Administrator

Administrator

በአዲስ አበባ ከተማ የሚገኘው የሉሲ አካዳሚ ተማሪዎች በየክፍላቸው ንዑስ ቤተመፃሕፍት አቋቋሙ። የሕፃናትንና ታዳጊ ወጣቶችን የንባብ ባህል ለማዳበር የተቋቋሙትና ትላንት የተመረቁት የየክፍሉ አብያተ መጻሕፍት በዝነኛ ሰዎች ስም ተሰይመዋል። ከ1ኛ-5ኛ ክፍል ያሉ ተማሪዎች ያቋቋሙት ቤተመጻሕፍት በደራሲ ሜሪ ጃፋር ስም የተሰየመ ሲሆን ቤተመጻሕፍቱን ደራሲ ሜሪ ጃፋር መርቀውታል፡፡ በክቡር ዶ/ር ከበደ ሚካኤል የተሰየመውን የ7ኛ ክፍል ቤተመፃህፍት ደግሞ ኢንጂነር ታደለ ብጡል ሲመርቁት በደራሲና ጋዜጠኛ ስብሃት ገብረእግዚአብሔር የተሰየመውን የ11ኛ ክፍል ቤተመፃህፍት ጋዜጠኛና ደራሲ ዘነበ ወላ መርቀውታል። ለ12ኛ ክፍል የሚያገለግሉት ሁለት አብያተ መጻሕፍት በክብርት ዶ/ር ስንዱ ገብሩ እና በደራሲ ፀሐይ መላኩ፣ የተሰየሙ ሲሆን አምባሳደር ዶ/ር ሳሙኤል አሰፋና ደራሲ ፀሐይ መላኩ መርቀውታል፡፡ ትምሕርት ቤቱ ካሉት 18 መማርያ ክፍሎች ስድስቱ በዚህ መልኩ ቤተመጻሕፍት ያገኙ ሲሆን የሌሎችም እንደሚቀጥል ማወቅ ተችሏል፡፡

በጋዜጠኛ፣ ደራሲና ጸሐፌ ተውኔት ቴዎድሮስ ተክለአረጋይ የተዘጋጀው “ፍልስምና ፫” የተሰኘው መፅሃፍ ለንባብ በቃ፡፡ በቃለ ምልልስ መልክ በተዘጋጀው መጽሐፍ ውስጥ ስምንት ባለሙያዎች የተካተቱ ሲሆን ከእነዚህም መካከል ኬሚካል ኢንጂነር ጌታሁን ሄራሞ፣ በቀለማት ፍልስፍናና ሥነ ልቦናዊ ማንነታቸው፣ ተፊሪ ንጉሤ በገዳ ሥርአት፣ በዋቂፈናና ኢሬቻ፣ ዶ/ር መስፍን አርአያ በማንነታችን ላይ የተናገሩት ይገኝበታል፡፡ 144 ገፆች ያሉት መጽሐፍ በ32 ብር እየተሸጠ ነው፡፡

በሌላ በኩል በግዛው ዘውዱ የተዘጋጀው “ኢትዮጵያ፣ ታሪክ፣ ትርክትና ታሪካችን” መጽሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ በ285 ገጾች የተቀነበበው መጽሐፍ በፋርኢስት ትሬዲንግ የታተመ ሲሆን በ60.70 ብር እየተሸጠ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል፡፡ መጽሐፉ በማጣቀሻነት ከተጠቀማቸው በርካታ ዋቢዎች መካከል የአለቃ ደስታ ተክለወልድ፣ የፕሮፌሰር ጌታቸው ኃይሌ፣ የነጋድራስ ገብረሕይወት ባይከዳኝ፣ የአሌክሳንደር ቡላቶቪችና የዶናልድ ሌቪን መጻሕፍትና ሌሎች ጽሑፎች ይገኙበታል፡፡

በኢትዮጵያ የመጀመርያው የኤፍኤም ሬዲዮ ጣቢያ ኤፍኤም አዲስ 97.1 የተመሰረተበትን 13ኛ ዓመት በዓል ነገ ከጧቱ 3 ሰዓት ጀምሮ በሐራምቤ ሆቴል እንደሚያከብር አስታውቋል፡፡ የ24 ሰዓት ስርጭት ያለው ብቸኛው የኢትዮጵያ ሬዲዮ ጣቢያ፣ ነገ በሚያከብረው በዓል ላይ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ መምህር ረዳት ፕሮፌሰር ታደሰ ዝናዬ “የኤፍ ኤም ጣቢያዎቻችን ለሕብረተሰብ ሁለንተናዊ እድገትና ለሀገር ልማት ያበረከቱት አስተዋጽኦ እና ጉድለቶቻቸው” በሚል ርእስ እንዲሁም የጣቢያው ጋዜጠኛ አቶ ዮናስ ወልደየስ “ኤፍ ኤም አዲስ 97.1 ከየት ወደየት?” በሚሉ ርእሶች ጥናታዊ የውይይት ፅሁፍ ያቀርባሉ፡፡ በውይይት ላይ ከ100 በላይ ተጋባዥ እንግዶች እንደሚገኙ የታወቀ ሲሆን ጣቢያው ከበዓሉ በኋላ የአንድ ዓመት ተኩል ጥናት ያደረገበትን የዝግጅቶች ለውጥ ያደርጋል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

እንደ ዓለት የጸና ታሪክ፣ እንደ ፏፏቴ የሚፈስስ ዜማ የሚያፈስሱ ከንፈሮች፣ የልብ አፍንጫ የሚነቀንቅ የፍቅር መዓዛ ያለውን የኢትዮጵያ ሶማሌ ህዝብ ለመጎብኘት ወደ ኦጋዴን ስንበርር፣ አውሮፕላኑ በሁለት ክንፎቹ ሲበር፣እኛም ሺህ ክንፎች ያወጡ ልቦች ነበሩን፡፡ ኦጋዴን ገብተን ፈንጂ አየር ላይ ከነወንበራችን ሲያንሳፍፈን፣ኦብነግ መንገድ ላይ ቆርጦ ሲማርከን…እና ሌሎችም ሃሳቦች ነበሩብን፡፡ ኋላ እንደሰማሁት ብዙዎቻችን በዚህ ቅዠት ውስጥ ነበርን። ደሞ ታሪክ የማወቅ ጉጉትም አድሮብናል፡፡ በተለይ የኢትዮጵያ ሶማሌዎች፤ ውሳኔ ህዝብ የሰጡበትን ታሪካዊ ቦታ ማየት፡፡ አውሮፕላኑ ሲበርር እኔ አጠገብ ከተቀመጡት የአማራ መገናኛ ብዙሃን ሃላፊ ጋር ጥቂት አወራን፡፡ እኔ የነበርኩበት አውሮፕላን የመጀመሪያው ዙር በራሪ ሲሆን የኢፌዴሪ ፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባዔ አቶ ካሳ ተክለብርሃንም ነበሩና እያንዳንዳችንን በየመቀመጫችን እየመጡ ሰላምታ ሰጡን፡፡

አፈ ጉባዔው ከሰው ጋር ያላቸው ቅርርብ አስደማሚ ነው፡፡ ጎዴ ስንደርስ የኢትዮጵያ ሶማሌ ሰማይ፣ በጥቁር አድማሳት አይኖቹን ኩሎ ነበር የጠበቀን። ከአውሮፕላን ስንወርድ ህዝቡ የናፍቆት ዓይኖቹን እንደ ችቦ እያበራ…እንደወንዝ በሚፈስስ ዜማ…እንደ ቄጠማ እየተወዛወዘ ተቀበለን፡፡ እኛም ሲቃ በተሞላ ደስታ እጆቻችንን እያውለበለብን አጸፌታውን መለስን፡፡ እውነትም የኢትዮጵያ ሶማሌ ፍቅር ነው። እውነትም ይወዱናል፡፡ በአይኖቻቸው ላይ ያነበብነው ፍቅር ሌላ ፍቅር በልባችን ወልዶ ብዙዎቻችን በተመስጦ ውስጥ ወደቅን፡፡ “ይህን ህዝብ ለምን በኪናዊ ስራዎቻችን አላየነውም

” በሚል ራሳችንን ወቀስን፡፡ ሰዓሊው እጁ ነደደ፤ደራሲው በአርምሞ ውስጡ ታመመ፤ሙዚቀኛው ነፍሱ ታመሰች፡፡ የሁሉም ልብ በየመስመሩ ፈሰሰ። የሁሉም ሰው ነፍስ በኢትዮጵያ ሶማሌዎች ፍቅር ተጎረሰ፡፡ ሶማሌ የሚለው መጠሪያ “ሶሜ” በሚል ቁልምጫ እስኪለወጥ የከያኒውን ልብ ወሰዱት፡፡ በመጀመሪያው ቀን የጎዴ አዳር ብዙዎቻችን ፈራን፤ በተለይ እባብና ጊንጡን፡፡ ከፊላችን ያደርነው ቴክኒክ ኮሌጅ ውስጥ ነበር፡፡ በተለይ ለተጓዡ ሁሉ የሳቅ ምንጭ ከነበረው ሽመልስ አበራ (ጆሮ) ጋር ልዩ ጊዜ አሳልፈናል። ጊንጥና ጃርት የየራሳቸው ታሪክ ነበራቸውና ሰው በሳቅ አልቆ ነበር፡፡ ያ ብቻ አይደለም፤ ከዚህ ቀደም በተለያዩ ፕሮግራሞችና የጥበብ ዝግጅቶች የሚታወሱ አስቂኝ ነገሮች በሙሉ ተዘርግፈዋል፡፡ ሽሜ ዋናው ኮሜዲያን ይሁን እንጂ ታገል ሰይፉና ሌሎቹም ማለፊያ መዝናኛ ፈጥረውልን ነበር፡፡ የኢትዮጵያ ሶማሌ ዜማዎችን ሳንረሳ ነው ታዲያ፡፡ እነዚህ ሰዎች በሙዚቃቸው ሃይል የፌዴሬሽን ምክር ቤት አፈ ጉባኤውን በተደጋጋሚ ከመቀመጫቸው አስነስተው አስጨፍረዋል፡፡

ትከሻ-ለትከሻ ገጥመው አብረው ጨፍረዋል፡፡ በጎዴው አዳራችን እባብና አይጥ ፈርተን አንዳንዶቻችን ፍራሾቻችንን ወደ መሃል ለመሳብ ሞክረናል፡፡ ታዲያ ሽመልስ አበራ በሳቅ ሆዳችንን እያቆሰለው ሸሽተን ወደመኝታችን ሄድን፡፡ ግና አላመለጥንም፤ እየተከተለ ኮረኮረን፡፡ ማምሻውን እንናፈስ ብለን ወደከተማ ስንወጣ ሰው ሁሉ ዝነኛ አርቲስቶችን በስማቸው ይጠራ ነበር። ሽመልስ አበራ፣ ጥላሁን ጉግሳና ሌሎቹ ከየአቅጣጫው ይጠሩ ነበር፡፡ እንደ አበበ ባልቻ መከራ ያየ፣ የተከበበና ፎቶ በመነሳት የተጨናነቀ ግን አልነበረም፡፡ ሁሉም ከተማ፣ ሁሉም ሰው ቀድሞ የሚጠይቀው አስናቀ መጥቷል እያለ ነው፡፡ እንዲያውም ደገሀቡር ከተማ ምሳ በልተን የቡና ወረፋ ስንጠብቅ፣ አንድ ጠንከር ያሉ አዛውንት እንዲህ አሉ፤ “ያ አስናቀ መጥቷል?” እኛም “አዎ መጥቷል” አልናቸው፡፡ ሰውየው ተቆጥተው “…እርሱ’ኮ ነው የድግሳችንን ወጥ ያሳረረብን… የ40 ቀን መታሰቢያ ድግሳችንን ያበላሸው!” አሉ፡፡ ስለሁኔታው ሌሎችን ጠየቅን “ሰው ለሰው በኢቴቪ ሲጀመር አስናቀ መጣ፣ አስናቀ መጣ!” ተብሎ ሴቶቹ ሁሉ ቴሌቪዥን ሊያዩ ወጡ፡፡

በዚህ መሃል ነው ወጡ አረረ የተባለው፡፡ ሰውየው ግን “ቆይ” ብለው እየዛቱ ወደ መሀል ከተማ ሄዱ፡፡ “አበበ ባልቻ እግዜር ይሁንህ!” አልን፡፡ በማግስቱ ጧት ወደ ታሪካዊቷ ከተማ ካሊ ነበር የተጓዝነው፡፡ እኛ መኪና ውስጥ ድምፃዊው ሞገስ ተካ፣ የሙዚቃ ሃያሲው ሠርፀ ፍሬስብሀት፣ ዲያቆን ዳንኤል ክብረትና ሁለት የአፋር ክልል፣ ሁለት የጋምቤላ ክልል ጋዜጠኞች አሉ፡፡ አልፎ-አልፎም ጋዜጠኛ ቴዎድሮስ ተክለአረጋይ አብሮን ይሆናል፡፡ አርቲስት አለለኝም ብቅ-ጥልቅ ይላል፡፡ ካሊ ስንሄድ ትንሽ አቧራ ነገር ነበር፡፡ ይሁንና ታሪኩ ለብዙዎቻችን የሚያጓጓ ነው፡፡ ያ ቦታ የኢትዮጵያ ሶማሌዎች፤ “ውሳኔ ሕዝብ” የሰጡበት ነው፡፡ እንግሊዛዊያን የሀገር ሽማግሌዎችን ሰብስበው “ከኛ ጋር ትሆናላችሁ ወይስ ከኢትዮጵያ?” ብለው ምርጫ የሰጧቸው ቦታ ነበር፡፡ አንድ የጉዟችን አባል ሲናገር እንደሰማሁት፤ እንግሊዞች እሾህ ላይ ነጠላ አንጥፈው ነጠላውን እሾህ ሲነክሰው “ኢትዮጵያ ማለት እንዲህ ናት!” ብለው አስጠንቅቀዋቸዋል፡፡ የኢትዮጵያ ሶማሌዎች ግን በዚያችው አደባባይ፣ ሰማይና መሬት እያዩ፣ ፀሐይ እየታዘበች፣ ቁጥቋጦው እያሸበሸበ “እኛ ኢትዮጵያዊያን ነበር፤ አሁንም ነን፣ ወደፊትም በኢትዮጵያዊነታችን እንዘልቃለን” በማለት ቁርጡን ተናገሩ፡፡ የኢትዮጵያ ሶማሌዎች ኢትዮጵያዊ የሆኑት በመወለድ ብቻ አይደለም፡፡ በምርጫም ነው፡፡ ምንም እንኳ ይህንን የጠራ ባህር ሕዝብ ታሪክ ለማበላሸት አፈር ቢበትኑም ዛሬም ግን ሕዝባችን ከማናችንም በተሻለ የሀገር ፍቅር በልቡ የሚነድድ፣ ነድዶም የማያባራ ሕዝብ ነው፡፡

ለዚህም ነበር እርጥብ ቅጠል ይዞ በፍቅር ነበልባል በታጀቡ አይኖቹ የተቀበለን፡፡ ከጐዴ ከወጣን በኋላ የደናን ከተማ ሕዝብ ግራና ቀኝ ተሰልፎ ነበር፡፡ ቀብሪደሀር ስንሄድ ወጣቶቹ በፉጨትና በአድናቆት ተቀበሉን፡፡ በሚገባ ባላጣራም አንድ ከሙቀቱ ጋር በቢራ ሞቅ ያለው አርቲስት “አምላኬ ሆይ! እንደታቦት በሕዝብ ታጅቤ በእልልታና በሆታ እሸኝ ዘንድ እኔ ማን ነኝ?” እያለ በአድናቆት ደረቱን ይደቃ ነበር፡፡ በዚህ ጉዞ የኔ ትዝታም ደማቅ ነው፡፡ ቀብሪደሀር ከተማ አንድ ሱቅ ገብቼ ደብተር ልገዛ ስል፤ ሻጩ ወጣ የያዝኩትን ብር ወደ እኔ ገፍቶ በነፃ ሊሰጠኝ ሲል ገፍቼ መለስኩለት። ቀጥሎም የታሸገ ለስላሳ መጠጥ ለመግዛት መቶ ብር የሰጠሁት መስሎኝ ሁለት መቶ ብር ሰጥቼው ኖሮ መቶ ብሩን ሲመልስልኝ አንጀቴ ተላወሰ፡፡ ወገኔ ባይሆን፣ ባይወድደኝ መች ይህን ያደርግልኝ ነበር? የሚለው ነገር ለሕዝቡ ያለኝን ፍቅርና ክብር ጨመረው። ታዲያ በየከተማው መሀመድ ጠዊል፣ ሀብተሚካል ደምሴ፣ ዘውዱ በቀለ (ወላይትኛ) በባህላዊ ዜማቸው ሕዝቡን እንደማዕበል ነቅንቀውታል፡፡ ቀብሪደሀር ስንገባ 12ኛ መተማ ክፍለ ጦር ግቢ ነበር የተስተናገድነው። የሠራዊቱ አባላት ዳስ ተክለውልን በሚደንቅ መስተንግዶ፣ በሀገራዊ ፍቅር የምንገባበት እስኪጠፋን ተቀብለውናል፡፡ ይህ ክፍለ ጦር ግቢ፣ በገበየሁ አየለ “ጣምራ ጦር” መፅሐፍ ውስጥ የተጠቀሰ ሲሆን በየመንገዱ ያየናቸው ኩይሳዎች፣ መንገዶችና መልከዐ ምድራዊ አቀማመጦች ሁሉ ወደኋላ መለስ ብለን ገፆቹን በትዝታ እንድንገልጥ አድርገውናል፡፡

ከከተማ ወጥተን ደገሀቡር ስንገባ፣ የደገሀቡር ሕዝብም በሚገርም ሁኔታ ተቀበለን፡፡ መቼም ደገሀቡር የሸጋዎች ሀገር ናት፡፡ እንደ ቄጠማ የሚወዛወዙ ቆነጃጅት ነበሩ፣ ጣፋጭ ዜማ የሚያሰሙት፡፡ ወንዶችም ቁመናቸው የሚያምር፣ ፈገግታቸው ልብ የሚነካ ለዛ የተሞሉ ነበሩ፡፡ ታዲያ እዚህ ግቢ መኝታ ክፍሎች ስለነበሩ የቡድናችን አባል ሽመልስ አበራ ጡንቻም ስላለው ሁለት ክፍል ይዞ ጠበቀን፡፡ እኔ፣ ተስፋዬ ገ/ማርያም (ብሔራዊ ቴአትር) መልካሙ ዘሪሁን (ፀሐፌ ተውኔት) አንድ ክፍል፣ ውድነህ ክፍሌ፣ ታገል ሰይፉና ሽመልስ ከኛ ትይዩ ገቡ፡፡ የምሽቱን ደማቅ የበአል አከባበር ተቀላቅለን ተመልሰን ሻወር ከወሰድን በኋላ ወደየመኝታችን ገብተን ተኛን፡፡ ለካ ሦስት ሰዎች መኝታቸው ከመግባታቸው በፊት በአካባቢው ስለነበረው አራዊት ጠይቀዋል፡፡ የጠየቁት መኮንንም ምንም የሚያስፈራ ነገር እንደሌለ ይነግራቸዋል፡፡ ይሄን ብሎ ግን አላበቃም፡፡ “ብ…ቻ አንድ… ነገር አለ” አላቸው፡፡ ሳሚና ታገል ጆሮ ሰጡት። ተረከላቸው፡፡ “በአርጃም ይባላል፡፡ አዞ የመሰለ ሆኖ አራት እግሮች አሉት፤ ርዝመቱ ሁለት ሜትር ያህል ይሆናል፡፡ እንቅልፍ ካልወሰዳችሁ አይናካም፣ ግን ሰው እንቅልፍ እንዲወስደው የሚያደርግ መላ አለው - በፊት እግሮቹ ደባብሶ እንቅልፍ ያመጣል፡፡ አይናከስም፣ ብቻ ሁለት ምላሶች አሉት፤ እንቅልፍ የወሰደው ሰው ሲያገኝ ሁለቱን ምላሶቹን አፍንጫ ውስጥ ሰድዶ አንጐልን ይመጥጣል፡፡

ልክ ደም መምጣት ሲጀምር ግን ትቶ ይሄዳል” ይላቸዋል፡፡ ጭንቅ በጭንቅ እንደሆኑ ይመጣሉ፡፡ ሙቀት ስለነበር በረንዳ አንጥፈው ለመተኛት ቢፈልጉም “አርጃኖ” ትዝ ይላቸውና ወደ ክፍላቸው ይገባሉ፡፡ ክፍላቸው ሲገቡ የሆነች ተባይ ታሳድዳቸውና መኝታ ውስጥ ይገባሉ፡፡ ይሄኔ የመኪናው ረዳት ወደ መግቢያው ላይ፣ ቀጥሎ ታገል ሰይፉ፣ ከዚያ ውድነህና ሽመልስ በተከታታይ ይተኛሉ፡፡ ታገል ጧት እንደነገረን፤ ከውጭ ንፋስ ሲያንቋቋ እርሱ አርጃኖን ያስባል፤ ተኝቼ እያለ አንጐሌን ይመጠው ይሆን? ሲል ያስብና “አይ ከኔ ቀድሞ ረዳቱ ስላለ እርሱን ሲገድል እሰማለሁ!” እያለ ሲያብላላ ይነጋል፡፡ ሽመልስ አድምቆ ያወራልን ሌላው ወሬ አብረን የሰማነው የአለምዬ ሶራ ዘፈን ተወዛዋዥ ነው። የሰቆጣው ልጅ ግንባሩ ላይ ትልቅ መስመር ነገር ጠባሳ ሆኖ ቀርቷል፡፡ ስለዚያ ሲተርክልን ከነብር ጋር ተናንቆ ታግሎ በመጨረሻው ነብሩን እንደገደለው ሲነግረን፣ ሁላችንም በግርምት ፈዝዘን ነበር፡፡ በማግስቱ ግን ሽሜ ምርጥ አድርጐ ተወነበት፡፡ ያ ሁሉ በመቀመጫው የፈሰሰ አርቲስት፣ ሆዱን እየያዘ ሳቀ፡፡ ሽሜ ምርጥ ኮሚዲያን ሆኖ ነበር፡፡

በዚህ ሁሉ ውስጥ ታዲያ የኢትዮጵያ ሶማሌዎች ፍቅር የሚረሳ አልነበረም፡፡ ሁላችንም ይህ ሕዝብ ፍቅር ነው! ውለታ አበዛብን! ፎንቃ አስያዘን እያልን ተገረምን። አትታዘቡኝና እኔ አሁን የኢትዮጵያ ሶማሌዎችን ሳይ እቅፍ አድርገህ “ሳማቸው ሳማቸው” ያሰኘኛል፡፡ እኔ ብቻ አይደለሁም፤ አጠገቤ የነበሩት ሁሉ ከጅጅጋ ስንወጣ በስደት ወደሌላ ሀገር እንደምንሄድ ተሰምቶን ነበር፡፡ ያ ፈገግታ… ያ… ዜማ… ያ ፍቅር እንዴት ሊረሳ ይችላል? በምን? ናፈቁን! ጅጅጋ ከተማ ገብተን በመጨረሻው ቀን መስተንግዶ ላይ የተሰማንን ገለጥን፣ ግጥሞች አቀረብን፣ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት እጅግ ውብ የሆነ ወግ አቀረበልን! …እያጣፈጠ አሳቀን፡፡ ጅጅጋ፣ የክልሉ እንግዶች ማረፊያ (Guest house) ግቢ ውስጥ ሦስት ነብሮች ታስረው ነበር። ታዲያ እነዚህን ነብሮች ያየ ሁሉ አብሯቸው ፎቶ መነሳት፣ ቪዲዮ መቅረፅ ጀመረ፡፡ ታገል ሰይፉ የአንዱን ነብር አንገት ደባበሰ፣ ሌሎችም አብረውት ፎቶግራፍ ተነሱ፡፡

ፀሐፌ ተውኔቱ ውድነህ ክፍሌ ግን ከሌሎች የተለየ እጣ ደረሰው፡፡ ነብሩ ሳያስበው ሁለት እጁን ቧጠጠው፡፡ ይሁን እንጂ በራሱ አንደበት እንደገለጠው፤ በሚያስደንቅ ጥበብና ስትራቴጂ ተጠቅሞ ራሱን አዳነ፡፡ ይህም በሳቅና ፌሽታ ተመንዝሮ ተሳቀበት፡፡ በጅጅጋ የማይረሳው ነገር ቢኖር የኢትዮጵያ ሶማሌ ፕሬዚደንት ንግግር ነበር። ሰውየው የማይቀመሱ እሳት፣ የሚጥሙ ጣፋጭ፣ የሚያስቁ ኮሜዲያን ነገር ናቸው፡፡ በመጨረሻው ቀን ስንብት አዳራሽ በገባን ቀን ሰውየው ንግግር ሊያደርጉ ነው ሲባል ሁላችንም ፈራን። አሰልቺ ንግግር ይሆናል ብለን ሃሞታችን ፈሰሰ። እንዳሰብነው ግን አልሆኑም፡፡ ያገር አርቲስት ልቡ እስኪፈርስ እየሳቀ እርስ በርስ እየተያየ፣ እጁ እስኪቃጠል እያጨበጨበ፣ ስብሰባው ተፈፀመ፡፡ የመጨረሻው ጭብጨባ ድምፅም እስካሁን በውስጤ ያስተጋባል። ሰውየው የዋዛ አይደሉም፤ አሁን ያለውን የኢትዮጵያ ሶማሌ መልክ ለማምጣትም ዋነኛው ተዋናይ፣ ደማቁ ቀለም እርሳቸው ናቸው ይባላል፡፡ ጉዟችን ወደ ሐረር ሲቀጥል የአቀባበል ውበት፣ የዜማው ሃይል የፈገግታው አቅም እየቀነሰ ሄዷል፡፡ ብዙ ነገሮች እየተዝረከረኩ አሰልቺ እየሆኑ መጡ፡፡ አብረውን የነበሩ ታዋቂ ሰዎች እጃቸውን እያነሱ ትርኪ ምርኪውን ሲያወሩ የብዙዎችንን ልብ ሰበሩት፡፡ መታወቅና ማወቅ ይለያያልና! ብዙ ዘባርቀው አንገታችንን አስደፉን፡፡ ጥሎ የማይጥል አምላክ፣ ሰርፀ ፍሬ ሰንበትን አስነስቶ “ኧረ እንደዚህ ብቻ አይደሉም፤ እንደዚህም ናቸው” የሚያሰኝ ምርጥ ሀሳብ፣ በሳይንስ የተደገፈ ጥበብ አወራ፡፡ ስለ አርአያነትም ረገጥ አድርጐ ገሰፀ፡፡ ቴዎድሮስ ተክለአረጋይም “ማሳሰቢያ” ብሎ በድሬዳዋው አዳራሽ አፈጉባኤው በተገኙበት አፋቸው እንዳመጣላቸው የሚናገሩ ሰዎችን አደብ ግዙ አለ፡፡ ድሬዳዋ ከተማ ሌላው ያየነው ነገር ሕፃናት ተሰብስበው ጥላሁን ጉግሳን “ዘሩ…ዘሩ…ዘሩ!” እያሉ ሲከብቡት ነው፡፡

መሄጃ ከልክለውት ነበር፡፡ ሳላጋንን ፖሊሶች ልጆችን እስኪለከልሉ ደርሷል፡፡ ይህ ነገር ያሳየኝ ልጆች የእሱን “ቤቶች” ድራማ የሚመለከቱት ከሆነ ለቀጣዩ ትውልድ መልካም ዘር መዝራት እንደሚገባው ነው፡፡ በመጨረሻው የጅጅጋ ሽኝት ቀንም ዘነበ ወላ፣ ሠራዊት ፍቅሬ፣ ሰርፀ ፍሬሰንበት፣ ዳንኤል ወርቁ፣ ንግግር አድርገዋል፡፡ ዶ/ር በድሉ ዋቅጅራና እንዳለ ጌታ ከበደ ግጥም ያቀረቡ ሲሆን ዲያቆን ዳንኤል ክብረትም ምርጥ ወግ አቅርቧል፡፡ ደስ የሚሉ ቀናት አሳልፈናል፡፡ በትዝታ የሚታተሙ ዜማዎች አድምጠናል፡፡ ስቀጥል ፍቅር ወድቀናል ኢትዮጵያ ሶማሌ ፍቅር ነው ብለናል፡፡ ለሴት ልጆች ባላቸውም ክብር ተደምመናል ሴት ክቡር ናት!

Saturday, 15 June 2013 10:47

ወደ ምስራቅ ተመልከቱ!

የዛሬ ሁለት ሳምንት 200 የሚደርሱ አባላት የተካተቱበት እውቅ የኪነጥበብ ባለሙያዎች፣ ጋዜጠኞችና የፖለቲከኞች ቡድን፤ በፌዴሬሽን ምክር ቤትና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልላዊ መንግስት አስተባባሪነት “የምስራቅ ኢትዮጵያን እንወቅ” በሚል መርህ የሶማሌ፣ የሃረሪ ክልል እና የድሬዳዋ መስተዳድርን ጐብኝተዋል፡፡ በዚህ ፅሁፌ በጉብኝቱ ወቅት ይፋ ስለተደረጉ አንኳር ፍሬ ጉዳዮች የማስቃኛችሁ ሲሆን ፅሁፌን የምጀምረውም የሱማሌ ህዝብ እንዴትና ለምን ኢትዮጵያዊ ሆነ ከሚለው ነው፡፡

አፍሪካን በቅኝ ግዛት በመቀራመት እንግሊዝ እና ፈረንሣይ ትልቁን ስፍራ ይይዛሉ፡፡ በምስራቅ አፍሪካ ላይ አንዣብባ የነበረችው ጣሊያንም ተጠቃሽ ናት፡፡ እነዚህ ሶስት ሃገሮች የዛሬዋን ሶማሊያ በመቀራመት የኢጣሊያ ሶማሌ፣ የእንግሊዝ ሶማሌ እና የፈረንሣይ ሶማሌ (ጅቡቲ) እያሉ ያስተዳድሩ ነበር፡፡ በወቅቱ በኢትዮጵያ ግዛት ውስጥ ይገኙ የነበሩ የሶማሌ ጐሣ አባላትንም በተለይ እንግሊዞች ድንበር ጥሠው እየገቡ አስተዳድረዋል፡፡ ለአካባቢው ማህበረሠብ ከማዕከላዊው የኢትዮጵያ መንግስት የተሠጠው ትኩረት እምብዛም በመሆኑም እንግሊዞች በአካባቢው የሶማሌ ተወላጆች ላይ የተለያዩ ጫናዎችን ያደርጉ ነበር፡፡

የተለያዩ እርዳታዎችንና እጅ መንሻዎችን በማቅረብም በማህበረሠቡ ዘንድ ትልቅ ተሠሚነት ያላቸውን የጐሣ መሪዎች እየሠበሠቡ በኢትዮጵያ መንግስት ላይ ክህደት ፈፅመው አብረዋቸው እንዲያብሩ ይገፏፏቸው ነበር፡፡ እንዲያውም የኢትዮጵያን መንግስት ትተው በእነሡ አስተዳደር ስር እንዲጠቃለሉ ይወተውቷቸው ነበር፡፡ የሃገር ሽማግሌዎችና የጐሣ አባላትን እየሠበሠቡ፣ ከኢትዮጵያ መንግስት “ቅኝ አገዛዝ” ይልቅ የእንግሊዝ መንግስትን አስተዳደር በመምረጥ የአውሮፓዊ ስልጣኔ ተቋዳሽ ሲሆኑ በተደጋጋሚ መክረዋቸዋል፡፡ ይህን ተደጋጋሚ ውይይት የሚያደርጉት ደግሞ የክልሉ እምብርት በሆነው ለኦጋዴን አካባቢ በመገናኘት ነው፡፡ አሁን ያለው የክልሉ መንግስት ለጉብኝቱ አባላት ስለዚህ ታሪካዊ ሂደት ገለፃ አድርጓል፡፡

ለ“ኢትዮጵያ” ሶማሌዎች የእንግሊዝ መንግስት በተደጋጋሚ የሚያቀርበው የእኔ ግዛት አካል ሁኑ ጥያቄ ለመጨረሻ ጊዜ እልባት ያገኘው ዛሬ በሸበሌ ዞን በደናን ወረዳ ውስጥ በምትገኘው “ካሊ” በተባለች ስፍራ ነው፡፡ በወቅቱ ተልዕኮ የተሠጣቸው የእንግሊዝ መንግስት ተወካዮች ካሊ በመገኘት የሃገር ሽማግሌዎችን ሠበሠቡ፡፡ ሽማግሌዎቹንም ወይ እንግሊዝን ወይ ኢትዮጵያን እንዲመርጡና ቁርጠኛ ውሣኔያቸውን እንዲያሣውቋቸው ጠየቁ፡፡ የሃገር ሽማግሌዎቹ ግን ከእንግሊዝ ይልቅ የኢትዮጵያ መንግስት ይሻለናል፡፡ እኛ ኢትዮጵያውያን እንጂ የእንግሊዝ ቅኝ ግዛት አካል መሆን አንፈልግም ሲሉ በዚህች ታሪካዊ ቦታ ላይ አሣወቁ፡፡ ከዚያን ጊዜ በኋላም ሱማሌዎች በኢትዮጵያዊነት ፀኑ፡፡ በጉብኝቱ ወቅት ይህን ታሪክ ለትውልድ የማስተላለፍ ሃላፊነት የወሠዱት የሃገር ሽማግሌዎች ለጉብኝቱ አባላት እንደገለፁት፤ እንግሊዞች በዚህ ውሣኔ ተናደው ከአባባቢው ከመሄድ ባሻገር ይህ በሚስጥር ሲያደርጉት የነበረው ድርድር በማዕከላዊው የኢትዮጵያ መንግስት እንዳይሠማ ስጋት አድሮባቸው ነበረ፡፡

ምክንያቱም በወቅቱ ሃገሪቱ ከኢትዮጵያ ጋር በወዳጅነት ላይ የተመሠረተ ግንኙነት ነበራትና ነው፡፡ በእንዲህ ያለ መልኩ ኢትዮጵያዊነትን የመረጡት ሱማሌዎች፤ ከተቀሩት ሱማሌዎች ንቀትና ጥላቻን አትርፈዋል፡፡ ይህ እውነታም ለዘመናት ደብዝዞ እንዲቀር የእነዚህ ሃይሎች ሚና ቀላል እንዳልነበረ መረዳት ይቻላል፡፡ የኢትዮጵያ ሱማሌ ህዝብ ከእንግሊዝ የቀረበለትን የሪፈረንደም ምርጫ ኢትዮጵያዊነትን በመምረጥ ያጠናቀቀ መሆኑ በማዕከላዊው መንግስት የሚታወቅ ባለመሆኑ፣ ሁሌም በሃገር ክህደት ጥርጣሬ የሚታይ ነው፤ ይህም ሆኖ በአፄ ሃይለ ስላሴ ዘመን ሃገሪቱን ከቅኝ ግዛት ናፋቂዎች በምስራቅ በኩል በመከላከል በደጀንነት ሚናውን ተወጥቷል፡፡ “እኛ ኢትዮጵያውያን ነን” የሚለው ውሣኔ በሃገር ሽማግሌዎች ከተላለፈ በኋላ፣ በክልሉ ህዝብ ሌላ የታሪክ ምዕራፍ የተገለጠው የዚያድ ባሬ ጦር በ1968 መላዋን ኢትዮጵያ ለመውረር በተንቀሣቀሠበት ወቅትና ከዚያ በኋላ እስከዛሬ ድረስ ባለው ጊዜ ነው፡፡ ታላቋን ሱማሊያ የመመስረት አላማ አንግቦ የተነሣው ዚያድ ባሬ፤ በኢትዮጵያ የሚኖሩ ሱማሌዎችን፣ በጅቡቲ ያሉ ሶማሌዎችንና በእንግሊዝና በጣሊያን ስር የነበሩ ሶማሌዎችን አንድ በማድረግ ታላቋን ሶማሊያ እውን ማድረግ ቀዳሚው አላማ አድርጐ ተንቀሣቅሷል፡፡ የወረራው ቀዳሚ ሠለባ የኢትዮጵያ ህዝብ በመሆኑም በርካቶቹ ጦርነቱን ሽሽት ወደ ዋናዋ ሱማሊያ እንዲሸሹ ተደረገ፡፡

የክልሉ የአሁኑ ርዕሠ መስተዳደር አብዲ መሃመድ ለጉብኝቱ አባላት ጅጅጋ ከተማ ላይ ባቀረቡት የክልሉ ታሪካዊ ዳራን የዳሠሠ ጥናታዊ ፅሁፍ ላይ፤ በወቅቱ ጦርነቱን ሸሽተው ወደ ሱማሊያ በመሄድ በካምፕ ያረፉ ስደተኞችን እየመለመለ፣ ዚያድ ባሬ በፕሮፓጋንዳ ያጠምቅ ነበር፡፡ ስደተኞቹን የታላቋ ሱማሊያ አካል ናችሁና ሃገራችሁን ከደርግና ከኢትዮጵያ አገዛዝ ነፃ ማውጣት አለባችሁ ይል ነበር፡፡ ሃሣቡን የተቀበሉትንም እያሠለጠነ ለሃይል ፍልሚያው ዝግጁ እንዲሆኑ አስታጠቃቸው፡፡ ድጋፋቸውን ማግኘቱን ሲያረጋግጥም በኬንያ፣ በሞቃዲሾ፣ በጅቡቲና በኢትዮጵያ ያሉ ሱማሌዎችን አንድ አድርጌ ታላቋን ሶማሊያ እውን አደርጋለሁ የሚለው ህልሙ የሚሳካ መስሎት የመጀመሪያ ኢላማውን ሠፊውን የሱማሌ ህዝብ አቅፋ በምትገኘው ኢትዮጵያ ላይ አነጣጠረ፡፡ ለጊዜው የተሣካ የመሠለ ድልም በመቀናጀት መሃል ሃገር ድረስ ዘልቆ በመግባት ብዙ ውድመቶችን አደረሠ፡፡ በርካታ ኢትዮጵያውያን ሱማሌዎችንም በአስተሣሠቡ አጠመቀ፡፡ ጥቂት የማይባሉትም ከዚያድ ባሬ ጦር ጋር በማበር መልሠው ሃገራቸውን ወጉ፡፡ አብዛኛው በተለይም ይህን ኢትዮጵያዊ የመሆን የሪፈረንደም ውሣኔ ያፀደቁና ሚስጥሩን የሚውቁት ግን አሁንም የዚያድ ባሬን ወረራ ተቃወሙ፡፡

እንዲያም ሆኖ ለማህበረሠቡ የተሠጠው የኢትዮጵያዊነት ማዕረግ አነስተኛ እንደነበር አቶ አብዲ በጥናታቸው ጠቁመዋል፡፡ በወቅቱ ደርግ የሱማሌ ማህበረሠብን እንደ ሌላው ኢትዮጵያዊ አይመለከትም፡፡ “አንተ ሽርጣም ሡማሌ” ከሚለው ዘለፋ ጀምሮ በጥርጣሬ ይመለከት ነበር፡፡ በዚህም ሳቢያ አብዛኛው ማህበረሠብ በኢትዮጵያዊነት አስተሣሠብ የተቀረፀ አልነበረም። ደርግ እንዲህ በጥርጣሬ ማህበረሠቡን ሲመለከት ዚያድ ባሬ በበኩሉ፤ ከእሡ ጐን ቆመው የማይዋጉትን ያሠቃይ ነበር፡፡ በዚህ የተነሣ ህዝቡ ከሁለት ያጣ ሆኖ ለወራት በዘለቀው ጦርነት ብዙ ተጐድቷል፡፡ እንዲያውም ደርግ በዚያድ ባሬ ጦር ተሸንፎ ከቀብሪ ደሃር ለቆ በመውጣት ወደ ደጋሃ ቡር ሲገባ “አንተም ሱማሌ ያም ሱማሌ” እያለ በርካቶችን መጨፍጨፉን አቶ አብዲ በጥናታቸው ይገልፃሉ፡፡ ደርግም ዚያድ ባሬም የኢትዮጵያ ሱማሌን በእኩል ጨፍጭፈዋል፡፡ ደርግ በሃገር ክህደት እየወነጀለ ሲጨፈጭፍ፣ ዚያድ ባሬ ደግሞ አርፋችሁ ተገዙ በሚል ይጨፈጭፍ ነበር፡፡ ህዝቡም በአፀፋው ደርግን ከመውጋት ይልቅ ዚያድ ባሬን ነበር የሚፋለመው የሚሉት አቶ አብዲ፤ በትግሉ ሂደትም ዚያድ ባሬ የሾማቸው የወረዳ አመራሮች ላይ በድብቅ ጥቃት ይፈፅም ነበር፡፡ ለትዕዛዛቸውም ቀና ምላሽ አይሠጥም፡፡

በዚህም ብዙ የዚያድ ባሬ የሡማሊያ አመራሮች ተገድለዋል፡፡ በድርጊቱ የተናደደው ዚያድ ባሬም ጦሩ ተሸንፎ ከኢትዮጵያ ሲወጣ በመውጫ መንገዱ ያገኛቸውን ኢትዮጵያውያን ሱማሌዎችን ጨፍጭፏል፡፡ የታላቋ ሶማሊያ ጦር ሃገሪቱን ለቆ ቢወጣም በተለይ ኦጋዴን አካባቢ የተለያዩ ጥያቄዎች ይነሡ ነበር፡፡ እነዚህ ጥያቄዎች ደግሞ በኋላ ሃገሪቱን ከደርግ ተረክቦ ማስተዳደር በጀመረው የኢህአዴግ ስርአትም ተጠናክረው ቀጥለዋል፡፡ የክልሉ ህዝብ ሶስተኛው የታሪክ ምዕራፍ የሚጀምረው ኢህአዴግ ኢትዮጵያን ከተቆጣጠረበት ከ1983 ዓ.ም በኋላ ነው፡፡ በወቅቱ ራስን በራስ ማስተዳደር የሚለው ሃሣብ ሲመጣ እንደ ሌላው የኢትዮጵያ ክፍል ሁሉ የተማሩ የሚባሉ የማህበረሠቡ ተወላጆች ፓርቲ ማቋቋም ጀመሩ። 14 ድርጅቶችም ወዲያው ተመሠረቱ፡፡

እነዚህ ድርጅቶች መመስረታቸው ባልከፋ ነበር፤ ነገር ግን ሁሉም የተመሠረቱት በዚያድ ባሬ ጊዜ የኢትዮጵያ መንግስትን ሲወጉ በነበሩ ጀነራሎችና የጦር መኮንኖች ነበር፡፡ እነዚህ መኮንኖች ፓርቲዎቹን ሲመሠርቱም በጐሣቸው ተከፋፍለው ስለነበር የኋላ ኋላ ብዙ መዘዞችን አስከትሏል፡፡ በወቅቱ ፓርቲዎቹ የተለያየ ፍላጐት ይዘው ቢመሠረቱም ሁሉንም አንድ የሚያደርጋቸው አጀንዳ ግን ነበራቸው፡፡ ይኸውም የሶማሌ ክልልን ከኢትዮጵያ መገንጠል የሚለው ነው፡፡ አስራ ሶስቱ ድርጅቶች በኢትዮጵያ ያለውን የሶማሌ ማህበረሠብ ግዛት ይዘን ወደ ታላቋ ሶማሊያ እንቀላቀል ሲሉ፣ የኦጋዴ ብሄራዊ ነፃ አውጪ ግንባር (ኦብነግ) በበኩሉ፤ ከሶማሊያ ጋር ሣንቀላቀል የኦጋዴን ነፃ ግዛት (ሃገርን) መመሥረት አለብን አለ፡፡ ይህ ሁሉ የሃሣብ ፍጭት ሲካሄድ ምንም እንኳ ኢህአዴግ አዲስ አበባን የተቆጣጠረ ቢሆንም የደርግ አመራሮች በሱማሌ ክልል መደበኛ ስራቸው ላይ ነበሩ፡፡ አቶ አብዲ እንደሚሉት፤ በወቅቱ የነበሩት የደርግ አመራሮች ቦታውን ለሱማሌ ተወላጆች ሣያስረክቡ ትንሽ ስልጠና ተሠጥቷቸው ቢቆዩ ኖሮ፣ የኋላ ኋላ በክልሉ የተፈጠረው የፖለቲካ ቀውስ ባልተከሠተ ነበር፡፡ ይሁን እንጂ ኢህአዴግ ደርጐችን ከቦታው ሲያስለቅቅ ወዲያው የዚያድ ባሬ ጀነራሎች እና የደህንነት ሠዎች ነበሩ ቦታውን የተቆጣጠሩት። የመጀመሪያውን የክልሉን መንግስት ስልጣንም ኦብነግ ተቆጣጠረ፡፡

የተቀሩት 13 ድርጅቶችም በጐሣ ተሰባጥረው “ሊግ” የሚባል የጋራ ህብረት የፈጠሩ ቢሆንም ብዙም ሣይቆይ ሊፈርስ ችሏል፡፡ ኦብነግ ነፃይቱን ኦጋዴን ለመመስረት ይንቀሣቀስ እንጂ ዋነኛ የአስተሣሠብ ቅኝቱ የዚያድ ባሬ ነበር፡፡ ኢህአዴግ ስልጣን ላይ ሲወጣ ጀምሮ የኢትዮጵያን ባንዲራ፣ የህዝብ መዝሙር፣ መከላከያ የመሣሠሉትን ብሄራዊ መገለጫዎችን አይቀበልም ነበር፡፡ ይህ ሁኔታም ክልሉ እስከተረጋጋበት እስከ 2000 ዓ.ም ቀጥሎ መስተዋሉን አቶ አብዲ ይገልፃሉ፡፡ የክልሉ ብሄራዊ መዝሙር ቀደም ሲል ለታላቋ ሶማሊያ ሠንደቅ አላማ የተዘመረ ነበር፡፡ በፍሬ ሃሣቡም የኢትዮጵያ መንግስትን አጥብቆ የሚቃወም ነው፡፡ ይህ መዝሙር ሲዘመር በነበረበት ከ1983-2000 ዓ.ም በርካታ የፌደራል መንግስት ባለስልጣናት የመዝሙሩን ፍሬ ሃሣብ ሣይገነዘቡ አብረው ቆመው ዘምረዋል የሚሉት አቶ አብዲ፤ በኋላ እውነታው ወጥቶ ከኦብነግ ርዝራዦች ከክልሉ ተጠራርጐ መጥፋት ጋር አብሮ መክሠሙን አስረድተዋል። አሁን ስለ ክልሉ ተጨባጭ ሁኔታ የሚዘረዝረው መዝሙርም ከሚያዝያ 4 ቀን 2000 ዓ.ም ጀምሮ በስራ ላይ እንደዋለ ተመልክቷል፡፡ ክልሉን ከኦብነግ ይፋዊ “ፋኖ ተሠማራ” አዋጅ በኋላ ተረክቦ ሲያስተዳድር የነበረው የሶማሌ ዲሞክራቲክ ፓርቲ (ሶዴፓ)ም ከጐሣ አመለካከትና ከኦብነግ አስተሣሠብ የፀዳ አልነበረም፡፡ በውስጡ የነበሩ በርካታ አመራሮች በሁለት ቢላዋ የሚበሉ ነበሩ፡፡ በአንድ በኩል ህገመንግስቱን የተቀበሉ በማስመሠል ከፌደራል መንግስት ጋር ተባብረው ሲሠሩ፣ በሌላ በኩል ጫካ ለሚገኘው ኦብነግ ስንቅ በማቀበልና የጥቃት በሮችን በመክፈት ይተባበሩ ነበር፡፡

ከፌደራል መንግስት የሚላከው በጀት ሣይቀር ጫካ ለሚገኙት የኦብነግ ታጣቂዎች በደሞዝ መልክ ጫካ ድረስ ተወስዶላቸው ፈርመው ይቀበሉ ነበር፡፡ ይህ ደግሞ የኋላ ኋላ ኦብነግ እየተጠናከረ መጥቶ ራስ ምታት ለመሆን የመቻሉ ምስጢር አንዱ ምክንያት ነው፡፡ ኦብነግ እንዴት ተጠናከረ? በዘውዳዊው ስርአትና በደርግ ጊዜ የክልሉ ማህበረሠብ የሁለተኛ ዜግነት ማዕረግ እንዲኖረው መደረጉና ከሌላው የሃገሪቱ ማህበረሠብ የተለየ ተደርጐ መቆጠሩ፣ ህዝቡ ነፃ እናወጣሃለን ለሚሉት ልቡ እንዲያደላ አድርጓል፡፡ ኢህአዴግ ከመጣ በኋላም ይህ አስተሣሠብ ባለመቀየሩ የበለጠ ለኦብነግ ፕሮፓጋንዳ አመቺ ሆነ፡፡ ኦብነግ ለህዝቡ በሚያስተላልፋቸው መልዕክቶች “አማርኛ የሚናገር ደርግ ሄዶ ትግርኛ የሚናገር ደርግ መጣ” ይል ነበር፡፡ በዚህ የህዝቡን በተለይም በማህበረሠቡ ትልቅ ቦታ የሚሠጣቸውን የሃገር ሽማግሌዎችና የሃይማኖት መሪዎችን ቀልብ መግዛት ቻለ፡፡ ድጋፍም በሠፊው አገኘ፡፡ በትጥቅ፣ በኢኮኖሚ፣ በኔትወርክ (ግንኙነት) በደንብ ተጠናከረ፡፡ በርካታ የክልሉን ዞኖችና ወረዳዎችም በእጁ አስገብቶ ያስተዳድር ነበር፡፡

በጅጅጋ፣ በጐዴ ከሚገኙ አራት ካምፖች በስተቀር ሁሉም ወታደራዊ ካምፖች በቁጥጥሩ ስር ነበሩ - እስከ 2000 ዓ.ም ድረስ፡፡ ይህን እንቅስቃሴያቸውን ደግሞ ከኢህአዴግ ጐን በአጋርነት ተሠልፎ ይመራ የነበረው የወቅቱ አስተዳደር ይደግፍ ነበር፡፡ የክልሉ አመራሮች ስድስት ወር ህዝቡን ቤተመንግሥት ሆነው ይመራሉ፤ ስድስት ወር ይዋጋሉ፡፡ የኢፌዲሪ የመከላከያ ሠራዊትም በጦርነት ይማርክ የነበረው ዋናዎቹን ተዋጊዎች አልነበረም፡፡ እነሡ ቀን ተዋግተው ማታ ከከተማው ነዋሪ ጋር ተመሣስለው ይኖሩ ነበር፡፡ ሌላው ለኦብነግ የማታ ማታ መጠናከር አስተዋፅኦ ያበረከተው “ጅሃዲስት” ነኝ የሚለው አስተሣሠቡ ነው፡፡ ለማህበረሠቡ የሃይማኖት አባቶችና ሼካዎች “ከክርስቲያን መንግስት ጋር ነው የምዋጋው” እያለ ድጋፍ እንዲያደርጉለት ይጠይቃል፡፡

በዚህም ህዝቡ በየአመቱ በዘካ መልክ ገንዘብ እንዲሠጥ ተገደደ፣ የክልሉን በጀት የሚቆጣጠሩት እነሡ በመሆናቸውም የኢኮኖሚ አቅማቸው ፈረጠመ፡፡ ከተለያዩ የአረብ መንግስታት ጋርም ግንኙነት ፈጠረ፡፡ ከምዕራባውያን ጋር ሲገናኝም “ናሽናሊስት” (ብሄርተኛ) ነኝ ብሎ እርዳታ ይቀበላል፡፡ የገንዘብ ድጋፍ ሲያደርጉለት ከነበሩት ውስጥ የቀድሞው የሊቢያው መሪ መሃመድ ጋዳፊ በዋናነት ይጠቅሳሉ፡፡ ጋዳፊ በሡማሌ ክልል ለሚንቀሣቀሡ ታጣቂ ሃይሎች ከ5 ሚሊዮን ዶላር በላይ ድጋፍ ሠጥተዋል፡፡ ኳታርና ግብፅም ከፍተኛ ድጋፍ ያደርጉ ነበር፡፡ የውጭ ሃገር መንግስታዊ ያልሆኑ ድርጅቶችም በተረጂዎች ስም እስከ 1999 ዓ.ም ድረስ ያመጡትን እርዳታ ለኦብነግ ያስረክቡ ነበር፡፡ ይህን ሁሉ ሚስጥር የፌደራል መንግስት አመራሮች አብጠርጥረው የተረዱት በ1999 ዓ.ም ነው፡፡ በወቅቱም የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ፣ በጉዳዩ ላይ ሠፋ ያለ ትንታኔ ያለው ፅሁፍ አዘጋጅተው እንደነበር አቶ አብዲ ይናገራሉ፡፡ በወቅቱ በተደረገው የተሃድሶ ጉባኤም የማጥራት እርምጃዎች ተወስደው በርካታ በሁለት ቢላዋ የሚበሉ አባላትና አመራሮች እንዲወገዱ ተደረገ፡፡ የፌዴራል መንግስት አስቀድሞ ችግሩን ባለመረዳቱ፣ ይህ ሁሉ የክልሉ የውስጥ ትግል ሲካሄድ ብዙም ድጋፍ አላደረገም ነበር፡፡

በ1999 ዓ.ም ግን አቶ መለስ ራሣቸው ዋነኛ ተሣታፊ በመሆን፣ የክልሉ ቀደምት ችግሮችን በመፍታት ትልቁን ድርሻ መወጣታቸውን አቶ አብዲ ገልፀዋል፡፡ በአሁን ወቅት ክልሉን የኢትዮጵያ ሶማሌ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ (ኢሶዴፓ) እየመራው ሲሆን ፕሬዚዳንቱም አቶ አብዲ መሃመድ ናቸው፡፡ ከሐምሌ 11 ቀን 2004 ዓ.ም ጀምሮም ቀደም ሲል “የሶማሌ ክልላዊ መንግስት” የሚለው ስያሜ በአዲስ መልክ “የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልላዊ መንግስት” ወደሚል ተቀይሮ በዚሁ ስያሜ እየተጠራ ይገኛል፡፡ ሌሎች የክልሉ አስተዳደር ቢሮዎችም “የኢትዮጵያ ሶማሌ” በሚል መነሻ ስያሜ እንዲጠሩ ተደርጓል፡፡ ክልሉ በመጪው ዓመት ህዳር 29 ቀን 2006 ዓ.ም 8ኛውን የብሄር ብሄረሠቦች በአል ለማዘጋጀት መመረጡ የሚታወስ ነው፡፡ የዚህ በአል አከባበር አካል የሆነው የመጀመሪያው የህዝብ ለህዝብ ግንኙነት “የምስራቅ ኢትዮጵያን እንወቅ” በሚል መሪ ቃል ባለፈው ሰሞን የኪነጥበብ ባለሙያዎችና የሚዲያ ሠዎች እንዲሁም ፖለቲከኞች ወደ ክልሉ የተጓዙ ሲሆን አንፃራዊ ሠላም የሠፈነበት ክልሉ በአሉን ለየት ባለ መልኩ ለማክበር እየተዘጋጀ መሆኑን ለመረዳት ችለናል፡፡

      በአሜሪካ ኮሎራዶ ግዛት የሚገኘው የአውሮራ የህዝብ ቤተመፅሃፍት ከ80 ዓመት በላይ ያስቆጠረ የዕድሜ ባለፀጋ ነው፡፡ የዕድሜ ብቻ ግን አይደለም፡፡ በመፅሃፍት፣በመረጃ፣በንባብና በዘመናዊ የቤተመፅሃፍት አገልግሎት አሰጣጥም የተደራጀና የበለፀገ ነው፡፡ ከሁሉም የሚገርመው ደግሞ ጅማሬው ነው- አነሳሱ፡፡ ይሄን የህዝብ ቤተመፅሃፍት የማቋቋም ሃሳብ የፀነሱት እ.ኤ.አ በ1925 ዓ.ም የከተማዋን ማደግ ተከትሎ የተመሰረተው የአውሮራ ሴቶች ክበብ አባላት ናቸው፡፡ እነዚህ ትጉህና በአዳዲስ ሃሳቦች የተሞሉ የክበቡ አባላት ከተማዋ እየሰፋች ፤የነዋሪዋ ቁጥር እየጨመረ ሲመጣ ለአዋቂዎችም ሆነ ለታዳጊ ህፃናት አገልግሎት የሚሰጥ የህዝብ ቤተመጽሃፍት እንደሚያስፈልጋት ያሰቡት ቀደም ብለው ነበር፡፡ ከሃሳብ በቀር ግን ቤሳቤስቲን አልነበራቸውም፡፡

የሁሉም ትላልቅ ፈጠራዎች መነሻ ሃሳብ (ህልም) ነው እንዲሉ… ሃሳባቸውን በወረቀት ላይ አስፍረው፤ዕቅድ ነድፈውና ግብ አስቀምጠው ወደተግባራዊ እንቅስቃሴ ገቡ፡፡ ቤተመፅሃፍት የማቋቋም ህልማቸውንም እውን ለማድረግ በቁርጠኝነት መትጋት ነበረባቸው፡፡ ገቢ ለማሰባሰብ ፓርቲ አዘጋጅተዋል፤ ሻይና ደረቅ ምግቦች ሸጠዋል፡፡ የፅህፈት መሳሪያዎችን ቸርችረዋል፡፡ ትያትር አዘጋጅተው አሳይተዋል-ለአዋቂዎች 25 ሳንቲም፤ ለህፃናት 15 ሳነቱም እያስከፈሉ፡፡ የአውሮራ ሴቶች ክበብ ለአራት ዓመት ባደረገው ከፍተኛ ጥረት ፌብሯሪ 10 ቀን 1929 ዓ.ም ሳራ የተባለች የክበቡ አባል በፈቀደችው አንዲት ክፍል ውስጥ ቤተመፅሃፍቱ ተከፈተ፡፡ የክበቡ አባላት ቤተመፅሃፍቱን ሲከፍቱ በእጃቸው ላይ የነበራቸው ገንዘብ 171ዶላር ብቻ ነበር፡፡ በአንዲት ክፍል ፤በአንድ የቤተመፅሃፍት ባለሙያና በ171 ዶላር ለከተማዋ የመጀመሪያ የሆነው ቤተመፃህፍት አገልግሎት መስጠት ጀመረ፡፡

ከአንድ ዓመት በኋላ በ1930 ዓ.ም የካፒታላቸው መጠን 200 ዶላር የደረሰ ሲሆን 3100 መፃህፍትና አንድ የቤተመፃህፍት ጠረጴዛ ነበራቸው፡፡ በዚህ ወቅት በዚህች አንድ ክፍል ውስጥ በአንድ ወር ብቻ 906 ተጠቃሚዎች መስተናገዳቸው ተመዝግቧል - በዚህችው አንዲት የቤተመፅሃፍት ባለሙያ፡፡ ከ20ዓመት በኋላ ቤተመፅሃፍቱ እያደገና እየሰፋ የመጣ ሲሆን ከተለመደው የቤተመፅሃፍት አገልግሎት በተጨማሪ አዳዲስ ዝግጅቶችም ተጀምረው ነበር፡፡ ለምሳሌ ታላላቅ የመፃህፍት ውይይቶች ከመደረጋቸውም ባሻገር፣ የበጋ የንባብ ፕሮግራም እና የህፃናት የትረካ ሰዓት የመሳሰሉት ይጠቀሳሉ፡፡ በዚህ ሁሉ መሃል የክለቡ አባላት ከግለሰቦች እንዲሁም ቤት ለቤት እየዞሩ የመፅሃፍት ልገሳ የመሳሰሉት ይጠቀሳሉ፡፡ አውሮራ ቤተመፅሃፍት አሁን ከተቋቋመ 84ኛ ዓመቱን ይዟል፡፡

በአንዲት ክፍል ቤት ተጀምሮ አራት ቅርንጫፎችን መክፈት ችሏል- ያውም ማራኪና ዘመናዊ በሆኑ ህንፃዎች ውስጥ፡፡ በ175 ዶላር የተጀመረው ቤተመፅሃፍቱ፤ እ.ኤ.አ በ2004 ዓ.ም ዓመታዊ በጀቱ 5ሚ. ዶላር ሊደርስ ችሏል፡፡ የሰራተኞቹ ቁጥርም 118 ደግሞ 118 ደርሷል፡፡ ይሄ ግን የበጎ ፈቃድ አገልጋዮችን አይጨምርም፡፡ በነገራችን ላይ አውሮራ ቤተመፅሃፍት ለህፃናት የመዋያና የመጫወቻ ስፍራዎችን ያዘጋጃል፤ ህፃናት በነፃ የስልክ አገልግሎት ትረካ የሚሰሙበት አሰራር ዘርግቷል፡፡ አረጋዊያንንም ግን አልዘነጋቸውም፡፡ የአዛውንት መጠለያ ማዕከላት ድረስ አገልግሎቱን ይሰጣል፡፡ ቤተመፅሃፍቱ ከመፅሃፍት፣ መፅሄቶችና ጋዜጦች በተጨማሪ የኢንተርኔትም አገልግሎት አለው፡፡ የኦንላይን መፃህፍት እንዲሁም ዲቪዲና ሲዲዎችም ያቀርባል፡፡ ይሄ ሁሉ እንግዲህ ከ80 ዓመት በፊት የተፀነሰ ታላቅ ሃሳብና ህልም ፍሬ ነው፡፡

የህዳሴ ግድብ አሳሳቢ ውዝግብንና የ“ቢግ ብራዘር” መናኛ ቅሌትን እኩል ያስተናገድንበት ሳምንት

1 ከስደተኛ ኢትዮጵያውያን የሚላክልንን ዶላር እንፈልገዋለን፤ ግን ስደትን በጭፍን እናወግዛለን።

2 መብት ላለመንካት ለወራት ምርመራ እንደተካሄደ በተነገረ ማግስት, ስለ“ቶርቸር” ሰምተናል።

3 የተቃውሞ ሰልፍ በሰላም ተጀምሮ መጠናቀቁን ካየን በኋላ፣ በጠላትነት ሲወነጃጀሉ ታዝበናል።

4 “የነቤቲ የቢግ ብራዘር ጨዋታ” ቅሌት ነው ባልንበት አፍ፣ የወንበዴ ዛቻ እያወረድንባት ቀለልን።

“ግራ የሚያጋባና የሚያደናብር የተደበላለቀ ሕይወት!”… በዛሬው ዘመን፣ የአገራችን ልዩ ምልክት ይመስለኛል። “መደናበርና ግራ መጋባት”፣ ጤናማ ምልክት አይደለም። ነገር ግን፣ ለሺ አመታት ከዘለቀው “ያልተበረዘና ያልተከለሰ የኋላቀርነት ታሪክ” ጋር ሲነፃፀር፣ የዛሬው ሳይሻል አይቀርም።

በትንሹም ቢሆን፣ አሮጌውን የኋላቀርነት ባህል የሚበርዙና የሚያለዝቡ፣ ነገሮች ብቅ ብቅ፣ ጎላ ጎላ እያሉ መጥተዋል። እነዚህን አዳዲስ ነገሮች፣ የህዳሴ ምልክቶች ልንላቸው እንችላለን። ጥሬ ቆርጥሞ ማደርና ዋሻ ውስጥ ተገልሎ መኖር እንደ ትልቅ ስኬት የሚቆጠርበት ኋላቀር ባህል፣ ለስንት ዘመን ስር ሰዶ እንደቆየ አስቡት። አገራችንን እስርስር አድርጎ ለሺ አመታት አላንቀሳቅስ አላላውስ ብሎ የቆየ አሮጌ ባህል ነው። ድህነትና አቅመቢስነት ነግሶብን የቆየውኮ አለምክንያት አይደለም።

ታዲያ አሮጌው ባህል ሙሉ ለሙሉ ባይወገድ እንኳ፣ ያንን የድህነትና የአቅመቢስነት ባህል ጥቂት በጥቂት የሚሸረሽሩና የሚበርዙ ነገሮች ሲገኙ ጥሩ አይደለም? ጥሩ ነው እንጂ። የህዳሴ ምልክቶች ናቸዋ። ለምሳሴ፣ ሕይወታቸውን ለማሻሻል የሚፍጨረጨሩና ቢዝነስ የሚጀምሩ ወጣቶች ትንሽ ሲበራከቱ ካየን፣ የህዳሴ ምልክት ነው። በእርግጥ፣ ድክ ድክ ለማለት እንኳ ያልቻለ እንጭጭ ጅምር መሆኑ አይካድም። ቢሆንም፣ ድህነትን የሚያወድስና የሚያመልክ አሮጌ ባህልን ሊበርዝና ሊያለዝብ የሚችል ቅንጣት የቢዝነስ ባህል ለፍንጭ ያህል መፈጠሩ አይከፋም።

በራሳቸው ጥረት ሃብት አፍርተው በትልልቅ የኢንቨስትመንት መስኮች ትርፋማ የሚሆኑ ባለሃብቶች በየቦታው ብቅ ብቅ ሲሉ ካየን፣ የህዳሴ ምልክት አይተናል ማለት ነው። “የትም ሄደው፣ የሚያዋጣቸውን ሰርተው” ህይወታቸውን ለማሻሻል የሚጥሩ ወጣቶችን ካየንም የህዳሴ ምልክት ነው - ወደ ውጭ አገራት የሚሰደዱትም ጭምር። በአለማቀፍ ደረጃ በሳይንስና በቴክኖሎጂ፣ በቢዝነስና በስፖርት ገንነው የሚወጡ ኢትዮጵያውያን ካጋጠሙን፣ የህዳሴ ምልክት እንዳየን ቁጠሩት - በክለብም ሆነ በብሄራዊ የእግር ኳስ ቡድኖች የምናየው ጅምር ስኬትም ጭምር። ሳይንስንና ቴክኖሎጂን፣ ብልፅግናንና ብቃትን በጠላትነት የሚያይ ኋላቀር ባህልን የሚበርዝ የስልጣኔ ፍንጭ ሲገኝ፣ እልል ባንል እንኳ ፊታችን ፈካ ማለት አለበት። የተቃውሞ ሰልፍ በሰላም ተጀምሮ በሰላም ከተጠናቀቀ፣ የተቃዋሚ ፓርቲ መግለጫ በመንግስት ሚዲያዎች ከተስተናገደም የህዳሴ ምልክት ነው - ሳይወሉ ሳያድሩ አመሻሹ ላይ በጠላትነት መወነጃጀላቸው አልቀረም። አሮጌው የመጠፋፋትና የመጠላለፍ ባህል ገና ምኑም አልተነካማ።

ቢሆንም፣ በአንድ ጥግ በትንሹ ቅንጣት ያህል እንኳ ቢሆን፣ ኋላቀሩን አሮጌ ባህል የሚበረዝ ነገር ሲገኝ፣ “ጥሩ ነው” ማለት ይኖርብናል። የ“ቢግብራዘር” ቅሌትና “የወንበዴ” ዛቻ ሌላው ቀርቶ፣ በ“ቢግብራዘር” ጨዋታ ውስጥ በአህጉር ደረጃ መካፈል የሚችሉ ኢትዮጵያውያንን ማየትም “እንደ አቅሚቲ” የህዳሴ ምልክት ነው። ቁምነገር ኖሮት አይደለም። ግን፣ ቢያንስ ቢያንስ ከጥንታዊው “የሃሜትና የአተካራ ባህል” በመጠኑ እንድንወጣ ያደርገናል። ሳንጋበዝና ሳንጠራ፣ በጎረቤታችንና በስራ ባልደረባችን የግል ሕይወት ውስጥ እየገባን ከምንፈተፍት፣ በሃሜትና በአተካራ የሰዎችን ኑሮ ከምናናጋ፣ የ“ቢግብራዘር” ጨዋታ ላይ ተጥደን መዋልና ማደር እንችላለን። ሕይወታቸውን ከጥዋት እስከ ማታ እየተከታተልን፣ የፈለግነውን ያህል ውሎና አዳራቸውን እያነሳን “በሃሜትና በወሬ” እንድንፈተፍት ፈቅደው ጋብዘውናል። የ“ቢግብራዘር” ትርኪምርኪ ጨዋታ፣ ለኑሯችን የሚፈይደው ነገር ላይኖር ይችላል። ቢሆንም፣ የሃሜትና የአተካራ ሱስ ካለብን፣ ያልደረሰብንና እንድንደርስበት የማይፈልግ ሰው ላይ ሱሳችንን እየተወጣንበት ኑሮውን ከምናናጋ፣ የ“ቢግብራዘር” ውሎና አዳር ላይ ብናወራና ብንነታረክ አይሻልም? በእርግጥ፣ ለሕይወታችን አንዳች ፋይዳ ሳይኖረው፣ የሰዎችን ውሎና አዳር የምንከታተል ከሆነ፣ በዛም አነሰ “የማንወደው” ወይም “የማንስማማበት” ነገር ማየታችን አይቀርም።

ለነገሩ፣ የ“ቢግብራዘር” አዘጋጆች ከመነሻው በግልፅ ተናግረዋል። ጨዋታው… የፆታ ጨዋታንም እንደሚጨምር ገልፀዋል። የፆታ ጨዋታውና ትርኪምርኪው ገንኖ እንደሚወጣ በገልፅ አልነገሩን ይሆናል። ግን፣ እንደዚህ አይነት ዝግጅት ሄዶ ሄዶ መጨረሻው፣ ከዚህ የተለየ አይሆንም። ለምን መሰላችሁ? ሰዎች፣ በሌሎች ጨዋታዎችና ውድድሮች ላይ ተሳታፊ ለመሆን የሚገቡት ለምን እንደሆነ እናውቃለን - ልዩ ብቃታቸውን ለማሳየት ነው - እግር ኳስም በሉት ሩጫ፣ በጥያቄና መልስ ውድድርም በሉት በንግድ ተሰጥኦ ውድድር፣ … የተሳታፊዎቹ ዋነኛ አላማ፣ በልዩ ብቃት ብልጫ ማሳየት ነው። ጨዋታውን የምንመለከተውም፣ የሰዎችን ልዩ ብቃት ለማየት ነው። በቢግብራዘር ጨዋታስ? የተሳታፊዎችና የተመልካቾች አላማ ምንድነው? ነገርዬው የብቃት ውድድር አይደለም። ገመናን አጋልጦ የማሳየት ውድድር ነው። ከገመናዎቹ መካከል፣ የፆታ ጨዋታው ገንኖ ቢወጣ ምኑ ይገርማል? አይገርምም። መጥፎነቱ ያፈጠጠ የወሲብ ጨዋታዎችን ቀርፆ በቲቪ ማሰራጨት፣ ወሲብን የሚያረክስ ቅሌት ነው። ግን፣ ያን ያህልም የምንንጫጫበት ምክንያት አልታየኝም። ምንስ ያንጨረጭረናል? ቅሌቱን መሸከም ያለበት የቅሌቱ ባለቤት እንጂ እኛ አይደለን! እርር ድብን ሳንል፣ “ይሄማ ቅሌት ነው” ብለን ብንናገርና መናኛነቱን ብንገልፅ ተገቢ ነው።

ብዙዎች ግን፣ ከዚያ አልፈው “ከነቤቲ መናኛ ቅሌት” የባሰ፣ “የወንበዴ ክፉ ቅሌት” ውስጥ ገብተዋል። “አሰደበችን፣ ወደ አገር መመለስ አለባት፤ መቀጣጫ እናድርጋት” የሚል ዛቻ በየደረሱበት ሲያራግፉ ሰንብተዋል። “የዛቻ ቅሌት”፣ “ከነቤቲ ቅሌት” የሚብሰው ለምን መሰላችሁ? የነቤቲን ቅሌት እንድናይ፣ እንድንሳተፍ ወይም ሰለባ እንድንሆን በጉልበት ጎትቶ የሚያስገድደን ሰው የለም። ቅሌቱንም ሆነ መዘዙን የሚሸከሙት ራሳቸው ናቸው። “የወንበዴ ዛቻ” ግን፣ ከዚህ በእጅጉ ይለያል። በሰዎች ህይወት ላይ እንዳሻው ለማዘዝና ፈላጭ ቆራጭ ለመሆን የሚቃጣው ሰው፣ የራሱን ሕይወት ብቻ ሳይሆን የሌሎችንም ሕይወት ያበላሻል።

በአጭሩ፣ ያልደረሱበት ሰዎች ላይ ይደርሳል - ምንም ሳይበድሉት ሊደበድባቸው፣ ሊያሳድዳቸው፣ ሊገድላቸው ይፈልጋል - “እረፍ” ብሎ አደብ የሚያስገዛው ህግ ከሌለ። ለእያንዳንዱ ሰው ነፃነት ቅንጣት ታክል ክብር የለውማ። እንዲህ አይነት ሰዎች በአገራችን ብዙ መሆናቸው አይገርምም። ለሕይወትም ሆነ ለነፃነት ብዙም ክብር የማይሰጥ ባህል ለዘመናት ስር የሰደደበትና በኋላቀርነት ሲዳክር የቆየ አገር ውስጥ ነው የምንኖረው። አብዛኛው ሰው፣ ለግለሰብ ነፃነት ክብር ከሌለው፣ ፓርቲዎችና ፖለቲከኞች፣ የመንግስት አካላትና ባለስልጣናትም እንዲሁ በአብዛኛው ለግለሰብ ነፃነት ክብር የሚሰጡ ሊሆኑ አይችሉም።

በአንድ በኩል፣ ስልጣን ሳይኖረን እንዳሻን ሰው ላይ እየዛትን፣ በሌላ በኩል ዞር ብለን፣ “ስልጣን የያዘው መንግስት ነፃነትን የሚያከብር እንዲሆን እንፈልጋለን” ብለን ብንናገር ትርጉም የለውም። ለዚህም ነው፤ “ሰዎች፣ የሚመጥናቸው አይነት መንግስት ይኖራቸዋል” የሚባለው። መብታችንና ነፃነታችንን የሚያከብር መንግስት እንዲኖረን ከፈለግን፣ በቅድሚያ ለእያንዳንዱ ሰው መብትና ነፃነት ከፍተኛ ክብር የምንሰጥ መሆናችንን ማረጋገጥ ይኖርብናል። ያኔ በህዳሴ ጎዳና (በስልጣኔ ባህል) ላይ ትልቁን እርምጃ ተጓዝን ማለት ነው። የህዳሴን ጅምር ከአሮጌው ባህል ጋር እያደባለቅን ከመደናበር የምንላቀቀውም ያኔ ነው። የሙስና ምርመራና የ“ቶርቸር” ምርመራ ከሳምንታት በፊት፣ የፀረ ሙስና ኮሚሽን ለፓርላማ ባቀረበው ሪፖርት ላይ፣ በሙስና የተጠረጠሩ ባለስልጣናትን ከማሰሩ በፊት ለበርካታ ወራት ምርመራ ሲያካሂድ መቆየቱን ገልጿል። ምርመራው ለምን ያን ያህል ጊዜ እንደፈጀ ተጠይቀው ኮሚሽነሩ ሲመልሱ፣ የአንድም ሰው መብት መነካት ስለሌለበትና አስተማማኝ ማስረጃ ማሰባሰብ ስለሚያስፈልግ የበርካታ ወራት ምርመራ መካሄዱን ተናግረዋል። እንዲህ አይነት አስተሳሰብ፣ የህዳሴ ምልክት ነው። በሁሉም የመንግስት ተቋማት ውስጥ በተለይም በፍትህ አካላት ውስጥ በስፋት ልናየው የሚገባ ስልጡን አስተሳሰብ ነው፤ በንግግር ብቻ ሳይሆን በተግባርም ጭምር።

አሳዛኙ ነገር፣ በርካታ ተጠርጣሪዎች ከታሰሩ በኋላ ወደ ፍርድ ቤት ሲቀርቡ፣ በርካታ አሳሳቢ አቤቱታዎችን አቅርበዋል - ከህዳሴ ጋር የሚቃረን አሮጌው ባህልን የሚጠቁሙ አቤቱታዎች። ከጠበቃ ጋር ለመገናኘት መቸገራቸውን የተናገሩ እንዳሉ ሁሉ፣ ድብደባ እንደደረሰባቸውና “ወተር ቦርዲንግ” የሚባለው ስቃይ እንደተፈፀመባቸው የገለፁም አሉ። ሰሞኑን ደግሞ፣ ከተጠርጣሪዎቹ መካከል አንዷ፣ በውድቅት ሌሊት እራቁቴን ቀዝቃዛ ውሃ እየተደፋብኝ ምርመራ ይደረግብኛል በማለት ለፍርድ ቤት አቤቱታ አቅርበዋል። አቤቱታ ሲቀርብ፣ እውነቱን ለማረጋገጥ፣ እውነት ሆኖ ከተገኘም ተጠያቂውን ሰው ለማወቅ ምርመራ መካሄድ እንዳለበት ግልፅ ነው። ፍርድ ቤቱ የሰጠው ትዕዛዝም ይህን የተከተለ ይመስላል። በስልጣናቸው አላግባብ ተጠቅመዋል (ሙስና ፈፅመዋል) ተብለው የተጠረጠሩ ሰዎች ሲታሰሩ፣ ተጠርጣሪዎቹን እመረምራለሁ ብሎ ስቃይ የሚፈፅምባቸው ከሆነ ስልጣኑን አላግባብ እየተጠቀመ (ሙስና እየፈፀመ) ወንጀል እየሰራ ነው ማለት ነው። በእርግጥ፣ የፖሊስም ሆነ የፀረሙስና ኮሚሽን ተቋማት፣ “እስረኛን አናሰቃይም” በማለት እንደሚያስተባብሉ አይካድም። ጥሩ፤ ተጠርጣሪዎችን ማሰቃየት እንደ ትክክለኛ የምርመራ ዘዴ እንደማይቆጥሩት መናገራቸውም አንድ ቁም ነገር ነው።

ነገር ግን፣ እንዲህ አይነት አቤቱታዎችን በጠላትነት አይን ማየት የለባቸውም። አንደኛ ነገር፣ የፖሊስ ዋና አላማ፣ ህግ ማስከበርና የሰውን መብት ማስጠበቅ ነው። አቤቱታ ሲቀርብ፣ በቅንነት ተቀብለው ማጣራትና ምርመራ ማካሄድ አለባቸው። ሁለተኛ ነገር፣ ተጠርጣሪን ማሰቃየት እንደ ትልቅ ጥፋት ወይም እንደ ወንጀል የማይቆጥሩ ብዙ ሰዎች ባሉበት አገር፣ የፖሊስ አባላት በሙሉ በጭራሽ ተጠርጣሪን ለማሰቃየት የማይሞክሩ እንከን የለሽ ቅዱሳን ናቸው ብሎ መከራከር የትም አያደርስም። ሞባይል ሲሰረቅበት፣ የሚጠረጥራቸው ሰዎች ሁሉ ታስረው እየተቀጠቀጡ እንዲመረመሩለት የሚፈልግ ሰው የሞላበት ኋላቀር አገር ውስጥ ነው የምንኖረው። ይህንን አስተሳሰብ የሚከተሉ ፖሊሶች ቢኖሩ ምን ይገርማል? ሞልተዋል። ይህንን ለማስተባበል ጊዜ ከማባከን ይልቅ፣ አገሪቱ ከአሮጌው ባህል ተላቅቃ በህዳሴ ጎዳና እንድትራመድ የሚያግዝ ጥረት ላይ ብናተኩር ይሻላል። ለዘመናት የዘለቀውን ኋላቀር ባህል በአንዴ መለወጥ ባይቻልም፣ በየጊዜው የሚቀርቡ አቤቱታዎች ላይ ምርመራ በማካሄድ ቀስ በቀስ ስልጡን አስተሳሰብና አሰራር እየተስፋፋ እንዲሄድ ማድረግ ይቻላል።

አንዲት የቆቅ ልጅ የስንዴ እሸት ትርክክ ብሎ በስሎ በሚገኝበት እርሻ አጠገብ ወጥመድ ተጠምዶ አይታ እናቷን “እናቴ ሆይ እሸት አምሮኝ ነበር፤ ከዚህ ማሣ ገብቼ እንዳልበላ ወጥመድ እንዳይዘኝ ሰጋሁ ምን ይሻለኛል?” ስትል ጠየቀቻት፡፡ እናቷም፤ “ተይ ልጄ ይቅርብሽ ትያዣለሽ አይሆንም” ብላ መከረቻት፡፡ ልጅቷ ግን “ግድየለሽም አይዙኝም ትንሽ ተክ ተክ አድርጌ ልውጣ” አለቻትና ገብታ ስትበላ ያ ወጥመድ እናቷ እንደፈራችው እግሯን ጥርቅም አድርጐ ያዛት፡፡ መቼም መከራ በመጣ ጊዜ በመጀመሪያ የሚታሰቡት ወላጆች ስለሆኑ፤ ያቺ የእናቷን ምክር አልሰማ ያለች ልጅ፤ “እናቴ ኧረ ተያዝኩልሽ” አለቻት፡፡ እናትየዋም፤ “ምነው ልጄ አስቀድሜ ነግሬሽ አልነበረም? አሁን ምን ላደርግልሽ እችላለሁ?” አለቻት፡፡

እማምዬ እባክሽ እርጂኝ? ፍቺልኝ ገመዱን?” “በምን እጄ?” “ታዲያ እንዴት ልሁን? ምን ይበጀኝ የኔ እናት?” “በዚህ ጊዜ እናት ለልጁዋ ምን ጊዜም ምክር አዋቂ ናትና፤ “ዝም ብለሽ የሞትሽ መስለሽ ተኝ” “ባለወጥመዱ ሲመጣ ሞታለች ብሎ ፈትቶ ይለቅሻል፡፡ ያኔ ታመልጫለሽ” አለቻት፡፡ ልጅ እንደተባለችው አደረገች፡፡

ባለወጥመዱ ሰው ሰብሉን ጐብኝቶ መጣና ቢመለከት ዝልፍልፍ ብላ ተኝታ ዐይኗን ጨፍና አገኛት፡፡ አጅሬ የሞተች መሰለውና “አዬ ጉድ ወጥመዴ ቆቅ ይዞልኝ ነበረ፡፡ ነገር ግን ሞተች” አለና አዘነ፡፡ ጓደኛው ከበላዩ ሰብል ይጠብቅ ነበርና “ወንድም” ብሎ ተጣራ “ወጥመዴ ቆቅ ይዞልኝ ነበረ፡፡ ነገር ግን በክታ አገኘኋት” ባልንጀራውም፤ እስቲ ወደላይ አጉናት” አለው ባለወጥመዱ ወደ ሰማይ ወርወር አደረጋት፡፡ ቆቋ ቱር ብላ ከጫካው ጥልቅ አለች፡፡

                                             * * *

ምክር መቀበልና ማክበር ይገባል፡፡ አደጋ ላይ ሊጥል የሚችልን ነገር አስቀድሞ ማሰብ፣ ማውጠንጠንና መጠንቀቅ ተገቢ ነው፡፡ ብዙ አደጋዎችን፣ ብዙ ችግሮችን፣ ብዙ ውጣ - ውረዶችን ያየችው አገራችን መከራዋን ትወጣው እንጂ አብዛኛዎቹ የተከሰቱት ምክር በማይሰሙ መሪዎች፣ ኃላፊዎችና ሥራ አስኪያጆች ሳቢያ ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ የታለፉ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ባህላዊ አጋጣሚዎች ደግመን ማጣት ከእንግዲህ ብርቱ ዋጋ ያስከፍለናልና ጥንቅቅ ብለን ማሰብ ይገባናል፡፡ የድህነት ነገር ሆኖብን ሁሌ ሥራችንን በዘመቻ እንድንሠራ እንገደዳለን፡፡ አንድን ሥራ በነጥብ መብራት አተኩረን መሥራት ትልቅ ጉልበት በማከማቸት ግብ እንድንመታ ይረዳናል፡፡ ሆኖም ዘላቂና የኔነት ስሜት ያለው ሥራ እንድንሠራ በሙያዊ ብቃት፣ በሥራ ክፍፍልና በሙሉ ስሜት እንድንራመድ ካልሆነ ለብዙ ችግር እንጋለጣለን፡፡ ጦርነትም ቢሆን እንኳ በኃይል በኃይሉ፣ በክህሎት በክህሎቱ ሲሰደር ነው ለግብ ይበቃል የሚባለው፡፡ የጋራ ጥቅም ላይ ያነጣጠሩ መስሎ የግል ጥቅምን በጐን ማሳደድ ሊነቃበት የሚገባ ጨዋታ ነው፡፡ “ሌላ ጊዜ አንቺ ይላል፤ ጠላ ስትጠምቅ እሜቴ ይላል” የሚለውን የወላይታ ተረት ከልብ ማስተዋል ዋና ነገር፡፡

መቼም የሀገራችን ነገር አንዱ ሲወርድ አንዱ ሲወጣ ያለበት ነው፡፡ ከሥራውም ይልቅ ሰውዬውን ለሚያይ ዘላቂነት ያለውና ያለፈውን ስህተት ለማረም የቻለ ጉዞ ነው ለማለት አያስደፍርም፡፡ የሠራተኛው፤ የፓርቲ አባሉ፣ የበታች ኃላፊው ሁሉ፣ ሁልጊዜ “እናቴን ያገባ ሁሉም አባቴ ነው” የሚልበት ዘመን ያከተመ ይመስላል፡፡ “ተሰናባች አይርገምህ፤ ተተኪው አይጥላህ” የሚለውን በጥንቃቄ ካዩት ትርጉም ያለው ቁምነገር ያስጨብጠናል። ተሰናባች በግፍ፣ በምቀኝነት ወይም በአድልዎ ተባሮ ከሆነ እርግማኑ ይደርስብኛል ብሎ ማሰብ የአባት ነው፡፡ ተተኪው በተንጋደደ ዐይን የሚያይ ከሆነና “ለዚያኛው ያልተኛ እኔን አይምረኝም” ብሎ ያሰበ ከሆነም ሲሰጉ መኖር ነው፡፡ ከዚህም ይሰውረን፡፡

የሚመጣውን ሁሉ ተዘጋጅቶ መጠበቅ ያለ ነው፡፡ ጣር መጣ ጦር መጣ እያሉ በጣም ያስፈራሩት ጀግና፤ በዝግታ እየተዘጋጀ፤ “ይምጣ ከመጣ ሞቼ ልጠብቀው እንዴ ልዘጋጅ እንጂ!!” አለ የሚባለውንም አንዘንጋ፡፡ ጉዳዩን የሚያቅ፤ የበሰለ፣ ባለገድልና ባለታሪክ ሰዋችንን አንናቅ፡፡ ከየቦታው ሰብስበን ሥራ ላይ እንዲቀመጥ እናድርግ፡፡ ልታይ ልታይ የሚለውንና የአደባባይ ጌጥ የሆነውን ትተን፤ ከልቡ ለሀገር የሚያስበውን እናስተውል፡፡ “ይቺ እንዴ ትጨፍራለች?” ቢባል፤ “ልብስ አጥታ እቤት የቀረችውን ባየህ!” አለ፤ የሚባለው የወላይታ ተረት የሚነግረን ይሄንኑ ነው፡፡

                       ካለፈው ሳምንት ጀምሮ በአገር አቀፍ ደረጃ እየተከበረ የሚገኘውን “የፍትህ ሳምንት” ምክንያት በማድረግ የተለያዩ የህግ ባለሙያዎችን የፍትህ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታን ጨምሮ የተለያዩ የፍትህ አካላትን ሃላፊዎች እንዲሁም የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች አነጋግረናል - በፍትህ ዙሪያ፡፡ “የህግ የበላይነት ለመልካም አስተዳደር መስፈን በህዝቦች ተሳትፎ” በሚል መሪ ቃል የፍትህ ሚኒስቴር፣ የፌደራል ፍርድ ቤቶች፣የፌደራል ማረሚያ ቤቶች አስተዳደር ፣የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽንና የአዲስ አበባ ፖሊስ ኮሚሽን በጋራ በመሆን ባዘጋጁት “የፍትህ ሳምንት” ላይ ጥናቶች ቀርበው ውይይቶችም ተካሂደዋል፡፡ ለመሆኑ የፍትህ ሳምንት መከበር ፋይዳው ምንድነው? በአገሪቱ ላይ ያለው የፍትህ ሁኔታስ ምን ይመስላል? የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ሰላም ገረመው ጉዳዩ ከሚመለከታቸው ወገኖች ያሰባሰበቻቸው አስተያየቶች እንደሚከተለው ቀርበዋል፡፡

“ውሳኔ ለማግኘት ሁለት አመት ድረስ ሊቆይ ይችላል”
የወንጀል ጉዳዮች ቶሎ አይወሰኑም፡፡ የፍትህ ስርአቱ ጥሩ አይደለም፡፡ የተወሰኑ ችሎቶች ላይ ከባድ የሚባሉ ችግሮች አሉ፡፡ 16ኛ የወንጀል ችሎት፣ 3ኛ የወንጀል ችሎትና ጠቅላይ ፍ/ቤት የፍትሃብሔር ችሎት አንድ በመሆኑ ከፍተኛ ችግር ይታይባቸዋል፡፡ የመጀመሪያ ደረጃ ደግሞ 7ኛ እና 11ኛ ችሎት አብዛኛውን ጊዜ አዳዲስ ሰዎች ስለሚመጡ ጉዳያችን ቶሎ አያልቅም፣ ውሳኔ ለማግኘት ሁለት አመት ድረስ ሊቆይ ይችላል፡፡ አቃቤ ህጐች ደግሞ ችግራቸው ክሶችን ቶሎ አይከፍቱም፡፡
አቶ ስሜነህ ታደሰ
(ጠበቃ)

“ፍትህ የሚከበር ሳይሆን የሚሰፍን ጉዳይ ነው”
የፍትህ ሳምንት መከበር ሳይሆን የሚያስፈልገው መበየን ነው ያለበት፡፡ ፍትህ የፈጣሪ ስራ ነው፡፡ ፍትህ የሚከበር ሳይሆን የሚሰፍን፣ የሚተገበር ጉዳይ ነው፡፡ ህጋዊነት ማስፈን ትንሽ ስራ ቢሆንም ለአገራችን ግን ህጉን አክብሮ መስራት በራሱ በቂ ነበር፡፡ ፍትህ የአንድ አገር ትልቅ ጉዳይ ነው፡፡ ማርኬሌሊ የተባለ የጣሊያን የፖለቲካ ፈላስፋ ሲናገር፤ “አንዳንዴ ሰዎች የምትናገረውን እንጂ የምትሠራውን አያዩም” ይላል፡፡ ስለ ፍትህ ስትናገሪ ስራሽን ያላዩ በንግግር እንዲታለሉ ለማድረግ ካልሆነ በስተቀር ሌላ ጥቅም የለውም፡፡ በእኔ ደንበኞች ላይ እየሆነ ያለው ነገር ይሄ ነው፡፡ ተጠርጣሪዎች ቶርች ተደርገው (ተገርፈውና ተደብድበው) በኢቴቪ አለአግባብ እንዲናገሩ እየተደረገና ከዚያም በዚህ ጉዳይ ላይ የፍትሀብሔር ክስ ለመመስረት ስንጠይቅ ፍ/ቤቱ ለመጀመሪያ ጊዜ አልቀበልም ብሏል፡፡ እንግዲህ “ፍ/ቤት ለሁሉም እኩል ነው” ተብሎ ነው የሚታሰበው፡፡ ግን ፍ/ቤት ራሱ ህግን ሳያከብር የፍትህ ሳምንት ማክበር ምን ይጠቅማል? በቶርች ማስረጃ ለማውጣት ሰው እየተሰቃየ ነው፡፡ የፀረ ሽብር አዋጁን ተቃውመን ለመንግስት አጣሪ ጉባኤ ጥያቄ ብናቀርብም እስካሁን ምላሽ አላገኘንም፡፡ የትላንት ባለስልጣናት ዛሬ ታስረው መብታችን ተጣሰ እያሉ በመጮህ ላይ ናቸው፡፡ ይሄን ሁሉ ስናይ በኢትዮጵያ ያለው ፍትህ የሚያስታውሰን የጣሊያኑን ፈላስፋ አባባል ብቻ ነው፡፡
አቶ ተማም አባቡልጎ
(ጠበቃ)

“ፖሊስ ተጠርጣሪዎችን ከያዘ በኋላ ማስረጃ መፈለግ የለበትም”
ፍ/ቤቶች ኮምፒዩተራይዝድ መሆናቸው ጥሩ ነገር ነው፡፡ በየቦታው ባሉ ህንፃዎች ላይ ፍርድ ቤቶች መከፈታቸው አንድ ለውጥ ነው፡፡ ፖሊስ ከአቃቤ ህግ ጋር መስራቱ፣ ክሱን ለመመስረት በአንድ ቦታ ስለሆኑ ጊዜን ያቆጥባል፤ በፊት የተለያየ ቦታ ስለሆኑ ክስ ለመመስረት ብዙ ጊዜ ይፈጅ ነበር፡፡ የፖሊስ ማስረጃ ፍለጋ ኋላቀር መሆን ግን አሁንም መስተካከል ይቀረዋል፡፡ ብዙ ጊዜ ተከሳሽን አስሮ “ምርመራ ይቀረናል” እያለ በወንጀል ጉዳይ የተጠረጠሩትን ያጉላላል፡፡ ታሳሪና ጠበቃ በዋናነት መገናኘት ያለባቸው በምርመራ ጊዜ ቢሆንም ፖሊስ ግን ምርመራ ሳልጨርስ ተከሳሽና ጠበቃን አላገናኝም ይላል፡፡ እንደውም ተከሳሽ ቃሉን ሊሰጥ የሚገባው ጠበቃው ባለበት ሁኔታ መሆኑን ህግም ይደግፋል፡፡ ሌላው ቢቀር ተከሳሽ ቃሉን ያለመስጠት መብት እንዳለው እየታወቀ፣ ከጠበቃው ጋር እንዳይገናኝ መደረጉ አግባብ አይደለም፡፡ ፖሊሶች ጋ ያለው የተሳሳተ አመለካከት፣ ጠበቆችን ፍትህ የሚያዛቡ አድርጐ ማየት ነው፡፡ አንድ ተከሳሽ በምርመራው ጊዜ ተገቢውን እርዳታ ካላገኘ፣ መደበኛ ክስ ሲከፈት በጣም አስቸጋሪ ነው የሚሆነው፡፡ ሌላው በወንጀል ጉዳይ የተጠረጠሩ ሰዎች ቶሎ ፍ/ቤት መቅረብ አለባቸው ፤ ፖሊስም ቢሆን መጀመሪያ ማስረጃ መያዝ አለበት እንጂ ተጠርጣሪዎችን ከያዘ በኋላ ማስረጃ መፈለግ የለበትም፡፡
አቶ ደበበ ኃ/ገብርኤል
(የህግ ባለሙያ)

“የፍትህ ስርዓቱ ብዙ ይቀረዋል”
የፍትህ ሳምንት መከበሩ ምን ይጠቅማል? ምናልባት የሚመለከታቸው ተገናኝተው ችግሮችን ለመቅረፍ ከሆነ ያስኬዳል፡፡ ዳኞችና አቃቤ ህጐች አብረው ሊበሉና ሊጠጡ ከሆነ ግን ውጤቱ ምን ሊሆን እንደሚችል መገመት አያስቸግርም፡፡ በአንድ በኩል ጥሩ ነገር አለው፤ በሌላ በኩል ችግር አለው፡፡ የአገራችን የፍትህ ስርአት ብዙ ይቀረዋል - ከአወቃቀር፣ ከአደረጃጀት፣ ከብቃት፣ ከሰው ሃይል ጀምሮ … የህግ እውቀት ማነስ ችግሮች ሁሉ አሉ፡፡ የፌደራል ፍ/ቤቶች በቤኒሻንጉል፣ በሱማሌ፣ በአፋር፣ በደቡብ እንዲቋቋሙ በአዋጅ የወጣው በ1995 ዓ.ም ነው፤ እስካሁን ግን አልተቋቋመም፡፡ ይሄ የሚያሳየው ተደራሽ አለመሆናቸውን ነው፡፡ የፌደራል አቃቤ ህጐችም በመላው ክልል ነው መቋቋም ያለባቸው፡፡ አሁን ያለው አዲስ አበባ እና ድሬደዋ ላይ ብቻ ነው፡፡
ዘርአይ ወ/ሰንበት
(የቀድሞ አቃቤ ህግ)

“የፍትህ ሳምንት ማክበር ማሾፍ ነው”
ፍትህ በሌለበት አገር የፍትህ ሳምንት ማክበር መቀለድ ነው የሚሆነው፡፡ ፍትህ ያጣ ህዝብ እያለቀሰ፣ ፖለቲከኛና ተቃዋሚ ስለሆኑ ብቻ ዜጐች እየታሰሩ፣ ሰዎች ከሃይማኖታቸው ጋር በተያያዘ “ሽብርተኛ” ተብለው እስር ቤት እየገቡ፣ ከዛም አልፎ ሃሳብን በነፃነት የመግለጽ መብት ተነፍጐ ጋዜጠኞች በሚታሰሩባትና አሁንም ድረስ “አምላክ ይፈርዳል” በሚባልባት አገር የፍትህ ሳምንት ማክበር ማሾፍ ነው፡፡ ፍትህ መታየት ያለበት በተግባር ነው፡፡ ባለፈው አመት ኪሊማንጀሮ የተባለ የጥናት ተቋም ባወጣው ሪፖርት፤ በኢትዮጵያ ውስጥ እምነት ከማይጣልባቸው ተቋማት አንዱ የፍትህ አካላት መሆናቸው ተገልጿል፡፡
ለምሳሌ አንዷለም አራጌን በእስር ቤት መጠየቅ አይቻልም፡፡ ከፍርድ ቤት ውሳኔ በፊት ኢቴቪ ተጠርጣሪዎችን “ሽብርተኛ” እያለ የሚፈርድበት ጊዜ አለ፡፡ በማረሚያ ቤት ደግሞ ድብደባ፣ ማንገላታት፣ ጨለማ ቤት ማሰር--- አለ፡፡ ታዲያ እዚህች አገር ላይ ነው የፍትህ ሳምንት የሚከበረው? ፍትህ የሚባለውን የምናውቀው በስም ነው፡፡
አቶ ዳንኤል ተፈራ
(የአንድነት ፓርቲ የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ)

“እዚህ አገር ይግባኝ የሚባለው ለእግዚአብሔር ነው”
የፍትህ ስርአቱ የተጠናከረ ነው፤ የኢህአዴግን ፖለቲካ እንዲያገለግል የተቀመጠ ነው፡፡ እንዲህ የምንለው የፍትህ ስርአቱን ደጋግመን በሞከርነው ነገር ስላየነው እንጂ ኢህአዴግን ስለምንጠላው አይደለም፡፡ ውሳኔዎቹ ፖለቲካዊ ናቸው፡፡ በቅርቡ እኛ ላይ የደረሰ የፍትህ መስተጓጎል አለ፡፡ የወረዳ ፓርቲ ሃላፊ የሆነ ግለሰብ የአባትህን መሬት አታርስም በሚል ፍ/ቤት ተከሶና ተፈርዶበት ሆሳእና ታስሮ ነው ያለው፡፡ ማስረጃ የማይሰማ ፍ/ቤት ባለበት ሁኔታ የፍትህ ሳምንት ማክበር ጨዋታ ነው፡
እኛ ራሳችን የአገራዊ ምርጫ ጉዳይ ህገወጥ ነው ብለን የተቃጠለውንና መፀዳጃ ቤት የተወረወረውን ድምፅ የተሰጠበትን ወረቀት ሰብስበን ስንሄድ “በእለቱ ነው ክስ መመስረት የነበረባችሁ” ተባልን፡፡ በእለቱ እንዳንሄድ እሁድ ነበር፤ እነሱ ግን እሁድም እንሠራ ነበር አሉ፡፡ ይሄንን ደግሞ ማንኛውም ኢትዮጵያዊ አያውቅም፡፡ ስለዚህ ይሄ የፍትህ ሳምንት ሽፋን ነው እንጂ ሌላ አይደለም፡፡ እዚህ አገር ይግባኝ የሚባለው ለእግዚአብሔር ነው፡፡
ፕ/ር በየነ ጴጥሮስ
(የመድረክ ፓርቲ ም/ሊቀመንበር እና
የህዝብ ግንኙነት ሃላፊ)

“መንግስት ችግሩን አሳምሮ ያውቃል”
በአፍሪካ ደረጃ በተደረገ ጥናት፣ ኢትዮጵያ ውስጥ እምነት የማይጣልባቸው ተቋማት ከተባሉት አንዱ የፍትህ ስርአት መሆኑ ተገልጿል፡፡ ዜጐች መፍትሔ እያጡ ነው፡፡ ፍትህ ማጣታቸው ገዝፎ እየታየ የመጣው ከአፄው ጀምሮ ነው፡፡ የፍትህ ሳምንት መከበሩም ከፕሮፖጋንዳ ያለፈ ነገር አለው ማለት አይቻልም፡፡ መንግስት ችግሩን አሳምሮ ያውቃል፡፡ ለፍትህ መጥፋቱ ዋናው እኮ የስልጣን ክፍፍል አለመኖሩ ነው፡፡ የአስፈፃሚው አካል እንደልቡ ተንቀሳቅሶ መስራት ካልቻለ ፍትህ ይዛባል፡፡
ዶ/ር መረራ ጉዲና (የመድረክ ፓርቲ ም/ሊቀመንበር)
“ፍትህን ለማስፈን በርካታ ስራዎች ተሰርተዋል”
ይቅርታ ለጠየቁ ታራሚዎች ሁሉ ይቅርታ ይሰጣል ማለት አይደለም፡፡ በሀገራችን ህግ እንደ መብት አልተቀመጠም፡፡ ይቅርታ ሰጪው አካል በተለያዩ ምክንያቶች ይቅርታ ሊሰጣቸው ይገባል ብሎ ለሚያስባቸው ወገኖች ይቅርታ ይፈቅዳል፡፡ እነዚህ ሰዎች ባለው አግባብ ይቅርታቸውን አቅርበው እንዲታይላቸው ማድረግ ይችላሉ፡፡ ጠይቀው ካልተፈቀደላቸው ደግሞ ከስድስት ወር በኋላ መልሰው የመጠየቅ መብት አላቸው፡፡ ይህንን ሚኒስትሩ ሲመጡ የሚወስኑት ይሆናል፡፡
በአገሪቱ ፍትህን ለማስፈን በተወሰዱ እርምጃዎች በርካታ ስራዎች ተሰርተዋል፡፡ የፍትህ አካሉን የባለሙያዎች ህገመንግስታዊ አመለካከቶች ለማረጋገጥና አቅማቸውን ለማጐልበት በርካታ ስራዎች ተሰርተዋል፡፡ የፍትህ ሳምንት የሚከበረው በቀጣይ ፍትህ በማስፈን ረገድ ምን ሊከናወን እንደሚችል ለማየት እንዲሁም እስካሁን የተሰሩ ስራዎችን በመገምገም ችግሮችን ለመቅረፍ ሲሆን ህዝቡ የፍትህ ስርአት ባለቤት በመሆኑ የአገራችንን የፍትህ ሁኔታ ለማሳየትም ጭምር ነው፡፡
አቶ ልዑል ካህሳይ
(የፍትህ ሚኒስቴር፤ ሚኒስትር ዴኤታ)

“ህብረተሰቡ ካላገዘን ውጤታማ አንሆንም”
ሙስና መኖሩ በአደባባይ የሚታይ ነገር ነው፡፡ ይሄንን ለእናንተ የሚናገሩ ሰዎች ለእኛም መጥተው መንገር አለባቸው፤ እንጂ በአደባባይ “ፍ/ቤት ውስጥ ሙስና ይሰራል” ብሎ ብቻ ማውራት አይጠቅምም፤ በእርግጥ ሙስና የሚሰሩ የሉም አንልም፡፡ ከዳኝነት አካላት ብቻ ሳይሆን ከታችም ያሉ ሰዎች ሊፈፀሙት ይችላል፡፡ በዳኛም ስም የሚፈፀም ይሆናል፤ የተወሰኑ ሰዎች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡
“ለዳኛ ብር እንሰጣለን” የሚሉ በርካታ ስራ ፈት ፍ/ቤት የሚውሉ ሰዎች እንዳሉ እንሰማለን፤ ግን ህብረተሰቡ ካላገዘን ውጤታማ አንሆንም፡፡ በዚህ ምክንያት ተቋሙ ተአማኝነት ያጣል፡፡ በጥቂት ሰዎች አላስፈላጊ ስራ ተቋሙ መወሰን የለበትም፡፡ በሙስና ብቻ ሳይሆን በሌላም ሊሆን ይችላል፡፡ ዳኞች ቢሆኑም ያደረጉት ከሆነ ውሳኔ እንሰጣለን፡፡ መረጃ በሌለበት ሁኔታ ግን ዳኝነት በነፃነት የሚታይ ነገር በመሆኑ ያለአግባብ መጠየቅ አንችልም፡፡ በተለይ ደግሞ እንዲህ አይነት መድረኮች መዘጋጀታቸው ከህብረተሰቡ ጋር በቅርበት በመገናኘት ችግሮችን ለመፍታት ያስችላል፡፡
የተከበሩ አቶ ተገኔ ጌታነህ
(የፌዴራል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዝዳንት)

“በታራሚዎች አያያዝ በርካታ መሻሻሎች አሉ”
የታራሚዎችን መብት ለማስከበር ከህገመንግስቱ ጀምሮ ለጠባቂዎቻችን ስልጠና እንሰጣለን፡፡ በእኛ ብቻ ሳይሆን ከሰብአዊ መብት ጋር ተነጋግረን ስልጠናውን እንዲያገኙ እናደርጋለን፡፡ የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ድርጅት በአንድ ወቅት ያደረገውን ጥናት ይፋ አድርጐ ነበር፡፡ በዚያ መነሻነት በዝርዝር እቅድ አውጥተን ግምገማ አድርገናል፡፡ ከእኛ ባለፈ ደግሞ ፓርላማ በየ6 ወሩ ይገመግመናል፡፡ አቅም በፈቀደ መንገድ ስራዎች ይከናወናሉ፡፡ ከህጉ ውጭ በታራሚዎች ሰብአዊ መብት ላይ ችግር የሚፈጥር ካለ አስተዳደራዊ እርምጃ እንወስዳለን፤ የወሰድንባቸውም አሉ፡፡ እነዚህን ሁሉ አድርገን በግለሰብ ደረጃ የሚፈፀሙ ጥፋቶች የሉም ማለት ግን አይደለም፤ በርካታ ታራሚዎች ስላሉ ችግር መከሰቱ አይቀርም ፤ነገር ግን በርካታ መሻሻሎች አሉ፡፡
አምስቱ ተቋማት የእድገትና ትራንስፎርሜሽን እቅድን መነሻ በማድረግ የጋራ ስትራቴጂክ እቅድ አዘጋጅተዋል፡፡ እነዚህ እቅዶችም እያንዳንዱ ተቋም ከራሱ ተጨባጭ ሁኔታ ተነስቶ ወደ እራሱ እየወሰደ የሚሠራበት እና በጋራ የሚሰሩ ስራዎችም ለማከናወን በአጠቃላይ በፍትህ ስርአት ውስጥ ያሉትን ክፍተቶች አይቶ በመነጋገር፤ የአሰራር ክፍተቶች ካሉ በመመልከትና በመቅረፍ ትኩረት ሰጥተን እየሰራናቸው ነው፡፡ ማረሚያ ቤትን ብንወስድ ከፍ/ቤት ጋር የሚያገናኙ ስራዎች አሉ፡፡ ለምሳሌ ዝዋይ የታሰረ ታራሚ በቀጠሮ ጊዜ ወደዚህ በመምጣት ከሚንገላታ በፕላዛ ቲቪ በቀጥታ የፍ/ቤቱን ጉዳይ እንዲከታተል የሚደረግበት አሠራር ዘርግተናል፡፡ የአመክሮና የይቅርታ አሠራር ሁኔታንም በተመለከተ ታራሚ እንዳይጉላላ ለማድረግ ከሚመለከታቸው አካላት ጋር እነዚህን ሁኔታዎች እየሰራን ሲሆን ጥምረታችን ደግሞ ይሄንን ለማከናወን ያግዛል፡፡
የፍትህ ሳምንት መከበሩ ጥቅም አለው፡፡ ስራችን ከህዝብ ውጭ አይደለም፤ እኛ ጥሩ ሰራን ብንልም በህዝብ ዘንድ ደግም እርካታን ያልፈጠሩ ነገሮች ይኖራሉ፡፡ እነዚህን ከህዝብ ጋር ተገናኝተን ለመወያየት እድል ይሰጠናል፡፡ ሁለተኛ የተቋማችንን ገጽታ ከመገንባት አንፃርም ትልቅ ድርሻ አለው፡፡
አቶ አብዱ ሙመድ
(የፌዴራል ማረሚያ ቤቶች ዋና ዳሬክተር)

“ህገመንግስቱን በማክበር እየሰራን ነው”
በሙስና ተጠርጥረው የተያዙ ሰዎች ፍ/ቤት ቀርበው የሰብአዊ መብት ጥሰት ተፈፀመብን ሊሉ ይችላሉ፣ ግን በማስረጃ አላረጋገጡም፡፡ የምርመራ ስርአታችን ህግን የተከተለ ነው፤ በተቻለ መጠን እኛ ጋ የምንመረምራቸው ወንጀሎች በአገርና በህዝብ ላይ ከፍተኛ ጉዳት ያደርሳሉ ተብለው የሚታሰቡትን ነው፡፡ እነዚህ ወንጀሎች የተለያዩ ግብአቶች ይኖራቸዋል፡፡ ተጠርጥረው የሚመጡት ደግሞ ንፁህ ሊሆን ይችላል ወይም ሊወሰንበት ይችላል፡፡ እኛ ጋ ደግሞ ይህንን ሁለቱንም በማየት ነው ምርመራ የምናደርገው፡፡ በምርመራችን ድርጊቱ ለመፈፀሙ በቂ ማስረጃ ካለን፣ ፈፃሚው ማነው? የመፈፀም ደረጃው ምንድነው? የሚለውን ማግኘት፣ መፈፀሙ ጥርጣሬ ካለው ማረጋገጥ፣ የፈፀመው ሌላ አካል ከሆነ እኛ ጋር በተጠርጣሪነት ያለውን ግለሰብ ነፃነት አረጋግጠን እንሸኛለን፡፡
ከዚያ አኳያ ሳይንሳዊ ምርመራዎች የምርመራ ህጐች የሚፈቅዳቸው አርትንም ጭምር ሁሉ እንጠቀማለን፤ መርማሪዎቻችን የካበተ ልምድ አሏቸው፡፡ በሽብር በተደራጁ፣ በሙስና ወንጀሎች፣ በፋይናንስ ወንጀሎች ጥሩ ውጤቶች አሏቸው፡፡ ከፍተኞች ለጀማሪዎች እነዚህን ልምዶቻቸውን የሚያስተላልፉበት እና አዳዲሶችም የተሻለ ነገር ለማድረግ የሚጥሩበት ሁኔታ ነው ያለው፡፡ በዚህ ሂደት በባህሪያቸው ብልጣ ብልጥ የሆኑና የማጭበርበር ባህሪ ያላቸው ፍ/ቤትን ለማሳሳት ይፈልጋሉ፡፡ የምርመራ መነሻ ላይ የመጀመሪያ ጥያቄ የዋስትና መብት፣ የዘመድ፣ የጠበቃ፣ የሃይማኖት፣ የመጠየቅ መብት ተከለከልን ነው፡፡ ሁለተኛው ነገር በምርመራ ሂደት እንዲህ ተደረግን፣ ሰብአዊ መብታችን ተጣሰ የሚሉ ነገሮች ናቸው፡፡ እኛ ግን ምርመራዎቻችንን የምናካሂደው ተጨባጭ በሆኑ ነገሮች ላይ ተጠቅመን ነው፡፡
በየደረጃው ያለን ሃላፊዎች የሚደረጉትን ምርመራዎች የምናይበት ሁኔታ አለ፡፡ ፍ/ቤት ባለው በማንኛውም ጥርጣሬ ላይ እውነቱን ማረጋገጥ ይችላል፡፡ የሰብአዊ መብት ቅሬታም ሲቀርብለት እኛን መጥቶ ማየት ይችላል፤ እኛም ህገመንግስቱን በማክበር እየሰራን ነው፡፡ተጠርጣሪዎቹ ያነሷቸው ነገሮች እንዳይፈፀሙ ከፍተኛ ጥረት ይደረጋል፡፡ በትላልቅ ወንጀሎች አንዳንድ ሰዎች እንዲህ አይነት ነገር ቢያነሱም የምርመራ ጊዜያቸውን ጨርሰው ማረሚያ ቤት ሲሄዱ የምርመራውን ሂደት ሲኮንኑ አይታዩም፡፡ ስለዚህ እንደ ህዝብ ሰብአዊ መብቱ ተጥሷል አልተጣሰም የሚለውን መገመት ይቻላል፡፡ ይሄ ዘዴ ክሱ ሲመሰረት መጀመሪያ ለማምለጥ የሚያደርጉት ቀላሉ ዘዴያቸው ነው፡፡
የፍትህ ሳምንት ዋና አላማው፣ የፍትህ አገልግሎት የምንሰጥ ተቋማት እና በቀጥታ አገልግሎት ተጠቃሚ የሆነው ህብረተሰብ እና ባለድርሻ አካላትን በፍትህ አሰጣጥ ዙሪያ ልዩ ትኩረት ሰጥተን እንድንወያይ ማድረግ እና ጥሩ አፈፃፀሞቻችንን ማጉላት፣ ደካማ አፈፃፀሞቻችንን ማሻሻል የምንችልበትን ውይይት እና ምክክር የምናደርግበት መድረክ ነው፡፡
ም/ኮሚሽነር ጀነራል መስፍን አበበ (የፌደራል ፖሊስ ወንጀል ምርመራ ዘርፍ ሃላፊ)

 

በሽብርተኝነት ወንጀል ክስ ቀርቦበት የ18 ዓመት እስራት የተፈረደበት እና ቃሊቲ ማረሚያ ቤት የሚገኘው ጋዜጠኛ እስክንድር ነጋ፤ ከባለፈው ቅዳሜ ጀምሮ ማንኛውም ሠው እንዲጠይቀው መደረጉን ባለቤቱ ጋዜጠኛ ሠርካለም ፋሲል ለአዲስ አድማስ ገለፀች፡፡ ላለፉት 22 ወራት ከአራት ሰዎች በስተቀር ማንም እንዳይጠይቀው ተከልክሎ እንደነበር የገለፀችው ሰርካለም፤ “አሁን ተመስገን ነው ልዩ ጠባቂም የተከለለ ቦታም ሳይዘጋጅ ረጅም ሠዓት ማዋራትና መጠየቅ ችያለሁ” ስትል ደስታዋን ገልፃለች፡፡

ከ10 ቀናት በፊት ሀሙስ ማለዳ ልትጠይቀው ስትሄድ በግምት 40 ሠዎች ብቻ በሚኖሩበት ዞን ሶስት እንደተለመደው ለ10 ደቂቃ አይታው መመለሷን የገለፀችው ሰርካለም፣ ቅዳሜ ዕለት ለ30 ደቂቃ የተፈቀደውን የመጠየቂያ ሰዓት ጠብቃ 4፡30 ስትደርስ “እስክንድር እዚህ የለም” ሲሏንመባሏንና ድንጋጤ ላይ መውደቋን ፣ በኋላ ከ170 በላይ የተለያዩ እስረኞች ወዳሉበት ዞን ሁለት መዛወሩን ሠምታ በመሄድ ያለ ልዩ ጠባቂ በነፃነት ለረጅም ሠዓት አዋርታው መመለሷንና፣ ይህን የሠሙ አንዳንድ ወዳጅ ዘመዶች መጠየቅ መጀመራቸውን በደስታ ገልፃለች፡፡

“ከዚህ በፊት እኔ፣ እናቴ፣ አክስቱና የአክስቱ ባል ነበርን የምንጠይቀው፣ ልንጠይቀው ስንሄድም አምስተኛው ሰው ፖሊስ ነው፤ አብሮን ተቀምጦ የምናወራውን ይሠማል፣ለብቻው የተከለለ ቦታም ነበር ስናስጠራው የሚመጣው” ያለችው የእስክንድር ባለቤት፣ “እንዴት እንደሆነ ባላወቅነው ሁኔታ አሁን እንደማንኛውም እስረኛ በነፃነት እየጠየቅነው ነው፡፡ በዚህም ደስተኛ ሆኛለሁ” ስትል ተናግራለች፡፡ ምንም እንኳ በአሁኑ ሠዓት በነፃነት መጠየቅ ብንጀምርም ጉዳዩ ወደፊት ቀጣይነት ይኑረው አይኑረው እርግጠኛ ሆኖ መናገር እንደማይቻል ጋዜጠኛ ሠርካለም ለአዲስ አድማስ ጨምራ ገልፃለች፡