Administrator

Administrator

በደብረዘይት (ቢሾፍቱ) ከተማና አካባቢዋ የሥነጽሑፍ አፍቃሪያን የተቋቋመው “ሆራቡላ ሥነጽሑፍ ማሕበር” 20ኛ የስነጽሑፍ ዝግጅቱን የፊታችን ሰኞ ከቀኑ 7፡30 በከተማው ሕይወት ሲኒማ ትንሿ አዳራሽ እንደሚያቀርብ አስታወቀ፡፡ “የብዕር አዝመራ” በሚል ርእስ በሚቀርበው ዝግጅት፤ የማሕበሩ አባላት የግጥም፣ መነባንብ፣ ጭውውት እና ሌሎች ኪነጥበባዊ ሥራዎቻቸውን ያቀርባሉ፡፡ ከዚህም በተጨማሪ ዝነኛው የፊልም ተዋናይ ግሩም ኤርምያስ፤የህይወትና የሙያ ተመክሮውን ለማህበሩ አባላት እንደሚያካፍል ለማወቅ ተችሏል፡፡

በ1940ዎቹ የተመሠረተው ጐንደር ዩኒቨርስቲ የተመሰረተበትን የ60ኛ አመት የአልማዝ ኢዮቤልዩ በዓል ለአንድ ዓመት በተለያዩ ዝግጅቶች በማክበር ላይ ይገኛል፡፡ ዩኒቨርስቲው ዘንድሮ ከሚያስመርቃቸው ተማሪዎች በተጨማሪ በዓሉን ምክንያት በማድረግ 3ሺ የቀድሞ ተማሪዎችንም በድጋሚ ያስመርቃል ተብሏል፡፡ ዩኒቨርስቲው በማስገንባት ላይ ያለውን ሆስፒታልም በሰኔ ወር እንደሚያስመርቅ ታውቋል፡፡ በታህሳስ 25 ቀን 2000 ዓ.ም በይፋ የተከፈተው የዩኒቨርስቲው ክብረ በአል የተለያዩ ዝግጅቶች የቀረቡበት ሲሆን ክብረ በአሉ እስከ ሰኔ ወር መጨረሻ ድረስ ይዘልቃል ተብሏል፡፡ ዩኒቨርስቲው ባካሄደው የ6 ኪ.ሜ የሩጫ ውድድር ላይ ከ2000 በላይ የተሳተፉ ሲሆን የሆቴልና ቱሪዝም ተማሪዎች ለቡርባክስ ህዝቦች መታሰቢያ ያደረጉትን የአዝማሪ ቅኝት አቅርበዋል፡፡ ዩኒቨርስቲው ከመንግስት ጋር በመሆን በማስገንባት ላይ ያለው ባለ አንድ ሺ መኝታ ሪፈራል ሆስፒታል በሰኔ ወር እንደሚመረቅ ተነግሯል፡፡

The secret በተሰኘው የመጀመሪያ መጽሐፏ ከፍተኛ ዝናን የተቀዳጀችው አውስትራሊያዊ ደራሲ ርሆንዳ ባይርኔ The hero በሚል ያወጣችው ሦስተኛ መጽሐፏ “ጀግና” ተብሎ ወደ አማርኛ ተተረጐመ፡፡ መጽሐፉን የተረጐመው ብርሃኑ በላቸው ነው፡፡ “እያንዳንዳችን ወደዚህች ምድር የመጣነው በየራሳችን መንገድ ራሳችንንና ዓለምን የማበልጸግ ዓላማ ይዘን ነው” የሚለው መጽሐፉ፤ “አንተም ልዩ ነህና ለስኬት ተዘጋጅ” ይላል፡፡ 182 ገፆች ያሉት መጽሐፉ፤ በ40.50 እየተሸጠ ነው፡፡

በገጣሚ ሲሳይ ታደሰ /ዘ-ለገሐሬ/ የተፃፉ የግጥም ስብስቦችን የያዘው ‹‹ለፍቅራችሁ›› የተሰኘ የግጥም መድብል ሰሞኑን ለንባብ በቃ፡፡ 106 ግጥሞችን ያካተተው መድበሉ፤ “ለፍቅራችሁ” የሚል ርዕስ የተሰጠው መጽሐፉ ለህትመት እንዲበቃ ያገዙትን ሁሉ ለማመስገን እንደሆነ ገጣሚው ገልጿል፡፡ የግጥሙ መድበል ለአገር ውስጥ በ30 ብር፤ ለውጭ ደግሞ በ15 ዶላር ይሸጣል፡፡

በአስፋው መኮንን የተፃፈውና አስቂኝ፣ ቀልዶችና ቁምነገሮች የተካተቱበት መፅሀፍ ሰሞኑን ለንባብ በቅቷል፡፡ በአገራችን በቃል የሚነገሩ በርካታ አዝናኝና ቁም ነገር አስተማሪ ቀልዶች ቢኖሩም ብዙዎቹ በመፃህፍት ተፅፈው ስለማይቀመጡ የሚረሱና የሚደበዝዙ ይሆናሉ፤ ስለዚህም መመዝገብ አለባቸው ብሏል አዘጋጁ፡፡ በ158 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፤ በ35 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡

Saturday, 11 January 2014 12:11

“አለሁ ---- አልሞትኩም”

ረቡዕ ማታ በዛሚ 90.7 ኤፍ ኤም ሬዲዮ ላይ “አርቲስት ፈለቀ አበበ አረፈ” በሚል በስህተት በተነበበ ዜና እረፍት

ምክንያት አርቲስቱ፣ ቤተሰቦቹ፣ጓደኞቹና አድናቂዎቹ እስከ ሀሙስ እለት ተረብሸው ነበር፡፡ በርካቶች ዜናውን ባለማመን

ነገሩን ለማረጋገጥ አርቲስት ፈለቀ አበበ ተንቀሳቃሽ ስልክ ላይ ሲደውሉ ማምሸታቸውንና መዋላቸውን አርቲስቱ

ገልጿል፡፡ በስህተት ከተሰራጨው ዜና እረፍት በኋላ አርቲስት ፈለቀ የማር ውሃ አበበ ስለተፈጠረበት ስሜትና አጠቃላይ

ሁኔታ ከጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ጋር  አጭር ቃለምልልስ አድርጓል፡፡

የሞትህን ዜና በምን ሁኔታ ሰማህ?
ረቡዕ ወደ ማታ ቤት ቁጭ ብዬ እየሰራሁ ሳለሁ፣ ባልተለመደ መልኩ ስልኮች በተከታታይ መደወል ጀመሩ፡፡ አስደንጋጭ

ነበር፡፡ ብቻ የሆነ ነገር እንዳለ ያስታውቃል፡፡
ዜና እረፍትህን ሰምተው መደወላቸውን እንዴት አወቅህ?
አንዱን ጓደኛዬን በድፍረት ጠየቅሁት፡፡ ምክንያቱም በዚህ ፍጥነት በተከታታይ ሲደወል ለእኔ የተለመደ አይደለም፡፡

“ምንድን ነው ነገሩ? አካባቢው ላይ የተፈጠረ ነገር አለ እንዴ? ብዙ ሰው በተከታታይ እየደወለልኝ ነው” ብዬ

ስጠይቅ፤“አይ ሞተሀል ተብሎ በሬዲዮ ተነግሮ ነው” ሲለኝ ክው ብዬ ደነገጥኩኝ፡፡ ደግሞ ያስታውቃል፤ አንዳንዶቹ ልክ

ስልኬን አንስቼ “ሀሎ” ስላቸው ቶሎ ይዘጉታል። ብቻ መኖሬን ነው ማወቅ የሚፈልጉት፡፡ እንደዚህ ካደረጉት ውስጥ

ጓደኛዬ አርቲስት ሰለሞን ቦጋለ አንዱ ነው፡፡ አማኑኤል መሀሪ እንዲሁም ቤተሰቦቼም ድምፄን ሰምተው ብቻ ስልክ

ዘግተዋል፡፡ ምክንያቱም ወደ ቤተሰቦቼም ይደወል ነበር፡፡ ከውጭ አገር ሁሉ የስልክ ጋጋታው ሊያቆም አልቻለም፡፡
ሲደውሉልህ የሰዎች ስሜት እንዴት ነበር?
በጣም ህመም የሆነብኝ እሱ ነው፤ በጣም የሚያለቅሱና ኡኡ የሚሉ ነበሩ (ለቅሶ…) በጣም ያሳዝናሉ፤ እኔም አብሬያቸው

አለቅስ ነበር (ረጅም ለቅሶ)…
ሬዲዮ ጣቢያው ጋ አልደወልክም ?
ትንሽ ቆይቶ--- ከዛሚ 90.7 ኤፍ ኤም ደወሉልኝ፡፡ “በስህተት ነው ፈለቀ አበበ ሞተ ያልነው፤ የሞተው ግን አርቲስት

ፈለቀ ጣሴ ነው፤ አንተ በጣም ታዋቂ ስለሆንክ ፈለቀ ስንል አፋችን ላይ የገባው የአንተ አባት ስም ነው” አሉኝ፡፡ ነገር

ግን ሰው በጣም ያለቅሳል፤ በጣም ያሳዝናል፡፡
ይቅርታ ጠየቁ ወይስ----
እኔን በግሌ ይቅርታ ጠይቀውኛል፡፡ አድማጮችን ይቅርታ ይጠይቁ አይጠይቁ አላውቅሁም፡፡ ነገር ግን በነገሩ በጣም

አዝኛለሁ፡፡ ማንም ከሞት አይቀርም ግን እንዲህ ቀላል የሚመስሉ ስህተቶች ከባድ ጉዳት ያመጣሉ፡፡ ለምሳሌ በድንጋጤ

ልቡ ቀጥ የሚል ቤተሰብ፤ ወዳጅ ዘመድ ይኖራል፤ መሞት አለ --- ስንት ነገር አለ፡፡
በዚህ ድንገተኛ ክስተት ምን ተረዳህ?
እንዴ… በጣም በጣም ተገረምኩ እንጂ! ይህን ያህል ሰው ይወደኛል ወይ ነው ያልኩት፡፡ በጣም ደነቀኝ፡፡
ዜና እረፍትህ ከተነገረ ጀምሮ ምን ያህል ሰው ደውሎልሀል?
ከ500 በላይ ስልክ ተደውሏል፤ በግምት ወደ 600 ሳይጠጋ አይቀርም፡፡
ከዚህ በስህተት ከተሰራጨ ዜና እረፍት መልካም አጋጣሚ የምትለው ነገር አለ?
 እንደውም በጣም እድለኛ ነኝ አልኩኝ፡፡ በቁሜ ይህን ያህል ሰው እንደሚወደኝ ማየት ችያለሁ፡፡ ግርምቴ እስካሁን

አልቆመም፡፡
ከዚህ በፊት ያልሞተ ሰው ሞተ ተብሎ የተነገረበትን አጋጣሚ ታውቅ ነበር?
ሰምቼ አውቃለሁ፡፡ ነገር ግን ብዙዎቹን የሰማኋቸው ዛሬ (ሐሙስ ማለቱ ነው) ነው፡፡ ለምሳሌ ጥላሁን ጉግሳ የሚባል

ሌላ አርቲስት ሲሞት፣ በስም መመሳሰል በህይወት ያለው ጥላሁን የመሰለበት አጋጣሚ  ትዝ ይለኛል፡፡ ሌላ ጊዜ

በቴሌቪዥን አርቲስት ሲራክ ታደሰ ሲሞት፣ የአርቲስት አለሙ ገ/አብን ፎቶ ማሳየታቸው ትዝ ይለኛል፡፡ ያጋጥማል ነገር

ግን ሰው የሚያለቅሰው… መንገድ ላይ ሲያዩኝ የሚሆኑት ሁኔታ በጣም ያሳዝናል፡፡
አሁን እንዴት ነው ስልኩ ቀነሰ? አንተስ ተረጋጋህ?
ያው እየተረጋጋሁ ነው፡፡ አንድ ነገር ወደ አዕምሮዬ መጣ፡፡ የህይወት እስትንፋስን የሚሰጠው እግዚአብሔር ነው፡፡

የምንኖረውም እግዚአብሔር የፈቀደልንን ያህል ነው፡፡ ማናችንም ከተቆረጠልን ቀን አናልፍም፡፡ ግን እዛው ቤቴ ውስጥ

ቁጭ ብዬ፤ “አሁንስ ለመኖሬ ምን ማረጋገጫ አለ” ብዬ መፈላሰፍ ጀመርኩኝ፡፡ ከዚያ “ኦኬ በቃ አለሁ ማለት ነው…”

ማለት ጀመርኩኝ፡፡ አንዳንዶች እኮ “እርግጠኛ ነህ ፈለቀ ነህ የምታናግረኝ” ብለውኛል፡፡ ስለሞት ብዙ ነገር ነው

ያሰብኩት፡፡ ከምንወለድበት ቀን ይልቅ የሞት ቀን ይሻላል የሚለውንም አሰብኩኝ፡፡ እንደውም የአዲስ አድማስ ባለቤትና

መሥራች አሰፋ ጎሳዬ  ሲሞት አዲስ አድማስ ግቢ ሆኜ  የፃፍኩት ግጥም ነበር፡፡
ትዝ ይልሃል ---ምን የሚል ነው?
ቢርቅም አይጠፋም ይልቃል ከሽቶ
በሰው ልብ ይኖራል ከመቃብር ሸሽቶ፡፡   የሚል ነበር፡፡ አየሽ --- በዚህ አጋጣሚ ያየሁት የሰው ፍቅር፤ የበለጠ

የምሰራበትና መልካም ያልሆኑ ነገሮች ካሉኝም ለማሻሻልና ጥሩ ለማድረግ የምተጋበት ነገር ተፈጥሯል፡፡ የበለጠ መልካም

ሆኜ እንዳልፍ የሚያደርግ ጥሪም ነው፡፡ ደጋግሜ የምነግርሽ… ሰው ለእኔ የሆነው ነገር ገርሞኛል… እንዲህ ነው ወይ

የምትወዱኝ ነው ያልኩት፡፡
አንዳንዴ ሞት የሚያናድደው ከሞትክ በኋላ ሰው ለአንተ ያለውን ፍቅርም ሆነ ጥላቻ ማየት ባለመቻሉ  ነው አይደለ?
እውነት ነው፡፡ እህቴም እንደዚህ ነው ያለችው፡፡ እህቴ ምስጢር ደምሴ ስትነግረኝ፤ መንግስቱ የተባለ ደራሲ “ሞቻለሁ”

ብሎ ቀጨኔ መድሀኒዓለም ሰው ተሰብስቦ ዋይ ዋይ ሲል፣ እሱ ተደብቆ ማን ቀብር እንደመጣና እንዳልመጣ፣ ማን ከልቡ

እንዳዘነና እንዳላዘነ ይመለከት ነበር፡፡ ይሄ ይገርማል። እሱ አስቦበትና ተዘጋጅቶ ነው፡፡ እኔ ደግሞ ከዚህ በተቃራኒው

ሌሎች በፈጠሩት ስህተት፣ የህዝቡን ፍቅር አይቼበታለሁ፡፡ እኔ ልሳቀቅ፣ እኔ ልደንግጥላቸው (ለቅሶ…)
የሞትህ ዜና ሲነገር ስራ ላይ እንደነበርክ ነግረኸኛል፡፡ ምን እየሰራህ ነበር?
የመጽሐፍ ቅዱሱን ዮሐንስ ራዕይን በትረካ መልክ ለማቅረብ  እየተረጐምኩ ነበር፡፡ በመተርጐም ላይ ሳለሁ ነው ስልኩ

በተደጋጋሚ መደወል የጀመረው። ሀሙስ ጠዋት ከቤት ስወጣ ገርጂ አካባቢ “ዊሽ ስቱዲዮ” የሚባል ፎቶ ቤት አለ፤ ፎቶ

ሲያነሱኝ አየሁ፡፡
ለምን እንደሆነ አልጠየቅሃቸውም?
አልጠየቅኳቸውም፡፡ እነሱ ማታ ሞቷል መባሉን ሰምተው አድረው ኖሮ፣ ፎቶ ካነሱኝ በኋላ “Fele this morning”

ብለው ፌስ ቡክ ላይ ፖስት አድርገውኝ አየሁ፡፡ ሌላም ሰው “Still alive” ብሎ ፖስት አድርጓል --- እና የሚገርም

ነው፡፡
እና አሁን ምን ትላለህ?
አለሁ አልሞትኩም፤ ፈጣሪ እስከፈቀደልኝ እኖራለሁ፡፡ የሞተውን ወዳጃችንን ፈለቀ ጣሴንም ነፍሱን ይማርልን፡፡ ማርክ

ትዌይን  ያለውን እናስታውስና እንጨርስ፤ “ሞቴን በተመለከተ የወጣው ዘገባ ያለቅጥ  ተጋንኗል” እናም አልሞትኩም።

በዚህ አጋጣሚ አንዱ ጓደኛዬ መኪና እየነዳ “ፈለቀ አበበ ሞተ” ሲባል በድንጋጤ መኪናውን መቆጣጠር አቅቶት

ከመስመር ወጥቶ ሊጋጭ ለትንሽ ነው የተረፈው፡፡ እህቴም ቀድማ አልሰማችም እንጂ በልብ ድካም ትሞት ነበር፡፡

ስለዚህ ጋዜጠኝነት ትልቅና የተከበረ ሞያ በመሆኑ በጥንቃቄ ሊያዝና ሊከበር ይገባል እንጂ በቸልታ የሚሰራበት

አለመሆኑን ልገልጽ እወዳለሁ፡፡ የኢትዮጵያን ህዝብ እግዚአብሔር ያክብርልኝ፤ እኔም እወዳችኋለሁ፤ ስለተጨነቃችሁ

ስላዘናችሁልኝ አከብራችኋለሁ እላለሁ፤ አመሰግናለሁ፡፡  

Saturday, 11 January 2014 12:06

የቀን ብዙ

አድረን ልንገናኝ….
ነግቶ ልትመጪልኝ….
ለአንድ ቀን ባጣሁሽ፣
በዚሁ ቀን ብቻ - ብዙ ቀን ናፈኩሽ፡፡

ማዕድኑ ሰው
እግዜር አመዛዝኖ፣
ከአፈሩ ዘግኖ፣
መሬት ላይ በትኖ…
‹‹ሰው ሁን›› ካለው ወዲህ…
መኖር ያልደፈረ…
መሞት ያልጀመረ…
ለአንዱም ያልበቃ፣
በአንዱም ያልነቃ፣
ስንት አለ ጥሬ ዕቃ!?

የሴት ልጅ ነኝ
የሴት ልጅ መባሌ - ቂም አያስይዘኝም፣
ምክንያቱም አባቴ - አላረገዘኝም፡፡
        በገጣሚ ሲሳይታደሰ /ዘ-ለገሐሬ/

        ሶስተኛው መርህ የንግድ ተቋማት ለወጣት ሰራተኞች፣ ለወላጆች እንዲሁም ለተንከባካቢዎቻቸው ምቹ የሆነና አቅምን ያገናዘበ የስራ አከባቢን መፍጠር እንዳለባቸው ያትታል፡፡ ሰነዱ እንደሚያስረዳው ወጣት ሰራተኞች ስንል በህግ ለስራ ከተፈቀደው ዝቅተኛ የእድሜ ወሰን(14 አመት) የዘለሉና በገቢ ማስገኛ ስራዎች ላይ ተሰማርተው የሚገኙትን ነው ፡፡ የእነዚህ ወጣት ሰራተኞች ስራ ወይም የስራ ሁኔታ አደገኛ በሚሆንበት ጊዜም ከጉልበት ብዝበዛ ጋር ሊዛመድ የሚችልበት ሁኔታ አለ፡፡ መርሁ በተለይም ለነዚህ ወጣት ሰራተኞች የመስራት ፣ከአደጋ ነጻ የሆነ የስራ አከባቢ የማግኘት፣ጾታን ያማከሉ የውሃና የንጽህና መጠበቂያ አቅርቦቶችን ማግኘት ላይ አትኩሮት በመስጠት እንዲሰራ ግፊት ያደርጋል ስለዚህም የንግድ ተቋማቱ የእነዚህ ወጣት ሰራተኞች ጥቅም ከግምት በማስገባት ይህን ጉዳይ የሚያሥተዳድር መመሪያ እንደሚያስፈልጋቸው ያስረዳል፡፡በተጨማሪም የንግድ ተቋማቱ የወጣት ሰራተኞችን ጤና ማህበራዊ ደህንነት እንዲሁም ተከታታየይነት ያለው አቅም ግንባታን ያማከለ ምቹ የስራ ሄኔታና መፍጠር እንዳለባቸው ሃላፊነት ይሰጣል፡፡በተጨማሪም እነዚሁ ተቋማት ላረገዙ& ጡት ለሚያጠቡ እናቶች፣ለተንከባካቢዎች እንዲሁም ለስደተኛ ሰራተኞች ላይ ልዩ ትኩረት ማድረግ እንዳለባቸው ያስገነዝባል፡፡

አራተኛው መርህ የሚያተኩረው የንግድ ተቋማቱ በሚያከናዉኗቸው እንቅስቃሴዎች እና በአቅርቦታቸው የህጻናትን ደህንነትና ጥበቃን የማረጋገጥ ሃላፊነት እንዳለባቸው ያትታል፡፡ መርሁ የህጻናት እንዲሁም የወጣት ሰራተኞችን ጥቃትና ብዝበዛን ብሎም ደህንነታቸውን አደጋ ላይ ሊጥል የሚችል ማንኛውም የንግድ እንቅስቃሴ በመከላለክለና ፈጣን ምላሽ ለመስጠት የሚያስችል መመሪያ ማካተትን እንዲሁም አግባብነት ያለው እርምጃ ስለመውሰዳቸው የማረጋገጥ ሃላፊነት እንዳለባቸው ያስገነዝባል፡፡ በተጨማሪም መርሁ የንግድ ተቋማት የህጻናትን ደህንነትን አስመልክቶ በዘላቂነት ሊተዳደሩበት የሚገባ ፖሊሲ ሊኖራቸው እንደሚገባና በሰነዱ ላይም ቀጣይነት ያለው ስልጠና ከመስጠት ባሻገር ሊሎች ተመሳሳይ ተቋማትም ይህን መመሪያ እንዲያካትቱ ማበረታታትና ተነሳሽነትን መፍጠር እንዳለባቸው ያስረዳል፡፡ የንግድ ተቋማቱ የሚያመርቷቸው ምርቶችና የሚሰጧቸው አገልግሎቶች ከህጻናት ጥቅሞች ጋር የማይጻረሩ እንዲያውም ደጋፊ መሆናቸውን ማረጋገጥ የሚለው የአምስተኛው መርህ ዋነኛ መልእክት ነው ፡፡

በመርሁ መሰረትም ህጻናት ሊጠቀሙበት ብሎም ተጠቃሚ ሊሆኑ ይችላሉ ተብለው የሚታሰቡ ማንኛውም ምርቶችና አገልግሎቶች የአለም አቀፍ እና ሀገር አቀፍ ጥራታቸውን የጠበቁ ስለመሆናቸው፣ደህንነታቸው የተጠበቀ ስለመሆኑና ምንም አይነት የአካል፣የአእምሮና ሞራላዊ ጉዳት ላለማስከተላቸው ቅድሚያ መረጋገጥ እንዳለበት ይገልጻል፡፡በተጨማሪም የንግድ ተቋማቱ የሚያመርቷቸው ምርቶች ወይም የሚሰጧቸው አገልግሎቶች ለህጻናት ጥቃትና ብዝበዛ መሳሪያነት እንዳይውል ለመከላከል የራሳቸውን ጥረት የማድረግን ሃላፊነት ያስረዳል፡፡በዚህ መርህ መሰረት የንግድ ተቋማት ሃላፊነት የሚያጠነጥነው የምርትና አገልግሎታቸውን አቅርቦትና ስርጭት ተደራሽነት በማስፋት የህጻናት ጥቅሞች ማስጠበቅ ነው፡፡

Saturday, 11 January 2014 11:40

ዋልያዎቹ ከቻን በኋላስ…

         3ኛው የአፍሪካ አገራት የእግር ኳስ ሻምፒዮንሺፕ ዛሬ በኬፕታውን ሲጀመር በምድብ 3 የመጀመርያ ጨዋታውን ሰኞ ከሊቢያ ጋር የሚያደርገው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ትናንት ወደ ደቡብ አፍሪካ አምርቷል፡፡ ኮንጎ ለውድድሩ በ2013 የመጨረሻ ቀን ደቡብ አፍሪካ በመግባት ከ15 እንግዳ ብሄራዊ ቡድኖች የመጀመርያዋ ስትሆን ሊቢያ በሳምንቱ አጋማሽ ላይ ገብታ እየተዘጋጀች ነው፡፡ ጋና ያለፈውን ሰሞን በናሚቢያ ስትዘጋጅ ቆይታለች፡፡ የቻን ውድድር ሁሉም ጨዋታዎች በዲኤስቲቪ “ሱፐር ስፖርት 4” እና በጎቲቪ “ሱፐር ሴሌክት” ቻናሎች የቀጥታ ስርጭት እንደሚኖራቸውም ሲታወቅ የኢትዮጵያ ሬዲዮና ቴሌቭዥን ድርጅት በውድድሩ ላይ የዘገባ ሽፋን ከመስጠት ባሻገር የቀጥታ ስርጭት አይኖረውም፡፡ 3ኛው የቻን ውድድር የሚዘጋጅባቸው ኬፕታውን፤ ብሎምፎንቴንና ፖልክዋኔ ከተሞች በስታድዬም ትኬት ሽያጭ አልተሳካላቸውም፡፡ የመክፈቻው ስነስርዓት 54ሺ ተመልካች በሚይዘው የኬፕታውን ስታድዬም ላይ በዛሬው ዕለት ሲከናወን ለመጀመሪያዎቹ ሁለት ጨዋታዎች 10ሺ ትኬት መሸጡን ያመለከቱ ዘገባዎች በብሎምፎንቴንና ፖልክዋኔ ከተሞች የቻን ትኬቶች በቅናሽ ቢቀርቡም እንደተጠበቀው አልሆነም ተብሏል፡፡ አዘጋጆቹ በደቡብ አፍሪካ የሚኖሩ የኢትዮጵያ፤ ዲሪ ኮንጎ፤ ናይጄርያና ዚምባቡዌ ዜጎች ለውድድሩ ድምቀት ይፈጥራሉ በሚል ተስፋ አድርገዋል፡፡

የቻን ውድድር ለተሳታፊዎቹ ለ16ቱ ብሄራዊ ቡድኖች መጠናከር ከማገዙም በላይ አንዳንዶቹ የአህጉሪቱን ጠንካራ ቡድኖች በመግጠም ልምድ ያገኙበታል፡፡ በወዳጅነት ጨዋታ ደረጃ የሚፈረጀው ውድድሩ የፊፋ ወርሃዊ እግር ኳስ ደረጃን በውጤት በማሻሻል ከሁለት ወራት በኋላ ለ2015 የአፍሪካ ዋንጫ ለሚደረገው ድልድልም ወሳኝ ይሆናል፡፡ በአፍሪካ ትልልቅ ሊግ ውድድሮች ተሳታፊ ለሆኑ ክለቦች የሚሰሩ በርካታ የተጨዋች መልማዮች በቻን ውድድር ይኖራሉ፡፡ በቻን ውድድር ከኢትዮጵያ በጉጉት የተጠበቁት አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ናቸው፡፡ ወደ ደቡብ አፍሪካ ከማቅናታቸው በፊት ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በኢንተር ኮንትኔታል ሆቴል ልዩ ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡ ‹‹አዲስ ነገር እንፈልግ፤ ለለውጥ ራሳችንን እናምጣ፤ ለብሄራዊ ቡድን ምን ይደረግ፤ ሰፋ ባለ ነገር ብንወያይ እመርጣለሁ፡፡ የእድገት አመላካች የሆኑ ጉዳዮች ላይ መስራት ያስፈልገናል፡፡ ይህ የናንተ ትውልድ ነው፡፡ በፊት የማናውቀው ታሪክ ውስጥ ነው ያለነው፡፡

ለአፍሪካ ዋንጫ ከ31 ዓመታት መራቅ በኋላ ተሳትፈናል፡፡ እስቲ በቀጣይ ተሳትፏችን እንዴት ማደግ አለበት በሚል እንጠያየቅ፡፡…. ይህ ቡድን የናንተ ነው፡፡ እኔ ከአሁን በኋላ 30 ዓመት ለመቆየት አልችልም፡፡ ከእንግዲህ ለኢንተርናሽናል ውድድሮች ማለፍ እና መሳተፍ አለብን፤ ለምን ውጤቱ የህዝብ ነው፡፡›› ብለው አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በጋዜጣዊ መግለጫው ተናገሩ፡፡ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ከቻን በኋላ በ2015 በሞሮኮ ለሚደረገው 30ኛው የአፍሪካ ዋንጫ፤ በ2018 በራሽያ ለሚደረገው 21ኛው ዓለም ዋንጫና በቻን ውድድር እንዲያልፍ የሚያስፈልገውን ጥረት በመጠቆም ጥሪ ማቅረብ ዋና ትኩረታቸው ነበር፡፡ በተጨዋቾች ምርጫ፤ ዝግጅትና፤ ዲሲፕሊን ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እንደገለፁት የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ለቻን ያደረገው ዝግጅት የተፈለገውን ያህል የተጨዋቾች ብዛት አካትቶ የተሰራበት አልነበረም። ከካፍ የተጨዋቾች ዝርዝር ማሳወቂያ መመርያ ቀነገደብ የመጀመርያው መጨናነቅ ነበር፡፡ ቀነገደቡ ያለፈባቸው አንዳንድ ተጨዋቾች የህክምና ምርመራውን ባለማድረጋቸው ሊሳተፉ አልቻሉም፡፡

በሌላ በኩል ባለፉት ሁለት ዓመታት በብሄራዊ ቡድኑ ቁልፍ ሚና የነበራቸው ወሳኝ ተጨዋቾችን ለመተካት የነበረው ሂደት ፈተና ነበር ፡፡ አስቀድመው የነበሩት ውጤታማ ተጨዋቾች ከአገር ውጭ ባሉ ክለቦች በመጫወታቸው በቡድኑ ሊያዙ አለመቻላቸው በዝግጅቱ ላይ ክፍተት ፈጥሮ እንደነበር የገለፁት አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው፤ በተጨዋች ምርጫቸው በተከላካይ፤ አማካይ እና አጥቂ መስመር በጎደሉ ተጨዋቾች የሚያስፈልጉ ተተኪዎችን ለቡድኑ ለማዘጋጀት እና ስብስቡን ለማስተካከል ስንጥር ጊዜ ወስዶብናል ሲሉ ተናግረው ዋናው ትኩረታቸው ለኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የሚመጥኑ ተጨዋቾች ለማግኘት ነበር ብለዋል። በቻን ለሚሳተፈው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን የተመረጡት 3 በረኞች፤ 8 ተከላካዮች፤ 8 አማካዮችን እና አራት አጥቂዎች ናቸው፡፡ ዋና አሰልጣኙ ምርጫቸውን በጎደሉ ቦታዎች ላይ ትኩረት በማድረግ ያካሄዱት እንደሁኔታው አማካይ እና አጥቂ በማድረግ እያቀያየርን የምናሰለፋቸውን ተጨዋቾች ለማብዛት እንደሆነ ያስረዳሉ፡፡ በሴካፋ ውድድር ተተኪ ተጨዋቾች ለማግኘት ሃሳብ ስለነበር ከየክለቡ ለብሄራዊ ቡድን ገብተው ያልተጫወቱ ልጆችን ለሴካፋ ይዘን በመሄድ አዳዲስ ልጆች ሞክረዋል፡፡ በአንድ ቀን ልምምድ በሴካፋ ባደረግናቸው ጨዋታዎች የአንዳንድ አዳዲስ ተጨዋቾችን ብቃት ተመልክቼ ነበር ያሉት አሰልጣኝ ሰውነት፤ ሙሉ ለሙሉ የነበሩትን ተጨዋቾች የሚተኩ ብቁ ተጨዋቾችን እንደፈለግነው አላገኘንም ብለዋል፡፡ ከሳምንት በፊት በናይጄርያ አቡጃ ከናይጄርያ የቻን ቡድን ጋር 2ለ1 ስለተሸነፉበት የአቋም መፈተሻ ግጥሚያ ሲናገሩ ደግሞ፤ በጨዋታው የናይጄርያ ቡድን የዓለም ሻምፒዮን ከሆነው የሀ 17 ቡድን በርካታ ተጨዋቾችን በስብስቡ በማካተት ሲቀርብ እኔ ከየት አሳድጌ ልቅረብ ብዬ ተከፍቻለሁ ብለዋል፡፡ የናይጄርያ ብሄራዊ ቡድን ባለው ጥንካሬ ለቡድናችን አቋም ጥሩ መፈተሻ ነበር ያሉት ዋና አሰልጣኙ፤ ስቴፈን ኬሺ በቡድናቸው አጨዋወት በመማረክ አድናቆቱን እንደገለፀላቸው ተናግረዋል፡፡ “በወዳጅነት ጨዋታው የተማርነው በመከላከል፤ በጎል ማስቆጠር ችግሮች አሁንምእንዳሉ ነው፡፡

በተከላካይ ተጨዋቾች በሚሰሩ ጥቃቅን ስህተቶች ጎሎች ይቆጠሩብናል፡፡ በአጥቂ መስመር ላይ ያሉን ተጨዋቾች ያገኙትን የግብ እድል መጠቀም እና የማግባት ችግርም እንዳለ ነው፡፡ ይህን ለማስተካከል አሁን ባሉ ተጨዋቾች ላይ የሚሆን አይደለም፡፡ ከታዳጊ ደረጃ ተነስቶ በመስራት የተጨዋች ብቃትን ማሻሻል ብቻ ይቻላል ብዬ አምናለሁ፡፡” በብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች ዲሲፕሊን ዙሪያ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ሲያስረዱ፤ አሁን የሚያሳስብ የዲስፕሊን ችግር ያለበት ተጨዋች የለም ሲሉ ተናግረው፤ የብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾች የስነምግባር መመርያ በማስቀመጥ ተጨዋቾችን ለመቆጣጠር ለጊዜው የሚያግዝ አሰራር አይሆንም፤ ምክንያቱ በርካታ ተጨዋቾችን ከሌሎች ጋር አፎካክሮ፤ በዲስፕሊን እየቀረፁ ለማሰልጠን በበቂ ሁኔታ ተተኪ አለመኖሩ እክል ይፈጥራል ብለዋል፡፡ በአሁኑ የቻን ቡድን የሚሰክር ተጨዋች የለበትም ሲሉም በልበሙሉነት ተናግረዋል፡፡ በአጠቃላይ ግን ለቻን በመረጥነው ቡድን በየክለባቸው ጥሩ የሚንቀሳቀሱትን፤ በወቅታዊ ብቃታቸው ያመንባቸውን መርጠናል፡፡ ምርጥ ብቃት ኖሮት ሳልመርጠው የቀረ እና የምቆጭበት ተጨዋች የለም በማለት አሰልጣኙ ይናገራሉ፡፡ የተጨዋቾች አያያዝ በክለቦችና ብሄራዊ ቡድን የብሄራዊ ቡድን ተጨዋቾችን በማሰባሰብ ለአንድ አህጉራዊ ውድድር ለማዘጋጀት አንድ ሳምንት በቂ ነበር የሚሉት ዋና አሰልጣኝ ሰውነት፤ የፕሪሚዬር ሊግ ውድድር ጥንካሬ ስለሌለው ይህን ማድረግ አልተቻለም፡፡ ሁል ጊዜ በአሰልቺ ሁኔታ ለመስራት ግድ እየሆነብን መጥቷል ብለዋል፡፡ በአጠቃላይ ግን እስከ 3 ሳምንት እና አንድ ወር ተጨዋቾች በሆቴል ተቀምጠው መስራታቸው ግድ እንደነበር የሚያስረዱት አሰልጣኙ፣ ሁኔታው ተጨዋቾቹን በተለይ በተመጣጠነ ምግብ ተጠቃሚ ስለሚያደርጋቸው በዚሁ መሠረት ዝግጅቱ መከናወኑን አመልክተዋል፡፡

ለብሄራዊ ቡድን የሚያዙ ተጨዋቾች በክለቦች ሲቆዩ ወጥ ስልጠና፤ አመጋገብ እና የዲስፕሊን ስርዓት ስለማይኖራቸው ለሶስት እና ለ4 ሳምንት በብሄራዊ ቡድን ተይዘው መስራታቸው ይገባል ነው የአሰልጣኙ እምነት፡፡ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እንዳስታወቁት አንዳንድ ተጨዋቾች ከብሄራዊ ቡድን ወጥተው ወደ ክለባቸው ሲመለሱ ከጥቅም ውጭ ሆነውና ከስተው ነው፡፡ በብሄራዊ ቡድን ደረጃ እና በፕሪሚዬርሊግ የሚወዳደሩ ክለቦች ያለው የተጨዋቾች አመጋገብ ይለያያል፡፡ ‹‹ ምግብ፤ ልምምድ እና እረፍት ተጨዋችን ብቁ የሚያደርጉ ነገሮች ናቸው፡፡ ከሶስቱ አንዱን ማጣት አያስፈልግም፡፡ በየክለቡ ተጨዋቾች ቅቅል እና ጥሬ ስጋ እየበሉ እንዴት ብቁ ይሆናሉ፡፡ ክትፎ እና ቀይ ወጥ እየተበላ ይቻላል እንዴ፡፡ ተጨዋቾች ብሄራዊ ቡድን ሲገቡ እኮ አካል ብቃታቸውን የሚገነቡት በአመጋገባቸው በባለሙያ በተዘጋጀ ሜኑ መሰረት ነው፡፡›› በማለት ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ለአህጉራዊ ውድድር በሚደረግ ዝግጅት ተጨዋቾች በብሄራዊ ቡድን ከ1 ሳምንት በላይ ተሰባስበው የመዘጋጀታቸውን ጥቅም ያስረዳሉ፡፡ በክለቦች የስልጠና መዋቅር ተጨዋቾች በበቂ ሁኔታ ዝግጁ ሆነው ቢገኙ ወደ ብሄራዊ ቡድን ገብተው ሲሰሩ ውጤታማ ለመሆን በተቻለ ነበር፡፡ ክለቦች ይህን የመሰለውን መሰረታዊ መዋቅር አለመከተላቸው ችግር እየፈጠረ ቆይቷል ብለዋል፡፡ “ተጨዋቾች እግር ኳስ ሙያቸው፤ የገቢ ማግኛቸው ህይወታቸው መሆኑን ማወቅ አለባቸው፡፡ ማንም ተጨዋች ራሱን ጠብቆ ለልምምድ የሚመጣበትን ሁኔታ መማር ማወቅ አለበት፡፡

ሆቴል ቁጭ ማድረግን እኛም አንፈልገውም። በማለት አሰልጣኝ ሰውነት የተናገሩት ክለቦች በስራቸው ከብሄራዊ ቡድን ጋር ተመጋጋቢ ሆነው የመስራታቸውን ጠቀሜታ ለማመልከት ነው፡፡ በቻን ስለሚጠበቅ ውጤት በደቡብ አፍሪካ በሚዘጋጀው 3ኛው የአፍሪካ አገራት ሻምፒዮንሺፕ ስንገባ የማናውቀውን ቻን ለማወቅ ነው ያሉት ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው፤ እንደማንኛውም ቡድን ቀዳሚ ግባችን ዋንጫውን ማምጣት፤ ካልሆነ አራት ውስጥ መግባት፤ ካልሆነ ሩብ ፍፃሜ መድረስ፤ ካልሆነ ተሸንፎ መምጣት ነው። ተሸንፎ መምጣት እንደ ውድቀት ሊቆጠር ይችላል ብለዋል። ብሄራዊ ቡድኑ በቻን ውድድር የመጀመርያ ተሳትፎውን በማድረጉ ብቻ ተጫውቶ ቢመለስ እንደ ስኬት መቁጠር ይገባል የሚሉት አሰልጣኙ፤ በማያውቀው ውድድር የገባ ስለሆነ በአሁኑ ወቅት የሚያደርጋቸው ነገሮች ሁሉ ስኬት ናቸው፡፡ ከዚያ በኋላ ብቻ ከተሳትፎ የዘለለ ውጤት መጠበቅ ይኖርበታል ሲሉ ተናግረዋል፡፡ ኢትዮጵያና ሊቢያ በቻን ውድድር የምድብ 3 የመጀመርያ ጨዋታ ላይ የሚገናኙት ለ8ኛ ጊዜ ነው፡፡ የሊቢያ ብሄራዊ ቡድን በአገር ውስጥ ክለቦች በሚገኙ ተጨዋቾች ለመገንባት ብዙም እንዳላደከመ ሲታወቅ በዘንድሮ ተሳትፎው እስከግማሽ ፍፃሜ ለመድረስ እቅድ ይዟል፡፡ ሊቢያ በቻን ውድድር የምትሳተፈው ለ2ኛ ጊዜ ሲሆን ለመጀመርያ ጊዜ በ2009 እኤአ ላይ በ1ኛው የአፍሪካ አገራት የእግር ኳስ ሻምፒዮንሺፕ ስትሳተፍ በምድቧ በሶስት ጨዋታ 2 ነጥብ አግኝታ ከጥሎ ማለፍ በፊት ከውድድሩ ተሰናብታለች፡፡

በታሪካቸው በሁሉም ውድድሮች 7 ጊዜ በተገናኙበት ወቅት እኩል ሶስት ጊዜ ሲሸናነፉ በ1 ጨዋታ አቻ ተለያይተዋል፡፡ ሁለቱ ቡድኖች ለመጀመርያ ጊዜ ሲገናኙ በ1969 እኤአ በዓለም ዋንጫ ማጣርያ የደርሶ መልስ ጨዋታዎች ነበር፡፡በመጀመርያው ጨዋታ ሊቢያ ሜዳዋ ላይ 2ለ0 ስታሸንፍ በመልሱ ጨዋታ ደግሞ ኢትዮጵያ 5ለ1 በሆነ ውጤት ለማሸነፍ በቅታለች፡፡ ሁለቱ ቡድኖች በ1979 እኤአ ላይ የተገናኙት በአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ የደርሶ መልስ ጨዋታዎች ነው፡፡ የመጀመርያውን ጨዋታ ሊቢያ 2ለ1 ስትረታ በመልሱ ጨዋታ በኢትዮጵያ ሜዳ አንድ እኩል አቻ ተለያይተዋል፡፡ በ1983 እኤአ ላይ ሁለቱ ቡድኖች ለአምስተኛ ጊዜ የተገናኙት በኢንተርናሽናል ጨዋታ ሲሆን ኢትዮጵያ ጨዋታውን በሜዳዋ በ1ለ0 አሸናፊነት ተወጥታለች፡፡ በ2006 እኤአ በአፍሪካ ዋንጫ ማጣርያ ተገናኝተው ኢትዮጵያ 1ለ0 ስታሸንፍ፤ በ2007 እኤአ ላይ ደግሞ በተመሳሳይ ውድድር 3ለ1 ያሸነፈችው ሊቢያ ነበረች፡፡ ታዋቂው የእግር ኳስ ዘጋቢ ድረገፅ ጎል ዶትኮም በሁለቱ ቡድኖች ጨዋታ ላይ አንባቢዎቹን አሳትፎ በሰራው የውጤት ትንበያ 19.05 በመቶ ኢትዮጵያ 3ለ1 እንደምታሸንፍ ሲገምቱ፤ ሌሎች 19.05 በመቶ ሊቢያ 2ለ0 እንደምታሸንፍ ሲገምቱ ቀሪዎቹ ገማቾች ሊቢያ 3ለ0 እንደምትረታ ጠብቀዋል፡፡ ቀዮቹ ሰይጣኖች ተብለው የሚጠራው የኮንጎ ኪንሻሳ ቡድን በ2000 እኤአ በአፍሪካ ዋንጫ ከተሳተፈ ወዲህ ወደ ትልልቅ ውድድሮች መመለስ ቸግሮት ቆይቷል፡፡ መካከለኛውን አፍሪካ በመወከል የብሄራዊ ቡድኑን ጥንካሬ ለመመለስ ተፎካካሪነቱ ተጠብቋል፡፡ ኮንጎ በቻን ውድድር ስትሳተፍ የመጀመርያዋ ሲሆን በካሜል ጃቡር የሚሰለጥነው ቡድኗ ያልተጠበቀ ብቃት እንደሚያሳይ ተገምቷል፡፡ ኮንጎ እንደ ኢትዮጵያ ሁሉ በዓለም ዋንጫ ማጣርያዎች አስገራሚ ውጤቶች ነበሯት፡፡

ኢትዮጵያ ከኮንጎ በሚያደርጉት ጨዋታ በጎል ዶት ኮም አንባቢዎች መቶ በመቶ የአሸናፊነት ግምቱ ለኢትዮጵያ ሲሆን ውጤቶቹ 3ለ1 እና 2ለ0 ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ ከኮንጎ ጋር በ3ኛው የቻን ውድድር ሲገናኙ በታሪክ ለ3ኛ ጊዜ ሲሆን፤ በ1967 እኤአ በኢንተርናሽናል ጨዋታ 1ለ0 እንዲሁ በ1968 በአፍሪካ ዋንጫ 3ለ2 ኮንጎ አሸንፋለች፡፡ በምድብ 3 ለኢትዮጵያ ከባድ ተጋጣሚ ትሆናለች የተባለችው ጋና በቻን ተሳትፏዋ ለማይክል ኤስዬን እና ለአንድሬ አየው ምትክ የሚሆኑ ወጣቶችን እንደምታገኝ ትጠብቃለች፡፡ ጋና በቻን ውድድር ምድቧን በቀላሉ ማለፍ እንደምትችል ግምት ከማግኘቷም በላይ ለዋንጫው ተፎካካሪነት እንደምትበቃም እየተነገረ ነው፡፡ በ2009 እኤአ ለመጀመርያ ጊዜ በቻን ውድድር ስትሳተፍ ሁለተኛ ደረጃ አግኝታ የነበረችውና በ2ኛው የቻን ውድድር ከምድብ ማጣርያ የተሰናበተችው ጋና ዘንድሮ ለዓለም ዋንጫ ዋናው ቡድኗ በማለፉ የቻን ቡድኗ ተጨዋቾች በከፍተኛ መነቃቃት አስገራሚ ብቃት ሊኖራቸው ይችላል፡፡ የቡድኑ አሰልጣኝ የሆኑት ማክስዌል ኮንዱ በስብስባቸው ከጋና ፕሪሚዬር ሊግ መሪ ክለብ አሻንቲ ኮቶኮ 8 ተጨዋቾች የያዙ ሲሆን በኳስ ቁጥጥር ያለውን ድክመት በመቅረፍ ውጤታማ ለመሆን አስበዋል፡፡ በጎል ዶት ኮም በኢትዮጵያ እና ጋና ጨዋታ ላይ በቀረቡት 3 የውጤት ግምቶች ኢትዮጵያ 3ለ1 እንደምታሸንፍ 33.33 በመቶ ሲገምቱ ጋና 2ለ0 33.33 በመቶ እና 3ለ1 33.33 በመቶ ውጤትን ተንብየዋል፡፡ኢትዮጵያ እና ጋና ሁለቴ ተጫውተው አንድ እኩል ተሸናንፈዋል፡፡ በ1963 እኤአ በአፍሪካ ዋንጫ ጋና 2ለ0 ስታሸንፍ፤ በ1996 እኤአ በኢንተርናሽናል ጨዋታ ኢትዮጵያ 2ለ0 ረታለች፡፡ በታዳጊና ወጣት ብሄራዊ ቡድኖች ተተኪዎችን ለማግኘት በአፍሪካ እግር ኳስ ኮንፌደሬሽን ሰሞኑን በ2015 እኤአ በታዳጊና ወጣት ብሄራዊ ቡድኖች በሚካሄዱ ውድድሮች ለመግባት የጥሎ ማለፍ ማጣርያዎችን የሚሳተፉ አገራት ተመርጠዋል፡፡

በሀ 20 ወጣት ብሄራዊ ቡድን ውድድሮች እንዲሳተፉ ከ54 የካፍ አባል አገራት 37 ሲመረጡ ፤በሀ 17 ታዳጊ ብሄራዊ ቡድን ውድድሮች የሚሳተፉት ደግሞ 40 ናቸው፡፡ ኢትዮጵያ በሁለቱም የታዳጊና ወጣት ውድድሮች እንድትሳተፍ ብትመረጥምም ሁለቱም ብሄራዊ ቡድኖች አለመኖራቸው የሚያሳስብ ነው፡፡ ከቻን በኋላ የኢትዮጵያ እግር ኳስ አሁን ባለበት ሁኔታ መቀጠል የለበትም በማለት በጋዜጣዊ መግለጫው ላይ በአፅንኦት ያሳሰቡት ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ናቸው፡፡ በቀጣይ ለአፍሪካ ዋንጫ ለማለፍ፤ በዓለም ዋንጫ ማጣርያዎች ጠሩ ተፎካካሪ ሆኖ ለመቀጠል በቻን ውድድር ቋሚ ተሳትፎ ለማግኘት በመላው አገሪቱ በመዘዋወር የታዳጊ ተጨዋቾችን ፈልጎ በመመልመል መስራት እንደሚገባ፤ ከ20 ዓመት በታች ጀምሮ ተተኪ ቡድኖች በየደረጃው በአገር አቀፍ ደረጃ ተዋቅረው መሰራት እንደሚያስፈልግ፤ ለብሄራዊ ቡድኑ ቀጣይ የውጤታማነት ጉዞ ግብዓት ሊሆኑ የሚችሉ አሰራሮችን መተግበር እንደሚገባ ሃሳብ አቅርበዋል፡፡ በየክልለሉ ታዳጊ እና ወጣት ተጨዋቾችን የማሰባሰብ ፍላጎት አላቸው፡፡ ይህንንም ለፌደሬሽኑ ገልፀው ምላሹን እየተጠባበቁ ነው፡፡ ዋና አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው ለታዳጊ እና ወጣት ቡድኖች ልዩ ልዩ ውድድሮች ማዘጋጀት፤ ልምድ የሚቀስሙባቸውን ኢንተርናሽናል የውድድር ተሳትፎዎች በትኩረት ማግኘት እና የልምድ ጨዋታዎችን በማድረግ እየተሰራ እና መሰረታዊ ስልጠና በስፋት መተግበር ከተቻለ አሳሳቢው የተኪ ተጨዋቾችን ችግር መቅረፍ አይከብድም በማለትም መክረዋል፡፡ ‹‹እነ ናይጄርያ ተተኪ ተጨዋቾች አላቸው፡፡ ከብሄራዊ ቡድን በታች በየእድሜ ደረጃው ቡድኖች አሏቸው በየጊዜው ያሳድጋሉ፡፡ አሁን ለእኛ ብሄራዊ ቡድን ከየት ነው የማሳድገው፡፡ እቅዴ ከቻን በኋላ በመላው የኢትዮጵያ ምድር መዞር ነው፡፡ እግር ኳስ በሚዘወትርባቸው፤ በውድድሮች ላይ ወጣቶችን ማፈላለግ ቀጣይ ትኩረቴ ነው፡፡ ወጣት ተጨዋቾች በመላው አገሪቱ በብዛት ስለመኖራቸው ቶክ ጀምስ ምሳሌ ነው፡፡

በሁለት ዓመት ውስጥ ነው ለብሄራዊ ቡድን ደረጃ የበቃው፡፡ የቶክ ጀምስ አይነት በየጨዋታው ስፍራ አስር እና አስራ አምስት ታዳጊ ተጨዋች በየትም ቢገኝ ዞሬ ላመጣ እፈልጋለሁ፡፡ አሁን ያለው የተጨዋቾች ስብስብ በሚቀጥሉት ሁለት ዓመታት 50 በመቶው ላይኖር ይችላል፡፡ ክለቦች ይህን ስራ ቢሰሩ ነገሩ ይቃለል ነበር፡፡ እስከዛሬ ግን አልተሰራም፤ ወደፊትም የሚሰራበት አቅጣጫ አይመስልም፡፡ በርግጥ ተጨዋቾች የሚገኙት ከክለቦች ነው፡፡ ክለቦች በየቡድን መዋቅራቸው ወጣቶችን ማሳደግ ካልቻሉ፤ በተገቢው መንገድ ካልሰሩ የብሄራዊ ቡድኑ እጣ ፋንታ ምን ሊሆን ነው፡፡ ክለቦች ካልሰሩ ተብሎ ግን መቀመጥ አያስፈልግም፡፡ ስለዚህም እቅዴን ለብሄራዊ ፌደሬሽኑ በማቅረብ በዚህ የወጣቶች ምልመላ ስራ ዙርያ ለመስራት አስባለሁ” በማለትም ስለሁኔታው አስፈላጊነት አስረድተዋል፡፡ በየክለቡ ይካሄዳል የሚባለው ምልመላ በኢትዮጵያ ሁሉም ክልሎች ያሉ ታዳጊዎችን አፈላልጎ በማግኘት የሚሰራበት መሆኑ ያጠራጥረኛል የሚሉት ዋና አሰልጣኙ ችሎታ እያላቸው ክለብ ያጡ ወጣቶች መዓት መሆናቸውን ለወጣቶች እድል ለመስጠት ለብሄራዊ ቡድን ተስፋ የሚሆን ቡድን መፍጠር እንደሚቻል አስገንዝበው። “የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ተጨዋች ኢንዱራንስ 2200 ነው በዓለም አቀፍ ደረጃ ይሄው መለኪያ 3500 ደርሷል፡፡ የኛ ተጨዋቾች ያላቸው የጨዋታ ፅናት 40 ደቂቃ ተጫውቶ መቆም ነው፡፡

ይህን ማሳደግ ይጠበቅብናል፡፡ እግር ኳስ ትምህርት ነው፡፡ በሌላው ዓለም እግር ኳስን ልጆች ከስድስት እና ሰባት አመት ጀምሮ ነው የሚማሩት እና የሚሰለጥኑት፤ በእኛ አገር ይህ አይነቱ አሰራር መቼ ነው የሚፈጠረው ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡” ሲሉ ሃሳባቸውን አጠቃልለዋል፡፡ ይለቃሉ፤ ይቀጥላሉ አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው በብሄራዊ ቡድኑ ባላቸው ሃላፊነት ከፌደሬሽኑ ጋር የተፈራረሙት የኮንትራት ውል ካበቃ ወራት ተቆጥረዋል፡፡ የኮንትራት ውላቸው ስለመራዘሙ እና ስለመቋረጡ የማውቀው ነገር የለምም ብለዋል፡፡ በቅርቡ ከፌደሬሽኑ ጋር በመመካከር ኮንትራታቸውን በቀጣይ ለሁለት አመት የማራዘም ሁኔታ ሊፈጠር እንደሚቻልም ይገምታሉ። “ለአሰልጣኝነት ቅጥር የጠየቁኝ ብዙ ናቸው ምን መልስ አልሰጠሁም፡፡የውጭ አገር አሰልጣኝ ለመሆን በፍፁም ጥያቄ አላቀረብኩም፡፡ ከተጠየቅኩ ደግሞ እምቢም ሆነ እሽ ማለት የራሴው መብት ነው፡፡ ‹‹ብዙ አገራት እና ክለቦች ቡድኖቻቸውን እንዳሰለጥንላቸው በተደጋጋሚ ጠይቀውኛል፡፡ ቡድናችሁን ላሰልጥን ብዬ ለማንም አላመለከትኩም፡፡ ክለቦች ቢጠይቁኝ አገሮች ቢጠይቁኝ ምላሼ አገሬን ለቅቄ ልምንድነው የምሰደደው አልሄድም ነው፡፡ አገሬ ላይ መስራት እፈልጋለሁ፤ በአገሬ የምበላው አላጣው፤ የምኖርበት ቤት አለኝ፤ ብዙሺ ዶላር ሰጥተው የጠየቁኝ ቢኖሩም አልተቀበልኩም›› በማለት አሰልጣኝ ሰውነት ብሄራዊ ቡድኑን የመልቀቅ ምንም አይነት ፍላጎት እንደሌላቸው ሊያስረዱ ጥረት አድርገዋል፡፡ ማበረታቻ እና ስፖንሰርሺፕ ድጋፎች በቻን ውድድር ለምስታስመዘግቡት ውጤት ከፌዴሬሽኑ በኩል ቃል የተገባላችሁ ማበረታቻ አለወይ ተብለው የተጠየቁት አሰለጣኝ ሰውነት “ካሸነፍን ሽልማቱ ይመጣል፡፡ የእኛ መጦርያችን እሱ ነው፡፡ ጥቅማችን ተጫውተን ስናሸንፍ ሽልማታችን ነው፡፡

እግር ኳስ ፌደሬሽን ማበረታቻ ለመስጠት ሁሌም ቃል የገባል፡፡ እኛ ውጤት አስመዝግበን ሽልማቱን ለመውሰድ ተቸገርን እንጅ፡፡” ብለዋል፡፡ የሐረር ቢራ ፋብሪካን የገዛው ታዋቂው የአውሮፓ ቢራ ጠባቂ ኩባንያ ሄኒከን የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ እና ሌሎች ትልልቅ የስፖርት ውድድሮችን በስፖንሰርሺፕ በመደገፍ የሚታወቅ ሲሆን በበደሌ ስፔሻል ምርቱ የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድንን አብይ ስፖንሰር ሆኖ ለሁለት ዓመታት 24 ሚሊዮን ብር ከፍሎ ነበር፡፡ የእግር ኳስ ፌደሬሽኑ የማርኬቲንግና ፕሮሞሽን ማናጀር አቶ ሳምሶን ጌታቸው እንደተናገሩት የበደሌ አብይ ስፖንሰርነት ከብሔራዊ ቡድኑ ጋር እንዳለ መሆኑን ጠቅሰው፤ የውል ስምምነቱ የሚያበቃበት ጊዜ እንዳልደረሰ እና ወደፊት ውሉን አድሶ በተሻለ የገንዘብ ድጋፍ ስፖንሰርሺፑን ለመቀጠል አቅሙ መኖሩን አስታውቀዋል፡፡

ከእለታት አንድ ቀን አንድ እረኛ ከብቶቹን ወደ ቤቱ እየነዳ ሳለ ወደ በረታቸው መቃረባቸውን በማሰብ ለመዝናናት ወደኋላ ይቀራል፡፡ ሳያስበው ግን በድንገት አንድ ተኩላ ይመጣበታል፡፡ ሮጦ በማያመልጥበት ርቀት ላይ በመሆኑ ባለበት ቆሞ ይቀራል፡፡ ተኩላውም፤ “እንዴት ብትደፍረኝ ነው፤ በእኔ ግዛት፣ በዚህ ምሽት፣ ያለ ፍርሃት እየተዝናናህ ያገኘሁህ?” ሲል ይጠይቀዋል፡፡ እረኛውም፤ “አያ ተኩላ፤ ብዙ ጊዜ ከብቶቼን እየነዳሁ ስሄድ ታየኛለህ፡፡ እስከዛሬም በጠላትነት ተያይተን አናውቅም፡፡ ስለዚህ በድፍረት ሳይሆን በፍቅር ተሳስበን እንተላለፋለን እንጂ በክፉ አንተያይም በሚል እሳቤ ነው ዘና ብዬ ወደ ቤቴ የምሄደው” አለው፡፡ ተኩላም፤ ነገር ፈልጐ ልጁን መብላት አስቦ ኖሮ፤ “በጭራሽ የንቀት ነው፡፡ ምናልባትም ውሾችህንና ጌታህን ተማምነህ ይሆናል፡፡ ማናቸውንም እንደማልፈራቸው ዛሬ አሳይሃለሁ!” እረኛው በሌላ መንገድ ሊያሸንፈው እንደማይችል ተገንዝቦ፤ “አያ ተኩላ፤ እራትህ ልሆን እንደምችል አውቄያለሁ፡፡

ላመልጥህም እንደማልችል አውቃለሁ፡፡ ውሾቼም ሆኑ ጌታዬ እንደማያድኑኝም ተገንዝቤያለሁ፡፡ ስለዚህ አንድ ውለታ ብቻ ዋልልኝ፡፡ ከእንግዲህ ዕድሜዬ በጣም አጭር ናትና ተደስቼ እንድሞት ዕድል ሰጠኝ፡፡” ተኩላውም፤ ልጁ ለመበላት ዝግጁ መሆኑ ደስ አለውና፤ “ከመበላትህ በፊት የሚያስደስትህ ምን እንደሆነ ንገረኝና በቀላሉ ላደርገው የምችለው ነገር ከሆነ አደርግልሃለሁ” አለ፡፡ እረኛውም፤ “እባክህ ዋሽንት ንፋልኝ፡፡ ጥሩ ዜማ ሰምቼ ለመሞት እፈልጋለሁ” ሲል ለመነው፡፡ አያ ተኩላም ከእራት በፊት ሙዚቃ መጫወት የሚከፋ ነገር አይደለም ብሎ በማሰብ የእረኛውን ዋሽንት ተቀብሎ መጫወት ጀመረ፡፡ እረኛውም መደነስ ቀጠለ፡፡ ብዙም ሳይቆይ የዋሽንቱን ድምጽ የሰሙ ውሾች፤ “በጭለማ ዋሽንት ማን ሊጫወት ይችላል? ከየት በኩል ነው ድምፁ የሚመጣው?” ተባባሉና ሙዚቃውን ወደሰሙበት አቅጣጫ ሲመጡ፤ አያ ተኩላ ዋሽንት ይጫወታል፡፡ ትንሹ እረኛ ይደንሳል፡፡ ሳያመነቱ ተኩላውን ለመያዝ እየሮጡ መጡበት፡፡ ተኩላው ዋሽንቱን ወርውሮ እግሬ አውጪኝ አለ፡፡ እየሮጠ ሳለ ግን ወደ ልጁ ዘወር ብሎ፤ “ዋና ሥራዬ ልኳንዳ ቤት ነው፡፡ ያገኘሁትን ሥጋ አርጄ መብላት ሲገባኝ እኔን ብሎ ሙዚቃ ተጨዋች! ዋጋዬን አገኘሁ!” እያለ ሩጫውን ቀጠለ፡፡

                                                             * * *

ያለሙያ መግባት ዋጋ ያስከፍላል፡፡ አገኘን የምንለውን ድል በአግባቡ ካልተጠቀምንበትና በዚያ ተኩራርተን ትርፍ መንገድ እንሂድ ካልን የጥፋተኝነታችንን ያህል ኪሣራውን መክፈል ግዴታችን ይሆናል፡፡ ፖለቲከኛው ባለሙያው ሥራ ውስጥ ተሸብልቆ ከገባ፣ ባለሙያ ባንድ ጀንበር ፖለቲከኛ ነኝ ብሎ ከተፈጠመ፤ ጉዟችን የእውር የድንብር ነው የሚሆነው፡፡ በእጃችን ያለውን ሙያ ትተን የማያገባን ሥር ውስጥ ገብተን መቧቸር ከሁለት ያጣ ያደርገናል። የሰለጠንበት ሙያ ሌላ፤ የምንሠራው ሥራ ሌላ ከሆነ፤ ከሁለት ያጣ እንሆናለን፡፡ የራሳችንንም ሥራ አልሠራን፤ ሌሎችም ሥራ እንዳይሠሩ አደረግን፡፡ የሀገራችን አንዱ ችግር ትክክለኛው ሰው በትክክለኛው ቦታ አለመቀመጡ ነው (The right man at the right place እንደሚሉት ነው ፈረንጆቹ)፡፡ ወይ በዘመድ፣ ወይ በታሪክ አጋጣሚ፣ አሊያም በዕድል ያለሙያችን የተቀመጥንበት ቦታ ከልማቱ ጥፋቱ ይበዛል፡፡ ሁሉ በጄ፣ ሁሉ በደጄ ማለታችን አይቀርምና ከእኛ በላይ የሚያውቅን ሰው አላግባብ ማጐሳቆላችን፣ “እኔ ብቻ ነኝ አዋቂ፣ እኔ ያልኩትን ብቻ ፈጽሙ” ወደሚል ግትርነት ማዘንበላችን አይቀሬ ነው፡፡

“ወዳጄ እጅግ ብዙ ምክር ያዳምጣል፡፡ የማታ ማታ የሚሰማው ግን የራሱን ልቦና ነው” ይለናል ደራሲ፡፡ ያ ደግሞ ለለውጥ አያመችም፡፡ “እግዚአብሔር ሲምር ምክር ያስተምር” የሚለውን ያስዘነጋልና፡፡ የጋራ አገር እንዳለን እንዲሰማን ያስፈልጋል፡፡ በጋራ እንደግ ብሎ ልብን መክፈት ያስፈልጋል፡፡ አገር ጥቂቶች የሚለፉባት ሌሎች የሚያፌዙባት እንዳልሆነች መገንዘብ ይገባል፡፡ ፀሐፌ ተውኔት ፀጋዬ ገ/መድህን “የአገሬ ሰው አብረን ወደላይ እንደግ ሲሉት፤ አሸብልቆ ወደታች ወደመሬት ማጐንቆል ይወዳል!” ይለናል፡፡ ቀጥሎም፤ “አንድም መንግሥት ማለት የአገሩ አዕምሮ እንጂ የልቡ ሮሮ አይደለም” ይለናል፡፡ ሀገራችንን በጋራ ዐይን እንያት፡፡ “ወዳጄ ልቤ ሆዬ የእኔ መከራ ያንተ መከራ አይደለምን?” እንባባል፡፡ (ብላቴን ጌታ ህሩይ እንዳሉት) የሀገርን አንድነት፣ የሀገርን ኢኮኖሚ፣ የሀገርን ባህል፤ ተጠንቅቆ ጠብቆ በቅጥ በቅጡ ለማቆየት፤ በፍቅርና በመተሳሰብ እንጂ “የራቀውን በመድፍ፣ የቀረበውን በሰይፍ” የምንልበት የምንበቃቀልበት፣ የምንጠፋፋበት ዓይነቱ ዘዴ፤ ቢያንስ ዘመናዊ አይደለም፡፡ “ጀግናን ዘገንኩና አፈር ብዬ ተውኩት”፣ እንዳለች ዕድሜዋን ትገፋለች አሉ የጐበዝ አገር እናት፡፡ ዛሬ፤ በዕውቀት ብርሃን የተጋ ዜጋ ያስፈልገናል፡፡

ሲወርድ ሲዋረድ የመጣ የአተካሮና የውሃ ወቀጣ ባህልን ዘሎ ማሰብ የሚችል አዕምሮ ብቻ ነው የመፍጠር ክህሎትን የሚቀዳጅ፡፡ ነፃ አዕምሮ ነፃ አስተያየትን ይወልዳል፡፡ ማርክ ትዌን፤ “በእኛ አገር በእግዚሃር ደግነት ሦስት ወደር የሌላቸው ነገሮች ተሰጥተውናል:- የመናገር ነፃነት፣ የሀሳብ ነፃነት እና ሁለቱንም በተግባር ያለማዋል ኩራት” ይለናል። ስለማንነት ሲናገርም “ቦስተን ውስጥ ምን ያህል ዕውቀት አለው? ተብሎ ይጠየቃል፡፡ ኒውዮርክ ውስጥ ምን ያህል ዋጋ አለው? ተብሎ ይጠየቃል፡፡ ፊላዴልፊያ ውስጥ ወላጆቹ እነማናቸው? ተብሎ ይጠየቃል” ይላል፡፡ የትኛውን ነን ብለን ራሳችንን መጠየቅ ያባት ነው፡፡ በተግባር የማንፈጽመውን አዋጅ ማወጅ፣ የማንከውነውን መመሪያ ማውጣት፣ በዕውቀት ላይ ያልተመሠረተ ፖለቲካ ማውራት፣ የሩቁን ትተን የዕለት የዕለቱን ብቻ እያወራን በአየር ላይ መኖር፤ “ያልወጋ ቀንድ ከጆሮ ይቆጠራል” የሚለው ትርጓሜ ነው የምንሆነው፡፡ መሠረት ያለው፣ ዕውቀትን የተንተራሰ ከወሬ ያለፈ ህብረተሰብ ለመገንባት ጥረት እናድርግ፡፡