Administrator

Administrator

በ14ኛው የዓለም አትሌቲክስ ሻምፒዮና መሀመድ አማን፤ የ800 ሜትር ውድድሩን በአስደናቂ የአጨራረስ ብቃት አጠናቆ የወርቅ ሜዳልያውን ከወሰደ በኋላ፣ መደበኛው ጋዜጣዊ መግለጫ የሚሰጥበትን አዳራሽ ያጣበብነው አምስት የኢትዮጵያ ጋዜጠኞች እና የብሄራዊ ቡድኑ ሃኪም ዶክተር አያሌው ነበርን፡፡ ውድድሩ ተጠናቅቆ ከምሽቱ ለአምስት ሰዓት ምናምን ጉዳይ ላይ ነው፡፡ በመሃመድ ታሪካዊ ድል ደስታችን ልክ አልነበረውም፡፡

በፕሬስ ኮንፍረንሱ አዳራሽ የተገኘነው ከየትኛውም አገር ጋዜጠኞች ቀድመን ነበር፡፡ መሃመድ አማን በ800 ሜትር ያስመዘገበው የወርቅ ሜዳልያ፣ በኢትዮጵያ አትሌቲክስ ፈርቀዳጅ ታሪክ መሆኑን፤ በሻምፒዮናው ታሪክ በ20 ዓመቱ የርቀቱን የወርቅ ሜዳልያ ለመውሰድ የበቃ ድንቅ አትሌት እንደሆነ ጋዜጠኞች ስንነጋገር፣ ዶክተር አያሌው መሃከል ገቡና፣ መሃመድ ለ800 ሜትር እና ለአጭር ርቀት ውድድር የተፈጠረ ምርጥ አትሌት መሆኑን በመጠቆም፣ በስፖርቱ ውጤታማ ለመሆን ባለው የስራ ፍቅርና ትጋት እንደሚያደንቁት ገለፁልን ፡፡ ውይይታችን በስፍራው የነበሩ የሌላ አገር ጋዜጠኞች እና የስፖርት ባለሙያዎችን ትኩረትም ስቦ ነበር፡፡
በፕሬስ ኮንፍረንሱ አዳራሽ ከመሃመድ አማን በፊት መግለጫ የሚሰጡ የሌላ ውድድር አሸናፊዎች ነበሩ፡፡ የዲስከስ ውርወራ እና የሄፕታትሎን ተወዳዳሪ የነበሩ ናቸው፡፡

የሁለቱ ስፖርቶች አሸናፊዎች መግለጫዎች ሲሰጡ ኢትዮጵያውያኑ ባይተዋር ነበርን ማለት ይቻላል፡፡ ለነገሩ በረጅም ርቀት እንጂ በ800 ሜትር ኢትዮጵያዊ አትሌት አሸንፎ ለጋዜጣዊ መግለጫ እንበቃለን ብለን አስበንም አልመንም አናውቅም፡፡ የወንዶች ዲስከስ ውርወራ አሸናፊዎች እና የሴቶች ሄፕታተሎን ውድድር ሜዳልያ ተሸላሚዎች መግለጫ ከተጠናቀቀ በኋላ፣ ተራው የእነ መሃመድ አማን ሆነ፡፡ ወደመግለጫው የገቡት የወርቅ ሜዳልያውን የወሰደው መሃመድ አማን፤ የብር እና የነሐስ ሜዳልያውን የወሰዱት የአሜሪካ አትሌቶች ነበሩ፡፡ መሃመድ አማን የወርቅ ሜዳልያውን ያስመዘገበው የሉዝንስኪ ስታድዬም በምርኩዝ ዝላይ ተወዳዳዳሪዋ ራሽያዊት ዬለና ኢዝንባዬቫ ምክንያት ጥቅጥቅ ብሎ በሞላበት ወቅት ነበር፡፡

መሃመድ አማን በ800 ሜትር ያሸነፈው በጣም ጠንካራ አትሌቶች በተሳተፉበት የ800 ሜትር የፍፃሜ ውድድር ሲሆን ርቀቱን የሸፈነበት 1ደቂቃ ከ43.31 ሰኮንዶች የውድድር ዘመኑ ፈጣን ሰዓት ሆኖ ተመዝግቧል፡፡ መሃመድ አማን በ5ሺ፤በ10ሺ እና በማራቶን ውድድሮች ስኬታማ አትሌቶች ከበዙባት ኢትዮጵያ መውጣቱ እያነጋገረ ሲሆን ከአጭር ርቀት ሯጭነት ወደ መካከለኛ ርቀት ምርጥ አትሌትነት መሻገሩም ያልተጠበቀ ነው ተብሏል፡፡
ከሁሉ የሚገርመው ደግሞ መሃመድ አማን መግለጫውን የሰጠው በእንግሊዘኛ መሆኑ ነው፡፡ ይሄም ሌላ ያልተጠበቀ ነገር ሆኗል፡፡ እስካሁን ኢትዮጵያውያኑ አትሌቶች በአስተርጓሚ ነበር ጋዜጣዊ መግለጫ የሚሰጡት፡፡ የእንግሊዝኛ ቋንቋ ችሎታውን ፊልሞች በመመልከት እና በማንበብ ነው ያዳበረው፡፡ ለመሃመድ የቀረበለት የመጀመርያው ጥያቄ ከመግለጫው መሪ የአይኤኤኤፍ ጋዜጠኛ ነበር፡፡
“መሃመድ ውድድሩ አስቸጋሪ ነበር፤ በሩጫው መሃል ወደ ኋላ ቀርተህ ከዚያ በኋላ ነው አፈትልከህ የወጣኸው፡፡ ስትራቴጂው ምን ነበር?” ሲል ጠየቀው፡፡
“የፍፃሜ ውድድር ነው፡፡ ስለዚህም ለማሸነፍ የተከተልኩት ስትራቴጂ ተገቢ ነው፡፡ በፍፃሜ ውድድር የሚሳተፉት ሁሉም አትሌቶች ምርጥ ብቃት እንዳላቸውና የማሸነፍ እድል እንደሚኖራቸው ግምቱ ነበረኝ፡፡ እስከመጨረሻዎቹ ሜትሮች ሁኔታውን እያጠናሁ በትዕግስት ተጠባብቄያለሁ፡፡ ከዚያም በአስፈላጊው ጊዜ አፈትልኬ ወጥቻለሁ፡፡›› በማለት መሃመድ ምላሹን ሰጥቷል፡፡
ቀጣዩ ጥያቄ ከፕሬስ ኮንፍረንሱ የመድረክ መሪ የቀረበ ሲሆን ያሸንፋል የሚል ግምት ለተሰጠው አሜሪካዊው ኒክ ሳይመንድስ እና ለነሐስ ሜዳልያው ባለድል የጅቡቲ አትሌት ነበር፡፡ “ኒክ ሳይመንድስ” በብር ሜዳልያው መወሰንህ ምን ስሜት ፈጠረብህ?” ተብሎ ለተጠየቀው ሲመልስ፤
‹‹በብር ሜዳልያው በጣም ደስተኛ ነኝ፤ ውድድሩ ሜትር እስኪቀረው ቀጣዩ የዓለም ሻምፒዮን መሆኔን እያሰብኩ ነበር፡፡ ግን አልሆነም፡፡ ባገኘሁት የብር ሜዳሊያ ብዙም አልተከፋሁም›› ያለ ሲሆን የነሐስ ሜዳልያ ባለቤቱ ጅቡቲያዊ በበኩሉ፤ ‹‹ደስተኛ ነኝ፤ ለአገሬ የተገኘ ብቸኛ እና የመጀመርያው ሜዳልያ ነው፡፡ ውጤቱ በጠንካራ ፉክክር የተገኘ በመሆኑም አኩርቶኛል›› በማለት መልሷል፡፡
ለመሃመድ አማን “በአገርህ ለወርቅ ሜዳልያ መጠበቅህ የፈጠረብህ ጫና ነበር ወይ” የሚል ጥያቄ ከኢንተር ስፖርት ዋና አዘጋጅ እና የአትሌቲክስ ዘጋቢ ብዙአየሁ ዋጋው ቀርቦለት ነበር፡፡
‹‹ኢትዮጵያ በረጅም ርቀት እና በማራቶን ውድድሮች ውጤታማ በሆኑ በርካታ አትሌቶቿ ትታወቅ ነበር፡፡ እኔ በአጭር ርቀት ውጤታማ በመሆኔ ብዙ ጫና አልነበረብኝም፡፡ እንዴት እንደሆነ አላውቀውም፡፡ ከፍተኛ በራስ የመተማመን ስሜት አለኝ፡፡ አራት የዳይመንድ ሊግ ውድድሮችን ማሸነፍ መቻሌ በጣም ልበ ሙሉ አድርጎኛል፡፡ የዓለም ሻምፒዮና ጠንካራ ፉክክር ያለበት ነው፡፡ በጥንቃቄ መሮጥ ያስፈልግ ነበር፡፡
ስለውድድሩ ላለመጨነቅ ስል ብዙ ሃሳብ ውስጥ አልገባሁም፡፡ ለጥ ብዬ እንቅልፌን ተኛሁ፡፡ አሰልጣኜ ስልክ ደውሎ ምን እየሰራህ ነው አለኝ፡፡ ስለ ውድድሩ ከማሰብ ጥሩ እረፍት እንደሚያስፈልገኝ አምኜበት መተኛቴን ነገርኩት” በማለት ምላሹን ሰጥቷል፡፡
የኢቴቪ ስፖርት ጋዜጠኛ እና የኢትዮጵያ የስፖርት ጋዜጠኞች ማህበር ፕሬዝዳንት ዮናስ ተሾመ በበኩሉ፤ “ለኢትዮጵያ አትሌቲክስ አዲስ ታሪክ ሰርተሃል፡፡ በአጭር ርቀት በአለም ሻምፒዮና የተመዘገበ ብቸኛ ድል ነው፡፡ ምን ተሰማህ?” የሚል ጥያቄ አቅርቦለታል፤ ለአትሌቱ፡፡
መሃመድ ሲመልስም፤ ‹‹ምንም የማይቻል ነገር የለም፡፡ ድል እንደማደርግ እምነት ነበረኝ፡፡ ያስመዘገብኩት ውጤት ትልቅ ታሪክ ነው፡፡ ለዚህ ስኬት የመጀመርያው በመሆኔም በጣም ደስተኛ ነኝ፡፡ ልምምዴን የምሰራው በኢትዮጵያ ነው፡፡ በእንጦጦ፣ በሰንዳፋና በአዲስ አበባ ዙርያ፡፡ በአዲስ አበባ ከሚገኙ በርካታ የብሄራዊ ቡድን አትሌቶች ጋር ነው የምሰራው፤ አሰልጣኜም ኢትዮጵያዊ ንጉሴ ጌቻሞ ነው፡፡ ›› በማለት አስረድቷል፡፡
እኔ ደግሞ እንዲህ ስል ጠየቅሁት፤ “በ800 ሜትር የዓለም ሪከርድ የያዘው፤ የዓለምና የኦሎምፒክ ሻምፒዮን የሆነው ኬንያዊው ዴቪድ ሩዲሻ ቢኖር የወርቅ ሜዳልያው እድል የጠበበ ይሆን ነበር ብለህ አላሰብክም?”
‹‹በመጀመርያ እኔ ልምምድ ስሰራ የቆየሁት ለዴቪድ ሩዲሻ ብቻ አልነበረም፤ሩዲሻ ባለመኖሩ አዝኛለሁ፡፡ ጉዳት ለብዙ አትሌቶች ፈተና እየሆነ ነው፡፡ እሱ ባይኖር እንኳን ለፍፃሜ የደረሱት ሌሎቹ ሰባት አትሌቶች እጅግ ጠንካሮች ነበሩ፡፡ እነሱን በማሸነፌ ውጤቴን አስደሳች አድርጎታል፡፡› ሲል መለሰልኝ፡፡
በመጨረሻም ወደ አገሩ ሲመለስ ደስታውን እንዴት እንደሚያከብር ነበር የተጠየቀው፡፡ አማን ወደ ትውልድ ቀዬው አሰላ ለመሄድ የሚፈልገው በመስከረም ወር ዋዜማ በብራሰልስ ከሚያደርገው የዳይመንድ ሊግ ውድድር በኋላ ነው፡፡ ከብራሰልስ በኋላ በቀጥታ ወደ እናቱ ቤት ለመሄድ እቅድ ይዟል፡፡ ቤተሰቡ በዳጉ የዓለም ሻምፒዮና እና በለንዶን ኦሎምፒክ ሲሮጥ ተመልክተውታል፡፡ በሁለቱም ውድድሮች እንዲያሸንፍ ጠብቀው አልተሳካለትም፡፡ አሁን ግን የልባቸውን አድርሶላቸዋል፡፡ የቤተሰቡን ብቻ ሳይሆን የመላው ኢትዮጵያዊያንን፡፡ ከብራሰልስ መልስ የዓለም ሻምፒዮና ድሉን ከወላጆቹ እና ከመላው ቤተሰቡ ጋር በፌሽታ እንደሚያከብር አማን በፈገግታ ተሞልቶ ገልፆልናል፡፡ አንድ ፌሽታ ሳይሆን ሺ ፌሽታ ይገባዋል፡፡

የደራሲ ሌሊሳ ግርማን ምርጥ ምናባዊ ታሪኮች የያዘው “መሬት ፣አየር፣ሰማይ” መፅሀፍ ለንባብ በቃ፡፡ ከምናባዊ ታሪኮቹ አንዳንዶቹ በአዲስ አድማስ ጋዜጣ የጥበብ አምዶች ላይ የተስተናገዱ ናቸው፡፡ ሃያ ዘጠኝ ታሪኮችን የያዘው ባለ 207 ገፅ መፅሀፉን ሊትማን ጀኔራል ትሬዲንግ የሚያከፋፍለው ሲሆን ዋጋውም 46 ብር ነው፡፡ ደራሲ ሌሊሳ ግርማ ቀደም ሲል “የንፋስ ህልም” እና “አፍሮጋዳ” የተሰኙ መፅሃፍት ለንባብ አብቅቷል፡፡

ባህላዊውን የቡሄ አከባበር የሚዘክርና ሀይማኖታዊና ባህላዊ ይዘቱ ሳይቀይር በዓለም ቅርስነት የሚመዘገብበትን ዘዴ የሚያውጠነጥን ዝግጅት የፊታችን ሰኞ ምሽት እንደሚቀርብ ኤልቤት ሆቴል አስታወቀ፡፡ የሆቴሉ ስራ አስኪያጅ የእናትፋንታ ውቤ እንዳስታወቁት፤ ፒያሳ በሚገኘው ሆቴል፣ ዝግጅቱ በችቦ ማብራትና ባህሉን የጠበቀ ህብስት ታጅቦ ሲቀርብ ቡሄን የተመለከቱ ሁለት ጥናታዊ ፅሁፎች የሚቀርቡ ሲሆን የኢትዮጵያ ደራሲያን ማህበር ስራ አስፈፃሚ አባል ደራሲ አፈወርቅ በቀለ የጥንቱን የቡሄ ባህል በተመለከተ የልጅነት ትዝታውን በሆቴሉ ለሚገኙት ሰዓሊያን ፣ደራሲያንና ሌሎች እንግዶች ያጋራል፡፡

 

የአማራ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ሰራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ቢሮ እና በባህርዳር የሚገኘው የሙላለም የባህል ማዕከል ሚሊኒየሙ የባህል ቡድን በጋራ ያዘጋጁት ህገወጥ የሰዎች ዝውውርን የሚያወግዝ ኪነጥበባዊ ፕሮግራም እየቀረበ ነው፡፡
የዛሬ ሳምንት በባህርዳር መቅረብ የጀመረው ዝግጅት፤ ግጥሞች፣ሙዚቃ፣ የ25 ደቂቃ ድራማ እንዲሁም ውይይት ተካሂዶበታል፡፡ ተመሳሳይ ዝግጅቶችን የችግሩ ሰለባ በሆኑ ዞኖች እንቀጥላለን ያሉት የባህል ማዕከሉ የፕሮሞሽን ቡድን አስተባባሪ አቶ ሰለሞን ታደሰ ከሌቻ፤ ተዘዋዋሪ የኪነጥበብ ዝግጅቱ ለውጥ ያመጣል ተብሎ ተስፋ እንደተጣለበት ተናግረዋል፡፡ ዝግጅቱ ከሚቀርብባቸው ከተሞች መካከል ወልዲያ፣ወረኢሉ፣መተማ እና ከሚሴ ይገኙበታል፡፡

በቀድሞ የኢትዮጵያ ፕሬዝዳንት መንግስቱ ኃይለማርያም የቤተመንግስትና የስራ ህይወት ዙሪያ የተፃፈው “የሌ/ኮ መንግስቱ ያልተነገሩ ሚስጥሮች” የተሰኘ መፅሀፍ ዛሬ ከማተሚያ ቤት ወጥቶ ለንባብ እንደሚበቃ አዘጋጁ አስታወቁ፡፡ የቀድሞው ልዩ ኃይል አባል እና የፕሬዝዳንት መንግስቱ አጃቢ በነበሩት እሸቱ ወንድሙ ወልደስላሴ የተፃፈው ባለ 120 ገፅ መፅሃፍ ዋጋ 35 ብር ከ45 ሳንቲም ነው፡፡ ለ14 ዓመታት በልዩ ጥበቃነት የሰሩት የመፅሃፉ አዘጋጅ፤ ካሁን ቀደም “ህይወት በመንግስቱ ቤተመንግስት” በሚል ርዕስ ሁለት ቅፅ መጻሕፍትን ያሳተሙ ሲሆን ባሁኑ መፅሀፍ ከተካተቱ ጉዳዮች መካከል መንግስቱ የ1981ዱ መፈንቅለ መንግስት አድራጊዎችን ምን እንዳሏቸው፣ ፕሬዝዳንቱ በትረመኮንናቸው ላይ ብእር መሰል ሽጉጥ እንዲሰራላቸው መጠየቃቸው ወዘተ…ይገኝበታል፡፡

የአዲስ አድማስ ፎቶ ጋዜጠኛ የሆነው አንተነህ አክሊሉ ያነሳቸው ከ30 በላይ ፎቶግራፎች የተካተቱበት “ላይት ኢን ሻዶው” የፎቶግራፍ አውደርእይ ካዛንቺስ በሚገኘው ኦዳ ታወር የፊታችን ሐሙስ ከምሽቱ 12 ሰዓት እንደሚከፈት አዘጋጁ አስታወቀ በኦዳታወር ሶስተኛ ፎቅ በቅርቡ በተከፈተው ኮክ ቺክን ባር እና ሬስቶራንት የሚከፈተው አውደርእይ “ጥበብ፣ ከተማና ገጠር” በሚል መሪ ቃል የሚካሄድ ሲሆን ባለፉት ሰባት ዓመታት ፎቶግራፈሩ በሀገሪቱ የተለያዩ ክፍሎች ተዘዋውሮ ያነሳቸው ምርጥ ፎቶግራፎች ይካተቱበታል፡፡ የፎቶግራፍ ኤግዚብሽኑ እስከ ነሐሴ 20 ለሕዝብ ክፍት ሆኖ ይቆያል፡፡

 

የግእዝ ቋንቋ እንዲያንሰራራ ያለመ ኪነጥበባዊ ዝግጅት ነገ ማምሻውን በቅድስት ሥላሴ መንፈሳዊ ኮሌጅ እንደሚካሄድ አዘጋጆቹ አስታወቁ፡፡ በኮሌጁ የምግብ አዳራሽ የሚቀርቡትን ድራማ፣የጥንታዊ ፅሁፎች ንባብ ፣ቅኔ፣ የግዕዝ ግሰሳ (ትንተና) ፣ጭውውትና ዜናን በግእዝ  የኮሌጁ የግእዝ ቋንቋ ተማሪዎች እና ሌሎች ተጋባዥ እንግዶች በህብረት እንደሚያዘጋጁት የጠቀሰው የአዘጋጆቹ መግለጫ፤ ለግእዝ ቋንቋ እና ለኢትዮጵያ የቀድሞ ስልጣኔ አክብሮት ያላቸው ወገኖች ሁሉ በነፃ ዝግጅቱን መከታተል እንደሚችሉ አብስሯል፡፡ የኮሌጁ የግእዝ ክፍለ ትምሕርት ኃላፊ መምህር ዘርአዳዊት አድሓና ስለጉዳዩ ማብራሪያ ጠይቀናቸው፤ ኮሌጁ ከ2002 ዓ.ም ጀምሮ ቋንቋውን በዲፕሎማ ደረጃ እያስተማረ መሆኑን ገልፀው “በየዓመቱ ደብረ ታቦር ሲከበር ክርስቶስ ለተማሪዎች ምስጢር መግለጡን አስታውሰን ከአብነት ትምህርት ቤቶችን በወረስነው ትውፊት ከበዓለ ደብረታቦር ጋር እናከብረዋለን” ብለዋል፡፡

Saturday, 17 August 2013 11:21

የአገር ሰምና ወርቅ 

ልለምንህ ጣና - ልማጠንህ ዓባይ - አዋሽ እሺ በለኝ
አገሬ ተድራ - አገር ጠርቻለሁ - የአገር ድግስ አለኝ፤
አገሩን የዳረ - አገር ህዝብ የጠራ
ለአገር የጠመቀ - ለአገር የደገሰ፣
መሬቱ እንጀራው ነው - ሀይቁም ወይንጠጁ
መች ይጨንቀውና - ደረሰ አልደረሰ፤
ይኸው አገር መጣ!
ይኸው አገር ወጣ!
አገር ድግስ በይ - አገር ላይ የወጣ - አገር ሊያይ የመጣ
ብትታየው ጊዜ - አገር ሙሽራዬ - ከአገር ሁሉ በልጣ
አገር ልቡ ቆመ - አገር ማድነቂያ አጣ - አገር አቅም አጣ፡፡
ይኸው ይቺውልህ፤
በአገር ፍቅር ቬሎ - በአገር ሰረገላ
አገር ስትመዘን - በሰው ተመስላ
ይህን ታህላለች
ይህን ትመስላለች
በል ሀቅ እንፈልቅቅ - ከሯጭ ህብረ - ቀለም
በአትሌት ሰምና ወርቅ - በ‹‹ሀገር›› ቀልድ የለም!!
ለዚያም ነው ጥሩዬ
አገር በልቧ አዝላ - በአገር ተውባ
በአገራት ሙሽሮች - በአገራት ተከባ
በአገር አደባባይ - አገር ስታገባ
አገር ወዲያ ጥላ - ወደ አገር ስትገባ
አገር ምድሩ ያለው - ጉሮዬ ወሸባ!!
ነው እንጅ ነውና!!
‹‹ጥሩ›› አገር ብትሆን ነው - አገርን ያከለች - አገር የተሰጠች
ከአገር ተፎካክራ - አገር ያስከተለች - አገር የበለጠች!!
ይኸው ነው ቀለሙ - ይኸው ነው እውነቱ
እሷ ስታሸንፍ - እኛ ሁላችንም - የጨፈርንበቱ!!
ስማ ጋዜጠኛ፤
ይኸውልህ እውነት - የሀቅ ህብረ - ቀለም
በጥሩነሽ አገር - ስለ አገር ቀልድ የለም፡፡
ካላመንክ ጠይቃት - ከአንደበቷ ስማ
እንዲህ ትልሃለች - አገር አስቀድማ...
‹‹ለሌላ አገር አትሌት - እንኳን ሜዳሊያ - መጨረስም ድል ነው
ለኔ አገር ህዝብ ግን - ብር ሽንፈት ሲሆን - ነሀስም ውራ ነው፤
በቃ በኔ ሀገር - ድል ነው እሚባለው
ወርቁን ከነክብሩ - ያስገኘህ ጊዜ ነው!!››
ይህ ነው ሰምና ወርቅ - በጥሩነሽ አገር - የአገር ህብረ - ቀለም
ወርቅ ለለመደ - ነሀስ ግድ አይሰጥም - ብርም ድል አይደለም፡፡
ነሐሴ 5 - 2005 ዓ.ም
(ለአትሌት ጥሩነሽ ዲባባ የሞስኮ ድል)

(የሚከተለውን ተረት - መሰል ታሪክ ከዚህ ቀደም ትንሽ ለየት ባለ መልኩ ተርከነዋል፡፡ የሚሰማ ጠፍቶ ታሪክ ሲደገም በማየታችን ደግመን አቅርበነዋል፡፡)
አንድ ፀሐፊ እንዳለው “እኔን ቅር የሚለኝ ታሪክ መደገሙ ሳይሆን፤ በበለጠ አስከፊ መልኩ መደገሙ ነው” ይላል፡፡
ዕውነት ሆነው ከመቆየት ብዛት ተረት የሚሆኑ ታሪኮች አሉ፡፡
ባለፈው ሥርዓት፣ ከዕለታት አንድ ቀን የነበሩ፤ ሁለት የትግል ጓዶች ነበሩ አሉ፡፡ ከጊዜ ብዛት ተቃዋሚ ድርጅታቸውን ትተው ወደመንግሥት ለመግባት ተወያዩ፡፡
አንደኛው - “እረ ይሄ ድርጅታችን የሚመች አልመሰለኝም፡፡ አደጋው እየበዛ መጣ”
ሁለተኛው - “ዕውነትክን ነው፡፡ እኔም ከዛሬ ነገ ሁሉም ነገር ቅር እያለኝ መሆኑን፤ ልነግርህ
ሳስብ ነበር፡፡”
አንደኛው - “ታዲያ ከዚህ ወጥተን ለምን ወደመንግሥት አንገባም?”
ሁለተኛው - “ይሻለናል”
ተስማሙና ባንድ በሚያውቁት ሰው በኩል ወደ መንግሥት የፖለቲካ መዋቅር ገቡ፡፡ ጠርናፊያቸው አንድ የሚያውቁት ሻምበል ሆነ፡፡
የፖለቲካ ርዕዮተዓለምና አቋም ላይ ተወያዩ፡፡ ተዋወቁ፡፡ ተማማሉ፡፡ የትግሉ አካል ሆኑ፡፡ ንቃታቸው አስተማማኝ ነው፡፡ ቀድሞ በነበሩበት ድርጅት ውስጥ በቂ ንባብ አድርገዋል፡፡
እየነቁ እየተደራጁ ቀጠሉ፡፡ በመካከል ከሁለቱ አንደኛው ወደ ኪዩባ የመሄድ ዕድል ያጋጥመዋል፡፡
ኪውባ ሄዶ፣ ንቃቱን አዳብሮ፣ ትምህርት አበልጽጐ ወደሀገሩ ወደ ኢትዮጵያ ይመለሳል፡፡
ተንሰፍስፎ ያንን የትግል ጓዱን ይፈልገዋል፡፡ ተገናኙ፡፡
“እንዴት ነህ?” አለ ከኩባ የመጣው፡፡
“በጣም ደህና ነኝ፡፡ አንተስ?” አለ አዲሳባ የቆየው፡፡
“ኪውባ በጣም ድንቅ ነበር፡፡ ብዙ ጓዶች አፍርቻለሁ፡፡ የዳበረ ዕውቀት ይዤ መጥቻለሁ ብዬ አምናለሁ” አለው በነቃ ኩራት፡፡
“መልካም፤ በሚገባ ታወራኛለህ!”
“ለመሆኑ ሻምበልስ? ጤናውን እንዴት ነው?”
“ዉ! ሻምበልኮ ታሰረ” አለው እዚህ የቆየው፤ በሀዘንና እንጉርጉሮ ቃና አቀርቅሮ፡፡
ይሄኔ ከኩባ የመጣው በጣም ግራ ገባው፡፡ “እንኲን ታሰረ!” እንዳይል በሳል የማይል ጓዱ ነው፡፡ “ለምን ይታሰራል?” እንዳይል፤ የራሱንም ዕጣ - ፈንታ አያቅም፡፡ ስለዚህ ሲቸግረው፤
“አቤት የአብዮታችን ፍጥነት?!” አለ፤ ጭንቅላቱን በሁለቱ እጆቹ መካከል ቀብሮ፡፡
ጊዜ አለፈና እንደተባለው ሁለቱም ዕጣ - ፈንታቸው እሥር ቤት የሚከትታቸው ሆነና እሥር ቤት ተገናኙ፡፡ ለንፋስ ወጥተው የግል ጨዋታ ሲጨዋወቱ፤
አንደኛው - “እህስ ጓድ፤ አሁንስ የአብዮታችን ፍጥነት ምን ይመስልሃል?”
ሁለተኛው - “አይ ወዳጄ!! አሁንማ አንደኛውን ጄት ሆኖልሃል! ሁላችንንም ጠራርጐን
ገብቷል!” አለ፡፡
* * *
ከሁሉ ነገር በፊት ከመከዳዳት ይሰውረን፡፡ ስለሰው ትተን ስለአብዮታችን ፍጥነት የማናወራበት ጊዜ ይስጠን፡፡ ሁላችንንም ጠራርጐን ገባ የማንባባልበት፤ “ውሃ ሲወስድ አሳስቆን” የማንዘባበትበት ቀና ዘመን ያምጣልን፡፡
የሮጠ ሁሉ እንደማያሸንፍ የሰሞኑ አትሌቲክስ ያስተምረናል፡፡ ድል፤ ሰዓት ጠብቆ ሊቀያየር እንደሚችልም የሰሞኑ አትሌቲክስ ያስተምረናል፡፡ አንዳንዱ ገና ከጅምሩ ሊያቋርጥ እንደሚችል የሰሞኑ አትሌቲክስ ይነግረናል፡፡ ብዙውን የሩጫ ክፍል ሄዶ ሄዶ ማብቂያው ግድም መሸነፍ ሊኖር እንደሚችልም የሰሞኑ አትሌቲክስ አሳይቶናል፡፡ ቢደክሙም፣ ቢዝሉም፣ ውጣ - ውረዱ ከባድ ቢሆንም፤ ሳይታክቱ፤ በጽንዓት ሮጦ እድሉ አምባ ለመድረስ እንደሚቻልም የሰሞኑ አትሌቲክስ ያለጥርጥር አመልክቶናል፡፡
ከሁሉም በላይ ደግሞ ራስን በማዘጋጀት፣ በልበ - ሙሉነትና በብልህነት ጊዜና ቦታን ማወቅ ያለውን ፈትልና ቀስም የሆነ፤ ግንኙነትና ትስስር በአጽንኦት እንድናስተውል ታላቅ ተመክሮን አጐናጽፎናል፡፡ ሩጫ ትንፋሽ እንደሚጠይቅ፤ ትግልም ትንፋሽ ይጠይቃል፡፡ ሩጫ ጉልበት እንደሚፈልግ ትግልም ጉልበት ይፈልጋል፡፡ ሳይዘጋጁ የገቡበት ሩጫ ተሸናፊ እንሚያደርግ፣ ሳይዘጋጁ የገቡበት ትግልም ከተሸናፊነት ጐራ ያስፈርጃል፡፡ ሲሮጡ የታጠቁት ሲሮጡ ይፈታል፤ ይሏል፡፡ ተዘጋጅቶ የሩጫው ሰንበር ላይ ወጥቶም መቼ ማፈትለክ እንዳለብን ካላወቅን፤ የተሻለ ብልጠት ያለው እንደሚቀድመን ሁሉ፤ በትግል ሠፈርም ተዘጋጅቶ ገብቶ ጊዜን ባለማወቅ ሳቢያ፤ ብልጡ ይቀድመናል፡፡ ከሩጫው ሜዳ የተፎካካሪን ብስለትና ጥንካሬ አንዳንዴም ተንኮል ከቁጥር መጣፍ ወሳኝ ነው፡፡ አንዳንዱ ተንከባክቦ የያዘው ጥንካሬ አለው፡፡
ተጋትሮም ተስፈንጥሮም ኬላውን ሰብሮ፣ በጥንካሬው ይዘልቃል፡፡ አንዳንዱ በልምድ ያዳበረው ብስለት አለው፡፡ ስለዚህም የተፎካካሪውን አቅምና በብልህነት የሚጠቀምበትን የጊዜ ሰሌዳ፣ ይመዝናል፡፡ አንዳንዱ የሌሎችን የመሮጫ ረድፍ በመዝጋት፣ ሲመች ጭራሹን በመገፋተር በብልጠትና በተንኮል ይሮጣል፡፡ የባሰበት እስኪነቃበት ዕፅ ይጠቀማል፡፡ እነዚህ የሩጫ ስልቶች የፖለቲካ ስልቶቻችን ተመሳሳይ ገጽታዎች ናቸው፡፡ ሩጫችን ለድል ያበቃን ዘንድ ግብዓቶቹን ሁሉ በአግባቡ ማጤን ዋና ነገር ነው፡፡ “ፈጣን ነው ባቡሩ” እንደምንል ሁሉ፤ “ያልተመለሰው ባቡርን”፤ አልፈን ተርፈንም፤
“እልም አለ ባቡሩ
ወጣት ይዞ በሙሉ” ማለታችንን አንርሳ፡፡
“አወይ መሶሎኒ፤ አወይ መሶሎኒ
ተሰባብሮ ቀረ፣ እንደጃፓን ስኒ” የሚለውም አንድ ሰሞን መዝሙር ነበር፡፡
ይድነቃቸው ተሰማ አንድ ጊዜ ስለሱዳን የእግር ኳስ ቡድን መሻሻል ተጠይቀው፤ “ሱዳን ዘግታ ስትለማመድ ቆይታ፣ ራሷን አጠናክራ፣ ወደፊት መጣች፡፡ እኛ እንደዱሯችን ነው የቆየነው፡፡ በአጠቃላይ አነጋገር “ቆመን ጠበቅናቸው፤ ጥለውን አለፉ!” ብለዋል፡፡ ራስን ማጠናከር ዋና ነገር ነው፡፡
በህመምም፣ በአቅም ማነስም፣ “አውቀው በድፍረት ሳያውቁ በስህተት” ጥፋት ያጠፉም፣ በበላይ ተንኮልና ጥላቻም፣ በፓርቲ ምሥረታም፣ በመተካካትም ሰበብ ሰዎችን ስናገልል ከአጠቃላይ የአገሪቱ ዕጣ - ፈንታ ስዕል አኳያ ማየት ብልህነት ነው፡፡ በተዘበራረቁና በተወሳሰቡ ፖለቲካዊ ምክንያቶች ቂም መያዝ፣ መከፋፈል፣ አንድነትን ማናጋት፣ ወይም መሰነጣጠቅና “የትልቁ አሣ ትንሹን አሣ መዋጥ አባዜ” ማስተናገድ ክፉ ልማድ ነው፡፡ ይህ ልማድ እንዳይደገም “ሃናኔና ሃሪቴ የአምስት ሣንቲም ቅቤ ተካፍለው ሲቀቡ ውለው፣ ወደማታ በአምስት ሣንቲም ጐመን ይጣላሉ” የሚለውን የወላይታ ተረት ማስተዋል ደግ ነው፡፡

ዓላማውን ሕገወጥ የሰዎች ዝውውርን በመከላከል ላይ ያደረገው “ሚስ ዩኒቨርስ” የቁንጅና ውድድር፤ በመጪው መስከረም ወር ለሁለተኛ ጊዜ እንደሚካሄድ አዘጋጁ “ክሬቲቭ ኮሙኒኬሽን ኤንድ ኤቨንትስ” አስታወቀ፡፡ የውድድሩ ምዝገባና ፈተና ነሐሴ 11 እና 12 በፓኖራማ ሆቴል የሚካሄድ ሲሆን መስከረም 10 በራዲሰን ሆቴል በሚካሄደው የ“ሚስ ዩኒቨርስ” የቁንጅና ውድድር፤ አሸናፊዋ ከምታገኘው ሽልማት በተጨማሪ ሕገወጥ ስደትን ለመቀነስ ማስተማርና መቀስቀስ ይጠበቅባታል፡፡