Administrator

Administrator

በኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ ስፖንሰርነት የአውሮፓ 24 ምርጥ ክለቦችን የሚያሳትፍ ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› ስለመታቀዱ በለንደኑ ታይምስ ጋዜጣ የቀረበ ልዩ ዘገባ እውነታ አልተረጋገጠም፡፡ ኳታር በ2022 እኤአ ላይ በመካከለኛው ምስራቅ በታሪክ ለመጀመርያ ጊዜ እንዲካሄድ የተፈቀደውን 22ኛው የዓለም ዋንጫ የምታዘጋጀው ናት፡፡ በሃሳቡ የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር እና ፊፋ እንዳይቀየሙ ተሰግቷል፡፡ የለንደኑ ታይምስ ጋዜጣ የኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ ትልልቅ የአውሮፓ ክለቦች በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› እንዲሳተፉ በማግባባት ላይ መሆናቸውን ሲዘግብ እስከ 175 ሚሊዮን ፓውንድ ለተሳትፏቸው ብቻ ለመክፈል ጥሪ አድርገጎላቸዋል ብሏል፡፡ ድሪም ፉትቦል ሊጉን በኳታር፤ በዩናይትድ አረብ ኢምሬትስ፤ በሳውዲ አረቢያ እና በባህሬን በሚገኙ 6 ከተሞች በማዘዋወር በየሁለት ዓመቱ ለማካሄድ መታቀዱን የገለፀው ታይምስ አራቱ የእንግሊዝ ክለቦች ማን ዩናይትድ፤ ማን ሲቲ፤ አርሰናልና ቼልሲ እንዲሁም የስፔኖቹ ሪያል ማድሪድና ባርሴሎና በቀጥታ የተሳትፎ ግብዣ እንደቀረበላቸውም አውስቷል፡፡

በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› መጀመር ዙርያ ጥሪ ቀርቦላቸዋል የተባሉት እነዚህ ክለቦች በጉዳዩ ላይ እስካሁን የሰጡት መግለጫ የለም፡፡ የኳታር እግር ኳስ ፌደሬሽን በኦፊሴላዊ ድረገፁ ስለ ድሪም ፉትቦል ሊጉ የሚወራውን ሲያስተባብል ጉዳዩ በቀጥታ የሚመለከታቸው የአውሮፓ እግር ኳስ ማህበር እና ፊፋ እስካሁን በጉዳዩ ላይ ይፋ መግለጫ ከማውጣት እንደተቆጠቡ ናቸው፡፡ የኳታር ባለሃብቶች በ‹ድሪም ፉትቦል ሊግ› ከ9 አመታት በኋላ አገሪቱ ለምታዘጋጀው 22ኛው ዓለም ዋንጫ ለማሟሟቅ ብለው ውድድሩን ያዘጋጁታል ያሉ ዘገባዎችም ወጥተዋል፡፡ ሌስ ካህሬስ ዴፉትቦል የተባለ የፈረንሳይ ሚዲያ በበኩሉ የለንደኑ ታይምስ ዘገባውን ከማሰራጨቱ አንድ ቀን ቀደም ብሎ የድሪም ፉትቦል ሊግ ጅማሮን በአዝናኝ ሃሳብነት ማቅረቡን ገልጿል፡፡

የአውሮፓ እግር ኳስ በድሪም ፉትቦል ሊግ መጀመር ዙርያ የወጡ መረጃዎችን ለማጣራት እንደሚፈልግ የገለፁ አንዳንድ ዘገባዎች ከሻምፒዮንስ ሊግ እና በፊፋ ከሚዘጋጀው የዓለም ክለቦች ዋንጫ ጋር የሚመሳሰለው ውድድሩ እንዲካሄድ በምንም አይነት ፈቃድ እንደማይሰጥ አብራርተዋል፡፡ በአውሮፓ እግር ኳስ የኳታር ንጉሳዊያን ቤተሰብ የገንዘብ ተፅእኖ እየጨመረ መጥቷል፡፡ በ2010 እኤአ ላይ ከኳታር የንጉሳውያን ቤተሰብ አንዱ የስፔኑን ክለብ ማላጋ በባለቤትነት ተያዘ፡፡ በ2011 እኤአ ላይ ሌሎች የንጉሳውያን ቤተሰብ አባላት የፈረንሳዩን ፓሪስ ሴንትዠርመን በባለቤትነት ገዙ፡፡ ኳታር ፋውንዴሽን ደግሞ የታላቁ የስፔን ክለብ ባርሴሎና ማልያ በታሪክ የመጀመርያው ስፖንሰር መሆን እንደቻለ ይታወቃል፡፡

ባለፈው ሳምንት በራሽያ ሰባት ሬስቶራንቶች ስላሏቸውና በቢሾፍቱ ---ሪዞርትን ስለከፈቱ ኢትዮጵያዊ ዶ/ር---- ሰፋ ያለ ቃለምልልስ አቅርበን ነበር፡፡ በቦታ ጥበት የተነሳ ኢንቨስተሩ ከራሽያ ማፍያዎች ጋር የነበራቸውን አስገራሚ ገጠመኞችና ውጣ ውረዶች ሳናቀርብ ቀርተናል፡፡ ዛሬ ይሄን ታሪካቸውን እንደሚከተለው አቅርበነዋል፡፡ ከኢንቨስተሩ ጋር ቃለምልልሱን ያደረገችው የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው ናት፡፡ እስቲ ከራሽያ ማፍያዎች ጋር ስላሳለፉት ውጣ ውረድ ያጫውቱኝ----- ራሽያ ውስጥ ከ1990-2000 ዓ.ም ድረስ ትልቅ ቀውስ ነበር፡፡ ለአስር ዓመት አገሪቱን ማፍያዎች የተቆጣጠሩበት ዘመን ነበር፡፡ ብዙዎቹ ከሶሻሊዝም መፈረካከስ በኋላ ሃያ ዓመትና ከዛ በላይ ወህኒቤት ታስረው የተለቀቁ ናቸው፡፡ ፓፓ ወይም ‹‹የማፍያ አባት›› በመባል የሚታወቁ ሲሆኑ ሁሉም በሥራቸው ሁለት መቶና ሶስት መቶ ሰዎች ያደራጃሉ፡፡ ከተማውን በሙሉ እነዚህ ሰዎች ተከፋፍለውት ነበር፡፡

በየሰፈሩ አንድ አንድ የሰፈር አለቃ ይኖራል፡፡ በአንደኛው ፓፓ ግዛት ሌላው ጣልቃ በመግባት ለመበጥበጥ ቢሞክር የሰፈር አለቆች አደብ ያስገዙታል፡፡ ማንኛውም በቢዝነስ ውስጥ የተሰማራ ሰው ለእነሱ በየወሩ የተጣለበትን ክፍያ (ደሞዝ) ይከፍላል፡፡ ማነው ክፍያውን የሚወስነው? ሚር X የተባለ የማፍያው ቡድን አለቃ (ፓፓ ይሉታል) የንግድ ቦታሽ ድረስ ይመጣና ‹‹ከማን ጋር ነው የምትሰሪው?›› ብሎ ይጠይቅሻል፡፡ (ከየትኛው የማፍያ ቡድን ጋር ማለቱ ነው) ስሙን መናገር አለብሽ፡፡

ፓፓ ከሌለሽ በየቀኑ ተመላልሶ የሚሸጠውን፣የሚወጣ የሚገባውን አይቶ፣ አጥንቶና ሰልሎ በወር 5ሺ ዶላር ወይም 10 ሺህ ዶላር ክፍያ ሊመድብብሽ ይችላል፡፡ በየወሩ የተመደበብሽን ገንዘብ ባትከፍይ ቤትሽ በቦንብ ሊፈነዳ ወይም በእሳት ሊቀጣጠል ይችላል፡፡ በጥይት ሊገሉሽም ይችላሉ፡፡ ማንም የሚደርስልሽ የለም፡፡ መንግስት የለም ማለት ነው? እንደሌለ ቁጠሪው፡፡ እነሱ ከመንግስትና ከፖሊስ ቁጥጥር ውጭ ነበሩ ማለት ይቻላል፡፡ ነገሩ ሳይገባሽ ለፖሊስ ወይም ለመንግስት ብታመለክቺ ጥይት በጭንቅላትሽ ላይ ይለቁብሻል፡፡ አንዳንዴ ለምሳሌ--አንቺ ካዛንቺስ የምትሰሪ ከሆነ----የልደታው ፓፓ (ንጉስ) ይመጣና ‹‹ለእኔ ይሄን ያህል መክፈል አለብሽ›› ብሎ ይወስንብሻል፡፡ ያኔ የፓፓሽን ስም ትጠሪያለሽ--- ካመነሽ ይሄዳል፡፡ ካላመነ ‹‹ደውልልኝ በይው›› ብሎ ስልኩን ትቶ ይሄዳል፡፡ ተደዋውለው ‹‹የእኔ ነው›› ከተባባሉ ነገሩ በዚያው ያልቃል፡፡ በቃ አንቺ ጋ አይደርሱብሽም ማለት ነው ፤ ለአንደኛው ብቻ ትከፍያለሽ፡፡

በዚህ ዓይነት ቢዝነስ ማስፋፋት አስቸጋሪ አይሆንም? አዎ!! ቢዝነስሽ እየሰፋ ሲመጣ ቢዝነስ በከፈትሽበት ቦታ ሁሉ ችግር ይገጥምሻል ----እንደአዲስ ክፍያ መጠየቅሽ አይቀርም፡ ለፓፓሽ ታሳውቂና እነሱ ተነጋግረው ስምምነት ያደርጋሉ፡፡ ይኼ የአንቺ ጉዳይ አይደለም፡፡ “እኔ ግዛት ውስጥ የአንተ “ቢዝነስማን” መጥቶ ስለሚሠራ፣ለአንተ ከሚከፍልህ አስር ሺህ ዶላር ውስጥ ሁለት ሺ ዶላሩን ለእኔ ትከፍለኛለህ፣ የእኔ ግዛት ነው›› ተባብለው እነሱው ይስማማሉ፡፡ አንቺ ፓፓሽ የወሰነብሽን ብቻ ነው የምትከፍይው፡፡ ማፍያዎቹ በቢዝነሳችሁ የሚያግዟችሁ--- የሚሰሩላችሁ ነገር አለ? በሬስቶራንቱ ውስጥ ጉልቤ ወይም ዱርዬ መጥቶ ሂሳብ አልከፍልም ካለ ደውለን እንነግራቸዋለን፣ መጥተው አንገቱን አንቀው አስከፍለውት ይሄዳሉ፡፡ ሌላ ችግር እፈጥራለሁ የሚል ካለም አንዱ የማፍያ አባት ከሁለት መቶ እስከ ሶስት መቶ የሚደርሱ ወታደሮች ስላሉት ችግር የለም፡፡ መጥተው አፍንጫውን ሰብረውት ይዘውት ይሄዳሉ፡፡

የገባሻትን ቃል ከጠበቅሽ ለደህንነትሽ ስጋት የለብሽም፡፡ እኔ እና አንቺ ስንሰራ ለምሳሌ ‹‹ስጋ አቀርብልሃለሁ›› ብለሽ ከእኔ መቶ ሺህ ብር ብትወስጅና ብትክጂኝ “ለፓፓ” እንጂ ለመንግስት ወይም ለፖሊስ ሪፖርት አታደርጊም፡፡ ፓፓው ቤትሽ መጥቶ ‹‹ያደረግሽው ነገር ጥሩ አይደለም፤ የእኛን ልጅ ሃቅ አጥፍተሻል፤ ስለዚህ በሳምንት ጊዜ ውስጥ ሁለት መቶ ሺ ብር ታመጪያለሽ›› ተብሎ ይበየንብሻል፡፡ ቅጣት መሆኑ ነው? አዎ ቅጣት ነው፡፡ ‹‹ይሄን ባትፈፅሚ ልጅሽን አታገኚውም፤ ባልሽ ከስራ አይመጣም፤ አንቺም ላትኖሪ ትችያለሽ›› በማለት አስጠንቅቀውሽ ይሄዳሉ፡፡ ስለዚህ ከየትም ታመጫታለሽ፤ ክህደት የሚባል ነገር አይወዱም፡፡ ነገር ግን አንቺን ለማስጠቃት ሆን ብዬ “መቶ ሺ አበድሬው አልመለሰልኝም›› ብዬ ብዋሽና አጣርተው ቢደርሱበት በተመሳሳይ ቅጣቱ በእኔ ላይ ይጣላል፡፡

ህግ አስከባሪ ማፍያዎች ማለትም ይቻላላ ..? ህግ አስከባሪዎች ናቸው (ሳቅ) ለምሳሌ ለመንግስት መክፈል ያለብሽን ታክስ ካልከፈልሽ አይለቁሽም፡፡ የተከራየሽውን ቤት ኪራይ በወቅቱ መክፈልም አለብሽ፡፡ በቢዝነስ ሥራ ውስጥ ከመንግስት የሚጠበቅብኝን ሁሉ መፈፀም አለብኝ፡፡ ስንት የማፍያ አባቶች ነበርዎት፤ያሳለፉት ውጣ ውረድ ምን ይመስላል? ብዙ ውጣ ውረዶች ነበሩ፡፡ የአንድ ቀበሌ ማፍያ አለቃ ድንገት ይመጣና ‹‹የአንተን የማፍያ አለቃ አላውቅልህም፤ ለእኔ ትከፍለኛለህ፡፡ ለእኔ ካልከፈልከኝ በግንባርህ ጥይት ነው የምለቅብህ›› ብሎ ይሄዳል፡፡ ወይንም ደግሞ ‹‹ነገ ጠዋት መቶ ሺህ ብር ይዘህ እንድትመጣ፣ እዚህ ቦታ መጥቼ እወስዳለሁ›› ሊልሽ ይችላል፡፡ ይሄኔ ለፓፓሽ ደውለሽ ትነግሪዋለሽ፡፡ እሱም ወይ ችግሩን በቀላሉ ተነጋግሮ ይፈታዋል አሊያም ደግሞ “አውቃቸዋለሁ፤እነሱ ጭንቅላታቸውን ያማቸዋል፤ ከእነሱ ጋር ያለኝን ችግር እስክፈታ ከአካባቢው ዞር ብትይ ይሻላል›› ብለው ይመክሩሻል፡፡

ችግሩ እስኪፈታ መኖርያ ቤት መቀየር አለብሽ፡፡ ሶስት አራት ጊዜ እንዲህ ፈትነውኛል፡፡ አንድ ጊዜ ምን አጋጠመኝ መሰለሽ.. ‹‹ጋጊስታን›› የሚባሉት እቤቴ መጡና.. ጋጊስታን ምንድን ናቸው? ተባራሪ ማፍያዎች ናቸው፡፡ እኛ ጎንደር፣ ጎጃም፣ ወሎ፣ ባሌ..እንደምንለው በየክፍለአገሩ ይኖራሉ፡፡ ‹‹እኛ ክልል መጥተህ በመስራትህ ለእኛ መክፈል ይገባሃል›› ይሉኛል፡፡ ‹‹እኔ እኮ የእራሴ ሰው (ፓፓ) አለኝ--- ለምን አትነጋገሩም?›› አልኳቸው፡፡ ‹‹ያንተን ፓፓ አናውቅም! ትከፍላለህ ትከፍላለህ›› ብለው አፋጠጡኝ፡፡ ጉድ ፈላ! እንደነዚህ አይነት ማፍያዎች ከተለያየ ቦታ መጥተው ዘርፈው ነው የሚሄዱት፡፡ ተንቀሳቃሽ ናቸው፡፡ አንዴ ቦጭቀው ይሄዳሉ፡፡ ለፓፓዬ ደወልኩና ነገርኩት፡፡

‹‹አንተ ጋ መጡ?›› አለኝ፡፡ ፓፓዬ አውቋቸዋል፡፡ ‹‹አዎ›› አልኩት፡፡ ‹‹ሌላም የገደሉት ሰው ስላለ ችግሩን እስክፈታው ሌላ አካባቢ ሂድና ቤት ተከራይተህ ተቀመጥ›› አለኝ፡፡ ሶስት ወር ሌላ አካባቢ ሄጄ ተቀመጥኩ፡፡ እነሱ ሲፈላለጉ፣ ሲቀጣጠሩ፣ ሲነጋገሩ ቆዩ - ‹‹የእኛ ነው፤ የእናንተ አይደለም፡፡ እኛ ነን በፊት የምናውቀው…ከየት ነው ያገኛችሁት፤ እኔ ነኝ አባቱ፤ አይደለህም›› የሚለውን ከተነጋገሩ በኋላ አንድ ቀን መጡና ይዘውኝ ሄዱ፡፡ “ንግግራችን ላይ አንተ መገኘት አለብህ” ብለው ነው የወሰዱኝ፡፡ አንድ ትልቅ ሬስቶራንት ምድር ቤት ውስጥ ነበር ውይይታቸው የተካሄደው፡፡ እኔን መሃል አደረጉኝና በግራና በቀኝ ሃያ ሃያ ሆነው ተቀመጡ - ‹‹የእኔ ልጅ ነው፤ የእኔ ልጅ ነው›› ክርክር ያዙ፡፡ ‹‹እናንተ የእኔ አባት ልትሆኑ አትችሉም፡፡

የወለደኝ ለገሠ ደምሴ የሚባል አባት አለኝ›› አልኳቸው (ሳቅ) እነሱ ግን ‹‹እኔ ነኝ መጀመሪያ ያየሁት›› ማለታቸው ነው፡፡ ከዛ እኔን የሚጠይቁኝን ከጠየቁኝ በኋላ ‹‹ውጣ›› አሉኝ፡፡ ለእኔ ጠባቂ ሰጥተውኝ፤ታጅቤ መኪና ይዤ ስለነበር ተሰባሰቡና “ከእርሱ ፀጉር አንድ ፀጉር ብትወድቅ ነፍስ ይጠፋል፤እንዳትተኩሱ መኪናውን አስነስቶ ይሂድ” ብለው ተናገሩ፡፡ (ይሄ ሁሉ እንግዲህ በጠራራ ፀሐይ መንግስት ባለበት ነው የሚካሄደው) ጠቡ ወደ መታኮስ የሚያመራበት ጊዜ የለም…? ብዙ ጊዜ ማፍያዎች ሲጣሉ አካፋና መዶሻ መኪና ላይ ጭነው ወደ መቃብር ሥፍራ ነው የሚሄዱት፡፡ እዚያ ይተኳኮሳሉ፤ይገዳደላሉ፡፡ የተረፉት አካፋቸውን ከመኪና ላይ አውርደው የሞተውን ቀብረው ወደቤታቸው ይመለሳሉ፡፡ መቃብር ቦታ ከሄዱ ጠንከር ያለ ጠብ ተፈጥሯል ማለት ነው፡፡ እነዚህ ማፍያዎች ቤተሰብ፣ ልጆች--- ምናምን የላቸውም እንዴ? በህጋቸው መሠረት ማፍያ ሚስት የማግባት መብት የለውም፣ ንብረት ማፍራት አይችልም፤ ከእናት አባቱ ጋር መኖር አይችልም፡፡ ክልክል ነው፡፡ የውስጥ ህግና ደንብ አላቸው፡፡

ከዕለታት አንድ ቀን አዕዋፋት ተሰብስበው እያደኑ ስለሚይዟቸው ጠላቶቻቸው ይወያያሉ፤ አሉ፡፡ ዋና ሰብሳቢያቸው ንሥር ነው፡፡ ንሥር ያቀረበው ሃሳብ የሚከተለው ነበር፡- “እንደምታውቁት የምንወያየው የጠላቶቻችንን ፈሊጥ ተረድተን ራሳችንን ለማዳን ምን እናድርግ በሚለው ላይ ሲሆን ለዚህ አስፈፃሚ የሚሆነንን ተወካይ በመጨረሻ ለመምረጥ ነው፡፡ የምንመርጠው ተወካይ

1ኛ/ ባላንጣዎቻችን ጋ ሄዶ ማሳመን የሚችል

2ኛ/ለመወዳደርና ለመመረጥ አቅም ያለው

3ኛ/ከነሱ ጋር ተግባብቶ ውስጣቸውን ጥሩ አድርጐ ለማየትና ለኛ ሪፖርት ለማድረግ የሚችል

4ኛ/ በአደጋ ጊዜ ፈጥኖ ሊርቃቸውና ሊያመልጥ የሚችል መሆን ይኖርበታል፡፡

ሰብሳቢው ንሥር ባቀረበው ቅድመ - ሁኔታ ላይ ሁሉም ተስማሙ፡፡ በዚህም መሠረት የተለያዩ አዕዋፋት ለምርጫ ቀረቡና በከፍተኛ ድምጽ የተመረጠችው ቆቅ ሆነች፡፡ ቆቅም ባደረገችው ንግግር፤ “ወንድሞቼ እህቶቼ፤ አዕዋፋት ሆይ! እናንተን እወክል ዘንድ ስለመረጣችሁኝና ዕምነታችሁን ስለጣላችሁብኝ ከልብ የመነጨ ምስጋናዬን አቀርባለሁ፡፡ እንደምታውቁት በአሁኑ ጊዜ መመረጥ ከፍተኛ ፈተና ያለበት ነው፡፡ ምክንያቱም፤ ሀ) ባላንጦቻችን ከመቼውም የላቀ አንድነት ያላቸው ሰዓት በመሆኑ፤ ለ) በውድድሩ እንድንሳተፍ ያደረጉን ተሳትፎ እንዲኖረንና ሌሎቹ ጫካ ነዋሪ እንስሳት ስለደግነታቸው እንዲያደንቋቸው ስለሆነ፤ ሐ) ወዳጅና ጠላታቸውን ለመለየት ቢያንስ ከእኛ አንዱ በመካከላቸው እንዲገኝ ብለው ስላሰቡ፤ ይመስለኛል። ሆኖም ካለመሳተፍ መሳተፍ የበለጠ ጥቅም ይኖረዋልና እናንተን መስዬ፤ እናንተን አክዬ እና እናንተን ሆኜ ለመቅረብ ዝግጁ ነኝ፡፡ ይህንንም ለማሳካት ሦስት ዘዴዎችን ለመጠቀም እሞክራለሁ፡፡

1ኛው ወቅታዊነት ነው፡፡ 2ኛው ከእነሱ የሰፋ አስተሳሰብ ይዞ፣ ቀድሞ መገኘት ነው፡፡ 3ኛው እነሱን አለመናቅና ሊበልጡኝ የሚችሉበት አንዳንድ ጉዳይ እንደሚኖር ማመን ነው፡፡ ሁሉም በቆቅ ሃሳብ ተስማሙና አጨበጨቡላት፡፡ በመጨረሻ እርግብ እንድትናገር እድል እንዲሰጣት ጠየቀች፡፡ ተፈቀደላት፡፡ እርግብም፤ “ወንድሞቼ፣ እህቶቼ አዕዋፋት ሆይ! ቆቅ በመመረጧ እንደማናችሁም በጣም ተደስቻለሁ፡፡ ሆኖም አንድ ቅር ያለኝ ነገር አለ፡፡ ይኸውም፤ ቆቅ፤ “ቆቅ” የሚለውን ስሟን ይዛ የትም አትደርስም የሚል ዕምነት ነው ያለኝ፡፡ ስለዚህ ስሟን ብትቀይር ጥሩ ነው እላለሁ፡፡ ማን እንበላት ካላችሁም እኔ “ዋ-ኔ” የሚል ስም ቢሰጣት መልካም ነው እላለሁ አለች፡፡” ሁሉም መስማማታቸውን በክንፋቸው በማጨብጨብ ገለፁ፡፡ እርግብም ቀጥላ “አሁን የሚያዋጣን ዛሬ ከባላንጦቻችን መወዳጀት ነው” አለች፡፡ “ለነገስ?” ብለው ጠየቋት፡፡ “ለነገማ የሆዳቸውን ስናውቅ እንወስናለን!” አለች፡፡

*** ከጥበብ ሁሉ የሚልቀው ወቅትን ማወቅ ነው፡፡ ወቅትን አለማወቅ አቅምን ካለማወቅ እኩል ነው፡፡ “እያንዳንዱ ድል አንድ አንድ ጠላት እንደሚወልድ አትርሳ” ይላሉ ፀሐፍት፡፡ ስለዚህም አሸነፍኩ ብሎ ዘራፍ ማለት ከመሸነፍ አንድ የሚሆንበት ጊዜ አለ፡፡ ድልን በማጭበርበር የምንቀዳጅ ከሆነም ዕድሜ ልካችንን እንቅልፍ እንዳይወስደን ያደርገናል፡፡ ፖለቲካ ብዙው እጁ ሸፍጥ ነው፡፡ ሁኔታዎችን ለራስ እንደሚመች ለማድረግ ማናቸውንም ዘዴ መጠቀም ይጠይቃል፡፡ ደራሲና ፀሐፌ ተውኔት ፀጋዬ ገ/መድህን በአንደኛው ቴያትሩ እንዳለው፤ “አብዮትኮ ኳስ ጨዋታ ነው፡፡ አቀበለ፣ ተቀበለ፣ ይዞ ሄደ - መታ - ፎሪ ወጣ፤ አብዮቱ ከሸፈ ይባላል፤ ወይም ቀጥሎ ደግሞ “ይዞ ሄደ! አብዶ ሰራ! መታ! - ጐል! አብዮቱ ግቡን መታ!! ይባላል፡፡

ይሄው ነው አብዮት ማለት - ኳስ ጨዋታ ነው፡፡ መቼ እንደምናቀብል፣ መቼ ወደፊት እንደምንሄድ፣ መቼ አብዶ (ምሣ) እንደምንሠራ ካላወቅን ፖለቲከኛ መሆን አንችልም፡፡ ይህንን ምንጊዜም መርሳት የለብንም፡፡ “የጐጃም ትውልድ በሙሉ ከአባይ እስከ አባይ” በሚለው መጽሐፉ፤ ደራሲ ግርማ ጌታኹን፣ እንዲህ ይላል … “ወለተ አልፋ አመተ አልፍን ወለደች፡፡ ከዚህ የሚአሳዝን ታሪክ አለበት፡፡ በአገር ላይ ያለ ወንድ ሁሉ በጦርነት አልቆ ወንድ ተወዶ ሳለ፤ ወለተ አልፋና ዓመተ አልፋ ዲማ ገበያ ሲሄዱ፣ ዝያ የሚባል ውሃ ሞልቶ አንድ ወንድ ጐዳነኛ ወስዶት ከዛፍ ላይ ሰቅሎት አዩ፡፡ “ሰው ነህ ግንድ” አሉት፡፡ እርሱ ግን የውርጭ ድደን ጥርሱን ገጥሞት መናገር ቸግሮት ነበርና ከዛፉ አውርደው ፀሐይ ቢአሞቁት፤ ዘመድ ላይ ከጃራ ሹም የመጣሁ ነበርሁ፡፡

ግን ውሃው አዋረደኝ ተፋኝ አለና ተናገረ፡፡ የዚህ ጊዜ እናትና ልጆች የኔ ባል ይሁን የኔ ባል ይሁን ተባባሉበት፡፡ ተያይዘው ከዲማ መነኮሳት ከነአባ ተጠምቀ መድኅንና ከነአባ ዮሐኒ ዘንድ ለፍርድ ሄዱ፡፡ እኒያም ሲፈርዱ አንች ባል አግብተሺ ቤት ሠርተሺ እርስዋን ወልደሻል፡፡ እርሷ ባል ሳታገባ ሳትወልድ ልታረጅ ነውና ለርስዋ ይሁን፡፡ አንች ብታገኝ አግቢ፤ ብታቂ መንኩሺና ተቀመጪ፣ ብለው ፈረዱ ይባላል፡፡” ወንድ ሁሉ ካገር የሚጠፋበት ዘመን አያድርስብን፡፡ እናትና ልጅ በአንድ ባል የሚጣሉበትን ጊዜ አይጣልብን! ድፍረትን ከሀፍረት ሳንነጥል የምናይበት ዐይን ይስጠን - በተለይ በምርጫ ወቅት፡፡ ዘራፍ ማለት፣ አለሁ አለሁ ማለት፣ ያለ እኔ ማን አለ ማለት፣ ካለፈው አለመማር፤ ከመርገምት ሁሉ የከፋ መርገምት ነው፡፡ ምንጊዜም ቢሆን፤ “የሚባለው ነብር ከጓዳ ሳይወጣ የሚበላው ፍየል ተክለፍልፎ መጣ” የሚለውን አገርኛ ግጥም አንርሣ!

የንባብ ባህልን ማበረታታት ዓላማው አድርጎ መጋቢት 7 ቀን 2002 ዓ.ም ፕሮግራሙን የጀመረው “ብራና” የሬዲዮ ፕሮግራም ሦስተኛ ዓመቱን ነገ በ8 ሰዓት በጣይቱ ሆቴል ጃዝ አምባ አዳራሽ ሲያከብር፣የሙዚቃ ተመራማሪው አርቲስት ሠርፀ ፍሬስብሃት “ለንባብ ባህል መዳበር የመንግስትና መንግስታዊ ያልሆኑ ተቋማት ሚና” በሚል ርእስ ጥናቱን ያቀርባል፡፡ በተመሳሳይ መልኩ ዲያቆን ዳንኤል ክብረት “የኢትዮጵያውያን የንባብ ልምድ በሀገር ውስጥና በባህር ማዶ” በሚል ርእስ አስተውሎቶቹን በቃለ ምልልስ መልክ እንደሚያቀርብ ይጠበቃል፡፡ በ “እናት ማስታወቂያ” እየተዘጋጀ በኤፍ ኤም አዲስ 97.1 የሚቀርበው የሬዲዮ ዝግጅት ዘወትር እሁድ ከምሽቱ 2 ሰዓት እስከ 4 ሰዓት በሚተላለፈው እያንዳንዱ ዝግጅት ላይ ጥያቄ ለሚመልሱ 10 አድማጮች መፃሕፍት እየሸለመ መሆኑን አዘጋጆቹ አስታውቀዋል፡፡

*የወንድ ልጅ ብልት ቆርጠው “ተጫወችበት” ይላሉ--- *ቦንብ ታጥቀሽ ራስሽን አፈንጂ ተብዬ ነበር ---- *አፍሪካውያንን በኤሌክትሪክ ማቃጠል የተሰጠኝ የሥራ ኃላፊነት ነበር--- *ውሃ ስንጠይቅ ሽንታቸውን ነበር የሚሰጡን …እላያችን ላይ ይሸናሉ … ከአማርኛ ይልቅ አረብኛ መናገር ይቀናታል፡፡ የምትናገረው በቁጭት፣ በእልህና በፍርሃት ስሜት ነው፡፡ ከአራት ዓመት በፊት ለሥራ ወደ ሶሪያ የተጓዘችው ሃረግ (ሜሪ)፤ በሶርያ ከጦርነቱ መጀመር ጋር ተያይዞ ያሳለፈችውን መከራና ስቃይ በአንደበቷ ትናገራለች - አንዳንዴ በሰመመን፣ ሌላ ጊዜ በመንገሽገሽ፡፡ ከሶሪያ በሱዳን በኩል አድርጋ ወደ ኢትዮጵያ በገባች በአምስተኛ ቀኗ ከጋዜጠኛ አበባየሁ ገበያው ጋር ያደረገችውን ቃለምልልስ ከዚህ በታች አቅርበነዋል፡፡ በሶርያ በምን ሥራ ላይ ነበር የተሰማራሽው? በ2009 ዓ.ም ወደ ሶርያ የሄድኩት በአውሮፕላን ነበር፡፡ እንደሌሎች ሴት እህቶቼ የቤት ውስጥ ሥራ ሳይሆን እርሻ ላይ ነበር ሥራ ያገኘሁት፡፡ ሥራዬ የወይራ ፍሬ መልቀም እንዲሁም ሙዝ፣ ትፋህ፣ አትክልትና ፍራፍሬ መኮትኮት፣ ማጨድ፣ ወዘተ ነበር፡፡ አንድ አመት ሙሉ ብቻዬን ነው የሠራሁት፡፡ ሴት ነሽ--- እንዴት የእርሻ ሥራን ልትመርጪ ቻልሽ? በመጀመሪያም ወደ ሶሪያ ስሄድ ሰው ቤት እንደምቀጠር አልነበረም የተነገረኝ፡፡ እዚያ ስደርስም ወደ ገጠር ነው የተላኩት፡፡ በእርግጥ ግብርናውን ወድጄው ነበር፡፡ ግን የምኖርበት ሰውዬ በጣም አስቸገረኝ፡፡ የተቀጠርኩበት ቤት እናትና ልጅ ነበሩ፡፡ ልጁ ትልቅ ሰው ቢሆንም የአእምሮ ዘገምተኛ ነበር፡፡ እናቱ አሮጊት ናት፡፡ ልጅዬው በተደጋጋሚ ይዝትብኝ ነበር፡፡ አብረሽኝ ካልተኛሽ እያለ ያስጨንቀኛል፡፡ ምን ልበልሽ… በጣም ያሳቅቀኝ ነበር፡፡ እና ስራዬን ሰርቼ ወደ ቤት መመለስ እንደ ጦር ነበር የምፈራው፡፡ ይመታኛል፣ ይጎትተኛል፣ ይጎነትለኛል … አንድ ዓመት ሙሉ በእነዚህ ሰዎች ቤት በስቃይ ቆየሁ ፡፡ ምን ያህል ነበር የሚከፈልሽ? ከዚህ ስሄድ 125 ዶላር እንደሚከፈለኝ ነበር የተነገረኝ፡፡ እዛ ስደርስ ግን መቶ ዶላር ሆነ፡፡ እንዲያም ሆኖ አንድ ዓመት ሙሉ የሰራሁበትን ገንዘብ ከሰዎቹ አልተቀበልኩም፡፡ በቃ ጠፍቼ ነው … የሄድኩት፡፡ በየወሩ አልነበረም ደሞዝ፡፡ አንድ ዓመት ከስድስት ወር ከሰራሽ በኋላ ነው የሚከፍሉሽ፡፡ እንዴት ጠፋሽ? በእርሻው ቦታ ላይ ስሰራ ጎረቤታችን የሆነ አንድ መልካም ሰው ሁልጊዜ ሁኔታዬን ያይ ነበር፡፡ አንድ ቀን አናገረኝ፡፡ እኔም የሚደርስብኝን በደል ሁሉ አጫወትኩት፡፡ እዚህ ሰውዬ ቤት ስቀጠር ህፃን ልጅ አለው ተብዬ ነበር … ይመስለኛል ለሰውዬው ማረጋጊያና ስሜት መወጫ ነው የወሰዱኝ፡፡ እኔ ከሄድኩ በኋላ እናቱን ሌላ አገር ልኳቸው እኔ ብቻ ከእርሱ ጋር ቀረሁ፤ ለሦስት ወር ሁለታችን ብቻ ነበር፡፡ በየጊዜው ይደበድበኝ ነበር፡፡ በተደጋጋሚ በስለት አስፈራርቶ ደፍሮኛል፤ እ..ከዛ በጣም ታመምኩኝ፣ አርግዤ ነበር፡፡ ‹‹ፔሬዴ ቀርቷል፤ ሃኪም ቤት ውሰደኝ አሊያም ወደ አገሬ ላከኝ›› አልኩት፡፡ ‹‹እገልሻለሁ›› አለኝ፡፡ ስንት ቀን እየፈራሁ ዛፍ ላይ ወጥቼ ‹‹አልወርድም›› እለው ነበር፡፡ … ይሄን ሁሉ ይመለከት ነበር - ያ ጎረቤታችን ሰውዬ፡፡ በኋላ ‹‹ከተማ ወስጄሽ የውጪ ዜጎች ቤት ትቀጠሪያለሽ›› አለኝ፡፡ ጎረቤትሽ ማርገዝሽን ያውቅ ነበር? አውቋል፡፡ ወደ ከተማ ሊወስደኝ የተነሳሳው እኮ ይህንንም ሚስጢር አጫውቼው ነው፡፡ ከዚያም ‹‹ማርሊዬስ›› የሚባል ክርስቲያን አረቦች የሚሄዱበት ቤተክርስትያን ወስዶ ጣለኝ፡፡ እዚያ ችግሬን ነገርኳቸው - ለቤ/ክርስቲያኑ ቄስ፡፡ ሀሙስ፣ አርብና ቅዳሜ ለሦስት ቀን ቤተክርስትያን ውስጥ አሳደሩኝ፡፡ “እሁድ ነው ኢትዮጵያውያኖች የሚመጡት፤ ከእነርሱ ጋር ትገናኛለሽ” አሉኝ፡፡ እሁድ ዕለት ኢትዮጵያውያኖች መጡ - ብዙ ናቸው፡፡ የደረሰብኝን በሙሉ አጫወትኳቸው፡፡ ቅዳሴ እንኳን ሳያልቅ ነው ይዘውኝ ወደ ቤታቸው የሄዱት፡፡ አንድ እንደ ትልቅ እህቴ የማያት ሴት ነበረች … ለእሷ ምስጢሬን ሁሉ አጫወትኳት፡፡፡ ‹‹ምንም ችግር የለም›› አለችና ሃኪም ቤት ሄድን፡፡ አስመረመረችኝ -----የሁለት ወር ተኩል እርጉዝ ነሽ ተባልኩ፡፡ እዛ አገር ማስወረድ ክልክል ነው፡፡ እርጉዝ ከሆንሽ ወደ አገርሽ አይልኩሽም፡፡ ከተወለደ በኋላ ልጁን ነጥቀው ነው አንቺን ወደ አገርሽ የሚሰዱሽ፡፡ በጣም አስቸጋሪ ህይወት ነው፡፡ ብወልደውም ልጄን አይሰጡኝም፤ ለማስወረድ ደግሞ ገንዘብ አልነበረኝም … እስከ አምስት መቶ ዶላር ያስፈልጋል ፡፡ ያቺ እንደ ትልቅ እህቴ የማያት ልጅ የምታውቀውን ሰው አነጋግራልኝ፣ እሱ ረዳኝና ፅንሱን አቋረጥኩ፡፡ ልጆች በእስር ቤት ወልደው የሚያሳድጉ ኢትዮጵያውያኖች አሉ ይባላል … በርካታ ኢትዮጵያውያኖች፣ ኤርትራውያኖችም … አሉ፡፡ እኔ ፅንሱን ካቋረጥኩ በኋላ … ሁለት ሳምንት … እቤቷ አረፍኩ፡፡ ምናልባት ሰውዬውም የሚያፈላልገኝ ከሆነ በሚል … ሁለት ሳምንት ሙሉ ከቤት አልወጣሁም፡፡ ከሌሎች ኢትዮጵያውያኖች ጋር ተገናኘሽ … ደማስቆ ውስጥ ያሉ ኢትዮጵያውያኖች በሙሉ እርስ በርስ ይተዋወቃሉ፡፡ በሳምንት አንድ ቀን እሁድ እሁድ አንድ ላይ እንውላለን፣ ቡና ይፈላል፣ ተሰብስቦ እረፍት መውሰድ፣ መዝናናት የተለመደ ነው፡፡ ሴቶቹ ሰው ቤት ነው የሚሠሩት፡፡ ወንዶቹ ግን አይቀመጡም--- እዛ አገር የሚሄዱበት ምክንያት በቱርክ አድርገው ወደ ሌላ አገር ለመሻገር ነው፡፡ አንቺ ከዛ በኋላ ሌላ ሥራ አገኘሽ ወይስ----- ራሴ አማርጬ ሰው ቤት ተቀጠርኩ፡፡ ቋንቋ ስለማውቅ ችግር አልገጠመኝም፡፡ አሮጊትና ሽማግሌ ባልና ሚስቶች ቤት ተቀጥሬ መሥራት ጀመርኩ ፡፡ ይኸኛውስ ቤት ተስማማሽ? ምን ያህል ይከፈልሽ ነበር? መጀመሪያ ስገባ መቶ ሃምሳ ዶላር ነበር፡፡ በኋላ ሁለት መቶ ሃያ አምስት ዶላር ሆነልኝ፡፡ አሮጊቷ ከተኛችበት አትነሳም፡፡ 85 ዓመቷ ነበር -- እሷን አንስቼ አጥባለሁ፡፡ ፓምፐርስ (የሽንትና የሰገራ መቀበያ) እቀይርላታለሁ፡፡ … መርፌ አወጋግ ልጃቸው አሰልጥናኝ -- መርፌ እወጋቸው ነበር፡፡ እንደ ልጃቸው ነበር የሚያዩኝ፡፡ ልጆቻቸው ዩኤን ነው የሚሠሩት፡፡ የመጀመርያው ቤት ፓስፖርቴን ትቼው ስለወጣሁ እዛ ተመዝግቤ በዚያ ወረቀት ነበር የምጠቀመው፡፡ አሮጊቷ የዛሬ ዓመት ሞተች፡፡ ከዛ ሽማግሌው ልክ እንደ ሚስቱ ሆነ፡፡ እሱን ሳነሳ ስጥል … (95 ዓመቱ ነበር፡፡) ግን በጣም ጥሩ ሰዎች ነበሩ፡፡ የቤቱ ሃላፊ እኔ ነበርኩ፡፡ በጣም ሀብታሞች ናቸው፡፡ መኪና አስመጪና ላኪ ነበሩ፡፡ ሴቷ ልጅ ነበረች የቤተሰቦቿን ሀብት የምታስተዳድረው፡፡ ምን ያህል ጊዜ ሰራሽ? አራት ዓመት ከ6 ወር አብሬአቸው ነበርኩ፡፡ ጦርነቱ ሲጀመር ሃብታሞች ስለሆኑ ሁሉን ነገር ትተውት ወጡ፡፡ በመሃል እኔ ቀረሁ፡፡ ልጅቷ ፓስፖርት ልታወጣልኝ በጣም ደክማልኛለች፤ ግን አልተሳካም፡፡ እና ቤቱን ለእኔ ጥለው ወደ ቤሩት ተሳፈሩ፡፡ አካባቢው በጣም አስቀያሚ ነበር፡፡ አሸባሪዎች እንደፈለጉ የሚገቡበት የሚወጡበት ቦታ ነበር፡፡ እዚያ መኖር እንደማልችል አውቄዋለሁ፡፡ የነበርኩባቸዉ ሰዎች ደግሞ ክርስቲያኖች ነበሩ፡፡ አሸባሪዎች ይፈልጓቸዉ ነበር፡፡ ያንን ትልቅ ቤት ጥለውልኝ ብቻዬን ተሸክሜው ስለቀረሁ ተጨነቅሁ … መወሰን ነበረብኝ፡፡ በርካታ ቤተክርስያኖች ተቃጥለዋል፡፡ ፈርሰዋል፡፡ የሚሸሸው ክርስቲያኑ ነው፡፡ ፓስፖርት ያለው ይሸሻል፡፡ ፓስፖርት ኖሮት ብር የሌለው ኢትዮጵያዊ አለ---ሁሉም መሸሽ ነው፡፡ እስር ቤት መግባትም አለ፡፡ እኔም እጣ ፋንታዬ ይሄው ሆነ፡፡ በእስር ቤት ውስጥ .. የነበረውን ሁኔታ ንገሪኝ? እስር ቤት አንድ ወር ተቀመጥኩ፡፡ እስር ቤት እኮ የገባሁት ልመጣ አካባቢ ነው ከዛ በፊት በአሸባሪዎች እጅ ወድቄ ስንት ነገር ደርሶብኛል..በአሁኑ ሰዓት በጣም በረዶ ነው፡፡ እስር ቤት አትበይው … ‹‹የምድር ጀሃነም›› ነው፡፡ እዚህ ካዛንቺስ ሆነሽ ፍንዳታ ከተሰማ ተነስተሽ መገናኛ ድረስ ነው የምትሮጪው፡፡ ትራንስፖርት የለም፣ ከተያዙ መያዝ ነው፤ የሚሞተውም ይሞታል፡፡ አሁን እኔ በወጣሁበት ሰዓት ከተማው ላይ ብዙም ጦርነት አልነበረም፡፡ ዳር ዳሩ ላይ ነበር፡፡ እኔ ደግሞ እንደ አቃቂ ባለ ከከተማው ዳር ነበር የምኖረው፡፡ ከደማስቆ ራቅ ይላል፡፡ በጣም ብዙ ኢትዮጵያውያን ሴቶች በሴተኛ አዳሪነት ይሠራሉ የሚባለው እውነት ነው? ወደው አይደለም ሴተኛ አዳሪ የሚሆኑት፡፡ ፓስፖርት የላቸውም፤ ሊቀጠሩ ሲሄዱ ፓስፖርት ይጠየቃሉ፡፡ ቀጣሪዋ ‹‹አልፈግሽም›› ብላ ልታባርራት ትችላለች ፡፡ መኖር፣ መብላት ስላለባቸው የግድ ለእንደዚህ ዓይነት ህይወት ይዳረጋሉ፤ እዚያ ደግሞ የኢትዮጵያ ቆንስላ የለም፤ ኤርትራውያን እንኳ ቆንስላ አላቸው፡፡ ኤርትራዊ ላይ አንድ ችግር ቢደርስበት ቆንስላው ወደተከራየው ቤቱ ይወስዳቸዋል፡፡ ኢትዮጵያውያን በጣም የሚያሳዝን ነው ኑሯቸው ፡፡ አሁን እንኳን ወደ አገራቸው መምጣት አቅቷቸው በየሜዳው ወድቀዋል፡፡ በጦርነቱ ቤቱ ሁሉ እየፈረሰ ነው፡፡ ተከራይተው የሚኖሩት ንብረታቸውን ማውጣት አልቻሉም፡፡ የሴቶች ህይወት … በቃ ይሄው ነው፡፡ ወደው አይደለም የገቡበት ---- ኢትዮጵያውያኖች ያ ባህል ኖሯቸው አይደለም፤ በችግር ነው፤ አማራጭ በማጣት፡፡ እስር ቤት ከመጣልሽ በፊት..በአሸባሪዎች እጅ ወደቅሽ? በጣም አሰቃቂ ነው … በአሸባሪዎች እጅ ላይ ወደቅሁኝ፡፡ /ሰውነቷ ይንቀጠቀጣል፣ ለደቂቃዎች በዝምታ ቆየች፤ አይኖቿ እንባ አቀረሩ …) አየሽ ሰውነቴን … (ትከሻዋ አካባቢ እያሳየችኝ … የተቃጠለ ገላ …) ምንድን ነው? ሲጋራ ተርኩሰውብኝ ነው … … አሸባሪዎቹ ናቸው እንዲህ ያደረጉኝ--- የት ነው የወሰዱሽ? ቢሄዱት የማያልቅ ምድር ቤት (Underground) አላቸው፡፡ ውስጥ ለውስጥ ተቆፍሮ … የቀለጠ ከተማ ነው፡፡ በአንድ አቅጣጫ ብቻ እንዳይመስልሽ … ወደ አምስትና ከዛም በላይ አቅጣጫ መግቢያ መውጭያ ያለው ነው … የታሰሩ ሰዎች የሚሰቃዩበት፣ የጦር መሳሪያ በየዓይነቱ በብዛት ያለበት … ኑሯቸውም እዛው ነው? አዎ፡፡ ሴቶችም ወንዶችም አሉ፡፡ ብዙ ጊዜ አሸባሪዎቹ አይወልዱም፡፡ ከወለዱ ግን የልጆቻቸው አስተዳደግ አሰቃቂ ነው፡፡ በፊት ለፊታቸው አንገት በቢላዋ እየተቀላ፤ እጅና ጣት እየተቆረጠ … ያንን እያዩ ነው የሚያድጉት፡፡ ወንዶችን በፊንጢጣቸው … ኤሌክትሪክ ይልኩባቸዋል፡፡ ሴቶችን ህፃናቱ ፊት ይደፍራሉ፡፡ … የ3 እና የ5 ዓመት ህፃናት እንዲያዩ እንዲለማመዱ ይገፋፏቸዋል፡፡ የአሸባሪዎቹ ሚስቶች እዚያው አሉ፡፡ እነርሱም ሰውን ያሰቃያሉ፡፡ ሴትን ሴት፤ ወንድን ወንድ ነው የሚያሰቃየው፡፡ ሚስቱ ካሰቃየችኝ በኋላ ‹‹አምጫት›› ብሎ ይደፍረኛል፡፡ ሱዳኖች፣ ናይጄሪያዎች፣ ሴኔጋሎች … ብዙ የአፍሪካ ዜጐች ነበሩ - የሚሰቃዩ፡፡ የተለያየ አደንዛዥ ዕፅ ይሰጡናል፤ በመርፌ የሚወጋ፣ የሚጨስ፣ የሚሸተት … በግዴታ ነበር፡፡ ከዚያ መጋረፍ ነው … ወንዶቹ ብልት ላይና ምላሳቸው ጫፍ ላይ ኤሌክትሪክ ያደርጉባቸዋል፡፡ እኔን … ቦንብ ታጥቀሽ ራስሽን ታጠፊያለሽ ብለውኝ ነበር፡፡ ‹‹ላ … ላ›› አልኳቸው፡፡ ከዛ … የደረሰብኝን ስቃይ … (ረጅም ትንፋሽ) እስቲ የደረሰብሽን ንገሪኝ … … በቃ ተይው ይቅር … (ለመሄድ ተነስታ ተመልሳ በማቅማማት ተቀመጠች) አይዞሽ ንገሪኝ … ስታወሪው ይሻልሻል … ለመናገር ይከብዳል፡፡ የወንድ ልጅን ብልት ቆርጠው አምጥተው “ተጫወችበት” ይላሉ--- በጣም … አስቀያሚ ነው … ተይኝ ባክሽ … በተደጋጋሚ ስትደፈሪ እርግዝና አልተፈጠረም? ሃሃ … (ሳቅ) የሚሰጡኝ መድሃኒትስ … አምፒሲሊን ይሁን … ምን ይሁን አላውቅም ግን ይሰጡኝ ነበር … ስለዚህ እርግዝና የለም፡፡ ስቃይ ሲበዛብሽ … ምንም አትይም … ቁጣ ወይ ደግሞ … “በቃ ራሴን አፈነዳለሁ” አልኳቸው:: ውይ ሳልነግርሽ … ምግብ የለም፣ ውሃ በምንጠይቅ ሰዓት ሽንታቸውን ነበር የሚሰጡን … ሲያሰኛቸው በገላችን ላይ ይሸናሉ፡፡ ትንሽ ውሃ በተለያዩ ማደንዘዣ ዕፆች ቀላቅለው ጠጡ ይሉናል ፡፡ ያን ከሰጡኝ በኋላ የሚያደርሱብኝ ስቃይ አይታወቀኝም … እና “አፈነዳለሁ” ብዬ ተስማማሁ … ወጥቼ ልሙት … አንድ ኢትዮጵያዊ ይህንን እንዳዳረገች ሁሉም ይወቅ ብዬ ወሰንኩ፡፡ ከእንግዲህ ምን ቀረኝ … ብሬን ንብረቴን ወስደውታል፡፡ አማርኛ የማወራው--- ችግሬን የማስረዳው ሰው እንኳን የለም፡፡ እንዲህ እናድርግ ምናምን ብላችሁ ከሌሎቹ ጋር አትማከሩም ነበር? እኔ ከሴቶች ጋር ሳይሆን ከወንዶች ጋር ነበር ይበልጥ የምቀራረበው፡፡ ናይጀሪያኖች፣ ሱዳኖች … ሱዳኖች በእኔ ስቃይ በጣም ተጐድተዋል … ስጮህ ይሳቀቁ ነበር፡፡ በእነሱ ፊት ይገናኙኝ ነበር፡፡ አፍሪካውያኖችን በኤሌክትሪክ አቃጥይ ይሉኝ ነበር፡፡ “ሂጅና አቃጥያቸው”፤ “ሽንትሽን ሽኝባቸው…” እባላለሁ፡፡ እነሱ ጋ ስደርስ በጣም አለቅስ ነበር፡፡ ጣታቸውን … እግራቸውን ይቆርጡባቸዋል፡፡ … ህክምና የለ፤ ደማቸው እየፈሰሰ ነው የሚውሉት … አቃተኝ (ረጅም ትንፋሽ) ምን ያህል ነበሩ? አስራ ሶስት፡፡ ከሞቱት ሌላ ማለቴ ነው---- (ደረትዋን ደጋግማ በእጅዋ ትይዛለች) አቤት ...ሽታው በልብሴ ...በሠራ አካላቴ ጠረኑ ሁሉ..ይመጣብኛል፡፡ ናይጀራዊው ጋ ሄጄ የታዘዝኩትን ስነግረው ..በአረብኛ ‹‹..አድርጊው..ካላደረግሽው አትወጪም፤ እኛንም አታድኝንም..አድርጊው..ለኩሽኝ..›› አለኝ፡፡ አልቻልኩም፤ የመጀመሪያ የጨካኝነት ልምምድ ነበር፡፡ አለቀስኩኝ፡፡ በብዛት ኮኬን እወስድ ነበር፡፡ ስትለኩሺያቸው ቆመው ያዩሽ ነበር? አዎ.. ደስ ይላቸዋል፡፡ .ናይጀሪያዊውን እየለኮስኩት ሳለ “ጭኔ ላይ የምታያት የበር ቁልፍ ናት፡፡ እቺን ይዘሽ መውጣት ትችያለሽ” አለኝ፡፡ እሱን እየለኮስኩ ቁልፉን ወሰድኩት፡፡ አረቡ እያየን አልነበረም፡፡ ናይጄሪያዊው ቁልፉን ከየት አገኘው? ከየት እንዳገኘው መጠየቅም አልፈለኩም፤ ጊዜውም አልነበረኝም፡፡ ማውራት አንችልም ነበር፤ ከናይጀሪያዊው ጋር ልንግባባ የምንችለው በአረብኛ ቋንቋ ብቻ ነው፡፡ በንግግርሽ ውስጥ እንግሊዝኛ ከሰሙ ...ጉድሽ ነው፡፡ የተለየ ቋንቋ እንድትናገሪ አይፈቀድልሽም፡፡ (ንግግርዋን አቋርጣ) ይቅር በለኝ--- አሰቃየኋቸው፡፡ በኤሌክትሪክ ከለኮስኳቸው በኋላ ስላለቀስኩ ..‹‹ለምን ታለቅሻለሽ›› ብለው አሰቃዩኝ፡፡ ‹‹የገነት ፓስፓርት›› የሚሉት አለ፡፡ የገነት ፓስፖርት ... ሰው ገድለው ገነት የሚገቡበት ፓስፖርት፡፡ የራሳቸው የቡድን ፓስፖርት ነው፡፡ ‹‹ነፍስ አጠፋለሁ›› ብዬ ስነሳ ፓስፖርት ተሰራልኝ፡፡ ፓስፖርቱ ምን አለው? ምንም፡፡ የእኔ ስምና የቤተሰቤ ስም ዝርዝር አለው፡፡ አረንጓዴ ነው፡፡ ፎቶ የለውም፡፡ ስትገልጪው ይሄ ብቻ ነው የያዘው መረጃ፡፡ “የገነት ፓስፖርት” ይላል ፅሁፉ፡፡ ፓስፖርቴ ተሰራልኝ፡፡ እላዬ ላይ ቦንብ ካጠመዱልኝ በኋላ የገነት መግቢያ ፓስፓርቴም፣ አብሮ ይታተምልኛል፡፡ ፓስፖርቴ ተሰራ፤ አብሬያቸው እሰግድ ነበር፤ ቁራን እንዴት እንደሚቀራ አስተማሩኝ፡፡ “የዛሬ 15 ቀን ወደ ገነት መሄጃሽ ነው ማረፍ አለብሽ” ብለው ነገሩኝ... እረፍቱ የት ነው …? ‹‹የምድር እረፍት›› ነው የሚሉት፡፡ 15 ቀኑን የሟች ሬሳ በተጠራቀመበት … (ፀጥ አለች) … ሰውነታቸው የተቆራረጠ ሰዎች በብዛት ተገድለው በተጣሉበት … ከነበርንበት ወደ አንድ ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ … ሬሳ ውስጥ … ከሙታን ጋር፡፡ ጨካኝ … እንድትሆኝ ነው … እዚያ የጉድጓድ መውጫ በር አለ … ያ … ናይጄሪያዊ የሰጠኝ ቁልፍ መውጫ ነው … እሱ እኮ ከታሰረ ሁለት ዓመቱ ነው … ጦርነቱ ሲጀምር የተያዘ ነው፡፡ እረፍት እንደሚወስዱኝ ሁሉ ያውቃል፡፡ … በዚያ አሰቃቂና ዘግናኝ ቦታ በአጋጣሚ ህይወቱ ያላለፈ ትኩስ ቁስለኛ … (የገደሉት መስሏቸው ትተውት የሄዱት) አገኘሁ፡፡ ለመሞት ጥቂት ደቂቃዎች ነበር የቀረው፡፡ የእረፍቱ ቦታ..... ሱሪ እና አሮጌ ነገር አለበሱኝ፤ ሬሳው ውስጥ ተቀመጥኩ፡፡ … እፀልይ ነበር … ቁልፉን እንዴት ይዘሽው ገባሽ? በማህፀኔ ውስጥ ደብቄ … በምኔም ልደብቅ አልችልም ነበር፡፡ ስፀልይ ሰውየውም ቀና አለ … እጅግ ያሳዝናል … ሰውነቱ ሁሉ የተጠባበሰ ነው … ተበለሻሽቷል፡፡ ይህ ሰው እንደተጋደመ “ሬሳዎቹን … ገለል ገለል አድርገሽ ውጪ” ብሎ አሳየኝ … የደረጃ መወጣጫ … አለው … እሱ ሲወጣ አስፓልት ይገኛል፡፡ እየመጡ አያዩሽም ነበር? በፍፁም አያዩኝም … 15 ቀን ካረፍኩ በኋላ መጥተው ይወስዱኛል … ብቅ ብለው ግን አያዩኝም፡፡ ከዛ ሰው ጋር ተግባባሁ፤ ውሃ … ሲለኝ ሽንቴን ሸንቼ ሰጠሁት፡፡ ህይወቱን ለትንሽ አተረፍኩት፡፡ … በሌሊት በሩን ከፈትን … ተሸክሜ … አወጣሁና ጣልኩት፡፡ እነሱ ለሊት ለሊት ስራ አይሰሩም፡፡ ስራቸው ቀን ነው፡፡ በግርግር ጫጫታ ባለበት ሰዓት እንጂ … ጨለማ ተገን አድርገው እንኳን ሰውን አይደበድቡም፡፡ ቢያስተጋባ ቢሰማብን ብለው ስለሚያስቡ ይፈራሉ፡፡ ሌሊት መጠጣት ነው ሥራቸው፡፡ የቆሻሻ ቱቦ … ስር ለስር … የትና የት የሚደርስ--- ውስጥ ለውስጥ የሚያስኬድ መንገድ መሰለሽ … እንደ ምንም ደረጃውን ተሸክሜው … እየጎተትኩት … ወጥተን ያ ናይጄሪያዊ በሰጠኝ የበለዘ ቁልፍ … ከፈትኩት … ስወጣ አስፓልት ላይ ነው የወጣሁት፡፡ ቅርብ ነው ለከተማው፡፡ ምሽት ላይ ነበር፤ ማንም ዝር አይልም፡፡ ‹‹ስምርዬ›› የሚባል ቦታ አለ፡፡ እንደ አውቶብስ ተራ ዓይነት ነው፡፡ አስፓልቱ ላይ ከወጣን በኋላ … ተሸክሜ ያወጣሁት ሰው … የተወሰነ ቦታ ድረስ እየጎተትኩት ከተማ አካባቢ ስንደርስ አደባባይ ላይ ጥዬው ሄድኩ፡፡ ከወጣሁ በኋላ ደክሞኛል … አሞኛል፡፡ ኢትዮጵያኖችን መጠጋት አልቻልኩም፡፡ ለምን? በጣም አስቀያሚ ሁኔታ ላይ ነበርኩ፡፡ ሀሺሽ ጠጥቻለሁ፣ ጠረኔ በጣም መጥፎ ነው፤ ፀባዬ ከፍቷል፡፡ በዛ ሰዓት የሄድኩት ቤተክርስቲያን ነው፡፡ ፀለይኩ … አለቀስኩ … የት እንደምሄድ አላውቅም፡፡ … ሁሉ ነገር ብርቅ ሆኖብኛል፡፡ መንገድ ላይ ስዘዋወር አንድ ኢትዮጵያዊ አገኘሁ፡፡ ሳናግረው “ሰምተናል ሰምተናል” አለኝ፡፡ ምኑን? አንዲት ኢትዮጵያዊ ተይዛለች መባሉን፡፡ ማን እንደሆነች ግን አላወቅንም ነበር፡፡ በአሸባሪዎች እጅ ወደቀች ሲባል ሰምተናል - አለኝ፡፡ በአገሪቱ ላይ ስልክ የሚባል የለም … አጋጣሚ ሆኖ በነጋታው ወደ ካናዳ የሚሳፈር ልጅ ነበር፤ በጣም አዘነ፡፡ ከዛ ጉድጓድ ከወጣሁ በኋላ ግን በጣም ፈራሁ … የሚያየኝ ሰው ሁሉ የሚያውቀኝ የሚከተለኝ… የሚገለኝ ይመስለኝ ነበር፡፡ ቀን ቀን ስታያቸው ኖሮማል ሰው ስለሚመስሉ፤ ለብሰው ዘንጠው ስለሆነ የሚወጡት … አንድ ሰው አስተውሎ ካየኝ ከእነርሱ መካከል አንዱ ይመስለኝ ነበር፡፡ በአጋጣሚ በዛን ወቅት ደግሞ በዊግ ቁጥርጥር ተሰርቻለሁ … በፀጉሬ ይለዩኛል ብዬ እሰጋም ነበር፡፡ “እባክህ ከአንድ ሱናዳዊና ናይጄሪያዊ የተሰጠኝ መልዕክት አለ … ስማቸው እገሌ ይባላል … ሂጂና ያሉበትን ቦታ ተናገሪ ስላሉኝ እዛ ውሰደኝ” አልኩት፡፡ ናይጄሪያዎች በጣም ጎበዞች ናቸው … እንዴት እንደሚወጣ … ያውቃሉ ----ጥበበኞች ናቸው እና ይሄን ልንገር አልኩት፡፡ የተባለው ቦታ ወሰደኝ፡፡ ... ነገርኳቸው፡፡ ተላቀስን -- ቁልፍ ሰጥቶ ያስወጣኝ የናይጄርያው ወንድም “ኢሾ” ይባላል፡፡ ምን ማድረግ እንዳለብን አወራን፡፡ ቦታው እንደዚህ ዓይነት ቦታ ነው፤ ቁልፉም ይሄው … ‹‹ስጪያቸው እነርሱ ምን ማድረግ እንዳለባቸው ያውቃሉ ነው ያለኝ” አልኩት፡፡ ቁልፉ ላይ … ሌላ መልዕክት አለው? እንዴ … እንዴት አወቅሽ? --- ቁልፉ ሰፋ ያለ ነው.. በላዩ ላይ በራሳቸው ቋንቋ ፅፈውበታል … ሰጠኋቸውና አወጣጤን ነገርኩት፡፡ አለቀሱ፤ በህይወት የለም ብለው ደምድመው ነበር፡፡ (እንባዋን እየጠረገች) አንድ ኢትዮጵያዊ ከአንድ ሱዳናዊ ጋር አገናኘኝ፡፡ በጣም ባለውለታዬ ነው-- እንደ ነገ ወደ ካናዳ በረራ ነበረው--- ለእኔ ሲል ቀኑን አራዘመ … በሃሺሽና በተለያዩ ሱሶች የተበከለው ደሜ … ባህሪዬን አስከፍቶት ስለነበረ መርዙ ከደሜ እስኪወጣ ድረስ ተቸገርኩ፡፡ ስለዚህ … አስመረመረኝ … ከሰው ጋር ትንሽ ትራቅና ትቀመጥ ተባለ … መድሃኒት ተሰጠኝ፡፡ ያ ያስተዋወቀኝ ያልኩሽ ሰው በሱዳን አድርጌ ወደ ኢትዮጵያ እንድመጣ ነገሮችን ያመቻችልኝ ጀመር፡፡ ሌላ ዳዊት ባህሩ የሚባል ኢትዮጵያዊ (እዛ የሚኖር የአሜሪካ ዜግነት ያለው) … የቻልኩትን ሁሉ እረዳታለሁ … ፓስፖርቷንም በማውቀው ሰው አወጣላታለሁ አለ፡፡ የምንኖረው አንድ አፓርታማ ላይ ነው፡፡ እኔን ይዞ ሲወጣ ሲገባ ያየ ሰው በትኩረት ያየኝ ነበር፡፡ ስወጣ ከእግር ጥፍሬ እስከ ራስ ፀጉሬ ተከናንቤ ነበር የምወጣው፡፡ እዛ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ደግሞ አይከናነቡም፡፡ ‹‹አሸባሪ ናት፤ ጥቁር ናት ግን ተከናንባ ነው የምናያት ፈራናት›› ብለው አስጠቆሙኝና እስር ቤት ገባሁ፡፡ የዩኤን ወረቀት ነበረኝ፡፡ የደረሰብኝን ነገር ሁሉ አጫወትኳቸው፡፡ እስር ቤት ውስጥ ስገባ ለእኔ እረፍት ነበር፤ አልተጐዳሁም፡፡ ከእስር ቤት ውጪ ያሉ ኢትዮጵያውያን በየሜዳውና በየመናፈሻው ወዳድቀው ተወንጫፊና፣ ተፈንጣሪ መሳሪያ እየወደቀባቸው ይሞታሉ፡፡ እኔ በቅርብ የማውቃት ልጅ የሞተች አለች፡፡ እኔ እዚህ ስመጣ … አሁንም የሚያስለቅሰኝ እዛ የሚኖሩ ኢትዮጵያውያን ሁኔታ ነው … ቢያንስ መቶ ኢትዮጵያውያንን ማምጣት ቢቻል ---

በጉብዝናህ ወራት የመጦሪያህን ነገር አስብ! ከድሬዳዋ ጅቡቲ መንገደኞችንና ለንግድ ሥራ የሚንቀሳቀሱ ኮንትሮባንድ ነጋዴዎችን የሚያመላልሰው ባቡር የዘወትር ደንበኛ ነበሩ፡፡ በድሬዳዋ ከተማም እኔ ነኝ ያሉ እውቅ የኮንትሮባንድ ነጋዴ በመሆናቸው ወ/ሮ ፋጡማ ሮብሌን የማያውቅ የድሬዳዋ ከተማ ነዋሪ አልነበረም፡፡ በወጣትነትና በጐልማሳነት የዕድሜ ዘመናቸው ከፊናንስ ወታደሮች እየደበቁ፣ አንዳንዴም እየተሻረኩ ደህና ጥሪት ለመያዝ ችለው ነበር፡፡ የኮንትሮባንድ ንግዱ ከጉምሩክ ፍተሻ ሲያልፍ አትራፊ፣ በኬላ ላይ በሚደረግ ፍተሻ ሲወረስ ደግሞ እጅግ አክሣሪ መሆኑን ቀድሞውኑ ያውቁ ነበርና በየጊዜው የሚያጋጥማቸው ነገር ሣይረብሻቸው ለዓመታት በዚሁ ንግድ ዘለቁ፡፡ የኩባንያ ሠራተኛ የነበሩት ባለቤታቸው በሞት ስለተለዩዋቸውና ሰባቱን ልጆቻቸውን የማሣደጉና የማስተማሩ ኃላፊነት በእሣቸው ትከሻ ላይ ብቻ በመውደቁ፣ ቀን ከሌት ሣይሉ የሚባትሉ ትጉህ ነጋዴ ነበሩ፡፡

በኮንትሮባንድ ንግዱ ላይ የሚደረገው ፍተሻና ቁጥጥር ከጊዜ ወደ ጊዜ እየጠነከረ ሲሄድ ሁሉም ነገር እንደቀድሞው ቀላል አልሆንላቸው አለ፡፡ በደካማ አቅማቸው እሣት ከላሱ ነጋዴዎች እየተጫረቱ የሚያመጡትን ልባሽ ጨርቆች ኬላ ላይ የፊናንስ ወታደሮች ያስቀሩባቸው ጀመር፡፡ ለምግብ እንጂ ለሥራ ያልደረሱት ልጆቻቸው ይህንን የእናታቸውን ችግር ለመረዳት የሚችሉበት ዕድሜ ላይ አልነበሩምና ችግራቸውን ለብቻቸው ለመወጣት መፍጨርጨራቸውን ቀጠሉ፡፡ ጨከን ብለው የኮንትሮባንድ ንግዱን ጥለው ወደ ሌላ ሥራ እንዳይሰማሩ አልችለውም የሚል ሥጋት ያዛቸው፡፡ ምን አድርጌ? …እኔ … ከልጅነት እስከ ዕውቀት ሥሠራው የኖርኩትና የማውቀው ሥራ ይህንኑ ብቻ ነው፡፡ ሌላ ሥራ አላውቅ፡፡ ጭንቀቱ ፈተናቸው፡፡ እስኪ ትንሽ ቀን … ነገ ምን እንደሚመጣ ማን ያውቃል … ተስፋቸውን ሰንቀው ጥረታቸውን ቀጠሉ፡፡ አንዴም ሲያስከፋ አንዴም ሲያስደስታቸው የኖረው የኮንትሮባንድ ንግድ፤ ከቀናቶች በአንደኛው ቀን የመኖር ተስፋቸውን የሚያጨልምና ህይወታቸውን አደጋ ላይ የሚጥል አጋጣሚ ፈጠረባቸው፡፡

ከድሬዳዋ ጅቡቲ መንገደኞችን አሣፍሮ ይጓዝ የነበረው ባቡር በመገልበጡ፣ በባቡሩ ላይ ተሳፍረው ከነበሩት መንገደኞች አብዛኛዎቹ የሞትና ከባድ የመቁሰል አደጋ ደረሰባቸው፡፡ እንደ ዕድል ሆነናም ወ/ሮ ፋጡማ በአደጋው ከባድ ጉዳት ደርሶባቸው ከሞት ከተረፉት መንገደኞች መካከል አንዷ ሆኑ፡፡ ሁኔታው እጅግ አሣዛኝ ነበር፡፡ በአደጋው በወ/ሮ ፋጡማ እግሮችና እጆች ላይ ጉዳት ደርሷል፡፡ እነዚያ ሮጠው የማይጠግቡት እግሮቻቸው ያለ ድጋፍ አልንቀሣቀስ አሏቸው፡፡ የሰው እጅ አላይም ብለው ሲታትሩ የኖሩት እናት፤ አካል ጉዳተኝነት ከቤት አዋላቸው፡፡ የወ/ሮ ፋጡማን ቤት ችግር ገባው፡፡ ልጆች ኑሮን ለመቋቋም አቅም አጡ፡፡ ህይወት ፈተና ሆነችባቸው፡፡ የወ/ሮ ፋጡማ ልጆች ይህንን የህይወት ፈተና እንደ እናታቸው ተጋፍጠው ለመቋቋም የሚያስችላቸውን አቅም አላገኙም፡፡ ቀስ እያሉ ከፈተናው እየወደቁ ቀሩ፡፡ ከወለዷቸው ሰባት ልጆቻቸው መካከል ደካማና ህመምተኛ እናትን የመጦርና የመንከባከብ፣ ታናናሽ እህትና ወንድሞችን የማስተማርና የማሣደግ ኃላፊነትን ለመወጣት የሚችል ልጅ ማግኘት የማይቻል ሆነባቸው፡፡

የሚሆነውን ሁሉ አልጋ ላይ ሆነው ከማየት የዘለለ ነገር የማድረግ አቅም አጡ፡፡ እነዛ የነገን ተስፋ የሰነቁባቸው፣ ተምረውና አድገው ይጦሩኛል ያሏቸውና ያለ አባት ያሣደጓቸው ሰባት ልጆቻቸው በየተራ ይህቺን ዓለም እየተሰናበቷት ሔዱና እናታቸውን ብቸኛ አደረጓቸው፡፡ ህይወት ይብስ ጨለመች፡፡ ሰባት ልጆቻቸውን ሞት የነጠቃቸውን እናት፤ ከልጆቻቸው መካከል አንደኛዋ አያት አድርጋቸው ነበርና ከዚሁ ህፃን ጋር ኦና ቤታቸውን ታቅፈው ቀሩ፡፡ እንደ ቀድሞው እዚህም እዚያም ብለው ሠርተው መኖር ባለመቻላቸው ቤታቸው የሚላስ የሚቀመስ ነገር ጠፋ፡፡ ይህንን ሁኔታ የተረዱት የአካባቢያቸው ሰዎች እዛው ድሬዳዋ ከተማ ውስጥ ወደሚገኘው “ዳዊት የአረጋውያን መጦሪያ ድርጅት” እንዲሄዱ መከሩአቸው፡፡ ወደ ድርጅቱ ሲመጡም የእሳቸው ዓይነት እጣ ፈንታ የገጠማቸውን በርካታ አረጋውያን በማየታቸው እንደገና የመኖር ተስፋቸው ለመለመ፡፡ ወ/ሮ ፋጡማ ዛሬ በማዕከሉ በየቀኑ ለቁርስ ብቻ የምትሰጣቸውን ምግብ ለመቀበል ማልደው እያነከሱ ወደ ማዕከሉ ይመጣሉ፡፡

ይህቺኑ ከድርጅቱ የምትሰጣቸውን ምግብ ከሚያሣድጉት የልጃቸው ልጅ ጋር እየተቃመሱና ለነፍስ ያሉ በጐ አድራጊ ግለሰቦች በሚያደርጉላቸው የአልባሳት እርዳታ ህይወታቸውን እየገፉ ይገኛሉ፡፡ እኚህን እናት ያገኘኋቸው Help age Ethiopia የተባለ ድርጅት ሰሞኑን በድሬዳዋ ከተማ ውስጥ የሚገኙ ሁለት የአረጋውያን መርጃ ማዕከላትን ባስጐበኘን ወቅት ሲሆን ወ/ሮ ፋጡማ በዳዊት የአረጋውያን መረጃ ማዕከል ውስጥ የሚረዱ እናት ናቸው፡፡ አሰገደች አስፋው የአረጋውያን መረጃ ማዕከልም በጉብኝት ፕሮግራሙ በጋዜጠኞች የተጐበኘ የአረጋውያን መረጃ ማዕከል ነው፡፡ ሁለቱም ማዕከላት በግለሰቦች የራስ ተነሳሽነት የተቋቋሙ ቢሆንም ለአረጋውያኑ የእርዳታ አገልግሎት የሚሰጡት በተለያዩ መንገዶች ነው፡፡ ወ/ሮ ፋጡማ ሮብሌን ያገኘሁበት “ዳዊት የአረጋውያን መርጃ ማዕከል” ለአረጋውያኑ እርዳታና እንክብካቤ የሚያደርገው አረጋውያኑ በመኖሪያ ቦታቸዉ ላይ ሆነው በየዕለቱ ጠዋት አንድ ጊዜ የምግብ አገልግሎት በመስጠት ሲሆን ህክምናና አልፎ አልፎ ደግሞ የአልባሣት ድጋፍም ያደርግላቸዋል፡፡ በወ/ሮ አሰገደች አስፋው መጦሪያ ማዕከል ውስጥ ያየኋቸው አረጋውያን ግን ሙሉ ኑሮአቸው በዚሁ ድርጅት ውስጥ ሆኖ፣ በቀን ሦስት ጊዜ ምግብ እየተመገቡ የቀንና የሌሊት ልብስ ተሰጥቶአቸው ህክምናም እንዲያገኙ እየተደረገ ነው፡፡

በሁለቱም የአረጋውያን መጦሪያ ማዕከላት ዘር፣ ሃይማኖትና ብሔር ቦታ የላቸውም፡፡ 950 አረጋውያን የሚረዱበት የ“ዳዊት አረጋውያን መርጃ ማዕከል” ዋና ሥራ አስኪያጅ አቶ ዳዊት በቀለ እንደነገሩን፤ ማዕከሉ ከተለያዩ በጐ አድራጊ ድርጅቶች የሚያገኘውን እርዳታ ለእነዚህ አረጋውያን እንዲደርሳቸው ያደርጋል፡፡ አረጋውያኑን ከአንድ ጊዜ በላይ ለመመገብ የማዕከሉ አቅም አለመፍቀዱን ተነግሮናል፡፡ ከማዕከሉ እርዳታ ከሚያገኙት አረጋውያን ብዙዎቹ ልጆቻቸው በህይወት የሌሉና እጅግ ከፍተኛ በሆነ የድህነት ህይወት ውስጥ ያሉ ናቸው፡፡ በማዕከሉ ውስጥ የኤች አይ ቪ ኤድስ ህሙማንም አግኝተናል፡፡ እነዚህ አረጋውያን ከዕድሜያቸው መግፋት በተጨማሪ በሽታው ባስከተለባቸው አዕምሮአዊና አካላዊ ህመም ሣቢያ እንደ ልባቸው ተሯሩጠው የዕለት ጉርሳቸውን ማግኘት አይችሉም፡፡ ማዕከሉ ደግሞ የሚሰጣቸው በቀን አንድ ጊዜ ለቁርስ የምትሆን ሩዝ፣ ዳቦ ወይም ቅንጬ ብቻ ነው፡፡

ይህ በቂና ተመጣጣኝ ምግብ ማግኘት ለሚገባው የኤች አይቪ ኤድስ ታማሚ የሚበቃ አይደለም፡፡ ሆኖም አረጋውያኑ በዚህች ብቻ ለመኖር ተገደዋል፡፡ ሰዓቱን ጠብቆ መወሰድ የሚገባውን መድሃኒት ለመውሰድ አረጋውያኑ ምግብ እስኪሰጣቸው አይጠብቁም፡፡ በባዶ ሆዳቸው ይውጡታል፡፡ ይህ ደግሞ ዕድሜ፣ ረሀብና በሽታ ያደከማቸው አረጋውያን አንጀት የሚችለው አይደለም፡፡ ይህንን ሁኔታ ማዕከሉ ታሳቢ አድርጐ በተለይ ለኤች አይቪ ህሙማን የተለየ እንክብካቤና ድጋፍ ሊያደርግላቸው ይገባል የሚል እምነት አለን፡፡ ሌላው በዳዊት የአረጋውን መርጃ ማዕከል ውስጥ ያገኘናቸው አዛውንቶች ትልቅ ችግር የመኖሪያ ቤት እጦት ነው፡፡ አብዛኛዎቹ አረጋውያን ወደ ማዕከሉ የሚመጡት ልጆቻቸውን ወይም ቤተሰቦቻቸውን በሞት ሲነጠቁና ጧሪና ረዳት ሲያጡ ነው፡፡ በተለያዩ ምክንያቶች ከመኖሪያ ቤታቸው ተፈናቅለው በየእምነት ተቋማቱ ደጃፍ እና በየጐዳው ላይ የወደቁ አረጋውያን ቁጥር በርካታ ነው፡፡ በዳዊት የአረጋውያን መርጃ ማዕከል ውስጥ ያገኘኋቸው ተረጂ አረጋውያን እንዳጫወቱኝ፤ በቅርቡ ሁለት የዚህ ማዕከል ተረጂ የነበሩ አዛውንቶች በጅብ የመበላት ክፉ እጣ ገጥሟቸዋል፡፡ ይህ እጣ ፈንታ በሌሎችም በእድሜ በገፉና ጧሪና ቀባሪ ባጡ አረጋውያን ላይ የማይደርስበት ምክንያት የለም፡፡ ሌላው በድሬዳዋ ከተማ ውስጥ አረጋውያንን ሰብስቦ እርዳታና ድጋፍ የሚያደርግላቸው ማዕከል የወ/ሮ አሰገደች አስፋው የአረጋውያን መጦሪያ ማዕከል ነው፡፡

በአንዲት እናት በጐ ፈቃደኝነት የተቋቋመው ማዕከሉ፤ ዛሬ አንድ መቶ ሰላሳ ረዳትና ደጋፊ የሌላቸውን አረጋውያን ሰብስቦ ይጦራል፡፡ ሰማንያ የሚደርሱትን ደግሞ እዚያው በመኖሪያ ቤታቸው ውስጥ እርዳታ እያደረገላቸው ይገኛል፡፡ የድርጅቱ መስራች ወ/ሮ አሰገደች አስፋው፤ የሞላ ቤት ንብረታቸውን ሸጠው፣ ወርቅና ጌጣቸውን በገንዘብ ለውጠው አረጋውያኑን ወደ መጦርና መንከባከቡ ሥራ ሲገቡ “አበደች” ያላላቸው ሰው አልነበረም፡፡ ከልጅነታቸው ጀምሮ እድሜያቸው የገፉ ሰዎችን መርዳትና መንከባከብ፣ የተቸገሩን ማገዝ ደስታ ከሚሰጧቸው ተግባራት መካከል ዋንኞቹ ነበሩ፡፡ ይህ በልጅነት እድሜ የተጀመረው ያጡትን የመርዳትና የመደገፍ ፍላጐት እድሜያቸው ከፍ እያለ ሲሄድ አልተዋቸውም፣ እንደውም ሀብትና ንብረትን አስንቆ ከአረጋውያንና ከደካማ ሰዎች ጋር አብሮ መኖር ይበልጥ ደስታ እንዲሰጣቸው አደረጋቸዉ እንጂ፡፡ ልጆቻቸው ከአገር ውጪ ቢሆኑም በእናታቸው ሀሳብና ስራ ላይ ተቃውሞ የላቸውም፡፡ ይልቁንም አቅማቸው በፈቀደ መጠን እናታቸውን ለማገዝ ጥረት ያደርጋሉ፡፡ ይህን የወ/ሮ አሰገደችን ብርቱ ጥረትና ቀና ተግባር የተመለከተው የአለማያ ዩኒቨርሲቲም ለወ/ሮ አሰገደች ሰባት የወተት ላሞችን በእርዳታ ሰጣቸው፡፡ እርዳታና ድጋፍ አድርጉልኝ ማለት የማይሆንላቸው እኚህ ሴት፤ ከብቶቹ ገቢ ለማስገኘት እንዲችሉና በራሳቸው ገቢ ለመተዳደር እንዲበቁ ጥረት ማድረጋቸውን ቀጠሉ፡፡ የአረጋውያን መጦሪያ ማዕከሉን ባቋቋሙበት የተንጣለለ ሜዳ ላይ የጓሮ አትክልቶችንና የፍራፍሬ እርሻዎችን ማልማት ጀመሩ፡፡

ከእርሻ የሚያገኙትን ፍራፍሬ ለገበያ በማቅረብ እና ከወተት ላሞቹ ከሚገኘው የወተት ምርት ሽያጭ የሚገኘው ገቢ የወ/ሮ አሰገደችን ሀሳብ ከግብ ለማድረስ አቅም ሆናቸው፡፡ “እኛ እርዳታና ልመና አናውቅም ሠርተን እንኖራለን፡፡ የድሬዳዋ ህዝብ ደግሞ ደግ ነው፡፡ ተለይቶንም አያውቅ፡፡ ሁሌም ከጎናችን ነው” የሚሉት ወ/ሮ አሰገደች፤ ዛሬ ለማዕከሉ ገቢ ማስገኛ የሚሆን የሚከራይ ህንፃ በመገንባት ላይ ናቸው፡፡ ለስራ እንጂ ለወሬ እምብዛም ቦታ የማይሰጡት ወ/ሮ አሰገደች፤ ስለማዕከሉና ስለሚሰጡት እንክብካቤና ድጋፍ ብዙ መናገር አይፈልጉም፡፡ “እኔ ያደረግሁት ነገር የለም፡፡ ሁሉም በፈጣሪና በድሬዳዋ ህዝብ የሆነ ነው፡፡” የሚል ነው ምላሻቸው፡፡ እዚሁ መጦሪያ ማዕከል ውስጥ አግኝቼ ያነጋገርኳቸው አቶ አድነው ሸዋረጋ የተባሉ የ78 አዛውንት ወደዚህ ማዕከል ከመጡ ሶስት አመት እንደሆናቸው አጫውተውኛል፡፡ በማዕከሉ የሚደረግላቸውን እንክብካቤና ድጋፍ አስመልክተው ሲናገሩ፤ “እኔ ቃል የለኝም፡፡ በህይወቴ ሁሉ ከኖርኩባቸዉ ጊዜያት እዚህ ማዕከል ውስጥ ያሳለፍኩት ሦስት አመታት እጅግ የተለዩና አስደሳች ነበሩ፡፡ ንፁህ በልቼ ንፁህ ለብሼና ንፁህ መኝታ ላይ ተኝቼ እየኖርኩ ነው፡፡ የወጣትነትና የጉልምስና ዘመኔን የኖርኩት ወደፊት ምን ያጋጥመኛል የሚል ስጋትና ሀሳብ ሳይኖርብኝ ነው፤አስቤውም አላውቅም ነበር፤ ለካ ጌታ ይሄን አዘጋጅቶልኝ ነው፡፡ ልጆች አልወለድኩም፡፡

ግን ጧሪና ተንከባካቢ እግዚአብሔር ሰጥቶኛል” ብለዋል፡፡ በኢትዮጵያ ከሚኖሩት አራት ሚሊዮን አረጋውያን መካከል አብዛኛዎቹ እጅግ በከፋ ድህነትና ችግር ውስጥ እንደሚኖሩ የሠራተኛና ማህበራዊ ጉዳይ ሚ/ር በቅርቡ ይፋ ያደረገው መረጃ ያመለክታል፡፡ ከእነዚህ አረጋውያን መካከል መደበኛ ወርሃዊ የጡረታ ገቢ የሚያገኙት 500ሺ ያህሉ ብቻ እንደሆኑና ቀሪዎቹ አረጋውያን ከቅርብ ዘመዶቻቸውና ቤተሰቦቻቸው በሚያገኙት ጥቂት ገንዘብ እንደሚተዳደሩ መረጃው ይጠቁማል፡፡ አረጋውያኑ ከተተኪው ትውልድ ክብርና እንክብካቤ የማግኘታቸው ሁኔታ በእጅጉ እየቀነሰ መምጣቱን የጠቆመው መረጃው፤ ለዚህም ምክንያቱ አረጋውያንን የመጦር ባህልና ወግ መሸርሸሩና ቤተሰባዊ ትስስሩ እየላላ መምጣቱ ዋንኞቹ ናቸው ይላል፡፡ አረጋውያን ረዳትና ደጋፊ እንዲያጡ ከሚያደርጓቸው ሌሎች ምክንያቶች መካከል ስደትና ኤች አይ ቪ ኤድስ እንደሚገኙባቸው የጠቆመው መረጃው ፤ ከተለያዩ አካባቢዎች ስራና ትምህርት ፍለጋ ወደ ዋና ከተሞች የሚፈልሱ ወጣቶች አዛውንት ወላጆቻቸውን ለከፋ ድህነትና ረጂ አልባነት እንደሚዳርጓቸው አመልክቷል፡፡

ትኩስ የወጣትነት ጉልበትና ብሩህ አእምሯቸውን ለሀገራቸውና ለወገናቸው ዕድገትና መሻሻል ሲገብሩ ኖረው የዕድሜ ጀምበራቸው ስታዘቀዝቅ፣ ጉልበታቸው ሲደክም፣ ጧሪና ተንከባካቢ ሲያስፈልጋቸው፣ ጀርባችንን ልንሰጣቸው አይገባንም፡፡ እነዚህ ሁለት በግለሰቦች ተነሳሽነት የተቋቋሙት የአረጋውያን መርጃ ማዕከላት በስፋት ሊሰራባቸውና በሁሉም ክልሎች ተግባራዊ ሊሆኑ ይገባል፡፡ መንግስትም ሆነ ዜጎች ለጉዳዩ ተገቢውን ትኩረት ሊሰጡት ያሻል፡፡ የዛሬው ወጣት የነገ አረጋዊ መሆኑ አይቀርምና በጉብዝና ወራት የመጦሪያን ነገር ማሰቡም ተገቢ ነው፡፡

በኢንተርኔት አማካኝነት የተቃዋሚዎችን መረጃ ለመሰለልና እንቅስቃሴያቸውን ለመከታተል የሚያገለግል ማጥመጃ ሶፍትዌር (Trojan horse) የሚጠቀሙ 25 አገራት እንዳሉ የገለፀ አንድ የካናዳ የጥናት ተቋም፤ ኢትዮጵያን በማካተት የበርካታ አገራትን በስም ጠቅሷል፡፡ የኢትዮጵያ መንግስት አስተባብሏል፡፡ ማጥመጃው ሶፍትዌር በተለያዩ መንገዶች የቫይረስ መከላከያ ዘዴዎችን አልፎ እየሾለከ ወደ ኮምፒዩተር መግባት የሚችል ሲሆን፤ መረጃዎችን ለመምጠጥ፣ ፓስዎርዶችን ለመስረቅ፣ የስልክና የስካይፒ ግንኙነቶችን ለመቅረጽ፣ በተለይም የኢሜይል መልእክቶችን ለመሰለል ያገለግላል ተብሏል፡፡

በቶሮንቶ ዩኒቨርስቲ “ስር ሲቲዘን ላብ” የተሰኘው የጥናት ተቋም ረቡዕ እለት ይፋ ባደረገው ማስጠንቀቂያ፤ ሰዎች በኮምፒዩተርና በሞባይል ስልክ ውስጥ የሚያስቀምጡት መረጃ እንዲሁም የሚለዋወጡት መልእክት ለስለላ የተጋለጠ ነው ብሏል፡፡ እንዲያውም በኮምፒዩተራችሁ ላይ የተገጠሙ ማይክሮፎኖችና ካሜራዎችን በመጠቀም ቤት ውስጥ የምታደርጉት እንቅስቃሴና የምትናገሩት ነገር ሁሉ፣ የስለላ አይንና ጆሮ ውስጥ ሊገባ ይችላል ብሏል፡፡

ለስለላ ያገለግላል የተባለውና “ፊንፊሸር” የተሰኘው ማጥመጃ ሶፍትዌር በተገኘባቸው አገራት ሁሉ፣ መንግስታት በተቃዋሚዎችና በዜጐች ላይ ስለላ ያካሂዳሉ ማለት ባይቻልም፤ እንደ ኢትዮጵያ የመሳሰሉ ገናና (authoritarian) መንግስታት እጅ ውስጥ መግባቱ ግን አሳሳቢ ነው ብሏል ተቋሙ፡፡ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማዕረግ የኢንፎርሜሽንና ኮሙኒኬሽን ቴክኖሎጂ ሚኒስትር ዶ/ር ደብረጽዮን ገብረሚካኤል በበኩላቸው፤ ስለማጥመጃ ሶፍትዌሩ የምናውቀው ነገር የለም ብለዋል፡፡

የካቲት 23 ቀን 2005 ዓ.ም “በኢንዲያን ኢንተርናሽናል ት/ቤት የተማሪዎች ወላጆች ቅሬታ አቀረቡ” በሚል ርዕስ በወጣው የአዲስ አድማስ ዘገባ ላይ ት/ቤቱ ቅሬታውን በደብዳቤ ገልጿል፡፡ ት/ቤታችን ከተመሠረተበት እ.አ.አ ከ2006 ጀምሮ ከተማሪ ቤተሠቦች እና ከባለድርሻ አካላት የተመሠገነ መልካም ስም ያገኘ ሆኖ ሣለ፤ ሚዛን ያልጠበቀ ዘገባ በምናከብረው ጋዜጣችሁ ማቅረባችሁ ሃላፊነት የጐደለው ሆኖ አግኝተነዋል ሲሉ የት/ቤቱ ዳይሬክተር ሃሳባቸውን ገልፀዋል፡፡ በአጠቃላይ የወላጆችን ቅሬታ እንጂ የሠራተኞችን ምላሽ ሳያካትት በወጣው ዘገባ ቅሬታ ተሠምቶናል ይላል ደብዳቤው፡፡

የአዲስ አበባ የትራንስፖርት ቢሮ፣ ውጤት እያስመዘገብኩ ነው አለ እንዴት ቢባል፤ የታክሲ ስምሪት ላይ ጥብቅ ቁጥጥር በማካሄድ ነዋ ሌላ አዲስ አበባ ካለ ይነገረን፤ ነባሯ ከተማ ግን ታክሲ ተቸግራለች ገና ምኑን አይታችሁ? የትራንስፖርት ሚኒስትርም ያሰበው ነገር አለ ከከተማ ውጭ፣ ማታ ማታ የመኪና ጉዞ ክልክል ይሆናል ተብሏል በዚህም ውጤት ይመዘገባል - የትራንስፖርት እጥረትን የሚያባብስ ሜክሲኮ አካባቢ፣ የስራ መውጫ ሰዓት ላይ፣ ወደ ጦር ሃይሎችና ወደ አውቶቡስ ተራ ለመሄድ አዳሜ ይጋፋል።

ከወዲያ ማዶ፣ ወደ ሳሪስና ወደ ጎፋ፣ መዓት ሰው ይተራመሳል። ወዲህ ዞር ስትሉም፣ ወደ መገናኛ ለመሄድ የሚጠብቅ እልፍ ሰው ታያላችሁ። የታክሲ ስምሪት ከታወጀ በኋላ፣ የትራንስፖርት እጥረት ተባብሶ፣ ግፊያውና ግርግሩ ጨምሯል። ለዚህም ነው፤ በርካታ ፌርማታዎች ላይ ወረፋ የተጀመረው። እዚያው ሜክሲኮ አካባቢ በገሃር መስመር፤ ወደ አራት ኪሎ ታክሲ ለመሳፈር የሚፈልግ ከ150 በላይ ሰው በሁለት አቅጣጫ ተሰልፏል። ታክሲ ጠፋ! ለነገሩ “ታክሲ ጠፍቷል አልጠፋም” ለማለት ያስቸግራል።

ወረፋ ከሚጠብቁ ሰዎች አጠገብ ከአስር በላይ ሚኒባስ ታክሲዎች ተሳፋሪ አጥተው ቆመዋል። ግን ወደ ቦሌ መስመር የተመደቡ ናቸው፤ ከዚያ ውጭ ቢንቀሳቀሱ ቅጣት ይጠብቃቸዋል። ምን የሚሉት ቅዠት ነው? ከመቶ በላይ ሰዎች ታክሲ አጥተው ለወረፋ ተገትረዋል፤ ከአስር በላይ ሚኒባስ ታክሲዎች ተሳፋሪ አጥተው በሰልፍ ቆመዋል። ወረፋ ጠብቀው አራት ኪሎ ሲደርሱም፣ ነገርዬው ተመሳሳይ ነው። ከአራት ኪሎ ወደ ፒያሳና ወደ መርካቶ ለመሄድ ብዙ ሰዎች ይሻማሉ - በታክሲ እጥረት። ዞር ብለው ሲያዩ ግን፣ ከአራት ኪሎ ወደ አምባሳደር መስመር የተመደቡ በርካታ ሚኒባሶች፣ ተሳፋሪ ጠፍቶ አፋቸውን ከፍተዋል።

ተሳፋሪ ወደሚበዛበት ቦታ ሄደው መስራት አይችሉማ። በደርግ ዘመን የነበረውን የታክሲ ስምሪት እንደገና ተግባራዊ ለማድረግ ውሳኔ ያስተላለፉ ባለስልጣናት፤ ገና ከጅምሩ መዘዙን ማሰብ አይችሉም ነበር? ይችሉ ነበር። ሰው ናቸው። ደግሞም፣ እነሱ ባይችሉ እንኳ፣ አስቦ የሚመክር አልጠፋም ነበር። ለምሳሌ፣ የስምሪት ቁጥጥር በግንቦት 2003 ዓ.ም ተግባራዊ ከመደረጉ በፊት በአዲስ አድማስ የወጡ ፅሁፎችን በምሳሌነት መጥቀስ ይቻላል። የታክሲ ስምሪት የትራንስፖርት እጥረትን በማባባስ አሁን የምናየውን አይነት ቅዠት እንደሚፈጥር በግልፅ ተንትኖ የሚያቀርብ ፅሁፍ በአዲስ አድማስ መቅረቡን አስታውሳለሁ (የካቲት 26 ቀን 2003 ዓ.ም የአዲስ አድማስ እትም)። “በየአቅጣጫውና በየመስመሩ፤ የትራንስፖርት ፈላጊዎች ብዛት እንደእለቱና እንደሰአቱ፣ እንደወቅቱና እንደሁኔታው ይለያያል።

... የሰኞ፤ የአርብ፣ የቅዳሜና የእሁድ ተሳፋሪዎች ቁጥር ተመሳሳይ አይሆንም። ማለዳ 11 ሰአት፤ ጥዋት ሁለት ሰአት፤ ረፋዱ ላይ፣ ከቀኑ 11 ሰአት፤ ከምሽቱ ሶስት ሰአት በኋላ በዚያው መስመር የሚኖረው የተሳፋሪ ቁጥር… ይለያያል። በክረምት፤ በበአል ቀናት፣ በልዩ ዝግጅቶች፣ በሰርግ ወራትም እንዲሁ ለየቅል ነው። “...ታክሲዎች የራሳቸውን ገቢ ለማሳደግ ብዙ ተሳፋሪ ማግኘት ስላለባቸው፤ በእያንዳንዱ መስመር ላይ እንደሰአቱና እንደእለቱ፣ እንደወቅቱና እንደሁኔታው የሚለዋወጠውን የተሳፋሪ ቁጥር በማስተዋል (መስመራቸውን እያስተካከሉ) ለመስራት ይጣጣራሉ። ... በስምሪት ቁጥጥር ከተመደቡበት መስመር ውጭ እንዳይሰሩ ከተከለከሉ ግን ገቢያቸው ይቀንሳል፣ ታክሲ ፈላጊውም ይጉላላል” “በሆነ ሰአት፤ …ተሳፋሪ ከመብዛቱ የተነሳ፤ በዚያ መስመር ከተመደቡት ታክሲዎች አቅም በላይ ይሆናል። ... ብዙ ሰዎች በትራንስፖርት እጥረት ለሰአታት ይቆማሉ፤ ሌሎች ታክሲዎች መጥተው መስራት አይችሉም። …በሌሎች ቦታዎች ደግሞ ተሳፋሪ ከማነሱ የተነሳ፤ በቦታው የተመደቡ ታክሲዎች ያለስራ ቆመው ጊዜ ያባክናሉ። በትራንስፖርት እጦት ብዙ ሰው ወደተጉላላበት ቦታ ሄደው መስራት አይችሉም። ከጥቂት ሰአታት በኋላ፤ ሁኔታው ይቀየራል። በመጀመሪያው ቦታ ተሳፋሪ ጠፍቶ ታክሲዎች ያለ ስራ ይቆማሉ። በሁለተኛው ቦታ ደግሞ፤ በታክሲ እጥረት፤ ተሳፋሪዎች ለረዥም ሰአት ይጉላላሉ።

” “…ተሳፋሪ አጥተው ያለ ስራ የሚቆሙ ታክሲዎችን እና ታክሲ አጥተው የሚንገላቱ ተሳፋሪዎችን ማበራከት ነው የቁጥጥሩ ውጤት። ቢሮክራቶቹ… የቁጥጥር ሱስ… የመጣው ይምጣ የሚያሰኝ እጅግ ሃይለኛ ሱስ ካልሆነባቸው በቀር፤ መዘዙን ያጡታል ብሎ ለማሰብ ይከብዳል” እንዲህ እንደምታዩት፤ የስምሪት ቁጥጥሩ ተግባራዊ ከመደረጉ በፊት ጠቃሚ ምክር ቢቀርብም፣ የሚሰማ ባለስልጣን አልተገኘም። ለነገሩ፣ ከአንዳንድ የታክሲ ባለቤቶችና ሾፌሮች በስተቀር አብዛኛው ሰው፣ የታክሲ ስምሪት ጠቃሚ እንደሚሆን ገምቶ ነበር - የትራንስፖርት ችግር የሚቃለልለት መስሎት። ለምን መሰለው? ታስታውሱ እንደሆነ፤ አንዳንድ የታክሲ ሾፌሮችና ባለቤቶች ቅሬታቸውን ሲገልፁ፤ “ስምሪቱን የሚቃወሙት፣ ጥቅማቸው ስለሚቀርባቸው ነው” ተባለ። የዚህ ትርጉም ምን እንደሆነ አስቡት። አሃ… “ባለታክሲዎችና ሾፌሮች ከተጎዱ፣ ተሳፋሪ ይጠቀማል” ማለት ነዋ። እንዴት እንዴት? በንግድ እና በቢዝነስ ዙሪያ የብዙ ሰው አስተሳሰብ በጣም የተዛባ ከመሆኑ የተነሳ፤ ሻጮችና ሸማቾች፣ ባለታክሲዎችና ተሳፋሪዎች… ተቀናቃኝ ባላንጣ ሆነው ይታዩታል። ስለ ታክሲ ሲያስብ፣ 5 ሳንቲም አሳልፎ የማስከፈልና 5 ሳንቲም አጉድሎ የመክፈል ጉዳይ ብቻ ጎልቶ የሚታየው ሰው፤ “አንደኛው ወገን ጥቅም የሚያገኘው በሌላኛው ጉዳትና መስዋእትነት ነው” ብሎ ያምናል።

እናም፣ “ስምሪቱ ባለታክሲዎችን የሚጎዳ ከሆነ፣ ተሳፋሪዎችን ይጠቅማል” ብሎ ይደመድማል። የሰዎች ኑሮ፣ ከአውሬዎች ሕይወት ብዙም የተለየ ሆኖ አይታየውም - እርስ በርስ እየተቦጫጨቁ መኖር። እውነታው ግን፣ የዚህ ተቃራኒ ነው። አንዱ የሚጠቀመው፣ ሌላኛው ሲጠቀም ነው። ባለታክሲው የሚጠቀመው መቼ ነው? በሆነ አቅጣጫ በክፍያ ለመጓዝ የሚፈልግ ተሳፋሪ ሲመጣለት። ተሳፋሪው የሚጠቀመውስ? ክፍያ ተቀብሎ ለማጓጓዝ የሚፈልግ ታክሲ ሲመጣለት። የባለታክሲው ጥቅም እየጨመረ የሚሄደው፣ ብዙ ተሳፋሪዎችን ፈልጎ ሲያገኝና ሲያስተናግድ ነው - ገቢው ያድግለታል። የተሳፋሪ ጥቅም የሚጨምረው ደግሞ፣ በርካታ ተሳፋሪዎችን የሚያስተናግዱ ታክሲዎች ሲመጡ ነው - በትራንስፖርት እጦት ተገትሮ አይውልም። አንደኛው ወገን ጥቅም የሚያገኘው፣ ሌላኛውም ወገን የሚጠቀም ከሆነ ነው። መሰረታዊው የቢዝነስ ቁምነገርም ይሄው ነው - አምስት ሳንቲም የማጉደልና የማሳለፍ ሳይሆን። የስምሪት ቁጥጥሩም፣ ይህንን መሰረታዊ ቁምነገር በማደናቀፍ ነው ባለታክሲዎችንና ተሳፋሪዎችን ለጉዳት የዳረጋቸው። ጉዳቱ ግን፣ ዛሬ የምናየው ቅዠት ብቻ አይደለም። የባለታክሲዎች ገቢ ከጊዜ ወደ ጊዜ እየቀነሰ በመጣ ቁጥር፤ ወደ ቢዝነሱ የሚገቡ ሰዎችም ቁጥራቸው ይቀንሳል። በተቃራኒው፣ ከቢዝነሱ የሚወጡ ሰዎች ይበራከታሉ።

ለዚህም ነው፤ በአዲስ አበባ የታክሲ አገልግሎት የሚሰጡ መደበኛ ሚኒባስ ታክሲዎች ከጊዜ ወደ ጊዜ ቁጥራቸው እየቀነሰ የመጣው። ከጥቂት አመታት በፊት ቁጥራቸው 12ሺ ደርሶ እንደነበር መረጃዎች ቢገልፁም፣ አሁን ግን በስራ ላይ የሚገኙት 9ሺ አይሞሉም። አላስፈላጊ የመንግስት ቁጥጥር፣ ለጊዜው ካልሆነ በቀር፣ ውሎ አድሮ መዘዙ የከፋ እንደሚሆን ከዚህ ቀውስ መረዳት እንችላለን። የታክሲ ወረፋ ባልነበረበት ከተማ፣ በጥቂት ወራት ውስጥ… “የታክሲ ወረፋ” የኑሯችን አካል ሆኖ አረፈው። ተሳፋሪ ያጣ ታክሲ ተደርድሮ፣ ታክሲ ያጣ ተሳፋሪ ተሰልፎ የምናይበት የቅዠት ዓለም ውስጥ ገብተናል። ይህም አልበቃ ብሎ፣ ቅዠቱን የሚያጦዝ መግለጫ እንሰማለን። የአዲስ አበባ መስተዳድር የትራንስፖርት ቢሮ፣ ረቡዕ እለት በመንግስት ሚዲያዎች በኩል የሰጠውን መግለጫ አላዳመጣችሁም? በየጊዜው በምወስዳቸው እርምጃዎች መልካም ውጤቶችን እያስመዘገብኩ ነው ብሏል - የትራንስፖርት ቢሮው። ለምሳሌ ያህልም፤ የታክሲዎች ስምሪት ላይ ቁጥጥሩን ለማጥበቅ እርምጃ እንደወሰደ ቢሮው ሲገልፅ፤ አሁን አሁን ከተመደበበት መስመር ውጭ ውልፍት የሚል ታክሲ የለም ብሏል። ችግሩ ምን መሰላችሁ? አላስፈላጊው ቁጥጥር በተፈጥሮው መጥፎ ወይም ጎጂ ስለሆነ፣ ቁጥጥሩ በጥብቅ ተግባራዊ ሲደረግ ጎጂነቱ ይጨምራል እንጂ መልካም ውጤት ሊመዘገብ አይችልም። መልካም ውጤት የተመዘገበባትና ባለስልጣናት ብቻ የሚያውቋት ሌላ “አዲስ አበባ” ከሌለች በቀር፤ በነባሯ ከተማ ውስጥ የታክሲ ግርግርና ወረፋ ሲበራከት ነው የምንመለከተው።

የፌደራል ባለስልጣናት ደግሞ በበኩላቸው ሌላ ቁጥጥር ተግባራዊ ለማድረግ እንደተዘጋጁ ገልፀዋል። ከአንድ ከተማ ወደ ሌላ ከተማ በማታ የሚደረጉ ጉዞዎች እንደሚታገዱ ለኢቴቪ የተናገሩ ባለስልጣናት፤ የትራፊክ አደጋዎችን ለመቀነስ የታሰበ እርምጃ ነው ብለዋል። ከከተማ ውጭ፣ በማታ በሚከናወን ጉዞ ላይ የትራፊክ አደጋ ይደርሳል ወይ? አዎ ይደርሳል። ነገር ግን፣ የከተማ ውስጥ እና የቀን ጉዞ ላይም የትራፊክ አደጋ ይደርሳል። ታዲያ፣ የትራፊክ አደጋ ለመከላከል አስበን፤ በከተማ ውስጥና ከከተማ ውጭ፤ በቀን እና በማታ የሚከናወኑ የመኪና ጉዞዎችን ለምን አናግድም? ለነገሩማ፤ አይነቱና መጠኑ ይለያያል እንጂ፤ በተፈጥሮው “አደጋ” የማያሰጋው አንዳችም የሰው እንቅስቃሴ የለም። ፎቅ መስራት፣ ጉድጓድ መቆፈር፣ መንገድ መጥረግ፣ መሬት ማረስ፣ ቤት ማፅዳት… ሁሉም አይነት ስራ፣ ቢሮ ውስጥ ተቀምጦ መስራት ሳይቀር፣ ተገቢው ጥንቃቄ ካልተደረገበት አደጋ ይደርሳል።

ለምሳሌ፣ ከፍተኛ አደጋ ከሚያጋጥማቸው ነገሮች መካከል፣ እርግዝናና ወሊድ ሊጠቀሱ ይችላሉ። ምን ይሄ ብቻ? እንደአረማመዱና እንደአሯሯጡ፣ እንደአጎራረሱና እንደአጠጣጡ፣ እንደአስተኛኘቱና እንደአለባበሱ ሁኔታ ለአደጋ የሚጋለጥ ሰው ጥቂት አይደለም። እና፣ አደጋዎችን ለማስቀረት አርፎ መቀመጥና ሞቱን መጠባበቅ አለበት? በጭራሽ! ሰው፣ የስራውንና የእንቅስቃሴውን ምንነት ለማገናዘብ፣ በጥረቱ የሚያገኛቸው ጥቅሞችንና ሊያጋጥሙ የሚችሉ አደጋዎችን ለማመዛዘን የሚያስችል አቅም አለው - የአእምሮ አቅም። ጥቅሞቹን የሚያሳድጉ ዘዴዎችና አደጋዎችን የሚያስቀሩ ጥንቃቄዎች የሚፈጠሩትም፣ በሰዎች የአእምሮ አቅም ነው። ያለ ድካም በፍጥነት ከቦታ ቦታ መጓዝ እጅጉን ጠቃሚ እንደሆነ ትጠራጠራላችሁ? መኪና የተፈጠረውና የሚመረተው፣ አስፋልት የሚቀየሰውና የሚገነባው፣ ለሌላ ምክንያት አይደለም - ያለ ድካም በፍጥነት ለመጓዝ ነው። በእርግጥ አደጋዎች ያጋጥማሉ።

ግን ከጥቅሙ ጋር ሲነፃፀር፣ አደጋው በጣም ትንሽ ነው። መኪናና አስፋልት ባልነበረበት ዘመን፣ የሰዎች አማካይ የሕይወት ዘመን 30 አመት ገደማ ብቻ ነበር። አስፋልት ላይ ፈጣን የመኪና ጉዞ፤ የሰዎችን ሕይወት አሻሽሏል። ነገር ግን፤ ከጥቅሙ ጋር ሲነፃፀር አደጋው ትንሽ ነው በሚል፤ አደጋውን ቸል ማለት አለብን ማለት አይደለም። “አደጋ አለው” በሚል ሰበብ እርግዝናንና ወሊድን ለማስቀረት ማሰብ እብደት ቢሆንም፤ አደጋውን ለመቀነስና ለማስቀረት የሚያስችሉ ጥንቃቄዎችን ከመተግበር መቦዘንም “እብደት” ይሆናል። የመኪና ጉዞም ተመሳሳይ ነው። የትራፊክ አደጋ ተፈርቶ፤ የመኪና ጉዞን ማስቀረት የጤንነት አይደለም። አደጋውን በ“ፀጋ” መቀበልም እንዲሁ። ለዚህም ነው፤ የትራፊክ ደንቦችና ምልክቶች፤ የትራፊክ መብራቶችና የማሽከርከር ስልጠናዎች የተፈጠሩት። ይህም ብቻ አይደለም። አማራጮችን አመዛዝኖ፣ የመጓጓዣ አይነቱን፣ አቅጣጫውንና ጊዜውን መምረጥ ያስፈልጋል።

ለምሳሌ፤ ዋጋውንና አቅርቦቱን፣ የመጓጓዣውንና የአሽከርካሪውን ብቃት ማነፃፀር አስፈላጊ የመሆኑን ያህል፤ በጥቅሉና በአመዛኙ ሲታይ፤ በብስክሌትና በሞተር ብስክሌት ከመጓዝ ይልቅ በመኪና መጓዝ የተሻለ መሆኑንም ማገናዘብ ይቻላል። በማታ ከመጓዝ ይልቅ በቀን፤ በመኪና ከመጓዝ ደግሞ በባቡር፤ በባቡር ከመጓዝ ደግሞ በአውሮፕላን ይሻላል። ለምን በጥቅሉ አማካይ የአደጋ መጠናቸው አነስተኛ ስለሆነ። እንዲህም ሆኖ፤ የአውሮፕላን ጉዞ የተሻለ ስለሆነ የመኪና ጉዞን ለማገድ፣ ወይም የመኪና ጉዞ ስለሚሻል የሞተር ብስክሌትን መከልከል፤ አልያም የቀን ጉዞ ስለሚሻል የማታ ጉዞን መከልከል… ከእብደት አይለይም። መከልከልና ማገድ ይቅርና፤ “ብስክሌት አትጠቀሙ፣ በማታ አትንቀሳቀሱ” ብሎ መምከርም ስህተት ነው።

ጥቅሙንና ጉዳቱን፣ ሰዓቱንና አቅጣጫውን፣ መጓጓዣውንና አሽከርካሪውን እያመዛዘናችሁ ተጠቀሙ ነው መባል ያለበት። “አትጠቀሙ፣ አትንቀሳቀሱ” ከሚለው የተሳሳተ ምክር አልፎ፤ ወደ ክልከላና እገዳ መግባት፤ ከመሳሳት አልፎ የሰውን ነፃነት መርገጥ ይሆናል። አለበለዚያማ፤ “የመንቀሳቀስ ነፃነት” ተብሎ በህገመንግስት የሰፈረው ፅሁፍ ምን ትርጉም አለው? ባለስልጣናት በፈቀዱት ሰዓት ብቻ ነው መንቀሳቀስ የሚቻለው? በደርግ ዘመን የ”ይለፍ” ወረቀት ያልያዘ ሰው ከከተማ ከተማ መንቀሳቀስ አይችልም ነበር። ከድሮው የደርግ ዘመን የሰዓት እላፊ አዋጅ፤ በከፊል ተቀንጭቦ ተግባራዊ ሊደረግ ነው ቢባል አይሻልም?