Administrator

Administrator

 ደራሲ፡-ተሾመ ብርሃኑ ከማል
                                      የታተመው፡-2009
                                      አሳታሚው፡- በግል
                                      የገጹ ብዛት፡- 200     

       የኢትዮጵያና የኤርትራ ጉዳይ  እጅግ ወቅታዊ  አጀንዳ ነው፡፡ ሊተዉ ከማይችሉ  (unavoidable) ርዕሰ ጉዳዮች አንዱና ዋነኛውም ይመስለኛል፡፡ ይህ ጉዳይ የታሪክ፣ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚ፣ የማህበራዊ፣ ---ወዘተ ብቻ ሳይሆን የሰው ልጅ ሂደት ማሳያም ጭምር ነው፡፡ ከዚህ አንጻር ነው በቅርቡ የታተመውን፣ የተሾመ ብርሃኑ ከማል፣ “የሰላም ፍኖት ለኤርትራና ለኢትዮጵያ ህዝቦች አንድነት” የተሰኘ መጽሐፍ፣  ልዳስሰው የተነሳሳሁት፡፡
የኢትዮጵያንና የኤርትራን ሕዝቦች ወቅታዊ ግንኙነት ከግምት በማስገባትም ይመስላል፣ የመንግሥትም ሆነ የሌሎች ፖለቲካ ድርጅቶች ወይም ግለሰቦች ተጽእኖ እንደሌለበት፣ ፕሮፓጋንዳም ሆነ ወገንተኛም አለመሆኑን ስጋት በተመላበት ሁኔታ ይገልጻል፡፡ ይህም ሆኖ፣  የኢትዮጵያና የኤርትራ ሕዝቦች በፖለቲካዊ ድንበር ቢለያዩም በማህበራዊ ኑሮ፣ በቋንቋ፣ በባህል፣ በስነ ልቦና፣ በታሪክ፣… ከጥንት እስከ ዛሬ አንድ መሆናቸውን በማውሳት፣ ወደ ቀዳማዊ አንድነታቸው ተመልሰው ጥንታዊ ታሪካቸውን እንዲያድሱ፣ የሕዳሴ እንቅስቃሴያቸውንም በሕዝቦች የታሪክ እርቅ ላይ እንዲመሠርቱ፣ የታሪክ እርቅን  መሥርተው የሚወስዱት መንገዶች ለሽምግልና የተሻሉ፣ ሰላማዊና ፍትሐዊ መሆናቸውን አውቀው በጋራ እንዲንቀሳቀሱ፣ ሰዎች “እኔ ማን ነኝ?” ብለው በመጠየቅ፣ ማንነታቸውን እራሳቸው እንዲመልሱ … ሐሳብ ለመሰንዘር ይሞክራል እንጂ በኃይል አንድ ይሁኑ ለማለት አይዳዳውም፡፡›› በማለት ከገጽ 7-8 ይገልጽና፣ ‹‹የተወሰኑ የገንጣይ ቡድኖችና ደጋፊዎቻቸው ሴራ ነው›› በሚል እምነት እንዳልተጻፈ፣ ሆኖም አንድ የነበሩ፣ በሥጋ ዝምድና፣ በጋብቻ፣ በማህበራዊና በኢኮኖሚ የተሳሰሩ ሕዝቦች፣ በታሪክ አጋጣሚ ተለያይተዋልና በሰላም ፍኖት እየተጓዙ፣ በመጀመሪያ የኢትዮጵያና የኤርትራ ሕዝቦች ወንድማማችነት ላይ የተመሠረተ ግንኙነት እንዲመሠርቱ፣ ደረጃ በደረጃ፣ ቀስ በቀስ፣ ስልትና ሐቅን በተከተለ መንገድ ከሁሉ አስቀድሞ የተለያዩ ግለሰቦች፣ ቤተሰቦች፣ ማህበረሰቦች፣ ህብረተሰቦች ብሎም ሕዝቦች በመንገድ፣ በስልክ፣ በደብዳቤና በመሳሰሉት እንዲገናኙ፣ ቀስ በቀስም በአንድ ላይ እንዲሆኑ፣ አንድ ሆነውም የተሻለ የጋራ ልማትና ብልጽግና በምሥራቅ አፍሪቃ እንዲያመጡ፣ ቢቻልም በረጅም ጊዜ ሂደት በኢኮኖሚ፣ በማህበራዊ ኑሮና በፖለቲካ እንዲዋሃዱ፣ ከተዋሃዱም በአፍሪቃ ቀንድ ስመ ገናና ሊሆኑ እንደሚችሉ ገለልተኛ በሆነ የሽምግልና ዓይን ለመጠቆም መሆኑን ያወሳል፡፡   
መጽሐፉ አዳዲስ መረጃዎችን አካትቷል። ከእነዚህም መካከል፡- የኢጣሊያውያን ወደ ኢትዮጵያ መምጣትና ኢጣሊያ በእንግሊዝ ድጋፍ ምጽዋን መያዝ፣ አሰብ በኢጣሊያ ቁጥጥር ስር ስለመሆን፣ የጁሰፔ ሳፔቶ፣ የኢጣሊያ ቅኝ ግዛት ፍለጋና የስለላ ሥራ፣ በሐሰን ቢን አሕመድ፣ በኢብራሂም ቢን አሕመድና በጁሰፔ ሳፔቶ መካከል የተፈረመ ስምምነት፣ በኢጣሊያ መንግሥትና በዓፋር ሱልጣኖች መካከል የተደረጉ ስምምነቶች፣ የኢጣሊያ መንግሥት ንጉሣዊ አዋጅ፣ በጣልያን ንጉሣዊ መንግሥትና በሮባቲኖ ድርጅት መካከል ስለ አሰብ ባለቤትነት ጉዳይ የተደረገ ስምምነት፣ በሱልጣን መሐመድ ሐምፈሬ፣ በንጉሥ ምኒልክና በኢጣሊያ ንጉስ እንደራሴ የተፈረመ ውልና ሌሎችም  ይገኙበታል፡፡
በመጽሐፉ ውስጥ በርካታ አስገራሚ ታሪኮች አሉ፡፡ ለምሳሌ ጁሰፔ ሳፔቶ፣ ከ1811-1895 (እኤአ) የኖረ ኢጣሊያዊ የላዛሪት ሚሽን ተከታይ ሲሆን ይህም የላዛሪት ሚሽን የተባለ ድርጅት፣ ድሆችን በመርዳት ስም ፓሪስ  በ1625 (እኤአ) ውስጥ ሴንት ቪንቸንት ፖል በተባለ የሃይማኖት አባት የተቋቋመ ነበር፡፡ ጁሰፔ ሳፔቶ የላዛሪት ሚሽን ተከታይ የሆነው በ18 ዓመቱ ሲሆን ወደ ምጽዋ ከመምጣቱ በፊትም (በ1837) ወደ ሊባኖስና ግብጽ ሄዶ እንደነበር የሕይወት ታሪኩን የጻፉ ሰዎች ይጠቁማሉ፡፡ ይሁንና ድርጅቱ ለድሆች እርዳታ ለመስጠት የተቋቋመ ይባል እንጅ ያቋቋመው የፖለቲካ ድርጅት እንደነበር ይነገራል፡፡ የታሪኩ ጸሐፊዎች እንደሚገልጹት፤ ወደዚህ ስፍራ የመጣው ከሁለት ፈረንሳውያን ወንድማማቾች ጋር ሲሆን ከእነርሱ ጋር ከ1837 እስከ 1847 ባለው ጊዜ ወደ መሃል ኢትዮጵያ በመግባት በአድዋና በጎንደር ጉብኝት አድርጓል፡፡   
ጁሰፔ ሳፔቶ፤ ፍራነቺሰ ጆቫኒ ከተባለ ሌላ ሚሽነሪ ጋር ኦገስት 23 ቀን 1851፣ በምጽዋ በኩል ወደ ከረን መጣ፡፡ በነዚህ ጸሐፊዎች መረጃ መሠረት፣ የላዛሪት ሚሽን ተልእኮውን ለመፈጸም የመጣው በመጀመሪያው የኢትዮጵያ ጉዞው በጸና ታሞ ወዳገሩ ከተመለሰ በኋላ ነው፡፡ በሁለተኛ ጊዜ ጉብኝቱም እንደ ሚሽነሪ ሳይሆን እንደ ጎብኝ ወደ ምጽዋ በመምጣት፣ ደናኪል (የዓፋር) ጨዋማ ስፍራዎችን፣ ቦጎስንና ሓባብን በ1851 ጎበኘ፡፡ በዚህም ጊዜ ግዕዝ፣ ትግረና ቢለን ቋንቋዎችን በማጥናት መዝገበ ቃላት አዘጋጀ፡፡ ከዚያም ወደ አሰብ መጣ፡፡ በ1858 አጼ ቴዎድሮስ በመንግሥታቸው ላይ ያመጸው አገው ንጉሥን ድል አድርገው፣ በገደሉበት ጊዜ፣ ጁሰፔ ሳፔቶን እስረኛ አድርገው፣ እንደ አስተርጓሚ ይጠቀሙበት ነበር፡፡ ሆኖም አጼ ቴዎድሮስ ከጊዜ በኋላ ነጻ አድርገው ስለለቀቁት ወደ ፓሪስ ተመለሰና በፓሪስ የቤተ መዘክር ሠራተኛ ሆነ፡፡ ስዊዝ ካናል በ1869 ሲከፈትም የኢጣሊያ መንግሥት በቀይ ባህር ዳርቻ እንደ ወደብ የሚጠቀሙበትን ቦታ እንዲያስገኝ አደራ ተሰጠው፡፡ ወደ አሰብ ከመጣ በኋላም የተሰጠውን አደራ ሳያሳውቅ፣ ከዓፋር ሱልጣኖች ጋር ወዳጅ መስሎ በመቅረብ፣ ከአሰብ የተወሰነውን መሬት፣ አፋር ግዛት በሚኖርበት ጊዜ ሊጠቀምበት በውል እንደገዛ፣ ከዚህ ቀደም ባልቀረበ መልኩ በመጽሐፉ ውስጥ ሰፍሮ ይገኛል፡፡
ሲኞር ጁሴፔ ሳፔቶ ኃላፊነቱን ከተወጣ በኋላ ወደ ኢጣሊያ ተመለሰ፡፡ በዚህም ጊዜ ከሚያውቁት ሰዎች ጋር እምብዛም አይገናኝም ነበር፡፡ ሲኞር ጁሴፔ ሳፔቶ ወደ ኢጣሊያ ከተመለሰ በኋላ በአራተኛው ዓለም አቀፍ ኦሪየንታሊስቶች ጉባኤ ላይ፣ በ1878 ተካፋይ ነበር፡፡ በዚህ ጊዜም የተለያዩ ኢትዮጵያን የሚመለከቱ ጥናታዊ ጽሑፎችን አቅርቧል፡፡
ከጁሴፔ ሳፔቶ በፊት የምናገኘው የሃይማኖት ሰው ጉልየሞ ማሳይ፣ በተለምዶ አባ ማስያስ (እ.ኤ.አ 1809-1889) የምንለው ቄስ ሲሆን ይህም ሰው ኢጣሊያ ቦቫ በምትባል ስፍራ የተወለደ ነው። በአገራዊ አባባል፣ አባ ማስያስ የተባለው የካቶሊክ እምነት ተከታይ በኢትዮጵያ በተለይም በደቡብና በደቡብ ምዕራብ ውስጥ ለ25 ዓመታት ኖሯል፡፡
አባ ማስያስ ወደ ኢትዮጵያ የተላከው በጉግሊየሞ ስም ሲሆን ጁሴፔ ከተባለ ሌላ ፈረንሳዊ ጋር በመሆን ወደ ሮም ሄዶ ስለ ኢትዮጵያ ሁኔታ ሪፖርት ካቀረበ በኋላ በ1846 ኦሮሞዎችን ክርስቲያን ለማድረግ በሚል ሰበብ ‹‹የኦሮሞ ቄስ›› ተብሎ እንደገና መጣ፡፡ ድሮውንም አባ ማስያስ እየተባለ የነበረው ኢጣሊያዊ አቡነ ባርቶኔሊ በሚል ስም ወደ ጎጃም ተልኮ እንደነበር እርሱን በሚመለከት የተጻፉ ድርሳናት ያመለክታሉ፡፡ በ1849 ደግሞ ብጹእ ወቅዱስ አቡነ ሞንሲኞር ተባለ፡፡ ይህ ሰው  በ1879  ወደ ሀገሩ የተመለሰ ሲሆን በ1880 በፈረንሳይ በተካሄደው ጉባኤ ላይ በመገኘት ለኦሮሞዎች ተጨማሪ ሚሺነሪዎች እንደሚያስፈልጋቸው አበክሮ የገለጸ ሲሆን በ1884 የካርዲናንነት ሲመት በሮማ ካቶሊክ ቤተክርስቲያን ርእስ ሊቃነ ጳጳሳት በአቡነ ሊዮ 33ኛ (1878-1903). ተሰጠው፡፡ በሀገሩም ውስጥ ሕይወቱ አለፈ፡፡ ይሁንና እርሱ ከሞተ ከ75 ዓመታት በኋላ የኢጣሊያ ፋሽስት የአባ ማስያስ በኢትዮጵያ ውስጥ መኖር ለኢጣሊያ ቅኝ ግዛት መመቻቸት ቅድመ ሁኔታ እንደነበር አስታውቋል፡፡ ነገር ግን አባ ማስያስ ፖለቲካዊ ሚና ይኑረው አይኑረው ያሳየው ፍንጭ አልነበረም።  ዳግማዊ አጼ ምኒልክም የዚህ ሰው ጥሩ ወዳጅ እንደነበሩ የሚታወቅ ሲሆን በአማርኛና በኦሮምኛ ያዘጋጀውን የሰዋስው መጽሐፍ አሳትመውለታል፡፡ አባ ማስያስ ከዚህም በተጨማሪ “በኢትዮጵያ ደጋማ ስፍራዎች በሚሽን የቆየሁባቸው 35 ዓመታት” በሚል ርእስ መጽሐፍ ያዘጋጀ ሲሆን ይህም ስለ ኢትዮጵያውያን ማንነት የሚያወሳ መጽሐፍ በ1936 መታተሙ ይታወቃል፡፡ መጽሐፉ ጠቃሚ ሆኖ በመገኘቱም ወደ እንግሊዝኛ፣ ፈረንሳይኛና ጀርመንኛ ተተርጉሟል፡፡
እነ አባ ጁሴፔ ሳፔቶና እነ አባ ማስያስ በአንድ በኩል ሃይማኖት በሌላ በኩል ደግሞ የፖለቲካ አማካሪ፣ በዋነኛነት ስለ ኢትዮጵያ ሁኔታ ለመንግሥታቸው መረጃ አስተላላፊ ሆነው ሲሰሩ ከቆዩ በኋላ ተልእኳቸውን ሲፈጽሙም ወደ ሀገራቸው እየተጠሩ ሹመት የተቀበሉ ሲሆን  የኢጣሊያ መንግሥት ደግሞ ያገኘውን መረጃ በመጠቀም፣ ቅኝ ግዛት የማስፋፋት ዓላማውን ለማስፈጸም ተጠቅሞበታል፡፡
ስለ ዓድዋ ጦርነት በሚያወሳው ምዕራፍ እንደተጠቀሰው ሁሉ ኢጣሊያ ኢትዮጵያን መውረር የጀመረችው በእነ ጋርባልዲና ማዚኒ ተበታትና የነበረችው ኢጣሊያ፣ በ1861 በተዋሃደች በ17 ዓመታት ውስጥ ነው፡፡ ያኔ ኢጣሊያ ከተዋሃደች በኋላ ብዙዎች ታላቋን ኢጣሊያ የመመስረት ሕልም ነበራቸው፡፡ በወቅቱ የኢጣሊያ ጠቅላይ ሚኒስትር የነበረው ፍራንሲስኮ ክሪስፒ፤ ኢጣሊያን ትልቅ ማድረግ የሚቻለው በአፍሪካ ውስጥ ቅኝ ግዛት ለማስፋፋት የተቻለ እንደሆነ ነው ብሎ ያምን ነበር። ስለሆነም ቀደም ሲል በተጠቀሰው ውል መሠረት ጁሰፔ ሳፔቶ፣ የአሰብ የተወሰነ ክፍል በ1869 ሲገዛ፣ ዓላማው ለራፌኤሎ ሩባቲኖ ኩባንያ የመርከብ ከሰል መሙያ የነበረ ሲሆን የኢጣሊያ መንግሥት ግን በውሉ ውስጥ የነበሩትን ቀዳዳዎች ተጠቅሞ፣ የቅኝ ገዥነት እግሩን የሚተክልበት ቦታ አደረገው፡፡
ከውህደት ወዲህ የመጀመሪያ ንጉሥ የነበረው ዳግማዊ ቪቶሪዮ ኢማኑኤልም “ኢጣሊያ መከበር ብቻ ሳይሆን መፈራት አለባት” የሚል አቋም ነበረው፡፡ የስዊዝ ካናል በ1869 መከፈት ለኢጣሊያ የንግድ እንቅስቃሴ ከፍተኛ አስተዋጽኦ በማበርከቱ፣ መርከቦቿ የድንጋይ ከሰል ነዳጅ የሚሞሉበትና ዕቃዋን በቅብብሎሽ ወደ ሌሎች አገሮች የምታሻግርበትን ወደብ ትፈልግ ነበር፡፡ በዚህም መሠረት ‹‹ሊጉሬ›› የተባለው የንግድ መርከብ ማህበር (Associazione Marittima Mercantile Ligure) ‹‹ቀይ ባህርን በማቋረጥ እስከ እሩቅ ምሥራቅ አገሮች መጓዝ የሚቻለው በእንፋሎት በሚሄድ መርከብ መሆኑንና እንፋሎት ለመፍጠር የሚያስችለው ድንጋይ ከሰል የሚራገፍበት ወደብ በአፍሪካ ቀንድ ማግኘት እንደሚገባ  ለመንግሥት ሪፖርት ካቀረበ በኋላ፣ ሐሳቡ ተቀባይነትን በማግኘቱ፣ የመንግሥት ባለስልጣናት በጉዳዩ መምከር ጀመሩ፡፡ በአፍሪካ ቀንድ ካሉት ስፍራዎች ያለ ችግር የሚያዙትና ለወደብነት የሚያመቸው የትኛው እንደሆነ ለማወቅ ከዚህ ቀደም ለመልክዓ ምድር ጥናት የላኳቸው ባለሙያዎች ያቀረቡትን መረጃ መመልከት ጀመሩ፡፡ ራፋኤሎ ሩባቲኖ፣ ያኔ ግንባር ቀደሙ የንግድ መርከቦች ኩባንያ ባለቤት ከመንግሥት ጋር መልካም ግንኙነት የነበረው ሲሆን መንግሥትም አዳዲስ የንግድ መስመሮችን በሜዲትራንያንና በቀይ ባህር አካባቢ ባሉ የአፍሪካ አገሮች የባህር ድንበር ላይ እንዲዘረጋ አደራ ጥሎበት ነበር፡፡  ‹‹ውሻ በቀደደው ጅብ ይገባል›› እንዲሉም ሲኞር ጁሰፔ ሳፔቶ ሆን ብሎ በውሉ ውስጥ እርሱ ለመኖሪያነት በገዛው መሬት ላይ ሌሎች የእርሱ ሰዎች መጥተው ቢኖሩ ምንም ዓይነት ተንኮል በአፋሮች ዘንድ እንደማይደርስባቸው ቅዱስ ቁርዓን አስይዞ አስምሏቸው ስለነበር በእርሱ እግር የሩባቲኖ ኩባንያ፣ በሩባቲኖ ኩባንያ እግር፣ የኢጣሊያ ቅኝ ገዥዎች እስከ መጨረሻው እያታለሉና እየሸፈጡ ቦታ ያዙ፡፡ ከፊል አሰብ ለሩባቲኖ ኩባንያ በ1870 ዓ.ም መሸጧን ተከትሎም ዘመናዊ ወደብ ተደርጋ ተሠራች፡፡ ከዘጠኝ ዓመታት በኋላም ኩባንያው ከአሰብ እስከ መሃል ሐበሻ የነበረውን ንግድ ሰላማዊ በሆነ መንገድ ለማካሄድ የጦር መርከቦች እንደሚያስፈልጉት ገለጸ፡፡
ጠቅላይ ሚኒስትር ካሮሊም የኢጣሊያ መንግሥት ምክር ቤት የተቀደሰ ሐሳቡን የደገፈው መሆኑን ገልጾ፤ ‹‹ቅኝ ግዛታችንን ለመጠበቅ ሁለት የጦር መርከቦች ልኬልሃለሁ›› የሚል መልእክት አስተላለፈለት፡፡  ክርሲፒ በሁለተኛው ደብዳቤው፣ በአሰብ የንግድ ማዕከል መቋቋሙ የሀገሪቱን የኢኮኖሚ እንቅስቃሴ በማሳደግ በኩል ጠቀሜታ እንደሚኖረው ጠቁሞ፣ በንግዱ ዘርፍ ብቻ ሳይሆን የኢጣሊያን የባህር ኃይል ለማደራጀትም አስተዋጽኦ እንደሚኖረው ገለጸለት፡፡ ከዚህ ደብዳቤ በግልጽ እንደምንረዳውም፣ ምንም እንኳን ጁሰፔ ሳፔቶ ለመኖሪያነት ገዝቶ ለነዳጅ መሙሊያነት ለራፋኤሎ ሩባቲኒ ቢያስተላልፈውም አሰብ ወደ ኢጣሊያ ቅኝ ግዛትነት የመቀየር ፍላጎት የነበራት መሆኑን ነው፡፡
በዚህም መሰረት፣ በአዋጅ ቁጥር 857፣ በአሰብ የጣልያንን ቅኝ ግዛት በተመለከተ በ5/6/1882 ዓ.ም በወጣ አዋጅ ነጋሪት ጋዜጣ ቁጥር (160/10/7/1882 ዓ.ም) ‹‹ቀዳማዊ ኡምቤርቶ የጣልያን ንጉሥ፣ የሕዝብ እና የዘውድ ምክር ቤቶች የተስማሙበትን በማጽደቅ ከዚህ ቀጥሎ የቀረበውን አወጀች፡፡ በዚህም አዋጅ፣ ከቀይ ባሕር በስተደቡብ ምዕራብ ጠረፍ የምትገኘዋ የአሰብ ክልል፣ የጣልያን ቅኝ ግዛት ሆኖ በጣልያን መንግሥት ሥር እንድትተዳደር ተደርጓል፡፡ ክልሉም ከራስ ደርሚክ እስከ ራእስ ሎማ ድረስ ያለው ስፋቱ ስድስት ማይልስ፣ ከራስ ሎማ እስከ ራስ ደውራን ድረስ ያለው ስፋቱ ሁለት ማይልስ የሆነ፣ ከሼክ ደውራን አስኮ ራእስ ሣንቶራ ድረስ ያለው ስፋቱ አራት ማይልስ የሆነ፣ ከራስ ሎማ ፊት ለፊት የሚገኘው የሠንዓቡር ደሴት፣ ከጠረፍ ፊት ለፊት የሚገኙ ደሴቶች- ከራስ ሉማ እና ከራእስ ሣንቱር ፊት ለፊት ያሉትን ያጠቃልላል፡፡ በጣልያን መንግሥትና በሩባቲኖ ድርጅት መካከል በማርች 10/1882 ተደርጎ የነበረው ስምምነት ስለጸደቀ፣ በስምምነቱም መሠረት፣ የድርጅቱ ንብረት ወደ ጣልያን መንግሥት ተሸጋግሯል፡፡›› ንጉሥ ኡምፔርቶ፣ ጁላይ 5 ቀን 1882 ሮማ፡፡
ከዚህም አዋጅ በኋላ በምድረ ኤርትራ ስለተሾሙት የኢጣሊያ ባለስልጣኖች ስም ዝርዝር በመጽሐፉ ውስጥ እናገኛለን፡፡ ‹‹የፈሩት ይደርሳል የጠሉት ይወርሳል›› እንዲሉ፣ የኢጣሊያ መንግሥት በ1882 ላይ አሰብ ቅኝ ግዛቱ መሆኗን አስታወቀ። ከሁለት ዓመታት በኋላም የውጭ ጉዳይ ሚንስትሯ ሲኞር ማቺኒ፣ የሸዋው ንጉሥ ምኒልክ፣ አሰብ ወደብን ከአውሮፓ ገበያ ጋር በቀጥታ የሚያገናኛቸው ማዕከል አድርገው ያለ አንዳች ችግር እንዲጠቀሙበት ጋበዘ፡፡ በእርግጥም አሰብ ለማደግ ከኢትዮጵያ ወደ ውጭ የሚሄድና ከውጭ ወደ ኢትዮጵያ የሚገባ ንግድ ያስፈልጋት ነበር፡፡
በመጽሐፉ ውስጥ መሠረታዊው ዓላማው የሽምግልና ጉዳይ በመሆኑ፣ ከሁሉ አስቀድሞ ኤርትራውያን ስለ ራሳቸው ምን እንደሚሉ ማወቅ እንደሚገባ ይገልጻል፡፡ በዚህም መሠረት ኤርትራውያን እንደሚሉት፤ ‹‹ኤርትራ ከሰሜን ሱማሊያ፣ ከጅቡቲና ከቀይ ባሕር ድንበር የሆነው የሱዳን ግዛት ጋር በመደመር የፑንት ግዛት ተብላ ጥንት በጥንት ግብጻውያን ዘንድ ትታወቅ ነበር። ትርጉሙም ምድረ እግዚአብሔር ማለት ነው። ስለዚችም አገር በታሪክ ምዕራፍ የሚጠራው ከክርስቶስ ልደት በፊት ከ25ኛው ክፍለ ዘመን ጀምሮ ነው፡፡ ጥንታዊ የፑንት ግዛት ነዋሪዎች፣ ከጥንታዊዋ የፈርኦን ስርወ መንግሥት ጋር ግንኙነት የነበራት ሲሆን በተለይም በንጉሥ ሳሁርና በንግሥት ሐትኮፐስት ዘመን ግንኙነቷ ጠንካራ ነበር፡፡ ያኔም በተለይም ከስምንተኛውና ሰባተኛው ክፍለ ዘመን (ቅድመ ልደት) ደዓማት የሚባል መንግሥት በኤርትራና በኢትዮጵያ ነበር። ዋና ከተማውም ይሃ ተብሎ በሚጠራው ስፍራ ሲሆን በዚህም ጊዜ የነበረው መንግሥት በመሥኖ  እርሻ ያለማ፣ የብረታ ብረት ቁሳቁሶችንና የጦር መሣሪያዎችን ይሠራ ነበር፡፡ የደዓማት ሥርወ መንግሥት ከ5ኛው ክፍለ ዘመን (ቅድመ ልደት) ከወደቀ በኋላ የአክሱም ስርወ መንግሥት በ1ኛው ክፍለ ዘመን ተመሥርቶ እስኪያስተባብራቸው ድረስ አነስተኛ ነገሥታት በተበታተነ መልክ አካባቢያቸውን (የጥንቷን ኤርትራንና ኢትዮጵያን) ያስተዳድሩ ነበር፡፡ በኢጣሊያ ጊዜም ሆነ ከዚያ በፊትና በኋላ አፋሮች በኤርትራ መሬት ምንም አያገባቸውም፡፡ ባሕረ ነጋሽ፣ ትግራይ ትግረኝ የሚባለው ማዕረግና ብሔረሰብ ያልነበረ ዝም ብለው ሰዎች የፈጠሩት ነው፡፡ ስለዚህ ኤርትራን ባህረ ነጋሾች አላስተዳደሯትም፡፡››  
---በ1920ዎቹ መጀመሪያ ላይ ላይ የኢጣሊያውንና የሌሎችን ነጮች የበላይነት፣ የኤርትራውያንና የሌሎች ጥቁሮችን የበታችነት በግልጽ የሚደነግግ አዋጅ አወጀ፡፡ ይህም በአንድ አገር ውስጥ ሁለት ሕግ እንዲኖር አስቻለ፡፡ በዚህ አዋጅ መሠረትም፣ ነጮችና ጥቁሮች በአንድ ሆቴል ውስጥ ተቀምጠው መመገብ አቆሙ፡፡ ጥቁሮችና ነጮች የተለየ የትራንስፖርት አገልግሎት መጠቀም ጀመሩ፡፡ ነጮች እንዲቀመጡባቸው በተከለሉት መንደሮች ጥቁር ኤርትራውያኖቹ እንዳይኖሩ ተከለከሉ፡፡ ጥቁሮቹ ኤርትራውያንና በኤርትራ ውስጥ የሚኖሩ ሌሎች ጥቁሮች ከነጮች ጋር በሕግ ፊት እኩል የመሆናቸው ነገር አበቃ፡፡ ነጮችና ጥቁሮች ለየብቻ መዳኘት ጀመሩ፡፡ ጥቁሮች በነጮች በደል ቢደርስባቸው እንደ በደል መታየት አቆመ፡፡ በወቅቱ የነበሩ ብዙዎቹ ኤርትራውያን ትምህርቸው ከአንደኛ ደረጃ ከፍ እንዳይል ተደረገ፡፡ ይህም ትምህርት በአመዛኙ ከኢጣሊያውያን ገዥዎቻቸው ጋር በቋንቋ ለመግባባትና ለመታዘዝ እንዲችሉ እንጅ ዕውቀት እንዲያገኙ የሚያስችል አልነበረም፡፡ ይህም ኤርትራውያንና በኤርትራ የሚኖሩ ጥቁሮች የበለጠ በጭቆና እንዲገዙ አደረጋቸው፡፡ የፋሽስታዊ አገዛዙ ስልትም በጦር ቃል ኪዳን አገሮች ጫና በደረሰበት ቁጥር እየጨመረ ሄደ እንጅ አልቀነሰም፡፡
ይህም ሆኖ ደግሞ በኤርትራውያኑ መካከል የነበረው የመደብ፣ የዘር፣ የጎሳ፣ የቋንቋ፣ የጾታ፣ የዕድሜ፣ የእምነት ልዩነት እንዲሰፋና እርስ በእርሳቸው እንዲናናቁ የሚያስችል ስልት ቀየሰ። በተለይም ከአገዛዙ ጋር አንስማማም ብለው ወደ ኢትዮጵያ በመግባት የከዱት መሬት የደመኛ መሬት እየተባለ ይወሰድ ጀመር፡፡ ከበስተጀርባቸው ኢትዮጵያና ኢትዮጵያውያን እንዳሉ የሚያውቁት የነቁ ኤርትራውያን፣ ኢጣሊያን እየከዱ ወደ ኢትዮጵያ መምጣትና መውጋት ጀመሩ፡፡ ኢትዮጵያን ጠቅልላ ካልያዘች እረፍት እንደማይኖራት የተገነዘበችው ኢጣሊያም በ1928 ላይ ሠራዊቷን ወደ ኢትዮጵያ አዘመተች፡፡  በ1933 በእንግሊዝ እስክትሸነፍ ድረስም ቆየች፡፡ ከዚያም በመጽሐፉ ውስጥ በሚተነተነው ሰፊ ምክንያት ከኢትዮጵያ ጋር ተዋሃደች፡፡
በመሠረቱ፣ በኤርትራውያንና በኢትዮጵያውያኑ ትግሬዎች መካከል የብሔር፣ የቋንቋ፣ የሃይማኖት አንድነት ቢኖርም ኢጣሊያ በገነባችው የጥላቻና የንቀት አመለካከት ሳቢያ ትግሬዎችንና አማሮችን አጥብቀው ይንቁ፣ ያንቋሽሹ ነበር፡፡ በተለይም፣ በኤርትራውያንና በሰሜን ትግራይ ሕዝብ መካከል ጥላቻ እንዲዳብር ያደረጉባቸው መንገዶች በርካታ ናቸው፡፡ ቀንደኛ ባንዶቻቸው ከትግሬዎች በእጅጉ እንዲጠነቀቁ ማድረግ አንዱ ነበር፡፡ ይህም የሆነበት መሠረታዊ ምክንያት ኤርትራውያን ሰፍኖ በነበረው ዘረኛ አመራር እየተበሳጩ ከሰሜን ትግራይ ወገኖቻቸው ጋር እየተገናኙ አደጋ ያደርሱባቸው ስለነበር ነው፡፡ የኢጣሊያን ሀብትና ንብረት ጨለማ ለብሰውና ጫካ ጥሰው ወደ ወገኖቻቸው ያሻግሩ የነበረ ሲሆን ከጌቶቻቸው ጋር ተጣልተው ሲመጡ እጃቸውን ዘርግተው ይቀበሏቸው ነበር። ከዚህም በተጨማሪ  የሰሜን ትግራይ ሰዎች አመችም ሲሆን ድንበሩን ተሻግረው የጠላትን ሀብት ከመዝረፋቸውም በላይ የኢጣሊያ ቅኝ ገዥዎችን ሲቃወሙ ያለ አንዳች ማወላወል የሚመጡት ወደ ትግራይ ዘመዶቻቸው ዘንድ ስለነበር ከትግሬዎች እንዲጠነቀቁ ቢመክሩ የሚደንቅም፣ የሚገርምም ሊሆን አይችልም፡፡ ብዙዎቹ ኤርትራውያን፣ በተለይም ከሰሜን ትግራይ ሕዝብ ጋር የሥጋ ዝምድና፣ የጋብቻ ዝምድናና የእምነት ዝምድና ስላላቸው ባይቀበሉትም አንዳንዶቹ ግን እራሳቸውን ማራቃቸውና የትግራይ ሕዝብን ማጥላላታቸው አልቀረም፡፡ ኢጣልያውያን ቅኝ ገዥዎቹ ወጥተው እንግሊዝ በሞግዚትነት ታስተዳድር በነበረችበት ጊዜም የዘረኛነት አመለካከቱ እንዲቀጥል ተደርጎ የነበረ ሲሆን ለዚህም ጥሩ ማስረጃ የሚሆነው  የከተማው አስተዳደር፣ ሕግ አስከባሪዎች፣ ዳኞችና ባለኢንዱስትሪዎቹ ኢጣሊያውያን ሆነው እንዲቀጥሉ ማድረጋቸው ነው፡፡
መጽሐፉ ከዚህም ሌላ፣ በኤርትራ የተቃዋሚ ፓርቲ መሪዎች ስለሆኑት  ወልደአብ ወልደማርያም፣ ራቢጣ አል-ኢስላሚያ፣ ዓብዱልቃድር ከቢረ፣ ኢብራሂም ሱልጣን ዓሊ፣ ኢድሪስ ሙሐመድ አደም፣ ሙሐመድ ሰዒድ ናዋድ፣ ሐሚድ ኢድሪስ ዓዋተ፣ ከአሚዶ ጉሌት ምን ያህል ያውቃሉ? አቶ ታምራት ላይኔን ጥርስ ውስጥ ያስገባቸው ጋዜጣዊ መግለጫ የቱ ነው? የኢትዮጵያ መንግሥትና የኤርትራ መንግሥት ወዳጅነት ለምን ምች እንደመታው ሰብል በአንድ ጊዜ ወየበ? የሚሉትን መሠረታዊ ጥያቄዎች በማንሳት ይተነትናል፡፡    
መጽሐፉ ከዚህ ቀደም ተነስቶ በማያውቅ ሁኔታ የኢሕአዴግ ትግልና የኤርትራ ነፃነት ትግልን፣ የኢህአዴግ አነሳስና እድገትን፣ በትግሬዎች ላይ ላለፉት መቶ ዓመታት የሚነዛው ቅኝ ገዥ ወለድ አስከፊ የንቀትና የጥላቻ አመለካከትን፣ የትግራይ ትግርኝ አጭር ታሪክን --- ከመተንተኑም በላይ ህወሓት፣ ኤርትራ ከኢትዮጵያ ለምን እንድትነጠል ፈለገ? ምንስ ጥቅም አስገኘ? (በመላምት ላይ የተመሠረተ ሐሳብ)፣ የሕዝባዊ ወያኔ የፖለቲካ መሪዎች ለምን የውሕደቱን ፍላጎት ትኩረት የሚነፍጉበት ጊዜ ተከሰተ? ምንስ ጥቅም አስገኘ? ---- የሚሉትን ጥያቄዎች  ለመመለስ ይሞክራል፡፡   
ከዚህ ቀደም ታትመው ለንባብ ከበቁ መጻሕፍት የማናገኘው ሌላው ክፍል፣ የኢህአዴግ አሸናፊነትና የሽግግር መንግሥት መቋቋምን፣ በተወካዮች ምክር ቤት መቀመጫ የያዙ የፖለቲካ ድርጅቶችን፣ በተወካዮች ምክር ቤት ከተከናወኑት ሥራዎች በከፊል፣ ለኤርትራ ሬፈረንደም በኤርትራ ጊዜያዊ መንግሥት በኩል የተደረገ ዝግጅትን፣ በሬፈረንደሙ ዋዜማ የኤርትራ ሬፈረንደም ውጤት አቀባበል አጭር ታሪክን፣ የኤርትራን ሬፈረንደም እንዲታዘብ የተላከው የኢትዮጵያ ሽግግር መንግሥት ልዑካን፤ በአስመራ ከተማና አካባቢው፣ በምጽዋና አካባቢው፣ በከረን፤ አቆርዳትና አካባቢው፣ በአካለ ጉዛይና ሠራዩ አውራጃዎች ያነጋገራቸው የተለያዩ የኀብረተሰብ ክፍሎች አስተያየት በዝርዝር ያቀርባል፡፡ የኤርትራን ሬፈረንደም እንዲታዘብ የተላከው የኢትዮጵያ ሽግግር መንግሥት የልዑካን ቡድን አባላት እነማን እንደነበሩም ያመለክታል፡፡
መጽሐፉ ኢትዮጵያና ኤርትራ በሰበበ ባድመ፣ በግጭት ዋዜማ የነበራቸውን ግንኙነትን በሚመለከትም የኤርትራና የኢትዮጵያ የኢኮኖሚ፣ የማህበራዊና የፖለቲካ ውህደት የምሥራች መግለጫ፣ ድንገተኛው የአቶ ታምራት ላይኔ ጋዜጣዊ መግለጫና ለእስር መዳረግ፣ የብር ኖት መቀየር፣ ኤርትራ የኢትዮጵያን ብር በናቅፋ የሚተካ አዋጅ ማውጣት፣ ፕሬዚደንት ኢሳያስ አፈወርቂ፤ የኢትዮጵያና የኤርትራ ግንኙነት ድንበር የለሽ እየሆነ መምጣቱን መግለጣቸውና በኋላም ‹‹ለኢኮኖሚ ችግራችን ኢትዮጵያን አንወቅስም›› ማለታቸው፣ የባድመ ጦርነት የድንበር ጥያቄ ወይስ ኤርትራን በሚገባ የማስገንጠል ዘዴ? የሚሉትን በዝርዝር ይዳስሳል፡፡
በመጨረሻም መጽሐፉ፣ የሌሎች አገሮች የሰላም ፍኖትን እንደ አብነት በመውሰድ (የቬትናም፣ የጀርመንና የየመን ውህደት ታሪክ) የኢትዮጵያንና የኤርትራ ሕዝብን አንድነት ለማምጣት የሚያስችለውን ጥቅል-የማንነት ጥያቄን ይፈትሻል። የታሪክ እርቅን ለማምጣት ምን መደረግ አለበት? ጥላቻ ምንድን ነው? ጦርነት የሚያስከትለው ጥላቻ፣ መታረም ያለበት እጅግ አደገኛ አዝማሚያ፣ የሰዎች ጥላቻ የመጨረሻ ደረጃ፣---- የመሳሰሉትን መሠረታዊ ጉዳዮች ይተነትናል፡፡ መልካም ንባብ፡፡

   ከቤተ ጉራጌ ህዝብ አንዱ የክስታኔ ጉራጌ ነው፡፡ የክስታኔ ጉራጌ የበርካታ ባህላዊ እሴቶች ባለቤትም ነው፡፡ ከባህላዊ እሴቶቹ መካከል ደግሞ አንዱ የደንጌሳት በዓል አከባበር ስርአት ነው፡፡ ይህ እጅግ ጥልቅ ባህላዊ ይዘት ያለውን በዓል በሰፊው ለማስተዋወቅ ሰፊ አላማ ይዞ የሚንቀሳቀሰው በክስታኔ - ጉራጌ ህዝብ የልማት ማህበር ስር የሚገኘው የክስታኔ - ጉራጌ እህትማማቾች ስብስብ ይህን የደንጌሳት ዝግጅት መስከረም 11 በአዲስ አበባ አየር ጤና አካባቢ በሚገኘው አንተለህ ሁለገብ
አዳራሽ ያካሂዳል፡፡ የዚህ ማህበር ሊቀ መንበር የሆኑት ወ/ሮ አስራቴነሽ ከበደ ከአዲስ አድማስ ጋዜጣ ጋር የአፍታ ቆይታ አድርገዋል፡፡

     ስብስቡ እንዴት ተመሰረተ?
የክስታኔ ጉራጌ እህትማማቶች ስብስቡን የመሰረትነው አስር ሆነን ነው፡፡ አሁን ላይ የአባላት ቁጥር ተበራክቷል፡፡ ማህበሩ በጠቅላላው አሁን 220 አባላት አሉት፡፡ ይህ የሴቶች ስብስብ ለጊዜው ተደራጅቶ ያለው በክስታኔ - ጉራጌ ህዝብ የልማት ማህበር ስር ነው፡፡ ለወደፊት ግን ራሱን ችሎ ፈቃድ አውጥቶ ይንቀሳቀሳል፡፡
አላማዎቹ ምንድን ናቸው?
በዋናነት አላማው የክስታኔ - ጉራጌ ሴቶች በክፉም በደጉም ለመጠያየቅ እንዲረዳቸው ነው። በክስታኔ ሴቶች ዙሪያ በገጠርም ሆነ በከተማ በርካታ ስራዎችን በመስራት አቅማቸውን ማጎልበት አንደኛው አላማ ነው፡፡ አንዳንድ መሰረታዊ የሆኑ ችግሮቻቸውን ለመቅረፍ የተለያዩ ፕሮጀክቶችን ቀርፆ የመስራት አላማ አለው፡፡ አሁን ላይ በየወሩ ተገናኝተን ስለማህበራችን ከመምከር ባለፈ በክስታኔ ጉራጌ ሴቶች አካባቢ የሚከበሩ አንዳንድ ባህላዊ ይዘት ያላቸው ክንውኖች የማስተዋወቅ ስራ እንሰራለን፡፡
ከሰራችኋቸው የማስተዋወቅ ስራዎች ጥቂት ቢጠቅሱልን …
ከዛሬ ሁለት ዓመት በፊት በ2008 መስከረም 11 የደንጌሳት በአል አዘጋጅተን ማህበረሰቡን ይበልጥ የሚያቀራርብ መርሃ - ግብር በደመቀ ሁኔታ አካሄደናል፡፡ በዚያ መንፈስ ቀጥለን በ2009 ለማድረግ አቅደን የነበረ ቢሆንም በአንዳንድ ሁኔታዎች ዝግጅቱን ለማካሄድ አመቺ ስላልነበረ ልናሳካው አልቻልንም፡፡ ዘንድሮ ግን በ2010 በተመሳሳይ ዝግጅቱን እናቀርባለን፡፡ ፕሮግራሙን የምናቀርበው አየር ጤና በሚገኘው በአንተነህ ሁለገብ አዳራሽ መስከረም 11 ቀን ይካሄዳል፡፡
የዝግጅቱ ይዘት ምንድን ነው?
የዝግጅቱ ይዘት ደንጌሳት ባህልን ለማያውቁት ለማሳወቅ፣ ለተተኪው ትውልድ ባህሉን ለማውረስ ነው፡፡ ምንግዜም የክስታኔ-ጉራጌባህል መለያና መገለጫ የሆኑትን እሴቶች መድረክ አመቻችቶ ለማንፀባረቅ የምናደርገው የማህበራችን አላማ አካል ነው ይህ ዝግጅት። ሌላው ማህበረሰብም የክስታኔ ህዝብን ባህል በሚገባ እንዲገነዘብ ማስቻልም ሌላው የዚህ ዝግጅት አላማ ነው፡፡
የወደፊት እቅዳችሁ ምንድን ነው?
ለወደፊት አሁን ካለውም በሰፋ ሁኔታ በርካታ ህዝብ የሚያሳትፍ ቀለመ ብዙ ዝግጅት በዚሁ በክስታኔ - ጉራጌ ሴቶች ህይወት ዙሪያ ሰፋ አድርገን ለማከናወን እቅድ አለን፡፡ ለጊዜው በዋናው ማህበር ስር ነው ይሄን የምንሰራው፡፡ ዋነኛው እቅዳችንም የክስታኔ ጉራጌ ሴቶችን የማንቃት፣ አቅም የመገንባትና በከተማም ሆነ በገጠር ባሉ የክስታኔ - ጉራጌ ሴቶች ላይ ተጨባጭ የኑሮ ለውጥ የማምጣት ስራ እንሰራን። በቀጣይ ዓመት የጉራጌ ዞን እንዲሁም የሀገሪቱ አንዱ የቱሪዝም መስህብ በሆነው በጢያ ትክል ድንጋይ አካባቢ ሰፊ ፌስቲቫል ለማዘጋጀት አቅደን እየተንቀሳቀስን ነው፡፡

  ከዕለታት አንድ ቀን አንድ በህይወት ኑሮው ሁሉ ነገር ተሳክቶለት፣ ይለጉመው ፈረስ፣ ይጭነው አጋሠሥ ያለው እጅግ የናጠጠ ዲታ ሰው ነበረ፡፡ እጅግ ቆንጅዬ ሚስት የነበረችው ሲሆን፤ ከእሷ የተወለዱ የሚያማምሩ ልጆችም ነበሩት፡፡ ታዲያ ይህን ሰው ሁልጊዜ የሚከነክነው በአገሩ ውሸት እንጂ ዕውነት አለመኖሩ ነበር፡፡ ስለዚህ አንድ ቀን ማለዳ ተነስቶ ሚስቱን፤
“ሰማሽ ወይ የኔ ቆንጆ?” ይላታል፡፡
“አቤት የእኔ ጌታ?” ትላለች፡፡
“ኑሮዬ ደርጅቶ ሁሉ ነገር የተሟላልኝ ሰው ሆኜ ሳለ፣ አንድ ነገር ግን በጣም ይቆጨኛል”
“ምን?”
“ዕውነትን አለማግኘቴ”
“ዕውነት ነው ያልከኝ?”
“አዎን”
“እባክህ ዕውነት የሚባል ነገር ኖሮ አያውቅም”
“አለ እንጂ እኛ መፈለግ አቅቶን ነው”
“በዚያ የምታምን ከሆነ ቤት ቁጭ ብለህ መቆጨት ሳይሆን ወጥተህ መፈለግ ነው ያለብህ”
“ካልሺስ ዛሬ ማለዳ የተነሳሁት ዕውነትን ፍለጋ ለመዞር ነው”
“ይቅናህ፡፡ ስታገኛት ግን ለእኔ ልታሳየኝ ቃል ግባልኝ”
ሊያሳያት ቃል ገባና ንብረቱን ሁሉ አውርሷት መንገድ ጀመረ፡፡ ከዚያ በኋላ ዕውነትን ለማግኘት ከለማኝ ጀምሮ ይጠይቅ ጀመር፡፡ ተራሮች ላይ ወጥቶ ፈተሸ፡፡ ሸለቆዎች ውስጥ እየገባ በረበረ፡፡ ትናንሽ መንደሮችንና ከተሞችን አሰሰ፡፡ ባህሮችንና የባህር ዳርቻዎችን መረመረ፡፡ ጨለማና ብርሃንን አጤነ፡፡ የቆሸሹ ቦታዎችንና በአበባ የተሞሉ አትክልት ሥፍራዎችን ሁሉ እየገባ አጣራ፡፡ ቀናትንና ሌሊቶችን አጠና፡፡ ሳምንታትን፣ ወራትን እና ዓመታትን በደምብ አጤነ፡፡ ዕውነት አልተገኘችም፡፡
አንድ ቀን በተራራ ግርጌ ባለ አንድ ዋሻ ውስጥ ዕውነትን ተሸሽጋ እንደምትኖር ምልክት አየና ፈጥኖ ወደሷ ዘንድ ሄደ፡፡ ዕውነት አንዲት የጃጀች አሮጊት ናት፡፡ ብልህ ናት፡፡ አስተዋይ ናት፡፡ በመላ ድዷ ላይ የሚታየው አንድ ጥርስ ብቻ ነው- እሱም የወርቅ! ፀጉሯ ሽበት ብቻ ነው፡፡ እሱንም ሹሩባ ተሠርታዋለች። የፊቷ ቆዳ የደረቀና የተጨማደደ ብራና ይመስላል፡፡ አጥንቷ ላይ ተጣብቋል፡፡ ይህ ሁሉ እንዳለ ሆኖ፣ በዕድሜ ብዛት የአሞራ ኩምቢ የመሰለውን ጣቷን እያወናጨፈች መናገርን ታውቅበታለች፡፡ ድምጿ የሚያምር፣ የተቃና፣ ለስላሳና ጣፋጭ ናት፡፡ ሰውዬው “አዎ፤ ይቺ ዕውነት እራሷ ናት” አለ፡፡
ለማጣራትም፤
“ዕውን ዕውነት አንቺ ነሽን?” ሲል ጠየቃት
“አዎን ነኝ” አለች፡፡
አብሯት አንድ ዓመት በመቆየት የዕውነተን ትምህርት ሊቀስም ወሰነ፡፡
የምታስተምረውን ሁሉ ተማረ፡፡
ከአንድ ዓመት በኋላ ወደ ቤቱ ለመሄድ ተነሳ! እንዲህም አላት፡-
“የዕውቀት ዕመቤት ሆይ! እስከ ዛሬ ያለሽን ዕውነት ሁሉ አጎናፀፈሺኝ፡፡ ማወቅ ያለብኝንም አሳወቅሺኝ! ላደረግሺልኝ ውለታ ካሣ ይሆንሽ ዘንድ ምን ባደርግልሽ ደስ ይልሻል?”
ዕውነትም፤
“በየደረስክበት ስለ እኔ ተናገር!
አደራህን ወጣትና ቆንጅዬ ሴት
መሆኔን ሳትታክት አስረዳልኝ!”
አለችውና ወደ ጓደዋ ገባች፡፡
*  *  *
ኬንያውያን አዘውትረው የሚናገሩት አንድ አባባል አላቸው፡- “አካፋን አካፋ ነው እንጂ ትልቅ ማንኪያ ነው አትበል!”
ስለ ማንነታችን፣ ስለ ዲሞክራሲያዊና ኢ- ዲሞክራሲያዊ ግንኙነታችን፣ ስለ ፓርቲያችን፣ ስለ ሀገራችንና ስለ መከላከያ ኃይላችን፤ ስለ ሥልጣናችንና ስለ ልማታችን ስናስብ፤ የኬንያውያኑ አባባል እናስታውስ! ሚሥጥራዊነታችን ፍንትው ብሎ እየታየ ከእኛ በላይ ግልፅ የለም፤ አንበል፡፡ በራችንን ሁሉ ክርችም አድርገን ዘግተን ስናበቃ እንወያያለን፣ ሀቁን እንገመግማለን ብንል ተዓብዮ እንጂ ሌላ ሊሆን አይችልም፡፡ እያየን አላየንም፤ እየሰማን አልተሰማንም፤ እያጠፋን አላጠፋንም ማለት በባህሪያችን የሰረፀ ቢሆንም፤ ቀስ በቀስ እየቀረፍን መጣል ያለብን ታላቅ ችግር ነው፡፡ በቡድናዊ ስሜት ተወጥረን ዴሞክራሲያዊነታችንን እያበለፀግን ነው፤ ብንል፤ በጠብታ ውሃ ውስጥ ጉማሬ ዓይተናል፤ ማለት ይሆንብናል፡፡ ዓላማችን በሀቅ ላይ የተመሰረተ ከሆነ፤ ተስፋችን ይለመልማል፡፡ ሴረኛና ደባ-ሠራሽ አንሆንም!
ያንን ያሸተትን ዕለት ወደ ጥፋት ጎዳና ማምራታችን ነው፡፡ ስለ ሴራ ህንዳዊው ፈላስፋ ካውቲላ ይህንን ፅፏል፡-
  “በዓላሚ ቀስተኛ፤ የተሰደደ ቀስት
 ሁለት ዕድል አለው፤ መግደል ወይም መሳት፡፡
 ግን በስል ጭንቅላት፣ ሴራ ከተሳለ ህፃንም ይገላል፣
 እናት ሆድ ውስጥ ያለ!!”
ይሄ ግጥም ሴረኞችን የሚያጋልጥ ነው፡፡ በአግባቡ እንድንሰጋ ያደርገናል፡፡ አደገኛነቱን እያየን እንድንጠነቀቅ ያግዘናል፡፡ ዕቅዳችንን በወቅቱ እናብስል!! የሌሎችን አስተያየት እንቀበል፡፡ “ካፈርኩ አይመልሰኝ”ን እንተው! ግትርን እንዋጋ፡፡ አያሌ ጊዜ ስለ አንድነትና ስለ መከፋፈል ተናግረናል፡፡ የተቋም አንድነት፣ የቡድን ስብስብ አንድነት፣ የግምባር አንድነት፣ የፓርቲ አንድነት ወዘተ አስፈላጊነቱን አውስተናል። ሆኖም ተፈታታኝ ሁኔታዎች የተገነባውን ሲንዱት፣ የተደራጀውን ሲያፈርሱት፣ የተመቻቸውን ሲያውኩ አስተውለናል፡፡ መፍትሔ ተብለው የሚቀመጡትን መላዎችም ለመመርመር ሞክረናል፡፡ በአብዛኛው በእነ ሌኒን ዘመን እንደተነገረው ዓይነት “The party purges itself” (ፓርቲ ራሱን አፀዳ እንደማለት) ያለ መርህ ነው የሚቀርበው፡፡ ተቀናቃኞችን ማስወገድ ነው ዘዴው፡፡ የተወገዱ ወገኖች፣ ለአስወጋጆቹ ወገኖች በጭራሽ አይተኙላቸውም፡፡ ወድቀው መቃብር እስኪገቡ ጉድጓድ ሲምሱላቸው ይከርማሉ፡፡ ይህ ተደጋጋሚ ክብ-ሩጫ መቆሚያ የለው፡፡ አንዳንዴ ወደ ደም መፋሰስ ሊደርስም ይችላል፡፡ ያ እንግዲህ ክፉ ገፅታው መሆኑ ነው፡፡ ይህ ዕውነታ በሀገራችን በተደጋጋሚ ተከስቷል፡፡ አሰቃቂ ሂደት ነው፡፡ አገር ይሸረሽራል፣ የተማረውን ወገን ያኮሰምናል፣ ሞራል ያደቃል፡፡ ፈፅሞ ለአገር የሚጠቅም ሂደት አይደለም! የጠላት ወገን እንኳ አንጃ ከተፈጠረበት፣ አንድ የነበረው ጠላት ሁለት- ሦስት ሆኖ ቁጭ ይላል፡፡
የሁኔታውን ፅናንነት ያዩ የተገነዘቡ፣ ፀሐፍት፤ ቅራኔዎች የማይታረቅ ደረጃ ሳይደርሱ በፊት በተቻለ መፍትሔ መፍጠር ብልህነት ነው ይሉናል፡፡ ዋናው ቁም ነገር፤ “መከፋፈል እንኳን ለወዳጅ ለጠላትም አይበጅ” የሚለውን አባባል በውል ማጤን ነው! ወደ ውስጣችን እንመልከት፡፡ “ጠጣሩ እንዲላላ፣ የላላውን ወጥር” እንደተባለው ነው!

Saturday, 09 September 2017 16:35

መልካም ዓዲስ ዓመት

  ደራሲ የኑስ በሪሁን ያዘጋጀው “በእርግጠኝነት መለሰኝ” የተሰኘ መፅሀፍ የፊታችን ሁሙስ ከቀኑ 11፡00 ጀምሮ በአዜማን ሆቴል ይመረቃል፡፡
በልብ ወለድ አተራረክ ስልት የተቃኘውና ታሪክንና ነባራዊ ሁኔታን ግምት ውስጥ በማስገባት፣ ያለፈውን ከአሁን እያጠቀሰ የሚቃኘው መፅሃፉ፤ መቼቱን በሰሜኑ የአገራችን ክፍል በሚገኝ ትልቅ ከተማ የትምህርት ተቋም ላይ ያደረገ ሲሆን ሁነቶችን እያሰናሰለ ለውጥ የሚፈጥር መፅሀፍ መሆኑን ደራሲው በመግቢያቸው አስፍሯል፡፡ በ317 ገፆች የተቀነበበው መፅሀፉ፤ በ120 ብር ለገበያ ቀርቧል፡፡ በምርቃት ስነስርዓቱ በመፅሀፉ ላይ ዳሰሳ የሚካሄድ ሲሆን የተለያዩ ኪነ-ጥበባዊ ዝግጅቶች ይካሄዳሉም ተብሏል፡፡

 የቀድሞው አንድነት ለፍትህና ለዴሞክራሲ ፓርቲ (አንድነት) ከፍተኛ አመራር የነበሩት የኢ/ር ዘለቀ ረዲ፤ “የ21ኛው ክፍለ ዘመን መሳፍንትና ኢትዮጵያን እንደ ሀገር የማስቀጠል ፈተና” የተሰኘ መፅሐፍ ለንባብ በቃ፡፡ መፅሃፉ  መሳፍንታዊ አስተሳሰብ ከጥንት ጀምሮ በአገሪቱ ላይ ስላስከተለው ጉዳት፣ አሁን ድረስ የዘለቀው ይህ አስተሳሰብ እንዴት ከፋፍሎ እንደሚገዛ፣ አስተሳሰቡ ህዝቡን ከፋፍሎ ስለሚገዛባቸው መሳሪያዎች፣ በአስተሳሰቡ የትኛው የህብረተሰብ ክፍል ሰለባ እንደሆነና እንዴት ስር ሰዶ አሁን እስካለንበት ዘመን እንደመጣ ይተነትናል፡፡
መሳፍንታዊ አስተሳሰብ አገሪቱን እንደ አገር ለማስቀጠል ምን ያህል ፈተና እንደሆነ የሚገልፀው መፅሃፉ፤ ይህን አስተሳሰብ ከስሩ ለመንቀል የሚያስችሉ የመፍትሄ ሀሳቦችን ይጠቁማል፡፡  በ14 ምዕራፎች  በ236 ገፆች የተመጠነው መፅሀፉ፤ በ75 ብር ከ99 ሳንቲም እና በ28 ዶላር ለገበያ የቀረበ ሲሆን ሎሚ ቡክስ በተባለ የኦላይን የመፅሀፍ ገበያም ጭምር እንደሚሸጥ ታውቋል፡፡

Sunday, 10 September 2017 00:00

በዳይመንድ ሊግ

 • ዘንድሮ የኬንያ አትሌቶች ድርሻ ከ740.5 ሺ ዶላር በላይ ሲሆን የኢትዮጵያ አትሌቶች ድርሻ እስከ 198ሺ ዶላር ነው፡፡
                      • በ2017 ኬንያ 4 የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖች ኢትዮጵያ ምንም
                      • ባለፉት 8 የውድድር ዘመናት ኬንያ 37 ኢትዮጵያ 12 የዳይመንድ ሊግ ድሎች
                   
       ዳይመንድ ሊግ በዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች የሚዘጋጅ ሲሆን ከፍተኛ የገንዘብ ሽልማት ከሚያቀርቡ የማራቶን ውድድሮች ቀጥሎ ለአትሌቶች ከፍተኛ የገቢ ምንጭ የሆነና በከፍተኛ እድገት ላይ የሚገኝ ዓመታዊ ውድድር ነው፡፡ ዳይመንድ ሊግ ዘንድሮ ለ8ኛ ጊዜ ሲካሄድ በአዲስ መዋቅር  ሲሆን በ32 የውድድር መደቦች በሁለቱም ፆታዎች 1200 አትሌቶች ተሳትፈውበታል፡፡ ትራክ ስታት www.track-stats.com የተባለ ድረገፅ በሰራው ስሌት  በ8ኛው የዳይመንድ ሊግ ላይ  ከቀረበው 8 ሚሊዮን ዶላር የገንዘብ ሽልማት 607 አትሌቶች ከ1ሺ ዶላር ጀምሮ እስከ 134ሺ ዶላር ተሸልመዋል፡፡ ዘንድሮ በዳይመንድ ሊጉ ከፍተኛውን የገንዘብ ሽልማት በመውሰድ አንደኛ ደረጃ የተሰጣት 134ሺ ዶላር ማሸነፍ የቻለችው  ኤለና ቶምሰን ከጃማይካ ስትሆን፤ ሽዋኔ ሚለር ከባህማስ በ127ሺ ዶላር፤ ማርያ ላስቲስኤኔ ከራሽያ በ100ሺ ዶላር እንዲሁም ሙታዝ ኡሳ ከቦትስዋና በ100ሺ ዶላር እስከ አምስተኛ ደረጃ አከታትለው ወስደዋል፡፡ ከኬንያ ኤለን ኦቡሪ፤ ከደቡብ አፍሪካ ካስተር ሴማንያ፤ ከቦትስዋና ኒጄል አሞስ፤ ከአሜሪካ ሽዋን ሄንድሪክስ፤ ከግሪክ ካተሪን ሴፈንዲ በነፍስ ወከፍ 90ሺ ዶላር እንዲሁም ከክሮሽያ ሳንድራ ፔርኮቪች 86ሺ ዶላር ከሽልማት ገንዘቡ በመቋደስ እስከ 10ኛ ደረጃ ለማግኘት ችለዋል፡፡
በሌላ በኩል በ8ኛው ዳይመንድ ሊግ በቅርብ ተቀናቃኞቹ የኬንያ እና ኢትዮጵያ አትሌቶች መካከል ከሽልማት ገንዘቡ በተገኘ ድርሻ ከፍተኛ ልዩነት ተስተውሏል፡፡ የትራክ ስታት የሽልማት ገንዘብ ስሌት እንዳመለከተው ኬንያውያን ከ1 እስከ 10፤ ከዚያም እስከ 20 እንዲሁም እስከ ሃምሳኛ እና እስከ መጨረሻው ደረጃ በርካታ አትሌቶችን በማሳተፍ ከገንዘብ ሽልማቱ በ3 እጥፍ ከኢትዮጵያ የሚልቅ  ድርሻ በማግኘት ተሳክቶላቸዋል፡፡ በአጠቃላይ በዳይመንድ ሊጉ ላይ ዘንድሮ ኬንያ 49 አትሌቶችን በማሳተፍ ከ740.5ሺ ዶላር በላይ ስትሰበስብ አራት የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖች አግኝታለች፡፡ ከ7 የውድድር ዘመናት በኋላ የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮን ሳታስመዘግብ የቀረችው ኢትዮጵያ 19 አትሌቶችን በማሳተፍ ከሽልማት ገንዘቡ ያስመዘገበችው ድርሻ 148ሺ ዶላር ብቻ ሆኗል፡፡  የኢትዮጵያ አትሌቶች ከዳይመንድ ሊጉ የሽልማት ገንዘብ የሚኖራቸው ድርሻ የቀነሰው በዓለም ሻምፒዮና ተሳትፎ ሳቢያ አትሌቶች ከውድድር ተሳትፎ በመታገዳቸው፤ በምርጥ አሰልጣኞች እና በቂ የልምምድ ጊዜ ባለመስራታቸው፤ በውስን የውድድር መደቦች በሁለቱም ፆታዎች በመሳተፋቸው እና በተቃናቃኝ አትሌቶች የውድድር ታክቲክ እና ቴክኒክ በመበለጣቸው ነው፡፡ የኬንያ አትሌቲክስ ፌደሬሽን የአትሌቶችን የዳይመንድ ሊግ ተሳትፎ ባለማገዱ እንዲሁም ከኢትዮጵያ በተሻለ የውድድር መደቦች በብዛት መሳተፋቸው ከሽልማት ገንዘብ ያገኙትን ድርሻ የላቀ አድርጎታል፡፡
በትራክ ስታት www.track-stats.com ስሌት መሰረት ከኢትዮጵያ አትሌቶች ግንባር ቀደም ሆኖ የሚጠቀሰው በ5ሺ ሜትር የዓለም ሻምፒዮን ለመሆን የበቃው ሙክታር ኢድሪስ በ42ሺ ዶላር የሽልማት ድርሻው ከዓለም 49ኛ ደረጃ በማግኘቱ ነው፡፡  ዮሚፍ ቀጀልቻ በ24ሺ ዶላር 93ኛ፤ ዳዊት ስዩም እና በሱ ሳዶ በ16ሺ ዶላር 136ኛ እና 137ኛ፤ ጉድፍ ፀጋይ በ15.5 ሺ ዶላር 142ኛ ላይ ናቸው፡፡ ሌሎች የኢትዮጵያ አትሌቶች ከ150ኛ በታች  እስከ 350ኛ ደረጃ ተዘበራርቀው ሊቀመጡ በቅተዋል፡፡ አማን ወጤ 13፤ ሶፍያ አሰፋ 13ሺ፤ ሃብታም አለሙ 12፤ ሰለሞን ባረጋ 12፤ ለተሰንበት ግደይ 11፤ የኔው አላምረው 8፤ በሱ ሳዶ 5.5፤ ገንዘቤ ዲባባ፤ 4.5፤ እቴነሽ ዲሮ 4.5፤ ጫላ ባዬ 3ሺ፤ ብርሃኑ ለገሰ 2.5፤ ስንታየሁ 1.5፤ ዳዊት ወልዱ 1.5 እንዲሁም ሰለሞን በልሁ 1ሺ ዶላር ከ8ኛው የዳይመንድ ሊግ የገንዘብ ሽልማት አግኝተዋል፡፡
ዳይመንድ ሊግ ከ1998 እኤአ እስከ 2010 እኤአ ለ11 የውድድር ዘመናት ይካሄድ የነበረውን የአይኤኤፍ ጎልደን ሊግ በተሻለ ደረጃ የተካ ነው፡፡ ለ12 የውድድር ዘመናት የተካሄደው ጎልደን ሊግ በ6 ከተሞች በሚደረጉ ውድድሮች የሚያሸንፉ አትሌቶችን 1 ሚሊዮን ዶላር ወይንም የወርቅ ጡቦች በማካፈል የሚሸለምበት ነበር። በጎልደን ሊግ በ1998 እኤአ ላይ ኃይሌ ገብረስላሴ 333,333 ዶላር፤ በ2006 እኤአ ላይ ቀነኒሳ በቀለ እና ጥሩነሽ ዲባባ በነፍስ ወከፍ 83,333 ዶላር እንዲሁም ቀነኒሳ በቀለ በ2009 እኤአ ላይ 333,333 ዶላር ተሸላሚዎች ነበሩ፡፡
የጎልደን ሊግ ውድድርን የተካው ዳይመንድ ሊግ  ባለፉት 8 የውድድር ዘመናት ከፍተኛ ለውጥ እና ድምቀት በማሳየት ከአይኤኤኤፍ ውድድሮች ስኬታማው ሆኖ እየተጠቀሰ ይገኛል፡፡ ዳይመንድ ሊጉ በየሚካሄድባቸው ከተማዎች ከፍተኛ የስታድዬም ተመልካች አለው። በተለይ በአሜሪካ ዩጂን፤ በስዊዘርላንድ ዙሪክ፤ በሞናኮ  እንዲሁም በእንግሊዝ በርሚንግሃም ከተሞች የሚካሄዱት የዳይመንድ ሊግ ውድድሮች ስታድዬም በሚገባ ተመልካች እየገዘፉ ናቸው፡፡ በቴሌቭዥ ስርጭት ከፍተኛውን ሽፋን በማግኘት ከአትሌቲክስ ውድድሮች ዋና ተጠቃሽ የሆነው ዳይመንድ ሊግ  የዓለም መገናኛ ብዙሃንን ትኩረት በመሳብ ውጤታማም ነው፡፡ በዳይመንድ ሊጉ የየአገራቱ ምርጥ አትሌቶች፤ የዓለምና የኦሎምፒክ ሻምፒዮኖችን መሳተፋቸው ምርጥ ፉክክር የሚስተዋልበት መድረክ አድርጎታል፡፡ ካለፉት ሁለት የውድድር ዘመናት ወዲህ በ4 አህጉራት ኤስያ፤ አውሮፓ፤ መካከለኛው ምስራቅ፤ አሜሪካን እንዲሁም አፍሪካን በማካለል የሚካሄደው ዳይመንድ ሊጉ በ4 ወራት  በ13 የተለያዩ አገራትና 15 ከተሞች ሲስተናገድ  በከፍተኛ የውድድር ደረጃው ሪከርዶች እና የውድድር ዘመኑ ፈጣን ሰዓቶች የሚመዘገቡበት ታላቅ መድረክ እየሆነ መጥቷል፡፡
በሌላ በኩል ባለፉት ስምንት የውድድር ዘመናት በዳይመንድ ሊጉ ተግባራዊ የሆኑ አዳዲስ የአሰራር መዋቅሮች በሻምፒዮናው የእድገት ደረጃ ፈጣን ለውጥ እንዲመዘገብ ምክንያት ሆነዋል፡፡ በዳይመንድ ሊጉ የአሰራር መዋቅር ለውጦች የተደረጉት ለ3 ጊዜያት ነው፡፡ በመጀመርያዎቹ 6 የውድድር ዘመናት በ12 ከተሞች ውድድሮች እየተካሄዱ ከ1 እሰከ 3 ለሚወጡ አትሌቶች ብቻ   አሸናፊዎችን ለመለየት  ነጥብ በመስጠት በውድድር ዘመኑ መጨረሻ ከፍተኛውን ነጥብ ለሚያስመዘግቡት ሻምፒዮንነቱ ይፀድቅ ነበር።  በ2016 እኤአ በ7ኛው የውድድር ዘመን በተመሳሳይ ሻምፒዮኖችን በከፍተኛ ነጥብ የመለያ መንገድ ከ1 እሰከ 6ኛ ደረጃ ለሚያገኙ አትሌቶች ነጥብ በመስጠት ተሰርቶበታል፡፡ በ2017 እኤአ ላይ ግን የአሰራር መዋቅሩ በጣም ልዩ ለውጥ ተደርጎበታል፡፡ በመጀመርያ 12 የማጣርያ ውድድሮች የተካሄዱ ሲሆን ከ1 እስከ 8ኛ ደረጃ ለሚያገኙት ነጥብ  ተሰጥቶ የዳይመንድ ሊጉ አሸናፊዎች የሚለዩት በሁለት ከተሞች በሚከናወኑ የፍፃሜ ውድድሮች ሆኗል፡፡ 12ቱን የዳይመንድ ሊግ የማጣርያ ውድድሮች ዘንድሮ ያስተናግዱት የዶሃ ከተማ በኳታር፤ የሻንጋይ ከተማ በቻይና፤ የዩጂን ከተማ  በአሜሪካ፤ የሮም ከተማ  በጣሊያን፤ የኦስሎ ከተማ በኖርዌይ፤ የቶክሆልም ከተማ በስዊድን የፓሪስ ከተማ በፈረንሳይ፤ የዙሪክ ከተማ በስዊዘርላንድ፤ የበርሚንግሃም ከተማ በእንግሊዝ፤ የራባት ከተማ በሞሮኮ ፤ የሞናኮ ከተማ በሞናኮ እንዲሁም የለንደን ከተማ በእንግሊዝ  ናቸው። ከእነዚህ የ12 ከተሞች የማጣርያ ውድድሮች በኋላ በከፍተኛ ነጥብ በየውድድር መደቡ የጨረሱ አትሌቶች የዳይመንድ ሊጉ ሻምፒዮኖች በሚለዩት በስዊዘርላንድ ዙሪክ እና በቤልጅዬም ብራሰልስ የሚካሄዱ ውድድሮች ተለይተዋል፡፡
ዓለም አቀፉ የአትሌቲክስ ፌደሬሽኖች ማህበር ዘንድሮ በዳይመንድ ሊግ ለማጣርያው እና ለፍፃሜ ውድድሮች ያቀረባቸው የተለያዩ የሽልማት ገንዘቦች ናቸው፡፡ በዳይመንድ ሊጉ በ12 ከተሞች በሚደረጉ የማጣርያ ውድድሮች  ከ1 እሰከ 8ኛ ደረጃ ላገኙ አትሌቶች በሚበረከተው የሽልማት ገንዘብ መሰረት ለ1ኛ 10ሺ ዶላር፤ ለ2ኛ 6ሺ ዶላር፤ ለ3ኛ 4ሺ ዶላር፤ ለ4ኛ 3ሺ ዶላር፤ ለአምስተኛ 2500 ዶላር፤ ለስድስተኛ 2ሺ ዶላር ፤ ለ7ኛ 1500 ዶላር እንዲሁም ለ8ኛ 1000 ዶላር የሚታሰብ ይሆናል፡፡ በሁለቱ የፍፃሜ ውድድሮች ደግሞ የሽልማት ገንዘቡ ለውጥ የተደረገለት ሲሆን ከ1 እሰከ 8ኛ ደረጃ ላገኙ አትሌቶች በሚበረከተው የሽልማት ገንዘብ መሰረት ለ1ኛ 50ሺ ዶላር፤ ለ2ኛ 20ሺ ዶላር፤ ለ3ኛ 10ሺ ዶላር፤ ለ4ኛ 6ሺ ዶላር፤ ለአምስተኛ 5ሺ ዶላር፤ ለስድስተኛ 4ሺ ዶላር ፤ ለ7ኛ 3ሺ ዶላር እንዲሁም ለ8ኛ 2ሺ ዶላር እንዲከፈል ተደርጓል። በፍፃሜዎቹ የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖች ለመሆን የሚበቁት 32 አትሌቶች በነፍስወከፍ ከሚያገኙት የ50ሺ ዶላር ሽልማት በተጨማሪ በአልማዝ ማእድን የተሰራ ልዩ የዳይመንድ ሊግ ዋንጫ  ይወስዳሉ። 4.9 ኪግ የሚመዝነው የዳይመንድ ሊግ ዋንጫው ተቀማጭነቱ በስዊዘርላንድ ዙሪክ የሆነው፤ ለ250 ዓመታት በዋንጫዎች፤ የክብር ሽልማቶች፤ ሰዓቶች እና ልዩ ልዩ ጌጣጌጦች ስራ የሚታወቀው ክሮኒዮ ሚቲዬሬ የሚሰራ እንደሆነ ታውቋል፡፡ የዳመንድ ሊግ ዋንጫው በ3 የአትሌቲክስ  ገፅታዎች በስታድዬም ፤ በተመልካች ድባብ እና በአትሌት ብቃት መገለጫነት የተቀረፀ ነው፡፡
12 የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖችና 6 የዳይመንድ ሊግ ክብረወሰኖች
የኢትዮጵያ 12 የዳይመንድ ሊግ ድሎች  በ10 አትሌቶች የተመዘገቡ ናቸው፡፡ በ800 ሜትር መሃመድ አማን በ2012 እና በ2013 እኤአ አሸንፏል። በ3ሺ እና 5ሺ ሜትር ወንዶች  በ2010 እና 2011 እኤአ ኢማና መርጋ እንዲሁም በ2013 እኤአ የኔው አላምረው ናቸው። አበባ አረጋዊ ዜግነቷን ሳትለውጥ በፊት በ1500 ሜትር በ2012 እኤአ ላይ አሸናፊ ነበረች፡፡ በሴቶች 5ሺ ሜትር መሰረት ደፋር በ2013 እኤአ ያሸነፈች ሲሆን በ3ሺ ሜትር መሰናክል ደግሞ 2014 እኤአ ላይ ህይወት አያሌው ድል አድርጋለች፡፡ በ2015 ደግሞ ዳይመንድ ሊጉን በ5ሺ ሜትር ለማሸነፍ የበቃችው ገንዘቤ ዲባባ ስትሆን በ2016 እኤአ ደግሞ በ3ሺ እና 5ሺ ሜትር መደብ አልማዝ አያና እና ሃጎስ ገብረህይወት አሸንፈዋል፡፡ በ2017 ኢትዮጵያ የዳመንድ ሊግ ሻምፒዮን አላስመዘገበችም፡፡
በ3ሺ ሜትር የኔው አላምረው በኳታር ዶሃ በ2011 እኤአ ላይ በ7፡27.26
በ5ሺ ሜትር ደጀን ገብረመስቀል በፈረንሳይ ፓሪስ በ2012 እኤአ 12፡46.81
በ10ሺ ሜትር ቀነኒሳ በቀለ በቤልጅዬም ብራሰልስ በ2011 እኤአ 26፡43.16
በሴቶች 1500 ገንዘቤ ዲባባ በፈረንሳይ ሞናኮ በ2015 እኤአ ላይ 3፡50.07 የዓለም ሪከርድ ነው፡፡
በሴቶች 5ሺ ሜትር አልማዝ አያና በሮም ጣሊያን በ2016 እኤአ 14፡14.32
በ10ሺ ሜትር ጥሩነሽ ዲባባ በአሜሪካ ዩጂን 2012 እኤአ ላይ በ30፡24.39
በ8  የዳይመንድ ሊግ የውድድር ዘመናት በሻምፒዮኖችና በክብረወሰኖች የአገራት  ደረጃ
ባለፉት 8 የዳይመንድ ሊግ የውድድር ዘመናት 59 የዳይመንድ ሊግ አሸናፊዎችና 9 የዳይመንድ ሊግ ክብረወሰኖች  ያስመዘገበችው አሜሪካ አንደኛ ደረጃ ይዛለች፡፡ ኬንያ በ37 የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖችና በ8 የዳይመንድ ሊግ ክብረወሰኖች ሁለተኛ ደረጃ ላይ ስትሆን፤ ጃማይካ በ18 የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖች እና 7 የዳይመንድ ሊግ ክብረወሰኖች ሶስተኛ ፤ ኢትዮጵያ በ2012 እኤአ ላይ አበባ አረጋዊ በ1500 ሜትር ዜግነቷን ወደ ስዊድን ሳትቀይር ያስመዘገበችውን ድል ጨምሮ በ12 የዳይመንድ ሊግ ሻምፒዮኖችና ስድስት የዳይመንድ ሊግ ክብረወሰኖች አራተኛ ደረጃ ላይ ትገኛለች፡፡

የተቸገሩትን የመርዳትና የመለገስ ልማድ በአለማቀፍ ደረጃ እየቀነሰ ቢመጣም አፍሪካን የመሳሰሉ ድሃ አህጉራት ግን ቸርነታቸውና ደግነታቸው እየጨመረ መምጣቱን ባለፈው ማክሰኞ ይፋ የተደረገ አንድ አለማቀፍ ጥናት አመልክቷል፡፡
በ139 የአለማችን አገራት ላይ የተሰራን ጥናት መሰረት ያደረገው አመታዊው አለማቀፍ የበጎ አድራጎት ልገሳ ሁኔታ አመላካች ሪፖርት እንዳለው፣ ባለፈው የፈረንጆች አመት የገንዘብ ልገሳ የማድረግ ወይም የማያውቁትን ሰው የመርዳት ልማድ በአለማቀፍ ደረጃ በ2 በመቶ የቀነሰ ሲሆን፣ የበጎ ፈቃደኝነት ተግባር ደግሞ በ1 በመቶ ቀንሷል፡፡
አሜሪካን ጨምሮ የአለማችን ቀዳሚዎቹ 10 ሃብታም አገራት፣ከአምናው ጋር ሲነጻጸር ዘንድሮ በለጋስነት ማሽቆልቆል አሳይተዋል ያለው ሪፖርቱ፤ከአለማችን 20ዎቹ የበለጸጉ አገራት መካከል ከቀዳሚዎቹ 20 ለጋስ አገራት ተርታ መሰለፍ የቻሉት ስድስት ብቻ ናቸው ብሏል፡፡
ላለፉት ሶስት ተከታታይ አመታት የአለማችን እጅግ ቸር እና ለጋስ ህዝቦች መኖሪያ ናት ተብላ በሪፖርቱ በቀዳሚነት የተቀመጠቺው ማይናማር፣ ዘንድሮም የአንደኛነትን ደረጃ ይዛለች ያለው ዘገባው፤ ኢንዶኒዢያ የሁለተኛነት ደረጃን መያዟን አመልክቷል፡፡ በአመቱ በቸርነትና በልግስና ከፍተኛ መሻሻል ያሳየቺው ኬንያ መሆኗን በመጠቆም፣ አምና 12ኛ ደረጃ ላይ የነበረቺው ኬንያ፣ ዘንድሮ ሶስተኛ ደረጃን ላይ መቀመጧንም ገልጧል፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ፣ በቸርነት ከአለማችን አገራት የመጨረሻውን ደረጃ የያዘቺው በእርስ በእርስ ጦርነት የፈራረሰቺው የመን መሆኗን አመታዊው ሪፖርት አስታውቋል፡፡
ቻሪቲስ ኤይድ ፋውንዴሽን በተባለው አለማቀፍ ተቋም የተሰራው ጥናቱ፤ የ139 የአለማችን አገራት ዜጎች የሆኑ ከ146 ሺህ በላይ ሰዎችን ቃለ መጠይቅ በማድረግ በተሰበሰበው መረጃ ላይ በመመስረት፣ የአገራቱን ዜጎች የበጎ ምግባር የገንዘብ ልገሳ ተሞክሮ፣ የበጎ ፈቃደኝነት ተሳትፎና የማያውቁትን ሰው የመርዳት ተነሳሽነት በመገምገም ደረጃ እንደሚሰጥም ተነግሯል፡፡

  100 የአመቱ ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝር ውስጥ አፍሪካዊ የለበትም


       የአለማችንን ዩኒቨርሲቲዎች የጥራት ደረጃ በየአመቱ ይፋ የሚያደርገው አለማቀፉ የዩኒቨርሲቲዎች ሊግ ሰሞኑንም የአመቱን የአለማችን ምርጥ 100 ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝር ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ የእንግሊዙ ኦክስፎርድ ዩኒቨርሲቲ ዘንድሮም እንደ አምናው በአንደኛነት ደረጃ ላይ መቀመጡን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
ለ13ኛ ጊዜ ይፋ በተደረገው የአለማችን የምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝር ውስጥ የእንግሊዙ ካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ የሁለተኛነት ደረጃን ሲይዝ፣ ባለፈው አመት የአለማችን ሁለተኛው ምርጥ የነበረው የአሜሪካው ካሊፎርኒያ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ ዘንድሮ ከአሜሪካው ስታንፎርድ ዩኒቨርሲቲ ጋር የሶስተኛነቱን ደረጃ ተጋርቷል፡፡
8ኛ ደረጃን ከያዘው ኢምፔሪያል ኮሌጅ ኦፍ ለንደን እና 10ኛ ደረጃን ከያዘው የዙሪክ የፌዴራል የቴክኖሎጂ ኢንስቲቲዩት በስተቀር፣ ከ3ኛ እስከ 15ኛ ያለውን ደረጃ የያዙት ሁሉም የአሜሪካ ዩኒቨርሲቲዎች መሆናቸውን የጠቆመው ዘገባው፣ እነሱም ማሳቹሴትስ ኢንስቲቲዩት ኦፍ ቴክኖሎጂ፣ ሃርቫርድ ዩኒቨርሲቲ፣ ፕሪንሴተን ዩኒቨርሲቲ፣ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ቺካጎ፣ ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ፔንሲልቫኒያ፣ ኮሎምቢያ ዩኒቨርሲቲ እና ዩኒቨርሲቲ ኦፍ ካሊፎርኒያ ናቸው ብሏል፡፡  
ከ30ዎቹ የአለማችን ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች መካከል ሰባቱ የአውሮፓ ዩኒቨርሲቲዎች ሲሆኑ ሶስቱ ደግሞ የእስያ አገራት ዩኒቨርሲቲዎች ናቸው ያለው ዘገባው፤ እስከ 100 ባለው የአመቱ ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች ዝርዝር ውስጥ አንድም አፍሪካዊ ዩኒቨርሲቲ አለመካተቱን አክሎ ገልጧል፡፡

  የሩዋንዳ መንግስት በርዕሰ መዲናዋ ኪጋሊ እየተባባሰ የመጣውን የትራፊክ መጨናነቅ ለማስወገድ በማሰብ፣የግለሰቦች የቤት መኪኖች በከተማዋ ጎዳናዎች ላይ እንዳይንቀሳቀሱ የሚከለክል ህግ ተግባራዊ ለማድረግ ማቀዱ ተዘግቧል፡፡
የአገሪቱ መንግስት ከቀጣዩ አመት አጋማሽ ጀምሮ ተግባራዊ ሊያደርገው ያሰበው ይህ ህግ፣ በመዲናዋ ኪጋሊ የህዝብ ትራንስፖርት ከሚሰጡና ከተፈቀደላቸው የተቋማት ተሸከርካሪዎች በስተቀር የግል መኪኖች መንቀሳቀስ አይችሉም ሲል ፐልስላይቭ ከትናንት በስቲያ ዘግቧል፡፡
በከተማዋ ለሚታየው ከፍተኛ የትራፊክ መጨናነቅ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከቱ የሚገኙት የግል መኪኖች በመሆናቸው የአገሪቱ መንግስት ህጉን ለማውጣት መገደዱንና የህዝብ ትራንስፖርት የሚሰጡ አውቶብሱችን በብዛት ወደ ስራ ለማስገባት ማሰቡን ዘገባው አመልክቷል፡፡
ህጉ ጸድቆ ተግባራዊ  ከሆነ፣ የቤት መኪና ያላቸው የኪጋሊ ነዋሪዎች፣ ከ2018 አጋማሽ አንስቶ ብስክሌት ወይም የህዝብ ትራንስፖርት አገልግሎት የሚሰጡ አውቶብሶችን ለመጠቀም ወይም በእግራቸው ለመጓዝ ይገደዳሉ ተብሏል፡፡