Administrator

Administrator

              ፈረንሳይ ከሌላው ሀገር የተለየ ቅርስ ወይም የተፈጥሮ መስሕብ የላትም፡፡ ነገር ግን ከሕዝብ ቁጥሯ በሚሊዮኖች የላቀ ቱሪስት በየዓመቱ ይጎበኛታል፡፡ ጎረቤቷ ጣሊያን ከፈረንሳይ በቁጥር የበለጡ ዓለምአቀፍ ቅርሶች ብታስመዘግብም እንደ ፈረንሳይ አልጎረፈላትም፡፡
ኢትዮጵያም ዓለም አቀፍ ቅርስ በማስመዝገብ ከአፍሪካ አንደኛ ናት - ዘጠኝ ቅርሶች በማስመዝገብ። ስምንት ስምንት ቅርሶች በማስመዝገብ የሚከተሏት ደቡብ አፍሪካ፣ ቱኒዚያ እና ሞሮኮ ናቸው። ጎረቤት ኬንያ ደግሞ አራት ቅርሶች ብቻ ነው ያስመዘገበችው፡፡
እ.ኤ.አ በ2007 ይፋ የተደረገውን ሃምሳ ምርጥ የዓለማችን ቱሪስት መዳረሻ ሀገሮች ዝርዝርን ስንመለከት ከአፍሪካ ግብጽ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ሞሮኮና ቱኒዚያ ነበሩ የተካተቱት፡፡ ግብፅ 8.6 ሚሊዮን ቱሪስቶች ስታስመዘግብ ቱኒዝያ 6.5 ሚሊዮን አስመዝግባለች፡፡ በእርግጥ ባለፉት ሦስት አመታት ከተከሰተው የአረብ አብዮት ጋር ተያይዞ የቱሪስቶች ቁጥር ማሽቆልቆሉ አልቀረም፡፡

አገራቱ ሲረጋጉ ግን እንደገና ቁጥሩ አድጓል፡፡ በኢትዮጵያ ደግሞ በ2002 ዓ.ም የተመዘገበው የቱሪስት ቁጥር ግማሽ ሚሊዮን እንኳን አልደረሰም - 468,365 ነው፡፡ የባሕልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ከስድስት ዓመት በኋላ በ2012 ዓ.ም ኢትዮጵያን ከአፍሪካ አምስት ምርጥ የቱሪስት መዳረሻ ሀገራት አንዷ ለማድረግ አቅዷል፡፡ ሆኖም እቅዱ ከእነቱኒዝያ፣ ታንዛንያ እና ኬንያ አንጻር ሲታይ ገና እጅግ በጣም ብዙ ይቀረዋል፡፡
በሌላ በኩል መንግስት ተጨማሪ ሰባት ቅርሶች በዩኔስኮ ለማስመዝገብ በእንቅስቃሴ ላይ ነው፡፡ ከቅርሶቹም መካከል የመስቀል በአል እና ባሕረሐሳብ የተሰኘው የኢትዮጵያ የዘመን አቆጣጠር ይገኙበታል፡፡ የሰሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ በደን ምንጠራና በሌላ የሰዎች ተጽዕኖ ከዓለም ቅርስነት የመፋቅ አደጋ አንዣቦበት እንደነበር ይታወቃል፡፡ ፓርኩን የመከለል እንቅስቃሴ በመጀመሩ ነው ከመሰረዝ የዳነው፡፡
የቱሪዝም ኢንዱስትሪውን ለማስፋፋት መንግሥት ከ2001 ዓ.ም ጀምሮ አምስት ክፍሎች ያሉት ብሔራዊ የቱሪዝም ልማት ፖሊሲ አዘጋጅቷል፡፡ የፖሊሲው ክፍል ሦስት፣ ቁጥር አራት “በዓለም አቀፍ የቱሪዝም ገበያ ፉክክር ውስጥ ብቁ ተወዳዳሪ ለመሆን የማስተዋወቅ ሥራን በመሥራት ጠንካራ የገበያ ትሥሥር” መፍጠር ወሳኝ መሆኑን ያወሳል፡፡

ተገቢ የፕሮሞሽን ሥራዎችን መስራት አስፈላጊ እንደሆነ ይጠቁማል - ፖሊሲው። በዚህም መሠረት የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር፤ ዓለም አቀፍ ዐውደርእዮችን እንደ ዋነኛ የቅስቀሳ ዘዴ እየተጠቀመባቸው ይገኛል፡፡ ሚኒስቴር መ/ቤቱ ሥራዬ ብሎ በዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ቅርሶችንም ሆነ የተፈጥሮ መስህቦችን ሲያስተዋውቅ አይታይም፡፡ መገናኛ ብዙሃኑ በራሳቸው ጊዜ መጥተው ስለ ቅርሶቹና መስሕቦቹ ከሚዘግቡት በቀር በዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ለምን መስህቦችን አታስተዋውቁም በሚል የተጠየቁት በሚኒስቴሩ የሕዝብ እና ዓለም አቀፍ ግንኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አወቀ ጤናው፤ “በዚህ መልኩ አናስተዋውቅም፡፡ ከዚያ ይልቅ በምናተኩርባቸው ሀገራት ያሉ ታዋቂ ፀሐፍትንና ሌሎች ተጽዕኖ ፈጣሪ ሰዎችን በመጋበዝ ስለ ኢትዮጵያ ቅርሶችና መስሕቦች እንዲጽፉ፣ እንዲናገሩ እናደርጋለን፡፡ በዓለም አቀፍ ዐውደርእዮች በመሳተፍም ሀገራችንን ይበልጥ እናስተዋውቃለን” ሲሉ መልሰዋል፡፡
በቱሪዝም ዘርፉ እንደ ድክመት ከሚጠቀሱ ጉዳዮች አንዱ በዘርፉ የሰለጠኑና የተካኑ ባለሙያዎች በበቂ ሁኔታ አለመኖር ነው፡፡ አቶ አወቀ በበኩላቸው፤ ሲቪል ሰርቪስ ሚኒስቴር በዘርፉ ብቃት ያላቸው ባለሙያዎችን መድቦ እየሰሩ መሆናቸውን ይናገራሉ፡፡
አቶ አብዱ ከድር በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ ለማስትሬት ዲግሪ ማሟያቸው እ.ኤ.አ በ2013 “Tourist Destination competitiveness of Ethiopia; The Tour operators perspective” በሚል ርእስ ባቀረቡት ጥናት ማጠቃለያ ላይ፤ “ኢትዮጵያ በዓለም አቀፍ የቱሪዝም ዐውደርእይ ላይ ስትሳተፍ ከፖለቲከኞች ይልቅ ገበያ ሊያመጡ በሚችሉ የዘርፉ ባለሙያዎች ብትወክል ይበጃታል” ብለዋል፡፡ መካከለኛው ምስራቅ በተለይም የዓረቡ ዓለም የተዘነጋ የኢትዮጵያ የቱሪዝም ገበያ ክልል እንደሆነም በጥናታቸው ጠቁመዋል፡፡ ሚኒስቴሩ አምና ባሳተመው መጽሔት ላይ ኢትዮጵያን ከሚጐበኙ ዓለም አቀፍ ቱሪስቶች ውስጥ 51.2 በመቶ የሚሆኑት የአሜሪካ፣ ቻይና፣ እንግሊዝ፣ ጀርመን፣ ኬንያ፣ ጣሊያን፣ ሳኡዲ አረቢያ፣ ሕንድና ፊንላንድ ዜጐች መሆናቸውን ያመለክታል፡፡
ችግሩ ግን እነዚህ ቱሪስቶች በሚጎበኟቸው ስፍራዎች አብዛኛውን ጊዜ የሚቀበሏቸው አስጐብኝዎች በቂ እውቀትና ልምድ የሌላቸው ከማስጎብኘት ይልቅ ከማገት የሚስተካከል ሚና የሚጫወቱ ወጣቶች እንደሆኑ ጥናቶች ያሳያሉ። በዚህም የተነሳ በዓመት ግማሽ ሚሊዮን እንኳን ያልደረሱት የኢትዮጵያ ጎብኚዎች በአገሪቱ ውስጥ ያላቸው ቆይታ በጣም ውሱን ነው፡፡ እስራኤል በቱሪስት ብዛት ቀዳሚ ከሆኑትን ፈረንሳይ እና አሜሪካ ጋር ልትወዳደር አትችልም፡፡ ነገር ግን የቆይታ ጊዜአቸውን በማራዘም ከቱሪዝም ዳጎስ ያለ ገቢ እንደምታገኝ መረጃዎች ይጠቁማሉ። አንዲት ትንሽዬ የእስራኤል ከተማን በቅጡ ጐብኝቶ ለመጨረስ ቀናት እንደሚፈጅ ይነገራል። ኢትዮጵያም የእስራኤልን ፈለግ የመከተል ብርቱ ጥረት ልታደርግ ይገባል፡፡ ለዚህ ደግሞ ደረጃቸውን የጠበቁ ሆቴሎችና መንገዶችን በስፋት በመገንባት የጉብኝት ስፍራዎችን ለማብዛት መትጋትን ይጠይቃል፡፡
ከዚሁ ጐን ለጐን የኢንተርኔት አገልግሎቶችን በተለይ የቱሪዝም መስህብ በሆኑ ስፍራዎች ማስፋፋት ብቻ ሳይሆን ፈጣንና ቀልጣፋ ማድረግም የግድ ነው፡፡ ባለፈው ሰኔ ወር መጨረሻ፣ የኮንሶ አካባቢ ዓለም አቀፍ መካነ ቅርስ የሆነበት አንደኛ ዓመት ሲከበር፣ በርካታ የውጭ ሀገር ጎብኚዎች የኢንተርኔት አገልግሎት ለማግኘት አርባምንጭ ድረስ ለመጓዝ መገደዳቸውን ታዝቤአለሁ፡፡
በቂ የቱሪዝም እውቀትና ልምድ የሌላቸው አስጐብኝዎች፣ መስተንግዶአቸው እንደነገሩ የሆኑ ሆቴሎች፣ ደካማና ፈዛዛ እንቅስቃሴ ይዘን ከአፍሪካ ምርጥ አምስት የቱሪዝም መዳረሻ አገራት አንዱ ለመሆን ማሰብ ከህልምነት አያልፍም፡፡
የቱሪዝም ኢንዱስትሪው በአንድ ወገን ጥረትና ትጋት የታሰበበት ደረጃ ላይ ሊደርስ አይችልም። ከግሉም ሆነ ከመንግሥት ዘርፍ የለያዩ ወገኖች ተዋናይ የሆኑበት ሰፊ ክፍለ ኢኮኖሚ በመሆኑ የተቀናጀ የጋራ ስራን ይፈልጋል፡፡ ከልብ መትጋትን ይጠይቃል፡፡ ያኔ የታቀደውም ሆነ የታለመው ሊሳካ ይችላል፡፡ በተለይ ደግሞ ራሳችንን በማስተዋወቁና በመሸጡ በኩል እጅግ ብዙ የቤት ሥራ እንዳለብን ማወቁ ተገቢ ነው፡፡

የውጭ ንግድ ፈቅ አላለም፤ ባለበት ደንዝዞ ቆሟል - የንግድ ሚኒስቴር መረጃ።
የግል ኢንቨስትመንት ተዳክሟል፤ ድርሻው በግማሽ ቀንሷል - የIMF መረጃ።
የአገሪቱ የባንክ ብድር፣ 90% ወደ መንግስት ይሄዳል - የአለም ባንክ ሪፖርት።
“ትልልቅ ፕሮጀክቶች በውጭ ምንዛሬ እጥረት እየተቀየዱ የሚሄዱበት እድል ሰፊ ነው” … የኤክስፖርት ገቢ መዳከሙን በመግለፅ ይህን የተናገሩት የንግድ ሚኒስቴር ሃላፊዎች ናቸው። ያሳስባል፣ እውነታቸውን ነው። ነገር ግን፣ ትልቁና አሳሳቢው ነገር፣ የመንግስት ፕሮጀክቶች መስተጓጎላቸው አይደለም። የውጭ ንግድ መዳከም፣ ጠቅላላ በአገር ኢኮኖሚና በዜጎች ኑሮ ላይ ተጨማሪ ችግር እንደተደቀነ የሚጠቁም ምልክት ነው። ደግሞስ፣ የመንግስት ገናናነት እየገዘፈ፣ የግል ኢንቨስትመንት እየቀጨጨ፣ እንዴት ጥሩ ውጤት ይገኛል ብሎ መጠበቅ ይቻላል?
አሳዛኙ ነገር፣ መንግስት ራሱን በራሱ ጠልፎ እየጣለ መሆኑን አለመገንዘቡ ነው። መንግስት “የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድ” ውስጥ የዘረዘራቸውን ትልልቅ ፕሮጀክቶች ለማሳካት ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ያስፈልገዋል። ግን ምን ዋጋ አለው? ዋነኛ የውጭ ምንዛሬ ምንጭ የሆነው የግል ኢንቨስትመንት እየቀጨጨ የመጣው፣ “በእድገትና ትራንፎርሜሽን እቅድ” ሳቢያ ነው። ተግባራዊ የተደረጉ የመንግስት እቅዶች፣ የኤክስፖርት ገበያውንና የውጭ ምንዛሬ ምንጮችን እንዴት እየጎዱ እንደሆነ ለማሳየት እሞክራለሁ።
በእርግጥ፣ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለማሪያም ደሳለኝ ከጋዜጠኞች ለቀረበላቸው ጥያቄ በሰጡት ምላሽ፣ በውጭ ምንዛሬ እጥረት ሳቢያ የሚስተጓጎል ፕሮጀክት የለም ብለዋል። የሕዳሴ ግድብ ግንባታ በጭራሽ አይጓተትም ያሉት ጠ/ሚ ኃይለማሪያም፣ ሌሎቹ ትልልቅ ፕሮጀክቶች ደግሞ በውጭ ብድር የሚካሄዱ በመሆናቸው የውጭ ምንዛሬ እጥረት እንደማያሳስብ ለመግለፅ ሞክረዋል።
እንዲያም ሆኖ፣ ከኤክስፖርት የሚገኘው ገቢ የታሰበውን ያህል እንዳልተሳካ አልካዱም። ቢሆንም፣ ይህንን ጉድለት የሚሸፍን ነገር ተገኝቷል። ከተለያዩ ምንጮች ወደ ኢትዮጵያ የተላከው የውጭ ምንዛሬ ከተጠበቀው በላይ ሆኗልና። ለነገሩ፣ በየአገሩ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን በየአመቱ የሚልኩት ገንዘብ ቀላል አይደለም። በአመት ከ3 ቢሊዮን ዶላር በላይ እየላኩ ነው። ከኤክስፖርት ከሚገኘው ዶላር ይልቅ፣ ከዳያስፖራ የሚመጣው በልጧል። በውጭ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ለቤተሰብና ለዘመድ የሚልኩት ገንዘብ መጨመሩ ጥሩ ነው። ነገር ግን፣ የኤክስፖርትን ጉድለት ይሸፍናል በሚል የሚያፅናና አይደለም - በእጅጉ የሚያሳስብ እንጂ።
ከሳምንት በፊት ጠ/ሚ ኃይለማሪያም፣ በውጭ ምንዛሬ እጥረት የመንግስት ፕሮጀክቶች እንደማይስተጓጎሉ ቢገልፁም፤ ከምር ሳያሳስባቸው የቀረ አይመስለኝም። በዚያው ሳምንት የንግድ ሚኒስቴር ሃላፊዎች ከክልል መስተዳድር ተወካዮች ጋር ተሰብስበው የተነጋገሩበት ዋና ርዕሰ ጉዳይ፣ በውጭ ምንዛሬ እጥረት ነው። ወደ ውጭ የሚላኩ የእርሻና የፋብሪካ ምርቶች፣ በጥራትና በብዛት እየቀረቡ አይደለም በማለት የተናገሩት የንግድ ሚኒስቴር ሃላፊዎች፣ “ትልልቅ ፕሮጀክቶች በውጭ ምንዛሬ እጥረት እየተቀየዱ የሚሄዱበት እድል ሰፊ ነው” በማለት አሳሳቢነቱን ገልፀዋል።
ከአመት አመት የኤክስፖርት እድገት እየተዳከመ መምጣቱን የሚክድ ይኖራል ብዬ አልገምትም። አሁን ደግሞ፣ ከነጭራሹ ቅንጣት እድገት አልታየም። እንዲያውም የኤክስፖርት ገቢ ቀንሷል። በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ውስጥ ከተዘረዘሩት “ግቦች” ጋር ሲነፃፀርማ፣ በእጅጉ ወደኋላ ቀርቷል። የእቅዱ ግማሽ ያህል እንኳ አልተሳካም።
በእቅዱ የመጀመሪያ ዓመት በ2003 ዓ.ም፣ ሁለት ቢሊዮን ዶላር የነበረውን የኤክስፖርት ገቢ በአንድ ቢሊዮን ዶላር ለማሳደግ (3 ቢሊዮን ዶላር ለማድረስ) ቢታሰብም፣ የእቅዱ 75 በመቶ ብቻ ነው የተሳካው። ቀላል እድገት ነው ማለቴ አይደለም። 2.75 ቢሊዮን ደርሷል። በቀጣዩ ዓመት ግን፣ እድገቱ ተዳክሟል። በ“ኦሪጅናሉ” እቅድ መሰረት፣ የኤክስፖርት ገቢ በ2004 ዓ.ም ወደ አራት ቢሊዮን ዶለር የሚጠጋ ይሆናል ተብሎ ነበር የታሰበው። በተግባር የተገኘው ገቢ ግን 3.15 ቢ. ዶላር ነው። ከመነሻው አመት ጋር ሲነፃፀር በሁለት ቢሊዮን ዶላር የሚበልጥ ገቢ ለማግኘት ቢታቀድም፣ በተግባር የተገኘው እድገት 1.2 ዶላር ገደማ ነው። እናም እቅዱ 60 በመቶ ብቻ ነው የተሳካው ማለት ይቻላል።
አሁንም ኦሪጅናሉን እቅድ ካስታወስን፣ በ2005 ዓ.ም ከአምስት ቢሊዮን ዶላር በላይ የኤክስፖርት ገቢ ለማግኘት ታስቦ እንደነበር እናያለን። በተግባር የተገኘው ውጤት ደግሞ 3.1 ቢሊዮን ዶላር ብቻ ነው። የአመት አመት እድገቱ ተዳክሞ ከመቆሙም በላይ፣ የኋሊት መንሸራተት ጀምሯል። በ2002 ዓ.ም ከነበረው መነሻ አሃዝ ጋር ስናነፃፅረው፣ በሦስት ቢሊዮን ዶላር የላቀ እንዲሆን ታቅዶ የነበረ ቢሆንም፣ 1.1 ቢሊዮን ዶላር ያህል ብቻ ነው የተሳካው። የእቅዱ 37% ብቻ ማለት ነው። ከአመት አመት የስኬቱ መጠን እየቀነሰ መሆኑን የምታስተውሉ ይመስለኛል።
ዘንድሮም የኤክስፖርት ገቢ ከሰባት ቢሊዮን ዶላር የሚበልጥ ይሆናል ተብሎ በእድገትና ትራንስፎርሜሽ እቅዱ ውስጥ ተጠቅሷል። ሃሙስ እለት የወጣው የአይኤምኤፍ መግለጫ እንደሚያመለክተው ግን፣ የኤክስፖርት ገቢው 3.6 ቢሊዮን ዶላር ገደማ ይሆናል ተብሎ ነው የሚጠበቀው።
እንግዲህ አስቡት፤ የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅዱ ላይ የሰፈረው፣ በ2002 ዓ.ም ሁለት ቢሊዮን ዶላር የነበረውን የኤክስፖርት ገቢ፣ በ2006 ዓ.ም በአምስት ቢሊዮን ዶላር ይጨምራል የሚል እቅድ ነው። በእውን ይታያል ተብሎ የሚጠበቀው ጭማሪ ግን 1.5 ቢሊዮን ዶላር ብቻ ነው። የእቅዱ 33% ብቻ መሆኑ ነው።
የእቅዱ ስኬት ከአመት አመት እየቀነሰና እየተሸረሸረ የመጣው አለምክንያት አይደለም። የእቅዱ መዘዝ ከአመት አመት እየጨመረና እየተደራረበ ስመጣ ነው። ‘መዘዝ’ ስል፣ ያልታሰበና ያልተጠበቀ መመዝ ማለቴ አይደለም። በደንብ ታስቦበታል። ከዚያም አልፎ፣ የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድ ላይ በይፋ ተዘርዝሯል። በአምስት አመታት ውስጥ በአገሪቱ ከሚካሄዱ የኢንቨስትመንት ስራዎች ውስጥ 67 በመቶ ያህሉ በመንግስት ፕሮጀክቶች፣ 33 በመቶ ያህሉ ደግሞ በግል ኢንቨስትመንት እንደሚሸፈን በ“እቅዱ” ውስጥ ተጠቅሷል። በሌላ አነጋገር፣ የመንግስት ፕሮጀክቶች፣ ከግል ኢንቨስትመንቶች በእጥፍ እንዲበልጡ ነው የታቀደው።
ድሮ እንደዚያ አልነበረም። ኢህአዴግ ስልጣን በያዘባቸው የመጀመሪያ አመታት፣ ከመንግስት ፕሮጀክቶች ይልቅ የግል ኢንቨስትመንት ድርሻ ይበልጥ ነበር - (የግል ኢንቨስትመንት 70 በመቶ የመንግስት ደግሞ 30 በመቶ)። መንግስት የነፃ ገበያ ኢኮኖሚን እገነባለሁ ቢልም፣ ቀስ በቀስ የግል ኢንቨስትመንት ድርሻ እየቀነሰ፣ በተቃራኒው የመንግስት ፕሮጀክቶች ድርሻ እየጨመረ መጥቷል። የዛሬ አስር አመት ገደማ ነው፣ የሁለቱ ድርሻ እኩል የሆነው (ሃምሳ በመቶ - ሃምሳ በመቶ)። የዚህን ጊዜም ነው፣ በመላው ዓለም ወደ ሶሻሊዝም ያዘነበሉ ናቸው ከሚባሉ አምሳ አገራት መካከል አንዷ ኢትዮጵያ መሆኗ የተገለፀው።
የቁልቁለት ጉዞው ግን በዚሁ አላቆመም። አይኤምኤፍ ሀሙስ እለት ባሰራጨው ዘገባ እንደገለፀው፣ የግል ኢንቨስትመንት ድርሻ ወደ 25 በመቶ እንደወረደና የመንግስት ፕሮጀክቶች ድርሻ 75 በመቶ እንደደረሰ ይገልፃል። በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ውስጥ ከተጠቀሰውም በላይ የከፋ መሆኑን ተመልከቱ። እንዲህ አይነት የመንግስት ገናናነት፣ በብዙ አገራት ውስጥ የለም። በእጅጉ ሶሻሊስታዊ የኢኮኖሚ አካሄድን ከሚከተሉ ሶስት የዓለማችን አገራት መካከል አንዷ ኢትዮጵያ ሆናለች የተባለውም በዚህ ምክንያት ነው። ነፃ ገበያ እንዲህ ነው እንዴ?
የመንግስት ፕሮጀክቶች ድርሻ እያበጠ፣ የግል ኢንቨስትመንት ድርሻ እየተደፈጠጠና እየቀጨጨ የመጣው፣ በተለያዩ ምክንያቶች ቢሆንም፣ ትልቁና ዋናው ሰበብ ግን ከባንክ ብድር ጋር የተያያዘ ነው። የባንክ ብድሮች ከአመት አመት ከግል ኢንቨስትመንት እየራቁ ወደ መንግስት ፕሮጀክቶች እንዲጎርፉ ተደርጓል። ከ20 አመታት በፊት፣ ከግማሽ በላይ የባንክ ብድሮች ለግል ኢንቨስትመንትና ለግል ቢዝነሶች የሚውሉ ነበሩ።
ግን ብዙም ሳይቆይ የባንክ ብድር አቅጣጫው ተቀይሮ፣ ወደ መንግስት ድርጅቶችና ፕሮጀክቶች መጉረፍ ጀመረ። በ2003 ዓ.ም፣ ከባንኮች አዲስ ብድር ውስጥ 70 በመቶ ያህሉ ለመንግስት ድርጅቶችና ፕሮጀክቶች እንደተሰጠ የሚገልፀው የአለም ባንክ ሪፖርት፣ ከዚያ ወዲህ ባሉ አመታትም የግል ድርጅቶች የሚያገኙት ብድር ይበልጥ እየቀነሰ እንደመጣ ያትታል። አሁን፣ ከባንኮች ብድር ውስጥ 90 በመቶ ያህሉን የሚወስዱት የመንግስት ድርጅቶችና ፕሮጀክቶች ናቸው። State Owned Enterprises are increasingly absorbing domestic banking sector credit. In the six-month period from June 2011 to December 2011, 71 percent of new loans were directed towards public enterprises. This share increased to 89 percent during the second half of 2012. A substantial share of the available foreign exchange is similarly diverted towards public investment. (የአለም ባንክ ሪፖርት Ethiopia Economic Update II፡ Laying the Foundation for Achieving Middle Income Status፡ June 2013 … ገፅ 24)
በዚህ መልኩ፣ ለግል ኢንቨስትመንት የሚውል የባንክ ብድር እየተንጠፈጠፈ፣ የግል ኢንቨስትመንት እየቀጨጨ ሲሄድ፣ የውጭ ምንዛሬ ገቢ እየቀነሰ መምጣቱን ምኑ ይገርማል? ከሞላ ጎደል በሸቀጦች ኤክስፖርት የሚገኘው ገቢ፣ በግል ድርጅቶችና ኢንቨስትመንቶች አማካኝነት የሚመጣ ነዋ። ታዲያ፣ መንግስት ራሱን በራሱ ጠልፎ አልጣለም ትላላችሁ? በእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድ ውስጥ የተዘረዘሩትን ትልልቅ ፕሮጀክቶች ለማከናወን ከፍተኛ የውጭ ምንዛሬ ያስፈልገዋል። ነገር ግን፣ “እቅዱ” ራሱ፣ የውጭ ምንዛሬ ምንጭ የሆኑ የግል ኢንቨስትመንቶችን የሚደፈጥጥና የሚያቀጭጭ ነው።

 

ዓለም አቀፍ ጉባኤው፤ ሲኖዶሱ የመንፈሳዊ ኮሌጁን ችግር እንዲፈታ አሳሰበ
የክልል መንግሥታት የወረዳ ባለሥልጣናት÷ የቤተ ክርስቲያን ሕንፃ እንዳይታነፅ፣ የመካነ መቃብር፣ የልማትና ማኅበራዊ አገልግሎት መስጫ ቦታዎች እንዳይፈቀዱ፣ የቦታ ይዞታ ባለቤትነት በሕግ እንዳይረጋገጥ፣ ምእመናን ሥርዐተ አምልኮአቸውን በሰላምና በነጻነት እንዳይፈጽሙ፣ መብታቸውን ሲጠይቁም አፋጣኝና አግባብነት ያለው ፍትሕ እንዳያገኙ በማድረግ ተጽዕኖና በደል እያደረሱብኝ ነው ስትል የኦርቶዶክስ ቤ/ክርስትያን ወቀሰች፤ አቤቱታዋም በጥንቃቄ ታይቶ አፋጣኝ ምላሽ እንዲሰጣት አሳሰበች።
ቤተ ክርስቲያኒቱ ከጥቅምት 4 ቀን ጀምሮ በጠቅላይ ቤተ ክህነት አዳራሽ ስታካሂድ በቆየችውና በዛሬው ዕለት እንደሚጠናቀቅ በሚጠበቀው ዓለም አቀፍ የመንበረ ፓትርያርክ ሰበካ መንፈሳዊ ጉባኤ ዓመታዊ ስብሰባ ላይ፣ የፌዴራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ተወካዮች ‹‹የብዝኃነት አያያዝ፣ አክራሪነት/ጽንፈኝነት ዝንባሌዎቹና መፍትሔዎቹ›› በሚል ርእስ ጽሑፍ አቅርበዋል፡፡ ‹‹የሃይማኖት መቻቻል›› በሚለው የአጠቃላይ ጉባኤው መርሐ ግብር ላይ በቀረበው በዚህ ጽሑፍ÷ ሌሎች አገሮች ብዝኃነትን ይዞና አቻችሎ አንድነትን ለማስቀጠል ተግዳሮት እንደኾነባቸው፣ የብዝኃነት ተምሳሌትና መገለጫ በኾነችው ኢትዮጵያ ግን በየጊዜው ወደ አገሪቱ የገቡ ሃይማኖቶች፣ በሰላም የተቀባበሉበትና በመገናዘብ የኖሩበት ጥልቅ ትርጓሜና ታሪክ እንዳለው ተገልጧል፡፡
ጽሑፉን ተከትሎ በነበረው ውይይት በሰሜን ወሎ፣ በምዕራብ ወለጋ ሦስት ዞኖች፣ በጋሞጎፋ ሦስት ወረዳዎች፣ በሶማሌ ዘጠኝ ዞኖች፣ በደቡብ ጎንደርና በወላይታ ኮንታ በዴሳ ወረዳ የሌላ እምነት ተከታይ በኾኑ የመንግሥት ባለሥልጣናት በቤተክርስቲያኒቱ ላይ ይፈጸማሉ የተባሉ የመብት መደፈሮች፣ የአስተዳደር፣ የፍትሕና የጸጥታ አካላት አድልዎች በሀገረ ስብከቶቹ ሊቃነ ጳጳሳት በዝርዝር ተሰምተዋል፡፡
ሊቃነ ጳጳሳቱ እንዳስረዱት÷ ለዞን መስተዳድር አካላት ውሳኔና መመሪያ የማይገዙ፣ የሌላ እምነት ተከታይ የኾኑና ሥልጣናቸውን ተጠቅመው ቤተ ክርስቲያኒቱን በፊውዳልነትና ነፍጠኛነት እየከሰሱ፣ ይዞታዋ እንዲነጠቅ ሕዝብን በበቀል ስሜት የሚያነሣሱ፣ በአማኞች ላይ አካላዊ ሥቃይና ሥነ ልቦናዊ ጫና በማድረስ ለመፈናቀልና ለሞት የሚዳርጉ፣ የሕዝቡን፣ የአገልጋዮችንና የሃይማኖት አባቶችን ጩኸት የማይሰሙ የወረዳ ባለሥልጣናት ጥቂቶች አይደሉም፡፡
በት/ቤት በአንገታቸው ማተብና መስቀል ያሠሩ የኦርቶዶክስ እምነት ተከታይ ተማሪዎች፣ ‹‹ከበላይ የመንግሥት አካል መምሪያ ተላልፎልናል፤ በሸሪዓ ሕግ ሴቶች ራሳቸውን እንዳይከናነቡ፣ ክርስቲያኖች ማተብና መስቀል እንዳያስሩ ተከልክሏል›› በሚሉ መምህራንና የፖሊስ አባላት ማተባቸው ከአንገታቸው ይበጠሳል፤ በጸሎተ ቅዳሴ ላይ ያሉ ምእመናን ከቤተ ክርስቲያን ውስጥ በማስወጣት፣ ጸሎተ ቅዳሴው እንዲስተጓጎልና በበዓላት ቀን ሥራ እንዲሠሩም ይገደዳሉ፡፡ በሞትም በሕይወትም መደጋገፍ በሚታይባቸው ዕድሮችና በሕዝብ መጓጓዣዎች ሕዝቡ እንዳይረዳዳና እንዳይገለገል የወረዳ ዳኛ፣ ‹‹ከኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ጋር አንድነት የለንም›› በማለት እስከ 80 ዓመት የቆየ ዕድር እንዲፈርስና ማኅበራዊ ግንኙነቶች እንዲታወኩ ምክንያት መሆኑ በስብሰባው ላይ በምሬት ተነግሯል፡፡
‹‹አንድ ሰው እግሩን እሳት እየበላው ቻል ይባላል? መቻቻል እስከ ምን ድረስ ነው?›› ሲሉ የጠየቁት የሰሜን ወሎ ሊቀ ጳጳስ አቡነ ቄርሎስ ‹‹እንድንቻቻል አድርጉን፤ እንችላለን›› ሲሉ የሚኒስቴሩን ተወካዮቹ አሳስበዋል፡፡
የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስቴር ተወካዮች በውይይቱ ላይ ክርስትና በአራተኛው መቶ ክ/ዘመን ወደ ኢትዮጵያ መግባቱን የተናገሩ ሲሆን ሊቃነ ጳጳሳቱ መረጃው የተሳሳተ መሆኑን ጠቁመው ማስተካከያ ሰጥተዋል፡፡ ‹‹ከቤተ ክርስቲያናችን አስተምህሮና ከመጽሐፍ ቅዱሱ ምስክርነት ጋር የሚጣረስ ነው፤ ክርስትናን የተቀበልነው ክርስቶስ ዐርጎ ዓመት ሳይሞላው፣ ሐዋርያትም ከኢየሩሳሌም ሳይወጡ በ34 ዓ.ም በጃንደረባው አማካይነት ከእግዚአብሔር ነው፤›› በማለት በቀጣይ የሚኒስቴሩ ተወካዮች በተመሳሳይ ርእሰ ጉዳይ በቤተ ክርስቲያኒቱ መድረኮች ተገኝተው ገለጻ ሲሰጡም፤ ክርስትና በአራተኛው መቶ ክፍለ ዘመን እንደገባ የሚጠቅሱትን አርመው እንዲቀርቡ መክረዋቸዋል፡፡
‹‹ክርስትና በአራተኛው መ/ክ/ዘ ወደ ኢትዮጵያ ስለመግባቱ የተናገሩት ዐፄ ኢዛና ክርስትናን በኦፊሴል ተቀብለው ያስፋፉበት ወቅት በመኾኑ ነው›› ሲሉ የተናገሩት የሚኒስቴሩ ከፍተኛ አማካሪ፤ በ34 ዓ.ም. ጃንደረባው እንደ ግለሰብ መቀበሉ ኢትዮጵያን ሊወክል ይችላል ተብሎ ከታመነ፣ ‹‹እኛ እናንተ ባላችሁት ለማስተካከል ችግር የለብንም፤ የተስማማችኹ ከኾነ በታሪክ መጻሕፍትም ሳይቀር እንዲስተካከል እናደርጋለን፤›› በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡
በሕገ መንግሥቱ አንቀጽ 27/2 ማንኛውም ሃይማኖት እምነቱን ለማስፋፋት ተቋማትን መመሥረት እንደሚችል፣ ለዚህም የቁጥር ገደብ እንዳልተቀመጠ ተወካዮቹ አውስተዋል፡፡
የተጠቀሱት በደሎችና ጥፋቶች በተጨበጠ ማስረጃ ተጠናክረው እንዲሰጧቸውና እነርሱን በተግባር በመፍታት በሂደት እንዲፈትኗቸው ያመለከቱት የሚኒስቴሩ ተወካዮች፣ ስሕተት በመንግሥትም በሃይማኖት አባቶችም ዘንድ እንዳለ፣ በታሪክ አጋጣሚ ወደ ኋላ በቀሩትና የመሠረተ ልማት ዝርጋታና ትስስር በሌላቸው ክልሎች ደግሞ ስሕተቱ እንደሚጎላ፣ ወቀሳውም እያንዳንዱ ቤተ እምነት በሁሉ ላይ የሚያሰማው እንደኾነ ጠቁመዋል፡፡
በሊቃነ ጳጳሳቱ ያልተነገሩ በየወረዳው ያሉ በርካታ ቅሬታዎችን መከታተሉን የሚኒስቴሩ ተወካዮች ገልጸዋል፡፡ እንደ ጥፋት ደረጃውም ርምጃ የተወሰደበት ሁኔታና ተቀጥተው የተለቀቁ አካላት ስላሉ፣ በሕግ የተያዙት ጉዳዮች በሕግ እንዲያልቁ ሊቃነ ጳጳሳቱ ጠንክረው እንዲከታተሉ ጠይቀዋል፡፡
በሌላ በኩል ‹‹ኮሽ ባለ ቁጥር ወደ ቃሊቲ መፍትሔ ስለማይሆን›› ሚኒስቴሩ ግንዛቤ ላይ መሥራትን እንደሚያስቀድም፣ በሃይማኖት ተቋማቱም ዘንድ አስተምህሮውን ጠንቅቀው ያወቁ ሰባክያን ብቻ መሰማራት እንደሚገባቸው አሳስበዋል፡፡ ‹‹እዚህ ተገኝታሁ ያቀረባችሁት ሐሳብ በጣም ጠቃሚ ነው›› በማለት ተወካዮቹን ያመሰገኑት ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ፣ ‹‹በየጊዜው መነጋገር ለሃይማኖትም ለጸጥታም የሚጠቅም ስለሆነ መማማሩ በአንድ ጊዜ የሚያበቃ ባይኾን ጥሩ ነው›› ሲሉ ውይይቱ እንዲቀጥል ያላቸውን ፍላጎት ገልጸዋል፡፡
በሌላ ዜና ዓለም አቀፍ ጉባኤው በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ ተማሪዎችና በአስተዳደሩ መካከል በተማሪዎች አቀባበልና የምዝገባ ቀን፣ መምህራን ከኮሌጁ መኖርያ ቤቶች እንዲለቁ ከተላለፈው የአስተዳደሩ ትእዛዝና ከኮሌጁ ሌሎች የአሠራር ችግሮች ጋር ተያይዞ ሰሞኑን ዳግመኛ ላገረሸው ውዝግብ፤ በቅርቡ የሚካሄደው ቅ/ሲኖዶስ ኹነኛ መፍትሔ እንዲሰጠው መጠየቁ ተዘግቧል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አንድ የሥነ - ከዋክብት ተመራማሪ በአንድ የገጠር ከተማ ይኖር ነበረ፡፡ የዚህ ሰው የሁልጊዜ ፈሊጥ ማታ ማታ ከቤቱ እየወጣ የሰማይ ላይ ከዋክብትን ማየትና የሰው ልጆችን ዕጣ -ፈንታና የተፈጥሮን አካሄድ መመርመር ነበር፡፡
ይህን ክህሎቱን ከጊዜ በኋላ የተረዱ የከተማይቱ ሰዎች ቀስ በቀስ ስለሱ አዋቂነት ማውራት ጀመሩ፡፡ ዋሉ አደሩና እየተከተሉት ዕጣ - ፈንታቸውን ይጠይቁት ያዙ፡፡
አንደኛው - “የሥነ - ከዋክብት አዋቂ ሆይ! የእኔ የወደፊት ዕጣ ምን ይሆን?” ሲል ጠየቀው፡፡
አዋቂ - “ያንተን የከዋክብት ፈለግ እንዳየሁት የመጨረሻ ዕልፈትህ ጠብ ውስጥ ገብተህ ነው፡፡ ያላሰብከው ሰው ነው የሚገድልህ” አለው፡፡
አንደኛው - “ታዲያ ምን ባደርግ ነው የሚሻለኝ?”
አዋቂ - “በምንም ዓይነት ጠብ አካባቢ አትገኝ”
ሌላ ተከታዩ ይመጣል፡፡
“አዋቂ ሆይ! የእኔስ ዕጣ ምን ይሆን?”
አዋቂ - “ኮከብህ የብልጽግና ነው፡፡ ነገር ግን ምቀኞች አሉብህ”
ተከታይ - “ታዲያ ምን ባደርግ ከእነዚህ ምቀኞች ተንኮል አመልጣለሁ?”
አዋቂ - “ደግ እየመሰሉ ከሚቀርቡህ ሰዎች ተጠንቀቅ”
እንዲህ እንዲህ እያለ በየጊዜው እየተከተሉ ዕጣ - ፈንታቸውን ለሚጠይቁት ሰዎች መልስ ሲሰጥና ሲመክር ሰነበተ፡፡
አንድ ማታ እንደተለመደው ከከተማው ዋና በር (ከተምበሪ) አልፎ ሄደ፡፡
ቀና ብሎ ዐይኖቹን ሰማዩ ላይ ተከላቸው፡፡ መመራመሩን፣ መጠበቡን፣ መፈላሰፉን ቀጠለ፡፡ ይህን የየከዋክብቱን አካሄድና እንቅስቃሴ እያየ፣ እንዳንጋጠጠ፣ መራመዱን ቀጠለ፡፡ ሳያስበው ከእግሩ ሥር ካለ አንድ ደረቅ ጉድጓድ ውስጥ ድንገት ጥልቅ አለ፡፡
እዚያ ጉድጓድ ውስጥ ሆኖ እንደወቀደ ያጓራና ያቃስት ገባ፡፡ አንድ ሰው በዚያ አቅራቢያ ሲያልፍ የዚያን የሚያስጓጉር አዋቂ ድምጽ ሰማ፡፡ ወደ ጉድጓዱ አፍ ቀረበና ቁልቁል ተመለከተ፡፡ ሁኔታውን ካስተዋለ በኋላ፤
“ምን ልታደርግ እዚያ ገባህ?”
“ወድቄ ነው”
“እንዴት ይሄን የሚያህል ጉድጓድ አላየህም?”
“ሰማዩ ላይ በጣም አተኩሬ ስለበረ ነው”
“አይ ወዳጄ!” እንደዛ ታላቅ አዋቂ ነህ ብለን የተቀበልንህ ሰው፤ ሰማይ ሰማይ ስታይ እግሮችህ ወዴት እንሚወስዱህ እንኳ ካላወቅህ፤ እኔ እንደሚሰማኝ፤ አሁን ያለህበት ቦተ ተገቢ ቦታህ ነው!” አለው፡፡
* * *
ሰማይ ሰማይ ስናይ እግራችን ሥር ያለውን ነገር አንዘንጋ፡፡ ሰማዩን አተኩረን ስናይ ቀልባችን ሙሉ በሙሉ እሱ ላይ ብቻ ካረፈ፤ ከሥር እግራችንን የሚመታንን እንቅፋትና የሚያሰምጠንን ጉድጓድ አናየውም፡፡ ወደኃያላን መንግሥታት ስናንጋጥጥ የራሳችንን ህዝብ እንረሳለን፡፡ አልፈን ተርፈንም የሰዎችን ዕጣ-ፈንታ ስንናገር የራሳችንን ዕጣ-ፈንታ ሳናቅ እንዳንቀር እንጠንቀቅ!
ኃያላን መንግሥታት ሲሻቸው የበኩር ልጅ፣ ሲሻቸው የእንጀራ ልጅ ማድረግን ይችሉበታል፡፡ ኃያላን መንግሥታት “ሲሞቅ በማንኪያ ሲቀዘቅዝ በእጅ” ገንፎ መብላትን ያውቁበታል፡፡ መልዕክተኞቻቸውን ሲሻቸው በእርዳታ ሰጪ መልክ፣ ሲሻቸው በሚሲዮናውያንና በሃይማኖተኞች መልክ፣ ሲሻቸው በዲፕሎማት መልክ፤ ካልሆነም በቀጥታ ስለላ መልክተኞች - አሊያም በቱሪስት ወይም በፒስኮር መልክ ይልካሉ፡፡ ከከፋም የውስጥ ዐርበኛ ይቀጥራሉ፡፡ ላላ ያለ ካገኙም አገራቸው ድረስ ጋብዘው፣ አስተናግደው ሾመው፣ ሸልመው አንቱ ብለው ይቀባሉ፡፡
ያለ፣ የነበረ ወደፊትም የሚኖር ዘዴያቸው ነው፡፡ ይሄ ሁሉ ካልተሳካ የቁርጡ ቀን መጣ ማለት ነውና እንደ ኢራቅ የጦር ዘመቻ ያካሂዳሉ፡፡ እንደግሎባላይዜሽን አበጋዞች ሳይሆን እንደጥንቶቹ ቅኝ ገዢዎች- በግልጽ ወረራ ያካሂዳሉ፡፡
ከሁሉም ይሰውረን፡፡ ሲያወድሱ ሰማይ፣ ሲጥሉ እንጦር አውርደው ከትቢያ ይደባልቃሉ፡፡ የሁልጊዜ መሳሪያቸው ነው፡፡ እስካመቸናቸው እስካልቆረቆርናቸው ድረስ ያለእኛ በትክክለኛው የዕድገት መስመር ላይ ያለ አገር አይገኝም፡፡ “እንዲህ እያልሽ ውቴልሺን ሽጪ” እንዳለው ወሎ፤ የሚነግራቸው ጠፍቶ ነው፡፡ ለእነሱ የከፋን ለታ ግን ያለእኛ ኋላቀር፣ ያለእኛ ደንቆሮ፣ ያለእኛ ጦርነት ናፋቂ፣ ያለእኛ ረሃብተኛ፣ ያለእኛ መናጢ ደሃ የለም፡፡ ”እፀድቅ ብዬ ባዝላት ተንጠልጥላ ቀረች” ይሉናል፡፡
ከበረታን፤ “አላህንም አትክዳ፣ ሐረጓንም አትልቀቅ” እንዳሉት ጠቢብ ማሰብ አለብን፡፡
የኃያላኑን የቢዝነስ ኮሙኒቲ አይተን እኛ ምን እንሥራ ማለታችን ደግ ነገር ሆኖ፤ ከእዚህ ሁሉ በስተጀርባ ምን አለ? ብሎ መጠየቅ ያባት ነው፡፡ ምን ያህል ከልባቸው ነው? እነሱ፤ ለህዝባችን ይበጃል ያሉትን ማንኛውንም እኩይ ተግባር ከመፀፈም ወደኋላ ብለው ያውቃሉን? ብለን እንጠይቅ፡፡ ሁሉንም በትጋት በጉጉት - ዐይን እናስተውል፡፡
የፖለቲካ ፀሐፍት እንደሚነግሩን፤ “ሥልጣን ላይ ያሉ ሰዎች የሚወድቁት ስህተት ስለሚሰሩ ሳይሆን ስህተታቸውን እንዴት እንደሚያርሙ ስለማያውቁ ነው፡፡ ይሄ የእኛም ችግር ነው፡፡ ሁለት ተጠቃሽ ባህሪዎቻችን፡- “ካፈርኩ አይመልሰኝ (Rigidity)”፣ እና “የአብዬን እከክ ወደእምዬ ልክክ (Blame shifting)” ናቸው፡፡ የሠራሁት ነገር ስህተት እንዳለበት ቢነገረኝም አልለቀውም፡፡ አንዴ አድርጌያለሁ ብያለሁ፡፡ ብያለሁ፡፡ ኃያላኑም ተናግረዋል፤ ማለት አይበጅም፡፡ በተቻለ መጠን በኃያላን ውዳሴ አለመማለል ብልህነት ነው! “ቅጥ - ያጣ መረጃ” ይዘን ነው እስካሁን የሄድነው ተብሏል፡፡ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ችግሮቻችን፣ የሚጨበጡትንና የማይጨበጡትን ጨምሮ፤ ስፍር - ቁጥር የላቸውም፡፡ በአንድ የድህነት ባኮ ከትተን ልንገላገላቸው መንገድ ከጀመርን ከራርመናል፡፡ አሁንም ግን በመጨለምና በንጨላጨል መካከል ነን፡፡
በሬዲዮ ጥያቄና መልስ ፕሮግራም “የሱዳን ዋና ከተማ ማን ትባላለች” ሲባል “አማርኛ ይሁንልኝ” …“የቆጡን አወርድ ብላ…” ጨርሰው ሲባል “ስፖርት ይሁንልኝ”፤ ዓይነት መልስ የሚመልስ ህብረተሰብ ይዘን እየዳከርን ነው፡፡ አገራችን፤ ላዩም ታቹም ይሄን መሳይ ነው!
በጭካኔ ፍትሕን ማምጣት (Brutal justice) እና የኢኮኖሚ አምባገነንነት (Economic Dictatorship) ቦታ ቦታ አላቸው፡፡ ጊዜ ጊዜም አላቸው፡፡ ለመተግበር ፍፁም ጥንቃቄን ይጠይቃሉ። ውጤታቸው ጠላት ማብዛት፣ ዜጋን ማስኮረፍ፣ ሕዝብን መሬት ውስጥ መክተት ሊሆን ይችላል፡፡ ሆደ - ሠፊና ለጋሥ አምባገነን መሆን (Benevolent Dictator) የዋዛ ነገር አይደለም፡፡ ህብረተሰብን በቅጡ ማሳመን ይሻል፡፡ በተለይም የተለያየ ሃይማኖት፣ ባህልና ብሔረሰብ ባለበት አገር እጅግ ከባድ አስተዳደራዊ ምሉዕነትን ይጠይቃል፡፡ የፈረንሳዩ መሪ ደጐል “ሶስት መቶ ስልሳ ዓይነት ዐይብ ያለውን ህዝብ ማስተዳደር ከባድ ነው” የሚለን ለዚህ ነው!

በኢትዮጵያ እና በናይጄሪያ የእግር ኳስ ጨዋታ በጋምቤላ ክልል ኚኝኛግ ወረዳ በደጋፊዎች መካከል በተፈጠረ ግጭት የወረዳው አፈጉባኤ እና ወታደሮች እንደሞቱ ምንጮቻችን ገለፁ።
የደቡብ ሱዳን አዋሳኝ በሆነችው የኚኝኛግ ወረዳ ባለፈው እሁድ ኢትዮጵያና ናይጄሪያ በአዲስ አበባ ስቴዲየም ለዓለም ዋንጫ ማጣሪያ ባደረጉት ጨዋታ፣ የናይጄሪያ ብሔራዊ ቡድን በማሸነፉ ደስታቸውን በጭፈራ በመግለጽ ላይ በነበሩ እና በድርጊቱ በተቆጡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ደጋፊዎች መካከል ግጭት ተፈጥሮ የኚኝኛግ ወረዳ አፈጉባኤና ከሁለት በላይ ወታደሮች እንደሞቱ ታውቋል፡፡
ችግሩ እንደተፈጠረ ከፌደራልና ከክልል የተውጣጡ ባለስልጣናት ቦታው ድረስ በመሄድ የማረጋጋት ስራ መሥራታቸውን ምንጮቻችን ጨምረው ገልፀዋል፡፡
የክልሉ ፕሬዝዳንት ሁኔታው ለማየት ወደ ስፍራው የሄዱ ሲሆን ስለ ጉዳዩ ፕሬዝዳንቱን በስልክ ለመጠየቅ ያደረግነው ተደጋጋሚ ሙከራ አልተሳካም፡፡

          ትግራይ ክልል የማይአይኒ በተባለ ስፍራ የሚገኝ የኤርትራ ስደተኞች ካምፕ ውስጥ በተቀሰቀሰ ረብሻ የአንድ ሠው ህይወት ከጠፋ በኋላ፣ ተጠያቂ ናቸው የተባሉ ሰዎች እንደታሰሩ ምንጮቻችን አመለከቱ፡፡ ስደተኞች የተባበሩት መንግስታት ድርጅትን በመቃወም ቢሮዎች የሰባበሩ ሲሆን፣ ወደ ጎንደር የሚወስደውም መንገድ ተዘግቶ ነበር፡፡
የረብሻው ምንጭ፣ ከሊቢያ ወደ ጣሊያን ሲጓዙ ለሞቱ በርካታ ኤርትራውያን የተዘጋጀ የመታሰቢያ ስነ ስርዓት እንደሆነ ምንጮቻችን ጠቅሰው ሻማ በማብራት የተጀመረው የመታሰቢያ ምሽት ወደ ተቃውሞ ረብሻ መቀየሩን አስታውሰዋል፡፡ በካምፑ ውስጥ የተፈጠረው ረብሻ ከቁጥጥር ውጭ ሆኗል በሚል ውሳኔ የፀጥታ ሀይሎች ጣልቃ እንደገቡ ምንጮቹ ጠቅሰው፤ በረብሻውና በግጭቱ የአንድ ሰው ህይወት እንደጠፋ ተናግረዋል፡፡
የተባበሩት መንግስታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን (UNHCR) የህዝብ ግንኙነት ተወካይ አቶ ክሱት ገብረእግዚአብሔር፤ በሜዲትራኒያን ባህር ላምፑዱስ የተባለ ደሴት አቅራቢያ ህይወታቸውን ላጡ ወገኖች የሻማ ማብራት ስነ ስርአት እናደርጋለን በሚል የተጀመረው ፕሮግራም ለምን ወደ አመፅ እንዳመራ አናውቅም ብለዋል፡፡ ስደተኞቹ ወደ ጎንደር የሚወስደውን መንገድ እንደዘጉ አቶ ክሱት ጠቅሰው፣ የመንግስታቱ ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን እና አብረውን የሚሠሩ የሌሎች መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ላይ ተቃውሞ ተቀስቅሶ የቢሮ መስኮቶችና በሮች ተሠባብረዋል ብለዋል፡፡ ካምፕ ውስጥ የነበሩና አማራጭ ያጡ ወገኖች በሊቢያ በኩል ወደ ጣሊያን ለመግባት ሲሞክሩ ሞተዋል የሚል ሃሳብ በስደተኞች በኩል እንደተሰነዘረ አቶ ክሱት ጠቁመዋል፡፡
የመንግስታቱ ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን፣ በህጋዊ መንገድ ስደተኞችን ቢያጓጉዝ ኖሮ የበርካቶች ህይወት አይጠፋም ነበር በማለት በኮሚሽኑ ቢሮዎች ላይ ጥቃት እንደተፈፀሙ ሰምተናል ብለዋል-አቶ ክሱት፡፡ ስደተኞች ወደተለያዩ አገራት የሚጓጓዙት በኮሚሽኑ ፍላጎት ሳይሆን በተቀባይ አገራት በጎ ፈቃድ ነው ያሉት አቶ ክሱት፤ ኮሚሽኑ ለስደተኞች እንግልት ተጠያቂ እንዳልሆነ ተናግረዋል፡፡

“የብርሃን ፈለጐች” ከቀደሙት ሁለት የደራሲው ሥራዎች (አጥቢያና ቅበላ) በገፁ ብዛት ዳጐስ ብሎ የቀረበ ከመሆኑ አንፃር፣ በበቂ የተለፋበትና የተደከመበት ሥራ እንድንጠብቅ የሚያደርገን ነው፡፡ በተለይም ደራሲው “አጥቢያ” እና “ቅበላ”ን አከታትሎ ለአንባቢ ካደረሰባቸው ከሁለት ዓመታት ያነሰ ጊዜ አንፃር “የብርሃን ፈለጐች” ከአራት ዓመታት በኋላ ሲመጣ፣ ከቀደሙት ሥራዎቹ ከአንባቢ ያገኘውን አስተያየት እንዲሁም የራሱን ስህተትና ክፍተት ሞልቶና አርሞ በተሻለ መገለጥ እንደመጣ መገመት የሚከብድ አልነበረም፡፡ በእርግጥም “የብርሃን ፈለጐች” የፈጠራ ድርሰት የመገምገሚያ መሠረታዊ አላባውያን በሆኑት በታሪክ ፈጠራ፣ በዘይቤ፣ በግጭት፣ በተዓማኒነት፣ በልብ ሰቀላና በአተራረክ ቴክኒክ እንዲሁም በሌሎች መመዘኛዎች የተሳካ ሥራ ለመሥራቱ የያዝኩትን ቅድመ ግምት ያጠናከረልኝ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፡፡
ይሁንና ከላይ የጠቀስኳቸውን መሠረታዊ የመገምገምያ ነጥቦች ተጠቅሜ በ“የብርሃን ፈለጐች” ዙሪያ ቅኝት ከማድረግ ይልቅ ለዛሬ የመጽሐፉን ታሪክ ከዋናው ገፀ-ባህርይ አንፃር ለመፈተሽና በዚሁ ላይ ተመስርቼም የደራሲውን የአፃፃፍ ፈለግ በመመርመር፣ አንዳንድ በወጉ መረዳት የሚገቡንን ነጥቦች ማስቀመጥን መርጫለሁ፡፡
ደራሲ አለማየሁ ገላጋይ ለዚህ መጽሐፉ መግቢያ የሚሆን ነገር አላበጀለትም፡፡ ከዚያ ይልቅ ሃያሲ አብደላ ዕዝራ ከሕትመት በፊት በእጁ የገባውን ረቂቅ ተመልክቶ በተረዳውና በገባው መጠን የሰጠውን አስተያየት በመጀመሪያው ገጽ እና ከእዚያው ውስጥ የተቀነጨበውን ደግሞ በመጽሐፉ የኋላ ሽፋን ላይ እንዲሰፍር አድርጓል፡፡ እርግጥ ነው ደራሲው ሥራው ለአንባቢ ከመድረሱ በፊት ለእንደ አብደላ ዕዝራ ዓይነቱ በኢትዮጵያ የስነ ጽሑፍ ሂስ ታሪክ አንድ ሥፍራ ለሚይዝ ባለሙያ አስተያየት አስቀድሞ ማቅረቡ ለአንባቢ ያለውን አክብሮትና ግምት እንዲሁም በሥራው ላይ ያለውን ትጋት የሚያሳይ ነው፡፡ ይሁንና በመግቢያ መልክ የተሰጠውን አስተያየት ቀንሶ በኋላ የመጽሐፉ ሽፋን ላይ መድገሙ ለምን አስፈላጊ እንደሆነ ግልጽ አልሆነልኝም፡፡
“አንባቢያን መጽሐፉ ከዚያ የላቀም ይሁን ያነሰ ታሪክ በውስጡ አልያዘምና አዲስ ነገርን በመፈለግ አትድከሙ” በማለት ሊያቆም ፈልጐም ከሆነ “blurb” ሆኖ የሰፈረልን ማሳሰቢያ በቂ በሆነን ነበር፡፡ ከዚያ ይልቅ (ግዴታም ባይሆን) ደራሲው በራሱ ብዕር የመግቢያውን ሥፍራ በመሰለው የግሉ እምነትና አስተሳሰብ ቢይዘው ኖሮ፣ ቢያንስ በአንባቢያን ዘንድ ስለመጽሐፉ ልዩ ምልከታና አስተያየት ሊፈጠር የሚችልበት የተሻለ አጋጣሚ በተፈጠረ ነበር እላለሁ፡፡
የዘመን ጉዳይ
“የብርሃን ፈለጐች” የሁለት ዘመን ትውልዶች የሚገለጡበት ልብ - ወለድ ነው፡፡ ይኸን ለማለት ያስገደደኝ በእኛ ሀገር የዘመንም ሆነ ትውልድ ሽግግርና ለውጥ በዓመታት ቀመር የሚሰላ ሳይሆን ዙፋን ላይ በተቀመጠው መንግሥት ምንነትና የአገዛዝ ባህርይ የሚወሰን ሆኖ ስለሚሰማኝ ነው፡፡ የአፄ ኃይለሥላሴ ዘመን ትውልድ ከደርግ፣ የደርጉ ደግሞ ከኢህአዴግ የሚለይበት የየራሱ መገለጫ ባህርይ እንደተሸከመው ማለት ነው፡፡ እርግጥ ነው በመጽሐፉ ውስጥ የምናገኘው ታሪክ የተፈፀመበትን ዘመን ደራሲው እንድንረዳ የሚያደርገን በገፀ ባህርያቱ አለባበስ፣ አኳኋንና አልፎም ንግግር ነው፡፡
“የግንፍሌ ማለዶች” በመጽሐፉ ውስጥ በቅድሚያ የምናገኘው የታሪክ ክፍል ሲሆን ዘመኑን ለመገመት ለሚነሳ አንባቢ ግን የራሱን ፈተና ከፊቱ ማስቀመጡ የሚቀር አልሆነም፡፡ የታሪኩ ዋና ገፀባህርይ የሆነው መክብብ፤ የልጅነት ዕድሜውን ያሳለፈባትን ግንፍሌን ከቤተሰቡ፣ ከጓደኞቹ፣ ከጐረቤቶቹና ከሠፈሩ ሰዎች ጋር ባለው ተራክቦ በሚገባ እንድናያት ደራሲው ማድረጉን ሳንክድ ነገር ግን የዘመን ጥያቄ ሲነሳ በአፄው ዘመነ መንግሥት ለመሆኑ ከግምት እንዳናልፍ የሚያደርጉን ሁለት ጉዳዮች እናገኛለን። የመጀመሪያው “ገዳማይ” የሚለው ዘፈን ተደጋግሞ መምጣት ሲሆን (ዘፈኑ በኋላ በደርግ ዘመን በሙሉቀን የተቀነቀነ ቢሆንም ከዐፄው ዘመን የወረሰው በመሆኑ) እና ሁለተኛው የአባቱ የፀጉር አቆራረጥ ከ“ፕሪስሊ” ጋር መገናኘቱ ነው፡፡ ዘፈኑም ሆነ የኤልቪስ ፕሪስሊ የፀጉር ፋሽን በሀገራችን ሰፊ ተቀባይነት የነበራቸው በ60ዎቹ መጀመሪያ ከመሆኑ ጋር በተገናኘ ግንፍሌን የምንመለከትበት መነጽርም የአፄው ዘመን እንዲሆን ብንወስን እንኳን ሌላ ፈተና ደግሞ መምጣቱ አልቀረም፡፡ ይኸውም ዘፈኑ የሚቀርብልን በመክብብ አባት የትዝታ እንጉርጉሮ በመሆኑ፣ ዘመኑን ወደ ደርግ የሚጐትተው ሲሆን የፀጉር አቆራረጥ ዘይቤውም ቢሆን አባቱ በውስጡ ለዓመታት ከተቆራኘው የሙዚቃ ፍቅር ማምለጥ አለመቻሉን የሚያስረግጥ ማሳያ እንጂ የሚገኝበትን ትውልድ የዘመን ፋሽን የመግለጥ አቅሙ ደካማ ከመሆኑ ላይ ነው፡፡ ምናልባት በዚሁ ዘይቤ ሌላ ገፀ ባህርይ ተስሎልን ቢሆን ወይም ተጨማሪ ገለፃ ከመቼት አንፃር ሰፍሮልን ቢሆን በግንፍሌ የታሪክ ዘመን ላይ ጥያቄ ባልኖረንም ነበር፡፡
ወደሁለተኛውና የመጽሐፉ ሰፊ የታሪክ መሽከርከሪያ ወደሆነችው ሞጆ ስንሻገር፣ የዘመን ጥያቄ በደራሲው በቂ ምላሽ የተሰጠበት ሆኗል። ቢያንስ በሁለት ገፀ ባህርያት አማካይነት ሞጆ የተገለፀችበት ዘመን የአብዮቱ ዓመታት እንደነበሩ ግልጽ ነው፡፡ የናፍቆት አባት ተደጋጋሚ “የአብዮታዊት ኢትዮጵያ” ስብከትና የመምህርቱ ሙና ያለፈ የኢህአፓ ትዝታ ሞጆ በየትኛው ዘመንና ትውልድ ተስላ እንደቀረበችልን በቂ ማሳያ ናቸው፡፡
እዚህ ላይ የዘመን ጉዳይ በፈጠራ ድርሰት ውስጥ ቀዳሚውን ሥፍራ ሊያገኝ የሚገባበትን አስፈላጊነት አጽንኦት ሰጥቼ ማስቀመጤ ምክንያቱ ግልጽ ይመሥለኛል፡፡ ይኸውም ማንኛውም የልብ ወለድ መጽሐፍ ለንባብ ሲበቃ፣ ደራሲው በውል የሚያውቀውን ዘመንና ሥፍራ የሚያሳይ መስታወት በአንባቢው ፊት የማቆሙን ግዴታ ከግምት በመክተት ነው፡፡ ድርሰት የቱንም ያህል የደራሲ የፈጠራ ውጤት ቢሆን ፍፁም ውሸት ተደርጐ የማይወሰደውም ከዚህ በመነሳት ነው፡፡ የፈጠራነቱ ባህርይ ውሸት ቢያደርገውም የሚፈጠሩት ገፀ ባህርያት፣ ጊዜያት (ዘመን)፣ ሥፍራዎች፣ ድርጊቶች … ወዘተ የገሃዱ ዓለም ነፀብራቅ በመሆናቸው ደግሞ “እውነት” ሊሆኑ የሚችሉ አድርገን መቀበላችን አይቀሬ ነውና፡፡
የአፃፃፍ ፈለግ
የዚህ ጽሑፍ ዋነኛ ጉዳይ ወደሆነው በ “የብርሃን ፈለጐች” ውስጥ ወደተስተዋለው የአፃፃፍ ፈለግ ደግሞ እናምራና መጠነኛ ፍተሻ እናድርግ። እንግዲህ አንድ ደራሲ እንደሚገኝበት ዘመንና በዘመኑ እንደነገሰውም አስተሳሰብ፣ የራሱን የአፃፃፍ ፈለግ የመከተል ነፃነት እንደተጠበቀ የመሆኑ ጉዳይ ተሰምሮበት ነገር ግን የማኅበረሰቡን ልማድ፣ ወግ፣ ንቃተ ህሊና፣ መሻትና ፍላጐት ደግሞ ከግምት የከተተ መሆኑ ተመራጭ ያደርገዋል፡፡
እርግጥ ነው ደራሲ ከማኅበረሰቡ የተለየ ዓይንና ማስተዋል የታደለ እንደመሆኑ መጠን የተመለከተውንና የታዘበውን ወይም ያስደነቀውን እውነት በመሰለውና ባመነበት መንገድ የማስቀመጡ ነፃነት ለእሱ የተተወ ነው፡፡ ለምሳሌ በአፃፃፍ ስልቱ (Style) ዙሪያ አንድም በምርጫ ወይም በግላዊነት ላይ ተመስርቶ ድርሰቱን ለመፃፍ ይችላል፡፡ በምርጫ ስንል ለምሳሌ የቀለም ምርጫ የግሉ ነው፡፡ ውበትን ለመግለፅ ቀይ ቀለምን ምርጫው ያደረገ ደራሲ “ለምን?” የሚል ክርክር ሊነሳበት አይችልም፡፡ ከግላዊነትም አንፃር ለምሳሌ ረዥም ወይም አጭር ዐረፍተ ነገርን መርጦ መጠቀሙ፣ ተረትና ምሳሌ ማብዛቱ፣ የዘይቤ ምርጫው ሁሉ ከዚሁ የግላዊነት ነፃነቱ የሚመነጩ ናቸው፡፡
ይህ እውነታ እንደተጠበቀ ሆኖ ደራሲ አለማየሁ በ “የብርሃን ፈለጐች” ውስጥ ገንኖ የወጣበት የአፃፃፍ ፈለግ በዘመናችን በርካታ አለም አቀፍና አንዳንድ ጥቂት የሀገራችን ደራስያን (አዳም ረታ ተጠቃሽ ነው) በሥራዎቻቸው በስፋት የሚጠቀሙበት የ“Postmodernism” የአፃፃፍ ፈለግ ሆኖ አግኝቼዋለሁ፡፡ ከዚህ አንፃር የደራሲውን ሥራ ከመቃኘቴ በፊት ይኼ የአፃፃፍ ፈለግ ዋነኛ አትኩሮቱ ምን እንደሆነ በቀላል ማብራሪያ አንባብያንን ግንዛቤ ማስጨበጥ ያሻል፡፡
የ“Postmodemism” እሳቤ በኪነጥበብ ዘርፍ ለማቆጥቆጥ መነሻ የሆነው በኪነ-ሕንፃ (architecture) ጥበብ ላይ የተነሳው አዲስ አስተሳሰብ እንደነበር ይታመናል፡፡ ይኼ ፈለግ ሁለት መሠረታዊ ደረጃዎችን ተሻግሮ፣ በተለይ በ1950ዎቹና 60ዎቹ ያቆጠቆጠ ሲሆን ከእሱ በፊት ቀዳሚ የነበሩት ሁለት ፈለጐች የመጀመሪያው “Premodernism” ሲሆን በመቀጠል ደግሞ “modernism” በመባል ይታወቃሉ፡፡ በ “Premodernism” ማንኛውም የጥበብ ሰው የአስተሳሰቡ መሠረት አድርጐ በሥራው እንዲያንፀባርቅ የሚጠበቅበት መንገድ ከባህሉና ወጉ ወይም እምነቱ የመነጨ ሊሆን ይገባል የሚል ነበር፡፡ በተለይ ይኼን አስተሳሰብ በማራመድ ተጠቃሽ የሆነችው የካቶሊክ ቤተክርስቲያን ስትሆን ማንኛውም የፈጠራ ሥራ በባህልና እምነት ተፅዕኖ ሥራ መውደቅ እንዳለበት ቀዳሚ ተከራካሪ ሆና ለዘመናት ዘልቃ ነበር፡፡ ከዚያ በመቀጠል የመጣው የ“modernism” ፈለግ ደግሞ የሰው ልጅ አብርሆ መቃኘት ያለበት አዲስ ነገርን በማሰብና በተፈጥሮ ሳይንስ ሊሆን ይገባል እንጂ በባህልና ህግ እንዲሁም በእምነት መሪዎች አስተሳሰብ ሥር መውደቅ የለበትም የሚል ነው፡፡ የዚህ አስተሳሰብ መሠረቱ የሕይወት ትርጉምም ሆነ እውነት የሚመነጨው ከግለሰቡ አመለካከትና አቋም እንጂ በላዩ ከተጫነበት እምነትና ባህል ሊሆን አይገባም የሚል ነበር፡፡ እናም የዚህ ፈለግ አራማጆች ማንኛውም የፈጠራ ሥራ የቀደመውን ባህልና ወግ እንዲሁም አስተሳሰብ ወደ ጐን አስቀምጦ አዲስና ቀልብን የሚማርክ ነገር በመፍጠር ላይ ያተኮረ ሊሆን ይገባል ባይ ናቸው፡፡
የዚህ ፈለግ ተቃዋሚ ሆነው ብቅ ያሉት ደግሞ በተለይ በስነጽሑፍ ዘርፍ በ1970ዎቹ እ.ኤ.አ ገንነው የወጡት “Postmodernist” ናቸው፡፡ “Postmodernist” በዋነኛነት የሚያራምዱት አስተሳሰብ በቀላል አገላለፅ ሲቀመጥ የ“modernism” አስተሳሰብ የሆነውን አዲስና ማራኪ የፈጠራ ሥራ መከወንን ተቀብለው፣ ነገር ግን መሠረቱ ሊያደርገው የሚገባው የቀደመውን ወይም ነባሩን ባህልና ወግ እንዲሁም እምነት ሊሆን ይገባል የሚል ነው፡፡ ከዚህ አንፃር የ “Postmodernist” የአፃፃፍ ፈለግ በዋነኛነት ለመመለስ የሚሻው ጥያቄ “የሰው ልጅ ማንነት (ሕልውና) በተፈጥሮ ውስጥ ያለው ሥፍራ ምን እንደሆነ” ፈልጐ ማግኘትን ነው። ለምን ተፈጠርኩ? ማነው የፈጠረኝ? የመፈጠርስ ዓላማ በፈጣሪ ወይስ በየግል የአስተሳሰብ አቋም የሚገለፅና የሚወሰን ነው? ከተፈጠርን በኋላስ በምድራዊ ሕይወታችን ለሚገጥመን ክፉም ሆነ በጐ አጋጣሚ ተጠያቂው የማኅበረሰቡ እምነትና ባህል? አካባቢያችንና ቤተሰባችን? ፈጣሪያችን? ወይስ ማን? የሚሉና መሰል ከውስጣዊ ማንነት ጋር የተያያዙ ጥያቄዎችን መንደርደሪያው ያደርጋል፡፡ ይሁንና የጥያቄዎቹ ምላሽ ሊፈለግ የሚገባው ደግሞ ግለሰቡም ሆነ ማኅበረሰቡ በተቃኘበት እምነት፣ ባህል፣ አስተሳሰብና ወግ ላይ ተመስርቶ ሊሆን እንደሚገባ “Postmodernist” ያሰምሩበታል፡፡
እንግዲህ ወደ “የብርሃን ፈለጐች” ስንመለስ፣ በአመዛኙ ይኸው የማንነት (የሕልውና) ጥያቄን መሠረቱ አድርጐ ከመቆሙ ባሻገር ለጥያቄው ምላሽ የሚያፈላልገው ደግሞ ከማኅበረሰቡ ባህልና ወግ ከዚያም ሲያልፍ በፈጣሪው ላይ ከገነባው እምነት የለሽ የመሆኑ እውነታ ነው፡፡ ለዚህ በቂ ማሳያ የሚሆነን ደራሲው በዋናው ገፀ ባህርይ መክብብ አማካይነት ደጋግሞ የሚያነሳውን የማንነት ጥያቄና ከቤተሰቡ እስከ ማኅበረሰቡ እንዲሁም ባህልና ወጉን አልፎም ፈጣሪውን የሚሞግትበት ስልት ይሆናል፡፡
ደራሲው ከመነሻው እንዲህ ዓይነቱን ጥያቄ የሚያነሳልን በመክብብ መፈንከት ይሆናል፡፡ መክብብ በጓደኛው ጋንጩር ተፈንክቶ በጓደኞቹ ሸክም ወደቤቱ ሲወሰድ ከመፈንከቱ በላይ ጥያቄ ፈጥሮበት ከራሱ ጋር ሙግት የሚያስገጥመውና ግርምት የሚፈጥርበት ከውስጡ የሚፈልቀው ደም ነበር፡፡
“አካላችን ውስጥ እንዳልነበር፣ የእኛ እንዳልሆነ በባዕድነት ዝም ብሎ መንዠቅዠቁ አስረገመኝ” (ገፅ 6)
ደራሲው በዋናው ገፀ ባህርይ ውስጥ ከጅምሩ የፈጠረው በራስ ላይ የሚነሳ የማንነት ጥያቄ፣ በቤተሰቡ ውስጥም የሚንፀባረቀው ብዙም ሳንጓዝ በእናቱ አማካይነት ይሆናል፡፡ የመክብብን እናት ማንነት የዘመን ወካይነቷን መነፅር አጥልቀን እንድናይ የምንጋበዘው በቤታቸዉ በሰፈነው ድባብ አማካኝነት ሲሆን ከግድግዳው መገርጣት፣ ከብርሃን ማጣቱ፣ እንደጐሬ ከመክበዱ … ወዘተ ጋር በተገናኘ ለእሱ ጭንቅ የሚፈጥርበት ክስተት በእናቱ ዘንድ ግን ተቃራኒ ስሜት የያዘና ከዚያ ያለፈ የመለወጥ ምኞትም የሚፈጥር አልሆነም፡፡ ለመክብብ የቤታቸው መገለጫ ከሆኑት “ብርሃን የሚውጡ” ቁሳቁሶችም ሆነ ስሜት ከሚያጨልመው ጣራና ግድግዳዉ መካከል ዓይን ሳቢ የነበረው የሚካኤል ስዕል ቢሆንም እሱም እንክብካቤ ተነፍጐና በጢስ ጠቁሮ በቤቱ መንፈስ የተዋጠ ሆኗል፡፡ ሕይወት ዕጣ-ፈንታው አድርጋ የለገሰችውን ድህነት፣ ቤተሰቡ በፀጋ ተቀብሎ መኖሩ ከልጅነቱ አልዋጥልህ ብሎ ጭንቁን የሚተነፍሰው መክብብ፤ ቢያንስ የእምነት መገለጫ የተደረገውን ስዕል እንኳን የመለወጥ ፍላጐት ከእናቱ ዘንድ ማጣቱ፣ እንደ ኑሮው እምነቱም በወደቀ ቤተሰብ ውስጥ ለመኖሩ ማንፀሪያ አድርጐታል፡፡
“ይሄ ምስል በአዲስ ይቀየር ብትባል እናቴ በጀ የምትል አይመስለኝም” (ገፅ 9) በማለት ድህነት ቤተሰቡ ላይ የፈጠረው የኑሮ ብቻ ሳይሆን የእምነት ዝንጋታ በመክብብ በኩል ሲነገረን፣ ደራሲውን የነበረው ባህል፣ ወግ፣ እምነት ላይ የተመሠረተ አዲስ ለውጥና መሻሻል ናፋቂ ሆኖ እናገኘዋለን። የ“Postmodernism” ፈለግ ይኸው ነው፡፡ የገፀ-ባህሪያቱን አስተሳሰብ፣ ስነ-ልቦና፣ እምነት፣ ምልከታ … ዘልቆ በመፈተሽ ከገሃዱ ዓለም እውነታ ጋር በንፅፅር የማቅረብና በአዲስ መንገድ የማስታረቅ ዓላማን አንግቦ የሚጓዝ፡፡
ደራሲው የማንነትን ጥያቄ ከገፀባህርያቱ ስነልቦና እየፈተሸ ምላሽ ሲያፈላልግ ከምናገኝበት ክስተቶች አንዱ በቤተሰብ ዙሪያ የሚያጠነጥን በተለይም በባልና ሚስት መካከል የሰፈነው ግንኙነት ምን መምስል እንደሚገባው የሚመለከት ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ ከእናቱ ይልቅ ወደ አባቱ የሚያደላ ፍቅር የምናይበት ዋናው ገፀ-ባህርይ መክብብ፤ በልጅነቱ የተቀረፀበትን “የወላጆቹ ትዳር በእናቱ የበላይነት መመራት” ከባህሉና ከወጉ ጋር የሚጣላ ብቻ ሳይሆን ፍፃሜው መፈራረስ መሆኑን የሚያሳየን በብዙ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ውጥንቅጥ የተሞላው የጐረቤቶቻቸው ትዳር እንደነበር ሲቀጥል፣ የወላጆቹ መጨረሻ ግን መለያየት እንደጠቀለለው በመተረክ ነበር፡፡ ቤተሰብ የማኅበረሰብ መሠረት እንደሆነና ድህነት የሚፈጥረው ፈተና እንኳን በቀላሉ እንደማይሰብረው ደራሲው ከግንፍሌ ነዋሪዎች ሕይወት እግረ-መንገድ እያነሳልን ካስጓዘን በኋላ ወደ ዋናው ገፀ ባህርይ ወላጆች ሲያደርሰን ግን የዘመኑን የትዳር መንፈስ ከኋለኛው የሚያነፃፅርበት ሰበዝ አድርጐ ይመዘዋል፡፡ እናም በራስ ላይ ለሚነሳ የ“ለምን አገባሁ?” ጥያቄና ለትዳር መፍረስ ምላሽ በማድረግ የሚያስቀምጠው ትዳር፤ በነባሩ የባህልና ወግ ሥርዓት መሠረት ወንዱ የሚገባውን የበላይነት ሥፍራ በቅድሚያ መልሶ ሲያገኝ እንደሆነ በመሞገት ነው፡፡
ደራሲው በዋናው ገፀ-ባህርይ መክብብ በኩል ይህንኑ የትዳር መሠረታዊ ችግር የሚያሳየን ከእናቱ አስተሳሰብ በመነሣት ነው፡፡
“እናቴ አባቴን ከጫካ አጥምዳ፣ የሚበላው እየሰጠች የገራችው የግሏ አውሬ ይመስለኛል” (ገፅ 14) ይላል፡፡
ደራሲው በመክብብ በኩል ከሚያነሳቸዉ የማንነት ጥያቄዎች አንዱ እንግዲህ ከሕልውና መሠረቶች አንዱ የሆነውን የቤተሰብን አወቃቀር እንዲህ የሚፈትሽና ምላሽ የሚያፈላልግ ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ የማኅበረሰብ መገለጫው በውስጡ እንደሚገኙ ቤተሰቦች (ትዳር) ጥንካሬና ድክመት የሚወሰን ሲሆን የሀገሩ ባህልም ሆነ እምነት በአወቃቀሩ ከማይደግፈው ከዚያ ቤተሰብ የተገኘው መክብብ ደግሞ በማኅበረሰቡ ውስጥ የሚመለከተውን በወንዱ የበላይነት የሚመራ ትዳር፤ ለወላጆቹ ከመሻቱ የተነሣ የፍቅራቸውን ሰዓት እንኳን የሚመለከተው በቅናት መንፈስ ተሞልቶ ነበር፡፡ ዘወትር የአባቱ በእናቱ ተሸናፊነትና ዝቅ ተደርጐ መመልከት፣ እንዲሁም የአባቱ የማያሰልስ ታዛዥነትና ትዳር የለገሰችውን ሥጋዊ ስሜቱን በነፃነት የማርካት መብት ሳይቀር በልምምጥ ለማግኘት በየምሽቱ መታተርን መታዘቡ፣ ለአባቱ በማዘን ብቻ ሳይሆን በመቆርቆርም እንዲያድግ አድርጐታል። ለዚህ ቀላል ማሳያ የምትሆነን የመክብብ እናት ወደ ሞጆ ለመሄድ ስትነሣ የተፈጠረውን ትዕይንት እንመልከት፡-
“እናቴ ወደ ሞጆ ስትሄድ አባቴ በሎሌነት ዘንቢሏን አዝሎ ይከተላታል፡፡ ዘንቢሉ የተሞላው በጆንያ፣ በከረጢት፣ በማዳበሪያና በስልቻ ነው። በዚህ ትዕይንት ትክክል ያልሆነ ነገር እንዳለ ይሰማኛል፡፡ እናቴ ጥቁር ከፋይ ካፖርት በነጠላ ክንንብ ላይ ደርባለች፡፡ ሦስት ማእዘን ቅርፅ ያላትን ቦርሳ ክንዷ ላይ አንጠልጥላለች፡፡ አባቴ ፕሪስሊውን እንደደፋ ኋላ ኋላዋ ቱስ ቱስ ይላል …
“ትክክል ያልሆነ ነገር እንዳለ ይሰማኛል፡፡ እናቴ የአባቴን ፍፁም ታዛዥነት ለመንደርተኛው የምታስመዘግብበት ትዕይንቷ ነው …” (ገፅ.36)
ከትዳር ትርጉም በላይ ደራሲው በመክብብ አማካኝነት የሚያነሳልን ሌላ የማንነት ጥያቄ ደግሞ አባቱ ምኞቱንና ሕልሙን በእናቱ ፍርሃት ሥር ጥሎ እንዲኖር ያስገደደውን የሙዚቃ ፍቅር ነበር። የዚህ ምኞትና ሕልሙ ማስተንፈሻ የነበረችው ጊታር፣ ከአልጋቸው ሥር ተጠቅልላ ስትወረወር፣ አባቱ በምድር ላይ የተፈጠረበትን ምስጢርና ዓላማ እንኳን ፈልጐ እንዳይደርስበት በሚስቱ ፍርሃት ተሸብቦ በዘበኝነት ለመኖር ምርጫው ማድረጉ፣ ለራሱ አስገራሚ ጥያቄ የሚፈጥርበት ነበር፡፡ ከአልጋ ሥር የተጣለችው የመክብብ አባት ጊታር ወደ ማኅበረሰቡ ሕይወት ወርዳ ስትመነዘር፣ ከእያንዳንዱ ሰው የመፈጠር ምክንያት ጋር የተገናኘ ምኞትና መሻትን እንዲሁም መክሊትን የምትወክል ሆና እናገኛታለን፡፡ መሆን የምናስበውንም ሆነ የምንችለውን እንድንሆን መንገዱን በቅድሚያ የሚሰጠን የምናድግበት ቤተሰብና አልፎም ማኅበረሰብ ቢሆንም በመንገዱ ላይ ለመጓዝ ግን ቤተሰብና ማኅበረሰብ የተመሠረተበትን ባህልና ወግ እንዲሁም እምነት መለስ ብሎ መፈተሽ እንደሚገባ ደራሲው የሚሞግት ይመስላል፡፡ ለዚህም ነው የአባቱን ሕልምና ምኞት ለጊዜውም ቢሆን በእናቱ የሞጆ ጉዞ ባገኙት ነፃነት ላይ መስርቶ ከወደቀበት ለማንሳት መክብብ የሚንደፋደፈው፡፡
ይኼን የአባቱ ሕልምና ምኞት ወኪል የሆነ ጊታር የተጣለው ደግሞ የምድሪቷን ድንጋይና አፈር እንዲሁም ቆሻሻ ሲረግጡ ኖረው ከተጣሉ አሮጌ ጫማዎች ሥር እንደነበር ስንመለከት፣ ደራሲው በእያንዳንዳችን ሕይወት ውስጥ ሊፈጥር የፈለገው ስነ-ልቦናዊ ጥያቄ ምን ያህል ጥልቅ እንደሆነ ለመገመት ያስችለናል፡፡ የመክብብ ልጅነት ለአባቱ አዲስ ማንነት (እንደእናቱ) ለመፍጠር የሚውገረገር ዓይነት ሳይሆን የተደበቀውንና የተሸነፈ የሚመስለውን የቀድሞ ሕልምና ምኞቱን እንደ አዲስ ነፍስ ሲዘራበት ለመመልከት የሚጓጓ ማንነትን የተላበሰ ነው፡፡ ከቆሻሻና ከተጣለ የእግር መሸፈኛ ሥር የአባቱን “ራዕይ” ሲጐትት ግን ስለዚያ የአባቱ ራዕይ የሚያውቀው አልነበረም ወይም ዘንግቶታል። ለአባቱ ደግሞ “ራዕዩ” የፍርሃትና የስጋቱ ምንጭ ነበር፡፡ (ገፅ 39-40)
ያለፈው ትውልድና ዘመን በኑሮ ጥያቄም ይሁን በባህልና እምነት ወግ ተሸንፎ የጣለውን የማንነት ፈለግ የአዲሱ ዘመንና ትውልድ ወኪል ሆኖ የቀረበልን መክብብ፤ በፍለጋው መሰማራት ብቻ ሳይሆን ለራሱ ማንነትም ፈለጉን ተከትሎ በመጓዝ ምላሽ እንዲሰጥ ጥያቄውን አሸክሞ ደራሲው ወደ አዲስ መንደር፣ ማኅበረሰብና ሕይወት ይከተዋል፡፡
መክብብ የማንነቱን ስነ ልቦና የቀረፁት ቤተሰብ፣ ማኅበረሰብና በተለይም አብሮ አደግ ጓደኞቹ በአዲሱ የሞጆ ሕይወቱ እንደ ቀላል የሚረሱና የሚጣሉ እንዳልሆኑ ስንመለከት ከላይ አስቀድመን የጠቀስነውን የ“Postmodernism” የአፃፃፍ ፈለግ ደራሲው በሚገባ እንደተከተለ የሚያስረግጥልን ይሆናል፡፡ ከግንፍሌው የቤተሰቡ የድህነትና የመከራ ሕይወት በመነሣት፣ በሞጆ የምቾትና የደስታ ኑሮ በአክስቱ ቤት የተቀበለው መክብብ የምናይበት ለውጥ የስነ-ልቦና ወይም የአስተሳሰብ ሳይሆን የሥጋ ብቻ ሆኖ ይቀራል፡፡ በ“Postmodernism” የአፃፃፍ ፈለግ አንዱ የደራሲ ትልቁ አቅም ሆኖ የሚቆጠረው በገፀ-ባህርያቱ እምነት፣ ፍልስፍና፣ አስተሳሰብ፣ አቋም … ውስጥ ዘልቆ በመግባት ማሳየት እንጂ ድህነት በሀብት፣ ክህደት በእምነት፣ ጥላቻ በፍቅር … የሚሸነፍበትን ውጫዊ ዓለም መፍጠር አይደለም፡፡ በዚህ ረገድ ደራሲው የተዋጣ ሥራዉን ለአንባቢ ማቅረቡን መመስከር የሚያስችሉ በርካታ ማስረጃዎች ማምጣት ይቻላል፡፡
ለምሳሌ በግንፍሌ ያለፈበት የድህነት ሕይወት መክብብን በሞጆ አልጠበቀውም፡፡ ነገር ግን የተቀማጠለ ኑሮው የማንነት ፍለጋውን የማስረሳት አቅም ደግሞ አላገኘም፡፡ በልጅነቱ ደሀና ድህነትን አስመልክቶ የነበረው አስተሳሰብና ጥያቄን በሞጆም ተሸክሞት ይዞራል፡፡ በልጅነቱ ከአባቱ የወረሰው ድብድብ ያለመፍራት ወኔና ድፍረቱን በግንፍሌ ሜዳ በጋሙዳ ላይ እንዳስመሰከረው፣ በሞጆ ደግሞ በረት ገልባጭ ላይ አሳይቶናል፡፡ የኑሮ ለውጡ በመክብብ ስነ-ልቦና ላይ የፈጠረው ይኼ ነው የሚባል ለውጥ በቀላሉ አናገኝም፡፡ በግንፍሌ የምናውቀው መክብብ፤ ፍቅር የሚፈራና የሚያርበተብተው ነበር፡፡ በግንፍሌዋ ንፁህ ላይ ያሳየን የፍቅር ፍርሃት ሞጆ ሲገባ ደግሞ በናፍቆት ሲደግመው እናያለን፡፡ ለመክብብ የኑሮ ምቾት፣ ትምህርት፣ አዲስ መንደርና ጓደኛ የማንነትን ጥያቄ የሚመልሱ ወይም የሚሽሩ አልሆኑለትም፡፡ ለእሱ ከሕይወት የተቀበለው የመፈጠሩ ምክንያት የተጣለውና የወደቀው የአባቱ ምቾትና ሕልም የተዘረጋበትን ፈለግ ተከትሎ መጓዝ ነው፡፡ የመፈጠሩን ሕልም ለትዳሩ መስዋዕት ያደረገው አባቱ፤ በምላሹ ውርደትን ሲቀበል ተመልክቷል። ፍቅርን በመፍራት የተያዘ ስነ-ልቦና ብናይበት አንደነቅም፡፡ መማር ሰርቶ ገንዘብ ከማግኘት ባለፈ ራዕይን ለመፈፀም እንደማያበቃ አሁንም ከአባቱ ማንነት የተረዳው በመሆኑ፣ በትምህርት የራሱን ማንነት እንደማያገኝ ተስፋ የቆረጠ ስነ-ልቦና ቢላበስ የሚገርም አይሆንም፡፡
ራዕይና መክሊትን ለአባቱ ሰጥቶ ደሀ ያደረገውን አምላክም ሕልውናውን ለመቀበል ሲቸገር ብንመለከት በማን-ፈለግ እየተጓዘ እንደሆነ ለመገመት አያስቸግረንም፡፡ በድህነት ሕይወቱ ከአባቱ የወረሰውን የማንነት ፍለጋ በተሻለ የምቾት ሕይወት ውስጥ ራሱን ሲያገኝ አለመዘንጋቱ እንዲሁ የሚጓዝበትን ፈለግ አመላካች ሆኗል፡፡ ደራሲ አለማየሁ ገላጋይ በ “ብርሃን ፈለጐች” ሥራው እነዚህንና ሌሎች የአንድ ዘመንና ትውልድ አባል የሆነ እንደመክብብ ዓይነቱ ሰው የሚያነሳቸውንና የሚያስጨንቁትን ስነ-ልቦናዊ ጥያቄዎች እስከ አእምሮው ጓዳ አብረነው ገብተን እንድንበረብር አድርጐናልና አድናቆታችንን ልንቸረው ይገባል፡፡
ማጠቃለያ
“የብርሃን ፈለጐች” በዓመቱ ከቀረቡልን የስነ-ጽሑፍ ትሩፋቶች ግንባር ቀደሙ ተደርጐ ቢወሰድ የምስማማበት ዋነኛው ምክንያት በአፃፃፍ ፈለጉ (“Postmodernism”) መሠረታዊውን የማኅበረሰብ ባህል፣ እምነት፣ አስተሳሰብ፣ ወግ ሳይለቅ ነገር ግን የትውልዱን መሻት፣ ሕልምና ፍላጐት ከሥጋዊ ስኬት ባሻገር ወደ ልቦናው ጠልቀን እንድንመለከት የመጋበዙ ጉዳይ ነው፡፡ መክብብ ያለፈው ትውልድና ዘመን ወኪል አድርገን በትዝታ የምናስበው ሳይሆን በዛሬው ትውልድ ስነ-ልቦና ውስጥ የተቀበረውን የማንነት ጥያቄ እንድንፈትሽና መልሱን እንደመረዳታችን መጠን እንድንደርስበት ምሳሌአችን ሆኖ የቆመ ሰባኪ ሆኖ አግኝቼዋለሁ። በእሱ “የብርሃን ፈለጐች” አብረን ስንጓዝ የምንደርስበት እውነትም ወደራስ ማንነት ከመመለስ በላይ ታላቅ ስኬት አለመኖሩን መረዳት ይሆናል፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አለቃ ገብረሃና ታመው ቤታቸው አልጋ ላይ ይውላሉ፡፡ አንዲት በሞጥሟጣነቷ በሰፈሩ የምትታወቅ ሴት ልትጠይቃቸው ትመጣለች፡፡
“አለቃ እንደምን አረፈዱ?”
“ደህና ነኝ - እግዚሃር ይመስገን” አሉ አለቃ፡፡
“ሰውኮ አጥብቆም አልነገረኝ፡፡ ለመሆኑ ምንዎትን ነው ያመመዎ?” አለቻቸው፡፡
አለቃ ላለመለስ ፈልገውም ይሁን፣ ግራ ተጋብተው ዝም ይላሉ፡፡ ሴትዮዋ፤
“አለቃ?”
“አቤት?”
“ምነው ዝም አሉኝ? አይመልሱልኝም እንዴ?”
“የዛሬ ህመም ከሚነገር ባይነገር የተሻለ ነው ብዬ ነው፡፡ ብመልስልሽም የምትፈይጅልኝ ነገር የለም፡፡ ህመሜን ላትታመሚልኝ፤ ይሄን አመመኝ ብልሽ ምን ይጠቅመኛል?”
“ቢሆንም፤ እምንዎ ላይ ነው?”
“እኔም አንቺም ያለን ቦታ ላይ ነው”
“አንገትዎ ላይ?”
“አደለም”
“ብብትዎ ውስጥ?”
“አይደለም”
“ንፍፊትዎ ላይ?”
“ደርሰሻል፣ ግን አደለም”
“አይ እንግዲህ፤ እራስዎ ይንገሩኝ?”
“ታፋዬ ላይ ነው ያመመኝ”
“እንዴት አመመዎት?”
“ብጉንጅ ወጥቶብኝ”
“በሞትኩት አለቃ አሁን እንዴት ሊተኙ ነው?”
“አንቺ እንዳልሽ!”
“እርሶ ደግሞ በቁም ነገር ላይ ቀልድ ይጨምራሉ”
“አይ የኔ ቆንጆ እሱም ተጨምሮ በገባሽና እሺ ባልሺኝ”
“እርሶ ጉደኛ ነዎት እናቴ! በሉ እግዜር ምህረቱን ይላክልዎት!” ብላ ለመሄድ ስትነሳ፤
“እንዳፍሽ ያርግልኝ!” አሏት፡፡
ወጥታ ሄደች፡፡ አለቃን የሚያውቅ የሠፈር ሰው ስትወጣ መንገድ አገኛትና፤
“አለቃን ጠይቀሽ መውጣትሽ ነው?”
“አዎን”
“ምን አሉሽ?”
“ብንጉጅ ታፋዬ ላይ አብጦ ነው አሉ፡፡ እግዚአብሔር ይማርዎት አልኳቸው “እንዳፍሽ ያርግልኝ” አሉኝ፡፡
ሰውዬው ከት ብሎ ስቆ፤
“አዬ ቀልደው ብሻል - እንዳፍሽ ሙጥሙጥ ያርግልኝ ማለታቸውኮ ነው” አላት
ሴትዮዋ ተናዳ ወደ አለቃ ተመለሰችና
“እንዴት እንዲህ ይሰድቡኛል አለቃ” ብላ ጠየቀች፡፡
“ለዚህ ነው የመጣሽ? “አይ እህቴ ልሰድብሽ ብፈልግ ኖሮማ ‘ሞጥሟጣ’ እልሽ ነበር” አሏት፡፡
                                                   * * *
ህመም ለህመም ካለመደማመጥ ይሰውረን፡፡ የተነገረንን ሳንረዳ በየዋህነት ከመሄድ ያውጣን፡፡ የሚነገርና የማይነገር ህመም ከማማረጥ ያድነን፡፡ ህመማችንን ተጋግዘን ከማዳን በሽሙጥና በወፍ አፍ ስንሸነጋገል፤ በሽታችን ካንሰር - አከል እንደሚሆን ማስተዋል ይገባናል፡፡
የፖለቲካ በሽታችን የጋራ መተሳሰብ ይፈልጋል፡፡ የኢኮኖሚ ድቀታችን የጋራ መደጋገፍ ይጠይቃል፡፡ ማህበራዊና ባህላዊ አኗኗራችን ለውጥ - ተኮርና አፈር - አቀፍ መሆንን ይሻል፡፡ አያሌ ብሔራዊና ሀገራዊ አጀንዳዎች ስላሉን፤ “አውቀን በድፍረት፣ ሳናውቅ በስህተት” የምናሳየው ቸልተኝነት የሀገራችንን ዕድገት እያዘገየን እንደሆን የመገንዘቢያ ሰዓት ነው!!
የቻይና መንግሥት ብሔራዊ ፍልስፍና ይበጀን ከሆነ ለእኛ እንደሚያመች አድርገን የማንወስድበት ምክንያት የለም፡፡ ሶስቱ ጭብጦቹ ሀ) ህግና ደምቦችን (በሶሺዮ - ኢኮኖሚ ደረጃችን አኳያ) በሚገባ ሥራ ላይ ማዋል፤ ለ) ገንዘብን ለሀገር ጥቅም በሚውልበት አኳያ መጠቀም፤ ሐ) ሁነኛ ባለሙያዎችን በሁነኛ ቦታ አስቀምጦ ማሠራት፤ ናቸው፡፡
በተለይ የሶስተኛው መርህ ትርጉም የሚኖረው፤ ሁነኛ ባለሙያ ማለት ቦታው ከሚፈልገው ያነሰ (Underqualified እንዲሉ) ብቻ ሳይሆን፣ ቦታው ከሚፈልገው በላይ (Overqualified እንዲሉ) መሆን፤ የየራሱ አበሳ አለው፡፡ አንዳንዴ “ቦታው ራሱስ አስፈላጊ ነወይ?” ብሎ መጠየቅም ያባት ነው፡፡
ተቃዋሚ ብለን ከፈረጅናቸው ወገኖች ጋር አብሮ የመሥራት እሳቤ ከሀገር ፋይዳው አንፃር መጤን ይኖርበታል፡፡ የሚሞሉት ክፍተቶች/ቀዳዳዎች በርካታ ናቸው፡፡ የአንድ ወገን ርብርቦሽ ብቻ አይሞላቸውም፡፡ እነዚህን ክፍተቶች ሙሉ በሙሉ ለመገላገልና ፍሬ ለማፍራት የሚጠብቀን መንገድ ቀላል አይደለም፡፡ ፍሬ የራሱ ባህሪ አለው፡፡ ያገራችን ገጣሚ እንዳለው
“ፍሬ በስሎ እሚበላው
…ወይ በራሱ ጊዜ ሲወድቅ፣ ወይ እኛ ስንለቅመው ነው!”
መረጃ ለህዝብ መስጠት መፍትሔ ለማግኘት የሚያስችል አጋዥ መሣሪያ ነው፡፡ መብራት ሲበላሽ ምክንያቱን ለህዝብ መንገር ነው፡፡ ኔት - ዎርክ እምቢ ሲል ምን እንደሚሆን ማንም ለመገመት አያቅተውም፡፡ መግለጽ ነው ችግሩ የደም - ሥሮቹ ይደፋፈናሉ፡፡ ሥራዬ ብሎ አትኩሮ ማየት ይገባል፡፡ ደህና መሥመር የያዙ ጉዞዎች ይወለጋገዳሉ፡፡ ሲከፋም ይበጣጠሱና ወደኋላ ይመልሱናል! የውስጥ ደም - መፍሰስ (Internal - bleeding) እያለ አዲስ ደም - ቅያሬ (New - blood - injection) ሙሉ በሙሉ ይሠራል ብሎ ማሰብ ቢያንስ የዋህነት ነው!
የህዝብ ድጋፍ ወሳኝ መሆኑን ምንጊዜም መዘንጋት አይገባም፡፡ ይሄን ለማየት የኢትዮጵያ ህዝብ ለስፖርተኞቻችን የሚሰጠውን ማበረታታትና ጭንቀት ማስተዋል ነው፡፡ በአንድ ጀንበር ሳይሆን የረዥም ጊዜ ውጣ ውረዱን አስቦ፣ ታግሶ፣ ሆደ - ሰፊ ሆኖ፣ ሌሎች የሚሉትን በጥሞና አድምጦ መሄድ ውጤት ላይ እንደሚያደርስ መገንዘብ ዋና ነገር የፖለቲካውን መድረክና የኳሱን ሜዳ አመሳስሎና አነፃጽሮ መሄድ አገራችንን ለመለወጥ በር ከፋች መንገድ ነው፡፡
ሕግ፣ ዳኛ፣ አራጋቢ፣ ተመልካች፣ አሰልጣኝ…አዳጊና ወራጅ ቀጠና …የፌዴሬሽን ሥርዓት… ልብ ላለ - መሬት ለረገጠ ለውጥ - ማስገንዘቢያዎች ናቸው!
(ለብሔራዊ ቡድናችን ቀናውን ሁሉ እንመኛለን!)
ሀገራዊ በሆነ ጉዳይ ፍፁም አንድነቱን ይሰጠን ዘንድ ዐይናችንን ከፍተን የሀገርን ደግ እንይ! አለበለዚያ፤ “እናታቸው አንድ ያልሆነች ልጆች - አንዱ “ቁይልኝ”፣ አንዱ “አንጉችልኝ” ይሆናል፡፡ ከዚህም ይሠውረን!

                ከዛጒዌ ስመ ጥር ነገሥታት አንዱ በነበሩት በንጉሥ ይምርሐነ ክርስቶስ ዘመነ መንግሥት ከተሠሩት ኪነ ሕንጻዎች አንዱ የኾነው ይምርሐነ ክርስቶስ፤ የወርልድ ሞኑመንትስ ፈንድ የ2014 ተተኳሪ መካነ ቅርስ (2014 World Monuments Watch) ሆኖ ተመረጠ፡፡
ፈንዱ መስከረም 28 ቀን 2006 ዓ.ም. ዋና ጽ/ቤቱ በሚገኝበት በኒው ዮርክ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳስታወቀው÷ እ.አ.አ በ2014 ዓለም በትኩረት ሊያውቃቸው፣ ሊጠብቃቸውና ለትውልድ ሊያስተላለፍላቸው ይገባል ካላቸው የ41 አገሮች ባህላዊና ታሪካዊ ቅርሶች መካከል ልዩ የኪነ ሕንጻ ጥበብ የሚታይበት የይምርሐነ ክርስቶስ መካነ ቅርስ አንዱ ኾኖ መመረጡ ተገልጧል፡፡
“ወርልድ ሞኑመንትስ ዎች” በተሰኘው ፕሮግራሙ ለአደጋ የተጋለጡና ዝነኛ የቱሪስት መስሕብ የኾኑ ታሪካዊ ኪነ ሕንፃዎችንና ባህላዊ መካነ ቅርሶችን በማስተዋወቅ፣ የቴክኒክና የገንዘብ ድጋፍ በመለገሥ ዘመን ተሻጋሪ እንዲኾኑ ዓለም አቀፍ ቅስቀሳ የሚያደርገው ወርልድ ሞኑመንትስ ፈንድ፣ በዝርዝሩ ያካተታቸው የተመረጡ ቅርሶች ዓለም አቀፍ ትኩረት እንዲያገኙና በአግባቡ እንዲጠበቁ በዓለም ዙሪያ ያሉ ባለድርሻ አካላት ሁሉ አስተዋፅኦ እንዲያበረክቱ ጥሪውን አስተላልፏል፡፡
በዩኔስኮ የተመዘገቡ በርካታ የዓለም ቅርሶች የፈንዱ ተጠቃሚ ሲኾኑ ከእኒህም መካከል ፈንዱ እ.ኤ.አ በ1966 ሲቋቋም የክብካቤና ድጋፍ ሥራውን የጀመረባቸው የቅዱስ ላሊበላ ውቅር አብያተ መቅደስ እንደሚገኙበት በመግለጫው ተመልክቷል።
የይምርሐነ ክርስቶስ መካነ ቅርስ በዓለም አቀፍ ፈንዱ ተመራጭ እንዲኾን በመጠቆምና ለምርጫው የሚያግዙ መረጃዎችን በማቅረብ ከፍተኛ ሚና መጫወቱን ለአዲስ አድማስ የገለጸው የኢትዮጵያ ታሪካዊ ቅርሶች ክብካቤና ልማት ማኅበር፤ መካነ ቅርሱ የ2014 የወርልድ ሞኑመንትስ ፈንድ ተመራጭ መኾኑ ኪነ ሕንጻውን የበለጠ ለማስተዋወቅና ለማልማት ዕድል ይሰጣል ብሏል፡፡ ቅርሶች ዘላቂ ምጣኔ ሀብታዊና ማኅበራዊ አገልግሎት ያበረክቱ ዘንድ ራእይ የሰነቀው ሀገር በቀል ማኅበሩን ጨምሮ በቅርስ ክብካቤ ዙሪያ የሚሠሩ ባለሞያዎች፣ የሥራ ሓላፊዎችና ድርጅቶች ከሚመለከታቸው የብዙኀን መገናኛና ሌሎች አካላት ጋራ በመተባበር እንንዲንቀሳቀሱም ምቹ ኹኔታ ይፈጥራል ተብሏል፡
ከዘጠኝ መቶ ዓመታት በፊት በሰሜን ወሎ ወግረ ስኂን በሚባል ቦታ ሰፊና ግርማ ሞገስ ባለው የተፈጥሮ ዋሻ ውስጥ በውኃ ላይ እንደታነፀ የሚታመነውና ልዩ የኪነ ሕንፃ ጥበብ የሚታይበት ይምርሐ ክርስቶስ÷ በአገራችን ረጅም ዕድሜ ያስቆጠረውን የቤተ መንግሥት ሕንጻ፣ በድንቅ ጥንታዊ ሥዕሎችና ንድፎች ያሸበረቀ ቤተ መቅደስ አሰናኝቶ የያዘ መካነ ቅርስ ነው፡፡ በተጨማሪም ልዩ ልዩ ተንቀሳቃሽ ቅርሶች፣ ያልፈረሱና ዕድሜ ጠገብ የሰው ዐፅሞች፣ የሀገር በቀል ዕፀዋት ጥቅጥቅ ደንና ማራኪ መልክአ ምድር የሚገኙበት ነው፡፡

 

               ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር (አይ.ኤ.ኤ.ኤፍ) በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ለ2013 የዓለም ኮከብ አትሌቶች ምርጫ በሁለቱም ፆታዎች የሚፎካከሩ እጩዎችን ስም ሲያስታውቅ ከእጩዎቹ መካከል ሶስት የኢትዮጵያውያን አትሌቶች ተካትተዋል፡፡ መሃመድ አማን ፤ ጥሩነሽ ዲባባ እና መሠረት ደፋር ናቸው፡፡ አትሌት መሃመድ አማን በ800 ሜትር የዓለም ሻምፒዮን ከመሆኑም በላይ በርቀቱ የዳይመንድ ሊግ አሸናፊ ለመሆን የበቃ እና በዓመቱ ካደረጋቸው 11 ውድድሮች አስሩን ያሸነፈ ነው፡፡ ዘንድሮ በ5ሺ ሜትር የዓለም ሻምፒዮን ለመሆን የበቃችው አትሌት መሰረት ደፋር በርቀቱ የዳይመንድ ሊግ አሸናፊ እንደሆነች ሲታወቅ በ3ሺ ሜትር እና በ10ሺ ሜትር የዓመቱን ፈጣን ሰዓት በማስመዝገብ ተሳክቶላታል፡፡ አትሌት ጥሩነሽ ዲባባ በበኩሏ በ10ሺ ሜትር የዓለም ሻምፒዮን ከመሆኗም በላይ በ10 ኪሎሜትር የዓመቱን ፈጣን ሰዓት አስመዝግባለች፡፡

በኮከብ አትሌት ምርጫው በሁለቱም ፆታዎች ለመጨረሻ ምዕራፍ የሚደርሱትን ሶስት እጩ ተፎካካሪዎች ለመለየት በድረገፅ በሚሰጥ የድጋፍ ድምፅ ይሰራል፡፡ የዓለም የአትሌቲክስ ማህበረሰብን በማሳተፍ የሚከናወነው የምርጫ ሂደት ከተጀመረ ሶስት ቀን አልፎታል፡፡ ለሶስቱ የኢትዮጵያ ምርጥ አትሌቶች በዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ድረገፅ (www.iaaf.org) አስፈላጊ የሆነውን ድምፅ በመስጠት ድጋፍ ሊሰጥ ይቻላል፡፡ እድሉ ለሚቀጥሉት ሶስት ሳምንታት ክፍት ሆኖ ይቆያል፡፡ በዓለም ኮከብ አትሌቶች ምርጫ ታሪክ ሶስት ኢትዮጵያውያን አትሌቶች ተሸላሚ ሆነው ያውቃሉ፡፡ እነሱም በ1998 እኤአ የተሸለመው ኃይሌ ገብረስላሴ፤ በ2004 እና በ2005 እኤአ አከታትሎ ያሸነፈው ቀነኒሳ በቀለ እና በ2007 እኤአ ላይ የተመረጠችው መሰረት ደፋር ናቸው፡፡