Administrator

Administrator

ኦኤምኤን ቴሌቪዥን ዛሬ ከአዲስ አበባ ስርጭቱን ይጀምራል

    መንግስት አገልግሎት እንዳይሰጡ ዘግቷቸው የነበሩ 264 የተለያዩ ድረ-ገጾችና የጦማርያን ገጾችን በመክፈት አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረጉን፣ የጠቅላይ ሚኒስትር ጽህፈት ቤት ሃላፊው አቶ ፍጹም አረጋ ትናንት በትዊተር ገጻቸው አስታውቀዋል፡፡
በአሜሪካ ፍቃዱን አግኝቶ የሚሰራጨው የኦሮሞ ሚዲያ ኔትዎርክ (OMN) ቴሌቪዥን፣ በዛሬው ዕለት ከአዲስ አበባ ሥርጭቱን እንደሚጀምር ታውቋል፡፡
ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ መብትን ማረጋገጥ፣ ለሌሎች መብቶች መከበር መሰረታዊ ጉዳይ መሆኑን የገለጹት አቶ ፍጹም፤ በመስኩ የማሻሻያ እርምጃዎችን በመውሰድ ላይ የሚገኘው የጠቅላይ ሚኒስትር አብይ አህመድ መንግስት፣ ተዘግተው የነበሩ ድረ-ገጾችን በመክፈት፣ አገልግሎት እንዲሰጡ ማድረጉን አመልክተዋል፡፡
ነጻ የመረጃ ፍሰት እንዲኖር ማድረግ፣ በአገሩ ጉዳይ ተሳታፊና ሃላፊነት የሚሰማው ዜጋ ለመፍጠር ቁልፍ ሚና ይጫወታል ያሉት አቶ ፍጹም፤ መንግስት የተዘጉ ድረገጾችን ከመክፈት በተጨማሪ የኢሳትና የኦኤምኤን የቴሌቪዥን ስርጭቶች በነጻነት እንዲታዩ መፍቀዱንም ገልጸዋል፡፡    
አሶሼትድ ፕሬስ በበኩሉ፤ መንግስት ዘግቷቸው የነበሩት ብዙዎቹ ድረ-ገጾች በአሜሪካና በሌሎች ውጭ አገራት የተከፈቱ እንደሆኑ በመጠቆም፣ በአገሪቱ ታስረው የነበሩ ከሞላ ጎደል ሁሉም ጋዜጠኞችና ጦማሪያን በአዲሱ የጠቅላይ ሚኒስትር አቢይ መንግስት ከእስር መለቀቃቸውንና መንግስትን በመተቸት በሚታወቁ አክቲቪስቶች ላይ ተመስርተው የነበሩ ክሶች መቋረጣቸውን ዘግቧል፡፡

 የሳምሰንግ ኩባንያ ምርት የሆነው ጋላክሲ ኤስ 9 ፕላስ ያለፈው ሚያዝያ ወር የአለማችን የሞባይል ሽያጭ ደረጃን ከአፕል ኩባንያው ታዋቂ ምርት አይፎን ኤክስ መረከቡን ቴክ ዶት ኮም ዘግቧል፡፡
ካውንተርፖይንት የተባለው አለማቀፍ የስማርት ፎን ገበያ ጥናት ተቋም ያወጣውን መረጃ ጠቅሶ ዘገባው እንዳለው፣ ከጋላክሲ ኤስ 9 ፕላስ በመቀጠል በሽያጭ እስከ አምስተኛ ያለውን ደረጃን የያዙት ጋላክሲ ኤስ 9፣ አይፎን ኤክስ፣ አይፎን 8 ፕላስ እና አይፎን 8 የሞባይል ስልኮች ናቸው፡፡
የሳምሰንግ ኩባንያ ምርት የሆኑት ጋላክሲ ኤስ 9 ፕላስ እና ጋላክሲ ኤስ 9፣ በሚያዝያ ወር የአለማችን የስማርት ፎን ገበያ ሽያጭ 2.6 በመቶ ድርሻ መያዛቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ አይፎን ኤክስ በበኩሉ 2.3 በመቶ ድርሻ መያዙን አመልክቷል፡፡
በወሩ የአለማቀፍ የስማርት ፎን ገበያ እንደ ቅደም ተከተላቸው፣ ከስድስተኛ እስከ አስረኛ ያለውን ደረጃ የያዙት ስማርት ፎኖች ደግሞ፣ ሬድሚ 5 ኤ፣ አይፎን 6፣ ሬድሚ 5 ፕላስ፣ አይፎን 7 እና ጋላክሲ ኤስ 8 ናቸው ተብሏል፡፡

ፕላቶ የተባለቺው የናይጀሪያ ግዛት ዋና አስተዳዳሪ የነበሩትና በአሁኑ ወቅት የኮንግረስ አባል የሆኑት ጆሽዋ ዳሪዬ፣ በ3.2 ሚ ዶላር ዝርፊያ ተከከስሰው የ14 አመታት እስር እንደተፈረደባቸው ተዘግቧል፡፡
ባለስልጣኑ እ.ኤ.አ ከ1999 እስከ 2007 የፕላቶ ግዛት ዋና አስተዳዳሪ ሆነው በሚሰሩበት ወቅት ለግዛቲቱ የአካባቢ ጥበቃ የተመደበውን 3.2 ሚሊዮን ዶላር ዘርፈው፣ ለግል ጥቅማቸው ማዋላቸው በመረጋገጡ፣ የእስር ቅጣቱ እንደተጣለባቸው ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
በተመሳሳይም ታራባ የተባለቺው የናይጀሪያ ግዛት ዋና አስተዳዳሪ የነበሩት ጆሊ ናይሜ፣ ከሁለት ሳምንታት በፊት በሙስና ተከስሰው፣ የ14 አመታት እስር እንደተፈረደባቸው ዘገባው አስታውሷል፡፡

አየርላንዳዊው ደራሲ ማይክ ማኮርማክ በአይነቱ ባልተለመደውና አንድ አረፍተ ነገር ብቻ ባለው የልቦለድ ስራቸው የዘንድሮው የደብሊን አለማቀፍ የስነጽሁፍ ሽልማት 100 ሺህ ፓውንድ ተሸላሚ መሆናቸው ተዘግቧል፡፡
ደራሲው በአለማችን እጅግ ከፍተኛውን የስነጽሁፍ የገንዘብ ሽልማት ለሚያስገኘው የደብሊን አለማቀፍ የስነጽሁፍ ሽልማት የበቁት፣ ሶላር ቦንስ የሚል ርዕስ በሰጡትና 270 ገጾች ባሉት የረጅም ልቦለድ መጽሃፋቸው ሲሆን የልቦለዱ ታሪክ ተጀምሮ የሚያበቃው በአንድ እጅግ እጅግ እጅግ እጅግ ረጅም አረፍተ ነገር ብቻ መሆኑንም አይሪሽ ታይምስ ጋዜጣ ዘግቧል፡፡ ይህ የረጅም ልቦለድ መጽሃፍ ከዚህ ቀደምም ጎልድስሚዝ ፕራይዝን ጨምሮ የተለያዩ አገራዊና አለማቀፍ የስነጽሁፍ ሽልማቶችን ማግኘቱን ያስታወሰው ዘገባው፤ መጽሃፉ በአንባብያንና በሃያሲያን ዘንድ ከፍተኛ ተወዳጅነትን እንዳገኘና መነጋገሪያ ሆኖ መዝለቁን ገልጧል፡፡
ባለፈው ረቡዕ ለተካሄደው የ2018 የደብሊን አለማቀፍ የስነጽሁፍ ሽልማት፣ ከ37 የአለማችን አገራት በድምሩ 150 መጽሃፍት በዕጩነት መቅረባቸውን የጠቆመው ዘገባው፤ አየርላንዳዊው ደራሲ ማይክ ማክሮማክ ከዚህ በፊትም አምስት ልቦለድ መጽሃፍትን ለንባብ ማብቃታቸውን አስታውሷል፡፡

ህገ-መንግስቱን ጥሰው በስልጣን ላይ የመቆየት ዕቅድ እንዳላቸው በስፋት ሲነገርላቸው የቆዩት የዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ፕሬዚዳንት ጆሴፍ ካቢላ፤ በቀጣዩ አመት ታህሳስ ወር በሚካሄደው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ላይ ለ3ኛ የስልጣን ዘመን እንደማይወዳደሩ በይፋ መነገሩን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
የአገሪቱ ህገ-መንግስት አንድ ፕሬዚዳንት ከሁለት ተከታታይ የስልጣን ዘመናት በላይ በመንበሩ ላይ እንዳይቆይ እንደሚከለክል የጠቆመው ዘገባው፤ፕሬዚዳንት ጆሴፍ ካቢላም ህጉን በማክበር በምርጫው እንደማይወዳደሩና ስልጣናቸውን በምርጫ ለሚያሸንፈው ተወዳዳሪ በሰላማዊ መንገድ እንደሚያስረክቡ ባለፈው ማክሰኞ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ቡርኖ ሺባላ ማስታወቃቸውን አመልክቷል፡፡
እ.ኤ.አ በ2001 የአባታቸውን ቦታ ተክተው ስልጣን የያዙት ጆሴፍ ካቢላ፤ በመጪው ታህሳስ ወር ላይ በሚከናወነው የአገሪቱ ፕሬዝዳንታዊ ምርጫ ላይ የመወዳደር ዕቅድ እንዳላቸው በስፋት ሲነገርና ብዙዎችም ይህንን ዕቅድ ሲተቹና ጉዳዩ በአገሪቱ ግጭት ሊቀሰቅስ ይችላል በሚል ስጋታቸውን ሲገልጹ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ካቢላ እንደማይወዳደሩ በይፋ ያስታወቁትም ይህን ስጋት ለመቅረፍ በማሰብ ሳይሆን አይቀርም መባሉን አስረድቷል፡፡
በተያያዘ ዜናም በህዝበ ውሳኔ ለተጨማሪ 14 አመታት በስልጣን ላይ ለመቆየት የሚስችላቸውን የህገ-መንግስት ማሻሻያ አስጸድቀዋል በሚል ከተቃዋሚዎችና ከአለማቀፍ ተንታኞች ውግዘት ሲወርድባቸውና በስልጣን ጥመኝነት ሲታሙ የከረሙት የብሩንዲው ፕሬዚዳንት ፔሪ ንኩሩንዚዛ፤ ባለፈው ሳምንት በሰጡት መግለጫ፣ በ2020 ስልጣን እንደሚለቁ መግለጻቸው  ይታወሳል፡፡
በ2020 የስልጣን ዘመናቸውን የሚያጠናቅቁት ፔሪ ንኩሩንዚዛ፣ በቅርቡ በተካሄደው ህዝበ ውሳኔ የህዝብ ድጋፍ አግኝቶ በህግነት በጸደቀው ማሻሻያ፣ ለተጨማሪ ሁለት የስልጣን ዘመናት ወይም 14 አመታት በመንበራቸው ላይ እንደሚቆዩ ብዙዎች በእርግጠኝነት ሲናገሩ ቢቆዩም፣ ፕሬዚዳንቱ ግን በስልጣን ላይ የመቆየት ፍላጎት እንደሌላቸውና በቀጣዩ ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ ላይ እንደማይወዳደሩ አስታውቀዋል፡፡


    “በስራ በዕውቀት
ግሎ ለመነሳት፣
ቆስቋሽ ይፈልጋል
የሰው ልጅ እንደ’ሳት!”
(የክቡር ዶክተር ከበደ ሚካኤል “አጭሬ”)
መነሾ ለነገር…     
በደቡብ መለስ አመራር አካዳሚ ለክልሉ ዓቃብያነ ህግ ተዘጋጅቶ በነበረ ስልጠና ላይ ለመሳተፍ ከሐይቋ ከተማ ሐዋሳ ተገኘሁ፡፡ የስልጠናው ማጠናቀቂያ ሰሞን ግቢው ውስጥ መጽሃፍ እያዞሩ የሚሸጡ ሰዎች ተከሰቱና “ለሙያ ባልደረባችን ድጋፍ እያሰባሰብን ስለሆነ፣ ይህቺን መጽሃፍ ግዙን” ብለው ከያዟቸው መጽሃፍት ውስጥ አንዱን ሰጡኝ፡፡ የመጽሃፉ ሽፋን ያምራል፣ ርዕሱም ቢሆን ሳቢ ነው፣ “አዲስ ሕይወት” የሚልና ከሽፋን ስዕሉ ጋር ስሙም ሆኖ ይህንኑ የሕይወት ጅማሬ በትክክል የሚወክል የችግኝ ምስል ትዕምርት ሆኖ አብሮት አለ፡፡ መጽሃፉ በ-137- ገጾች “ለምን እኔ?” ከሚለው ቀዳሚው ምዕራፍ ጀምሮ፣ “ቅድመ ታሪክ” እስከሚለው ፍጻሜ፣ በ-6- ምዕራፎች እጥር ምጥን ተደርጎ የተዘጋጀ ነው፡፡
ከመጽሑፉ መግቢያ ቀጥሎ፣ “አንባቢያን ሆይ” በሚል ርዕስ የተቀመጠውን የደራሲውን መልዕክት በጥሞና ስመለከት፣ ብዙ ነገሮች ውስጤ ተመላለሱ፡- “አሁን ይህንን መጽሃፍ በምታነብበት ሠዓት በተለያዩ ችግሮችና ሁኔታዎች ውስጥ ትሆናለህ… እስቲ ምንም ነገር ከመወሰንህ በፊት ወይም የማማረር ህይወትህን ከመቀጠልህ በፊት ስለ ራሴ ልንገርህ። ይህንን መጽሃፍ በምጽፍበት ሰዓት በደረሰብኝ ጉዳት ከአንገቴ በታች ያለውን ሙሉ የሰውነቴን ክፍል መቆጣጠርም ሆነ ማዘዝ አልችልም፡፡ እጆቼ መያዝም ሆነ መጨበጥ አይችሉም። እግሮቼ መቆምም ሆነ መራመድ አይችሉም፡፡ ሽንትም ሆነ ሰገራ አልቆጣጠርም። የተኛሁበትን ጎን መቀየርም ሆነ መገላበጥ አልችልም። ማንኛውንም እንቅስቃሴ ከሰው ዕርዳታ ውጪ የማድረግ አቅም የለኝም… እንግዲያው አንተ ያለህበትንና እኔ ያለሁበትን ሁኔታ አስተያይ፡፡ ከኔ በባሰ ሁኔታ ውስጥ ነህ? አይደለህም! ብትሆን እንኳን ይህ ባንተ የደረሰው በማንም ላይ ያልደረሰ አዲስ ጉዳይ ካለመሆኑም በላይ ምንም አይነት መውጫ መንገድ የሌለው አይደለም፡፡”
ጉዳቱ የደረሰበት የመጽሃፉ ደራሲ፣ ወጣት የህግ ባለሙያ ነው፡፡ ዳግማዊ አሰፋ ይባላል፡፡ በምን ምክንያት ጉዳቱ እንደደረሰበትና የደረሰበትን ጉዳት ምንነት ስጠይቅ፣ በአካባቢው የነበሩ የሙያ መሰሎቼና የመጽሃፉ አከፋፋዮች ተያይተው፤ “እንዴት እስካሁን…?” በሚል ግርምታ ዝምታን መረጡ፡፡
ይበልጥ ግራ መጋባቴን ሲያስተውሉ ግን ታሪኩን ቀንጭበው ተረኩልኝ፡፡ ፊልም እንጂ እውነት የማይመስል መሳጭ ታሪክ ነው፡፡ ከአይረቤ የመንደር መሸታ ቤት ትርክቶች ያልወጡት ፊልመኞቻችን፣ ሊሰሩት የማይፈልጉት አይነት ፊልም፡፡
“እኔ የማውቀው ሰውዬው መሞቱን ነው” አልኩ፡፡
“አልሞተም በህይወት አለ!” ተባልኩ፡፡
እናም ራሴን እንዲህ አልኩት፤ “አንተ ሰው ሆይ! የምታውቀው የታሪኩን ከፊል ገጽታ ብቻ ነውና፣ ለሌላው የከፊል ገጽ ዕውቀት ይህ መጽሃፍ ያስፈልግሃል!” የአራተኛ አመት ተማሪ እያለሁ፣ አንድ መምህራችን ይህንኑ ጉዳይ አንስቶ፣ የህግ ባለሙያ መሆንን ከባድነት ማሳያ አድርጎ ሲናገር አስታውሳለሁ። ትኩረት ነፍጌው’ንጂ በወቅቱ ብዙ መነጋገሪያ ሆኖ እንደነበርም ይታወሰኛል… እነሆ የታሪካችን ተራኪ፣ ትርክቱን እንዲነግረኝ ጉጉቴና ሙሉ ፈቃዴ ሆነ፡፡
ህይወት ብርቅርቅታ!
የሰው ልጅ ህይወት ሁለት ገጽታዎች አሏት። በህይወት የመጀመሪያው ምዕራፍ ውስጥ ሰው፤ ከልደት እስከ ሞቱ በፈተና የተከበበና አንድም ለድልና ሽልማት፣ አንድም ለሌላ ዙር ፈተና የሚታጭበት ሲሆን የህይወት “ምዕራፍ ሁለት” ደግሞ የማሸነፍ ትግል የሚካሄድበትና ብቁ ሆኖ የተገኘው በህይወት “The fittest will survive (የጸና ይኖራል!)” መርህ መሰረት፣ ኑረቱን የሚቀጥልበት ነው፡፡
እንደ ስሙ “ዳግማዊ” ህይወትን ያገኘው ዳግማዊ አሰፋ፤ የመጽሃፉን ምዕራፍ አንድ የሚጀምረው ከመጽሃፍ ቅዱስ ውስጥ ያለ አንድ ሃይለ ቃል በመጥቀስና “ህይወት ብርቱ ሰልፍ ናት” በማለት ነው። ይህ የቅዱስ መጽሃፍ ቃል ደግሞ ህይወት በትግል የመሞላቷን እውነታ ተናጋሪ ነው፡፡ ሊያውም በህይወት ፈተና የጸኑቱ ብቻ የሚያሸንፉበት ብርቱ ትግል፡፡፡
ደራሲው የአስረኛ ክፍል ተማሪ ሳለ ነበር፣ በህግ የትምህርት ዘርፍ ለመዝለቅ ከቁርጥ ውሳኔ ላይ የደረሰው፡፡ ይህን ከመሰለ አይቀለበሴ ውሳኔ ላይ እንዲደርስ ያደረገውም፣ ከመኖሪያ ቤታቸው ከማይርቀው የሐዋሳ ከተማ ከፍተኛ ፍርድ ቤት አንድ ቀን እግር ጥሎት ሲገኝ የታዘበው የችሎት ሥነ-ሥርዓትና ድባብ ነበር፡፡ ያኔ እርሱ ለዚች ሃገር ጎበዝ ዳኛ ወይም ጎበዝ ጠበቃ መሆንን ሲያልም፣ ብዙዎች “ህግ በሌለበት ሃገር ለምን ህግ ትማራለህ? ቢቀርብህ ይሻላል!” ይሉት እንደነበርም ጽፏል፡፡
በእርግጥ ይህን አባባል ሳይሰማና ምናልባትም ራሱ ለራሱ ሳይለው የቀረ የህግ ተማሪ የሚኖር አይመስለኝም፡፡ ዳግማዊ ከህግ ትምህርት ቤት ከተመረቀ በኋላ በዚሁ በሚወደው የጥብቅና ሙያ ተሰማርቶ፣ ገና በያኔው የተማሪነትና የወጣትነት ዘመኑ ከሚያውቀው፣ ገና ያኔ ህግ የመማር ውሳኔውን ያጠነክርለት ከነበረው፣ “ይህ መጽሃፍ መታሰቢያነቱ ዓይኔ እያየ በግፍ ለተገደለው ለዳንኤል ዋለልኝ ይሁን” ላለለት የህይወት ዘመን ጓደኛው፣ ዳንኤል ዋለልኝ ጋር የጥብቅናን ስራ ጀመረ፡፡
በዚሁ የጥብቅና ስራ ላይ እያለ ነበር አገልግሎታቸውን የፈለገ አንድ ደንበኛ እነሱ ቢሮ የመጣው፡፡ ይህ ሰው ከአንድ ሌላ ሰው ላይ በሐዋሳ ከተማ የሚገኘውን “ብሉ ናይል” የተሰኘ ዕውቅ ሆቴል፣ በ35 ሚሊዮን ብር የገዛ ሰው ሲሆን የሚፈልገው የጥብቅና አገልግሎት ደግሞ ሆቴሉን የሸጠለት ግለሰብ፣ የመንግስትና የህዝብ ድርሻ የሆነውን 3 ሚሊዮን ብር ግብር አልከፍልም በማለቱ፣ ገዢው ከራሱ ከፍሎ ስለነበር፣ ይህንን በትርፍ የከፈለውን እላፊ ገንዘብ ሆቴሉን ከሸጠለት ሰው ማስመለስን ወይም መቀበልን የሚመለከት ነበር፡፡
ሆቴሉን የሸጠው ግለሰብ በአንጻሩ የመንግስትን ድርሻ ላለመክፈል ይደራደራቸው፣ ሆን ብለው እንዲሸነፉና ያቀረበላቸውን የ600 ሺህ ብር እጅ መንሻ እንዲወስዱ ያስፈራራቸውም ነበር፡፡ ሰውዬው ታምራት ሙሉ ይባላል፡፡ የመንግስትን ግብር በማጭበርበር ወንጀል ተከሶ በሌለበት የ12 ዓመት እስር የተፈረደበትና በፖሊስ እየተፈለገ ያለ ሰውም ነበር፡፡ ዳግማዊ መስከረም 27 ቀን 2007 ይህንን ሰው ቢሯቸው በር ላይ መኪና ሲያቆም አየው፡፡ “ትኩር ብሎ ላየው ሰው ግርማ ሞገሱ እንኳን ወንጀል የሚፈጽም ክፋት የሚያውቅም አይመስልም፡፡” ይለናል በትረካው-(ገጽ-103) ሰውዬው ግን የልቡን በልቡ የያዘ ነበር፡፡
በዚህ ዕለት ጠበቃውን ዳንኤልንና ረዳቱን ዳግማዊን ቢሮ ሳያገኝ የተመለሰው ይህ ሰው፤ በማግስቱ መስከረም 28 ንጋት ላይ መጣ፡፡ ዳንኤልና ዳግማዊ እየተነጋገሩ ነበር፤ ሰውየው ኮፍያ አድርጎና በጃኬት ተጀቡኖ ከቢሯቸው የተከሰተው፡፡ ሁሉም ነገር በፍጥነትና ቅጽበታዊ ሆኖ ተከናወነ… ክፍሉ በጥይት ባሩድ ሽታ ተሞላ፡፡ ሰውዬውም ከመጣበት ፍጥነት በፈጠነ ሁኔታ ከቢሮው ሮጦ ወጣ፡፡ ድንጋጤ፣ ደም፣ ስቃይ ያዘለ የጣር ጩኸት…. ከዚህ ዝብርቅርቅ መልስ የዳግማዊ አይኖች የዳንኤልን ጣርና ደም ተመለከቱ….. “ያዙት!.. ያዙት!” እያለ ሰውዬውን መከተል ሲጀምርም፣ ተባራሪው መውጫ በር ላይ ደርሶ ነበር፡፡ ወደ ዳግማዊ ዞረ፡፡ አነጣጠረና አንዲት ጥይት ተኮሰ፡፡ ዳግም በዚያች ቅጽበት የሆነውን እንዲህ ይተርከዋል፡-
“አንድ ነገር በቀጥታ አንገቴ ላይ መጥቶ ሲሰነቀርና መላው ሰውነቴን የመደንዘዝ ይሁን የመጎተት ስሜት ሲወረኝና ሲነዝረኝ ተሰማኝ፡፡ ራሴን መቆጣጠርም ሆነ ሚዛኔን መጠበቅ አልቻልኩም፡፡ ከአምስተኛው ደረጃ በቀጥታ ቁልቁል ወደ ታች በግንባሬ ወደቅኩ… አንድ ከውሃ ወፈር ያለ ጣዕሙን አሁን በቃል ለመግለጽ የሚከብደኝ ፈሳሽ ነገር ከግንባሬ ወርዶ አፌ ውስጥ ሲገባ ታወቀኝ፡፡ ደም፡፡ ደም ነው፡፡ በግንባሬ ስወድቅ የደረጃው ጠርዝ መሃል አናቴን ተርትሮት ስለነበር፣ ከዚያ የሚፈስ ደም ነው፡፡” (ገጽ-101)
ዳግም ሲቀጥል፤ የሁላችንንም ሃሳባዊ እውነት ነው የሚነግረን፡፡ “እንዲህ አይነት ነገር በእኔ ሕይወት ይሆናል ብዬ አስቤም አላውቅም፡፡ ጉዳት ስለደረሰባቸው ሰዎች ብዙ ጊዜ የሰማሁ ቢሆንም፣ ጉዳቶች በሌሎች እንጂ በእኔ የሚደርስ ክስተት ይሆናል ብዬ ገምቼ አላውቅም። ለካ ሰው የሚችለው ማለምና ማቀድ ብቻ ነው፡፡ ለካ ሰው ከቤቱ የሚወጣው ምን እንደሚገጥመው አንኳን ሳያውቅ ነው፡፡ ለካ ለስራ ብሎ ለሞት የሚወጣ ብዙ ሰው አለ፡፡” ይለናል፡፡
የዳግማዊ ፈተና በዚህ ብቻ አልተገደበም፡፡ ከዚህ ክስተት በኋላም ህይወቱ ከተደጋጋሚ አደጋዎች ተርፋለች፡፡ ሐዋሳ ሪፈራል ሆስፒታል እሱ የተኛበት ክፍል ውስጥ ያለው ኦክስጂን ፈንድቶ ለጥቂት ተርፏል። (ገጽ-107)
ስለ አምቡላንስ ጉዞ ፈታኝነት የነገረን ቁምነገር እንዳለ ሆኖ፣ ለተሻለ ህክምና በሚል በአምቡላንስ ከሐዋሳ ወደ አዲስ አበባ ኮሪያ ሆስፒታል ሲመጣ፣ “ኦክስጂን አለቀ!” መባልን የሰማበትን ቅጽበት ሲተርክልን፣ እኛ ከቁምነገር የማንጥፋቸውን የፈጣሪ ጸጋዎች እርሱ እንዲህ እያስተዋላቸው ነበር፡- “ሁሉም ሰው ደነገጠ፡፡ እኔ ደግሞ የበለጠ ደነገጥኩ፡፡… ሀገሩን ሁሉ የሞላው አየር ሆኖ፣ አብረውኝ ያሉትና ሌሎችም ሰዎች ሁሉ የማያሳስባቸው አየር ለእኔ ግን አለቀ፡፡ ምግብ አይደል እየተራብኩ አልጓዝም፡፡ መጠጥ አይደለ እየተጠማሁ መንገዱን አልቀጥልም፡፡ ያለቀው አየር ነው፡፡ ለካ ቀን ሲከፋ አየርም ያልቃል… የምንተነፍሰው አየር በክፍያ የሚገኝ ቢሆን ለአንድ ደቂቃ የምንከፍለው ክፍያ ስንት ይሆን?” (ገጽ-109)
ለምን?… ለምን አኔ ላይ?
ብርቱው ሰው፤ “ለምን እኔ?” በሚል ርዕስ ለመጽሃፉ የመጀመሪያ ምዕራፍ መግቢያነት የተጠቀመበትን ፈረንጃዊ ብሂል እዚህ ልድገመው፡- “When life puts you in tough situations, don’t say “Why me?” Just say “try me!” (ሕይወት በአስቸጋሪ ሁኔታ ውስጥ ስታስቀምጥህ፣ ‹ለምን እኔን?› ብለህ አትልፈስፈስ፡፡ ይልቁንም ‘እስኪ እንሞካከር!’ ብለህ ለትግል ተዘጋጅ‘ንጂ! እንደ ማለት”
ሃዘንና ደስታ እንደ ሌትና ቀን ተፈራራቂ  የህይወት ገጽታዎች ናቸው፡፡ ዳግማዊም አደጋው ከተከሰተበትና ህይወቱ እሱ ካሰበው በሌላ አቅጣጫ መቀጠሏን ሲያስተውል፣ ይህንኑ ጥያቄ መጠየቁ አልቀረም፡፡ “ብዙዎቻችን መልካም በሆንንና መልካም ባሰብን፣ ያላሰብነው መከራ ወደ ሕይወታችን ሲመጣና ሕይወታችን ላይ በጎ ያልሆነ ለውጥ ሲከሰት የምንጠይቀው የመጀመሪያው ጥያቄ ‘ለምን?’ ‘ለምን እኔ?’… የሚል ነው፡፡ በዚህ ዓለም ላይ “ለምን?” ብለን የምንጠይቅባቸው ነገር ግን በቂ ምላሽ የማናገኝባቸው ብዙ ጉዳዮች አሉ፡፡ ሞት፣ ህመም፣ ማጣት፣ መራብ፣ የተፈጥሮ አደጋና የመሳሰሉት ችግሮች ፈልገንም ይሁን ሳንፈልግ ፣ለምን፣ እንድንል ያደርጉናል፡፡ የምንኖርባት ዓለም እንቆቅልሽዋ ብዙ ነው፡፡” ይለናል፡፡ የዚህን ጥያቄ ተፈጥሯዊነትና ምክንያታዊነት በመግለጽም ከፈጣሪ ጋር የተሟገተባቸው ቀናት በርካታ እንደነበሩ እንዲህ ጽፎልናል፡-
“ከ12 ዓመቴ ጀምሮ በእግዚአብሄር ቤት ሳገለግል አድጊያለሁ፡፡ ይህንን አደጋ እስካስተናገድኩበት ጊዜ ድረስም አገልጋይ ነበርኩ፡፡ በዚህም ምክንያት ጤነኝነትና ከአደጋ የጸዳ ነጻ ሕይወትን እንደ መብት ይገባኛል ብዬ እቆጥር ነበር… እግዚአብሔር እንዴት እኔን አገልጋዩን ለዚህ አደጋ አሳልፎ ይሰጣል…? ብያለሁ፡፡  “አይገባኝምም” ብያለሁ፡፡  “አይገባህምም” ተብያለሁ፡፡ ይህንኑ ጥያቄ ደጋግሜ እያነሳሁም ለወራት ቆይቻለሁ፡፡” ይለናል፡፡
የዳግም የህይወት ፍልስፍና በጊዜ ሂደት ስለመቀየሩና ይህ የምሬት አመለካከት የተሳሳተ መሆኑን በመረዳት “ለምን እኔ እንዲህ ሆንኩ?” እያለ ባጉረመረመ ልክ “ለምን ሌላው እንዲህ አልሆነም?” እያለ እንደሆነ ተረድቷልና፣ ይህም የጠነነ ራስ ወዳድነት ሆኖበታል፡፡ እርሱ በሌሎች ላይ ሊፈርድ ተገቢ እንዳይደለ “ለምን እኔ?” ብሎ እንደተማረረና ችግርን ለሌሎች እንደተፈጠረ አድርጎ ማሰቡን ሁሉ በመተው “ለምን ሌላውስ?” ይሉትን መልካም ትምህርት ፈጣሪው ከልቦናው አሳደረለት፡፡ የትናንት ፈተናውም እነሆ ለዛሬ የከፍታው መተረኪያ ሆነ፡፡
“አምኖ መቀበል” ከባዱ ነገር!
ታዋቂው ኮሜዲያንና የሾው አዘጋጅ ቢል ኮዝቢ “changes; becoming the best you can be” በሚል ርዕስና dedicated with love to all በሚል የእንካችሁ ስጦታ ካሳተማት ቆየት ያለች አነስተኛ መጽሃፍ መግቢያ ላይ ያነበብኩት ምክር አዘል ጸሎት “Grant me the courage to change those things I can change; Grant me the patience to accept those things I can’t change; Grant me the wisdom to the difference!” ይላል፡፡ በእርግጥ አንዳንድ ነገሮችን መቀበል ፈታኝና ጊዜን የሚወስድ ቢሆንም አምኖ አለመቀበሉ ለውጥ የማያመጣልን ከሆነ ግን ሲያማርሩ መኖር ለሌላ የከፋ ምሬት ይዳርጋል፡፡
ዳግማዊም በተደጋጋሚ የሚነግረን ነገር መቀበሉ፣ የመናገርን ያህል ቀላል እንዳልሆነ ነው፡፡ “ነገሩ ሁሉ ግን በህልሜ ይመስለኛል፡፡ በመሃል ከእንቅልፌ የምነቃ እየመሰለኝ እጠብቃለሁ፡፡ አዎ እነቃለሁ! .... ህልም መሆን አለበት፡፡ አስቀያሚና መጥፎ ህልም። ነገር ግን ሁሉም ነገር እውነት ነው፡፡ ለመቀበል የሚከብድ እውነት፡፡ እስከዚህ ሰዓት ድረስ ጉዳት እንደደረሰብኝ ባውቅም የዚህን ያህል ይሆናል ብዬ ግን አልጠበቅኩም።” (ገጽ-108)
ዳግም ሁለት አይነት መቀበልን ተቀበሉ ይለናል። የመጀመሪያው አይነት “መቀበል” ለእኛው የተሻለ ጥንካሬ ሲባል ፈጣሪ በተለያየ የፈተና ትግል ውስጥ እንደሚፈትነንና እንደሚያሳልፈን አምኖ መቀበል ሲሆን ይህም ጭቃ ውስጥ እያለ ማንም ሊረግጠው እንኳ ይጸየፈው የነበረው ወርቅ በእሳት ተፈትኖ ያለፈ ቀን የሚኖረውን ልዩ የክብር ጌጥነት አይነት ነው፡፡ ሁለተኛው አይነት “መቀበል” ደግሞ “የምትወደውን ካላገኘህ ያገኘኸውን ውደድ!” ብለን ልንጠቀልለው የምንችለው አይነት መቀበል ነው፡፡ ችግርን መቀበል አለመቻል በዚያው ልክ ለችግሩ መፍትሄ መሻቱንም ይሰውርብናልና… ይህ ማለት ችግሩን አሜን ብሎ ተቀብሎ መቀመጥን ሳይሆን ለምን እኔ ላይ እያሉ ሲያማርሩ ከመኖር ይልቅ ችግሩ አብሮን እያለም ቢሆን እንዴት በደስታ ልንኖር እንደምንችል በማሰብ፣ ቀለል ያለ ህይወት የመኖር ጥበቡን መቀበል ነው፡፡ ከተጨማሪ ጉዳት ራሳችንን መጠበቁን መቀበል፡፡
ዳግም በህይወት አለ፡፡ መኖር ብቻም አይደለም፤ ለእኛም የተረፈ ሆነ ጥንካሬው፡፡ በየጽሁፎቹ መካከል እንዲህ ይለናል፤ “ሁሉም ሰው እንዲረዳልኝ የምፈልገው እውነት ግን ነገሮች ሁሉ ቀላል ነበሩ ማለቴ አይደለም፡፡
ሰው ጠያቂ ፍጥረት ነውና “ለምን!” ብለን የምናማረርባቸው፣ ለቅሶ የምናበዛባቸውና መፈጠራችንን የምንጠላባቸው ጊዜያቶች ይኖራሉ…..።” ለምን ተረፍኩ ብሎ ራሱን ሲጠይቅ፤ ነብሱ የምትነግረው ጻድቅ መሆኑን አይደለም፡፡ ድጋሚ ዕድል የተሰጠው የተፈጠረበትን ዓላማ ፈልጎ እንዲያገኝና ለዚያም እንዲተጋ ስለመሆኑ እንጂ፡፡ “መሞትን ሁሉም ሰው ይሞታል፡፡ እገሌ ይህን አድርጓል ተብሎ መሞት ግን መልካም ነው፡፡ ያለሁበት ሁኔታ እንዳለ ሆኖ እንደ ማንኛውም ሰው ስራ እሰራለሁ… የመከራን ቀን ጎንበስ ብሎ ማሳለፍ መልካም ነውና በዝምታ የአምላኬን ቀን እጠብቃለሁ፡፡” (ገጽ-92)
ትናንት ዛሬ እና ነገ!
ዳግም በመጽሃፉ ብርሃንን እንጂ ጨለማን አይሰብክም፣ ስለ ማበብና መለምለም እንጂ ስለ መጠውለግና መድረቅ አያወራም፡፡ የሰው ልጆችን በህይወት እስትንፋስ ዛሬ ላይ የሚያኖረን የትናንቱ ትዝታና የነገው ተስፋ ነውና ዳግምም በትውስታና በተስፋ የዛሬን እያንዳንዷን ቅጽበት እየኖራት ነውና እንዲህ ይለናል፡- “በአዲሱ ሕይወት ይህንን ተርኬያለሁ፡፡ ቀን አልፎ ይህ ጨለማ ሲገፈፍ ደግሞ የምተርከው ይኖረኛል፡፡” (ገጽ-92)
“ከትላንት ተማር፣ ዛሬን ኑር፣ ለነገ ደግሞ ተስፋ አድርግ” እንዲል አልበርት አንስታይን፤ ነገ የሚባል አዲስ ቀን እስካለ ድረስ አዲስ ተስፋ ሁሌም አለ። አዲስ ተስፋ እስካለ ደግሞ አዲስ ሕይወት መኖሩ አይቀሬ ነው፡፡ ዳግማዊም የትናንቱን ነገር በጸጋ እንድንቀበለውና የዛሬውን ችግርም በጽናት በመቆም እንድንጋፈጠው፣ ይህንንም አሳልፈን በእምነትና በተስፋ ነገን የተሻለ ይሆናል ብለን እንጠብቀው ይለናል፡፡ (ገጽ-87) በየጽሁፉ መካከልም “ሁሉም ሰው እንዲረዳልኝ የምፈልገው እውነት ግን ሁሉም ነገር ቀላል ነው እያልኩ እንዳልሆነ ነው፡፡ አምርሬ ያለቀስኩባቸው፣ መፈጠሬን የጠላሁባቸውና አንገቴን የደፋሁባቸው ቀናት ብዙ ናቸው፡፡… ከሞት አፋፍ ላመለጠ ሰው፤ ሌላው የህይወት ትግል አይከብደውም። በከባዱ የተማረ ሰው በቀላሉ አይሸነፍም፡፡” የሚል ነው ምክሩ፡፡
ስለ “አዲስ ሕይወት”
ኤርነስት ሄሚንግዌይ “ስለ ህይወት ለመጻፍ በቅድሚያ ያንን የምትጽፈውን ህይወት ልትኖረው ይገባል፡፡” ይላል፡፡ ዳግማዊ በመጽሃፉ መግቢያ ስር ይህንን መልዕክት ሲያስቀምጥ፣ ኖሮ ያለፈውን ህይወት እንደጻፈልን እየነገረን ነው፡፡ “ብዙዎቹ ለዓለም ጠቃሚ የሆኑ መጽሃፎች ተጽፈው የተገኙት ከስደተኞች፣ ከእስረኞችና ከችግረኞች በጠቅላላው ሕይወት በብርቱ ከፈተነቻቸውና ካስተማረቻቸው ሰዎች ነው። እነዚህን መጽሐፍት እጅግ ጠቃሚና ሕይወት ለዋጭ ያደረጋቸው ከዕውቀት ሳይሆን ከልብ መጻፋቸው ነው።”
እነማን ያንብቡት?!
የዚህ ጠያቂ ንዑስ ርዕስ መልስ፤ በመጽሐፏ መግቢያ ላይ እንዲህ ተመልሷል፡- “ከአዕምሮ የተጻፉ ጽሁፎች ዕውቀትን መሰረት ያደረጉ ሲሆኑ፣ ከልብ የተጻፉ ጽሁፎች እውነተኛ የሕይወት ልምድን ተመርኩዘው የሚጻፉ በመሆናቸው፣ በጎ ለውጥና ተጽዕኖ ይፈጥራሉ… ከዚህ ቀጥሎ ያለው ጽሁፍም በተለይ በተለይ በፈተና ሸለቆ ውስጥ ላሉ ሰዎች መንገድ የሚመራና አቅጣጫ የሚጠቁም ይሆናል ብዬ አምናለሁ፡፡”
በተስፋ መቁረጥ ድባብ ውስጥ ላሉና ለቀቢጸ-ተስፋ ፍጡን ተጠቂዎች ብቻ ሳይሆን ማንበብን የሚችሉ ሁሉ ቢያነብቡት ችግርን ለመጋፈጥ ይበረታሉ ብዬ አምናለሁ፡፡ በየትኛውም የህግ ሙያ ዘርፍ የተሰማሩ የህግ ባለሙያዎች ደግሞ ይህንን መጽሃፍ ማንበብ ብቻ ሳይሆን ደጋግመው ማንበብ አለባቸው ብዬም አምናለሁ፡፡ አምኜም ጋብዤአችኋለሁ፡፡
ሠላም

· “ኢሮብ ከሥርዓቱ ያልተጠቀመ ማህበረሰብ ነው”
 · የትግራይ ጠቅላይ ግዛት አካልና ህዝቡ ኢትዮጵያዊ ነው
 · በኤርትራውያን ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነት አለን
 · ህዝብ የኖረበት ቦታ፣ ከደሙና ህልውናው የተቆራኘ ነው
 · ማህበረሰቡ ከኢህአፓ ጋር ተያይዞ ብዙ ይነሳ ነበር


   ኢትዮጵያና ኤርትራ በ1990 ዓ.ም ከድንበር ጉዳይ ጋር በተያያዘ በ100ሺዎች የሚገመት ህይወት የጠፋበት አስከፊ ጦርነት ማድረጋቸው ሳያንስ የኢትዮጵያን ሉአላዊነት አደጋ ላይ የሚጥል ስምምነት በአልጀርስ መፈራረማቸውን ተከትሎ 20 ዓመታት በሁለቱም አገራት ላይ ውጥረት ሰፍኖ፣ ጦርነትም ሰላምም በሌለበት ድባብ ውስጥ መዝለቃቸው ይታወቃል፡፡ ባለፈው ሳምንት ግን አዲስ ነገር ተከሰተ የኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ባወጣው መግለጫ፤ ለሰላምና ለወንድማማችነት ሲባል የአልጀርሱን ስምምነት ያለምንም ቅድመ ሁኔታ እንደሚቀበለው መወሰኑን አስታወቀ፡፡ ውሳኔውን ተከትሎም በባድመ ድንበርና አካባቢው ላይ የሚገኘው የኢሮብ ማህበረሰብ፣ ውሳኔውን በመቃወም ሰላማዊ ሰልፍ አድርጓል፡፡ የአልጀርሱን ስምምነት መተግበር፤ “በአገርም ሆነ በማህበረሰቡ ህልውና ላይ አደጋን የጋረጠ ነው” ይላሉ ውሳኔውን የሚቃወሙ - የኢሮብ ነዋሪዎች፡፡
በአዲስ አበባ የሚኖሩ የማህበረሰቡ ተወላጅ ምሁራን፣ ባለሀብቶችና ግለሰቦችም ነገ ከጠዋቱ 3፡00 ጀምሮ ውሳኔውን በመቃወም በመዲናዋ ሰላማዊ ሰልፍ እንደሚያደርጉ አስታውቀዋል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፤ የሰልፉ አስተባባሪ ኮሚቴ አባል ከሆኑት ከአቶ ፀሐይዬ አለማ ካህሳይ ጋር ተከታዩን ቃለ ምልልስ አደርጋለች፡፡

    እስኪ ራሰዎትን በደንብ ያስተዋውቁን …
ትውልድና እድገቴ በምስራቅ ትግራይ፣ በኢሮብ ልዩ ወረዳ፣ መሀል ኢሮብ አሊቴና አካባቢ ነው፡፡ አንደኛና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴንም ያጠናቀቅኩት በትውልድ ቦታዬ ነው፡፡ ከዚያ ቀጥሎ ወደ አዲግራት ነው የሄድኩት፡፡ ከአዲግራት አዲስ አበባ መጣሁ፡፡ ከዚያም ለትምህርት ወደ ውጭ ሄጄ ነበር፡፡
እስቲ ስለ ማህበረሰቡ አኗኗር፣ ባህል፣ ታሪክ እንዲሁም ከሌሎች ማህበረሰቦች ጋር ስላለው መስተጋብር ያጫውቱኝ …
እዛ አካባቢ ያለው የኢሮብ ማህበረሰብ እንደ ሌላው የኢትዮጵያ ማህበረሰብ ተከባብሮና ተሳስቦ የሚኖር ነው፡፡ የራሱን ማንነት የገነባና በኢትዮጵያ ህገ መንግስት እውቅና ያለው ብሄረሰብ ነው። ቁጥሩ ላለፉት 20 ዓመታት 30 ሺህ እየተባለ ነው የቆየው፡፡ አንዳንዴ እንደውም የህዝቡ ቁጥር እንዴት አይጨምርም የሚባል ጥያቄ ይነሳል፤ ግን 30 ሺህ ላይ ነው የቆመው፡፡ እንደኔ ማህበረሰቡ ትኩረት ተሰጥቶት በአግባቡ ባለመቆጠሩ እንጂ ከዚያም በላይ ይሆናል። ባህሉን በተመለከተ ከላይ ከትግሬዎች፣ ከታች ደግሞ ከሙስሊሞች እንዲሁም ከኤርትራዊያን ጋርም የሚወራረስ ባህል አለው፡፡ ሆኖም የራሱን ኢሮብኛ ቋንቋ የሚናገር ሲሆን የዘር ግንዱ ከሙስሊሞችም ሰናአፌ ከሚገኙ ኤርትራዊያንም ከላይ ደግሞ ከአዲግራትና ከዛላንበሳ ህዝቦች ጋር የተዋለደ ነው፡፡ ቋንቋው ከአፋር ሳሆ ጋር ይቀራረባል፡፡ ህዝቡ እውነትን አክባሪ ነው፡፡ ነገሮችን እያመዛዘነ፣ የወደፊቱን አርቆ እያስተዋለ፣ የቆየ ሢሆን በአጠቃላይ ብልህ ማህበረሰብ ነው፡፡
ብዙ ሰው ኢሮብን ማወቅ የጀመረው ከአልጀርሱ ስምምነት በኋላ ይመስለኛል፡፡ ከዚያ በፊት ብዙም ሲነሳ ሰምቼ አላውቅም፡፡ ተሳስቻለሁ?
 ይሄ ለእኔ ትልቅ ጥያቄ ነው፡፡ ማህበረሰቡ ብዙ አይነገርለትም፤ አልተነገረለትም፡፡ እንዲነገርለትም አይፈለግም፤ በተለይ በዚህ ስርዓት፡፡ እንደውም የኢሮብ ማንነት በ60ዎቹ የፖለቲካ እንቅስቃሴ፣ በተለይ ከኢህአፓ ጋር ተያይዞ ብዙ ይነሳ ነበር፡፡ በተሳትፎውም ደረጃ በተለይ ኢህአፓ ውስጥ ከፍተኛ ነበር፡፡ በአመራር ደረጃ እንኳን ብዙ የኢሮብ ልጆች ነበሩ፡፡ አሲምባ ራሱ የኢህአፓ ዋና ማዕከል ከነበሩት ቦታዎች አንዱ ነው፡፡ አሲምባ ኢሮብ ውስጥ ነው የሚገኘው፡፡ እንግዲህ በዛን ወቅት የኢህአፓ ዋና ማዕከላት ከነበሩት ውስጥ አሲምባ፣ ሰንገዳ፣ ኢንጋልና ካልሃሳይ የተባሉት ዋና የኢህአፓ የጦር ካምፖች ነበሩ፡፡ ከዚህ ጎን ለጎን የህውሓት ታጋዮችም ወራአትሌና አይጋ በሚባል ስፍራ ላይ እንቅስቃሴ ያደርጉ ነበር፡፡ ይህ አካባቢ እንደውም ዴሞክራሲን ቀድሞ የተለማመደና ተግባራዊ ያደረገ አካባቢ ነው፡፡
እንዴት? እስኪ ያብራሩት …
በዛን ወቅት የህውሓት ታጋዮች ይመጣሉ፤ አላማቸውን ያስተዋውቃሉ፡፡ ኢህአፓዎችም ይመጣሉ፤ አላማቸውን በግልፅ ያስተዋውቃሉ፡፡ ይህን ተራ በተራ እንሰማለን፡፡ በገበያ፣ በቀብርና በተለያዩ ህዝብ በተሰበሰበባቸው አካባቢዎች እየመጡ፣ አላማቸውን ሲያስተዋውቁ፣ ህዝቡ ያለ ተፅዕኖ ይሰማል። የሚፈልገውን ሃሳብ ይወስዳል፣ የማይፈልገውን ይተዋል፡፡ ለምሳሌ በወቅቱ የኢሮብ ትልልቅ ሰዎች “ኢህአፓዎች ሃይማኖት የላቸውም፤ እግዚአብሔርን አያውቁም” እያሉ ሲወቅሷቸውና ሲጠሏቸው ልጅም ብሆን አስታውሳለሁ፡፡ ኢሮቦች ከኢህአፓ የሚጠሉት እምነት የለውም በሚል ብቻ ነው፡፡ በወቅቱ ስለ ማርክሲዝም ሌኒንዝም እንዲሁም ስለ ሌሎች ርዕዮተ ዓለማት ብዙ ማወቅና መገንዘብ ችለናል፡፡ ስለ አብዮት በዘፈንም በግጥምም፣ ከዚህኛውም ከዚያኛውም ወገን ስንሰማ ነው ያደግነው፡፡ በአጠቃላይ የ60ዎቹ የፖለቲካ እንቅስቃሴ ፓርቲዎች፤ ኢሮብን እንደ ስደተኛ ካምፕ ተጠቅመውባታል፡፡ ህዝብ ሁሉንም ተቀብሏል። በተለይ ኢህአፓን በደንብ ተቀብሏል፡፡ ህውሃትንም የሚቀበሉ ነበሩ፡፡ ሌላው አገር በቀል የግጭት አፈታትን በራሱ ያዳበረና የተገበረ ማህበረሰብም ነው፡፡ ለምሳሌ ህውሓትና ኢህአፓዎች እንዳይጣሉ፣ ልዩ ልዩ ዘዴዎችን ይጠቀም ነበር፡፡ የኢህአፓ አባሎች ኢሮብ ወይም አንድ ቤት ውስጥ ካሉና ህውሓቶች ድንገት ሲመጡ ካዩ፣ ኢህአፓዎችን ቀስ አድርገው፣ በጓሮ በር አስወጥተው፣ በመሸኘት፣ ግጭትና ተኩስ እንዳይከፍቱ ያደርጉ ነበር፡፡
ከካቶሊክ ሚሲዮናዊያን መግባት ጋር በተያያዘ፣ በአገራችን ዘመናዊ ትምህርት በመጀመር ኢሮብ ፈር ቀዳጅ እንደሆነ ይነገራል፡፡ ምን ያህል እውነት ነው?
በጣም ጥሩ! በኢሮብ ዘመናዊ ትምህርት የተጀመረው በ1835 ዓ.ም እንደሆነ ታሪክ ይነግረናል፡፡ አሊቴና ያለው ቤተ መፃሕፍት በጣም ጥንታዊ ነው፡፡ የሙዚቃ መሳሪያዎችም ነበሩት፣ የጥንት ስነ ፅሁፎችም ያሉበት አካባቢ ነው፡፡ አንድን ትምህርት ዘመናዊ የሚያደርገውን ጂኦግራፊ፣ ቋንቋ፣ ታሪክ ይማሩ ነበረ፡፡ ቋንቋ የውጭም የአገር ውስጥም ተምረው እንደነበር ይነገራል፡፡ ለምሳሌ ላቲን ይማሩ ነበር፡፡ አማርኛ በደንብ ይማሩና ይናገራሉ፡፡ እንግሊዝኛም እንዲሁ፡፡ የግዕዝም የሂሳብም ትምህርት ይሰጥ ነበር፡፡ በኢትዮጵያ ደረጃ ስኮላርሺፕ አግኝተው ወደ ውጭ የሄዱት ከዚያ ት/ቤት ነው፡፡
ቀደም ሲል “በዚህ ስርዓት ስለ ኢሮብ ብዙ አይነገርም፤ እንዲነገርም አይፈለግም” … ያሉኝ ለምንድን ነው?
ባለፉት 20 ዓመታት በተነሳው የድንበር ጦርነት አካባቢው በጣም ጉዳት የደረሰበት ነው፡፡ ብዙ ጦር የሰፈረበት፣ ለብዙ መፈናቀል የተዳረገና ከኢሮብ ወጥቶ ዛላንበሳ አዲግራትና በየበረሃው ለመኖር የተገደደ ማህበረሰብ ነው፡፡ በዚህ ምክንያት ህልውናው አደጋ ላይ ወድቆ ትኩረት ስለተነፈገው አይነሳም፡፡ መሰረተ ልማት አልተስፋፋለትም፡፡ ሌላው ቀርቶ እንደ ልዩ ወረዳነቱ፣ አስፓልት እንኳን የለውም፡፡ መንግስት ባወጣው ስትራቴጂ፤ ወረዳዎችን ከዋና ዋና ከተሞች ጋር የማገናኘት አሰራር አለው፡፡ ይህ ማህበረሰብ ግን ምንም አይነት ጠቀሜታ ከስርዓቱ ከስርዓቱ አላገኘም፡፡ መንገድ ከሌለ መሰረተ ልማት ከሌለ፣ ወደዚያ የሚሄድ ኢንቨስትመንት ቱሪዝምና መሰል ነገር አይኖርም፡፡ መሰረተ ልማት አልተስፋፋም ማለት ደግሞ አካባቢው እንዲነሳ አይፈለግም ማለት ነው፡፡ ሌላ ምንም ትርጉም የለውም፡፡ የመጠጥ ውሃ የለም፤ ውሃ ከታች ቀድቶ ለመመለስ ቀጥ ያለ ዳገት፣ 40 እና 45 ደቂቃ መውጣት ግድ የሚልበት አካባቢ ነው፡፡
ታዲያ ማህበረሰቡ የሚያስታውሰው ከሌለ፣ ራሱን በራሱ ለማስተዋወቅ መጣር የለበትም? የአካባቢው ተወላጅ ባለሀብቶችስ አካባቢያቸውን አይጎበኙም? አያስተዋውቁም? ማለት ነው?
እንደነገርኩሽ፤ ህዝቡ በትግል፣ ራስን በማሸነፍ ሩጫ የተጠመደ ነው፡፡ ተምሮ ለመለወጥ፣ በንግድ ለማደግ … ብቻ ራስን የማዳን ስራ ላይ የተጠመደ ማህበረሰብ ነው፡፡ ጉዳዩ የህልውና (የሰርቫይቫል) ነው፡፡ ኑሮውን ለማሸነፍ ከመጣር አልፎ ራሱን ፕሮሞት ማድረግና ሌሎች እንቅስቃሴዎች ለማድረግ አቅሙ የተገደበ ነው፡፡ እንዳልኩሽ የመሰረተ ልማቱ ነገር ባለመሟላቱ፣ ኢንቨስት የማድረጉ ነገር ብዙ ትኩረት አይስብም፡፡ ተወላጅ ባለሀብቶችም ፀጥታው አስተማማኝ ባልሆነ አካባቢ ምን ሊያደርጉ ይችላሉ? ብቻ ብዙ ጭንቅና ችግር የተሸከመ ማህበረሰብ ነው። ከስርዓቱ ምንም ያልተጠቀመ ማህበረሰብ (አካባቢ) ነው፡፡
የኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ፣ የአልጀርሱ ስምምነትን በተመለከተ ያስተላለፈው ውሳኔን በተመለከተ ምን ይላሉ?
ይሄ ከባድና የማልስማማበት ውሳኔ ነው፡፡ አንደኛ፤ ባድመን አሳልፈን ከሰጠን በኋላ ኤርትራ ሰላም ትሰጠናለች ወይ? የሚለው ጥያቄ፤ የምንጊዜም ጥያቄ ነው፡፡ ሁለተኛ፤ አንድን አገር ቆርሶ መስጠት፣ ከሉአላዊነት አኳያስ እንዴት ነው የሚታየው፡፡ በነገራችን ላይ ኤርትራ የ“ዱርዬ” የ“ወመኔ” ስራ ሰርታ ነው የወረረችን፤ ከእነ ቅጣቷ መሬታችንን ለራሳችን ማድረግ ሲገባን፣ ለወረረን አገር መሬት መስጠት፣ ከስጋዬ ተቆርሶ እንደተሰጠ ነው የምቆጥረው፡፡ በጣም ያምማል፡፡ በዚህ ቦታ ላይ የመላው ኢትዮጵያዊ አጥንት ተከስክሷል፤ ደም ፈስሳል፡፡ 70 ሺህና ከዚያ በላይ ወገን ገብረናል፡፡ የእነዚህ አርበኞች ውለታስ ይሄ ነው? እኔ በበኩሌ ታሪካዊ ክህደት ነው የምለው፡፡ በዚያ ወረራ 152 የኢሮብ ሰዎች ታፍነው ወደ ኤርትራ ከሄዱ በኋላ የገቡበት አይታወቅም፡፡
የአልጀርሱ ስምምነት ቢተገበር ትልቁ አደጋ የሚሉት ምንድነው?
የኢሮብ ህዝብ በተለያዩ ችግሮች የተበታተነና የተመናመነ ህዝብ ነው፡፡ ውሳኔው ደግሞ ህዝቡን ለሁለት ይከፍለዋል፡፡ ግማሽ ኤርትራ፣ ግማሽ ኢትዮጵያ፡፡ ይሄ ምን ማለት ነው …  እንደ ኢሮብ ህዝቡን ለሁለት ከፍሎ፣ የመነጣጠልና ጭራሽ ኢሮብን ከምድረ ገፅ ለማጥፋት የተቃጣ ነው፡፡ በዘመነ መሳፍንት፣ በደርግም ጊዜ፣ በኃይለ ሥላሴ ጊዜም ሆነ በፌዴሬሽን ጊዜ ኤርትራ ነበረች፡፡ ይሄ ሁሉ ሲሆን፣ ታሪክ ሲሄድና ሲመጣ፣ የኢሮብ ምድር የኤርትራ ሆኖ አያውቅም፡፡ የትግራይ ጠቅላይ ግዛት፣ አካልና ህዝቡም ኢትዮጵያዊ ነው፡፡ ሌላው ቀርቶ ኤርትራ የኢትዮጵያ በነበረችበት ጊዜ ኢሮብ የትግራይ አካል ሆኖ ነው የኖረው፡፡ የኢሮብ ህዝብ የህልውና ጉዳይ በአሁኑ ወቅት ምርጫ ውስጥ የሚገባ አይደለም፡፡ ለምርጫም የሚቀርብ አይደለም። ኢሮብ ኢትዮጵያ ነው፤ ህዝቡም ኢትዮጵያዊ ነው፡፡ የምርጫ ጉዳይ ቢሆን እኮ ህዝቡ ወደ ኤርትራ ቢሄድ የተሻለ ጥቅም ሊያገኝ ይችላል፡፡
ከምን አንፃር ነው ተጠቃሚ ሊሆን የሚችለው?
ከባህር ወደብም በይው ከግብይትና መሰል ጉዳዮች አንፃር ተጠቃሚ ሊሆን ይችላል፤ ግን ህዝቡ አገሩን ማንነቱን ማጣት የማይፈልግ በመሆኑ፣ የኢሮብ ጉዳይ የምርጫ ሳይሆን የህልውና ጉዳይ ነው፡፡ የሰላምን አስፈላጊነት ካነሳን፣ መሬቱን የሰጠነው ሰላም ለማስፈን ነው የሚለው ምክንያት አይዋጥልኝም፡፡ የሰላምን አስፈላጊነት ከኢሮብ ህዝብ በላይ የሚያውቅ አለ ብዬ አላምንም፡፡ የኢትዮጵያና የኤርትራ ህዝብ ከጦርነቱ በፊት በፍፁም ፍቅር፣ በፍፁም መከባበርና ሰላም የኖረ ህዝብ ነው፡፡ እኛም ኢሮቦች፤ በኤርትራዊያን ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነት ያለን ህዝብ ነን፡፡ እኛም እንዲሁ እንወዳቸዋለን፡፡
አንድ ነገር ልንገርሽ በኤርትራ እዛ ማዶ አንድ ኤርትራዊ ሲሞት፣ የኢሮብ ህዝብ ወዲህ ማዶ ትልቅ ተራራ ላይ ነጭ ለብሶ ይቆማል፡፡ ነጭ የሚለብሰው ለባለለቅሶው ጎልቶ እንዲታይ ነው፡፡ እናም የቀብር ሥርዓቱ እስኪፈፀም ይቆማል፡፡ ሲያልቅ ወደ ቤቱ ይመለሳል፡፡ ይሄ ማለት ቀብር ላይ ተገኝቷል፤ ቀብሯል ማለት ነው፤ መሻገርና መሄድ አይችልማ፡፡ እነሱም ይህንን ያደርጋሉ፤ እስኪ ምን ያህል የምናሳዝን፣ ሁለት ህዝቦች እንደሆንን ተመልከቺ …
ምንም እንኳን ወራሪዋ ኤርትራ ብትሆንም በመጨረሻ መሬቱ ግን የተወሰነው ለኤርትራ ነው ተብሏል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስትም የተፈራረመው ይሄንኑ ነው፤ አይደለም እንዴ?
ባድመን ለመስጠት አይደለም የተስማሙት፤ አለም በሚፈርደው እንስማማለን ነው ያሉት፤ ምክንያቱም ኢትዮጵያን የሚያክል ትልቅ አገር ተስማሙ ሲባል አልስማማም አይባልም፡፡
እና በእርስዎ አመለካከት ምን ተወስኖ ነው ኢትዮጵያ የተስማማችው ይላሉ?
ዓለም ይሄን የመሰለ አስቀያሚ ፍርድ ይወሰናል ብለው ላያስቡ ይችላሉ፡፡
እንዴት አይገምቱም? ጂኢፖለቲክሱን ያውቁታል … ሁኔታውን ያውቁታል … የጦርነቱን መጀመሪያና መጨረሻ ያውቁታል … ሌላው ቀርቶ ዓለም ምን ሊወስን እንደሚችል መገመታቸው አይቀርም…?
ለማንኛውም እኔ እያልኩ ያልኩት “እናደራድራችሁ” ሲሏቸው፤ “እሺ አደራድሩን” አሉ። “እንደምትደራደሩ እና በውሳኔው እንደምትስማሙ ፈርሙ” ተባሉ፡፡ ይሄ ውጤት እንደሚመጣ ቀድመው ላያውቁ ይችላሉ ነው ያልኩት፡፡ በኋላ ውሳኔው ተወሰነ፡፡ ውሳኔው ከተወሰነ በኋላ የኢትዮጵያ መልስ ምን ነበር፡፡ ውሳኔውን በመርህ ደረጃ እንቀበለዋለን ግን ብዙ ችግር አለው፤ አምስት የመፍትሄ ሀሳብ እንሰጣለን፤ በዛ መሰረት ይፈፀም ተባለ፡፡
አምስቱ የመፍትሄ ሀሳቦች ምንድናቸው?
ከአምስቱ አንዱን ነው የማውቀው፡፡ አንዱ ምን መሰለሽ … ውሳኔውን መሬት ላይ አውርደን እንየው ተባለ፤ ምክንያቱም ውሳኔው ቤቶችን ሳይቀር ለሁለት የከፈለ፣ አንድን ህዝብ ለሁለት የከፈለ፤ ነገር ግን ጠረጴዛ ላይ ብቻ የተወሰነ ነው፤ ስለዚህ መሬት ላይ ይውረድ ተባለ፡፡ መሆን ያለበትም ይሄ ነው፡፡ በነገራችን ላይ ይሄ አገር የአፍሪካ ህብረት መቀመጫ የሆነ ትልቅ አገር ነው፡፡ አልደራደርም አልስማማም ሊል አይችልም። ውሳኔው መሬት ላይ ሲወርድ ግን የሚመጣው ህዝቡ ጋ ነው፡፡
ህዝቡ ደግሞ የትኛው ድንጋይ የኢትዮጵያ፣ የትኛው ዛፍ የኤርትራ መሆኑን ጠንቅቆ ያውቃል፡፡ የአሁኑን ውሳኔ ራሳቸው ኤርትራዊያኑ አይቀበሉትም። ድንበሩ ከአይጋ እንደሆነ፣ ድንበሩ ከእንዳልጌዳ በታች በኩል እንደሆነ ያውቃሉ፡፡ ዕድሉ ቢሰጠው ህዝቡ ራሱ በሰላም የሚጨርሰው ነገር ነው፡፡ ስለዚህ ውሳኔውን እንቃወማለን! ችግሩ አሁን በወሰኑትም፣ በፊት በፈረሙትም የተፈጠረ ችግር ነው፡፡ ነገር ግን በፊት ተፈርሟል ተብሎ፣ አሁን በእጃችን ያለን ነገር አሳልፎ መስጠት ስህተት ነው፡፡ በነገራችን ላይ አሁን የኢሮብ ህዝብን ለሁለት የከፈለው ውሳኔ፣ የተባበሩት መንግስታት በማይኖሪቲ ራይት ስር ያለውን ድንጋጌ በእጅጉ የሚፃረር ነው፡፡ አንድ ህዝብ ለሁለት አይከፈልም፡፡
በነገራችን ላይ በአንድ ወቅት አንድ አገር የነበሩ፣ ለሁለት ሲከፈሉ አንድ የባህር በር ሲጠቀሙ ከነበረ ሁለቱም የባህር በሩን የመጠቀም መብት አላቸው የሚል ይመስለኛል … ዓለም አቀፍ ህጉ?
ትክክል ነው፡፡ ኢትዮጵያ እስካሁን ይሄን የባህር በር የመጠቀም መብት አላት፡፡ ለምን መብታችንን አልተጠቀምንም ብዬ ራሴን ስጠይቅ፣ መልሱን ማግኘት ይከብደኛል፡፡ ግራ ይገባኛል፡፡ ሌላው ኢሮብን ትንሽ መሬት ነው፣ ቢሄድና ሰላም ቢመጣ ምንም አይደለም ብሎ የሚያስብ መንግስትም ሆነ ግለሰብ ካለ ስህተት ነው፤ የትንንሽ መሬት ድምር ውጤት ነው፤ አገር የሚባለው፡፡ ህዝብ ደግሞ “እኔ ኢትዮጵያዊ ነኝ” እያለ መገፋት የለበትም፤ “መሬቱ ይሂድ፤ አንተ ና” አይባልም፡፡ ህዝቡ የኖረበት ቦታ ከደሙና ከህልውናው ጋር የተቆራኘ ነው፡፡
ይህንኑ ውሳኔ በመቃወም የኢሮብ ህዝብ በቅርቡ ሰላማዊ ሰልፍ ወጥቶ ቅሬታውን ገልጿል፡፡ እናንተም አዲስ አበባ የምትኖሩ የአካባቢው ተወላጆች፤ ነገ በመዲናዋ ላይ ሰላማዊ ሰልፍ ለማድረግ አቅዳችኋል። ተቃውሞው ውጤት ያመጣል ብላችሁ ታስባላችሁ?
የማይቀበለስ ውሳኔ አለ ብዬ አላምንም፡፡ ሰው ነው ውሳኔውን የሚወስነው፡፡ አንድ እውነታ ደግሞ የትኛውንም ውሳኔ ሊቀለብስ ይገባል፡፡ እኛም በዚህ እምነታችን ቅሬታችንን ለማሰማት አንቦዝንም፡፡ ኢሮቦች ብቻቸውን ሰልፍ ስለወጡ ግን የሚቀለበስ አይደለም፤ የመላው ኢትዮጵያ የቤት ሥራ መሆን አለበት ብዬ አምናለሁ፤ ምክንያቱም የመድብለ ፓርቲ ሥርዓትና ሚዲያ ያለበት አገር ነው፡፡ ይህ ሆኖ እያለ ህዝብን ማዕከል ያላደረገ ውሳኔ አዎንታዊ ሰላም አያመጣም፡፡ ይሄ ሌላ ቦታ፣ ሌላ ቦንብ የሚቀብር ውሳኔ ነው፡፡ ስለዚህ በእጅጉ ሊታሰብበት ይገባል፡፡ ውሳኔው የፍትህና እኩልነትን የተላበሰ መሆን አለበት፡፡

 ለመሆኑ ኢትዮጵያዊነት ምንድነው? እኔ እንደተረዳሁት፣ ኢትዮጵያዊነት ከአስራ ሶስት አምዶች የተሰራ የጥበብ ቤት ነው፡፡
ኢትዮጵያዊነት ማስተዋልና አርቆ አሳቢነት ነው
ብልሀተኛ ምርጫ ከማድረግ አንስቶ ለምንንና እንዴትን እስከ ማወቅ ይሄዳል፡፡ ሀበሻ ያለውን የትክክለኛነት ፍቅር፣ ልበ ሰፊነት፤ ለመለኛነትና ነገር አዋቂነት ያለው አድናቆት፣ ለትኩረትና አንክሮ ተዘክሮ ያለው ግዴታ እና የነግ በኔ ፍቅሩ ይህን አስተዋይነቱንና አርቆ አሳቢነቱን የሚመሰክሩለት ናቸው፡፡
ኢትዮጵያዊነት በትዕግስት የታሸ ጀግንነት ነው
ጨዋነቱ ወይም ያልነኩትን አለመንካቱ፣ አገር ወዳድነቱ፣ ለነፃነት ያለው ፍቅርና ታሪክ በደማቁ የፃፈለት የጀግንነት ገድሉ፣ የሞት ፍርሀትን መፀየፉና ታሪክ ሰሪነቱ የዚህ ምስክሮች ናቸው - ለሀበሻ።    
ኢትዮጵያዊነት ከግላዊነት የራቀ ማህበራዊ ፍቅር ወይም ከራስ ወዳድነት የተለየ የወገን ተቆርቋሪነት ነው
በህብረተሰቡ፣ መብትን ሳያጣጥሉ /በፈቃድ/ መብትን ሰውቶ ማገልገል ይበረታታል፣ የምንለው ለዚህ ነው፡፡ ግብዝነት የሌለበት ወንድማማችነቱ፣ የማስተዋል ደግነቱና እንግዳ ተቀባይነቱ፣ የመቻቻል ትብብሩና አስታራቂነቱ፣ በሰው አክባሪነትና በጓደኛ መካሪነት ጭምር የሚገለጡት ብፅዕናዎቹ ለማህበራዊ ፍቅሩ ምስክሮች ናቸው፡፡
ኢትዮጵያዊነት ርኩሰት የሌለበት ቅድስና ነው
ቁጥብነትና ትዕምርትን /ጨዋነትና ግብረገብነትን/ መከተሉ፣ ለቃል መታመንንና አደራ ጠባቂነትን ማንገሱ፣ ቀናነትንና የልብ ንጽህናን ማክበሩ፣ ቁምነገረኛነትን ማበረታታቱ ለዚህ ማስረጃ ሆነው የሚቀርቡ ናቸው፡፡
ኢትዮጵያዊነት ትህትና ያልተለየው፤ የክብር መንፈስ ወይም የክብር ፀጋ ያልተለየው የትህትና መንፈስ ነው
ክብርን መጠበቅና ሰው አክባሪነት አብረው ያሉበት፤ ኩሩነትና ጭምትነት የተዳበሉበት፣ ትምክህተ እግዚአብሔርና ፈሪሀ እግዚአብሔር ያልተነጣጠሉበት ህይወት ነው፣ በህብረተሰቡ የሚንፀባረቀው፡፡ ይህን ኖሎታዊ የህሊና አያያዝ ልንለው እንችላለን፡፡ ይህም በከፍታ ጊዜ ዝቅታን፣ በዝቅታ ጊዜ ከፍታን እያሰቡ ሚዛን መጠበቅ ማለት ነው፡፡  
ኢትዮጵያዊነት የሰከነ ስሜት፣ የነቃ ህሊና ነው
ስሜቱ የሰከነ፣ የሰከነ እርጎ ተብሎ ይመሰገናል። መረጋጋት ይወደዳል፡፡ ራስን በማወቅ መደላደል፣ ደግሞም ለጉዳይ መንቃት ይደገፋል፡፡
ኢትዮጵያዊነት እንደ እባብ ልባምነት፣ እንደ ርግብ የዋህነት ነው
ልባምነት፤ ጠንቃቃነትና ራስን መጠበቅ ማለት ነው። የሚፈለገው አጉል ብልጣብልጥነትና ሞኛሞኝነት ሳይሆን ለብልጦች ብልጥ፣ ለገሮች ገር መሆን ነው፡፡
ኢትዮጵያዊነት የምንዳቤ ታጋይነትና የእድገት ርዕዮት ነው
እድገትን መመኘትና እድልን የማስፋት መሻት፣ መንፈስ ብርቱ መሆን ነው፡፡ የሚያስመሰግነው ከችግር ጋር መታገል፣ ትጋትና ስራ ወዳድነት፣ ባለጉዳይነትና ባለሙያነት ነው፡፡
ኢትዮጵያዊነት ሥርዓታዊነትና አግባባዊነት ነው
ደንቡ ምንድነው? የሚለውን ሀበሻ አስቀድሞ ማወቅ የሚሻው ነገር ነው፡፡ ጋጠ ወጥነትና ህገ - ወጥነት ውጉዝ ነው፡፡ ሁሉን እንደ አግባቡ እንደ ደንቡ መሥራትና ባህልና ወግ አክባሪነት የተመሰገነ ነው፡፡
ኢትዮጵያዊነት ተራዳይነት ያልተለየው የእናት አባት ፍቅር ነው
እናትና አባትህን አክብር የሚለው ቃል በሰፊው የሚነገር ምክር ነው፡፡ ለእናት ያለ ልዩ ፍቅር፣ አባትን የመምሰል አኩሪነት፣ ጧሪ ቀባሪነት፣ አደራ ጠባቂነት ተፈላጊና የሚያስመሰግን ነገር ሆኖ እናገኘዋለን - በሀበሻ፡፡
ኢትዮጵያዊነት የግብረ ገብ ሥነ - ልቦና አንድነትና የአፋዊ ሥርዓት ህብር ነው
የጋራ ባህላችን በአንድ ቃል ከተነገረ ግብረ ገባዊ የጋራ ባህል ነው /ነገር ግን ብቸኛው አይደለም/ ልዩ ልዩ ብሔረሰቦች እንደ ጭፈራ ባሉት አፋዊ ስርአቶችና ስነ - ስርዓቶች ሊለያዩ ቢችሉም፣ በግብረ ገብ ስነ ልቦና አንድ ናቸው፡፡ ወይም ደራሲ አያልነህ ሙላት እንዳሉት፣ የኢትዮጵያ ህዝብና ማህበረሰቦች በአንድ መደብ የበቀሉ አበቦች ናቸው፡፡
 ኢትዮጵያዊነት ችኮ ድርቅና የራቀው የለምለም ጽናት ነው
ትልቅ የሚያስብለው መጀመር ሳይሆን መፈጸምና በጽናት ማስቀጠል መቻል ነው፡፡ ምክር ሰሚነትም የልባምነትና የቁም ነገረኛነት ምልክት ነው፡፡
ኢትዮጵያዊነት ሃይማኖተኛነትና እጅን ወደ እግዚአብሔር መዘርጋት ነው
ይህም ግልጽ ሆኖ የሚታይ ነው፡፡ ህዝቡ ሃይማኖተኛ ነው፡፡ “ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች፡፡” ሌሎችንም ማስረጃዎች ከምሳሌያዊና ፈሊጣዊ ንግግሮች አውጥተን ማየት እንችላለን፡፡

 ከዕለታት አንድ ቀን፣ አንድ አሮጌ ውሻ፤ ከጌታው ጋር የመጨረሻ የመለያያ ውይይት ያደርጋሉ፡፡
ጌታው - እንግዲህ ውሻ ሆይ! በህይወታችን በጣም ረዥም መንገድ ተጉዘናል፡፡ አያሌ ውጣ ውረዶችንም አልፈናል፡፡ የእናንተ የውሾች ሞቅ ያለው ኑሮ የጉልበታችሁ ዘመን ላይ ያለው፤ ወርቃማ ጊዜ ነው፡፡ ሰውም እንደ እንስሳ ወርቃማ ጊዜ አለው፡፡
ውሻው - አዎን ጌታዬ! ለማንም ቢሆን ጉልበት የሚሰማው ዕድሜ፣ ጥበብ የሚሰማው ዕድሜና አዳዲስ ዘዴ ለመፍጠር ህዋሳቱ የነቁበት የተሐድሶ ወቅቱ ነው!
ጌታው - አዎን፡፡ ውሻ ልዩ ልዩ ለሰው ጠቃሚ ባህሪያት አሉት፡፡
ውሻ - አዎን ቤት ይጠብቃል፡፡
ጌታው - ታማኝ ነው፡፡
ውሻ - የጌታውን ወዳጅና ጠላት ይለያል፡፡
ጌታው - ባለቤቱ እንቅልፋም ቢሆን እንኳ እሱ ንቁ ነው፡፡
ውሻ - ብቻ ምንም ውለታ ይዋል፤ ምንም፤ በመጨረሻ ጌታው የበቃው ዕለት ያባርረዋል፡፡
ጌታው - ሁሉም ጌታ፤ እንደዚያ ላያደርግ ይችላል፡፡
ውሻ - አይመስለኝም፡፡ የጌታ ሁሉ ጠባይ፣ ደረጃው ይለያያል እንጂ ያው ነው!
ጌታው - ይልቅ ሌላ ስለ ውሻ መልካም ጠባይ ያላነሳነው ካለ አስታውሰኝ!
ውሻ - እ … አንድ በጣም ትልቅ ፋይዳ፣ ከውሻ ባህሪ ውስጥ ተጠቃሽ፣ አስታዋሽነቱ ነው፡፡ የሠራውን ያስታውሳል፡፡ የተሰራበትንም ያስታውሳል፡፡ ስለዚህ ውሻ ከሰው ይልቅ ሙሉ ነው!!
ይህ የመጨረሻው አባባል ህሊናውን እየጠቀጠቀው፣ ጌታዬው ውሻውን አሰናበተው!
ከዓመታት በኋላ እንድ ሌባ በፖሊስ ተይዞ፣ ወደ ጌትየው ቤት መጣ፡፡ ጌትየው የዚያን ሌባ መምጣት ጨርሶ አያስታውስም፡፡ ትዝ ያለው ነገር ውሻው በማስታወስ ጉዳይ እንደማይታማ የነገረው የመጨረሻ ቃል ነው፡፡ ስለዚህ ፈልጉልኝ አለ፡፡ በእግር በፈረስ ያስፈልገው ጀመር፡፡ በመካያው ተገኘ ውሻው!! ውሻው ዝርዝሩን አወቀው፡፡
ሌባው - “የዛን ሌሊት ይሄ ውሻ ባይኖር፣ ጌትዬውን ገድዬ፣ ቤቱን ዘርፌ ልሄድ ነበር ዕቅዴ! ዕድሜ ለዚህ ያረጀ ውሻ ፈርቼ ሄድኩ! አንተን ሰውዬውን ሳይሆን የውሻህን ግርማ ሞገስ ነበር የፈራሁት!!” አለ፡፡
ጌትዬውም፤
“ለካ ከመጮህም፣ ከመናከስም በላይ ግርማ ሞገስ የበለጠ ልምድ ነው!” ብሎ፤ “ውሻዬን ግርማ ሞገሱን አክብሬ ማስቀመጥ አለብኝ!” ብሎ ወሰነ!!
*   *   *
ሰራተኛ መቅጠርና ማባረር (hire and fire) በካፒታሊስት ስርዓት እጅግ የተለመደ ክስተት ነው! መታሰብ ያለበት ግን የሥራ ልምድ ጥያቄ ነው! የለመደውና ሥራውን የሚያውቀው ለቅቆ መሄዱ፤ አዲሱ፣ ጉልበተኛው ሰራተኛ አዲስ ደም ይዞ ወደ ሥርዓቱ ሲገባ (New blood - injection እንዲሉ)፤ የቆየውን የነባሩን ልምድ ስለሚያጣ ስራው ጎዶሎነት የማያጣው አይሆንም፡፡ ትልቁ ቁምነገር አዲሱን አስለማጅ ማስፈለጉን ልብ ማለትና የሂያጁን ልምድ መቅሰሚያ ዘዴ ማስፈለጉን ማስተዋል ላይ ነው፡፡ አገር የተገነባችውና ለዘመናት የቢሮ ሥርዓት ሀዲዷን ጠብቃ እስከ ዛሬ የዘለቀችው አበው ጠዋት ባሰመሩት መስመር ላይ እየተጓዘች፣ እንከንና ግድፈቷን እያረመች ነው፡፡ ነገም ተረካቢው ትውልድ ኃላፊነቱን በወጉ እያስተናገደ ከመራመድ ሌላ ብዙ አማራጭ የለውም! የዚህ ታላቅ አደራ ተረካቢ ደግሞ ወጣቱ ትውልድ ነው፡፡ ሳይቸኩል፣ በፍቅር በተስፋና በጉጉት፣ እያሰበ ለውጥን ማሰብ፣ ልዩነትን በሰለጠነ መንገድ መፍታትት የፈርጀ ብዙ ችግር አገር ተረካቢ መሆኑን አውቆ በልክ በልኩ፣ በቅጥ በቅጡ፣ ጥሬውን ማብሰል፣ ብስሉን በፍትሃዊ መንገድ ማከፋፈልና መምራት ይጠበቅበታል፡፡ መደማመጥ፣ መወያየት፣ አንጋፋን ማክበር፣ ከባለሙያ መማር፣ በሥነ ምግባር መታነፅ ዋና ዋና ተግባራት ናቸው፡፡
አገር መውደድ ከዘፈን፣ ከግጥም፣ ከስሜታዊነትና ከትኩሳት ባሻገር፤ የጠለቀና የመጠቀ ደርዝ መጨበጥን እንደሚጠብቅ እናስተውል፡፡ አገርን ማገልገል ቀናነትንና ብስለትን፣ ሀቀኝነትንና ከቤተሰብ እስከ ህብረተሰብ ያሉትን እርከኖች ጠንቅቆ የማወቅን ፅናት ይጠይቃል፡፡ የሚከተለውን ግጥም ልብ እንበል፡-
            እሳት ያልገባው ልብ
            ሚሚዬን ጠየኳት፡-
            “ሁል ጊዜ አረንጓዴ፣ ለምለም ፍቅር አለ
            ትወጃለሽ ሚሚ፣ ይህን የመሰለ?”
            ሚሚዬ እንዲህ አለች
            ሳስቃ መለሰች፡-
            “የምን እኝኝ ነው፣ ዕድሜ ልክ ካንድ ሰው
            ቋሚ ፍቅር ይቅር፣ ለብ ለብ እናርገው!”
            ፍቅሯ ለብ ለብ
            ትምህርቷ ለብ ለብ
            ዕውቀቷ ለብል
            ነገር - ዓለሟ ግልብ፤
            እንዴት ይበስል ይሆን
            እሳት ያልገባው ልብ!?
                                                            (ነ.መ.)
ኢትዮያ እሳት የገባው ልብ ያለው፣ አዲስ ኃይል ያስፈልጋታል፡፡ የዕውቀት ኃይል ወሳኝ ረሀቧ ነው፡፡ ጤና የጧት ማታ ህመሟ ነው፡፡ ኢኮኖሚያዊ ጉልበቷ እንደ አዲስ መፈተሽ ያለበት ነው፡፡ ፍትሐዊ ውስጠ ነገሯ፤ መመርመር ያሻዋል፡፡ ሁሉም እሳት የገባው ልብ ይኖራቸው ዘንድ ግድ ይላል፡፡ አንድ ነገር ግን ዛሬን ከትላንቱ ጥያቄ ይለየዋል፡፡ ሰጪና ተሰጪ የለም፡፡ ሁሉም ድርሻዬ ምንድን ነው ብሎ የሚገነባው ዲሞክራሲ፣ እኩልነትና ፍትሐዊ ሥርዓት መሆን አለበት፡፡ መጠንጠኛው የሀገር ፍቅር መሆን አለበት፡፡  
ደራሲ ዘውዴ ረታ፤ “የቀዳማዊ ኃይለሥላሴ መንግስት” በሚለው መጽሐፋቸው እንደገለፁት፤
“ለኢትዮጵያ ኃላፊነትን ለሚቀበለው መሪ፣ በኢትዮጵያዊነት ግዳጄ ለማገልገል የምቀርበውም፤ ለሀገራችን ዕድገት፣ ለህዝባችን ደህንነት የሚጥር፣ የሚያስብና የሚሰራ ሆኖ ሳገኘው ነው እንጂ፤ በውርስ ንጉሥ፣ በዘሩ መስፍን ነው ብዬ አይደለም፡፡ የለፈው ታሪኬ በትክክል እንዳሳየው፤ ልጅ እያሱ አጉል ጠባያቸውን አሻሽለው ኢትዮጵያን ከነክብሯ በሰላም እንዲመሯት ብዙ ደክሜ ሳይሆንልኝ ሲቀር፤ ለለውጡ ከሸዋ መኳንንት ጋር የተሰለፍኩት፤ ኢትዮጵያን የምወድ፣ ለኢትዮጵያ የቆምኩ በመሆኔ ብቻ ነው፡፡ ዛሬም እኔና ጓደኞቼ የምንመካውም ሆነ የምንኮራው በኢትዮጵያ ላይ ብቻ ስለሆነ፤ ኢትዮጵያንና ህዝቧን በቅንነት ከማገልገል ሌላ የሚያረካን ነገር አይኖርም” የሚል የሀገር መሪ ለኢትዮጵያ መድሕን ይሆናል፡፡ ያም ሆኖ ህብረተ ሱታፌን የሚያምን ህዝብ ሲኖር ነው! ሕብረተ ሱታፌን የሚቀበል የለውጥ አራማጅ ሲኖር ነው!
ይህን ዓይነት አስተሳሰብ የማይጥማቸው በርካታ ሰዎች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ወደፊት የሚራመድን ሁሉ የኋሊት የሚጎትቱ፣ በየሥርዓተ ለውጡ ይከሰታሉ፡፡ ፈረንጆች “You can’t teach an old dog a new trick” የሚሉት ወደው አይደለም፡፡ አሮጌ ውሻን አዲስ ዘዴ ማስተማር አዳጋች ነው እንደማለት ነው፡፡ አንድም ደግሞ ምንም ዓይነት ስልጠና ብንሰጥ፣ ምንም ዓይነት የመግራት ችሎታ ቢኖረን፣ ከባህሪ የተጣባን ነገር ማስወገድና ማልመድ ከባድ ነው፡፡ የቆቅ ለማዳ የለውም የሚለው ተረት ቢውጠነጠን፤ ብዙ ገፀ ባህሪያትን እንድንመረምር ያግዘናል፡፡ ህብረተሰባችን፣ ቡድኖች፣ ፓርቲዎችና ማህበራት ውስጣቸው ተከፋፍቶ ሲታይ፣ የቤት ጣጣ እንዳለባቸው እንገነዘባለን! ቆም ብለን እናስብ! ቆም ብለን እንምከር! የነገዋን ኢትዮጵያ ዛሬውኑ ልናያት እንጣር!

 “መግለጫው እርስበርሱ የሚጣረስና ግራ የተጋባ ነው” - አረና

   የኢህአዴግ ሥራ አስፈፃሚ በኢትዮ - ኤርትራ የድንበር ግጭትና በኢኮኖሚ የማሻሻያ እርምጃ ላይ ያሳለፈውን ውሳኔ ተከትሎ፣ ስብሰባ የተቀመጠው የህውሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ፤ ኢህአዴግ አስቸኳይ ስብሰባ እንዲጠራ የጠየቀ ሲሆን የግንባሩንም መግለጫ አብጠልጥሏል፡፡
የህወሓት ማዕከላዊ ኮሚቴ ባወጣው መግለጫም፤ “ኢህአዴግ የአመራር ብልሹነት አጋጥሞታል፤ የድርጅቱ አብዮታዊ ዲሞክራሲ መስመር አደጋ ላይ ወድቋል” ሲል በስጋት የታጀበ ትችት ሰንዝሯል፡፡
የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ በስብሰባው፣ በመጋቢት 2010 የም/ቤት ስብሰባ ላይ የተላለፉ ውሣኔዎች የደረሡበትን ደረጃ ሊመለከት ይገባው ነበር ያለው ህውሓት፣ ምክር ቤቱ በወቅቱ ያስቀመጣቸው ድርጅቱን ከአደጋ የማዳኛ መንገዶችና አቅጣጫዎች አሁንም በጥብቅ ዲሲፒሊንና ተጠያቂነት ሊተገበሩ ይገባል ብሏል፡፡
የኢትዮጵያና የኤርትራ የ18 አመታት ግጭት በሠላማዊ መንገድ እንዲፈታ እንዲሁም የመንግስት የልማት ድርጅቶችን አስመልክቶ የወጣው መግለጫ ከአብዮታዊ ዲሞክራሲ ፖሊሲ ጋር የሚቃረን አለመሆኑን የጠቆመው የህወኃት ማዕከላዊ ኮሚቴ፤ አፈፃፀሙ ግን በጥንቃቄ መከናወን እንዳለበት አሳስቧል፡፡
በኢትዮ-ኤርትራ ጉዳይ ላይ የተሠጠው ውሣኔ ለህዝብ ይፋ መደረግ አልነበረበትም ያለው ድርጅቱ፤ በመጀመሪያ ህዝቡ ሊውያይበት ይገባ ነበር ብሏል፡፡ በጉዳዩ ላይ አጋር ድርጅቶችም መወያየት እንደነበረባቸው በመጠቆም፡፡
በዚሁ የአቋም መግለጫ በዴሞክራሲ ሃይሎችና በጥገኝነት መካከል ቀጣይ ትግል ይደረጋል ያለው ህወሓት፤ “ህገ መንግስቱ በሚገባ መልስ የሰጠባቸውን የማንነትና የወሰን ጥያቄዎች፣ ፌደራላዊ ስርአቱን በመፃረርና የህዝቡን ክብር በሚነካ መልኩ በሃይልና በተፅዕኖ፣ የትግራይ ህዝብን አንድነትና ሠላም ለመረበሽ እየተደረጉ ያሉ ፀረ ዲሞክራሲ እንቅስቃሴዎችን ከህዝቡ ጋር በመሆን በፅናት እታገላለሁ ብሏል፡፡
ልማታዊ ዲሞክራሲያዊ መስመራችን ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ አደጋ ውስጥ ወድቋል የሚለው ድርጅቱ፤ የኢህአዴግ አመራር አብዮታዊ ዲሞክራሲ ባህሪው እየተሸረሸረ በከፋ የጥገኛ ዝቅጠት አረንቋ ውስጥ መዘፈቁን አስታውቋል። ለአብዮታዊ ዲሞክራሲ መስመር ወድቀትም አመራሩ ተጠያቂ ነው ብሏል- ህወኃት በመግለጫው፡፡
አንዳንድ የኢህአዴግ ስራ አስፈፃሚ ውሳኔዎችን በመግለጫው ያብጠለጠለው ህወሓት፤ በድርጅቱ ውስጥ ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በግልፅ እየታየ የመጣውን የአመራር ብልሹነት መመልከት ይገባው ነበር ብሏል፡፡
በአሁኑ ወቅት በኢህአዴግ ደረጃ እየተደረጉ ያሉ የአመራር ምደባዎች የኢህአዴግን ህገ-ደንብና ተቋማዊ አሠራር ያልተከተሉ ናቸው ሲል በመተቸትም፤ የአመራር ምደባዎቹ እንዲታረሙ ጠይቋል፡፡ ለድርጅቱ ነባር አመራሮች እውቅና እንዲሠጥም ህወሓት ጠይቋል፡፡
የትግራይ ህዝብና መሪ ድርጅቱ ህወኃት፤ እንዳለፈው ጊዜ ሁሉ የአብዮታዊ ዲሞክራሲ መስመራችን አስተማማኝ ደጀን በመሆን፣ ትግሉን ያጠናከራል ብሏል በመግለጫው፡፡
ሠላማዊ ህጋዊ መንገድ ተከትለው አማራጭ ሃሣብ ከሚያቀረቡ ሃይሎች ጋር አብሮ እንደሚሠራ የጠቆመው ድርጅቱ፤ ህውሓትንና የትግራይን ህዝብ ለማዳከምና ለመምታት በተለያዩ መንገዶች፣ ፀረ-ትግራይ ህዝብና ፀረ-ህወኃት እንቅስቃሴ የሚያደርጉ የውስጥም የውጭም ሃይሎችን ህዝቡ አምርሮ እንዲታገላቸው ጥሪ አቅርቧል፡፡
የህወሓትን መግለጫ አስመልክቶ አስተያየታቸውን ለአዲስ አድማስ የሰጡት የአረና ትግራይ ፓርቲ ምክትል ሊቀመንበር አቶ ጎይቶም ፀጋዬ፤ መግለጫው እርስ በእርሡ የሚጣረስና ግራ የተጋባ ነው ብለዋል፡፡
“ህወኃት የተቃወመው አንድ ነገር ቢኖር፣ የህዝብ ድጋፍ ያለው የባለስልጣናት በጡረታ መሰናበትን ነው” የሚሉት አቶ ጎይቶኦም፤ መግለጫው በኤርትራ ጉዳይና በልማት ድርጅቶች ላይ ህወኃት ከኢህአዴግ የተለየ አቋም እንዳላንፀባረቀ ያመላክታል ብለዋል፡፡