Administrator

Administrator

Sunday, 10 September 2017 00:00

በዳይመንድ ሊግ

 • ዘንድሮ የኬንያ አትሌቶች ድርሻ ከ740.5 ሺ ዶላር በላይ ሲሆን የኢትዮጵያ አትሌቶች ድርሻ እስከ 198ሺ ዶላር ነው፡፡
                      • በ2017 ኬንያ 4 የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖች ኢትዮጵያ ምንም
                      • ባለፉት 8 የውድድር ዘመናት ኬንያ 37 ኢትዮጵያ 12 የዳይመንድ ሊግ ድሎች
                   
       ዳይመንድ ሊግ በዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች የሚዘጋጅ ሲሆን ከፍተኛ የገንዘብ ሽልማት ከሚያቀርቡ የማራቶን ውድድሮች ቀጥሎ ለአትሌቶች ከፍተኛ የገቢ ምንጭ የሆነና በከፍተኛ እድገት ላይ የሚገኝ ዓመታዊ ውድድር ነው፡፡ ዳይመንድ ሊግ ዘንድሮ ለ8ኛ ጊዜ ሲካሄድ በአዲስ መዋቅር  ሲሆን በ32 የውድድር መደቦች በሁለቱም ፆታዎች 1200 አትሌቶች ተሳትፈውበታል፡፡ ትራክ ስታት www.track-stats.com የተባለ ድረገፅ በሰራው ስሌት  በ8ኛው የዳይመንድ ሊግ ላይ  ከቀረበው 8 ሚሊዮን ዶላር የገንዘብ ሽልማት 607 አትሌቶች ከ1ሺ ዶላር ጀምሮ እስከ 134ሺ ዶላር ተሸልመዋል፡፡ ዘንድሮ በዳይመንድ ሊጉ ከፍተኛውን የገንዘብ ሽልማት በመውሰድ አንደኛ ደረጃ የተሰጣት 134ሺ ዶላር ማሸነፍ የቻለችው  ኤለና ቶምሰን ከጃማይካ ስትሆን፤ ሽዋኔ ሚለር ከባህማስ በ127ሺ ዶላር፤ ማርያ ላስቲስኤኔ ከራሽያ በ100ሺ ዶላር እንዲሁም ሙታዝ ኡሳ ከቦትስዋና በ100ሺ ዶላር እስከ አምስተኛ ደረጃ አከታትለው ወስደዋል፡፡ ከኬንያ ኤለን ኦቡሪ፤ ከደቡብ አፍሪካ ካስተር ሴማንያ፤ ከቦትስዋና ኒጄል አሞስ፤ ከአሜሪካ ሽዋን ሄንድሪክስ፤ ከግሪክ ካተሪን ሴፈንዲ በነፍስ ወከፍ 90ሺ ዶላር እንዲሁም ከክሮሽያ ሳንድራ ፔርኮቪች 86ሺ ዶላር ከሽልማት ገንዘቡ በመቋደስ እስከ 10ኛ ደረጃ ለማግኘት ችለዋል፡፡
በሌላ በኩል በ8ኛው ዳይመንድ ሊግ በቅርብ ተቀናቃኞቹ የኬንያ እና ኢትዮጵያ አትሌቶች መካከል ከሽልማት ገንዘቡ በተገኘ ድርሻ ከፍተኛ ልዩነት ተስተውሏል፡፡ የትራክ ስታት የሽልማት ገንዘብ ስሌት እንዳመለከተው ኬንያውያን ከ1 እስከ 10፤ ከዚያም እስከ 20 እንዲሁም እስከ ሃምሳኛ እና እስከ መጨረሻው ደረጃ በርካታ አትሌቶችን በማሳተፍ ከገንዘብ ሽልማቱ በ3 እጥፍ ከኢትዮጵያ የሚልቅ  ድርሻ በማግኘት ተሳክቶላቸዋል፡፡ በአጠቃላይ በዳይመንድ ሊጉ ላይ ዘንድሮ ኬንያ 49 አትሌቶችን በማሳተፍ ከ740.5ሺ ዶላር በላይ ስትሰበስብ አራት የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖች አግኝታለች፡፡ ከ7 የውድድር ዘመናት በኋላ የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮን ሳታስመዘግብ የቀረችው ኢትዮጵያ 19 አትሌቶችን በማሳተፍ ከሽልማት ገንዘቡ ያስመዘገበችው ድርሻ 148ሺ ዶላር ብቻ ሆኗል፡፡  የኢትዮጵያ አትሌቶች ከዳይመንድ ሊጉ የሽልማት ገንዘብ የሚኖራቸው ድርሻ የቀነሰው በዓለም ሻምፒዮና ተሳትፎ ሳቢያ አትሌቶች ከውድድር ተሳትፎ በመታገዳቸው፤ በምርጥ አሰልጣኞች እና በቂ የልምምድ ጊዜ ባለመስራታቸው፤ በውስን የውድድር መደቦች በሁለቱም ፆታዎች በመሳተፋቸው እና በተቃናቃኝ አትሌቶች የውድድር ታክቲክ እና ቴክኒክ በመበለጣቸው ነው፡፡ የኬንያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን የአትሌቶችን የዳይመንድ ሊግ ተሳትፎ ባለማገዱ እንዲሁም ከኢትዮጵያ በተሻለ የውድድር መደቦች በብዛት መሳተፋቸው ከሽልማት ገንዘብ ያገኙትን ድርሻ የላቀ አድርጎታል፡፡
በትራክ ስታት www.track-stats.com ስሌት መሰረት ከኢትዮጵያ አትሌቶች ግንባር ቀደም ሆኖ የሚጠቀሰው በ5ሺ ሜትር የዓለም ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው ሙክታር ኢድሪስ በ42ሺ ዶላር የሽልማት ድርሻው ከዓለም 49ኛ ደረጃ በማግኘቱ ነው፡፡  ዮሚፍ ቀጀልቻ በ24ሺ ዶላር 93ኛ፤ ዳዊት ስዩም እና በሱ ሳዶ በ16ሺ ዶላር 136ኛ እና 137ኛ፤ ጉድፍ ፀጋይ በ15.5 ሺ ዶላር 142ኛ ላይ ናቸው፡፡ ሌሎች የኢትዮጵያ አትሌቶች ከ150ኛ በታች  እስከ 350ኛ ደረጃ ተዘበራርቀው ሊቀመጡ በቅተዋል፡፡ አማን ወጤ 13፤ ሶፍያ አሰፋ 13ሺ፤ ሃብታም አለሙ 12፤ ሰለሞን ባረጋ 12፤ ለተሰንበት ግደይ 11፤ የኔው አላምረው 8፤ በሱ ሳዶ 5.5፤ ገንዘቤ ዲባባ፤ 4.5፤ እቴነሽ ዲሮ 4.5፤ ጫላ ባዬ 3ሺ፤ ብርሃኑ ለገሰ 2.5፤ ስንታየሁ 1.5፤ ዳዊት ወልዱ 1.5 እንዲሁም ሰለሞን በልሁ 1ሺ ዶላር ከ8ኛው የዳይመንድ ሊግ የገንዘብ ሽልማት አግኝተዋል፡፡
ዳይመንድ ሊግ ከ1998 እኤአ እስከ 2010 እኤአ ለ11 የውድድር ዘመናት ይካሄድ የነበረውን የአይኤኤፍ ጎልደን ሊግ በተሻለ ደረጃ የተካ ነው፡፡ ለ12 የውድድር ዘመናት የተካሄደው ጎልደን ሊግ በ6 ከተሞች በሚደረጉ ውድድሮች የሚያሸንፉ አትሌቶችን 1 ሚሊዮን ዶላር ወይንም የወርቅ ጡቦች በማካፈል የሚሸለምበት ነበር። በጎልደን ሊግ በ1998 እኤአ ላይ ኃይሌ ገብረስላሴ 333,333 ዶላር፤ በ2006 እኤአ ላይ ቀነኒሳ በቀለ እና ጥሩነሽ ዲባባ በነፍስ ወከፍ 83,333 ዶላር እንዲሁም ቀነኒሳ በቀለ በ2009 እኤአ ላይ 333,333 ዶላር ተሸላሚዎች ነበሩ፡፡
የጎልደን ሊግ ውድድርን የተካው ዳይመንድ ሊግ  ባለፉት 8 የውድድር ዘመናት ከፍተኛ ለውጥ እና ድምቀት በማሳየት ከአይኤኤኤፍ ውድድሮች ስኬታማው ሆኖ እየተጠቀሰ ይገኛል፡፡ ዳይመንድ ሊጉ በየሚካሄድባቸው ከተማዎች ከፍተኛ የስታድዬም ተመልካች አለው። በተለይ በአሜሪካ ዩጂን፤ በስዊዘርላንድ ዙሪክ፤ በሞናኮ  እንዲሁም በእንግሊዝ በርሚንግሃም ከተሞች የሚካሄዱት የዳይመንድ ሊግ ውድድሮች ስታድዬም በሚገባ ተመልካች እየገዘፉ ናቸው፡፡ በቴሌቭዥ ስርጭት ከፍተኛውን ሽፋን በማግኘት ከአትሌቲክስ ውድድሮች ዋና ተጠቃሽ የሆነው ዳይመንድ ሊግ  የዓለም መገናኛ ብዙሃንን ትኩረት በመሳብ ውጤታማም ነው፡፡ በዳይመንድ ሊጉ የየአገራቱ ምርጥ አትሌቶች፤ የዓለምና የኦሎምፒክ ሻምፒዮኖችን መሳተፋቸው ምርጥ ፉክክር የሚስተዋልበት መድረክ አድርጎታል፡፡ ካለፉት ሁለት የውድድር ዘመናት ወዲህ በ4 አህጉራት ኤስያ፤ አውሮፓ፤ መካከለኛው ምስራቅ፤ አሜሪካን እንዲሁም አፍሪካን በማካለል የሚካሄደው ዳይመንድ ሊጉ በ4 ወራት  በ13 የተለያዩ አገራትና 15 ከተሞች ሲስተናገድ  በከፍተኛ የውድድር ደረጃው ሪከርዶች እና የውድድር ዘመኑ ፈጣን ሰዓቶች የሚመዘገቡበት ታላቅ መድረክ እየሆነ መጥቷል፡፡
በሌላ በኩል ባለፉት ስምንት የውድድር ዘመናት በዳይመንድ ሊጉ ተግባራዊ የሆኑ አዳዲስ የአሰራር መዋቅሮች በሻምፒዮናው የእድገት ደረጃ ፈጣን ለውጥ እንዲመዘገብ ምክንያት ሆነዋል፡፡ በዳይመንድ ሊጉ የአሰራር መዋቅር ለውጦች የተደረጉት ለ3 ጊዜያት ነው፡፡ በመጀመርያዎቹ 6 የውድድር ዘመናት በ12 ከተሞች ውድድሮች እየተካሄዱ ከ1 እሰከ 3 ለሚወጡ አትሌቶች ብቻ   አሸናፊዎችን ለመለየት  ነጥብ በመስጠት በውድድር ዘመኑ መጨረሻ ከፍተኛውን ነጥብ ለሚያስመዘግቡት ሻምፒዮንነቱ ይፀድቅ ነበር።  በ2016 እኤአ በ7ኛው የውድድር ዘመን በተመሳሳይ ሻምፒዮኖችን በከፍተኛ ነጥብ የመለያ መንገድ ከ1 እሰከ 6ኛ ደረጃ ለሚያገኙ አትሌቶች ነጥብ በመስጠት ተሰርቶበታል፡፡ በ2017 እኤአ ላይ ግን የአሰራር መዋቅሩ በጣም ልዩ ለውጥ ተደርጎበታል፡፡ በመጀመርያ 12 የማጣርያ ውድድሮች የተካሄዱ ሲሆን ከ1 እስከ 8ኛ ደረጃ ለሚያገኙት ነጥብ  ተሰጥቶ የዳይመንድ ሊጉ አሸናፊዎች የሚለዩት በሁለት ከተሞች በሚከናወኑ የፍፃሜ ውድድሮች ሆኗል፡፡ 12ቱን የዳይመንድ ሊግ የማጣርያ ውድድሮች ዘንድሮ ያስተናግዱት የዶሃ ከተማ በኳታር፤ የሻንጋይ ከተማ በቻይና፤ የዩጂን ከተማ  በአሜሪካ፤ የሮም ከተማ  በጣሊያን፤ የኦስሎ ከተማ በኖርዌይ፤ የቶክሆልም ከተማ በስዊድን የፓሪስ ከተማ በፈረንሳይ፤ የዙሪክ ከተማ በስዊዘርላንድ፤ የበርሚንግሃም ከተማ በእንግሊዝ፤ የራባት ከተማ በሞሮኮ ፤ የሞናኮ ከተማ በሞናኮ እንዲሁም የለንደን ከተማ በእንግሊዝ  ናቸው። ከእነዚህ የ12 ከተሞች የማጣርያ ውድድሮች በኋላ በከፍተኛ ነጥብ በየውድድር መደቡ የጨረሱ አትሌቶች የዳይመንድ ሊጉ ሻምፒዮኖች በሚለዩት በስዊዘርላንድ ዙሪክ እና በቤልጅዬም ብራሰልስ የሚካሄዱ ውድድሮች ተለይተዋል፡፡
ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር ዘንድሮ በዳይመንድ ሊግ ለማጣርያው እና ለፍፃሜ ውድድሮች ያቀረባቸው የተለያዩ የሽልማት ገንዘቦች ናቸው፡፡ በዳይመንድ ሊጉ በ12 ከተሞች በሚደረጉ የማጣርያ ውድድሮች  ከ1 እሰከ 8ኛ ደረጃ ላገኙ አትሌቶች በሚበረከተው የሽልማት ገንዘብ መሰረት ለ1ኛ 10ሺ ዶላር፤ ለ2ኛ 6ሺ ዶላር፤ ለ3ኛ 4ሺ ዶላር፤ ለ4ኛ 3ሺ ዶላር፤ ለአምስተኛ 2500 ዶላር፤ ለስድስተኛ 2ሺ ዶላር ፤ ለ7ኛ 1500 ዶላር እንዲሁም ለ8ኛ 1000 ዶላር የሚታሰብ ይሆናል፡፡ በሁለቱ የፍፃሜ ውድድሮች ደግሞ የሽልማት ገንዘቡ ለውጥ የተደረገለት ሲሆን ከ1 እሰከ 8ኛ ደረጃ ላገኙ አትሌቶች በሚበረከተው የሽልማት ገንዘብ መሰረት ለ1ኛ 50ሺ ዶላር፤ ለ2ኛ 20ሺ ዶላር፤ ለ3ኛ 10ሺ ዶላር፤ ለ4ኛ 6ሺ ዶላር፤ ለአምስተኛ 5ሺ ዶላር፤ ለስድስተኛ 4ሺ ዶላር ፤ ለ7ኛ 3ሺ ዶላር እንዲሁም ለ8ኛ 2ሺ ዶላር እንዲከፈል ተደርጓል። በፍፃሜዎቹ የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖች ለመሆን የሚበቁት 32 አትሌቶች በነፍስወከፍ ከሚያገኙት የ50ሺ ዶላር ሽልማት በተጨማሪ በአልማዝ ማእድን የተሰራ ልዩ የዳይመንድ ሊግ ዋንጫ  ይወስዳሉ። 4.9 ኪግ የሚመዝነው የዳይመንድ ሊግ ዋንጫው ተቀማጭነቱ በስዊዘርላንድ ዙሪክ የሆነው፤ ለ250 ዓመታት በዋንጫዎች፤ የክብር ሽልማቶች፤ ሰዓቶች እና ልዩ ልዩ ጌጣጌጦች ስራ የሚታወቀው ክሮኒዮ ሚቲዬሬ የሚሰራ እንደሆነ ታውቋል፡፡ የዳመንድ ሊግ ዋንጫው በ3 የአትሌቲክስ  ገፅታዎች በስታድዬም ፤ በተመልካች ድባብ እና በአትሌት ብቃት መገለጫነት የተቀረፀ ነው፡፡
12 የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖችና 6 የዳይመንድ ሊግ ክብረወሰኖች
የኢትዮጵያ 12 የዳይመንድ ሊግ ድሎች  በ10 አትሌቶች የተመዘገቡ ናቸው፡፡ በ800 ሜትር መሃመድ አማን በ2012 እና በ2013 እኤአ አሸንፏል። በ3ሺ እና 5ሺ ሜትር ወንዶች  በ2010 እና 2011 እኤአ ኢማና መርጋ እንዲሁም በ2013 እኤአ የኔው አላምረው ናቸው። አበባ አረጋዊ ዜግነቷን ሳትለውጥ በፊት በ1500 ሜትር በ2012 እኤአ ላይ አሸናፊ ነበረች፡፡ በሴቶች 5ሺ ሜትር መሰረት ደፋር በ2013 እኤአ ያሸነፈች ሲሆን በ3ሺ ሜትር መሰናክል ደግሞ 2014 እኤአ ላይ ህይወት አያሌው ድል አድርጋለች፡፡ በ2015 ደግሞ ዳይመንድ ሊጉን በ5ሺ ሜትር ለማሸነፍ የበቃችው ገንዘቤ ዲባባ ስትሆን በ2016 እኤአ ደግሞ በ3ሺ እና 5ሺ ሜትር መደብ አልማዝ አያና እና ሃጎስ ገብረህይወት አሸንፈዋል፡፡ በ2017 ኢትዮጵያ የዳመንድ ሊግ ሻምፒዮን አላስመዘገበችም፡፡
በ3ሺ ሜትር የኔው አላምረው በኳታር ዶሃ በ2011 እኤአ ላይ በ7፡27.26
በ5ሺ ሜትር ደጀን ገብረመስቀል በፈረንሳይ ፓሪስ በ2012 እኤአ 12፡46.81
በ10ሺ ሜትር ቀነኒሳ በቀለ በቤልጅዬም ብራሰልስ በ2011 እኤአ 26፡43.16
በሴቶች 1500 ገንዘቤ ዲባባ በፈረንሳይ ሞናኮ በ2015 እኤአ ላይ 3፡50.07 የዓለም ሪከርድ ነው፡፡
በሴቶች 5ሺ ሜትር አልማዝ አያና በሮም ጣሊያን በ2016 እኤአ 14፡14.32
በ10ሺ ሜትር ጥሩነሽ ዲባባ በአሜሪካ ዩጂን 2012 እኤአ ላይ በ30፡24.39
በ8  የዳይመንድ ሊግ የውድድር ዘመናት በሻምፒዮኖችና በክብረወሰኖች የአገራት  ደረጃ
ባለፉት 8 የዳይመንድ ሊግ የውድድር ዘመናት 59 የዳይመንድ ሊግ አሸናፊዎችና 9 የዳይመንድ ሊግ ክብረወሰኖች  ያስመዘገበችው አሜሪካ አንደኛ ደረጃ ይዛለች፡፡ ኬንያ በ37 የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖችና በ8 የዳይመንድ ሊግ ክብረወሰኖች ሁለተኛ ደረጃ ላይ ስትሆን፤ ጃማይካ በ18 የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖች እና 7 የዳይመንድ ሊግ ክብረወሰኖች ሶስተኛ ፤ ኢትዮጵያ በ2012 እኤአ ላይ አበባ አረጋዊ በ1500 ሜትር ዜግነቷን ወደ ስዊድን ሳትቀይር ያስመዘገበችውን ድል ጨምሮ በ12 የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖችና ስድስት የዳይመንድ ሊግ ክብረወሰኖች አራተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች፡፡

የተቸገሩትን የመርዳትና የመለገስ ልማድ በአለማቀፍ ደረጃ እየቀነሰ ቢመጣም አፍሪካን የመሳሰሉ ድሃ አህጉራት ግን ቸርነታቸውና ደግነታቸው እየጨመረ መምጣቱን ባለፈው ማክሰኞ ይፋ የተደረገ አንድ አለማቀፍ ጥናት አመልክቷል፡፡
በ139 የአለማችን አገራት ላይ የተሰራን ጥናት መሰረት ያደረገው አመታዊው አለማቀፍ የበጎ አድራጎት ልገሳ ሁኔታ አመላካች ሪፖርት እንዳለው፣ ባለፈው የፈረንጆች አመት የገንዘብ ልገሳ የማድረግ ወይም የማያውቁትን ሰው የመርዳት ልማድ በአለማቀፍ ደረጃ በ2 በመቶ የቀነሰ ሲሆን፣ የበጎ ፈቃደኝነት ተግባር ደግሞ በ1 በመቶ ቀንሷል፡፡
አሜሪካን ጨምሮ የአለማችን ቀዳሚዎቹ 10 ሃብታም አገራት፣ከአምናው ጋር ሲነጻጸር ዘንድሮ በለጋስነት ማሽቆልቆል አሳይተዋል ያለው ሪፖርቱ፤ከአለማችን 20ዎቹ የበለጸጉ አገራት መካከል ከቀዳሚዎቹ 20 ለጋስ አገራት ተርታ መሰለፍ የቻሉት ስድስት ብቻ ናቸው ብሏል፡፡
ላለፉት ሶስት ተከታታይ አመታት የአለማችን እጅግ ቸር እና ለጋስ ህዝቦች መኖሪያ ናት ተብላ በሪፖርቱ በቀዳሚነት የተቀመጠቺው ማይናማር፣ ዘንድሮም የአንደኛነትን ደረጃ ይዛለች ያለው ዘገባው፤ ኢንዶኒዢያ የሁለተኛነት ደረጃን መያዟን አመልክቷል፡፡ በአመቱ በቸርነትና በልግስና ከፍተኛ መሻሻል ያሳየቺው ኬንያ መሆኗን በመጠቆም፣ አምና 12ኛ ደረጃ ላይ የነበረቺው ኬንያ፣ ዘንድሮ ሶስተኛ ደረጃን ላይ መቀመጧንም ገልጧል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ፣ በቸርነት ከአለማችን አገራት የመጨረሻውን ደረጃ የያዘቺው በእርስ በእርስ ጦርነት የፈራረሰቺው የመን መሆኗን አመታዊው ሪፖርት አስታውቋል፡፡
ቻሪቲስ ኤይድ ፋውንዴሽን በተባለው አለማቀፍ ተቋም የተሰራው ጥናቱ፤ የ139 የአለማችን አገራት ዜጎች የሆኑ ከ146 ሺህ በላይ ሰዎችን ቃለ መጠይቅ በማድረግ በተሰበሰበው መረጃ ላይ በመመስረት፣ የአገራቱን ዜጎች የበጎ ምግባር የገንዘብ ልገሳ ተሞክሮ፣ የበጎ ፈቃደኝነት ተሳትፎና የማያውቁትን ሰው የመርዳት ተነሳሽነት በመገምገም ደረጃ እንደሚሰጥም ተነግሯል፡፡

  100 የአመቱ ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝር ውስጥ አፍሪካዊ የለበትም


       የአለማችንን ዩኒቨርሲቲዎች የጥራት ደረጃ በየአመቱ ይፋ የሚያደርገው አለማቀፉ የዩኒቨርሲቲዎች ሊግ ሰሞኑንም የአመቱን የአለማችን ምርጥ 100 ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝር ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ የእንግሊዙ ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ዘንድሮም እንደ አምናው በአንደኛነት ደረጃ ላይ መቀመጡን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
ለ13ኛ ጊዜ ይፋ በተደረገው የአለማችን የምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝር ውስጥ የእንግሊዙ ካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ የሁለተኛነት ደረጃን ሲይዝ፣ ባለፈው አመት የአለማችን ሁለተኛው ምርጥ የነበረው የአሜሪካው ካሊፎርኒያ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ ዘንድሮ ከአሜሪካው ስታንፎርድ ዩኒቨርሲቲ ጋር የሶስተኛነቱን ደረጃ ተጋርቷል፡፡
8ኛ ደረጃን ከያዘው ኢምፔሪያል ኮሌጅ ኦፍ ለንደን እና 10ኛ ደረጃን ከያዘው የዙሪክ የፌዴራል የቴክኖሎጂ ኢንስቲቲዩት በስተቀር፣ ከ3ኛ እስከ 15ኛ ያለውን ደረጃ የያዙት ሁሉም የአሜሪካ ዩኒቨርሲቲዎች መሆናቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ እነሱም ማሳቹሴትስ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ፣ ሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ፣ ፕሪንሴተን ዩኒቨርሲቲ፣ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ቺካጎ፣ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ፔንሲልቫኒያ፣ ኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ እና ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ካሊፎርኒያ ናቸው ብሏል፡፡  
ከ30ዎቹ የአለማችን ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች መካከል ሰባቱ የአውሮፓ ዩኒቨርሲቲዎች ሲሆኑ ሶስቱ ደግሞ የእስያ አገራት ዩኒቨርሲቲዎች ናቸው ያለው ዘገባው፤ እስከ 100 ባለው የአመቱ ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝር ውስጥ አንድም አፍሪካዊ ዩኒቨርሲቲ አለመካተቱን አክሎ ገልጧል፡፡

  የሩዋንዳ መንግስት በርዕሰ መዲናዋ ኪጋሊ እየተባባሰ የመጣውን የትራፊክ መጨናነቅ ለማስወገድ በማሰብ፣የግለሰቦች የቤት መኪኖች በከተማዋ ጎዳናዎች ላይ እንዳይንቀሳቀሱ የሚከለክል ህግ ተግባራዊ ለማድረግ ማቀዱ ተዘግቧል፡፡
የአገሪቱ መንግስት ከቀጣዩ አመት አጋማሽ ጀምሮ ተግባራዊ ሊያደርገው ያሰበው ይህ ህግ፣ በመዲናዋ ኪጋሊ የህዝብ ትራንስፖርት ከሚሰጡና ከተፈቀደላቸው የተቋማት ተሸከርካሪዎች በስተቀር የግል መኪኖች መንቀሳቀስ አይችሉም ሲል ፐልስላይቭ ከትናንት በስቲያ ዘግቧል፡፡
በከተማዋ ለሚታየው ከፍተኛ የትራፊክ መጨናነቅ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ የሚገኙት የግል መኪኖች በመሆናቸው የአገሪቱ መንግስት ህጉን ለማውጣት መገደዱንና የህዝብ ትራንስፖርት የሚሰጡ አውቶብሱችን በብዛት ወደ ስራ ለማስገባት ማሰቡን ዘገባው አመልክቷል፡፡
ህጉ ጸድቆ ተግባራዊ  ከሆነ፣ የቤት መኪና ያላቸው የኪጋሊ ነዋሪዎች፣ ከ2018 አጋማሽ አንስቶ ብስክሌት ወይም የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ አውቶብሶችን ለመጠቀም ወይም በእግራቸው ለመጓዝ ይገደዳሉ ተብሏል፡፡

የብራዚል የቀድሞ ፕሬዚዳንቶች ሉዊስ ሉላ ዳሲልቫ እና ዲልማ ሩሴፍ፣ ግዙፍ የወንጀለኞች ቡድን በማቋቋም ለአመታት ታላላቅ የወንጀል ተግባራትን ሲያከናውኑ ነበር በሚል ባለፈው ማክሰኞ በአገሪቱ ጠቅላይ ፍርድ ቤት ክስ ተመስርቶባቸዋል፡፡
የአገሪቱ አቃቤ ህግ ሁለቱን የአገሪቱ የቀድሞ ፕሬዚዳንቶች እና የፓርቲያቸው አባላት የሆኑ ስድስት ግብረ አበሮቻቸው፣ በስውር ባቋቋሙት የወንጀለኞች ቡድን፤ ሙስናንና የህገወጥ የገንዘብ ዝውውርን የመሳሰሉ የተለያዩ የወንጀል ተግባራትን ሲፈጽሙ እንደነበር በመጥቀስ ክስ መመስረቱን ሮይተርስ ዘግቧል።
በስልጣን ዘመናቸው በሙስና መልክ ከ480 ሚሊዮን ዶላር በላይ ገንዘብ አካብተዋል በሚል ክስ የተመሰረተባቸው የቀድሞው የአገሪቱ ፕሬዚዳንት የሉላ ዳ ሲልቫ እና የአልጋ ወራሻቸው የዲልማ ሩሴፍ ጠበቆች ክሱን መሰረተቢስ ውንጀላ በማለት የተቃወሙት ሲሆን ደንበኞቻቸው ከተባለው የወንጀል ድርጊት ነጻ መሆናቸውን በመጥቀስ ተቃውሟቸውን አሰምተዋል፡፡
የሰራተኞች ፓርቲ በበኩሉ፤ ክሱ የተመሰረተው ያለምንም ተጨባጭ ማስረጃ ነው፣ ህዝቡ ሌሎች የወንጀል ምርመራ ጉዳዮችን እንዲረሳና ትኩረቱን እንዲቀይር ለማድረግ ታስቦ ሆን ተብሎ የተመሰረተ ክስ ነው ሲል አጣጥሎታል፡፡
አሁንም ድረስ ብዙ ደጋፊዎች ያሏቸውና በመጪው የአገሪቱ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ለመወዳደር ያቀዱት የቀድሞው የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሉላ ዳ ሲልቫ፤ ከዚህ ቀደምም የሙስና ክስ እንደተመሰረተባቸው ያስታወሰው ዘገባው፣ የፍርድ ቤቱ ውሳኔ ለምርጫ እንዳይወዳደሩ ሊያግዳቸው ይችላል ተብሎ እንደሚሰጋም ገልጧል፡፡
በ2002 ወደ ስልጣን የመጡት ሉላ ዳ ሲልቫ፣ለሁለት የስልጣን ዘመን ብራዚልን ካስተዳደሩ በኋላ መንበረ መንግስቱን ለሩሴፍ ማስረከባቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ሩሴፍ በበኩላቸው የአገሪቱን በጀት በህገ ወጥ መንገድ አስተዳድረዋል በሚል በ2016 ከስልጣን መነሳታቸውን አክሎ ገልጧል፡፡

 የአፍሪካ መንግስታት፣ ሽብርተኝነትንና ጽንፈኝነትን ለመዋጋት በማሰብ የሚፈጽሟቸው ድርጊቶችና የሚወስዷቸው እርምጃዎች፣ በተቃራኒው ዜጎችን ወደ ጽንፈኝነት ገፍተው እያስገቡ እንደሆነ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ከትናንት በስቲያ ይፋ ባደረገውና ሶስት አመታትን በፈጀው የጥናት ሪፖርት አስታውቋል፡፡
ተመድ ይፋ ያደረገው የጥናት ውጤት እንደሚለው፣በአፍሪካ ውስጥ የሚገኙ በመቶዎች የሚቆጠሩ የጽንፈኛ ቡድኖች አባላት፣ የጽንፈኛ ቡድኖችን አስተሳሰብ በመደገፍ አባል ለመሆን የወሰኑት፣ የየአገሮቻቸው መንግስታት በሚወስዷቸው የጸረ ሽብርተኝነትና ጽንፈኝነት እርምጃዎች ተገፋፍተው እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
የአፍሪካ መንግስታት ቦኮ ሃራምንና አልሻባብን የመሳሰሉ ጽንፈኛና አሸባሪ ቡድኖችን ለመደምሰስ የሚያደርጉት ትግል፣ የአገራቱን ዜጎችና ቤተሰቦቻቸውን ተጎጂ የሚያደርጉባቸው አጋጣሚዎች በርካታ እንደሆኑ የዘገበው ዘ ጋርዲያን፤ ይህም ዜጎችን ወደ ጽንፈኝነት በመግፋት ያልተፈለገ፣ አሉታዊ ተጽዕኖ እየፈጠረ እንደሚገኝ አመልክቷል፡፡
የጽንፈኛ ቡድኖች አባላት ከነበሩና በጥናቱ ከተካተቱ 500 በላይ አፍሪካውያን መካከል 71 በመቶ የሚሆኑት፣ የአገራቸው መንግስት ጽንፈኝነትን ለመዋጋት በወሰዳቸው እርምጃዎች፣ ቤተሰቦቻቸው ወይም ጓደኞቻቸው መገደላቸው፣ መታሰራቸው አልያም የሌሎች በደሎች ሰለባ መሆናቸው፣ የቡድኖቹ አባል ለመሆን ዋነኛ ምክንያት መሆኑን መወሰናቸውን ተናግረዋል፡፡
በአፍሪካ ባለፉት ስድስት አመታት ብቻ ጽንፈኛ ቡድኖች በፈጸሟቸው የሽብር ጥቃቶችና የጥፋት እርምጃዎች ከ33 ሺህ በላይ የአህጉሪቱ ዜጎች ለህልፈተ ህይወት መዳረጋቸውን ያስታወሰው ዘገባው፣ ጽንፈኝነት በሚሊዮኖች የሚቆጠሩ አፍሪካውያንን ለመፈናቀልና ለሰብዓዊ ቀውስ መዳረጉንም አስረድቷል፡፡
አፍሪካውያንን ወደ ጽንፈኝነት እንዲገቡ ይገፋፋሉ ተብለው በጥናቱ ከተለዩት ሌሎች በርካታ ምክንያቶች መካከልም፣ ፍትሃዊ ያልሆነ የሃብት ክፍፍል እንዲሁም የትምህርትና የስራ ዕድል ዕጦት እንደሚገኙበትም ዘ ጋርዲያን በዘገባው ጠቁሟል፡፡

   በዘንድሮ የአዲስ ዓመት ዋዜማ፣ በመዲናዋ የትኞቹ ሆቴሎች፣ ቴአትር ቤቶች፣ የምሽት ክለቦች … የሙዚቃ ድግሶችና  የአውዳመት የመዝናኛ ፕሮግራሞች ተዘጋጅተዋል? ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ እንዲህ ቃኝታቸዋለች፡፡

                 
                   “እንቁጣጣሽ ክላሲክ ኮንሰርት” - በካፒታል ሆቴል

     ባለአምስት ኮከቡ ካፒታል ሆቴል፤ በአዲሱ አመት ዋዜማ ከምሽቱ 12፡00 ጅምሮ “እንቁጣጣሽ ክላሲክ ኮንሰርት” የሚል ስያሜ የተሰጠው የሙዚቃ ድግስ አሰናድቷል፡፡ በዚህ ድግስ ተወዳጆቹ ድምፃውያን ሳሚ ዳን፣ ሚካኤል ለማ ደምሰው፣ ፀደንያ ገ/ማርቆስ፣ የባላገሩ አይዶል አሸናፊ ዳዊት ፅጌ፣ አስገኘሁ አሸኮ (አስጌ ዴንዳሾ) ታዳሚውን በዘፈኖቻቸው የሚያዝናኑ ሲሆን ዲጄ ዊሽና ዲጄ ጆ ዋዜማውን በምርጥ ሙዚቃዎች ያደምቁታል ተብሏል፡፡
በሙዚቃ ድግሱ ላይ ለሚታደሙ ከእራት በፊት ለአንድ ሰው 699 ብር፣ እራትን ጨምሮ 1199 ብር፣ ለጥንዶች ያለ እራት 1199 ብር፣ እራትን ጨምሮ 1999 ብር የሚያስከፍል ሲሆን ዝግጅቱ እስከ ሌሊቱ 8፡00 ድረስ እንደሚዘልቅ የሆቴሉ ማርኬቲንግ ሃላፊ፣ ወ/ሪት ተወዳጅ አሰፋ ለአደስ አድማስ ገልፀዋል፡፡


-----------------

                    ልዩ የእራት ፓርቲ-በኢሊሊ ሆቴል

      ባለ አምስት ኮከቡ ኢሊሊ ኢንተርናሽናል ሆቴል ደግሞ በዘመን መለወጫ ዋዜማ ምሽት ልዩ የእራትና የሙዚቃ ድግስ አዘጋጅቷል፡፡ በዚህ ምሽት ኦሮምኛን ጨምሮ የተለያዩ የብሄር ብሄረሰቦች ሙዚቃና ባህላዊ ጭፈራ የሚቀርብ ሲሆን ስታንዳፕ ኮሚዲ፣ የባንድ ሙዚቃና ሌሎችም ዝግጅቶች ተሰናድተዋል ተብሏል፡፡ ጳጉሜ 5 ከምሽቱ 1፡00 ሰዓት ጀምሮ የሆቴሉ በሮች ለታዳሚያን ክፍት ሲሆኑ የመግቢያ ዋጋው እራትን ጨምሮ (ውስኪ መጠጦችን ለሚጠቀሙ) 1500 ብር፣ ከእራት ጋር የወይን መጠጦችን ለሚወስዱ 1 ሺህ ብር መሆኑ ተገልጿል፡፡ ሆቴሉ ከዚህ በተጨማሪም የሞሀ ለስላሳ መጠጦችን፣ ጊዮርጊስ ቢራና አኳ አዲስ ውሃን በነፃ ያቀርባል፡፡ አምራቾቹ ለበዓሉ ስፖንሰር ማድረገቸውን በመግለፅ፡፡  የመዝናኛ ድግሱ እስከ እኩለ ሌሊት እንደሚቀጥል የሆቴሉ የህዝብ ግንኙነትና ማህበራዊ ሚዲያ ሃላፊ አቶ ታሪኩ ዋሲሁን ለአዲስ አድማስ ገልፀዋል፡፡  

-----------------

                     ሀሴት አኩስፒክ ባንድ ከአዝማሪዎች ጋር በጎልደን ቱሊፕ ሆቴል

      ቦሌ ኤድናሞል ጀርባ የሚገኘው ባለ አራት ኮከቡ ጎልደን ቱሊፕ ሆቴል በበኩሉ፤ አኩስቲክ ባንድን ከአዝማሪዎች ጋር በማጣመር ዓለም አቀፍና ባህላዊ ሙዚቃን ለማቅረብ በምሽቱ ከሀሴት አኩስቲክ ባንድ ሚኪያስ ፍሬው፣ አይዳ ሰለሞንና ሌሎችም የሚሳተፉ ሲሆን ከአዝማሪዎች ቱፓክ በሚል ቅፅል ስሙ የሚታወቀው አዝማሪ ናርዶስ ከተሰኘች አዝማሪ ጋር ስራውን እንደሚያቀርብ ታውቋል፡፡
በዕለቱ በባህል ዘፈን ላይ ከፍተኛ አስተዋፅኦ ላበረከቱ ሁለት ዘፋኞች ሆቴሉ እውቅና እንደሚሰጥም ተነግሯል፡፡ በዚህ ምሽት ላይ ለመታደም ለአንድ ሰው እራትን ጨምሮ 699 ብር ሲሆን ለጥንዶች እራትን ጨምሮ 1299 ብር እንደሚያስከፍል የሆቴሉ ማርኬቲንግ ኃላፊ መርሀዊት ፀጋዬ ገልፀዋል፡፡

------------------

                         የጥበብ ድግስ - በብሔራዊ ቴአትር

      አንጋፋው ብሔራዊ ቴአትር አዲሱን አመት ምክንያት በማድረግ ለአንድ ወር የሚዘልቅ የጥበብ ድግስ እንደሚያቀርብ አስታውቋል፡፡ ከዛሬ ጀምሮ እስከ መስከረም 28 ቀን 2010 ዓ.ም በሚዘልቀው የጥበብ ድግስ፤ ከመደበኛው ሙዚቃና ልዩ ልዩ የኪነጥበባት ዝግጅት በተጨማሪ የአረጋዊያን የፋሽን ትርኢት፣ የአርበኞች ልዩ ዝግጅት፣ የአንጋፋው አርቲስት ጥላሁን ገሰሰ የመታሰቢያ ፕሮግራም የ”ሚስ ናሽናል ቴአትር” የቁንጅና ውድድርና ሌሎችም የመዝናኛ ፕሮግራሞች እንደሚቀርቡ ብሔራዊ ቴአትር አስታውቋል፡፡

 ጉዳዩ፡- ሚሊኒየም አዳራሽ ፈርሶ፣ ባለ 5 ኮከብ ኮንቬንሽን ሴንተር


      ክቡርነትዎ፤ ይህችን አነስተኛ ማስታወሻ የጻፍኩት፣ እንደ አንድ የአገር ተቆርቋሪ፣ የአዲስ አበባ ነዋሪነቴ ነው። እንደሚታወቀው፤ የኢትዮጵያ ሚሊኒየምን ለማክበር በታቀደ ጊዜ፣ በወቅቱ  ሰፊ አዳራሽ ባለመኖሩ፣ ሼክ መሐመድ ሁሴን አላሙዲን፣ አዳራሹን ለመስራት ቃል ገቡ፡፡ ይሄን ተከትሎም ለመሥሪያ የሚሆን ቦታ (ካልተሳሳትኩ፣ከሊዝ ነፃ የሆነ) ቦሌ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ መግቢያ ላይ ተረክበው፣ አዳራሹ በፍጥነት ተሰራ፡፡ ለታለመለት ተግባርም ዋለ፡፡ ሚሊኒየሙ፣ በዘፈንና በጭፈራ በደመቀ ሁኔታ ተከበረ፡፡ ሼክ መሐመድ ሁሴን አላሙዲን፣ ቦታውን ሲረከቡ ግን፣ ይህ በጥድፊያ የተሰራ ኮንቴነር አዳራሽ ፈርሶ፣ በምትኩ በአውሮፓ ስታንዳርድ፣ ዘመናዊ አዳራሽ እንደሚገነቡ ቃል መግባታቸውን  አስታውሳለሁ፡፡
 እነሆ፤ ኢትዮጵያ ሚሊኒየሙን ካከበረች ድፍን አስር አመታት አስቆጥራለች፡፡ የዛሬ 10 ዓመት ለጊዜው ተብሎ የተሰራው ሚሊኒየም አዳራሽ፣አሁንም ባለበት ነው። የተባለው ደረጃውን የጠበቀ አዳራሽ ይሄን ሁሉ ዓመት አልተገነባም፡፡ በእኔ እምነት ሼክ መሀመድ፣ይሄንን አዳራሽ አፍርሰው፣ ባለ አምስት ኮኮብ የሆነ ዓለም አቀፍ ደረጃው የጠበቀ አስደናቂ አዳራሽ ማስገንባት  አያቅታቸውም። ከተማችን አዲስ አበባ፣ የአፍሪካ ዋና ከተማ መሆኑዋ ይታወቃል፡፡ ዓለም አቀፍ ስብሰባዎች ለማካሄድ የምትመረጥ ከተማም እየሆነች መጥታለች። በዚህም የተነሳ ደረጃውን የጠበቀ ዘመናዊ  አዳራሽ እንደሚያስፈልጋት እሙን ነው፡፡
ክቡር ከንቲባ፡-
ሚሊኒየም አዳራሽ ላለፉት 10 ዓመታት በርካታ የሙዚቃ ድግሶችንና ኤግዚቢሽኖችን እያስከፈለ ሲያስተናግድ ቆይቷል፡፡ ከዚህ አንጻር አሁን ዓለም አቀፍ ደረጃውን የጠበቀ ዘመናዊ አዳራሽ ለመስራት የሚያስችል አቅም እንደገነባ መገመት ይቻላል፡፡ እንደ ነጋዴ፣ እንዲህ ከፍተኛ ገቢን የሚያስገባ አዳራሽ ማፍረስ ሊያጓጓ ይችላል፡፡ ነገር ግን ቃል በተገባው መሠረት፣ ስታንዳርዱን የጠበቀ አዳራሽ መገንባት እንዳለበት አምናለሁ፡፡ ይሄንን የማስፈጸም ሃላፊነት ደግሞ የከተማ መስተዳድሩ እንደሆነ ይታወቃል፡፡
ከውጪ ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡ ታላላቅ የሀገር መሪዎችና ጎብኚዎች፣ መጀመሪያ የሚመለከቱት ቦታ ላይ ተገትሮ የሚገኘው ቅርፅ የለሽ ኮንቴነርና ድንኳኖች ፈርሰው ፣አዲስ አበባ የአፍሪካን መዲናነቷን የሚመጥናት፣ ባለ አምስት ኮከብ Convention Center መገንባት አስፈላጊ ነው፡፡ በዚህ አጋጣሚ አገር ወዳድ ለሆኑትና ለኢትዮጵያ በርካታ ጥሩ ነገሮች ላበረከቱት ባለሀብት ሼክ መሀመድ፣ ያለኝን አክብሮት ለመግለፅ እወዳለሁ፡፡  ነገር ግን ለጊዜያዊ ችግር ታስቦ የተሰራው 10 ዓመታት ያስቆጠረው ሚሊኒየም አዳራሽ፣ በአዲስ ደረጃውን የጠበቀ አዳራሽ መተካት ያለበት ይመስለኛል። መስተዳደሩም ሃላፊነቱን በአፋጣኝ መወጣት ይገባዋል ብዬ አስባለሁ፡፡  
 በላይ ጨብሲ /ልማታዊ ሀብት/
This email address is being protected from spambots. You need JavaScript enabled to view it.    

   “ለሀገር አንድነት፣ ሠላም፣ እድገት … ተግተን መስራት አለብን” - ዶ/ር ነገሪ ሌንጮየመንግሥት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ፅ/ኃላፊ ሚኒስትር

        መንግስት ያለፈውን ዓመት እንዴት አሳለፈ? ሊጋፈጣቸው ያልቻላቸው ተግዳሮቶች ምን ነበሩ? ስህተቶቹንና ጉድለቶቹን ያውቃቸዋል? ካወቃቸው … ለማረም ምን አደረገ? የአዲሱ ዓመት ፈተናዎችና ተስፋዎች ምንድን ናቸው ይላል? የመንግስት ኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ፅ/ቤት ኃላፊ ሚኒስትር ዶ/ር ነገሪ ሌንጮ በ2010 ዋዜማ ላይ ለአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አለማየሁ አንበሴ የገለፁትን እነሆ፡-
ያለፈው አመት በመንግሥት በኩል ምን ተከናወነ? እንዴትስ አለፈ? ምንስ ተግዳሮት ገጠመው?
በአንድ ዓመት ውስጥ የተከናወኑ ስኬቶችና ተግዳሮቶችን በተወሰኑ ደቂቃዎች ውስጥ በዝርዝር ለመግለፅ ያስቸግራል፤ ነገር ግን በተወሰነ ደረጃ አንዳንድ ጉዳዮችን ማንሳት ይቻላል፡፡ በ2008 ዓ.ም በተለይ በኦሮሚያ፣ አማራና ደቡብ ክልል አንድ ዞን ላይ በተከሰቱ ችግሮች ምክንያት አዳዲስ አሰራሮችን የተከተልንበት ጊዜ ነው - 2009 ዓ.ም፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁም የነበረበት ዓመት ነው፡፡ በአጠቃላይ ግን ሀገርን ለማሳደግ፤ በኢኮኖሚ፣ በማህራዊ መስክ ሀገሪቱን ወደፊት ለመውሰድ የታቀዱት ስራዎች፣ በታቀደላቸው እየሄዱ እንደሆነ ነው፤ ግምገማው የሚያሳየው፡፡ ውጤትም ተገኝቶባቸዋል፡፡ ይሄ ውጤት የመጣው ግን እንዲሁ አልጋ በአልጋ በሆነ ሁኔታ አይደለም፡፡ ብዙ ተግዳሮቶች የታለፈበት ነው፡፡ ይሄም ሆኖ በዓመቱ መንግስት ትላልቅ አላማዎችን አስቀምጦ፣ ከህዝቡ ጋር በመተባበር አከናውኗል፡፡ በተለይ የሠላም ጉዳይ ለህዝባችን ወሳኝ ነው፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት በ2008 አካባቢ የነበሩ የሰላም ችግሮችን በመቅረፍ ረገድ ከህዝቡ ጋር በመተባበር፣ ትልቅ ውጤት የተገኘበት አመት ነበር ማለት ይቻላል፡፡ መንግስት የያዛቸው እቅዶችም ነበሩ፡፡ ዓመቱ ተግዳሮቶችን በመቋቋም፣ ውጤት የተገኘባቸው ጊዜ ነበር፡፡ ይህም የሆነው በህዝብ ትብብርና በመንግስት መሪነት ነው፡፡ በኢኮኖሚው ትልቅ ውጤት ተገኝቷል፡፡
በተለይ በ2009 መሪው ፓርቲ ራሱን የፈተሸበት ዓመት ነው፡፡ እንደገና ደግሞ በመንግስት ደረጃ ያሉትን ችግሮች በመዳሰስ፣ አስፈላጊ የሆኑ እርምጃዎችን ወስዷል፡፡ በሺዎች የሚቆጠሩ የፓርቲው አባላትና አመራር ላይ እርምጃ በመውሰድ፣ የአቅም ግንባታን በመስራት፣ የአመለካከት ቀረፃ ላይ በሚፈለገው ደረጃ የህዝብ አገልጋይነት መንፈስ እንዲሰፍን፣ መሪው ፓርቲ ትልቅ ስራ ሰርቷል፡፡ በፌደራልና በክልል ደረጃ ትልልቅ ለውጦች የተካሄዱበት ዓመት ነው ማለት ይቻላል፡፡ ከካቢኔ ለውጥ ጀምሮ በርካታ ትልልቅ ለውጦች ተደርገዋል፡፡
የተለያዩ የመንግስት ባለስልጣናት እንደ ጥፋታቸው መጠን፣ ከኃላፊነታቸውና ከፓርቲው እንዲባረሩ የተደረገበት ሁኔታ አለ፡፡ በዚህ ጉዳይ ሚዲያው ምን ያህል ትኩረት ሰጥቶ፣ ለህዝቡ አሳውቋል የሚለው ነው ጥያቄው እንጂ በ2009 መንግስት ትልልቅ ስራዎችን የሰራበት አመት ነው ማለት እንችላን፡፡ ለምሳሌ ጊዜያቸው ተጓትቶ የነበሩ ሜጋ ፕሮጀክቶች በፍጥነት እንዲጠናቀቁ የተደረገበት አመትም ነበር፡፡ የኢንዱስትሪ ፓርኮችም ተመርቀው አገልግሎት መስጠት ጀምረዋል፡፡ ሌሎችም የኢንዱስትሪ ፓርኮች ግንባታ ተጀምሯል፡፡
ከሰላምና መረጋጋት ጋር በተያያዘም ትልቅ ስራ ተሰርቷል፡፡ በዚህ መሃል ግን በአንዳንድ ክልሎች የወሰን ግጭቶች ነበሩ፡፡ ለምሳሌ በኦሮሚያና በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል፣ በጋምቤላና በኦሮሚያ፣ በቤንሻንጉልና በኦሮሚያ፣ በአፋርና በትግራይ፣ በአማራ፣ በደቡብ አጎራባች ክልሎች … ህዝብን ያጋጩ የነበሩ የድንበር ችግሮችን ለመፍታት፣ በትጋት ተሰርቷል፡፡
በሌላ በኩል ገዥው ፓርቲና ተፎካካሪ ፓርቲዎች የሚያደርጉት ድርድር አለ፡፡ የሲቪክና የዲሞክራሲ ተቋማት እንዲበረታቱ የተደረገበት ሁኔታም አለ። የሚዲያ ተቋማት፣ ዲሞክራሲና የመልካም አስተዳደር ጉዳዮች ላይ ያተኮረ መድረኮችን እንዲያዘጋጁ፣ ፖለቲካ ፓርቲዎችን እንዲያሳትፉ … ጥረት ተደርጓል፡፡ በሚዲያው ረገድ አጠቃላይ ሪፎርም ለማከናወን እየተሰራ ነው ያለው፡፡
ከጎረቤት ሀገራት ጋር ያለን ግንኙነት የተሻሻለበት ሁኔታ አለ፡፡ ከአባይ ተፋሰስ ሀገራት ጋርም ትልቅ ዲፕሎማሲያዊ ድሎች ተገኝተዋል። ከሩቅ ሆነው ሀገሪቷን ለማተራመስ የሚሞክሩ፣ በተለይ በአሜሪካ፣ በአውሮፓ ሆነው፣ የሀገሪቷ ጉዳይ ያገባናል የሚሉ ነገር ግን ከልማቷ ወደ ኋላ ለማስቀረትና ጫና ለማድረግ የሚያስቡ አካላት አላማቸው እንዳይሳካ የተደረገበት አመት ነበር፡፡ በዚህም ትልቅ ድል ተገኝቷል፡፡
ድርቅ አንደኛው ተግዳሮት ነው፡፡ ከድርቅ ጋር በተያያዘ በሚሊዮን የሚቆጠሩ ዜጎቻችን ለጎዳበት ተዳርገዋል፡፡ እነሱን ለመታደግ መንግስትና ህዝብ በጋራ ተረባርቧል፡፡ በሚገርም ሁኔታም አንድ ክልል እህል፣ ግጦሽና ውሃ እየጫነ፣ ለሌላው የሚያደርስበት መተሳሰብና መተጋገዝ የታየበት ሁኔታም ነበር። መንግስት ጉዳት እንዳይደርስ ከፍተኛ ርብርብ አድርጓል፡፡
ሌላው ተግዳሮት፣ በ2008 መገባደጃ እና በ2009 መጀመሪያ አካባቢ የነበረው ያለመረጋጋት ነው፡፡ ያ የሰላምና መረጋጋት ችግር ባይኖር ኖሮ፣ በሙሉ አቅም በልማት ላይ መስራት ይቻል ነበር። የመልካም አስተዳደር ችግርም ቀላል ተግዳሮት አይደለም፡፡ ጊዜ የፈጀ ጉዳይ ነበር፡፡ የተፈጥሮ አደጋዎችም ነበሩ፡፡
መንግስት አዲሱን ዓመት ከወትሮው በእጅጉ በተለየ መልክ ለመቀበል ምን አሳሰበው?
በሚሊኒየሙ መግቢያ፣ መሪዎቻችን ኢትዮጵያን ወደ ሚፈለገው ስልጣኔ ለመምራት “መጪው የኢትዮጵያ ህዳሴ ነው” ብለው ከህዝቡ ጋር ቃል የገቡበት ነበር፡፡ ባሳለፍነው 10 ዓመት ውስጥ ያገኘናቸው ስኬቶች ምንድን ናቸው? ጉድለቶቻችንስ? ብለን የምናስብበት ነው፡፡ መጪው አስር ዓመት ደግሞ በቀላሉ የሚታይ አይደለም፡፡ በ2017 መካከለኛ ገቢ ካላቸው ሀገራት ተርታ ለመሰለፍ በጥንካሬ እየተሰራ ነው፡፡ ስለዚህ ዜጎቻችን ይሄን አላማ ማወቅ አለባቸው፡፡ ለአላማው ስኬት መነቃቃት አለባቸው፡፡ የሀገር ፍቅር ስሜታችን መነሳሳት አለበት፡፡ ኢትዮጵያን እንደ ሀገር ለማስቀጠልና በዓለም ደረጃም የምንፈልጋት ሀገር ለማድረግ የምናስታውሳቸው እሴቶቻችን ስላሉ ነው፣ ቀናቶችን ሰይሞ መዘከር ያስፈለገው። ለሠላም፣ ለሀገር አንድነት፣ ለሀገር ፍቅር፣ ለአረጋውያን፣ ለመሪዎቻችን፣ ለታዳጊዎች ያሉን እሴቶች አሉ፡፡ 2010ን በመነቃቃት የምንቀበል ከሆነ፣ ሁሉም በየፊናው፣ በንቃት ተሳትፎ፣ ለውጥ የምናመጣበት ይሆናል፡፡
የመንግስት የአዲስ ዓመት ተስፋዎች ምንድናቸው?
በሚቀጥለው ዓመት በመንግስት በኩል የተያዙ ትላልቅ የልማት እቅዶች አሉ፡፡ በዋናነት ህዝባችንን ማብቃት ነው የሚያስፈልገው፡፡ የህዝብ ተሳትፎ በላቀ ደረጃ እንዲያድግ፣ መንግስት በቁርጠኝነት ይንቀሳቀሳል፡፡ ቁርጠኝነቱ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጨመረ ነው፡፡ የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ፣ እያንዳንዱ ዜጋ፣ የተሻለ አመራርና ተስፋ እንዳለ ማየት አለበት። ለያዝነው የእድገት እቅድም ሁኔታዎች የተሻሉ እንደሆነ መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ መንግስት ህዝቡን ለማዳመጥና ለማገልገል ያለው ቁርጠኝነት በጣም ተስፋ ሰጪ ነው፡፡ ኃላፊነቱን፤ ተጠያቂነት ባለው መልኩ ለመወጣት፣ እየሰራ ያለው ስራ፣ ተስፋ ሰጪ በመሆኑ ሁላችንም የተሻለ መልካም ውጤት የምናስመዘግብበት ዓመት ይሆናል፡፡
አዲሱ ዓመት የተሻለ፣ ብሩህ ዘመን እንደሚሆን በማወቅ መቀበል አለብን፡፡ ሀገራችንን የተሻለች የምናደርገው እኛው ነንና፣ በውጪም ሆነ በሀገር ውስጥ የምንኖር ሁሉ፣ ከምንም በላይ ለሀገር አንድነት፣ ለሀገር ሰላም፣ ለሀገር እድገት … ተግተን መስራት አለብን፡፡ በተረፈ መልካም አዲስ ዓመት ይሁንልን!!

    አመልካች እኔ ሳምሶን ጌታቸው ተክለሥላሴ, በሀገረ ኢትዮጵያ የዋና ከተማዋ አዲስ አበባ ነዋሪ ስሆን፤ ሰሞኑን በሀገሬ ላይ በተከሰቱ አንዳንድ አስፈሪ የፖለቲካ ጉዳዮች የተነሳ, ይህንን የአቤቱታ ደብዳቤ ለመጻፍ ተገድጃለሁ፡፡ ይህን አቤቱታ በዚህ መልክ ከመጻፌ በፊት ነገሮች በራሳቸው ጊዜ ወይም በሆኑ የሀገራችን ሰዎች አማካይነት ይስተካከሉ ይሆናልም ብዬ ተስፋ አድርጌ ነበር፡፡ እያንዳንዱ ሰው እየተነሳም በትላልቅ የሀገር ጉዳዮች በዚህ መልኩ አቤቱታ ላሰማ ካለም ለአሰራርም ሆነ ለውጤታማነቱ አስቸጋሪ እንደሆነም ስለማውቅ እና በሌሎች ተያያዥ ምክንያቶች በግሌ ለብዙ ጊዜያት ዝም ማለትን መርጬ ነበር፡፡ ነገር ግን የነገሮች አደገኛ ጎርፍ፣ ሀገሬንና ሕዝቦቿን ባለንበት ጠራርጎ ሊወስደን እየተንደረደረ መሆኑን ስመለከት፤ ቢያንስ የአቅሜን ማበርከት አለብኝ ብዬ በመወሰኔና በዚያም መንፈስ ሆኜ ይኼንን ደብዳቤ ልጽፍ ወደድሁ፡፡
በመጀመሪያ ከሁሉ አስቀድሜ ለዘመናት የሀገሬ ኢትዮጵያ የልብ ወዳጅ፣ የችግሯ ጊዜ ሁሉ ፈጥኖ ደራሽ፣ የዕድገቷና የሥልጣኔዋ ጉዞ ፍፁም አጋዥ እና ደጋፊ ለሆነችው፣ የዓለም ኃያሏ ሀገር ዩናይትድ ስቴትስ ኦቭ አሜሪካ ሕዝብ እና መንግሥት የከበረ ሠላምታዬን በታላቅ ትህትና አቀርባለሁ፡፡ በዚሁ የተለየ አጋጣሚ ሀገሬ እና ሕዝቦቿ ወደ ሥልጣኔ በሚያደርጉት እርምጃ እና ጉዞ ሁሉ ከአሜሪካ ሕዝብ እና መንግሥት ለተደረገልንና እየተደረገለን ስለሚገኘው ውለታ፣ እንዲሁም ይህንኑ ከቅንነት፣ ከርኅራኄ እና ከፍቅር የመነጨ ድጋፍ ባለኝ የዜግነት ድርሻዬ በሀገሬ ስም ከልብ የመነጨ ምሥጋናዬን ላቀርብ እወዳለሁ፡፡ 
በመቀጠልም ሀገሬ ኢትዮጵያ በአሁኑ ሠዓት አንገት ለአንገት እየተናነቀች ከምትገኘው የከፋ ድህነት እና ኋላቀርነት ባሻገር፣ በቀላሉ የማይታይ የፖለቲካ ችግርም እየተስተዋለባት እንደሚገኝ በአደባባይ የዋለ ሀቅ ከሆነ ከራርሟል፡፡ የፖለቲካ ችግሯ በተለያየ ደረጃና መንገድ ተጉዞ አሁን የደረሰበት አደገኛ ደረጃ ላይ መገኘቱ፣ ከወዳጃችን የአሜሪካ መንግሥት የተደበቀና ድንገተኛ ክስተት እንዳልሆነም ይታወቃል፡፡ ይህንንም ስል የአሜሪካ መንግሥት በተለያዩ ጊዜያት የሚስተዋሉ መሠረታዊ የአስተዳደርና የአካሄድ ችግሮችን፣ በዚህ ደረጃ ሥር ሳይሰዱ መስተካከል ይችሉ ዘንድ በተለያዩ መንገዶች የወዳጅ ምክሮችን ሲያስተላልፍ እንደነበር ይታወሳልና ነው፡፡
የሆነው ሆኖ ለተፈጠረው የፖለቲካ ውጥንቅጥ የመፍትሔ አካል ሆኖ ከመገኘት ይልቅ ይበልጥ የሚያወሳስብ እና የከፋ መልክ እንዲይዝ የሚያደርጉ ሁኔታዎች እየተስተዋሉ ይገኛል፡፡ በእኔ ዕይታ እና አስተውሎት ከመንሥዔው ባልተናነሰ የችግሩ ዋነኛ አባባሾች እና አወሳሳቢዎች ደግሞ አንዳንድ በአሜሪካ ሀገር በነዋሪነት የሚገኙ የኢትዮጵያ ሰዎች ናቸው፡፡ የዚህ የአቤቱታ ማመልከቻ ደብዳቤዬ ዋነኛ መነሻዎቹም እነሱ ናቸው፡፡ እነዚሁ ወንድሞቻችን የአሜሪካ ሕዝብ እና መንግሥት ባመቻቹላቸው የኑሮ፣ የትምህርት እና የሥራ ዕድል ተጠቅመው፤ በተማሩት ትምህርት፣ በቀሰሙት ዕውቀት፣ በተግባር በተመለከቱት የሥልጣኔ ምጥቀት መሠረት፣ የሀገራቸውን የኢትዮጵያ አንድነት አስጠብቀው እና የሕዝባቸውን የፍትሕ፣ የዴሞክራሲ እንዲሁም የሥልጣኔ ጥማት ለማርካት እንደመጣር፣ በሀገሪቱ የተፈጠረውን ትልቅ የፖለቲካ ሥህተት የሚታረምበትን መንገድ እና የተሻለ አማራጭ እንደመፈለግ፤ በተቃራኒው እነሱ ግን ሁኔታውን እንደ ምቹ አጋጣሚ በመጠቀም ጭራሽ ወደ ከፋ ሁኔታ እንዲያመራ እና እንዲባባስ በማድረግ፣ ሀገራችን ኢትዮጵያን ሊበታትን እና ሕዝቦቿን ሊያበጣብጥ በሚችል ደረጃ፣ በክልላዊ ብሔርተኝነት ስም በጥላቻ ላይ የተመሠረተ የጎሣ ፓለቲካ ሥራ ላይ ተሰማርተው ይገኛሉ፡፡
በኢትዮጵያ ሕዝብ አሰፋፈር እና ስብጥር፣ መልክዓ ምድራዊ አቀማመጥ፣ ታሪካዊ፣ ባሕላዊ እና ሐይማኖታዊ አኗኗር፣ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ ትሥሥር እንዲሁም የደም ለደም ውህደት ምክንያት ፈፅሞ ሊተገበሩ ቀሮቶ ሊታሰቡ የማይችሉ የተሳሳቱ የጎሣ ፖለቲካ አስተሳሰቦችን፣ በመስበክ እና በመቀስቀስ፣ ዛሬን ብቻ አሸናፊ መስለው ለማለፍ በመሞከር፣ ሕዝባችንን በተሳሳተ እና ፍፁም አደገኛ በሆነ በክልል ብሔርተኝነት ላይ በተንጠለጠለ የጎሰኝነት ሥነ ልቦና ላይ እንዲገኝ ከፍተኛ አስተዋጽኦ በማድረግ ላይ ይገኛሉ፡፡ የዚሁ ድርጊታቸው ውጤትም ከተራ ቅስቀሳነት አልፎ መርዛማ ፍሬውን አፍርቶና በመጠኑም ቢሆን በስሎ በተግባር በተለያዩ ሁኔታዎች መታየት ጀምሯል፡፡ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በተለያዩ የኢትዮጵያ ክፍላተ ሀገር የተከሰቱ እንቅስቃሴዎችን መመልከት ይቻላል፡፡
የሀገራችን ሕዝቦች ለዘመናት ሲታገሉለት የኖሩትን የፍትሕ፣ የመብትና እና የመልካም አስተዳደር ጥያቄዎችን በመጥለፍና ተገቢውን አቅጣጫ በማሳት፤ ጥላቻ አዘል የጎሣ ፖለቲካ ያለከልካይ እየሰበኩ እና እያራገቡ ሀገራችንን የመበተን አቅሙን ከዕለት ወደ ዕለት በዕጃቸው እያስገቡት ይገኛል፡፡ ዛሬ ላይ ይኸው ድርጊታቸው ምናልባት ጀብድ እንደሚወድ ትንሽ ልጅ “እኔ ነኝ ይኼን ያደረኩት፣ ጉልበቴም እዚህ ድረስ ነው” ከማለት ያለፈ አንዳች ዘላቂ ጥቅም በግላቸው አያስገኝላቸውም፡፡ ነገር ግን ችግሩ የሚጀምረው ስህተታቸው ሥር ሰዶ መጨረሻው ደረጃ ላይ የደረሰ ቀን ነው፡፡ በዚህም ምክንያት በእነሱ ያልተገባ የፖለቲካ ጨዋታ የመከራ ደመና በሀገሬ ኢትዮጵያ ሰማይ ላይ እያንዣበበ እንደሚገኝ ይሰማኛል፡፡ አይበለውና ይኼው የመከራ ደመና ከዘነበ፤ ሀገሬ ኢትዮጵያ በአፍሪካም ሆነ በቅርቡ በመካከለኛው ምሥራቅ አንዳንድ ሀገራት ከተከሰተው ያልተናነሰ፤ ምናልባትም ከዚያም በከፋ ታይቶ በማይታወቅ ሁኔታ አሰቃቂ የሕዝብ ፍጅት እና ዕልቂት ልታስተናግድ ትችላለች፡፡
የእነዚሁ ወንድሞቻችን ከበዙ አደገኛና አጥፊ ድርጊቶቻቸው መካከል እንደ አንድ ምሳሌ ለመጥቀስ ያህል ብሞክር፤ ኢትዮጵያን እነሱ በመሰላቸውና በዘፈቀደ እንዲሁም ለጊዜያዊ የፖለቲካ ጥቅማቸው ሲሉ ባሴሩበት መንገድ ብቻ፣ የወደፊት ሀገራችን ብለው የዛሬዎቹን የክልሎች ስያሜ ተከትለው፣ የራሳቸውን ድንበር በወረቀት ላይ አካለው እስከመጨረስ ደርሰዋል፡፡ ከጅምሩ የተነሱበት ሀገርን የመገነጣጠል ፖለቲካቸው በዕውነተኛ የሕዝቦች ጥያቄ ላይ የተመሠረተ ስላልነበረ እና እነሱ ራሳቸው በፈበረኩት የልብወለድ ታሪክ ለይ የተንጠለጠለ በመሆኑ፤ ጉዳዩን በተጨባጭ መሬት ላይ ለማውረድ በሚጥሩበት ጊዜ ደግሞ የማይያዝና የማይጨበጥ ሆኖ ሲያስቸግራቸው ይታያል፡፡ ለዚህም የሚነድፏቸው የድንበር ወሰን አመላካች ካርታ፣ አንደኛው የእኔ ግዛት ብሎ ያሰፈረው እና ሌላኛውም የእኔ የድንበር ወሰን ብሎ ከደነገገው ጋር እርስ በእርስ ተደራርቦ መገኘቱን መጥቀስ ይቻላል፡፡ ይህን ድርጊት አሁን ላይ እንደ ቀልድ አይቶ መተው ቢቻልም፤ በሂደት ግን በሀገራችን ሕዝቦች መካከል ያልተገባ ከፍተኛ እና ማባሪያ የሌለው ግጭት የማስነሳት ዕምቅ አቅም ያለው እና ጊዜውንም ጠብቆ ሊፈነዳ የሚችል አጥፊ ተግባር ነው፡፡ ይህን ጉዳይ ዛሬ ላይ ተሁኖ በዝምታ ማለፍ በተዘዋዋሪም ቢሆን የዚያ የጥፋት ድርጊት ተባባሪ እንደመሆን ያስቆጥራል፡፡ እንዲህ ያለውን አጥፊ ድርጊት የረጅም ዕደሜ እና ሠፊ ታሪክ ባለቤት በሆነች ሉዐላዊት ሀገር ላይ ለመተግበር ከመሞከር የባሰ ምንስ በደል ምንስ ሕገ-ወጥነት ይኖራል?
ይኼንኑ ድርጊት በማስረጃነት ለመጥቀስ ያህል ከዚህ ደብዳቤ ጋር በአባሪነት በብዙ ሰዎች ቅብብሎሽ በየኢንተርኔቱ ለመቀስቀሻነት በመሰራጨት ላይ የሚገኙ በየብሔሩ የተሸነሸነችውን የኢትዮጵያ ካርታ የሚያሳይ ምስል አያይዣለሁ፡፡
በእውነቱ እንዲህ ያለው የጭካኔ ሥራ አርቃቂ እና አስፈፃሚ ሆኖ መገኘት፣ በታሪክ ተወቃሽ ከማድረጉም አልፎ ጊዜውን ጠብቆ የሕግ ተጠያቂነትን የሚያስከትል ያልተገባ ተግባር እንደሆነ፣ በዚህ መልኩ ያለፉ ሀገራትን ልምድ ወደኋላ ዞር ብሎ መመልከት ብቻ በቂ ትምህርት ነበር፡፡ ከአንድ ሀገሩን እና ሕዝቦቿን በቅንነት ከሚወድ ዜጋ በሚጠበቅ ደረጃ የሚያኮራ ድርጊት እንዳልሆነም ይታወቃል፡፡
አሜሪካንን በሚያህል የአንድነት፣ የዴሞክራሲ፣ የሕዝቦች ዕኩልነት፣ የሥልጣኔ፣ የዕውቀትና ብልፅግና ተምሣሌት በሆነች ሀገር ላይ ሲኖሩ፤ የተማሩትን፣ ያዩትን፣ የቀሰሙትን ዕውቀት እና ልምድ ወደ ሀገራቸው በሚመጥን መልኩ አምጥተው ለመተግበር እንደመጣር፣ ያን ያህል ዕውቀት እና ልፋት በማይጠይቀው የሀገርን አንድነት በመበታተን እና በማፈራረስ ተግባር ላይ ተሰማርቶ መገኘት ምን ይባላል፡፡ ይህም ድርጊታቸው የጋራ ሀገራችን ለሆነችው ኢትዮጵያ አውዳሚ ሲሆን፤ ዕድሉን ሰጥታ በከፍተኛ ወጪ ላስተማረቻቸው አሜሪካ ደግሞ ኪሳራ ነው፡፡ በእርግጥ ለቅንነት እና ለፍቅር ልቡን መስጠት ለማይችል ሰው የዕውቀት ዕድል ቢመቻችለትም ትርፉ እንዲህ ያለው ጥፋት ነው፡፡ መገለጫውም አፍራሽ ሥራ ነው፡፡ በጣም ያሳዝናል፡፡ ሆኖም ይህን ስል ግን ከአስቸጋሪዎቹ የሀገራችን ሰዎች በተቃራኒው ቁመው፤ ዕድሜያቸውንና ዕውቀታቸውን ሁሉ ለሀገራችን ዕደገት፣ ሰብአዊ መብቶች መከበር፣ ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ እና ብልፅግና የሚተጉ ብዙ ቁጥር ያላቸው ወንድሞቻችንም መኖራቸውም የታወቀ ነው፡፡
ኢትዮጵያ ካላት ከፍተኛ የሕዝብ ብዛት አንፃር፣ ብዙም መረጋጋት በማይስተዋልበት የምሥራቅ አፍሪካ ክልል ከመገኘቷም ጭምር፤ የእሷ መተራመስ በቅድሚያ የገዛ ሕዝቦቿን በሚዘገንን መልኩ የመከራው ዋና ተጠቂዎች ቢያደርግም፤ የውድቀቱ ንዝረት እና ርዕደት ደግሞ በመላው ዓለም ከጫፍ እስከ ጫፍ በሁሉም አቅጣጫ መሰማቱ እና ማናወጡ አይቀርም፡፡ በዚህም ምክንያት ዓለም ለብዙ ጊዜያት ሲታገለው እና ሲፋለመው ረዥም ርቀት የተጓዘበትን የሽብርተኝነት ተግባር፣ እንደ አዲስ እንዲያንሰራራ እጅግ የተመቻቸ ሁኔታን ስለሚፈጥርለት፣ የዓለምን ሽብርተኝነትን የመታገልና የመደምሰስን ልፋት መልሶና ቀልብሶ በብዙ ርምጃዎች እንደገና ወደኋላ የሚመልስ ውጤትም ማስከተሉ አይቀርም፡፡ በተጨማሪም በሰው ልጆች ታሪክ ውስጥ ከተከሰቱና አስከፊ ከሚባሉ የሕዝብ ፍልሰትና ስደት ታሪኮች ባልተናነሰ ምናልባትም የባሰ ሁኔታ በዓለም ላይ ሊያስከስት ይችላል፡፡
ስለሆነም ያ አሰቃቂ ጥፋት እና መከራ ከመከሰቱ በፊት፣ በእኔ ዕይታ የአሜሪካ መንግሥት ጉዳዩን ትኩረት ሠጥቶ በጥሞና ቢመለከተው ነገሩን በአጭሩ ማስቀረት የሚያስችል መፍትሔ እንደሚገኝለት እተማመናለሁ፡፡ የአሜሪካ ምድር ለሰው ልጆች ሁሉ የመብትና የነፃነት ምድር እንደሆነች ይታወቃል፡፡ ይሁን እንጂ መብትንም ሆነ ነፃነትን በመጠቀም ጊዜ ደግሞ፣ በሌሎች ሰዎች ላይ አሉታዊ ተጽዕኖ ወይም ውጤት እንዳያመጣ በሚገባ መጠንቀቅ ዋነኛው የመብቱ ተጠቃሚ ኃላፊነት መሆኑም የታወቀ ነው፡፡ ነገር ግን ከላይ ለመጥቀስ በተሞከረው መሠረት በሀገሬ ኢትዮጵያ ላይ ያልተገባ የክልል ብሔርተኝነትን አስተሳሰብ በማቀጣጠል ላይ ያሉት ወንድሞቻችን፣ በመሠረታዊ ደረጃ ይህን የመብት አጠቃቀም አግባብነት ባላገናዘበ ወይም ሆን ተብሎ ወደ ጎን በተወ መልኩ፣ የአሜሪካ ሀገር ነዋሪነታቸውን ብቻ ተገን በማድረግ እየፈፀሙ ስለመሆናቸው አልጠራጠርም፡፡ በዚህም ምክንያት እነዚሁ የሀገሬ ሰዎች የተሰጣቸውን መብት እና ነፃነት ላልተገባ ዓላማ እያዋሉት እንደሚገኙ አምናለሁ፡፡ በመሆኑም ይህ ድርጊታቸው ኢትዮጵያን ማለቂያ ወደሌለው የጎሣና የማንነት ጥያቄ ትርምስ፣ የድንበር ይገባኛል ውዝግብ፣ የነፃ አውጪዎች ጋጋታ፣ የሐይማኖት ቡድንተኝነት መዘዝ እናም በአጠቃላይ አሰቃቂ የእርስ በእርስ መተላለቅ ወደሚያስከትል የመከራ ገደል እየገፋት ይገኛል፡፡
አሜሪካ ሽብርተኝነትን አጥብቃ የምትኮንነው እና የምትዋጋው የዘመናችን አስከፊ የሰው ልጆች ሁሉ ጠላት የሆነ ተግባር እንደሆነም ይታወቃል፡፡ ሽብርተኝነት ደግሞ ብዙ መልክ እና መገለጫዎችም እንዳሉት እርግጥ ነው፡፡ በእኔ አረዳድ ለማንኛውም ዓላማ ሲባል፤ በሠላማዊ ሕዝቦች መካከል እልቂትን የሚፈጥር ቅስቀሳ ማድረግ፣ ነውጥን መጠንሰስ፣ ማስተባበር ብሎም ተግባራዊ ማድረግ፣ የሀገርን ብሔራዊ አንድነት የሚያናጋ የትርምስ ተግባራት ማቀድና መሳተፍ፣ በአጠቃላይ በሰው ልጆች እና በሀገር ላይ የሚፈፀሙ አውዳሚ ተግባራት ሁሉ የሽብር ድርጊቶች ናቸው፡፡ ጥፋቱ በገዛ ሀገር እና ሕዝብ ላይ ሲፈፀም ደግሞ ከሽብር ድርጊትነቱ በተጨማሪ የሀገር መክዳትን ተጠያቂነትም አብሮ የሚያስከትልና የሚያካትትም ይመስለኛል፡፡
የአሜሪካ መንግሥት ከሌሎች ሀገራት የተቃውሞ ፖለቲካ አራማጆች በተለየ፣ ለእኛዎቹ የኢትዮጵያ ሰዎች ሠፋ ያለ የመጫወቻ ሜዳ ሳያመቻችላቸው አልቀረም፡፡ ይህም ለሀገራችን ካለው የወዳጅነት ስሜት የመጣ እንደሆነ እርግጠኛ ሆኖ መናገር ይቻላል፡፡ ነገር ግን ይህን የተመቸ ዕድል በኃላፊነት ተጠቅመው ለሀገራቸውና ለሕዝባቸው የተሻለ የፖለቲካ አማራጭ እንደማስተዋወቅ፤ አሜሪካንን እንደ የጦር ዕዝ ሠፈር በማስመሰል ኢንተርኔትን ደግሞ እንደ ጦር መሣሪያ በመቁጠር የውጊያ መመሪያ መስጫ የማድረግ ሙከራዎች እየተስተዋሉ ይገኛል፡፡ ይህም መብት እና ነፃነትን በአግባቡ የመጠቀምን አስፈላጊነት እና ግዴታን ወደጎን ከመተው አንዳንዴም ከግድየለሽነት በመነጨ መልኩ ስለመሆኑ፣ ከድርጊታቸው በመነሳት እርግጠኛ ሆኖ መናገር ይቻላል፡፡
ታላቋ አሜሪካ ዛሬ ለምትገኘው ሀገሬ ኢትዮጵያ በፍፁም ወዳጅነት እና አጋርነት ያበረከተችው አስተዋጽኦ እና ድጋፍ በሀገሪቱ ታሪክ ሁሉ የሚረሳ አይደለም፡፡ በአጠቃላይ በማኅበራዊ፣ በኢኮኖሚያዊ እና በፖለቲካዊ ጉዳዮች ሁሉ በወንድማዊ ስሜት የተደረገልን ልባዊ ድጋፍ ለሁል ጊዜ ሲዘከር ይኖራል፡፡ በመሆኑም አሜሪካ በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ፣ ስለኢትዮጵያ ከእኛ ከዜጎቿ ባልተናነሳ ከፍተኛ አቅሟን አውጥታ ስትለፋ ኖራለች፡፡ የዚህ ሁሉ የአንድ ክፍለ ዘመን ዕድሜ በላይ የአሜሪካ ሕዝብ እና መንግሥት ልፋት እና ጥረት ደግሞ የተረጋጋችና የበለጸገች ኢትዮጵያን የማየት ራዕይ እንደሆነ የታወቀ ሀቅ ነው፡፡
ስለሆነም ታላቋ ሀገር ዩናይትድ ስቴትስ ኦቭ አሜሪካ ለኢትዮጵያ ባላት እጅግ የላቀ ወዳጅነት፣ አጋርነት እና ተሰሚነት ምክንያት የሚከተሉትን አንኳር ነጥቦችን የያዙ ሁለት ጥያቄዎችን በአክብሮት ለማቅረብ እወዳለሁ፡፡
1ኛ) ዩ ኤስ አሜሪካ በዓለም መድረክ በተግባር ከምትታወቅበት ለፍትሕ፣ ለሰው ልጆች መብትና ዴሞክራሲ ከመቆሟ አንፃር፤ በአሜሪካ የሚኖሩ የአንዳንድ ወንድሞቻችን ድርጊት በእርግጥ በዚያ ትክክለኛ ማዕቀፍ ውስጥ መሆኑን የአሜሪካ መንግሥት እንዲያጤነው፣ አጢኖም ከላይ እኔ በዘረዘርኩት መጠን የአካሄድ ስህተት መኖሩ ከታወቀ ደግሞ፣ ይህን የተወገዘ እና ያልተገባ ድርጊት በሀገረ አሜሪካ ላይ ቁጭ ብለው በገዛ ትውልድ ሀገራቸው ላይ እየፈፀሙ የሚገኙትን የሀገራችንን ሰዎች ተግባር ጉዳዩን ከሕግ አግባብነት፣ በሀገሬ ኢትዮጵያ እና ሕዝቦቿ ላይ ከሚያስከትለው ጉዳትና ውድመት አንፃር ተመልክቶ የእርምት እርምጃ እንዲወስድ
2ኛ) ከላይ ባልተገባ ድርጊታቸው ከወቀስኳቸው ወንድሞቻችን ባልተናነሰ፤ ሀገራችን ኢትዮጵያ አሁን ለምትገኝበት አስፈሪ የፖለቲካ ሁኔታ እና ውጥንቅጥ፣ ከጅምሩም ሆነ አሁን ለደረሰበት ደረጃ የሀገሬ መንግሥት ዋናው ባለድርሻ አካል መሆኑን አምናለሁ፡፡ የሆነው ሆኖ አሁን የደረስንበት አደገኛ ሀገራዊ ሁኔታ ከመወነጃጀል አልፈን ነገሮችን በጣም በፍጥነት፣ በቅንነት እና በእርቅ መንፈስ ለማስተካከል ካልተጣረ፣ መጪው ቅርብ ጊዜ ለሀገሬ ኢትዮጵያ ማንም ምንም የማያተርፍበት እጅግ የከፋ የውድመት እና የመከራ ሊሆን እንደሚችል መገመት አያዳግትም፡፡
በአሁኑ ሰዓት ሁሉንም ሰው በብሔር ማንነቱ ጥግ የማስያዝ ክፉ አስተሳሰብ ሀገራችን ላይ በመስፈሩ፣ ለሁሉም የሀገራችን “ፖለቲከኞች” በጋራና በዕኩልነት ተሰሚነት ያለው ሀገራዊ የሚባል አስታራቂ እና መካሪ ትልቅ ሰው እንዳይኖረን ተደርጓል፡፡ ስለሆነም ከፊት ለፊታችን ከተደቀነብን አስከፊ ሀገራዊ ጥፋት ለመዳንና መፍትሔ ለማግኘት፣ ሌላ የጋራ ወዳጅ እና ገለልተኛ አካል ማስፈለጉ ተገቢ መስሎ ይሰማኛል፡፡ በመሆኑም በእኔ ዕውቀት በዚህ ሰዓት ከታላቋ አሜሪካ መንግሥት በላይ ለኢትዮጵያ የቀረበ ተሰሚነት እና ተጽዕኖ ያለው አጋር መኖሩን እጠራጠራለሁ፡፡
ስለሆነም የአሜሪካ መንግሥት ሀገሬ ኢትዮጵያ በጉልህ የተደቀነባትን አስፈሪና አደገኛ ሁኔታ ቅርብነትና ድርስነት ከግምት ውስጥ አስገብቶ፣ ልዩ ተኩረት እንዲሰጠው እና መንግሥታችንን ጨምሮ በሁሉም ጎራ በያገባኛል ስሜት የሚንቀሳቀሱ የፖለቲካ ሰዎችን፣ በተገቢው ጫና እና ምክር ወደሚበጀው ሀገራዊ ስምምነት እንዲመጡ ጥረት እንዲያደርግልን፣ የአሜሪካ መንግሥት የተለመደ የወዳጅነት እና የመፍትሔ አፈላላጊነት ሚናውን እንዲያበረክት ከልብ በመነጨ አክብሮት ባለኝ የዜግነት ድርሻዬ እማፀናለሁ፡፡ ኢትዮጵያ እና ሕዝቦቿ የተደቀነባቸው አስከፊ ውድመት ከመከሰቱ በፊት ዛሬ አድኑልን፡፡ ከውድመት እና ከፍጅት በኋላ የሚደረጉ ርብርቦሾች በሁሉም ነገሩ አስከፊ፣ አክሳሪ፣ የማይሽር ቁስል ጥሎ የሚያልፍ እና ወደነበረበት የመመለስ ዕድሉም በበዙ መልኩ የመነመነ ነውና፡፡
ከልባዊ አክብሮት ከመነጨ ምሥጋና ጋር
ሳምሶን ጌታቸው ተክለሥላሴ