ ቁርሴ አንተ ነህ!” ይለዋል፡፡ ውሻውም፤ “ጌታ ተኩላ ሆይ! እኔ ባሁኑ ሰዓት ምን ዓይነት ኮሳሳ ፍጥረት እንደሆንኩ ታያለህ! አሁን እኔን በልተህ ምንም አትጠቀምም፡፡ ምክንያቱም አጥንቴ የቀረ ልሞት ጥቂት የቀረኝ እንስሳ ነኝ፡፡” ተኩላም፤ “ታዲያ እንዲሁ ባዶ ሆዴን እንድውልልህ ነው የምትፈልገው?” አለ፡፡ ውሻ፤ “የለም፡፡ ሁለት ሶስት ቀን ብትታገስ፤ የእኔ ጌታ ትልቅ ድግስ ለመደገስ እየተዘጋጀ ነው፡፡ ከድግሱ በርካታ ትርፍራፊ እጄ ይገባል፡፡ ያኔ ብዙውን ሥጋ፤ አጥንትና ቅባት የጠጣ ምግብ፤ ላንተ አስረክብሃለሁ፡፡ ከዛ በኋላ፤ ከፈለግህ እኔን ጨምረህ ለመብላት ትችላለህ” ይለዋል፡፡ ተኩላው፤ በጉጉት ቆበሩን እየደፈቀ፤ “ይሄ በጣም ጥሩ ዕቅድ ነው፡፡

እንዳልከው ትንሽ ቀን መታገስ አያቅተኝም” ብሎ ውሻውን ጥሎ ወደጫካው ሄደ፡፡ በሶስተኛው ቀን ተኩላው ተመልሶ ወደ እርሻው ቦታ መጣ፡፡ ውሻው ግን እበረቱ ጣራ ላይ ተኝቶ ፀሐይ ይሞቃል፡፡ “ደህና ዋልክ አያ ውሻ” አለ ተኩላ፡፡ ውሻም፤ “እንደምን ሰነበትክ፤ ሰሞኑንኮ ከዛሬ ነገ ትመጣለህ እያልኩ ስጠብቅህ ከረምኩ፡፡ ምነው ጠፋህ?” ተኩላም፤ “ሁለት ሦስት ቀን ስላልከኝ፤ ጊዜ ልስጥህ ብዬ ነው፡፡ ይኸው በሶስተኛው ቀን መጣሁ፡፡ ጌታህ ይደግሳል ያልከኝ ድግስ የታለ? በስምምነታችን መሠረት ውረዳ?” ሲል ጠየቀው፤ ምላሱን ካፉ እያወጣ፣ ከንፈሩን እየላሰ የመብላት ስሜቱን በመግለጽ፡፡ ውሻም፤ “አይ አያ ተኩላ! ጌታዬማ ድግሱን ለሚቀጥለው ዓመት አዛወረው፡፡ ከእንግዲህ እኔንም ሁለተኛ ባለፈው ያገኘኸኝ ገላጣ ሜዳ ላይ አታገኘኝም፡፡ በእጅህ የገባልህን ነገር ትተህ፣ ገና ለገና አገኘዋለህ ብለህ፣ በተስፋ የተመኘኸውን ድግስ ልትበላ ስትስገበገብ፤ ሁለት ቀን ፆምህን መዋልህ ነው፡፡ ይልቅ አሁን ጌታዬ መምጫው ስለደረሰ ከዚህ ዞር ብትል ይሻልሃል” አለው፡፡ ተኩላው እየተናደደና እየዛተ መንገዱን ቀጠለ፡፡ ውሻ እየሳቀ ፀሐይ መሞቁን ተያያዘው፡፡

                                                          * * *

ፀሐይ የሚሞቅ ውሻ ሁሉ ሞኝ አይደለም፡፡ ለነገ እበላዋለሁ የሚል ጅል ተኩላ ግን ምን ጊዜም አይጠፋም፡፡ ይህን ሁሉ የሚታዘብ ህዝብ እንዳለ የሚያውቅ ካለ የብልህም ብልህ ነው፡፡ ከላይ ከተረቱም እንደምንረዳው፤ የሌሎችን ግብና አዕምሮ ማማለልንና ማዘናጋትን የሚያውቁበት ሰዎች እንዳሉ አንርሳ! ተስፋ በመስጠት እንደዳማና እንደ ቼዝ ጠጠር (ወታደር) በፈለጉት አቅጣጫ ይገፉናል፡፡ ፍላጐታችንን ያከበሩ በመምሰል ፍላጐታቸውን የሚያሟሉ ሰዎች አደገኞች ናቸው፡፡ የህንዱ ፈላስፋ ካውቲላ “በቀስተኛ የተሰደደ ቀስት፣ አንድን ነጠላ ሰው ሊገድልም ላይገድልም ይችላል፡፡ የተቀመረ ሴራ ግን እናት ሆድ ውስጥ ያለውን ህፃን ሳይቀር ሊገድል ይችላል” ይላል፡፡ በዚህ የተካኑ ሰዎችን በዐይነ - ቁራኛ ማየት ያባት ነው፡፡ ስሜትን ተቆጣጥሮ ደባና ሴራን ጠንቅቆ ማየትና በጠዋት መንቃት ተገቢ ነው፡፡ እንደ ናፖሊዮን “ጠንካራ እጅህን ከሀር በተሰራ ጓንት ውስጥ ክተት” የሚሉ እንዳሉ እንገንዘብ፡፡ ድቀትና ዝቅጠት ሲያይል አሉባልታና ጥርጣሬ ይነግሳል፡፡ አንድም፤ “ጊዜ ሲበሳበስ መሾም መሸለም እየቀለለ ይመጣል”፡፡

(ሄልሙት ክሪስት እንዳለው) በእንዲህ ያለው ሰዓት አፍ - አዊ እየበረከተ፣ ልባዊና ተግባራዊ እየሳሳ ይመጣል፡፡ ይሄኔ መጠንቀቅ ይበጃል፡፡ ኒቼ እንደሚለን “የአንድ ነገር ዋጋ በዚያ ተገልግለን በምናገኘው ጥቅም አይለካም፡፡ ይልቁንም ያንን ነገር ለማግኘት በምንከፍለው መስዋዕትነት ነው የሚለካው”፡፡ አገር እንገነባለን ስንል ይህን ብሂል አለመርሳት ነው፡፡ ይሆነናል የምንለውን ሰው መርጠን ስንሾምም ይህንን አለመዘንጋት ነው፡፡ ባለሙያው እያለ ስለዚያ ሙያ የሚያወራ ሲበዛ ጠንቀቅ ማለት ያሻል፡፡ “አያገባው ገብቶ አያወዛው ተቀብቶ” እንደተባለው መሆኑን ልብ ማለት ነው፡፡ መጪዎቹ የፓርላማ ጊዜያት የጠነከሩ፣ ልባዊነት የሞላባቸውና አመርቂ እንዲሆኑ እንመኝ፡፡ “ሸንጐ/አደባባይ የሰለጠነ ጦርነት ነው” የሚባለው በዋዛ አይደለም፡፡ መሪዎች የሸንጐን ጥበብ መካን አለባቸው፡፡ አደባባይ መዋል የራሱ የክት ጠባይ አለው፡፡ “ሸንጐ የሚያውቅ ሰው፤ መልኩን መቆጣጠር ይችላል፡፡ በቀላሉ ልቡን አይሰጥም፡፡ ለክፉ አድራጊዎች ዕድል አይሰጥም፡፡ ለጠላቶቹ ፈገግ ማለት ይችላል፡፡ ንዴቱን መዋጥ ያቅበታል፡፡ ወገናዊነቱን መሸፈን ይችላል፡፡ የልቡን ደብቆ እሱ በዚያች ቅጽበት ልመስል ወይም ልሆን ይገባኛል የሚለውን፤ የሚፈልገውን ስሜት ያስተናግዳል፡፡ የራሱን ቦታ፣ መሬት፤ አገር፣ ውሉን አይስትም” ይለናል፤ ፈረንሣዊው ዣን ዴላ ብሩዬር፡፡ ፕሬዚዳንት ስንመርጥ እንዲህ ያለውን ቁም ነገር አንርሳ፡፡

ህግ ብቻውን ሁሉን ጉዳይ አይጨርስልንም፡፡ አስተዋይ አመራር፣ አስፈፃሚና ተጠያቂነትን ገምጋሚ እንዲኖር ያሻል፡፡ ያ ደግሞ ግልጽነትን ልማድ የሚያደርግ መሆን አለበት፡፡ አሉባልታ የሚቆመው ግልፅነትና መረጃ ሰጪነት ሲከበር ነው፡፡ “የፕሬዚዳንቱ ቤት ኪራይ ጉዳይ፤ የእገሊት የውጪ ባንክ ገንዘብ ጉዳይ፣ የእነ እገሌ ህንፃ… ይሄ ተሸጠ፣ ያ ተገዛ…ወዘተ” የጥርጣሬና የሟርት ዘመን ምልኪዎች ናቸው፡፡ በምንም ዓይነት ግን የፖለቲካ ትግልን እንደማይተኩልን ማሰብ ተገቢ ነው! የፖለቲካ ትግል ከሁሉም በፊት መደራጀትን፣ ተደራጅቶም መስዋዕትነትን፣ በሀገር ላይ ለውጥ የማየት ልባዊ ስሜትን ይጠይቃል! በተግባር ሳይሆን አሉባልታዊና ሐሜተኛ ማህበረሰብ እየተገነባ ከመጣ የመዝቀጥ አሊያም የመስበስ ክፉ አባዜ መምጣቱን ይጠቁማል (Decadence እንዲሉ)፡፡ ተግባራዊና የሚለውን የሚተረጉም ማህበረሰብ ካልፈጠርን ሟርት ይበዛል፡፡ “የማይወርስ ጐረቤት በሟርት ይገድላል” ይላል የወላይታ ተረትና ምሣሌ፡፡ ይሄንኑ ሁኔታ በቅጡ ሊነግረን ፈልጐ ነው፡፡

               ተቃዋሚ ፓርቲዎች በተለያዩ የአገሪቱ ክፍሎች የሚያደርጓቸው የተቃውሞ ሰልፎች ተደጋጋሚና መንግስት አቋም የያዘባቸውን ጉዳዮች የሚያነሱ እንደሆኑ የጠቆሙት ጠ/ሚኒስትር ኃ/ማርያም ደሳለኝ፤ መንግስት ለእያንዳንዱ ሰልፍ ጥበቃ ማድረግ ስለማይችል ሰልፎቹ በተለመደው መልኩ ላይቀጥሉ እንደሚችሉ ተናግረዋል፡፡ ጠ/ሚ ኃይለማርያም ደሳለኝ ትናንት በጽ/ቤታቸው ለጋዜጠኞች በሰጡት መግለጫ፤ ተቃዋሚ ፓርቲዎቹ የሚያነሷቸው ጥያቄዎች የራሳቸው የፓርቲዎቹ ሳይሆኑ የሌሎች ሃይሎች እንደሆኑ ገልፀዋል፡፡

ፓርቲዎቹ ሰልፍ ማካሄድ ህገመንግስታዊ መብታቸው መሆኑን የጠቀሱት ጠ/ሚኒስትሩ፤ መንግስት በተደጋጋሚ ጥበቃ ሲያደርግ ቢቆይም፣ በሰልፎቹ የሚነሱት ጥያቄዎች ፋይዳ ቢስ ከመሆናቸውና ከፓርቲዎቹ ብዛት አንፃር መንግስት በቀጣይ ለሰልፎች ጥበቃ ለማድረግ የሚቸገርበት ሁኔታ ሊፈጠር እንደሚችል አስረድተዋል፡፡

 ተቃዋሚ ፓርቲዎች፤ መንግስት በተደጋጋሚ ምላሽ የሰጠባቸውን ጥያቄዎች መላልሰው የሚያቀርቡት በመንግስት ላይ ጫና በመፍጠር አቋሙን ለማስቀየር በማሰብ ሊሆን ይችላል ያሉት ጠ/ሚኒስትሩ፤ ይሄ ግን በፍፁም የማይሳካ ሃሳብ ነው ብለዋል፡፡ “ግንቦት ሰባት” በቅርቡ መንግስትን ለመጣል ወታደራዊ እርምጃ እንደሚወስድ በይፋ መግለፁን በተመለከተ ተጠይቀው ሲመልሱም፣ የፓርቲው አመራሮችና ደጋፊዎች ተጨባጭ ያልሆነ ህልም ውስጥ ሆነው የተናገሩት ነገር እንደሆነና ከህልማቸው ሲነቁ እውነታውን እንደሚገነዘቡት ጠ/ሚኒስትሩ ተናግረዋል፡፡ ኢህአዴግ ውስጥ መከፋፈልና የሃይል መጠባበቅ አለ የሚለውን መረጃ በተመለከተም “ይህ የአንዳንድ አፍራሽ ሃይሎች ከንቱ ምኞትና ተጨባጭ ያልሆነ አሉባልታ ነው” ሲሉ አጣጥለውታል፡፡

የ3 ወሩ ህዝባዊ ንቅናቄ “ዋጋ የተከፈለበት” ነው ብሏል

                  ባለፉት ሶስት ወራት “የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት” በሚል መሪ ቃል የመጀመሪያ ዙር ህዝባዊ ንቅናቄ ሲያደርግ የቆየው አንድነት ለፍትህና ለዲሞክራሲ ፓርቲ፤ ባለፈው እሁድ የማጠቃለያ ሰልፉን ሲያደርግ ደርሶብኛል ላለው የሞራልና የንብረት ጉዳት የአዲስ አበባ አስተዳደርና ፖሊስን በህግ እንደሚጠይቅ አስታወቀ፡፡ አንድነትና 33ቱ ፓርቲዎች ከትላንት በስቲያ በአንድነት ፅ/ቤት በሠጡት መግለጫ፤ የህዝባዊ ንቅናቄ ማጠቃለያ ሰልፉን መስከረም 19 አዲስ አበባ ላይ ለማካሄድ እንደምንችል የሚያረጋግጥ የእውቅና ደብዳቤ የከተማ መስተዳደሩ የከንቲባ ፅ/ቤት ቢሰጣቸውም፣ በእጅ አዙር ሠልፉ በመስቀል አደባባይ እንዳይደረግ መከልከላቸውን፣ ከህግ ውጪ በፀጥታ ተቋማት አካባቢ ሰልፉ እንዲከናወን መገደዳቸውንና ቅስቀሣ እንዳይደረግ መታገዳቸውን አመልክተዋል፡፡

ፖሊስም ህገ መንግስቱንና ህዝቡን መጠበቅ ሲገባው “ለመቀስቀስ፣ ፖስተር ለመለጠፍና በራሪ ወረቀቶችን ለማሠራጨት ፈቃድ ያስፈልጋል፣ ትዕዛዝ አልደረሠንም” በማለት ህገ መንግስታዊ መብቶችን ጥሷል ያሉት ፓርቲዎቹ፤ የአንድነትን ሊቀመንበር ጨምሮ 101 አባላትን ከማክሠኞ እስከ እሁድ ማሠሩንም ገልፀዋል፡፡ “ፖሊስ ለህግ የበላይነት መቆም ሲገባው በድብቅ ለተሠጠው ትዕዛዝ ተገዢ በመሆኑ ጉዳዩን ለህግ እናቀርባለን” ብለዋል - ፓርቲዎቹ፡፡ የፓርቲው አመራር አባል አቶ አስራት ጣሴ በተለይ ለአዲስ አድማስ በሰጡት ቃለምልልስ፤ ስለ ሠላማዊ ሠልፍና ህዝባዊ ስብሠባ ማድረግ የወጣው አዋጅ “ማንኛውም ሠላማዊ ሠልፍ ወይም ህዝባዊ የፖለቲካ ስብሠባ በጦር ሃይሎች፣ በጥበቃ እና የህዝብን ሠላምና ደህንነት በሚቆጣጠሩ የመንግስት የስራ ክፍሎች አካባቢ 300 ሜትር ክልል ውስጥ ሊደረግ አይችልም” እንደሚል ጠቅሠው፤ የአዲስ አበባ መስተዳደር የአዋጁን አንቀፅ በመጣስ፣ እነዚህ ተቋማት በሚገኙበት ጃንሜዳ እንድንሰባሠብ ሊያስገድደን ሞክሯል ብለዋል፡፡ ፓርቲው ያቀረባቸውን ዘጠኝ ያህል አማራጭ ቦታዎች በመከልከል አዋጁን በጣሠ መልኩ በጃንሜዳ አድርጉ የሚል ትዕዛዝ ማስተላለፉ ከፍተኛ የህግ ጥሠት መሆኑን የጠቀሱት አቶ አስራት፤ ፓርቲው ያቀረባቸውን አማራጭ ቦታዎች ገምግሞ አለመፍቀዱም ሠላማዊ ሠልፍ የማድረግ ህገ መንግስታዊ ድንጋጌውን የጣሠ በመሆኑ በአስተዳደሩ ላይ ክስ እንመሰርታለን ብለዋል፡፡

ፓርቲው በፖሊስ ተቋማት ላይ የሚያቀርበው ክስ የተሻሻለውን የፓርቲዎች የምዝገባ አዋጅ መሠረት አድርጐ ነው ያሉት አቶ አስራት፤ አዋጁ የህዝብን የፖለቲካ ግንዛቤ ማዳበር፣ የፓርቲውን አላማ ለህዝብ ማስረፅ እንዲሁም ዜጐች በሃገሪቱ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ውስጥ ንቁ ተሣትፎ እንዲኖራቸው መቀስቀስ… የፖለቲካ ፓርቲ የዕለት ተዕለት ተግባራት መሆናቸውን እንደሚገልጽ ጠቅሰው፤ የአዲስ አበባ ፖሊስ አዋጁን በመጣስ በዚህ ሠላማዊ ሠልፍ ብቻ ከ100 በላይ ሠዎችን አስሯል ብለዋል፡፡ ከዚህም በተጨማሪ መኪና፣ ሞንታርቦና ጀነሬተር የመሣሠሉትን የፓርቲው ንብረቶችን ያለ አግባብ ስላገደ፣ በሁለቱም የመብት ጥሰቶች እንከሳለን ብለዋል፡፡ የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳየች ፅ/ቤት ሚኒስትር ዴኤታ አቶ ሽመልስ ከማል ከእሁዱ ሠላማዊ ሠልፉ በኋላ ለመንግስት መገናኛ ብዙሃን በሠጡት መግለጫ፤ “ፓርቲው ባካሄደው የተቃውሞ ሠልፍ ላይ በሽብር ወንጀል ተከሠው የተፈረደባቸውን ግለሠቦች አቋም ማንፀባረቁና ማወደሱ የህግ መዘዝ ያመጣል፤ ፓርቲው ለሚመጣው የህግ መዘዝ ዝግጁ መሆን አለበት፡፡” ማለታቸው ይታወሳል፡፡

አቶ አስራት የአቶ ሽመልስ ከማልን መግለጫ በተመለከተ ሲናገሩ፤ “የህግ ጥሠት የፈፀሙት የመንግስት አካላት ስለሆኑ መከሠስ ያለባቸው እነሡ ናቸው፤ ከዚያ የተረፈው ዝም ብሎ ማስፈራራት ነው፤ እኛ ግን በሃገራችን አንፈራም፣ ልንፈራም አይገባም” ብለዋል፡፡ ከሠኔ 12 ቀን 2006 ጀምሮ እስከ መስከረም 19 ቀን 2006 በቆየው የሶስት ወር ህዝባዊ ንቅናቄ ፓርቲው በጐንደር፣ በደሴ፣ በባህር ዳር፣ በአርባ ምንጭ፣ በጅንካ፣ በአዳማና በፍቼ አባሎቹ እየተደበደቡና እየታሠሩም ቢሆን የተቃውሞ ሠልፎቹን ማካሄዱን ጠቅሶ፤ በመቀሌና በባሌ ሮቤ ጫናውን መቋቋም ባለመቻሉ ሣይካሄድ መቅረቱን አመልክቷል፡፡ በከፍተኛ ጫና ውስጥ ታልፎ የተደረገው ህዝባዊ ንቅናቄ የእስር፣ የድብደባ፣ የሞራል ጉዳትና የንብረት ማጣት ዋጋ የተከፈለበት እንደሆነ ፓርቲው አስታውቋል፡፡

Saturday, 28 September 2013 14:00

“ሲኖዶሱ ስለመስቀሉ

መግለጫ እስኪሰጥ ህዝቡ በትዕግስት ይጠባበቅ”
ስለመስቀሉ ከሰማይ መውረድ በጀመሪያ መረጃው እንዴት ነው የደረሳችሁ?
መስቀሉ ከሰማይ ወረደ ስለሚባለው የሻለ መረጃ የምታገኙት ወረደ ከተባለበት ቤተክርስቲያን አስተዳዳሪዎችና አገልጋዮች ነው። እኛ ከሰማይ ወረደ ከተባለ ከቀናት በኋላ ነው በስፍራው የተገኘነው፡፡ ስለዚህ እነሱ እንደነገሩን እንጂ አይተናል ሰምተናል ብለን አይደለም መረጃ የምንሰጣችሁ፡፡
እነሱ ግን እንዴት እንደወረደ አይተናል ስላሉ መረጃውን ከእነሱ ነው ያገኘነው፡፡ ከእነሱ የተነገረን እንግዲህ ነሐሴ 23 ለ24 አጥቢያ ሌሊት እንደወረደ ነው፡፡ ነሐሴ 23 የቅድስት ክርስቶስ ሰምራ ክብረ በአል ነው፡፡ ጽላቷም ከቅዱስ ገብርኤል ጋር በተደራቢነት አለ፡፡ ሌሊት ማህሌት ቆመን ሳለ ከፍተኛ ድምጽ ተሰማ ነው የሚሉን፡፡ ተደናግጠን ስንወጣ ወደ ቤተልሄሙ አካባቢ መስቀሉ ወድቆ የሚንቦገቦግ ብርሃን አየን ነው ያሉት፡፡ ወዲያውኑ ሲነጋ እንዳንነካ ፈርተን ማንሳትም አልቻልንም፤ ነገር ግን በወቅቱ ዝናብ ስለነበር እዚያው ላይ መስቀሉ ሳይነሳ ድንኳን ተከልንበት ነው ያሉን፡፡ የታቦት መጐናፀፊያ ለማልበስም ወደ መስቀሉ ሳንቀርብ፣ ወርውረን አለበስነው ብለውናል፡፡ እኛ ነሐሴ 24 ወዲያውኑ ከሰአት ነበር የሄድነው፡፡ ስንሄድ ከባድ ዝናብ ስለዘነበና ቦታውም በጣም አስቸጋሪ ስለሆነ መድረስ አልቻንም፤ ተመለስን፡፡ በ25 እንዲሁ ጥረት አድርገን ነበር፡፡ አልተሳካም። ነገር ግን በ27 ከሰዓት በኋላ ሄድን፡፡ መንገዱ እጅግ ፈታኝና በጣም አስቸጋሪ ነው፡፡ ምንም ማድረግ ስለማይቻል ነው እንጂ መንገዱ ከአቅሜ በላይ ነበር፤ ነገር ግን ሊቀጳጳሱ ካልመጡ ለማንሳት እንቸገራለን ስላሉ እንደምንም ቦታው ደረስን።
ህዝቡም በጣም ይጐርፍ ነበር፡፡ ፀጥታ አስከባሪዎችም በብዛት ነበሩ፡፡ ወደ 10 ሰአት አካባቢ ደረስን፡፡ የት ነው ያለው አልናቸው። ወደ ድንኳኑ መሩን፡፡ መሬት ላይ ወድቆ ተመለከትነው፡፡
በወቅቱ ከመሬቱ ላይ እንዲነሳ እነሱ ብዙም ፍቃደኞች አልነበሩም፡፡ እዚያው ላይ እያለ ቤተክርስቲያን እንዲሠራለት ነው የፈለጉት፡፡ ነገር ግን ቤተክርስቲያን የሚሰራለት ከሆነም መስቀሉ መሬት ላይ ሆኖ አይደለም የሚቆፈረውና የግድ ወደመቅደሱ መግባት አለበት አልናቸው፡፡ የእግዚአብሔር ፍቃድ ከሆነ ለወደፊት ሊሠራ ይችላል ብለናቸው ውዳሴ ማርያም ደግመን የሚገባውን ፀሎት ከካህናቱ ጋር አደረስን፡፡ ከዚያም ወደ ድንኳኑ ገብተን መስቀሉን አነሳን። መጀመሪያ እኔ ነበርኩ መስቀሉን ያነሳሁት። ከዚያም ሰባኪያኑ እንዲይዙት አድርገን ቤተክርስቲያኑ አንድ ጊዜ ዞረን፣ ወደ መንበረ ታቦቱ እንዲገባ አደረግን፡፡ እስካሁን እንግዲህ ይህ ነው ያለው ሂደት፡፡
መስቀሉ ሲነሳ ብርሃናማና የሚያቃጥል ነበረ፣ ብዙ ተአምራቶችም ታይተዋል ተብሏል? በእርግጥ እነዚህ ነገሮች ነበሩ?
ያቃጥል ነበር የሚለው እንደው የሚያቃጥል ቢሆን ኖሮ መቼ እናነሳው ነበር፤ አናነሳውም። እኔ እንደዛ መስሎኝም ነበር የሄድኩት እንጂ መነኮሳቱ ማንሳት ይችሉ ነበር፡፡ የሚያቃጥል ነበረ፣ የሚበራ ነበረ ምናልባት ጨለማ ሲሆን ታይቶ ይሆናል እንጂ እኛ ምንም አላየንም፡፡
ወርቃማና የሚያንፀባርቅ ነው የተባለ ነውስ?
እንግዲህ ወደፊት ስለመስቀሉ በስፋት የሚገለጽ ይሆናል፡፡ ሰዎችም በተለያዩ መንገዶች ስለመስቀሉ እየጠየቁን ነው ጉዳዩን ለሲኖዶሱ አቅርበን፣ ሲኖዶሱ የሚሰጠውን መመሪያ ተቀብለን ያለውን ነገር እንገልፃለን፡፡ እንግዲህ አሁን ህዝጀ ምዕመኑ ግማሹ ያለውን ነገር ተቀብሎ ይሄዳል ግማሹ ደግሞ እንዲሁ ለማታለል ነው ይላል፡፡ በዚህ ሁኔታ ህዝቡ ግራ የተጋባ በመሆኑ የግድ ሀገ ስብከታችን ሰፋ ያለ መግለጫ የሚሠጥበት ይሆናል፡፡ ብዙ የተባለለት ጉዳይ ስለሆነም የቅዱስ ሲኖዶስ ውሳኔ የግድ ያስፈልጋል፡፡ እዚያ ካሉ ሰዎች ጋርም ሰሞኑን እየተነጋገርንበት ነው፡፡
መስቀሉ በቅዱስ ሲኖዶሱ እውቅና ባላገኘበት ሁኔታ ፎቶግራፉን በ10 ብር ለሽያጭ ማቅረብና ገቢ ማሰባሰብ አግባብ ነው?
እንግዲህ ይሄን የመሳሰለውን ጉዳይ ለማስተካከል ከቤተክርስቲያኑ አስተዳደሮች ጋር እየተነጋገርን ነው፡፡ ችግሩ ምን መሰላችሁ? ቤተክህነት እውቅና ሳይሰጠው ቀድሞ ህዝቡ እውቅና ይሰጠዋል፡፡ እኔ ሄጄ በነበረ ጊዜ ስለመስቀሉ አስተያየት ብሰጥ ኖሮ ምን አይነት ትርምስ ይፈጠር እንደነበረ ትገነዘቡታላችሁ ብዬ አምናለሁ፡፡ የሆነ ሆኖ ለወደፊት በስፋት ትምህርት እንዲሰጥ ጥረት ይደረጋል፡፡ የቋሚ ሲኖዶሱ የሚሰጠው ልዩ መመሪያ ይኖራል፤ ከዚያ በኋላ መግለጫ ይሰጥበት ሲባል በኋላ መረጃ በስፋት ይሰጣል፡፡
ብዙ ጊዜ ተመሳሳይ ተአምራት ታይተዋል ይባላል፡፡ ለእነዚህ ተአምራት እውቅና የሚሰጠው የትኛው አካል ነው?
ቅዱስ ሲኖዶስ ነው፡፡
ሲኖዶሱ ካልሰጠ ተቀባይነት አይኖረውም?
አዎ አይኖረውም፡፡ ስለዚህ መስቀሉም ቅዱስ ሲኖዶሱ ውሣኔ ካልሰጠ ተቀባይነት የለውም። በመሠረቱ መስቀሉ ያቃጥላል፣ ይፋጃል የሚባለው ሃሰት ነው፤ መስቀል ይፈውሳል እንጂ አያቃጥልም፡፡ እንዲህ ከዚህ ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን በተመለከተ ለወደፊት በስፋት ትምህርት የሚሰጥበት ሊሆን ይችላል፡፡
በዚህ ላይ ሲኖዶሱ መቼ ነው ውሣኔ የሚያሳልፈው?
እንግዲህ ዛሬ ከሰአት የቤተክርስቲያኗን አስተዳዳሪዎች ጠርተናቸዋል (ይህ ቃለ ምልልስ የተደረገው ማክሰኞ ጠዋት ነው) ቅዱስ ሲኖዶሱ መረጃ ከነሱ ይጠይቃል፤ ከምን ተነስተው እንደዚህ እንዳሉ ከዚያ በኋላ ጉዳዩ በውይይት እስኪታይ ጊዜ ይወስዳል፡፡ ስለዚህ በዚህን ጊዜ ውሣኔ ይተላለፍበታል ብሎ ለመናገር አሁን አይቻልም፡፡
መስቀሉን ብፁዕነትዎ ሄደው ተመልክተውታል፡፡ ታዲያ ስለመስቀሉ በእርግጠኝነት መናገር እንዴት አይቻልም? ፓትርያርኩም ባሉበት ነው የሚታየው ብላችኋል?
ፓትሪያርኩ እሄዳለሁ አላሉም እስከመጨረሻውም ላይሄዱ ይችላሉ፡፡ አይደለም እሣቸው እኔም ላልሄድ እችል ይሆናል፡፡ ፓትርያሪኩ ውሣኔ የሚያስተላልፉ ከሆነም በየደረጃው ያሉ ፈፃሚዎች ጉዳዩን የሚከታተሉት ይሆናል፡፡ አሁን ላይ ብዙ መናገሩ ለስህተት ይዳርጋል፡፡ እንዳልኳችሁ የቋሚ ሲኖዶሱ ውሣኔ ይጠበቃል፡፡
ቢያንስ በስልጣን ደረጃ እርስዎ የአዲስ አበባ ሀገረ ስብከት ሊቀጻጳስ ነዎት፡፡ መስቀል ወርዷል ተብሎ ፎቶግራፉ ለሽያጭ ሲቀርብ ዝም ብሎ መመልከቱ ተገቢ ነው? ገንዘቡስ በምን ሞዴል ነው ገቢ የሚሆነው?
ሞዴልማ አድባራቱ ሁሉ አላቸው፡፡ በቤተክርስቲያናችን መመሪያ መሠረት፣ የአንድ አጥቢያ ቤተክርስቲያን ሰበካ ጉባኤ ወሳኝ አካል ነው፤ ቤተክርስቲያኗን ወክሎ ይከሳል፣ ይከሰሳል ውል ይዋዋላል፣ የልማት ስራ ይሰራል፡፡ ስለዚህ ሰበካ ጉባኤው ሙሉ ስልጣን አላቸው፡፡ ስርቆትና ማጭበርበር ተፈፀመ የሚባል ከሆነ አጣሪ አካል ሄዶ ነው ሪፖርቱ የሚመጣው፡፡ ነገር ግን የትኛውም ቤተክርስቲያን በተቀመጠለት የአሰራር መመሪያ ገንዘብ የመሰብሰብ መብት አለው፡፡ ይሄ መስቀልም ሰበካ ጉባኤው ወስኖ ፎቶግራፉ 10 ብር ወይም 5 ብር እየተሸጠ ለህዝቡ ይሰራጭ ብሎ ነው ሊሆን የሚችለው፡፡ በትክክልም በዚህ መል/መ ገቢው ለቤተክርስቲያኑ ከሆነ ህጋዊ አሠራር ነው፡፡
ወረደ የተባለው መስቀል የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን የምትጠቀማቸው የመስቀል አይነት አይደለም የሚሉ አስተያየቶችም እየተሠነዘሩ ነው…
እንግዲህ ስለመስቀሉ አሁን ዝርዝር ነገር መናገር አልችልም፡፡ በእርግጥ ከሠማይ ወርዷል? የማን መስቀል ነው? ከየት የመጣ ነው? የሚለው ከቋሚ ቅዱስ ሲኖዶስ ውሣኔ በኋላ እንገልፃለን፡፡ ውሸት ሆኖ ከተገኘም ሠዎቹ ተጠያቂ ሊሆኑበት ይችላል፡፡
እርስዎ መስቀሉን ከተመለከቱት ይሄ የኦርቶዶክስ ነው አይደለም ለማለት እንዴት ከበድዎት?
እንደነገርኳችሁ የአንድ ሠው አስተያየት ተገቢ አይደለም፡፡
ቅዱስ ሲኖዶሡ መስቀሉን አስቀርቦ ከተመለከተ በኋላ የሚሠጠው ውሣኔ የግድ ነው። ለነገሩ መስቀል መስቀል ነው፤ ይሄ የእገሌ ነው ያ የእኔ ነው የሚባል አይደለም፡፡ እንግዲህ መስቀሉ ላይ የሥነ ስቅለት ምስል አለበት፡፡ ይሄ አሣሣል የኛ የኦርቶዶክሣያውያን አይደለም የሚለውን የሲኖዶሡ ውሣኔ የሚያረጋግጠው ይሆናል፡፡ ሲኖዶሡ ውሣኔ እንሠጣለን እያለ በዋዜማው እኔ ሌላ ነገር ብናገር አግባብ አይሆንም፡፡ ህዝቡንም ያምታታል፡፡
ለህዝቡ የሚያስተላልፉት መመሪያ ካለ?
እንግዲህ ይሄ በኛ ሃገር ብቻ አይደለም የሚፈጠረው፡፡ በግብፅ (ዘይቱና) እመቤታችን ታየች ተብሎ እኔም አይቸዋለሁ፡፡ አሁን በቅርቡ ደግሞ በሩሲያም ሠማይ ላይ ትልቅ መስቀል ተስሎ ታየ ተብሎ በየሚዲያው ሲነገር የሩስያ ቤተክርስቲያን መግለጫ ስትሠጥበት ነበር፡፡ እና ይሄ በኛ ብቻ ሣይሆን በሁሉም ያለ ነውና ህዝቡ እውነታውን ለማወቅ መታገስ አለበት። ሲኖዶሡ መግለጫ ቢሠጥበት እንኳ ሁሉም ህዝብ በእኩል አረዳድ አይረዳውም፡፡ ግማሹ ተአምር ነው ሊል ይችላል፡፡ ሌላው አይደለም ሊል ይችላል። ለማንኛውም ከቅዱስ ሲኖዶሡ ውሣኔ በኋላ በየሚዲያው መግለጫ የሚሠጥበት ይሆናል፡፡ ህዝቡ ሲኖዶሡ ውሣኔ እስኪሠጥበት ድረስ “ይሄ ነው ያ ነው” ሣይል፣ ተረጋግቶ የራሱን ትችትና ውሣኔ ሣይጨምርበት እንዲጠብቅ እንጠይቃለን፡፡
ውሣኔው በቅርቡ በመገናኛ ብዙሃንና በየቤተክርስቲያኑ የሚሠጥ ይሆናል፡፡ እስከዚያው መታገስ ያስፈልጋል፡፡

Saturday, 28 September 2013 13:58

የአዳማ ጉዞ ማስታወሻ!

(ካለፈው የቀጠለ)
“አንኳኩ ይከፈትላችኋል”
ከአዳማ ዕድሮች፣ የእንረዳዳ ዕድሮች ማህበር፣ ሰብሳቢ ከአቶ ታምራት አስፋው ጋር መወያየት ላይ ሳለሁ ነበር ባለፈው ጽሑፌን ያቋረጥኩት። የማህበሩ ሰብሳቢ ባለ ሁለት እርከን ፎቅ በገቢ ምንጭነት ለመሥራት እንዳቀደ፤ የተለያዩና ተያያዥ አካላትን በር እንዳንኳኳ ነገረኝ፡፡
በተለይ ከሃይማኖት ድርጅቶች ጋር በጥብቅ ትስስር እንደተግባቡ አወጋኝ፡፡
“ገብርኤል ቤተክርስቲያን ውስጥ ትልቅ መድረክ ተፈጥሮ ነበር፡፡ ሰባቱ ወንጌሎች ተጋብዘው ሌሎችም ምዕመናን በተገኙበት ትልቅ ጉባዔ አድርገን፣ ከፍተኛ ድጋፍ ተገኘ” አለኝ። “ምን ብላችሁ ተናግራችሁ ነው?” አልኩት። አቶ ታምራት የሚገርም መልስ ነው የሰጠኝ፡፡ “መጽሐፍ ቅዱስ ወላጆቻቸውን ስላጡ ህፃናት ምን ይላል? ህብረተሰቡ ምን ሊያደርግላቸው ይገባል? ምንድነው ግዴታው? ይህንን በተመለከተ አባት መምህራንና ካህናት ለምዕመኑ አስተማሩልን፡፡ የደከሙ አረጋውያንን ስለመርዳት መጽሐፍ ቅዱስ ምን ይላል? ምዕመናንስ ምን ይጠበቅባቸዋል? አስረዱልን አልን፡፡ ትልቅ ትልቅ ትምህርት ሰጡልን” ምዕመናኑ፤ ምን ያህል ይሆናሉ ብዬ ጠየኩት፡፡ “ከ10ሺ በላይ” አለኝ በኩራት፡፡
አሁን ደግሞ እንደዚሁ ከሙስሊሞቹም ጋር ተግባብተናል፡፡ አንድ መድረክ ሊፈጥሩልን ነው፡፡ ከካቶሊኮች፣ ከፕሮቴስታንቶችም እንደዚያው ብቻ፤ አንኳኩ ይከፈትላችኋል ነው ሚስጥሩ፡፡ ለሥራህ ራስህን መስጠት ነው፡፡ አሳታፊ ዓይነት አሠራር ካለ የማይከፈት በር የለም፡፡
ከዚያ ሠሌዳ ላይ ያሉ ፎቶዎች አሳየኝ። “ምንድናቸው?” አልኩት፡፡ “ባለሀብቶች” አለ ኮራ ብሎ፡፡ “አላማችንን ተረድተው በሙያም፣ በገንዘብም፣ በቁሳቁስም ድጋፍ የሰጡን ናቸው። ከብፁዕ አቡነ ጐርጐሪዮስ የምሥራቅ ሸዋ አገረ ስብከት ሊቀጳጳስ ጀምረህ፤ የክሊኒክ ባለቤት በል፣ የሆቴል ባለቤት በል፤ የዩኒቨርሲቲ መምህር/ወጣት (ባለቀይ ክራቫት፣ መምህር የበጐ ፈቃድ አገልጋይ) እነዚህ ሁሉ ህፃናትን በነፃ በማከም፣ በየወሩ ለዕድሜ ልክ የገንዘብ መዋጮ በመስጠት፣ አረጋውያንን በመደገፍና ልጆችን በማሳደግ ስኮላርሺፕ በመስጠት ከፍተኛ ትብብር እያሳዩን ነው፡፡ ሌላውን ተወውና፤ ለህፃናት 25ሺ ለአረጋውያን 25ሺ እና በዓመት ግማሽ ሚሊዮን የሰጠን ሰው አለ፡፡ ያበረታታናል ባለሀብቱ፡፡
“ይቺ በር ማንኳኳት በጣም ጥሩ ናት እ”? አልኩት፡፡
“መጽሐፉ ነዋ ያለው! ለምን እንቆጠባለን፡፡ አለዚያ ትዕዛዝ ማፍረስኮ ነው!”
በኦሮሚያ ሴቶች ጉዳይ ጽ/ቤት በኩል ከአምናው ማስ ስፖርት 326,955.55 ብር አግኝተናል” አለኝ፤ አሁንም በሥራ እርካታ፡፡ ሌላ የተደረደሩ ፎቶዎች አየሁና “እነዚህስ?” አልኩት፡፡ “እነዚህ አረጋውያን ናቸው፡፡ የምንረዳቸው ናቸው፡፡ ቀይ መስቀል ወጣቶችን አስተባብረን ግቢያቸው ይፀዳል፡፡ ልብሳቸው ይታጠባል፡፡ ሲታመሙ እናሳክማቸዋለን፡፡ በዓመት በዓል ቀን ሥጋ ቋጥረን በባጃጅ እንልክላቸዋለን፡፡ ጐረቤት እንዲያጐርሳቸው እናስተባብራለን”፡፡
በምን መረጣችኋቸው? አልኩት፡፡ “መመዘኛ አለና! አምስት መስፈርቶች አሉ” ለአሳዳጊዎች ብድርና ቁጠባ አገልግሎት እንሰጣለን፡፡ ፋይናንሱን በሂሳብ ህግ በባለሙያ ነው የምናስተዳድረው፡፡ ግልጽ አሠራር ነው ያለን፡፡ ካልሆነ ነገ አለመታመን ይመጣና ያ ሁሉ ግርማ ሞገስ ይሟሽሻል፡፡ ዓላማው ሟሸሸ ማለት ነው፡፡ ምስክርነት ካጣን ማህበር የለም ማለት ነው፡፡ ለዚህ ነው እንደድሮ ልጃገረድ የምንጠነቀቀው!!
ቀጥዬ፤ “አሁን እንደእየሩሳሌም የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ያሉት አብረዋችሁ የሚሠሩ ድርጅቶች ቢለዩዋችሁ እንዴት ትቀጥላላችሁ?” አልኩት፡፡ “በጭራሽ አትጠራጠር፤ ራሳችንን ችለናል። ለወጣቱ መዝናኛ ማዕከል ዘርግተናል፤ የባለሁለት ፎቁ ገቢ አለ፣ ዘመናዊ ቀብር ማስፈፀሚያ አቅደናል፣ ፎቶ ኮፒ ማዕከል ልናቋቁም ነው፤ ምኑ ቅጡ! ዘላቂነታችን አስተማማኝ ነው፡፡
ከታምራት ጋር ሻይ ቡና ብለን ተለያየን፡፡
* * *
ቁጥር 5 የቅዱስ ገብርኤል መረዳጃ ዕድር - “ልጅነቴን ያስታወሰኝ ዕድር”
“ካፒታላችን ህዝባችን ነው!”
- የዕድሩ ሰብሳቢ
ናዝሬት (አዳማ) አገሬ ነውና ከእንረዳዳ ማህበር ቀጥዬ ካራመራ ሆቴል ጀርባ ወደሚገኘው ቁጥር 5 የቅዱስ ገብርኤል መረዳጃ እድር አመራሁ፡፡ የናዝሬት ፀሐይ ማቃጠል ጀምሯል፡፡ የጥንት የጠዋት የአዳማ ልጅ ብሆንም አልማረችኝም፡፡ “ከልጅ ልጅ ቢለዩ ዓመትም አይቆዩ” ነው መሰለኝ የናዝሬት ፀሐይ መርህ!
“ነባር ዕድር ይመስላል” አልኩት፤ ለዕድሩ ሰብሳቢ ለአቶ ክፍሌ፡፡
“ይሄ ዕድር እኔ ከቤተሰብ የወረስኩት ነው” አለኝ መካከለኛ ዕድሜ ላይ ያለ የሚመስለው ጠይሙ፤ አጠር ያለው መሪ - አቶ ክፍሌ፡፡ ፀሐፊውና ፕሮጄክት ሃላፊው፤ የሥራ ባልደረቦቹ አጠገቡ አሉ፡፡ “ዕድራችን፤ በኃይለ ሥላሴ ጊዜ የተቋቋመ ነው፡፡ ደርግ ሲመጣ ቤቶቹን ወረሰ፡፡ ከሚከራዩት ቤቶች ማህል እስካሁንም ያልተመለሱ አሉ” አለ ክፍሌ በቁጭት፡፡ ከአዳማ እጅግ ነባር ዕድሮች ውስጥ ምናልባት አንደኛ ነው በሚባለው ቅፅር ግቢ ውስጥ ነው ያለነው፡፡ (62 ዓመት ያህል ሆኖታል፤ 1937 ዓ.ም ስለተመሠተ) ክፍሌ ሲናገር በቁጭት ነው፡፡ “ዕድሩ ቤት ተቸግሯል፡፡ ሌላው ይጠቀምበታል፡፡ ዞሮ ዞሮ እስከደርግ ማብቂያ ድረስ የዕድሩ የልማት ሀሳብ ተቀዛቅዞ ቆየ፡፡ ከ417 በላይ አባላት የነበሩት አንጋፋ ዕድር፤ ግማሹ - አገር እየቀየረ፣ ግማሹ እያረጀ፣ ከፊሉ እየሞተ፤ አሁን ወደ 340 ግድም አባላት አሉት፡፡ በዚህ ዘመን እንግዲህ የልማት አቅጣጫዎች ቀርበዋል፡፡ መንግሥትም ሁኔታዎችን አመቻችቷል፡፡”
“ዕድሩ እንዴት የልማት አቅጣጫ ያዘ?”
“በድሮ ጊዜ የነበረው ባህላዊ የመረዳዳት መንፈስ ብቻ ሳይሆን፣ ለምን ወደ ልማት አንገባም? አልን። ገባን፡፡ መንግሥት በዚሁ ከተማ 680 ካ.ሜ ቦታ ሰጠን፡፡ ባለ 4 ፎቅ ት/ቤት ሠርተን-ሥራ ጀምሯል፡፡ አቅጣጫው፤ ላይ ወደ መድሐኒዓለም ነው!”
“በምን ገንዘብ ነው የምትንቀሳቀሱት?” አልኩት።
“የህብረተሰቡን መዋጮ በመጠቀም ነው። ይሄ ህ/ሰብ ሁሉን ያሟላል፡፡ በቂ ደሀ አለው፡፡ መካከለኛና ከፍተኛ ሀብታም አለው፡፡ በዕውቀትም ከመጨረሻ ወለል እስከ ላይ ድረስ አለው፡፡ በጋራ ይሠራሉ። ለምሣሌ ምህንድስናውን የያዙልን አባላት አሉን። በጎ-ፈቃደኞች ማለቴ ነው። የሚገርምህ ቦታውን ስንጠይቅ የተጠየቅነውን ጥያቄ ነው ያነሳህልኝ-“በምን ገንዘብ ትሠሩታላችሁ? ካፒታላችሁን አሳዩን?” አሉን፡፡ ካፒታላችን ህዝባችን ነው፣ ነበር ያልናቸው፡፡ ዕውቀት ያለው፣ ገንዘብ ያለው ህዝብ አለን! በሃሳቡ ተስማሙ፡፡ በደስታ ሰጡን። ት/ቤቱ ዛሬ በወር 17ሺ ብር ያስገባል፡፡ በዚህ አላቆምንም። በየጎዳናው ላይ የሚወድቀውን፣ ረዳት ያጣውን፣ ከኑሮ ወለል በታች የወደቀ ድሀ እንርዳ ብለን ተነሳን፡፡ ያን ጊዜ እየሩሣሌም ህፃናትና ማ/ሰብ ልማት ድርጅት እንዲህ ያለ የተቀደሰ ተግባር የሚያካሂዱ ዕድሮችን ያፈላልግ ስለነበር፤ እኛን ያገኘናል፡፡ ሁሉንም ጠይቆን ፕሮጀክታችንንና ዓላማችንን ከተረዳ በኋላ፤ በገንዘብ ሊደግፈን ፈለገ፡፡ ርዳታ ሰጠን፡፡ እኛም በሚገባ ተግባራዊ አደረግን፡፡ ወላጆቻቸውን ላጡ ህፃናት ድጋፍ ሰጠን፡፡ ለአሳዳጊዎቹ የብድርና ቁጠባ አገልግሎት ሰጠን፡፡ አደጉና ራሳቸውን ቻሉበት፡፡ ለህፃናት የት/ቤት ቁሳቁስ ከላጲስ እስከ ዩኒፎርም ልብስ፣ ቦርሳ፣ መደበኛ ልብስ፣ ጫማ ስናደርስ ቆየን፡፡ ይሄ አንደኛው ፌዝ (Phase) ነበር፡፡ ቀጠልን፡፡ በሁለት፣ ሦስት መርሀግብር ተራ (Phase) 200 ህፃናትንም በትምርት አቅርቦት በኩል ምንም ሳይጐልባቸው እንዲማሩ ወላጆቻቸውና አሳዳጊዎቻቸው ራሳቸውን እንዲለውጡና ራሳቸውን እንዲችሉ ብድር ሰጥተን አጠነከርናቸው፡፡ ህፃናት፤ ከህክምና ማዕከል ጋር እየተነጋገርን እንዲታከሙ አድርገናል፡፡
(ሌሎቹ የዕድሩ አባላት የሰጡት አንኳር አንኳር አስተያየት በሚቀጥለው ሣምንት ከደብረ ዘይትና ከአዋሳ ጉዞ ማስታወሻዬ ጋር ይቀርባል!)
(ይቀጥላል)

Saturday, 28 September 2013 13:28

ዴንጌሣት

ዴንጌሣት - የልጅ እሳት
ዴንጌሣት - የልጅ መብራት…
የባህል ችቦ መቀነት
ከዘመን ዘመን ማብሰሪያ፣የመስቀል ብርሃን “ኬር” በሥራት፡፡
“በእሳት አትጫወት” ይላል አበሻ ልጁን ሲያሳድግ
ዴንጌሣትን ባያውቀው ነው፤ የጉራጌን ባህልና ወግ
ገና በጥንስስ በጭሱ፣ መስቀልን እንደሚታደግ
በችቦ ማህል ተወልዶ፣ ንግዱን እንደሚያንቦገቡግ
በእሳት አልፎ እሳት ሲሆን
አላየውም ጉራጌውን
ዴንጌሣት ነው የዚህ እርከን!
ጉራጌ የላቡን ሠርቶ
ዓመቱን በንግዱ ገፍቶ
በፍቅሩ ልጆቹን አይቶ
የለማው በፊናው ለፍቶ
የተገፋውም ተገፍቶ፤
ላንደኛው አዱኛ በርቶ
ያንዱ መክሊቱ ከስቶ
ያም ሆኖ በቀኑ ተግቶ
መስቀሉን በዕድሜው አብርቶ
የልጅ - እሳት፣ የዴንጋ - እሳት፤ ለምለም ጨረር ይዞ መጥቶ
ይሄው በመስቀል ወር ጥቢ፣ ኬር! ይላል የዓመቱን ንጋት
ኬር! ይላል የዓመቱን ብሥራት
ፍሬው በስሎ፣ ቅርሱ ሲያብብ፤ ማየት ነው ያገሬው ኩራት
ዴንጌሣት የልጆች ምትሃት
ጐርፍ ላይ የሚሄድ እሳት
ዓመቱን እንደብጤቱ፣ ሰው መቼም አቅሙን ለክቶ
እንደየርምጃው ነውና፣ የሚሄድ ብርሃን አይቶ
እንደዘመን እንደ ዓመሉ…ነግዶም አርሶም አምርቶ
ወይ ጀግኖ አሊያም ፈርቶ
ወይ ሸሽቶ ወይ ዝቶ ኮርቶ
ወይ ተኮራርፎ ወይ ታርቆ
ወይ ከስሮ ወይ አንሰራርቶ
አትርፎ ወይ “ፓሪ” ወጥቶ
በጋን እንደበጋ ፀሐይ፣ ክረምትን እንደዶፍ ዝናብ
ሁሉን ችሎ ሁሉን አዝሎ፣ ሁሉን የንግድ አጀብ ወጀብ
ተቀብሎ ታግሎ፣ ጥሎ፤
አቀርቅሮ ቀና ብሎ
የተስፋ ጐሁን በችቦ፣ ቀዶ በዴንጌሣት ፍካት
በዝናብ ውጋገን እሳት
የመስቀል ደመራ ዜማ
ያውዳመት ሆታ ዋዜማ
የልጆች ርችት ማማ
አገር ሲታጠር በአበባ
የኮከቦች ሳቅ ሲተባ
የማይሞት የማይነቀል
ኗሪ የጉራጌ ባህል፤
እንደህፃን ፍልቅልቅ ፊት፣ እነደመስክ ብርሃን ወለል፤
መስከረም ወር ፍንትው ሲል፣
ገጠር ከተማውን ዳብሶ፣ ዴንጌሣት ዙሪያ ይሞላል!
ዴንጌሣት የፍቅር እሳት
የልጅ መቅሰስ ያዋቂ እራት
ነግ እንዲያበራ ይህ ልማድ፣ መስቀል - ወፍ እንድትዘምረው
ምራቅ የዋጥን፣ ልማድ ያቀፍን፤
አሻግረን እንለኩሰው
ለአገር ልጅ እናስረክበው
ጐዶሏችንን እንሰብስብ፣ ሙሉማ አለ በጃችን
ዘለዓለምን ለማሸነፍ፣ ብርሃን ነው መሣሪያዎችን !
ሁሌም ዴንጌሣት ለማየት፣ አሁን ያለን እንበቃለን፡፡
ይህን የልጆች ህብር እሳት፣ እጅ በእጅ እንለኩሰው
ወትሮም በእፍኝ ጭራሮ ነው፣ አገር - ምድሩ የሚበራው
ባህል የሚኖር እንዲህ ነው፣ ትውልድ የሚጫር በዚህ ነው!
አገር ማለት ዴንጌሣት ነው!
ኬር እንሁን ኬር እናርገው!
የጉራጌ ብርሃን ህልም፣ እዚህ ጋ ነው ትርጉም ያለው፡፡
ዴንጌሣት የልጅ አገር ነው፤
አገር ማለት ዴንጌሣት ነው፡፡
መስከረም 14/2006
(ለዴንጌሣት በዓልና ባህሉን ለሚያከብሩ)

 

ላለፉት 12 ዓመታት ኢትዮጵያን በርዕሰ ብሔርነት የመሩትና በሚቀጥለው ሳምንት ስልጣን የሚያሥረክቡት ፕሬዚዳንት ግርማ ወልደጊዮርጊስን የሚዘክር የፎቶግራፍ አውደርእይ ባለፈው ረቡዕ በኢትዮጵያ ብሔራዊ ትያትር ቀረበ፡፡ አውደርዕዩ ፕሬዚዳንቱ በስልጣን ላይ ሳሉ ያከናወኗቸውን ተግባራት እንደሚያስቃኝ “ታሪኳ ኤቨንት ኦርጋናይዘር” አስታውቋል፡፡

የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስትያን የቅርስ ጥበቃና የቤተመጻሕፍት ወመዘክርና ቱሪዝም መምርያ፤ በፌደራል ፖሊስ ኮሚሽን ሊወገዱ የነበሩ ሦስት ጥንታዊ የብራና መጻሕፍትን ተረከበ፡፡ እንደ መምሪያው ገለፃ፤ ከቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ጊዜ ጀምሮ በቬርባል ሲገላበጡ ቆይተው ለመወገድ በዝግጅት ላይ የነበሩት የብራና መፃሕፍት የተገኙት በፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽን አባል ጥቆማ ነው፡፡ መጻሕፍቱ በፖሊስ ኮሚሽን ግምጃ ቤት እንደሚገኙ በጠቆሙን መሰረት ተጻጽፈን ባለፈው ሰኞ መጻሕፍቱን ተረክበናል ብለዋል - የመምርያው ሃላፊ መምህር ሰለሞን ቶልቻ፡፡ የተገኙት የብራና መጽሐፍት እያንዳንዳቸው ከ200 ገጽ በላይ ሲሆኑ፤ መፃሕፍቶቹም ድርሳነ ኡራኤል፣ ድርሳነ ማህየዊ እና ድርሳነ ሚካኤል ናቸው፡፡ መምርያቸው ተመሳሳይ ሥራዎችን እየሰራ መሆኑን ሃላፊው ገልፀዋል፡፡