Administrator

Administrator

አይሲስ በሊቢያ አግቷቸው የነበሩ 28 ኤርትራውያን ተለቀቁ

    የተለያዩ የአፍሪካ አገራት ዜጎች የሆኑ 1 ሚሊዮን ያህል ስደተኞች በሊቢያ በኩል አድርገው ወደ አውሮፓ አገራት ለመግባት በማሰብ እጅግ አስቸጋሪ በሆነው የስደት ጉዞ ላይ እንደሚገኙ ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
ባለፉት 3 ወራት ብቻ 590 ያህል አፍሪካውያን ስደተኞች በሜዲትራኒያን ባህር ሰጥመው መሞታቸውን የጠቆሙት በሊቢያ የእንግሊዝ ኤምባሲ የቀድሞ ሃላፊ  ጆ ዎከር ከዚንስ፣ 1 ሚሊዮን ያህል አፍሪካውያን ስደተኞች ለሞት በሚያጋልጠው በዚህ አስቸጋሪ ጉዞ ላይ እንደሚገኙ መናገራቸውን ዘገባው ገልጧል፡፡
ባለፈው የፈረንጆች አመት 2016፣ ሜዲትራኒያን ባህርን አቋርጠው ጣሊያን የገቡ አፍሪካውያን ስደተኞች ቁጥር 181 ሺህ እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፤ ባለፉት ሶስት ወራት ብቻ በዚሁ የስደት መስመር ጣሊያን የገቡ አፍሪካውያን ስደተኞች 22 ሺህ ያህል እንደሚደርሱም  አመልክቷል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ አሸባሪው ቡድን አይሲስ በሊቢያ ሲርጥ ውስጥ አግቷቸው የነበሩና ቡድኑ ባለፈው ታህሳስ ወር ላይ አካባቢውን ለቅቆ ከሄደ በኋላ የትሪፖሊ መንግስት ከሽብር ቡድኑ ጋር ግንኙነት ሊኖራቸው ይችላል በሚል አስሯቸው የቆዩ 28 ኤርትራውያንና ሰባት ናይጀሪያውያን ስደተኞች መለቀቃቸውን ሮይተርስ ዘግቧል፡፡
ከእስር ከተለቀቁት ከእነዚህ ስደተኞች መካከል ወደ አውሮፓ ለመግባት በስደት ጉዞ ላይ የነበሩ ሴቶች እንደሚገኙበት የጠቆመው ዘገባው፤ የአይሲስ ታጣቂዎች ሴቶቹን በማገት ለወሲብ ሲጠቀሙባቸው እንደነበርም ገልጧል፡፡
ስደተኞቹ ባለፈው ረቡዕ ከእስር መለቀቃቸውን ተከትሎ፣ የተባበሩት መንግስታት ድርጅት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን የተቀበላቸው ሲሆን  የህከምና ምርመራ ተደርጎላቸው ወደ መጠለያ እንዲገቡ መደረጉንም ዘገባው አመልክቷል፡፡

 በወጣቱ ደራሲ ሙሉጌታ አለባቸው የተጻፈው “መሐረቤን ያያችሁ” የአጫጭር ታሪኮች ስብስብ መጽሐፍ ባለፈው ረቡዕ ምሽት በሞዛይክ ሆቴል በተከናወነ ልዩ ፕሮግራም ተመርቆ በገበያ ላይ ውሏል፡፡
የስነ-ጽሁፍ ቤተሰቦች በተገኙበት ስነ-ስርዓት የተመረቀውና ማሕበራዊ፣ ታሪካዊና ፖለቲካዊ ሀሳቦችን የሚዳስሰው “መሐረቤን ያያችሁ”፣ መቼቱን በ1980ዎቹ መጨረሻ የኢትዮጵያ ማሕበራዊ ሕይወት ላይ አድርጎ፣ በርካታ ርዕሰ ጉዳዮችን የሚያነሳ ሲሆን በአዳዲስ የትረካ ቅርጾች የተዋቀረ ነው፡፡
የደራሲ አዳም ረታን “ሕጽናዊነት” የተባለ ልዩ የአጻጻፍ ስልት መጠቀሙን በመጽሃፉ መግቢያ ላይ የጠቆመው ደራሲው፤ በ215 ገጾች የቀረቡት አስራ ሁለት አጫጭር ትረካዎች እርስ በእርስ በቀጫጭን የትረካ መስመር እንደሚገናኙም ገልጧል፡፡
በሕጽናዊነት የአጻጻፍ ስልት ዙሪያ ጥልቅ ትንታኔዎችን ሲያቀርብ የቆየው ደራሲው፤ “ይሄን ስልት መጠቀሜ ሕጽናዊነትን የማስቀጠል ደፋር ሙከራዬ ነው” ሲል አብራርቷል፡፡
ደራሲ አዳም ረታ በመጽሃፉ የጀርባ ሽፋን ላይ በሰጠው አስተያየት፤ “የሙሉጌታ አለባቸው ቋንቋ ውብ ነው፡፡ ይሕ መጽሐፍ ሊናቅ የማይችል የአንድ ወጣት የስነጽሑፍ ጀብደኛ ዘራፍ ነው” ብሏል፡፡
በአዲስ አድማስና በሌሎች ጋዜጦችና የህትመት ውጤቶች ላይ ለረጅም ጊዜያት አጫጭር ልቦለዶችን፣ ስነጽሁፋዊ ትንተናዎችን፣ መጣጥፎችንና የትርጉም ስራዎችን ለንባብ በማብቃት የሚታወቀው ሙሉጌታ አለባቸው፤ መጽሃፉ በአዲስ አበባና በክልል ከተሞች በመጽሃፍት ቤቶችና በአዟሪዎች እየተሸጠ እንደሚገኝም በተለይ ለአዲስ አድማስ ገልጧል፡፡

 በደራሲ መላኩ ደምሰው ተፅፎ በአቦወርቅ ሀብቴ የተዘጋጀውና በአቡ ፊልም ፕሮዳክሽንና በአሰፋ ገረመው ፕሮዲዩስ የተደረገው “ፈልጌ አስፈልጌ” የተሰኘ ልብ አንጠልጣይ የቤተሰብ ድራማ ፊልም ዛሬና ነገ በሁሉም የግልና የመንግሥት ሲኒማ ቤቶች እንደሚመረቅ ተገለፀ፡፡ ፊልሙ በዋናነት አንድ አደራ የተሰጠው ወጣት አደራውን ለመወጣት የሚያደርገውን ውጣ ውረድና ፈልጎ አስፈልጎ የሚያገኘውን አደራውን የመጠበቅ መንገድ እንደሚያሳይ የፊልሙ ዳይሬክተርና ፕሮዲዩሰር አቶ የአቦወርቅ ሀብቴ ተናግረዋል፡፡ ሐሙስ ረፋድ ላይ በአዜማን ሆቴል ፊልሙን አስመልክተው ደራሲውና ፕሮዲውሰሩ በሰጡት መግለጫ፤ ፊልሙን ሰርቶ ለማጠናቀቅ 18 ወራትና 900 ሺህ መፍጀቱን ጠቁመው፤ የ1 ሰዓት 23 ደቂቃ ርዝመት እንዳለውም ተናግረዋል፡፡ በፊልሙ ላይ ተዘራ ለማ፣ ዝናህብዙ
ፀጋዬ፣ ፍ ፁም ፀ ጋዬ፣ ያ የህይራድ ማ ሞ፣ ኢ የሩሳሌም ደረጀ፣ ዳንኤል አበበ፣ ሀረግ መኳንንት፣ አማን ታዬ፣ መላኩ ደምሰውና ሌሎችም ወጣት ተዋንያን ተሳትፈውበታል፡፡ በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ የፊልም ባለሙያው ብርሃኑ ሽብሩ በወቅቱ የአገራችን ፊልም ተግዳሮቶችና መፍትሄዎቻቸው ዙሪያ ሙያዊ አስተያየቱን ሰጥቷል፡፡

  ሚዩዚክ ሜይዴይ ኢትዮጵያ ከኢትዮጲስ ኮሌጅ ጋር በመተባበር ነገ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ በብሔራዊ
ቤተ - መፃሕፍትና ቤተ - መዛግብት ኤጀንሲ አዳራሽ፣ “ለራስ የተፃፈ ደብዳቤ” እና “የብርሃን ፍቅር” በተሰኙ
የገፃሚ ደበበ ሰይፉ የግጥም መድበሎች ላይ ውይይት ያካሂዳል፡፡ ለውይይቱ የመነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት ደራሲ
ዳንኤል ወርቁ እንደሆኑ የገለፀው ሚዩዚክ ሜይ ዴይ፤ ፍላጎት ያለው በውይይቱ ላይ እንዲሳተፉ ጋብዟል፡፡

  69ኛው የግጥም በጃዝ ምሽት የፊታችን ረቡዕ ከምሽቱ 12፡00 ሰዓት ጀምሮ በራስ ሆቴል ይካሄዳል፡፡ በዕለቱ ገጣሚና ደራሲ ነቢይ መኮንን፣ ደራሲና ፀሐፌ ተውኔት አያልነህ ሙላቱ፣ ዶ/ር ኤሊያስ ሌዊ ዲስኩር የሚያቀርቡ ሲሆን አለማየሁ ታደሰ፣ አስቴር በዳኔ፣ ሽመልስ አበራና እታፈራሁ መብራቱ አጭር ተውኔት እንደሚያቀርቡ የፕሮግራሙ አዘጋጆች በላኩት መግለጫ አስታውቀዋል፡፡

 በወሩ መጨረሻ ባሉት ቅዳሜና እሁድ የሚካሄደው ትራኮን የመፅሀፍት አውደ ርዕይና የሂስ ጉባኤ፤ ዛሬና ነገ ጥቁር አንበሳ ፊት ለፊት በሚገኘው ትራኮን ታወር ይካሄዳል፡፡ ዛሬ ከቀኑ 8፡00 ሰዓት ጀምሮ ለሂስ የሚቀርበው መፅሀፍ የዶ/ር ምህረት ከበደ የመጀመሪያ ስራ የሆነው “የተቆለፈበት ቁልፍ” ሲሆን ለዚህ መፅሐፍ የውይይት መነሻ ሀሳብ የሚያቀርቡት በ“ፍቅር እስከ መቃብር” መፅሐፍ ላይ ለየት ያለ ትንታኔን “እውነትና ገሀድ” በተሰኘው መፅሀፋቸው ያስነበቡትና የስነ መለኮት ሊቁ ዶ/ር ዘካሪያ አምደ ብርሃን እንደሚሆኑ የዝግጅቱ አስተባባሪ አቶ በፍቅሩ
ዳኛቸው ገልፀዋል፡፡
    እነሆ መፅሀፍት መደብር፣ ሊትማን ቡክስና ክብሩ መፅሐፍት መደብር በመተባበር “ሀሳብን በሀሳብ መፈተን” በሚል መሪ ቃል በሚያዘጋጁት በዚህ አውደ ርዕይና የሂስ ጉባኤ፣ የመፅሀፍ እቁብን ጨምሮ ከ25 እስከ 50 በመቶ ቅናሽ የተደረገባቸውን መፅሐፍት መግዛትና በውይይቱ ላይ መሳተፍ የእውቀት አድማስን ማስፋት ነው ሲሉ አዘጋጆቹ ጋብዘዋል፡፡

Monday, 10 April 2017 11:06

የፀሐፍት ጥግ

 · አና ካሬኒናን በቅጡ ማንበብ ሌላ ምንም ነገር ባያስተምርህ እንኳን የስትሮበሪ ጃም አሰራርን ያስተምርሃል፡፡
    ጁሊያን ሚሼል (እንግሊዛዊ ደራሲና ፀሃፌ ተውኔት)
· ገጣሚ የአደባባይ ሰው አይደለም፡፡ ገጣሚ መነበብ እንጂ መታየት የለበትም፡፡
   ሴሲል ዴይ-ልዊስ (ትውልደ አየርላንድ እንግሊዛዊ ፀሃፊ)
· ሰው ዝንባሌው እንደመራው ነው ማንበብ ያለበት፤ እንደ ሥራ የሚያነብ ከሆነ ብዙም አይጠቅመውም፡፡
   ሳሙኤል ጆንሰን (እንግሊዛዊ የመዝገበ ቃላት አዘጋጅና ፀሃፊ)
· በጣም ብዙ መፃህፍትን ማንበብ ጎጂ ነው፡፡
   ማኦ ዜዶንግ (ቻይናዊ አንጋፋ የፖለቲካ ሊቅ)
· ለረዥም ጊዜ የቢዝነስ ህይወት ስመራ በመቆየቴ የንባብ ጣዕሜን አጥቻለሁ እናም አሁን ምን ባደርግ ይሻላል?
   ሆራስ ዋልፖል (እንግሊዛዊ ፀሃፊ)
· የአካል እንቅስቃሴ ለሰውነት እንደሚያስፈልገው ሁሉ፣ ንባብም ለአዕምሮ ያስፈልገዋል፡፡
   ሪቻርድ ስቲሌ (ትውልደ አየርላንድ እንግሊዛዊ ወግ ፀሃፊ፣ ፀሃፌ ተውኔትና ፖለቲከኛ)
· ሥነ ፅሑፍ ይሰለቸኛል፤ በተለይ ታላላቅ ሥነፅሁፍ፡፡
   ጆን ቤሪማን (አሜሪካዊ ገጣሚ)
· በትራጄዲ ውስጥ እንሳተፋለን፤ ኮሜዲ ሲሆን ግን መመልከት ብቻ ነው፡፡
   አልዶዩስ ሁክስሌይ (እንግሊዛዊ ደራሲና ወግ ፀሃፊ)
· እያንዳንዱ አርቲስት የየራሱን ግለ ታሪክ ይፅፋል፡፡
   ሃቬሎክ አሊስ (እንግሊዛዊ የሥነ ልቦና ባለሙያ)
· ፀሃፊ እሞታለሁ ብሎ ማሰቡ ጥሩ ነው፤ ተግቶ ይሰራል፡፡
  ቴኒዚ ዊሊያምስ (አሜሪካዊ ፀሃፌ ተውኔት)
· ውሸት የልብወለድ መጀመሪያ ነው፡፡
  ጃማይካ ኪንሳይድ (ትውልደ አንቲጓን አሜሪካዊ ደራሲና ጋዜጠኛ)
· ደራሲያን የሚፅፉበት ብዙ ምክንያቶች አሉ፤ ሁሉም ግን አንድ ነገር ያመሳስላቸዋል - አማራጭ ዓለም የመፍጠር ፍላጎት፡፡
  ጆን ፎውሌስ (እንግሊዛዊ ደራሲ)
· አንድ ልብወለድ በሁለት መንገዶች ሊጠና ይችላል፡- አንድም በአርቲስቱ የተወከለውን ምስል በማጥናት አሊያም ሕይወትን ራሱን በማጥናት፡፡
   ቤኒቶ ፔሬዝ ጋልዶስ (ስፔናዊ ደራሲና ፀሃፌ ተውኔት)
· ጓደኛ እንደምትመርጠው ሁሉ ደራሲም ምረጥ፡፡
   ዌንትዎርዝ ዲሎን (ትውልደ አየርላንድ እንግሊዛዊ ገጣሚ)

  አርቲስት ደበበ እሸቱ ምን ይላል?

         አርቲስት ደበበ እሸቱ ባለፈው ሳምንት በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ በተከበረው 55ኛው የዓለም የቴአትር ቀን ላይ ከተሳተፉትና በበዓሉ ላይ በተለያየ መልኩ ጉልህ ሚና ከነበራቸው አንጋፋ የኪነ-ጥበብ ባለሙያዎች አንዱና ግንባር ቀደሙ ነበር፡፡ ከሚናዎቹ መካከል ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ኢትዮጵያን ወክሎ የአለም የቴአትር ተቋም አባል እንዲሆን የድርድሩንና መሰል ሂደቶች በማካሄድ ትልቁን ሚና ተጫውቷል፡፡ አርቲስቱ በተጨማሪም ወልቂጤ ዩኒቨርስቲ
ባዘጋጀውና በ1905 ዓ.ም በጅሮንድ ተክለሀዋሪያት ተ/ማሪያም በፃፉት ‹‹የአውሬዎች መሳለቂያ ኮሜዲ›› (ፋቡላ) ቴአትር ላይ በመሪ ተዋናይነት ተጫውቷል፡፡ የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ፣ አርቲስት ደበበ እሸቱን በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ አግኝታው በቅርቡ በቤተ እስራኤላዊያን ላይ በሚያጠነጥነው ‹‹ቀያይ ቀንበጦች” (Red Leaves) በተሰኘውና በመሪ ተዋናይነት ስለተወነበት ፊልም፣ ኢትዮጵያ የአለም የቴአትር ተቋም አባል እንድትሆን ስላደረገው ጥረት፣በወቅቱ የአገራችን የቴአትር ሁኔታና ስለ ወደፊት ሀሳቡ እንደሚከተለው አነጋግራዋለች፡፡

     ከሁለተኛው የ”ጉማ ሽልማት” የህይወት ዘመን ሽልማትህ በኋላ ትንሽ ጠፍተሀል፡፡ የጠፋኸው ደግሞ እስራኤል ውስጥ እየሰራህ በነበረው ፊልም ምክንያት ነው ይባላል፡፡ እውነት ነው?
እውነት ነው፡፡ አሜሪካዊያንና እስራኤሎች የሚሰሩት በቤተ እስራኤላዊያን ላይ የሚያጠነጥን ፊልም ነበር፡፡ እሱን በዋና ገፀባህሪነት ለመስራት ተመርጬ፣ ወደ እስራኤል አቅንቼ ለስድስት ወራት ቆይቼ፣ ፊልሙ ተሰርቶ ካለቀ በኋላ ወደ አገሬ ተመልሼ ነበር፡፡ ፊልሙ ለእይታ ሲከፈት እንደገና ተመልሼ ሄድኩኝ፡፡ እዛም ፊልሙ ተሸለመ፡፡
ምን አይነት ሽልማት አገኘ? የፊልሙስ ጭብጥ ምንድን ነው?
በታጨበት ዘርፍ ብልጫ ያለውና አዲስ አቀራረብ የታየበት በሚል ተሸለመ፤ ለእኔም እውቅና ሰጥተው አመስግነውኛል፤ ይበቃኛል፡፡ የፊልሙ ጭብጥ በዓለም ዙሪያ የተበታተኑ ቤተ እስራኤላዊያን ተመልሰው ወደ እስራኤል ይካተታሉ የሚልና ኢትዮጵያን እንደ ምሳሌ የወሰዱበት ነው፡፡ ፊልሙ ሁሉንም ዓለም የሚመለከትና በፍልሰት ምክንያት የሚያጋጥምን ፈተና በተለይ ቤቴ እስራኤላዊያን ላይ የደረሰን ችግር በጉልህ የሚያሳይ ነው፡፡ እውነት ለመናገር በፊልሙ ላይ እኔ ስለተወንኩ አይደለም፤ ግን በጣም በጥሩ ሁኔታ የተሰራ በመሆኑ ቫንኮቨር ላይም ለፌስቲቫል ቀርቦ ከታየ በኋላ ከቀረቡት 36 ፊልሞች ጥቂት ተመርጠው ሲያልፉ 10ኛ ሆኖ አልፎ ነበር፡፡ ከዚያ የመጨረሻው ሶስት ፊልሞች ውስጥ ገብቶ፣ ‹‹The Best leading Actor Golden Leopold Award›› የሚል ሽልማት ተሸልሜበታለሁ፡፡ የተሰራበት ቋንቋ አማርኛና ሂብሩ ሲሆን እንግሊዝኛ ሰብታይትል ተሰርቶለታል፡፡
ጋሽ ደበበ --- በአሁኑ ወቅት ቴአትሩ አካባቢ ምን እየሰራህ ነው ?
እኔ እንግዲህ መፅሐፎች እተረጉማለሁ፤ በቅርቡ የተረጎምኩት ‹‹ኢትዮጵያ የባሩድ በርሜል›› የተሰኘ መፅሐፌ፣አሜሪካ በፀሐይ አሳታሚ ታትሞ ለገበያ ቀርቦ ነበር፡፡ በድጋሚ ኢትዮጵያ ታትሞ ለገበያ ውሏል፡፡
መፅሐፉ በጣም የቆየና ስለ አንድ ኦስትሪያዊ የኢትዮጵያ ጥላቻ የሚያወሳ ነው፡፡ ይህን የቆየ መፅሐፍ የተረጎምክበት ዓላማ ምንድን ነው?
እንዳልሽው መፅሐፉ አንድ ኦስትሪያዊ ፋሽስት ለኢትዮጵያ ከፍተኛ ጥላቻ ስለነበረው ኢትዮጵያ የአለም መንግስታት ማህበር (league of Nations) አባል እንዳትሆን ሽንጡን ገትሮ ሲሟገት የነበረ ነው። ይህንን መፅሀፍ አግኝቼ ሳነበው፣ በሰውየው ስራ በጣም ስለተናደደኩ፣ ተርጉሜው ለኢትዮጵያ ህዝብ ይቅረብና ህዝቡም እንደኔው ይናደድ ብዬ ነው፡፡ መፅሐፉ ለንባብ ከበቃ በኋላ ያንን ውጤት እያየሁ ነው፡፡ አሁንም እየተረጎምኳቸው ያሉ መፅሐፍት አሉ፡፡
ኢትዮጵያ የዓለም የቴአትር ተቋም አባል እንድትሆን ያንተ ከፍተኛ ጥረት እንደነበረበት ሰምቻለሁ፡፡ እስቲ ስለዚህ ሂደትና በተቋሙ የአፍሪካ ተወካይ ሆነህ ስለሰራህበት ዘመን ንገረኝ?
እ.ኤ.አ ከ1980 ዓ.ም ጀምሮ ባህል ሚኒስቴር በአንድ አጋጣሚ በኢንተርናሽናል ቴአትር ኢንስቲትዩት ስብሰባ ላይ እንድካፈል ልኮኝ፣ ምስራቅ ጀርመን ውስጥ በተካሄደው በዚህ ስብሰባ ላይ ተካፍዬ ነበር፡፡ በዛን ጊዜ ስለ ተቋሙ ብዙ እውቀት አልነበረኝም፡፡ እዚያ ከደረስኩ በኋላ መፅሐፍት ፈልጌ አንብቤ ነው የዩኔስኮ የባህል ምዕራፍ እንደሆነ የገባኝ፡፡ በወቅቱ በዚህ ስብሰባ ላይ የተሳተፉት በጣም ጥቂት የአፍሪካ ተወካዮች ነበሩ፤ ነገር ግን ብዙ አይናገሩም ነበር፡፡
እኔ አንድም ብዙ ካለማወቅ የተነሳ፣ሁለተኛ እንደ አፍሪካዊነቴ አፍሪካ ልትወከል ይገባታል በሚል ደጋግሜ ብዙ ጥያቄዎችን አንስቼ ነበር፡፡ በጊዜው የነበረው የITI ዋና ፀሀፊ የአፍሪካ የITI ተወካይ ሆነህ እንድትሰራ መርጠንሀል አለኝ፡፡ እግዜር ይስጥልኝ ብዬ ተቀበልኩት፡፡ ከዚያ እንደተመለስኩኝ ዚምባብዌ ውስጥ ‹‹Theatre for Development and Non Formal Education›› የሚል ወርክሾፕ ይካሄድ ነበር:: እዚያ ላይ እንደ ባለሙያ ሄጄ እንድሳተፍ ሆነ፡፡ እዚያ እያለን ስመለከት ከሌላው አገር ሀላፊነት ወስደው የመጡትና ስለ ቴአትር የሚናገሩት (የአፍሪካን ጭምር የወከሉት)፣ ስለ አፍሪካ ባህል አስተያየት የሚሰጡት ጀርመኖች፣ እንግሊዞች፣ ከፈረንሳይ የመጡት ናቸው፡፡ እኛን ባለቤቶቹን አንዳንዴ እስኪ ተናገሩ እያሉ እያናገሩን ለካ እነሱ ዶክትሬታቸውን ነው የሚሰሩት፡፡
ይሄ ጉዳይ በምን ታወቀ?
በቃ ታወቀ፤ መቼስ ፍንጭ አይጠፋም፡፡ እኔ ይሄን ነገር በግልፅ ተቃወምኩ፡፡ ከታዛኒያ የመጣች ዶ/ር ፔኒና ምላማ፣ አሁን የዳሬሰላም ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ሆናለች፤ እሷና እኔ ሌሎችንም አስተባብረን፣ እኛ የተጎዳነው አንድ አፍሪካን የሚወክል ማህበር ስለሌለን ነው፤ ለምን ማህበር አናቋቁምም በሚል የውስጥ ለውስጥ እንቅስቃሴ ጀመርን፡፡ ከዚያ እንግሊዞቹ፣ ጀርመኖቹና ፈረንሳዮቹ ኑና አስረዱ ሲሉን፣ አይ እናንተው አስረዱ እኛ ልንረዳ ነው የመጣነው፤ እናንተ ራሳችሁን ቻሉ በሚል አለመግባባት ተፈጠረና ማህበሩን እንድንፈጥር አንድ ምክንያት ሆነን፡፡ በሌሎች አገሮች ሞክረን አልተሳካልንም ነበር፤እዚያ ተሳካልን፡፡
ማህበሩ ሲመሰረት የትኞቹ የአፍሪካ አገራት መስራችና አባል ሆኑ?
19 የአፍሪካ አገሮች መስራች ሆነው ነበር፡፡ ከፈረንሳይ ተናጋሪዎቹና እንግሊዝኛ ተናጋሪዎቹ፣ ወደ ደቡብ ያሉት አንድ ላይ ሆነው ኬንያ፣ ታንዛኒያ፣ ኡጋንዳ፣ ጋምቢያ፣ ዚምባብዌ፣ ደቡብ አፍሪካ፣ ናይጄሪያ፣ ኢትዮጵያና ሌሎችም በግለሰብ ደረጃ ተሰባስበን ያቋቋምነው ማህበር ነው፡፡ “The African Union of African Performing Artists” ይባላል፡፡ እ.ኤ.አ. በ1985 ዓ.ም ነው የተቋቋመው፡፡ ይህ ማህበር ሲቋቋም እኔ አንዱ የአስመራጭ ኮሚቴ አባል አድርገውኝ ገባሁ፡፡ በነጋታው ሊመረጡ የተጠቆሙት ሰዎች ሲመጡ፣ ከዚምባብዌ የመጡት ተጠቋሚዎች ነጮች ናቸው፤ እኔ እንደ አስመራጭ ኮሚቴ አባልነቴ ነጮቹን አልቀበልም አልኩኝ፡፡ ምክንያቱም እነዚህ ሰዎች ቅኝ ገዢዎች ናቸው፤ ዚምባብዌ ውስጥ ገንዘቡ የነሱ ነው፤ ከ7 በላይ ቴአትር ቤት አላቸው፡፡ የዚምባብዌ የቴአትር ባለሙያዎች ግን ከነዚህ ነጮች ቴአትር ቤት የመከራየት መብት ተነፍጓቸው ዛፍ ስር ነው የሚሰሩት፤ ስለዚህ ከተጠቋሚዎቹ ውስጥ ትክክለኛ ዚምባብዌያውያን መሆን አለባቸው አልኩኝ። ከዚምባብዌ የተወከለው ሰው ግን የኔን ውሳኔ ባለመቀበል ከነጮቹ ጋር ወግኖ ወጣ፡፡ በኋላ ይሄ ጥቁር የዚምባብዌ ዜጋ ለምን እንዲህ እንዳደረገ ሳጣራ፣ መንግስት የተቀበለውን እኛ እምቢ ለማለት ምን መብት አለን ብሎ በፍርሃት እነሱን መደገፉን ሰማሁ፡፡ በወቅቱ የተሰበሰብንበት አዳራሽ ከተለያዩ የአፍሪካ አገራት የመጡ ሰዎች እንጂ የዚምባብዌ አይደለም፤ ስለዚህ አንተን መምረጥ ነበር የፈለግነው አልነው፤ እሱ እሺ ለማለት ትንሽ ዘመም ቢልም ሌሎች ሰዎች ግን እሱን አንፈልግም አሉ፡፡
ከዚያስ?
ከዚያማ ሌላ አስመራጭ ኮሚቴ ምረጡ ብለን ከመድረክ ልንወርድ ስንል፤ ‹‹በቃ ደበበን ፕሬዚዳንት አድርገን መርጠናል፤ ሌላ ምንም ስብሰባና ቀጠሮ አንፈልግም›› አሉና የመግቢያ ሰነድ ተፈራርመው ለዩኔስኮ ላኩ፡፡ የዛን ጊዜ መጀመሪያ የ ITI የአፍሪካ አስተባባሪ ነበርኩኝ፤ በኋላም በአፍሪካ የተቋቋመው ማህበር ፕሬዚዳንት ሆኜ በመመረጤ ከኢንተርናሽናል ቴአትር ኢንስቲትዩት ጋር ለብዙ አመት አብረን ሰርተናል፡፡ ዩኔስኮ ‹‹ኢንሳይክሎፒዲያ ኮንቴምፖራሪ ቴአትር››ን ሲያሳትም፣ የአፍሪካው ክፍል ላይ የኤዲቶሪያል ቦርድ አባልም ነበርኩኝ፡፡
እስቲ ኢትዮጵያ የITI አባል እንድትሆን ስላደረግኸው ጥረት አውጋኝ?
እንግዲህ የዛሬ ሁለት ዓመት 53ኛውን የአለም የቴአትር ቀን ይህ አዲስ የተቋቋመ ዩኒቨርሲቲ፣ ያውም የተቋሙ አባል ሳይሆን ለማክበር ደፋ ቀና ሲሉ የነበሩት የዩኒቨርሲቲው የቴአትር መምህራንና ተማሪዎች ጋበዙኝ፡፡ በእውነት ያንን የወጣቶቹን ጥረትና ጥሩና ያማረ ዝግጅት ስመለከት እንባ ተናነቀኝ፤ እናም ያን ቀን አንድ ነገር ወሰንኩ፡፡
በቃ ከITI ጋር ሰፊ ቆይታ ስለነበረኝ የማውቃቸውን ሰዎች ለምኜም ቢሆን፣ የኢትዮጵያ የቴአትር ኢንስቲትዩት ማህፀን፣ ወልቂጤ ዩኒቨርስቲ መሆን አለበት የሚል ውሳኔ ላይ ደረስኩ፡፡ ማንም ለምን አደረግህ ሊለኝ አይችልም፤ መብቴ ነው። ከዚያ በኋላ ዘንድሮ እነዚህ ልጆች በበዓሉ ላይ ሊጋብዙኝ እንደሚችሉ ገምቻለሁ፤ እርግጠኛ ግን አይደለሁም፤ከጋበዙኝና ከጠሩኝ ግን አንድ ነገር ይዤ መሄድ አለብኝ ብዬ፣ ከITI ሰዎች ጋር ስፃፃፍ ነበር። በመጨረሻም እሺታቸውን ገለፁልኝ፡፡ ይህም ብቻ አይደለም፡፡ አሜሪካ ሎስ አንጀለስ የሚኖር አንድ መልካም ኢትዮጵያዊ ነበር የእኔን መፅሐፍ ያሳተመው፣ በአስቸኳይ መልዕክት አንድ መቶ ኮፒ ለወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ልኮ አስረክቤያቸዋለሁ። ሁለተኛ ደግሞ ለሁለት ዓመት የአባልነት ክፍያ የሚከፍልላቸውም አግኝቻለሁ፡፡ ፀሀይ አሳታሚ ነው መፅሐፌን ያሳተመው፡፡ አሳታሚው ሎያላ ዩኒቨርስቲ ውስጥ የሚገኝ ነው፤ ስለዚህ ሎያላ ዩኒቨርሲቲና ወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የእህትማማችነት ግንኙነት እንዲኖራቸው እየሰራ ይገኛል፡፡
በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የቴአትር መምህራንና ተማሪዎች የሚያደርጉት እንቅስቃሴ የኢትዮጵያ ቴአትርን በተመለከተ ምን ተስፋ ፈጠረብህ?
በጣም የሚገርምሽ በዚህ በወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ ያሉ መምህራን በሌሎቹ ቦታዎችና ዩኒቨርሲቲዎች የሚታየውን የተማሪና አስተማሪ እንደ ጌታና ሎሌ መተያየትን አላስፈላጊ ግንኙነት የሰበሩ ናቸው፡፡ በዩኒቨርሲቲው ትልልቅ ስልጣን ላይ ተቀምጠው ሙያውን አልተውትም። ሙያው ውስጥ ሲገቡ ከተማሪዎቻቸው እኩል መድረክ ላይ ለመሰለፍ፣ እኩል የሙያ አስተዋፅኦ ለማድረግ በጣም ፈቃደኛ ሆነው ነው ያገኘኋቸው፡፡ ይሄ በሙያው ላይ የሚታየኝ ትልቁ ተስፋና ለውጥ ነው፡፡ በዚሁ ከቀጠለ ለወደፊት ተማሪና አስተማሪ በመምህርና በደቀ መዝሙር ደረጃ እየተወያዩና ስህተታቸውን እየተራረሙ አብረው እያደጉ፣ ሙያውንም የሚያሳድጉት ይመስለኛል፤ ይሄ ትልቅ ተስፋ ነው፡፡
በመምህራንና ተማሪዎች መካከል ለምንድን ነው የጌታና ሎሌ ዓይነት ግንኙነት የሚኖረው?
ቀደም ሲል መምህሩ የተናገረውን ያለ ጥያቄ መቀበል ግድ ነበር፡፡ መምህሩ ይፈራል። አሁንም በአንዳንድ ዩኒቨርሲቲዎች ይሄ ሁኔታ የሚታይበትና የቀጠለበት አሰራር አለ፡፡ ተማሪዎቹ አስተማሪን ጥያቄ መጠየቅ የሚፈሩበት ሁኔታ ሁሉ አለ። አንዳንዱ መምህር ልከበር ከሚል አኳያ ነው፡፡ አንዳንድ መምህራን ደግሞ ከተማሪው የሚሰነዘረው ጥያቄ ስለሚከብዳቸው ተማሪዎቹን ማግለል ነው የሚፈልጉት፡፡ የወልቂጤዎቹ በእውነቱ እንደዚህ አይደሉም፤ ከተማሪው ጋር አብረው ይውላሉ፤ ከክፍል ውጭ ይወያያሉ፡፡ ከተማሪው ጋር መድረክ ላይ በሙያ ደረጃ አብረው ይሰለፋሉ። የሚታሙበት እንከን የሚገኝባቸው አይደሉም፤ ስለዚህ እነዚህ የመጪው ዘመን የቴአትር ተስፋዎች ናቸው፡፡
ጋሽ ደበበ አንተ በመሪ ተዋናይነት ስለተወንክበት በ1905 ስለተፃፈው የበጅሮንድ ተክለሀዋሪያት ተ/ማሪያም “አውሬዎቹ ኮሜዲ መሳለቂያ (ፋቡላ)” ቴአትር አጫውተኝ፡፡ በመተወንህ ምን ተሰማህ? አዲስ ስለመጣው “መልቲ ሚዲያ ቴአትር” ጥበብስ ምን ትላለህ?
በመጀመሪያ የዚህ ፕሮዳክሽን አካል ያደረጉኝን የወልቂጤ ዩኒቨርሲቲ የቴአትር ጥበባት ትምህርት ክፍል መምህራንን በጣም አመሰግናቸዋለሁ፡፡ በጣም ነው የተደሰትኩት፣ በጣም ነው የኮራሁትና የረካሁት በነዚህ ወጣቶች፡፡ በነገራችን ላይ ፕሮዳክሽኑ ሲሰራ ነበር ያየሁት፤ ከዚያ በኋላ ከተመልካቹ እኩል ነው ያየሁት። እነሱ ያቀረቡት በጅሮንድ ተክለሀዋሪያት እንዴት አድርገው ይሄን ቴአትር ፃፉት የሚለውን ነው፤ በጣም ምሉዕ ነው፡፡
እነዚህ ወጣቶች ፊልምንና እውን የሆነውን ቴአትር- ትወና አስተሳስረው ነው ያመጡት። “መልቲ ሚዲያ ቴአትር” በሚል ደራሲው እንዴት ፃፉት የሚለውን ወደፊት ለተማሪዎችም በሚያገለግል መልኩ ነው የሰሩት፡፡ አየሽ በፊልም በመድረክ በፅሁፍ መልክ ታግዞ የቀረበ ነው፡፡ ይህ አዲስ አሰራርና አስተሳሰብ በጣም የሚያስደስት ነው፡፡ በዚህ ቴአትር ላይ ከነዚህ ወጣቶች ጋር በመተወኔ በጣም ተደስቻለሁ፤ ወጣቶቹን አመሰግናለሁ፡፡
በዩኒቨርስቲው 55ኛው የአለም የቴአትር ቀን ላይ ከቀረቡ 8 ጥናታዊ ፅሁፎች መካከል በመቀሌ ዩኒቨርሲቲው ተካልኝ ገ/ሚካኤል የቀረበው ‹‹የቴአትር ትምህርት በኢትዮጵያ›› የተሰኘው ጥናታዊ ፅሁፍ፤ቴአትሩ ላይ የተጋረጡትን ዘርፈ ብዙ ችግሮችና  ፈተናዎች  ያመላከተ ነው፡፡ ብዙ መሠረት ልማት ባልተሟላበት፣ ባልፀደቀ ሥርዓት ትምህርት እያስተማሩ እንደሚገኙ ተጠቅሷል። ተባባሪ ፕሮፌሰር አቦነህ አሻግሬም የውጭው አገር ተሞክሮ በአገራችን እንዲተገበር በጥናታቸው ጠቁመዋል። ከሁለቱ የትኛው መቅደምና መከተል አለበት ትላለህ?
የአቦነህ ጥናት ምክር አዘል አስተዋፅኦ ያለው ነው ለምን? መንግስት ለስነ ትበቡ ለኪነ ትበቡ ለቴአትር ትምህርት ሊያደርግ የሚገባውን ነገር ነው ያስቀመጠው በሌላው አለም እየተደረገ ስለሆነ እዚህም ዘርፍ መደገፍ አለበት መንግስት ዘርፉን ቢደግፍ ይጠቀማል እንጂ ምን የሚጎዳው ነገር አለ ነው፡፡
ለምሳሌ ቀረጥን በተመለከተ ከቴአትር የሚወስደው ቀረጥ የመንግስትን የትኛውንም ቀዳዳ አይሞላም አንድን የመንግስት ሰራተኛ የአመት ደሞዝ እንኳን አይሸፍንም። ሰዎች ተነቃቅተው ለጥበቡ ልግስና በሚያደርጉበት ጊዜ ያ ገንዘብ ከቀረጡ ላየ የሚቀነስላቸው መሆኑን ቢያውቁ ማንንም ሳያስቸግሩ እነዚህ ሰዎች በሚሰጡት ድጋፍ ብቻ ትልቅ ደረጃ መድረስ ይቻል ነበር፡፡ ይሄንን ነው አቦነህ ያስቀመጠው የተካልኝ ጥናት በበኩሌ በጣም ያስደነገጠኝና ያሸማቀቀኝ ጥናት ነው፡፡ አንድ ቡና ቤት እኮ መፀዳጃ ክፍልህ ንፁህ አይደለም ተብሎ ይዘጋል፤ አንድ ሆስፒታል የሚያቀርበው የህክምና እርዳታ በህብረተሰቡ ላይ ትንሽ ህፀፅ ሲገኝበት ያንን አላሟላህም ተብሎ ይዘጋል፡፡ እነዚህ የተቋቋሙ ስምንት የቴአትር ጥበብ ዩኒቨርሲቲዎች ተማሪችን የሚያስተምሩበት እውቅና ባላገኘ ስርዓተ ትምህርት ነው፡፡ ነገ ይህንን ፈቃድ የሚሰጠው ተቋም ያገኛችሁት ዲግሪ ባልፀደቀ ካሪኩለም ነውና አላውቃችሁም ቢል እነዚህ ልጆች የት ነው የሚወድቁት ትምህርት ሚኒስቴር አይመለከተኝም ካለ ለሌላ ለሚመለከተው አካል አሳፎ ይሰጥ። እንዴትስ ነው ለሳምንት ዩኒቨርሲቲ ሶስት አራት አይነት ካሪኩለም የሚወጣው፡፡ ዩኒቨርስቲዎቹ በአንድ ኤኔት ሰርዓት ትምህርት በአንድ አይነት መንገድ ተማሪዎቹን ማሰልጠንና ማስመረቅ ይገባቸዋል፡፡ ያለበለዚያ ምስቅልቅሉ የወጣ ጉዳይ ነው የሚሆነው፡፡ ይሄ እንግዲህ ተመልካች የማጣት ጉዳይ ነው የሚል እምነት አለኝ፡፡ ለጥበቡ ምን አገባኝ የማለት ነገር ይመስለኛል፡፡
ግን እኮ እንደ ቴአትር ያሉ ጥበባትን መንግስት ለተለያዩ ጉዳዩች ይጠቀማል አይደለም እንዴ?
ለመጠቀሙማ በደንብ ይጠቀምባቸዋል ጥበቡን መጥቀም ነው እንጂ የተሳነው፡፡ እንደሚጠቀምበት ሁሉ ጥበቡ እንዲያድግና ጥበበኛው እንዲጠቀም ቢያደርግ ኖሮ መልካም ነበር፡፡ የተካልኝም ጥናት የሚያመላክተው ይሄንኑ ነው ባልተሟላ የሰው ሀይል ባልተሟላ መሰረት ልማትና ባለፀደቀ ካሪኩለም ተማሪዎችን እስተማርን ነው ያለው ይሄ ትክክል አይመስለኝም፡፡
በሌላው አለም የኪነ-ጥበብ መማክርት አለ ሙያውን ለማስከበር አርቲስቱን ይተባበራል መብቱን ያስከብራል እየተባለ ነው ለመሆኑ በአገራችን አርቲስቱ እርስ በእርስ የመተባበርና የመከባበር ባህል አለው ወይ ይህ ባልኖረበት ሁኔታ መብታችንን ይከበር ማለት ያስኬዳል ወይ? ሌላው የቀድሞ ጠቅላይ ሚኒስቴር መለስ ዜናዊ አርቲስቱን በሰበሰቡበት ወቅት ቤተ መንግስትና ኤርፖርት ገብተን እንድንቀርፅ ይፈቀድልን የሚልና ከጥበቡ ጋር ግንኙነት የሌለው ጥያቄ ከማንሰትና ትዝብት ውስጥ ከመግባት ባለፈ ለኪነ-ጥበቡ የሚበጅ ጥያቄ ሳያነሳ መበተኑ አሁን አልተከበርንም ለማለት ሙያው አልተከበረም ማለት አግባብ ነው ትላለህ?
በነገራችን ላይ ስለዚህ ስብሰባ ካነሳሽ አይቀር ስሜቴን ልናገር፡፡ እኔ ስብሰባውን እቤቴ ቁጭ ብ እንደ ማንኛውም ተመልካች ነበር በቴሌቪዥን ያየሁት፡፡
እንዴት? አልተጋበዝክም ነበር?
አልተጋበዝኩም፡፡ በዕለቱ በውስጤ የመጣው የመጀመሪያው ጥያቄ ማን ነው ይህን ስብሰባ ያዘጋጀው? እነማን ናቸው አርቲስቱን ወክለው የተገኙትና ጥሪ የተደረጉት? እማንስ ናቸው እየመሩት ያሉት የሚለው ነበር፡፡ በኋላ ሳየው በሙያው ምንም ብቃት የሌላቸው ሰዎች ነበሩ እንደ ቁንጮ ባለሙያ ሆነው ሲያጋፍሩት የነበሩት ስለ ሙያው ስለኪነ ጥበቡ ሊጠየቅ የሚገባው በርካታ ጥያቄ ምልቶ ነበርኮ አንድ የቴአትር ባለሙያ ካሜራ በነፃ ይግባልን ብሎ አይጠይቅም ይህን መጠየቅ ያለበት ነጋዴው ነው ምክንቱም ቴአትሩን እሰራው ያለው ነጋዴው አይደለም እንዴ ነጋዴ ስል በጅምላ መናገሬ አይደለም፡፡ አሁን ቴአትር እየሰራ ያለው ባለሃብቱ ነው ለማለት ነው። በጥበቡ ላይ የሚነግዱ ሰዎች ስላሉ ነው ነጋዴ እያልኩ ያለሁት፡፡ ቴአትረኛው ምን ሊደርግበት ነው ካሜራ በነፃ ይግባልኝ የሚለው? የጥበቡ ባለሙያ ካሜራ ከቀረፅ ነፃ ቢገባ የሚጠቀመው ምንድ ነው? ይልቅ የሚጠቅመው መብት ቢከበርለት ነበር፡፡ ለእሱ የሚጠቅመው የስራው ስራ እውቅና ቢያገኝለት ከብዙ ፈተናዎች ነፃ ቢሆንለት ነው። ስለዚህ ስብሰባውም በስብሰባውም ላይ የተነሳው ጥያቄ ትክክል አይደለም። በስብሰባውም አፍሬያለሁ በስብሰባው ባለመካፈሌም እግዛብሄርን አመስግኘዋለሁ። መጠየቅ አለበት ብሎ የጠበቀው ጥያቄ ባለመጠየቁ ጠቅላ ሚኒስትሩም ጥሏቸው ወጣ እኮ! ሙያተኛው ራሱ አልተሰባሰበም በተለያየ ምዕራፍ የተለያየ ፍላጎት ያላቸው ሰዎች ሙያተኛውን ተከፋፍለውታል፡፡
ኪነ ጥበቡና ጥበበኛው እንዲከበር ምን መደረግ አለበት ትላለህ?
አሁን ባነሳሺው ጥያቄ ላይ በምሰጠው ምላሽ ብዙዎች ሊጠሉኝ ይችላሉ፡፡ ባለቤቴና ሙያዬ እስካልጠሉኝ ድረስ ሌላው ቢጠላኝ ጉዳዬ አይደለም። የሆነ ሆኖ ሙያውን ከሸቀጥነት ወደ ጥበብነት ለመለወጥ ባለሙያው ፈቃደኛ መሆን አለበት፡፡ ምንም የሞያ ክህሎት የሌለው በሞያው ስልጠና የሌሎው ገንዘብ ስላለው ብቻ ፊልም ዳይሬክት ላደረግ ነው ብሎ ቢጠራን አልሄድም በበኩሌ፡፡ የፈለገው ገንዘብ ሊቀር ይችላል። በሙያው ሰልጥኖ ብቃት አግኝቶ የወጣ ከኔ በጣም በዕድሜ የሚያንስና ልጄ ሊሆን የሚችል ባለሙያ ግን ቢጠራኝ በነፃም ቢሆን እሰራለሁ ምክንቱመ እሱ አድጎ እንዲተካኝ ስምፈልግ፡፡ ነገር ግን አንድ ሰው ገንዘብ ስላለው ናና ስራ ቢለኝ ያኔ አልቃስ አይደለሁም፡፡ አላደረግውም ስለዚህ ችግሩን የፈጠረው ሁሉ ባለሙያው ስለሆነ ከዚያ ችግር ውስጥ ራሱን ማውጣት አለበት እንጂ ጣቱን ወደሌላው እየቀሰረ እንዲህ አደረገኝ እከሌ ይህን አላደረገልኝም የሚባል ነገር አይሰራም፡፡ ባለሙያው ችግሩን ያውቀዋል መፍትሄው ራሱ እንደሆነ ያውቀዋል ባለሙያው መብቱን ማስከበርና በመብቱ መጠቀም አለበት ስለዚህ ባለሙያው ከዚያ ችግር ራሱን ካላወጣ ምንም ማድረግ አይቻልም፡፡ ቁጭ ብሎ ሲያማርርና እዬዬ ሲል ከመኖር በስተቀር ቆይ እኔ እምለው ጦርነቱን ማን እንደዋጋለት ነው ባለሙያው የሚጠብቀው፡፡ በሙያው ላይ የተቃጣውን ጦርነት ሁሉ ባለሙያው በሰላማዊ መንገድ ታግሎ ማሸነፍ አለበት፡፡ እንደገናም በችግራቸው ላይ ተሰብስበው ተነጋግረው አንድ ሆነው መቅረብ ነው ያለባቸው፡፡ ተበታትነው ተለያይተው በየአቅጣጫው ሲሯሯጡ መንግስትም እኮ ግራ ይገባዋል፡፡ እዚህ አንድ ማህበር እዚያ ሌላ ማህበር ሌላ ቦታም እንዲሁ አነንደኛውን የፅዋ ማህበር አድርገውታልኮ የማሪያም የገብርኤል የጊዮርጊስና ፅዋ አይነት የእነዚህ አባላት እንኳን ከአንዱ ወደ አንዱ አይሄዱም ተከባብረው ነው የሚኖሩት ሀይማኖታዊ ሰርዓት ስላለው፡፡ እንዴ ሙያም እኮ የራሱ ሰርዓት አለው በስርዓት መሄድ አለበት፡፡ ለስንቱ ማህበር ነው ድጋፍ የሚያደርገው አካል ድጋፉን ሚሰጠው?

   ከዕለታት አንድ ቀን በአንድ ትልቅ አውቶቡስ በርካታ መንገደኞች ይጓዛሉ፡፡ ከተጓዦቹ መካከል አንዲት ህፃን ልጅ የያዘች እናት አለች፡፡ ልጇን እሹሩሩ ትላለች፤ ታባብላለች፡፡
በመካከል እዚያው ተጓዦች ዘንድ ያለ አንድ ዠርዣራ ሰካራም ከተቀመጠበት ይነሳል። እየተንገዳገደ፤ ፊት ለፊቷ ይቆምና ቁልቁል እያያት፤
“ስሚ ሴትዮ፤ እኔ በህይወቴ እንደዚህ ያለ አስቀያሚ ልጅ አይቼ አላውቅም” አላት እየተኮለታተፈ፡፡
ሴትዬዋ በመከፋትና በቁጣ መካከል ባለ ድምፅ፤
“ምን አገባህ! አርፈህ አትቀመጥም?” አለችው፡፡
“እኔ ቢያገባኝም ባያገባኝም ልጁ አስቀያሚ መሆኑን አይለውጠውም!” አላት ደግሞ።
ሴትዮይቱ በጣም ሆድ ባሳትና ስቅስቅ ብላ አለቀሰች፡፡
ተጓዡ ህዝብ በጣም ከማዘኑ የተነሳ አንዱ ተነሳና ያን ሰካራም ገፈተረው፡፡ ሌላው በቦቅስ ተቀበለው፡፡ ግርግር ተፈጠረ፡፡
ይሄ ሁሉ ሲሆን ሴትዮይቱ መንሰቅሰቋን ቀጠለች፡፡ እዬዬዋን አስተጋባች፡፡ ጩኸቷ በጣም ከመሰማቱ የተነሳ በመጨረሻ ሹፌሩ አውቶቡሱን ከመንገዱ ወደ ጥግ አደረገውና፣ ልቅሶዋን ወዳላቆመችው ሴት ዞሮ፤
“እሄውልሽ የእኔ እህት፤ ያ ጭንጫ ራስ ሰካራም ምን ክፉ ነገር እንደተናገረሽ አላውቅም፡፡ ሆኖም እንድትረጋጊ አሁን ሄጄ ሻይ ይዤልሽ እመጣለሁ፡፡ አንቺ ግን አይዞሽ፤ ረጋ በይ!”
አላትና ከዓይን ተሰወረ፡፡
በአቅራቢያው ወዳለ አንድ ሬስቶራንት ገብቶ፣
“ለአንድ ለከፋትና ሆድ ለባሳት ሴት የሚሆን ቆንጆ ሻይ ስጠኝ” አለው አስተናጋጁን፡፡
“ቅመም ይኑረው ጌታዬ?” አለና ጠየቀው ቦዩ፡፡
“አዎ፡፡ ያጣፍጠዋል ያልከውን ማናቸውንም ቅመም ጨምርበት፡፡ ብቻ ሴትዮዋን ሰላም ይስጣት”
“ሁሉንም አረጋለሁ፤ ጥቂት አረፍ ይበሉ”
ቆይቶ ሹፌሩ ወደ ሴትዮዋ ተመለሰና እንዲህ አላት፡-
“ተረጋጊ የእኔ እመቤት፡፡ ሁሉም ነገር ይረጋጋል፡፡ ታገሺ፡፡ ይሄውልሽ በጣም ምርጥ የሆነ፣ በቅመም ያበደ ሻይ አምጥቼልሻለሁ፡፡ ላንቺ ቀርቶ ለዚህ ዝንጀሮ ለመሰለ ልጅሽም ሙዝ ገዝቼለታለሁ!”
*          *       *
የችግሩን መንስኤ ሳናውቅ መፍትሄ እንፈልግ ማለት ተጨማሪ ችግር ወደ መሆን እንድናመራ ሊያደርገን ይችላል፡፡ ልጇ ተሰድቦባት ለምታነባ እናት፤ ምንም ዓይነት ማባበያ እንስጣት፣ መልሰን ልጇን እምንሰድብባት ከሆነ በቁስል ላይ ቁስል ጨመርንባት ማለት ነው፡፡ የህዝብን ችግር መንስኤ ሳናውቅ ጊዜያዊ መፍትሔ ብቻ በመፍጠር ጉዳዩን ገለነዋል ብለን ማሰብ ቢያንስ የዋህነት ነው፡፡ “አለባብሰው ቢያርሱ በአረም ይመለሱ” መሆኑን አለመዘንጋት ነው፡፡ ህዝብ፤ ቀን ጠብቆ፤ ይብስም ምሬቱን አመርቅዞ፣ እንደሚመጣ በጭራሽ አለመርሳት ነው፡፡
ሰዎችን ከሥልጣን ሥልጣን  ቦታ በመቀያየር መሰረታዊ ለውጥና መፍትሄ አናመጣም፡፡ ተሐድሶም ሆነ ጥልቅ - ተሐድሶ የኃላፊዎችን ውስጠ ሕሊናዊ መለወጥ በቅድሚያ ይጠይቃል፡፡ “ዕውነተኛ ንቃት የሚኖረው አንቂው አስቀድሞ ሲነቃ ነው” ይላሉ አበው፡፡ የአንቂዎች ከሙስና ፅዱ መሆን ወሳኝ ነው፡፡ የአንቂዎች ፍትሐዊ መሆን እጅግ ወሳኝ ነው፡፡ የጎሸ ይጠራ ዘንድ፣ የታመመው ይፈወስ ዘንድ፣ የደከመው ይጠነክር ዘንድ፣ የማይድን ጋንግሪን ቁስል ደረጃ የደረሰው፤ በመላ ተቆርጦ ይጣል ዘንድ፣ አይነኬ አይሞከሬ ነው የተባላ ሹም፣ ቡድን፣ ተቋም የግድ የሚፈተሽበት ዘዴ ይፈጠር ዘንድ፤ ወቅቱ ይጠይቃል፡፡ ከሁሉም በላይ ግን ቡድነኝነት (groupism)፤ የማይመለስ መዓት (irreversible catastrophe) ላይ ሊጥደን እንደሚችል ሳይመሽ መገንዘብ ጥበበኝነት ነው፡፡ የሚመለከተው አካል የተረጋጋ ቦታ ቆሞ ሊያጤነው የሚገባ ጉዳይ ነው፡፡ በመፈራራት አገር ወደ አዘቅት ስትወርድ እያዩ እርምጃ ሳይወስዱ እጅን አጣጥፎ መቀመጥ በታሪክ ያስጠይቃል፡፡ የሴራ መረቦችን መበጣጠስ ያሻል፡፡ ቀልባሽ (subversive) አካሄድን በንሥር ዓይን ማየት ለእርምጃ መውሰድ ዝግጁነትን ያመላክታል፡፡ ተናጋሪ ምላሶች የዕውነት ምስክር ናቸው ማለት አይቻልም፡፡ “ነገር አሳማሪ አድሮ፣ ሾተል ሰንዛሪ” እንዲሉ፣ ተጠንቅቆ መከታተል የአባት ነው፡፡ “እባብ ለእባብ፣ ይተያያል ካብ ለካብ” የዋዛ ተረት እንዳልሆነ ልብ ማለት የሚገባን ዛሬ ነው፡፡
ጎራና ወገን ለይቶ የእኔ ድምፅ የተለየ ቃና አለው ማለት፤ ትላንት ካሰመርኩት መስመር ውጪ ንቅንቅ አልልም ማለት፤ ቃል መግባትና አድሮ መሻር፣ ስብሰባን ረግጦ ለመውጣት ሁሉ ማኮብኮብ፣ ብቆጣም እመታሻለሁ፣ ብትቆጪም እመታሻለሁ ማለት፤ አሳሳቢ ነው፡፡ ዋናው ነገር በማናቸውም ተደራዳሪና ዕርቅ-ፈላጊ ወገን ላይ ኢ-ፍትሃዊ አካሄድ መከሰት የለበትም፡፡ ሆደ ሰፊነትና ብልህነት መቼም ቢሆን መሳሪያዎቻችን መሆናቸውን በብስለት ማየት፤ ለአገርና ለህዝብ ለቆመ ሁሉ ተስፋ ሰጪ ማረጋገጫው ነው፡፡ አለበለዚያ ግን “ሹሩባ ልትሰራ ሄዳ ፀጉሯን ተነጭታ መጣች”  የሚለው ብጤ ይሆናል! 

• ለመንበረ ፓትርያርኩ ሪፖርት እንዲያደርጉ ቢጠሩም ለመታዘዝ ፈቃደኛ አልኾኑም
                           • ለ19 ዓመታት የተከማቸውን የደብሩን ገንዘብ፣ የማኅበር ሀብት ነው፤ በሚል ክደዋል

       በኦስትርያ - ቪየና፣ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን ምእመናንን በመክፈልና የቤተ ክርስቲያኒቱን ሁለት ታቦታት ከንዋያተ ቅድሳታቸው ጋራ በማውጣት፣ የኢትዮጵያን ቅዱስ ሲኖዶስ አላውቅም፤ በማለት ኮብልለዋል የተባሉት የቀድሞው አስተዳዳሪ፣ መጋቤ ስብሐት አባ ብርሃኑ ደበበ ጉዳይ እያነጋገረ ነው፡፡
አስተዳዳሪው የኮበለሉት፣ ከቅዱስ ሲኖዶስ ለተላለፈላቸው  መመሪያ ባለመታዘዝ ከሓላፊነታቸው ከተነሡና በሌላ አስተዳዳሪ መተካታቸውን ተከትሎ እንደኾነ ተገልጿል፡፡
በኦስትርያ - ቪየና በምትገኘው የደብረ ሲና ቅድስት ኪዳነ ምሕረት ቤተ ክርስቲያን፣ ላለፉት 12 ዓመታት በአስተዳዳሪነት የቆዩት መጋቤ ስብሐት አባ ብርሃኑ፣ ከአስተዳደር ሥራዎች ጋራ በተያያዘ፣ ባለፈው ዓመት ጥቅምትና ኅዳር ወራት፣ በደብሩ ሰበካ ጉባኤና በምእመናን ተደጋጋሚ አቤቱታ የቀረቡባቸው ሲኾን፤ ችግሩን ለመፍታትና የተጓደለውን አገልግሎት ለማሟላት እንዲቻል፣ ንብረቱን ለሰበካ ጉባኤው አስረክበው ወደ አዲስ አበባ እንዲመለሱና ለመንበረ ፓትርያርክ የውጭ ግንኙነት መመሪያ ሪፖርት እንዲያደርጉ አስቸኳይ ትእዛዝ ተላልፎላቸው እንደነበር ተጠቅሷል፡፡
ይኹንና፣ “ለጠቅላይ ቤተ ክህነቱ የተላከው ደብዳቤ ለእኔም ይላክልኝ” የሚል ተገቢ ያልኾነ ጥያቄ በመጠየቅ በትእዛዙ መሠረት ወደ ሀገር ቤት ባለመመለሳቸው፣ ካለፈው ዓመት መጋቢት ጀምሮ ከአስተዳዳሪነታቸው ተነሥተው፣ መጋቤ ብሉይ አባ ዘተክለ ሃይማኖት ገብረ መስቀል በተባሉ ሌላ ሓላፊ መተካታቸው ታውቋል፡፡
በቅዱስ ሲኖዶስ የተመደቡት አዲሱ አስተዳዳሪ ወደ ስፍራው ቢጓዙም፣ መጋቤ ስብሐት አባ ብርሃኑ፣ የደብሩን ንዋያተ ቅድሳትና ንብረት ለማስረከብ ፈቃደኛ ባለመኾናቸውም በተፈጠረው ውዝግብ፣ ቤተ ክርስቲያኗን አዘግተው፣ ቍልፉን እስከማስወሰድ ደርሰው እንደነበር ተነግሯል፡፡
ብፁዕ ወቅዱስ ፓትርያርክ አቡነ ማትያስ፣ በኦስትርያ ለካቶሊካዊት ቤተ ክርስቲያን ካርዲናልና የጳጳሳት ጉባኤ ሰብሳቢ በጻፉት የትብብር ጥያቄ፤ ቤተ ክርስቲያኑን ለመክፈት ቢቻልም፣ የቀድሞው አስተዳዳሪ፣ የደብሩን የቅድስት ኪዳነ ምሕረትና የቅዱስ ገብርኤል ታቦታት ከንዋያተ ቅድሳታቸው ጋራ በማውጣትና ምእመናኑን በመክፈል ከቤተ ክርስቲያን ማዕከላዊ አስተዳደር ኮብልለዋል፤ ተብሏል፡፡ ላለፉት 19 ዓመታት ከተለያዩ የገቢ ምንጮች አስተዋፅኦ እየተደረገ የተቀመጠውን፣ ከ75ሺሕ ዩሮ በላይ የቤተ ክርስቲያኒቱን የባንክ ሒሳብ፣ ‹‹የማኅበር  ሀብት ነው፤›› በሚል ፍጹም ክሕደትን ፈጽመዋል፤ ይላል፣ የምእመናኑ አቤቱታ፡፡
ቀደም ሲል የሚመደቡት ሓላፊዎች፣ ከአስተዳደር ሥራቸው ጋራ በካቶሊክ ቤተ ክርስቲያን የሚሰጠውን ስኮላርሽፕ የመከታተል ዕድል እንደነበራቸውና ለመንበረ ፓትርያርኩ ጥሪም ታዛዥ እንደነበሩ የገለጹት ምእመናኑ፣ በውዝግቡ ሳቢያ ዕድሉ ሊሰረዝ እንደሚችል ጠቁመዋል፡፡
ጉዳዩም በሕግ ሒደት ላይ የሚገኝ ሲኾን፣ አስተዳዳሪው በችሎት ቀርበው፣ ‹‹የኢትዮጵያን ቅዱስ ሲኖዶስ አላውቅም›› በማለት ክሡን መካዳቸውን ለማወቅ ተችሏል፡፡