Administrator

Administrator

  በደርግ ስርዓት የኢህአፓ ታጋይ ሆነው ለእስርና ለእንግልት ስለተዳረጉ ወጣቶች የሚተርከው ‹‹ከኒያ ልጆች ጋር›› የተሰኘ መፅሐፍ ሰሞኑን ገበያ ላይ ዋለ፡፡ ከአባላቱ አንዱ በነበረው ትንሳኤ የተባለ የኢህአፓ ታጋይ ጋር በተደረገ ቃለ ምልልስ፣ በፋሲካ መለሰ የተዘጋጀው መጽሐፉ፤ባለታሪኩ በእስርና በስደት ባሳለፈው ህይወት ላይ ተመስርቶ ስለ ሌሎች ተመሳሳይ ህይወት ያሳለፉ ኢትዮጵያዊያን ወጣቶች የሚተርክ ሲሆን ወጣቶቹ ምን አይነት ገድል እንደፈፀሙ፤እንዴት እንደታሰሩና እንዴት እንደተፈቱ በስፋት ይተነትናል ተብሏል፡፡ በ17 ምዕራፎች  የተከፋፈለው መፅሐፉ፤ በፋርኢስት ማተሚያ ቤት ታትሞ በክብሩ መፅሐፍ መደብር እየተከፋፈለ ሲሆን በ90 ብር ከ99 ሳንቲም ለአገር ውስጥና በ20 ዶላር በውጭ አገራት ለገበያ መቅረቡ ታውቋል፡፡

• ጃንሆይ አምላክ መባላቸውን በመቃወም፣ጃማይካ ውስጥ የቤተ-ክርስቲያን ማሰሪያ ገንዘብ ሰጥተዋል
• በሻሸመኔ መጀመሪያ መሬት የተሰጣቸው ጥቁር አሜሪካውያን እንጂ ራስ ተፈሪያን አይደሉም
• መስፍን አበበ “በኢትዮጵያ የመጀመሪያው ጊታር ተጫዋች ነኝ” ማለቱ ውሸት ነው

የፎቶግራፍ ባለሙያው ንጉሴ ተሾመ ደጀኔ የተወለዱት በአዲስ አበባ ልደታ አካባቢ ነው፡፡ በልጅነታቸው ከቤተሰቦቻቸው ጋር በኤርትራ ደቀመሀሪ ለተወሰኑ ዓመታት ተቀምጠው ወደ አዲስ አበባ የተመለሱ ሲሆን ለአንድ ዓመት በሊሴ ገ/ማርያም ት/ቤት ተምረው እንደገና ከቤተሰቦቻቸው ጋር ወደ ሻሸመኔ በማቅናት፣ በአፄ ናኦድ ት/ቤት እስከ 8ኛ ክፍል መማራቸውን ይናገራሉ፡፡ ላለፉት 50 ዓመታት በፎቶግራፍ ባለሙያነት የሰሩት አቶ ንጉሴ፤ ፎቶግራፍ የተጻፈ ታሪክን ተጨባጭና ተዓማኒ ያደርገዋል ይላሉ፡፡ በተለይ እውነቱን የማውቀው ታሪክ ተጣሞና ተዛብቶ ሲቀርብ በጣም እናደዳለሁ የሚሉት ባለሙያው፤ በፎቶግራፎች ማስረጃነት የተዛቡ ታሪኮች እንዲታረሙ ተደጋጋሚ ጥረት ማድረጋቸውን ይናገራሉ፡፡ “ራስ ተፈሪና የራስ ተፈሪያን ማንነት” በሚል ርዕስ የጻፉት መጽሃፍም የህትመት ብርሃን እየተጠባበቀ እንደሚገኝ ገልጸዋል፡፡ ለመሆኑ ወደ ፎቶግራፍ ባለሙያነት እንዴት ገቡ? ፎቶግራፍና ታሪክን እንዴት አስተሳሰሩት? እስካሁን ምን ያህል የተዛቡ ታሪኮችን በፎቶግራፎች ማስረጃነት ለማረም ሞከሩ? ሥራና ኑሮአቸውስ ምን ይመስላል? የአዲስ አድማስ ጋዜጠኛ ናፍቆት ዮሴፍ ባለፈው ሳምንት መጨረሻ ለስራ አዳማ በሄደችበት ወቅት፣ የፎቶግራፍ ባለሙያውን አቶ ንጉሴ ተሾመን አግኝታ በሙያቸው ዙሪያ አነጋግራቸዋለች፡፡ እንዲህ ተጠናቅሯል፡-

ቤተሰቦችዎ ከቦታ ቦታ የሚዘዋወሩት በምን ምክንያት ነበር?
በወቅቱ አባቴ ሹፌር ስለነበሩ የተለያየ ቦታ ይጓዛሉ፡፡ በዚህ ምክንያት ቤተሰባችን ተረጋግቶ አይቀመጥም ነበር፡፡ በኋላ ላይ አባቴ ማዕከላቸውን ሻሸመኔ አደረጉና፣ እኛም ከ1949 ዓ.ም ጀምሮ እዚያ መኖር ጀመርን፡፡ አፄ ናኦድ ት/ቤት እስከ 8ኛ ክፍል ተማርኩኝ፤ አባቴም ዲላ ወላይታ እየሄዱ በሹፍርና ይሰሩ ነበር፡፡ በቃ እዚያው አደግሁኝ፡፡ ስለ ሻሸመኔ ብዙ ነገር አውቃለሁ፤ ብዙ የፎቶግራፍ ማስረጃዎችም አሉኝ፡፡
እንዴት ወደ ፎቶግራፍ አንሺነት ሙያ ሊገቡ ቻሉ? ለመጀመሪያ ጊዜ ፎቶግራፍ ያነሱትና ካሜራ የጨበጡት መቼ ነበር?
በ1963 ዓ.ም የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቴን እንዳጠናቀቅኩ በ27 ብር “ሉቢቴልቱ” የተባለች የራሺያ ካሜራ ከነማኑዋሏ ገዝቼ፣ ከዚያን ጊዜ አንስቶ ከተማ እየዞርኩ ታሪክ ማስቀረት ጀመርኩ። ፍላጎቱ ያደረብኝ በአሰብ መንገድ አንድ ተኮላ የሚባል ኢንጂነር መንገድ እያሰራ ፎቶ ያነሳና ስዕል ይሰራል፤ ስዕሉን ከፎቶው ላይ ነበር አስመስሎ በትልቁ የሚስለው፡፡ እሱ በወቅቱ ያቀረበውን የስዕል ኤግዚቢሽን በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን አየሁኝ፡፡ በካሜራ ካነሳሁ በኋላ ነው የምስለው ብሎ ሲናገርም ሰማሁ፤ ለምን እኔስ በካሜራ እያነሳሁ አልስልም በሚል ካሜራውን ገዛሁ፤ከዚያ በኋላ ማንሳቱን ቀጠልኩኝ ማለት ነው፡፡
እስከ ዛሬ ከ200 ሺህ በላይ ፎቶዎችን አንስተዋል ይባላል፡፡ እውነት ነው?
አይበልጥም ብለሽ ነው፡፡ ምክንያቱም ዲጂታል ካሜራ ከመጣ ያነሳሁት እንኳን ብዙ ስለሆነ ያለኝ የፎቶ ብዛት ወደ 300 ሺህ ሳይጠጋ አይቀርም፡፡ የካሴት ከቨር የሆኑ ወደ 300 አልበም ፎቶዎች አሉኝ። የቀድሞው ቱሪዝም ኮሚሽን የሚያሳትመውን ፖስተርና ፖስት ካርድ ሰብስቤ ከ400 በላይ አለኝ፡፡ እነሱ ጋ አንድም የለም፤ሸጠው ሸጠው ጨርሰውታል፤የተሳሳተ ነገር ሲያወጡ እየፃፍኩ አርማቸዋለሁ፡፡  
በሻሸመኔ መጀመሪያ መሬት የተሰጠው ለራስ ተፈሪያን አይደለም፤የሚለውን ማስረጃ ከየት ነው ያገኙት?
 ቀደም ብዬ እንደነገርኩሽ እኛ ሻሸመኔ በቋሚነት መኖር የጀመርነው በ1949 ዓ.ም ነው፡፡ በ1942 ግን በጃንሆይ በጎ ፈቃድ መሬት የተሰጠው ለሶስት አፍሮ አሜሪካዊያን ነው፡፡ እነሱም፡- ግላድስተን ሮቢንሰን፣ ጀምስ ፓይፐር እና ባለቤታቸው ወ/ሮ ፓይፐር ብቻ ነበሩ፡፡
እነዚህ አፍሪካ አሜሪካዊያን እንዴት ከጃንሆይ መሬቱ ሊሰጣቸው ቻለ?
በጣም ጥሩ፡፡ ፋሽስት ጣሊያን ለሁለተኛ ጊዜ አገራችንን በ1928 ዓ.ም በወረረ ጊዜ ጃንሆይ ለአምስት አመታት ለንደን ነበሩ፡፡ ያኔ ጥቁር አሜሪካውያን ኒውዮርክ ሀርለም ላይ ኢትዮጵያን ለማገዝና ለመዋጋት 17 ሺህ ያህል ሆነው ተመዝግበው ነበር፡፡ ነገር ግን ፈረንሳይ፣ ጣሊያንና እንግሊዝ ዙሪያውን ከበው ስለነበር መግባት አይቻልም ነበር፡፡ ስለዚህ ሶስት ተደማጭነት ያላቸው አፍሮ አሜሪካዊያን ተመርጠውና ተወክለው ጃንሆይ የሚኖሩበት ለንደን ድረስ ሄደው አነጋገሯቸው፡፡ የጥቁር አሜሪካዊያኑንም ኢትዮጵያን የማገዝ ፍላጎት አስረዷቸው፡፡ ከህዝቡ ማለትም ከአሜሪካውያኑ የተውጣጣውን አራት ሚሊዮን ብርም ሰጧቸው፤ ምክንያቱም ኒውዮርክ ላይ “የምኒሊክ ክበብ” የሚል አቋቁመው የእርዳታ ገንዘብ ያሰባስቡ ነበር፤ ጥቁር አሜሪካውያኑ፡፡ በኋላ ጃንሆይ “ወደ ኢትዮጵያ መግባት አትችሉም፤ዙሪያውን በቅኝ ገዢዎች የተከበበ ነው፤ ለስንቅና ትጥቅም አይመቻችሁም፤ እዛው ሆናችሁ ታገሉልን” አሏቸው “እንግዲያውስ አንድ አስተባባሪ ስጡን; ብለው ጠየቁ፡፡ ከዚያ ዶክተር መላኩ አማኑኤል በያን የተባለውን የአጎታቸውን ልጅ፣ ጃንሆይ በአስተባባሪነት ሰጧቸው፡፡ ዶ/ር መላኩ በአሜሪካ የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊ ዶ/ር ነው፡፡ ዶ/ር መላኩም አሜሪካ ሄዶ “Ethiopian World Federation” የተባለ ማህበር እ.ኤ.አ በ1937 አቋቋመ፡፡ ከዚያም እርዳታውን እያስተባበረ ለአርበኞች ትጥቅና ስንቅ፣ መድሀኒት፣ ለጃንሆይ መኖሪያ ሁሉን ማሟላት ጀመረ፡፡
 ጦርነቱ ካበቃ በኋላ ጃንሆይ ወደ አገራቸው እንደተመለሱ ለጥቁር አሜሪካዊያኑ ደብዳቤ ፃፉ፡፡ በጣሊያን ወረራ ጊዜ ላደረጉት ውለታ ለማመስገን፣ ሻሸመኔ ላይ መጥተው እንዲኖሩ የሚጋብዝ ደብዳቤ ነው፡፡ በዚህ ግብዣ መሰረት ሚስተር ጀምስ ፓይፐር፣ ባለቤታቸው ወ/ሮ ፓይፐርና ግላድስተን ሮቢንሰን በ1942 ዓ.ም ወደ ኢትዮጰያ መጥተው ሻሸመኔ መኖር ጀመሩ፡፡ የሚገርምሽ ወ/ሮ ፓይፐር ለንደን ውስጥ ለጃንሆይ ምግብ ያበስሉላቸው ነበር፡፡ እንዲያውም በወቅቱ የሻሸመኔ አካባቢ ባላባትና ሹም ፊታውራሪ ጁላ ሾቤ ይባሉ ነበር፡፡ ከዚያም ጃንሆይ ለፊታውራሪው፤“እነዚህ ባለውለታችን ስለሆኑ አምስት ጋሻ መሬት ፈልገህ ለአውራ ጎዳናው ቅርብ የሆነ ቦታ ስጣቸው” ብለው አዘዙ፡፡ ፊታውራሪውም፤ “ጃንሆይ፤ የመንግስት መሬት አውራ ጎዳናው ላይ የለም፤ መሬት ያለው ከከተማው ርቆ ወደ ኮፈሌ ገጠሩ ውስጥ ነው፤እዚያ ደግሞ አውሬዎች በብዛት ስላሉ ለመኖር አስቸጋሪ ነው፡፡ ስለዚህ ወደ ወላይታ ይሂዱና እዚያ ይኑሩ” የሚል ምላሽ ሰጡ፡፡ ጃንሆይ ደግሞ “አይ አንዴ አዝዤሀለሁ፤ከየትኛውም ሰው ላይ ቀምተህ ስጣቸውና ቤተ-መንግስት መጥተህ ሪፖርት አድርግ” የሚል ቀጭን ትዕዛዝ አስተላለፉ፡፡ በዚህ መሰረት ፊታውራሪ ጁላ፤ ከቄስ ገመኔ ላይ ሶስት ጋሻ መሬት፣ ከዋቻሞው ባላባት ላይ ሁለት ጋሻ ቀምተው አውራ ጎዳናው ላይ ያለ መሬት ሰጧቸው፡፡ ከዚያ ጀምስ ፓይፐርና ባለቤታቸው ወይዘሮ ፓይፐር እንዲሁም ግላድስተን ሮቢንሰን ከ1942 ጀምሮ መኖር ጀመሩ፡፡ ባልና ሚስቱ የአይሁድ እምነት ተከታይ ሲሆኑ ግላድስተን ሮቢንሰን የኦርቶዶክስ እምነትን ተቀብሎ ተጠምቆ በኋላ ስሙ ፍቅረ ስላሴ ይባል ነበር፡፡ ስምህ ማን ነው ሲባል እንኳን የባርነት ስሜ ግላድስተን ሮቢንሰን፣ የነፃነት ስሜ ፍቅረ ሥላሴ እያለ ይመልስ ነበር፡፡ በቅርብ ከአራት አመት በፊት ነው ፍቅረ ስላሴ የሞተው፤ እንቀራረብ ነበር፡፡
ታዲያ ጃማይካዊያን መቼ ነው ወደ ሻሸመኔ የመጡት?
ጃማይካዊያኑ በ1962 ዓ.ም ማለትም አፍሮ አሜሪካኑ ከመጡ ከ20 ዓመታት በኋላ ነው ስምንት ሆነው ወደ ሻሸመኔ የመጡት፡፡ አፍሮ አሜሪካኑ ወደ ኢትዮጵያ ሲመጡ ጃማይካዊያን በወቅቱ በእንግሊዝ ቅኝ አገዛዝ ስር ስለነበሩ ሻይቅጠልና ትምባሆ እያስተከሏቸው ነበር፡፡ ያን  ጊዜ ለራሳቸውም ነፃነት ስላልነበራቸው ኢትዮጵያን እንደ አሜሪካዊያን ሊያግዙ አልቻሉም ነበር፡፡ ከ20 ዓመታት በኋላ በ1962 ዓ.ም ስምንት ጃማይካዊያን መጡ፤በወቅቱ የግቢ ሚኒስትር በነበሩት ፀሐፌ ትዕዛዝ ተፈራወርቅ ኪዳነወልድ፣ ከቤተ መንግስት፤ “በሉ እንግዲህ ከእናንተ ጋር ይኑሩ” ብለው ወደ ሻሸመኔ ላኳቸው፡፡ አፍሮ አሜሪካኖቹ ተቃወሙ፡፡
ምን ብለው ተቃወሙ?
“እኛ አፍሮ አሜሪካዊያን ነን፤እነሱ ጃማይካዊያን ናቸው፤ በምንም አንገናኝም እንዴት አብረን እንኖራለን፤ይሄ መሬት የተሰጠው በኢትዮጵያ ወርልድ ፌደሬሽን ስም ለእኛ ነው” የሚል ነበር ተቃውሞው፡፡ ከዚያም የላኳቸው ፀሀፌ ትዕዛዝ፤“መልካችሁ አንድ አይነት ነው የአገራችሁ ርቀትም እንደዚያው፤በዚያ ላይ ለኢትዮጵያም ያላችሁ ፍቅር አንድ አይነት ነው ስለዚህ አብራችሁ ኑሩ” ሲባል “አብረን አንኖርም” ብለው አሻፈረኝ ሲሉ፣ የጃንሆይ ልጅ ልዕልት ተናኘወርቅ ጣልቃ ገብተው፤ “ለወደፊቱ እኔ ወንዶገነት ወዳለኝ መሬት እወስዳቸዋለሁ፤ አሁን አምስት አምስት ሄክታር ይሰጣቸውና ይቀመጡ; ተብሎ የዝዋይ አውራጃ ገዢ በተገኙበት (ፊታውራሪ ጁላ በወቅቱ ሞተው ስለነበር) ልጃቸው ነጌሶ ጁላ እየለካ፣ አምስት አምስት ሄክታር ሰጥቷቸው መኖር ጀመሩ፡፡ ይህ ሲደረግ የተፈረመው ደብዳቤ በእጄ ላይ ስላለ ማስረጃ ነው፡፡ ይህንን እውነታ ለምን እንደሚቆለምሙት አይገባኝም፡፡
ጃንሆይ ጃማይካን ለመጎብኘት በሄዱ ቀን ሲዘንብ ያደረ ዝናብ ቆመ እንጂ እሳቸው እዚያ ሲደርሱ ዝናብ አልዘነበም ብለው እንደሚከራከሩም ሰምቻለሁ-----
አዎ እከራከራለሁ፡፡ ለምን መሰለሽ----ጃንሆይ በጃማይካዎቹ አምላክ የተባሉት በ1923 ገና ዘውድ እንደጫኑ ነው፡፡ ጃማይካን የጎበኙት እ.ኤ.አ በ1958 ሊወርዱ ሲሉ ነው፡፡ ጉብኝቱም በጃማይካ መንግስት ግብዣ የተደረገ ነው፡፡ የዝናቡን ጉዳይ በተመለከተ ጃንሆይ እዚያ ከመድረሳቸው ከአንድ ቀን በፊት ሲዘንብ አደረና፣ ከገጠር ከአገሪቱ ጥግ ሁሉ ኪንግስተን ከተማ አምላኩን ለመቀበል የመጣውን የጃማይካ ህዝብ ሲቀጠቅጥ አድሮ፣ በነጋታው ጃንሆይ እዚያ ሲደርሱ ዝናብ አልነበረም፡፡ ፊልሙ እኔ ጋር ይገኛል፤ላሳይሽ እችላለሁ፤በዕለቱ በአቀባበሉ ላይ ጃንጥላም አልተያዘም፡፡
ጃንሆይን አምላክ ብሎ የተቀበለውም ያልተቀበለውም የጃማይካ ህዝብ እሳቸውን ለማየት ኪንግስተን ከተማ ወጥቶ ዝናብ እየቀጠቀጠው ስለነበር ጃንሆይ ከአውሮፕላን ሳይወርዱ አየር ላይ ለሶስት ሰዓት ያህል ቆይተዋል የሚባለውስ----?
ትክክለኛውን ስሚኝ፡፡ አየር ላይ አልቆዩም፤እንደውም ከአውሮፕላን ሲወርዱ ህዝቡ አጥሩን ሰብሮ ክቡር ዘበኛውን ጥሶ፣ አውሮፕላኑ ስር ይፍለከለክ ነበር፤ ይሄ ነው የሆነው፡፡
ታዲያ የታሪክ መፋለሱ የመጣው ከታሪክ ፀሐፊዎች ነው ወይስ በጃንሆይ ወገን የተወራ ነው?
እንደውም ጃንሆይ ስለ ራሳቸው አጋንነው የሚያወሩት ነገር የለም፡፡ አንድ ጊዜ ማርከስ ጋርቬይ እንግሊዝ ሊጎበኛቸው ሄዶ እንኳን አልተቀበሉትም፡፡
ማርከስ ጋርቬይ በ1890ዎቹ መጨረሻ “ከኢትዮጵያ አምላክ ይወጣል ወደ አፍሪካ ተመለሱ” እያለ የነበረና አሜሪካ የሚኖር ጃማይካዊ አይደለም እንዴ?
አዎ፤ እሱ ጃንሆይን አምላክ ነው ብሎ የሚናገር፣ በጃማይካዊያን ዘንድ እንደ ትንቢት ተናጋሪ የሚቆጠር ስለነበር፣ እኔ አምላክ ሳልሆን አምላክ እያለ ያወራል ብለው አልተቀበሉትም ነበር። በኋላ ጃንሆይ “ህዝባቸውን ለጣሊያን ትተው ወደ እንግሊዝ ሄደዋል” እያለ ሲከሰሳቸው ዶ/ር መላኩ አማኑኤል በያን ያልኩሽ የጃንሆይ የአጎት ልጅ፣ ክሱን በመቃወም መልስ ይሰጠው ነበር። ስለዚህ ጃንሆይ አምላክ መባላቸውን አጥብቀው ከመቃወማቸው የተነሳ ጃማይካ ውስጥ የቤተ ክርስቲያን ማሰሪያ የሚሆን ገንዘብ ሰጥተዋል፤ ትልልቅ የሀይማኖት መሪዎቻቸውን ሰብስበው፡፡ አባ ላዕከ ማሪያም የተባሉ የኦርቶዶክስ ቄስ በአጥማቂነት መድበው፣ “እኛ የምንከተለውን የኦርቶዶክስ ሀይማኖት ተከተሉ፤ እኛ አምላክ አይደለንም” ነው ያሉት ጃንሆይ። ጃማይካዎች “እናውቃለን ይሄ የትህትና ንግግር ነው፤ ኢየሱስ ክርስቶስም እኔ ክርስቶስ መሆኔን ለማንም እንዳትናገሩ ብሏል በመፅሀፍ ቅዱስ፤ ስለዚህ እኛ እርሶ አምላክ እንደሆኑ እናምናለን” አሉ፡፡ ኦርቶዶክስን የተቀበሉ ተጠመቁ፤ ያልተቀበሉ እርሳቸውን አምላክ ናቸው ብለው ቀጠሉ፤ ይሄው ነው፡፡ ወሬው ግን ከየት ተነስቶ የት እንደሚደርስ ተመልከቺ፡፡ ለምሳሌ የሻሸመኔ ልጆች ማህበር አለን፡፡ ከመሃላችን ትልልቅ የመንግስት ኃላፊዎችም አሉ፤የአካባቢው ተወላጆች የሆኑ----ስንሰበሰብና ራስ ተፈሪያን መጀመሪያ መሬት እንዳልተሰጣቸው፣ ለጥቁር አሜሪካውያኑ የተሰጠ የምስጋና መሬት እንደሆነ በፊት ለፊታቸው ስንናገር፣ ትንፍሽ አይሉም፤ እውነታውን ያውቁታላ፡፡
እርስዎ እንግዲህ የፎግራፍ ባለሙያ እንጂ የታሪክ ተመራማሪ አይደሉም፡፡ ይህን ሁሉ ታሪክ ያወቁት አካባቢው ላይ ስለኖሩ ብቻ ነው ወይስ ታሪክ የመሰነድ ፍላጎትም አለዎት?
በነገራችን ላይ ፎቶግራፍ ስታነሺም ታሪክ ነው የምታሰባስቢው፡፡ አንዳንድ ታሪኮች ተፅፈው በፎቶግራፍ ሲደገፉ ታሪክን የበለጠ ተጨባጭና ተዓማኒ ያደርጉታል፡፡ በዚያ ላይ ፎቶግራፍ ስታነሺ ገብቶሽ አንድን ነገር መሰረት አድርገሽ ስለምታነሺ፣በመረጃነት በአዕምሮሽም በወረቀትም ይቀመጣል፡፡ ታዲያ ታሪክ ሲዛባ ስትመለከቺ፣ ለምን የሚለውን ጥያቄ ታነሺና ፎቶዎቹን በማስረጃነት ታቀርቢያለሽ፡፡ ለምሳሌ በቅርቡ የጊታር ተጫዋቹ መስፍን አበበ በሰይፉ በኢቢኤስ ላይ ቀርቦ፣ በኢትዮጵያ የመጀመሪያው ጊታር ተጫዋች ነኝ ብሎ ተናግሯል፡፡ ነገር ግን ውሸት ነው፤አሁን በእርግጥ በህይወት የለም እንጂ ፊት ለፊት እንነጋገር ነበር፡፡ የሆነ ሆኖ እኔ ዘንድ በርካታ መረጃ አለ፡፡ መስፍን አበበ አምስተኛ ጊታር ተጫዋች ነው፡፡ ለዚህም “የጊታር አጀማመር በኢትዮጵያ” በሚል 60 ገፅ ፅሁፍ ፅፌ፣ 120 ያህል ፎቶግራፎች አስገብቼበት ተቀምጧል፡፡ በቅርቡ ይፋ ይሆናል፡፡
የመጀመሪያዎቹን ማለትም ከመስፍን አበበ በፊት ጊታር ተጫውተዋል የሚሏቸውን በቅደም ተከተል ሊነግሩኝ ይችላሉ?
አንደኛ የክቡር ዘበኛው ተዘራ ሃይለሚካኤል በ1952 ዓ.ም ተጫውቷል፣ ሁለተኛው የጅማው ግርማ ምንተስኖት በ1962 ጊታር ይጫወት ነበር፤ በኢቲቪ ሁሉ ይታይ ነበር፡፡ ሶስተኛው በ1968 የዘፈነው ፀጋዬ መርጊያ ነው፣ ሙሉጌታ ረታ አለሙ በ1970 በጊታር ዘፍኗል፡፡ መስፍን አበበ ከአራቱ በኋላ በ1972 ነው የመጣው፡፡ ይሄ መስተካከል አለበት፤ በሚል በመረጃ አስደግፌ በቅርቡ እለቀዋለሁ ብያለሁ፡፡
ሌላው የአርሲዋ ሴት ጉደቱ ካዎ ጉዳይ ነው። ይህቺ የአርሲ ሴት የቀድሞው ቱሪዝም ኮሚሽን ፎቶዋን በፖስት ካርድነት ይጠቀመው የነበረች ሴት ናት፡፡ ስለዚህች ሴት እኔ በ1981 ዓ.ም በዛሬይቱ ኢትዮጵያ ጋዜጣ ላይ፣ “አባቴን አፈላልጉኝ” በሚል ርዕስ ከአስር በላይ መጣጥፍ ፅፌ ነበር፡፡
 ምክንያቱም ፎቶውን ያነሳሁት እኔ ነኝ በሚሉ ሰዎች መሀል ጭቅጭቅ ተነስቶ ነበር፡፡ የሆነ ሆኖ በ2000 ዓ.ም የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትር የነበሩት መሀመድ ድሪር፣ የግብርና ሚኒስትር የነበሩት ሰው፣ የኦሮሚያ ባህል ቢሮ ኃላፊው እሷም አሀራ ተቀምጣ፣ ትልቅ ዝግጅት ተዘጋጅቶ አዳማ ላይ 105 ካ.ሜ ቦታ ተሸልማለች፡፡ የሀራምቤ ኮሌጅ ባለቤት ለ10 ዓመት በየወሩ 300 ብር እንድትወስድ ቃል ሲገባ በቦታው ተገኝቼ ፎቶ አንስቻለሁ፤ ስትወስድም አውቃለሁ፡፡ ቦታውን 45 ሺህ ብር መሸጧንም አውቃለሁ፤ነገር ግን በ2006 ዓ.ም በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ምንም እንዳልተደረገላት ክዳለች፡፡
ጋዜጠኛውን ስለ ራሷ የተፃፉ 10 የጋዜጣ ኮፒና 15 ፎቶግራፎች ሰጥተነው፣ 15 ቀን ስጡኝ አስተካክላለሁ ብሎ ሁለት ወር ተጠበቀ፤ አልመለሰም፡፡ ከዚያ እውነታውን በፌስቡክ “የኢቲቪ ጋዜጠኛ የቀደዳ አርበኛ” በሚል ለቀቅኩት፡፡ ይሄው እዚህ አዳራሽ ውስጥ ለጥፌዋለሁ፤ አንብቢው፡፡ እውነተኛ ማስረጃ ስላለኝ አንድም ሰው አልተቃወመም፡፡ ለምን ታሪክ ይዛባል። አቶ ሀብተስላሴ ታፈሰስ መዋሸት ነበረባቸው?
አቶ ሀብተስላሴ-----?
 አቶ ሀብተስላሴ ታፈሰ የኢትዮጵያ ቱሪዝም ኮሚሽን ኮሚሽነር የነበሩት ናቸው፡፡ እኔ በግሌ ለቱሪዝም መበልፀግ በሰሩት ትልቅ ስራ ክብር አለኝ፤ ነገር ግን በዚች ሴት ፖስት ካርድ ላይ አሻጥር ሰርተዋል። ፎቶውን ያነሳት አንቶኒዮ ቪራኖ የተባለው ጣሊያናዊ ነው፡፡ ክሪያዚዝ ዜርፎዝ የተባለ ፎቶ ቤት የነበረው አርመን፣ አሁን ፒያሳ ክሪያዚዝ ኬክ ቤት አጠገብ የነበረ ፎቶ ቤት ባለቤት “ከለር ማተም ጀምሬያለሁና ስጠኝ ጥሩ አድርጌ ላትምልህ” ይልና ከአንቶኒዮ ይቀበላል፡፡ ኮሚሽነሩ የክሪያዚዝ ጓደኛ ስለነበሩ፣እሳቸው ጋ ወስዶ በራሱ ስም አሳተማት፡፡
 አንቶኒዮና ክሪያዚዝ አቶ ሀብተስላሴ ጋ ሄደው ይካሰሳሉ፡፡ ለክሪያዚዝ አግዘው ፍርድ ሳይሰጡ ፎቶዋን እንደያዙ ደርግ መጣና እስር ቤት ከተታቸው፡፡ ከዚያ ራሱ ደርግ ፈታና መልሶ የቱሪዝም ኮሚሽን ኮሚሽነር አደረጋቸው፡፡ ፊልሟን አገኟትና በራሳቸው ስም፤ “Girl On the Baro River Gambella” ብለው አወጥዋት፡፡ ይሄንን ታሪክ ከራሷ ከጉዳቱ ካዎ መስማት ትችያለሽ፤ አርሲ ነገሌ በህይወት ያለች ሴት ናት፤ ታገኚያታለሽ፡፡ ላገናኝሽ እችላለሁ፡፡
ይህን ሁሉ ውሸት ለማጋለጥ ነው በ1981 በዛሬይቱ ኢትዮጵያ ላይ “አባቴን አፈላልጉኝ” በሚል ርዕስ በተከታታይ 10 መጣጥፍ ያወጣሁት፡፡ ያኔ ቱሪዝም ኮሚሽን “ስህተቱን እናርማለን” በሚል የፃፈልኝ ደብዳቤ በእጄ ላይ አለ፡፡
 የኢቲቪው ጋዜጠኛ ይህን ሁሉ ማስረጃ ካሰባሰበ በኋላ ነው ያልሆነ ታሪክ ያወጣው፡፡ በጣም ያሳዝናል፡፡ በተለይ እውነታውን እያወቅሁት ተጣሞና ተዛብቶ ሲቀርብ በጣም እናደዳለሁ፡፡
ሌላው ሰው ጋ የማይገኝና እኔ ብቻ አለኝ የሚሉት ፎቶ አለዎት?
እኔ ከሌላው የምለየው በአንድ ወቅት በምንም ሁኔታ ያነሳሁትን ፎቶ አልጥልም፤ ምክኒያቱም ፎቶ ቅርስ ነው፣ማስረጃ መፅሀፍ ነው፡፡ ሌላው ያነሳና ይጥለዋል፡፡ እኔ  በማንኛውም ጉዳይ ላይ መረጃ ስፈልግ አቀርባለሁ፤ልክ አሁን ለተዛቡ ታሪኮች መረጃ እንደማቀርበው ማለት ነው፡፡ ለፎቶግራፎች ክብር ሰጥቼ በማስቀመጤ ነው ከሌላው የምለየው፡፡ ስለዚህ አንቺ ፎቶ አንስተሸ ከጣልሽ እኔ ጋ አለ፤አንቺ ጋ የለም ማለት ነው፡፡
የፎቶግራፍ ኤግዚቢሽን አቅርበው ያውቃሉ?
በጣም ብዙ ጊዜ በተለያየ ቦታ አቅርቤያለሁ። በጣሊያን ካልቸር፣ በአሊያንስ ኢትዮ-ፍራንሴዝ፣ በፑሽኪን አዳራሽ ---- በበርካታ ቦታዎች አቅርቤያለሁ፡፡
በራስ ተፈሪያን ላይ የጻፉት መጽሀፍ በምን ደረጃ ላይ ነው?
ተፅፎ ካለቀ ቆይቷል፡፡ ታሪኩን በትክክል እንዲቀመጥ ለማድረግ ነው እንጂ ብር የለኝም። አሁን ግን የኔ የፎቶ ተማሪ የነበረ፣ እንደገና እኔን ኤዲቲንግ ያስተማረኝ በኃይሉ ግርማ የተባለ ልጅ፣እንደሚያሳትምልኝ ቃል ገብቷል፤እግዚአብሔር ይርዳው እንግዲህ፡፡
እስኪ ስለ ራስዎ ይንገሩኝ---በምን ሁኔታ ነው የሚኖሩት?
አሁን በቋሚነት የምኖረው አዳማ ነው፡፡ 45 ዓመት እዚህ የኖርንበትን ቤት፣ “ለእናታችሁ ነው ያከራየነው አናቅህም” ተብዬ ሰባት ዓመት ተከራክሬ አሸንፌ፣እዚሁ ቤት ውስጥ ብቻዬን እኖራለሁ። በትዳር በኩል የመጀመሪያዋ ባለቤቴ ከመላዕክና ከሰው የተፈጠረች ነበረች፤ በጣም ትረዳኝ ነበር ፈጣሪ ወሰዳት፤ አላመሰገንኩትም መሰለኝ፡፡
ሁለተኛዋ ባለቤቴ፣ ጥሩ ጥሩ ልጆች ሰጥታኛለች፤ሶ ስት ልጆች ከሰጠችኝ በኋላ እራሴ እንደመጣሁ እራሴ እሄዳለሁ አለች፤ ሸኘሁ መቼስ ምን አደርጋለሁ፡፡ አሁን ብቻዬን ነው የምኖረው፡፡
ልጆችዎ የት ነው ያሉት?
ልጆቹን ወስዳቸዋለች፡፡ ከአባት እናት ይበልጣል በሚል ሀዋሳ ይዛቸው ትኖራለች፡፡ ከሟች ሚስቴ የወለድኳት የመጀመሪያ ልጄ ትዝታ ንጉሴ፣ ራሷን ችላ እየሰራች ነው፡፡ እኔም ራሴን ችዬ እየኖርኩ ነው።



   ሌሊቱ እንደ ልማዱ አሸልቦ ማለዳው ለረፋዱ ቦታውን ሲለቅ ዝናቡም በካፊያ ይተካ ጀመር፡፡ ቀስ በቀስም ሰማዩ እየጠራ ብሩህ ቀን ከፊት ለመዘርጋቱ ተስፋ ይሰጥ ጀመር፡፡
 ሰኔ 23 ቀን 2ዐዐ8 ዓ.ም፣ ቢሾፍቱ ከተማ፡፡ የጨለለቃን ሀይቅ የሚጎራበተውና ሁሌም ፀዓዳ የማይለየው ባለግርማ ሞገሱ ጄክዶ ኦፖርቹኒቲ ፎር ቼንጅ የሥልጠና ማዕከል ግቢ ድባቡ ከወትሮው ለየት ብሏል፡፡ አለፍ አለፍ ብለው በተተከሉ ነጫጭ ድንኳኖች፣ በፌዴራልና በክልል ባንዲራዎችና በማስታወቂያ ባነሮች አሸብርቆ ለሁለተኛ ጊዜ የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማትን የመልካም ተሞክሮ ዓመታዊ በዓል ለማክበር ዝግጅቱን ሁሉ አጠናቅቋል፡፡
የዕለቱ ዝናብ ያልበገራቸው የማህበረሰብ ምስርት ተቋማት አመራሮችም በየድንኳኖቻቸው ደጃፍ ላይ ቆመው ለወራት ሲለፉበት የነበረውን ድግሳቸውን ለማቋደስ ጉብኝዎቻቸውን በመጠባበቅ ላይ ናቸው፡፡
በኢየሩሳሌም የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት (ኢ/ህ/ማ/ል/ድ) አዘጋጅነት “የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት አጋርነት ለዘላቂ ልማት” በሚል መሪ ቃል የሚከበረው ይህ በዓል ከተለያዩ የአገሪቷ ክልሎች የተወጣጡ 60 የሚደርሱ የኢ/ህ/ማ/ል/ድ አጋር የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማትን ያሳተፈ ነው፡፡ ለችግር ለተጋለጡ የህብረተሰብ ክፍሎች ሁለገብ ድጋፍ በመስጠት የተሻለ ኑሮ እንዲኖሩ በማስቻል ሥራ ላይ ከተጠመደ 30 ዓመታትን ያስቆጠረው ኢ/ህ/ማ/ል/ድ  በአሁኑ ሰዓት በአማራ፣ በኦሮሚያና በደ/ብ/ብ/ህ ክልሎችና በአዲስ አበባና በድሬዳዋ ከተማ አስተዳደሮች ውስጥ በተለያዩ የማህበረሰብ ልማት እንቅስቃሴዎች ላይ ጠንካራ ተሳትፎ እያደረገ ነው፡፡ በተለይ ላለፉት 15 ዓመታት የማህበረሰብ አቀፍ ተቋማት ጋር በጋራ በመሥራትና አቅማቸውን በተለያየ መልኩ በመገንባት ሕብረተሰቡ የራሱን ችግር በራሱ እንዲፈታ በማስቻል በኩል ጠንካራ ልምድ አካብቷል፡፡ የዚሁ ጥረቱ አካል የሆነው የቢሾፍቱው መርሀ-ግብርም ያለፉትን ስኬቶች ከመዘከር በሻገር የወደፊት አቅጣጫዎች የሚመላከቱበት፤ ማህበራቱም ጠቃሚ ተሞክሮዎችን የሚጋሩበትና የእርስ በርስ ትስስርም የሚፈጥሩበት መድረክ ነው፡፡
የተለያዩ ከተሞች የመንግስት ጽ/ቤቶች፣ የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት፣ የለጋሽ ድርጅቶች እና መንግሥታዊ ያልሆኑ ድርጅቶች ተወካዮች፣ ጋዜጠኞች እና ሌሎች ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች ሁሉ ቀስ በቀስ ወደማዕከሉ እየደረሱ ጊቢውም ሞላ ማለት ጀመረ፡፡ የዕለቱ ዋነኛ ባለጉዳዮች የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት ተወካዮችም እስከመጨረሻው ሰዓት ድረስ ተፍ ተፍ ማለታቸውን አላቋረጡም፡፡  
ልክ ከጠዋቱ 3፡3ዐ ሰዓት ሲሆን የዕለቱ የክብር እንግዳ የቢሾፍቱ ከተማ ከንቲባ ተወካይ፣ ወ/ሮ ዘውድነሽ አሰፋ የበዓሉን በይፋ መከፈት አበሰሩ፡፡ እናም የሁሉም ትኩረት የመጀመሪያው መርሀ-ግብር ወደሆነው ወደ ተቋማቱ የልማት አስተዋፅኦ ዐውደ-ርዕይ ሆነ፡፡ ይሄን ጊዜ በማህበረሰባቸው ለማህበረሰባቸው የተቋቋሙትና በሰዎች ሞት ጊዜ ከመረዳዳት ባሻገር በድህነት ግብዓተ መሬት ላይ ለመረባረብ የቆረጡት ዕድሮች ያካበቷቸውን ልምዶች በፎቶግራፍና በሠነድ አስደግፈው በተራ በተራ በርቱዕ አንደበት ለታዳሚው ማካፈል ጀመሩ፡፡ ሁሉም ጆሮውን ሰጥቷል፤ ባየውና በሰማው መደሰቱንና አድናቆቱን ይገልጻል፤ ተጨማሪ ማብራሪያ የፈለገ ይጠይቃል፤ ሌላው ዐውዱን በፎቶ ግራፍና በተንቀሳቃሽ ምሥል ለማስቀረት ይጣጣራል ወዘተ. ብቻ ከአንድ ነጭ ድንኳን ወደ ሌላ ነጭ ድንኳን ሲታለፍ ሌላ ቁም ነገር፣ ሌላ ስኬት፣ ሌላ መደመም!
ክብርት ወ/ሮ ዘውድነሽ አሰፋ ዐውደ ርዕዩን አስመልክተው ሲናገሩ “መርሀ-ግብሩ ህብረተሰቡን ማዕከል ያደረገ ሰፊ ሕዝባዊ መሠረት ያለው የልማት ሥራ በሁሉም የአገሪቱ ክፍሎች እንዲሰራጭ ልዩ ዕድል ይፈጥራል” ሲሉ አድናቆታቸውን ገልጸዋል፡፡ የማህበራቱ ተወካዮችም ይህንኑ መስክረዋል፡፡ “ተረጂዎችን በተናጠል ከመደገፍ ይልቅ ዘላቂነት ባለው መልኩ ራሳቸውን ችለው እንዲንቀሳቀሱ በቡድን በማደራጀት የገቢ ምንጫቸውን እንዲያዳብሩ ለማስቻል በሌሎች ማህበራት የሚደረገውን ጥረት ተምረን በሥራ ላይ ለማዋል አስበናል” በማለት የጋይንት ንፋስ መውጫ ከተማ የዕድሮች ህብረትን ወክለው የተገኙት አቶ መቆያ ፈንቴ የክብርት ወ/ሮ ዘውድነሽን ሀሳብ ያጠናክራሉ፡፡
በዐውደ ርዕይው የተደመሙትና ከማህበራቱ በርካታ ተሞክሮ የተቋደሱት የበዓሉ ታዳሚዎች በባህላዊ ጭፈራ እየተዝናኑ አጠር ያለ የሻይ እረፍት ካደረጉ በኋላ ወደተንጣለለው የማዕከሉ አዳራሽ በመከተት ወደተከታዩ መርሀ-ግብር ተሸጋገሩ፡፡
ከጥቂት ክንውን በኋላም ሁሉንም ያስጨበጨበ የምሥራች ከማህበራቱ ዘንድ ተሰማ፡፡ ባለፈው አንድ ዓመት ጊዜ ውስጥ ብቻ
ለ5,974 ለችግር የተጋለጡ ህፃናት የተቀናጀ ድጋፍ በመስጠት፣
ለ4,670 ለችግር የተጋለጡ ህፃናት አሳዳጊዎች፣ ቤተሰቦች እና ሴቶች የኑሮ ማሻሻያ ድጋፍ በመስጠት፣
ለ956 ለችግር የተጋለጡ ወጣቶች የሥልጠናና የሥራ ፈጠራ ዕድል በማመቻቸት፣ እንዲሁም
1,750 ለሚሆኑ የማህበረሰብ አባላት በዘላቂ የማህበረሰብ ልማት ዙሪያ የግንዛቤ ማስጨበጫ በመስጠት የዜጎች ህይወት እንዲለወጥ ትልቅ ሚና ተጫውተናል፤  ወደፊትም የበለጠ አጠናክረን እንቀጥላለን ሲሉ የኢ/ህ/ማ/ል/ድ አጋር የሆኑ 46 የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት በተወካያቸው አማካይነት ለቤቱ አሳወቁ፡፡
ተከታዩ ዝግጅት የፓናል ውይይት ነበር፡፡ በውይይቱ የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት ለዘላቂ ልማት ያላቸውን አስተዋፅኦ ዙሪያ የተካሄደ የዳሰሳ ጥናት ግኝት ላይ ሰፊ ውይይት ተካሂዷል፡፡ እንደጥናቱ ከሆነ  ተቋማቱ በዘላቂ ልማት ውስጥ ያላቸው ሚና እንደማያጠያይቅ እና ለዚህም ያበቃቸው አደረጃጀታቸውና አሠራራቸው ሕዝባዊ መሠረት ያለው መሆኑ፤ አመራራቸው በበጎ ፈቃደኞች መሸፈኑ እና ከመንግሥትና ከሕግ አስፈፃሚ አካላት ጋር ያላቸው ትብብርና ትሥሥር ተጠቃሽ ናቸው፡፡
እንዲያም ሆኖ የጥናቱ ሌላ ገፅታ የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት ግሥጋሤ ከተግዳሮቶች የፀዳ አለመሆኑን አሳይቷል፡፡ በበጎ ፈቃደኝነት የሚያገለግሉ ተተኪዎችን የማፍራት ሥራ ከፍተኛ ጥረት መጠየቁ እና የግል ባለሀብቶችን በማስተባበር ሀብት የማሰባሰቡ ሥራ በስፋት አለመሠራቱ በዚህ ረገድ ከተነሱት ዋና ዋና ነጥቦች መካከል ናቸው፡፡  ከዚህ ባሻገር ከተለያዩ አካላት ጋር ያለውአጋርነት፣ አዎንታዊ የሆነ አስተሳሰብ ለውጥ ማስፈን እና ከከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ጋር መቀናጀት በማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት አማካይነት ዘላቂ ልማትን ለማምጣት የሚያስችሉ ጠቃሚ መሣሪያዎች እንደሆኑ በውይይቱ ተመላክተዋል፡፡
በውይይቱ ከተሠነዘሩና ማህበራቱን በእጅጉ ካበረታቱ ሀሳቦች መካከል ተጠቃሽ የሚሆነው የተከበሩ አቶ ታጠቅ አምሳሉ፣ የደብረ ብርሃን ከተማ ከንቲባ ቃል ነው፡፡ “ዘላቂ ልማት በመንግሥት ብቻ አይመጣም” በማለት የጀመሩት ክቡር ከንቲባው “የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት የመንግሥት የልማት አቅሞች እንደመሆናቸው መጠን መንግሥት ተቋማቱን በቅርበት ማወቅና ማገዝ ያስፈልጋል” ብለዋል፡፡ አክለውም “ማህበራቱን ከማወቅ በዘለለ የሚጎላቸውን ለይቶ አውቆ ያንን ክፍተት በመሙላት በኩል ከህበረተሰቡና ከመንግሥት ብዙ ይጠበቃል” ብለዋል፡፡ በመንግሥት የልማት ዕቅዶች ውስጥ የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማትን ፍላጎትና ያልተነካ አቅም ማካተትና መጠቀም አስፈላጊ እንደሆነ ከንቲባው ሳይጠቁሙ አላለፉም፡፡በዓሉ ከመጠናቀቁ በፊት የተከናወነው ሌላ ቁም ነገር 60 ለሚሆኑ የነቃ የልማት ተሳትፎ ላደረጉና 7 የተሻለ አፈፃፀም ላስመዘገቡ የማህበረሰብ ምሥርት ተቋማት እውቅናና የማበረታቻ ሽልማት መስጠት ነው፡፡ በመጨረሻም አዘጋጆቹም ሆኑ ተጋባዦች ሁሉም ባዩትና በሰሙት ረክተው፣ የገበዩትንም እውቀት ለነገአቸው ሰንቀው በታላቅ ቁርጠኝነት ተሰነባበቱ፡፡ ማን ነበር “ነገ ዛሬ ጠንክረው ለሠሩት ነው” ያለው?

   ተቀማጭነቱ በእስራኤል የሆነው ሹራት ሃዲን የተባለ የመብቶች ተሟጋች ቡድን በቅርቡ በፍልስጤም ከተከሰቱ የሽብር ጥቃቶች ጋር በተያያዘ በታዋቂው የማህበራዊ ድረገጽ ፌስቡክ ላይ የአንድ ቢሊዮን ዶላር ካሳ የሚጠይቅ ክስ መመስረቱን አሶሼትድ ፕሬስ ዘገበ፡፡
በሽብር ጥቃቶች የተገደሉ አሜሪካውያን ግለሰቦችን ቤተሰቦች በመወከል ክሱን የመሰረተው ቡድኑ፣ የማህበራዊ ድረገጹ የአሜሪካን የጸረ ሽብር አዋጅ በመጣስ ለሽብርተኞች የጥፋት መልዕክቶችን ማሰራጫ መንገድ ሆኖ አገልግሏል በሚል ፌስቡክን ለደረሰው ጥፋት ተጠያቂ ማድረጉን ዘገባው ገልጧል፡፡
የመብት ተሟጋች ቡድኑ ሃማስን የመሳሰሉ ቡድኖች አዳዲስ አባላትን እንዲመለምሉ፣ ጽንፈኛ አመለካከቶቻቸውን እንዲያራምዱና ለሽብር ለሚያሰማሯቸው ታጣቂዎች መመሪያ እንዲያስተላልፉ ምቹ ዕድል ፈጥሯል በሚል ባለፈው ሰኞ በኒውዮርክ በሚገኝ ፍርድ ቤት በፌስቡክ ላይ ክሱን እንደመሰረተ ተነግሯል፡፡
ቡድኑ በመሰረተው ክስ ላይ የተጠቀሱት የሽብር ጥቃት ሰለቦች የሆኑ አምስት ቤተሰቦች ሁሉም አሜሪካውያን እንደሆኑ የጠቆመው ዘገባው፣ ከእነዚህም መካከል ባለፈው መጋቢት ወር ላይ እስራኤልን ሲጎበኝ በፍልስጤማውያን ጥቃት የተገደለው ቴለር ፎርስ የተባለው የ28 አመት አሜሪካዊ ቤተሰቦች እንደሚገኙበት አክሎ ገልጧል።

     አለማቀፉ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት በዘር ማጥፋት ወንጀል የከሰስኳቸውንና የእስር ትዕዛዝ ያወጣሁባቸውን የሱዳኑ ፕሬዚዳንት አልበሽርን በቁጥጥር ስር አላዋሉም በሚል በጅቡቲና በኡጋንዳ መንግስታት ላይ ወቀሳ ማሰማቱን አሶሼትድ ፕሬስ ዘገበ፡፡
ፕሬዚዳንት አልበሽር ባለፈው ግንቦት ወር ወደ ሁለቱ አገራት አምርተው እንደነበር ያስታወሰው ዘገባው፣ ፍርድ ቤቱም የአገራቱ መንግስታት ይህን መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ፕሬዚዳንቱን በቁጥጥር ስር አላዋሉም ሲል ባለፈው ማክሰኞ ለተባበሩት መንግስታት ድርጅት የጸጥታው ምክር ቤት መውቀሱን ገልጧል፡፡
ፍርድ ቤቱ የጦር ወንጀልና ኢ-ሰብዓዊ የወንጀል ተግባራትን መፈጸም የሚሉ ሁለት ክሶችን በ2009 አልበሽር ላይ መመስረቱንና ከአንድ አመት በኋላም የዘር ማጥፋት የሚል ተጨማሪ ክስ መመስረቱን ያስታወሰው ዘገባው፣ ፍርድ ቤቱ በፕሬዚዳንቱ ላይ የእስር ትዕዛዝ ቢያስተላልፍም አንድም አገር ተፈጻሚ እንዳላደረገው ጠቁሟል፡፡ ፍርድ ቤቱ ፕሬዚዳንት አልበሽርን ለማሰር ፈቃደኞች አልሆኑም በሚል ተመሳሳይ ወቀሳዎችን ሲያሰማ መቆየቱን ያስታወሰው ዘገባው፤ ባለፈው ሰኔ ወር ላይም የፍርድ ቤቱ ዋና አቃቤ ህግ አልበሽርን አናስርም ባሉ አገራት ላይ እርምጃ አልወሰደም በሚል በተመድ የጸጥታው ምክር ቤት ላይ ትችት መሰንዘራቸውንም አክሎ ገልጧል፡፡


ቴለር ስዊፍት በ12 ወራት 170 ሚ. ዶላር በማግኘት ትመራለች
    ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት በ2016 ከፍተኛ ገቢ ያገኙ የዓለማችን 100 ዝነኞችን ዝርዝር በሳምንቱ መጀመሪያ ይፋ ያደረገ ሲሆን አለማቀፍ ዝናን ያተረፈቺው ድምጻዊቷ ቴለር ስዊፍት ባለፉት 12 ወራት 170 ሚሊዮን ዶላር ገቢ በማግኘት በዝርዝሩ የመጀመሪያውን ደረጃ ይዛለች፡፡
ድምጻዊቷ በአመቱ ያከናወነቺው 1989 የተባለ አለማቀፍ የሙዚቃ ጉዞ ከፍተኛ ገቢን እንዳስገኘላት የጠቆመው ፎርብስ፤በማስታወቂያና በሌሎች መንገዶች ያገኘቺው ገቢ ተደምሮ በአመቱ ከፍተኛ ገቢ ያገኘች ቁጥር አንድ የዓለማችን ዝነኛ እንዳደረጋት ገልጧል፡፡ዋን ዳይሬክሽን የተባለው የሙዚቃ ቡድን በ110 ሚሊዮን ዶላር ሁለተኛ ደረጃን ሲይዝ፣ ታዋቂው ደራሲ ጄምስ ፓተርሰን በ93 ሚሊዮን ዶላር ሶስተኛ ደረጃ ላይ መቀመጡን የገለጸው ፎርብስ፤ ዶክተር ፊል ማክግሮው በ88 ሚሊዮን ዶላር፣ ፖርቹጋላዊው የእግር ኳስ ኮከብ ክርስቲያኖ ሮናልዶ በ88 ሚሊዮን ዶላር የአራተኛና የአምስተኛ ደረጃ መያዛቸውን አስታውቋል፡፡
በዘንድሮው የፎርብስ ዝርዝር ውስጥ ድምጻውያን፣ የፊልም ተዋንያን፣ ኮሜዲያን፣ አትሌቶች፣ የእግር ኳስ ተጫዋቾችና በሌሎች ዘርፎች ታዋቂ የሆኑ የአለማችን ዝነኞች የተካተቱ ሲሆን እነዚህ 100 ዝነኞች ከሰኔ ወር 2015 እስከ ሰኔ ወር 2016 ባለው ጊዜ ውስጥ በድምሩ 5.1 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ማግኘታቸው ተነግሯል፡፡
በፈረንጆች አመት 2015 በዝርዝሩ ውስጥ ተካተው የነበሩ 34 የዓለማችን ታዋቂ ግለሰቦች፣ በዘንድሮው ዝርዝር ውስጥ ለመካተት በለስ እንዳልቀናቸው የጠቆመው ፎርብስ፤ ከእነዚህም መካከል ታዋቂዎቹ ድምጻውያን ሌዲ ጋጋ እና ጀስቲን ቲምበርሌክ እንደሚገኙበት አስታውቋል፡፡
እስከ 20ኛ ባለው ደረጃ ከተቀመጡት የአለማችን ታዋቂ ድምጻውያን መካከል በ80 ሚሊዮን ዶላር 9ኛ ስፍራን ያያዘቺው አዴል፣ በ76.5 ሚሊዮን ዶላር 12 ደረጃን የያዘቺው ማዶና እና በ75 ሚሊዮን ዶላር 13ኛ ደረጃን የያዘቺው ማዶና ይገኙበታል፡፡

    ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ሰው በጠና ታመመና አልጋ ላይ ዋለ፡፡ በየጊዜው እየሄደ ዶክተሮች ያነጋግራል፡፡
1ኛው ሐኪም - “አይዞህ ቀላል ነው፡፡ ለክፉ አይሰጥህም” አለው፡፡
ህመምተኛው - “ዕውን ሐኪም በዚህ ተፅናንቼ ልቀመጥ?”
1ኛው ሐኪም - “እርግጡን ነው የነገርኩህ”
ህመምተኛው - “እንዳፍዎ ያድርግልኝ!”
ግን አያርፍም ህመምተኛው - ወደ ሁለተኛው ዶክተር ይሄዳል፡፡  
ሁለተኛው ሐኪም - “ምንም ችግር የለብህም፤ አሁን የያዘህ በሽታ በረዥም ጊዜ የሚድን ስለሆነ ብቻ ነው አልጋ መያዝ ያስፈለገህ”
ህመምተኛው - “ቃልዎትን አምኜ ዝም ብዬ ልተኛ ሐኪም?”
ሁለተኛው ሀኪም - “እቺን ታክል አትጠራጠር!”
ህመምተኛው - “እንዳፍዎ ያድርግልኝ!”
ወደ ሶስተኛው ሀኪም በሚቀጥለው ቀን ይሄዳል፡፡
ሶስተኛው ሐኪም - ከሁሉም የተለየ ነገር ነው የነገረው፡፡
“ወዳጄ የያዘህ በሽታ ፈፅሞ ጊዜ የሚሰጥ አይደለም፡፡ እንዲያውም ሀያ አራት ሰዓት ለመቆየት መቻልህን እጠራጠራለሁ፡፡ ስለዚህ ምንም አላደርግልህም”
ህመምተኛው አመስግኖ ሄደ፡፡
ሁኔታው ሶስተኛው ሐኪም እንዳለው ሳይሆን ቀረ፡፡ ሰውየው ከቀን ቀን እየተሻለው መጣና በጥቂት ሳምንታት ውስጥ ካልጋው ተላቆ ቆሞ መሄድ ቻለ፡፡ በእርግጥ ግን ህመሙ ብዙ ስጋውን ስለበላው በአፅሙ የሚሄድ ይመስላል፡፡
አንድ ቀን መንገድ ላይ ሶስተኛውን ሐኪም አገኘው፡፡ ሐኪሙ በጭራሽ ያየውን ማመን አልቻለምና፤
“የወዲያኛውን ዓለም አይተህ ተመልሰህ መጥተህ መሆን አለበት፡፡ ለዚህ ጥርጥር የለኝም፡፡ ከዚህ ቀደም ተለይተውን ወደ ሰማይ ቤት የሄዱት ወዳጆቻችን እንዴት ናቸው ባክህ?”
ህመምተኛውም - “እጅግ በጣም ተመችቷቸው፣ ደልቷቸው ነው የሚኖሩት፡፡ ዘለዓለማዊውን ውሃ ጠጥተውና የዓለም ችግር ሁሉ ረስተው፤ በጣም ተመችቷቸው ይኖራሉ፡፡ በነገራችን ላይ እኔ ከዛ ለቅቄ እየመጣሁ ሳለሁ ምድር ላይ ባሉ ዶክተሮች ላይ ፍርድ ለመስጠት እየተዘጋጁ ነበር፡፡ ያስቀመጡት ምክንያት ህመምተኛ ሰዎች በተፈጥሮአዊ መንገድ እንዳይሞቱ ጥበብ እየተጠቀሙ በህይወት እንዲቆዩ በማድረጋቸው ነው፡፡ አንተንም ከሌሎቹ ጋር እንደሚቀጡህ ሲያስቡ ነበር፡፡ እኔ ግን እሱን ተዉት፤ ምክንያቱም እሱ አባይ ጠንቋይ እንጂ ዶክተር አይደለም አልኳቸው!”
*              *           *
ውሸተኛ ዐባይ ጠንቋዮች እየበዙ፣ ዕውነተኛ ዶክተሮች እየሳሱ ከመጡ አገራችን አደጋ ላይ ናት! ዐባይ መምህራን እየበዙ ዕውነተኛ መምህራን ከተመናመኑ የትምህርት ነገር አዲዮስ! የሚባል ይሆናል! ዐባይ ጠበቆችና ዐባይ ዳኞች ከተበራከቱና ዕውነተኛ ዳኞችና ሀቀኛ ጠበቆች ከጠፉ “O! Justice thy has flown to beasts!!” (ፍትሕ ሆይ! ወደ አራዊት በረርሽን!) እንዳለው ሼክስፒር ይሆናል፡፡ ግልፅነትና ተጠያቂነት ለአፍ አመል ብቻ እየተስፋፉ በተግባር ግን ሁሉ ድብቅ፣ ሁሉ የአዋቂ አጥፊ እየሆነ የሚገኝ ከሆነ፤ የለበጣ ዲሞክራሲ እንጂ ሌላ የለም፤ ሃሳዊ መብት እንጂ ለዕድገት የቆመ ሀቀኛ ሥርዓት አይኖርም፡፡ የካብነው እየተናደ፣ አደግን ያልነው ቁልቁል እየሔደ፤ በየቀኑ በችግር ማጥ ውስጥ መላሸቃችን አሳዛኝ ነው! የግል ት/ቤቶች ዕውቅናና ፈቃድ አስቂኝ  ደረጃ ላይ ደርሷል! የት/ቤቶች ተቋማት ዕድሳት ዘወትር በማስጠንቀቂያና በማስፈራሪያ የሚታለፍ የመስፈራሪቾ (Scare-crow) ሂደት ሆኗል፡፡ ሥርአተ- ትምህርት አደረጃጀቱን ማጥራት እንዳቃተው ከረመ! የግብዓት አቅርቦትና አገልግሎት እንከን አልባ ለመሆን አልታደለም! የዝውውር ፖሊሲ እንደተሽመደመደ ነው፡፡ የመረጃ አያያዝ የተቆጣጣሪ ያለህ! እያሰኘ ነው፡፡ በት/ቤት ተቋማት ውስጥ ‹‹በአጋዥ መፃሕፍት› ሰበብ ያለንግድ ፈቃድ የችብቸባ ሥርዓት መፈጠር ዘግናኝ ዕውነት ነው፡፡ የወላጆች አቤቱታ የምድረ ባዳ ጩኸት ሆኗል (Crying in the Wilderness)፡፡ የዚህ ሁሉ ውጤት የሆነው የፈተና ብቃት አለ ወይ? ብለን ገና መልስ ሳናገኝ፤ የፈተና ስርቆሽ አደጋ አናታችን ላይ ያንዥብባል? ያውም ኢንተርኔት እስከማዘጋት የደረሰ የሌብነት መንግሥታዊ ሥጋት … ይህ ሁሉ ሲታይ እንዴት ሚሥጥራችን በሀገር ደረጃ ይጠበቃል? ብለን ዕምነት እንጣል፡፡ ዕምነት ማጣት ያለመረጋጋት እናት መሆኑን እንርሳ!
ችግሮችን የመፍታት መንገዳችን ወይ መንገድ አደለም፤ ወይ ወልጋዳ መንገድ ነው፡፡ ይህ ማለት ችግርን ለመፍታት ሌላ ችግር መንገድ ነው፡፡ ይህ ማለት ችግርን ለመፍታት ሌላ ችግር መቀፍቀፍ ነው፡፡ ችግር በችግር አይፈታም፡፡ ዘላቂ መፍትሔ በማይሆን መልኩ ጥገናዊ ማስታመሚያዎች ብንደረድር ቁስላችን ማመርቀዙ አይቀሬ ነው፡፡ ውስጣችን መፈተሽ አለበት፡፡ አንዱ ባንዱ ላይ በማላከክ ሳይሆን ዕውነተኛውን በሽታ ፈልቅቆ በማውጣት ነው ህክምናችን የተሳካ የሚሆነው፡፡ አለበለዚያ፤ አንደኛው ሀኪም ቀላል ነው፤ ሁለተኛው ሀኪም በረዥም ጊዜ የሚድን በሽታ ነው፤ ሦስተኛ ሀኪም- ሀያ አራት ሰዓት አትቆይም! አይነት መፍትሔ ይዘን እንደ አፍዎ ያርግልኝ እያልን በጥንቆላ የምንተዳደር ሊመስለን አይገባም፡፡ በሽታችን የሚወሳሰበው ጊዜ ወስደን በጥሞና ስለማንከታተለው ነው፡፡ የበሽታችንን መንስዔ ከስር መሰረቱ ለማወቅ፣ አካሚውም ታካሚውም ግልፅነት ስለሌለን ነው፡፡ በሽታውን የደበቀ መድሀኒት አይገኝለትም የሚለው ዕውነት እንዳለ ሆኖ፤ መድህን አያገኝም የሚለው ታክሎብናል፡፡ የመጨረሻው አሳሳቢ ነገር ደግሞ ትክክለኛውን መረጃ አለማግኘት ነው፡፡ ይህ እክል አንድም ከመረጃ ሰጪ ንፉግነት የሚመነጭ ነው፡፡ አንድም የመረጃ ሥርዓቱ ብቃት ማጣትና ይሆነኝ ተብሎ እንዲጥመለመል ማድረጉ ነው፡፡ አሊያም ጨርሶ ለመረጃ ፋይዳ ጥረት አለመስጠት ነው! ከሁሉም ይሠውረን፡፡ እጅግ አስከፊው ገፅታችን ግን፤ ‹‹ላም ባልዋለበት ኩበት ለቀማ›› እንዲሆን ካደረግን ነው፡፡ ሆን ብለን መረጃ ካጣመምን ማለትም መረጃ ተቀባይ ትክክለኛውን መረጃ ሳይሆን የተሳሳተውን ወስዶ ሌሎችን እንሳስት አድርገን፤ እኛም መልሰን እሱን ከሳሽ ከሆንን የመርገምት ሁሉ መርገምት ይሆንብናል! እንዲህ ያለውን ሂደት መዋጋት የግድ ነው፡፡ መረጃ፤ መረጃ የሚሆነው ለሚመለከተው ጉዳይ በአግባቡ ሲውል ነው፡፡ አለበለዚያ፤ ‹‹ከአንበሳና ከዝሆን ማን ያሸንፋል?›› ቢለው፤ ‹‹ከሁሉም ከሁሉም አሳ ሙልጭልጭ ነው!›› የሚለውን ተረት ስናደምቅ መኖራችን ነው!

“መንግስት እንደፈለገ ያድርገን ብለን ቁጭ ብለናል”

   በነፋስ ስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ ወረዳ 1 ልዩ ስሙ ‹ማንጎ› የተባለው አካባቢ፣በቤት ፍርስራሾች ተሞልቷል፡፡ ቦታው በጦርነት ወይም በተፈጥሮ አደጋ የወደመ ነው የሚመስለው፡፡  የወዳደቁ የቤት ፍራሽ እንጨቶች፣የተጨረማመቱ የቤት ክዳን ቆርቆሮዎች ለዓይን ይታክታሉ፡፡ በፍርስራሾቹ ጥጋጥጎች ላይ በተጨረማመተቱ ቆርቆሮዎችና በፕላስቲክ የተሰሩ ዳሶች በብዛት ይታያሉ፡፡ በቤቶቹ ፍርስራሾች ላይ ተፈናቃዮች ተጠልለው ይገኛሉ፡፡ ከእነዚህም መካከል አረብ ሀገር ሰርታ ባጠራቀመችው ገንዘብ ከአርሶ አደር ላይ ቦታ ገዝታ ባለ 3 ክፍል ቤት በመሥራት፣ ላለፉት 10 ዓመታት በቦታው ላይ መኖሯን የምትናገረው ወጣት ትገኝበታለች፡፡  
  ባለትዳርና የአንድ ልጅ እናት ስትሆን፤ ቤቷ ከፈረሰ በኋላ ከእነቤተሰቦቿ እዚያው ፍርስራሹ ላይ በፕላስቲክና በቀዳዳ ቆርቆሮ ከለላ ሰርታ መጠለሏን ገልጻልናለች፡፡   
በህይወቴ እንዲህ ያለ ምስቅልቅሎሽ አጋጥሞኝ ቀኑ ይጨልምብኛል፣ መግቢያ አጣለሁ ብዬ አስቤ አላውቅም ነበር የምትለው ወጣቷ፤መሄጃ አጥቼ ከእነልጄ ጭቃ ላይ እየተንከባለልኩ ነው የማድረው ብላለች-ግራ በመጋባት ስሜት ተውጣ፡፡ በዳስዋ ውስጥ ለአፍታ በነበረን ቆይታ ጥቂት ጥያቄዎችን አቅርበንላት መልስ ሰጥታናለች፡-
 ይሄ ሁሉ ቤት በስንት ቀን ነው የፈረሰው?
በአንድ ቀን ነው ያፈረሱት፡፡
አስቀድሞ ይፈርሳል ተብሎ ተነግሯችሁ ነበር?
እኛ አካባቢ ይፈርሳል የሚል ወሬ ፈፅሞ አልሰማሁም፡፡ የሰማሁት ኤራኤልና፣ ጨሬ ቀርሳ ነው፡፡ ግን ሳናስበው ያንን አጋጣሚ ተጠቅመው የኛንም አፈረሱብን፤መግቢያ አሳጡን፡፡
ቤታችሁ ከፈረሰ በኋላ ያነጋገራችሁ የመንግስት አካል አለ?
ማንም ያነጋገረን አካል የለም፡፡ እናንተ ናችሁ ለመጀመሪያ ጊዜ መጥታችሁ የጠየቃችሁን፤ሌላ ዞር ብሎ ያየን የለም፡፡ ሀገር እንደሌለን ሜዳ ላይ ስንወድቅ የጠየቀን ማንም የለም፡፡
እናንተስ ---- ለመንግስት አቤቱታ ለማቅረብ አልሞከራችሁም?
እኛማ ማጣፊያው አጥሮናል’ኮ! የት ብለን ማንን እንጠይቅ፡፡ በቃ የሆነውን እንሁን ብለን እዚችው የቤቷ ፍራሽ ላይ ቀርተናል፡፡ ለራሴም ቤት ሰርቼ፣ አንድ ሁለት ክፍል ሰርቪስ ቤቶች ከጎን ቀጥዬ እያከራየሁ ገቢ አገኝ የነበረው ቀርቶ፣ዛሬ ይኸውና ለራሴም መጠለያ የሌለኝ ሆኛለሁ፡፡ ሀብት ንብረቴ ሁሉ ወድሟል፡፡
አሁን በምንድን ነው የምትተዳደሪው?
ቤቱ ከፈረሰ በኋላ ምንም ገንዘብ የማገኝበት ነገር የለም፤ሰው እየረዳኝ ነው የምኖረው፡፡
የሚከራይ ቤት ለማግኘት አልሞከራችሁም?
እኔ እዚህ ምንም ዘመድ የሌለኝ ሰው ነኝ፡፡ ማን ጋ ልጠጋ? ቤት ተከራይቼ እንዳልኖር ትንሹ የቤት ኪራይ 1500 ብር ነው፤ ከየት አመጣለሁ? ምንም ገቢ የማገኝበት ነገር የለኝምኮ! አቅሜ አይፈቅድም፡፡ በቃ ባዶዬን ቀርቻለሁ፡፡
መንግስት ምን እንዲያደርግ ነው የምትፈልጉት?
 ቦታውን እፈልገዋለሁ ብሎ እንዲህ ካደረገን በኋላ ምንም ማድረግ አንችልም፡፡ እኛም የዚህች ሀገር ዜጎች ነንና ያስብልን፡፡ ለዚህች ሀገር ልማት እናዋጣ የነበርን ዜጎች ነን፡፡ መንግስትን ምን በደልነው? ልጆቻችንስ በልጅነት አይምሮአቸው ለምን ይጎዱ፡፡
 ልጆቼ እየተሳቀቁ የሚበሉት አጥተው እየተቸገርን ነው፡፡ ወንድሜ እስቲ ንገረኝ ---- የገቢ ምንጭ ከወደመ በኋላ ይህችን ልጅ ምን ላብላት? … ዘንድሮ በኔ የመጣ ቁጣ እንዲህ ነው ተብሎ አይነገርም፡፡
“ከጅብ ጋር እየተፋጠጥን ነው የምናድረው”
አንዱ በአንዱ ላይ የተደረማመሱትን ቤቶች እየተመለከትን፣ከአንደኛው የቤት ፍራሽ ጥግ ላይ ወደተቀለሰች ዳስ አመራን፡፡ በዳሱ ውስጥና በራፉ ላይ አራት ሰዎች ቁጭ ብለው ቡና እየጠጡ ነበር፡፡ ጎራ ብለን ማነጋገር ጀመርን፡፡
ቤታችሁ ከፈረሰ በኋላ በእንዲህ ያለ ሁኔታ እዚህ ለመኖር ለምን መረጣችሁ? ቤት ተከራይታችሁ አትኖሩም?
(ከመካከላቸው አንደኛው በፍጥነት ምላሽ መስጠት ጀመረ …)
እየውላችሁ ወንድሞቼ---እኛ የቀን ሰራተኞች ነን፤ ከተማ ገብተን በ4ሺ እና 5ሺህ ብር ቤት ለመከራየት ይቅርና ለእለት ጉርሳችንም ስንቸገር የኖርን ነን፡፡ በምን አቅማችን ነው ቤት የምንከራየው?
በፊት በምን ነበር የምትተዳደሩት?
አንድና ሁለት ክፍል ቤት ከመኖሪያ ቤታችን ጎን ቀጥለን እየሰራን፣እያከራየንም ገቢ እናገኛለን፡፡ አብዛኞቻችን የቀን ሰራተኞች ነን፡፡ እኔ የምሰራው ድንጋይ ፈላጭነት ነው፡፡ ኮብልስቶንም እንሰራለን … በዚህ ነው የምንተዳደረው፡፡
ቦታውን ከአርሶ አደር ላይ ስትገዙ ህገወጥ መሆኑን አታውቁም ነበር?
በወቅቱማ ማንም አልተቃወመንም፡፡ አንድም ቀን ህገ-ወጥ ናችሁ ተብለን አናውቅም፡፡ ቤት ስንሰራ ደንቦች ይመጣሉ፤ግን አፍርሱ አይሉንም ነበር፡፡ አሁን እንኳ ሊፈርስብን ሰሞን መንገድ ለመስራት ባዋጣነው ገንዘብ፣የፍሳሽ ማስወገጃ ቱቦ ተገዝቶ ሊቀበር በዝግጅት ላይ ነበር፡፡ ገንዘብ አዋጡ ተብለን እያዋጣን መብራት፣ መንገድ፣ ውሃ አስገብተናል፡፡
ውሃ በየግቢያችን እንዲገባ የተላከ ከወረዳው በማህተም የተደገፈ ወረቀት አይተናል፡፡ ለልማት 9 ሚሊዮን ብር ያስፈልጋል ተብለን ስናዋጣ ነበር፡፡
 ይሄን ሁሉ ስናለማ ዝም ብለውን፣ ዛሬ አንገታችንን ቀና አደረግን ስንል፣እንዲህ መልሶ ቅስማችንን የሚሰብረን መንግስት ምን አድርገነው ነው? ምን በድለነው ነው? ለአንድ ቀን እንኳ ማስጠንቀቂያ ቢሰጠን ምን አለበት?
ከመፍረሱ በፊት እቃችሁን አውጥታችሁ ነበር?
ድንገት እኮ ነው ማፍረስ የጀመሩት፡፡ የቻልነውን አትርፈናል፡፡ ብፌ፣ ሶፋ ግን እንዳለ ወድሞብናል፡፡
ለምን እቃችሁን ለማውጣት አልቻላችሁም?
ማን ያውጣው!? ወንዶቹን እየለቀሙ ነው ያሰሩት፤ግማሹ ሸሽቶ ከአካባቢው ራቀ፡፡ ሴቶች ብቻ ነበሩ የቀሩት፡፡ በዚያ ላይ 8 ማሽን ነበር ቤቱን ሲያፈርስ የነበረው፡፡ አካባቢው በአቧራ ታጥኖ … ሁኔታው ሁሉ አስፈሪ ነበር፡፡ እንዲህ እንደሚወራው ቀላል እደለም፡፡
አሁን እንዴት ነው የምትኖሩት?
ይኸው እንደምታዩት ጭቃ ላይ ፍራሽ አንጥፈን ነው የምንተኛው፡፡ አሁን የምንጠጣውን … ቡና ዘመድ ነው ያመጣልን፡፡ ልጆቻችን ተበታትነዋል፡፡
 ሁላችንም ዘመድ ከምናስቸግር ብለን በየቦታው በትነናቸው ነው እኛ እዚሁ የቀረነው፡፡ ት/ቤት ሄደው እስኪመጡ የማናምናቸው ሰዎች ዛሬ ምን ይሁኑ አናውቅም፡፡
ያነጋገራችሁ የመንግስት አካል የለም?
ማንም ዞር ብሎ ያየን የለም … ወገን እንደሌለን ሜዳ ላይ ቀርተናል፡፡
(አባወራዎቹ ቦታውን አንዱን ካሬ ሜትር በ100 ብር ሂሳብ እንደገዙት ይናገራሉ፡፡)
ለወደፊት ተስፋ የምታደርጉት ምንድን ነው?
ምን ተስፋ አለን?! ምንም ተስፋ የለንም፤መሄጃ የለንም፡፡ እንደሚባለው ትርፍ ቤት ቢኖረን እዚህ ቦታ ውሃና ጭቃ ላይ አንተኛም ነበር፡፡ መንግስት እንደፈለገ ያድርገን ብለን ቁጭ ብለናል፡፡




    ኢየሩሳሌም የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት፤ የማህበረሰብ ምስረታ ተቋማት የመልካም ተሞክሮ ቀን በዓል አከበረ፡፡ ድርጅቱ ሰሞኑን በቢሾፍቱ ከተማ ውስጥ በሚገኘውና የጄክዶ አፖርቹኒቲ ፎር ቼንጅ እየተባለ በሚጠራው የስልጠና ማዕከሉ ውስጥ ባከበረው በዚሁ የመልካም ተሞክሮ ቀን ክብረ በዓል ላይ የማህበረሰብ ምስርት ተቋማቱ ተወካዮች ተገኝተው ከድርጅቱ ጋር በማከናወን ላይ ስለሚገኙት የልማት ስራዎች ገለፃ አድርገዋል፡፡ “የማህበረሰብ ምስርት ተቋማት አጋርነት ለዘላቂ ልማት” በሚል መሪ ቃል በተከናወነው በዚህ የመልካም ተሞክሮ ቀን በዓል ላይ ተሞክሮአቸውን ለማካፈል ከተገኙት የማህበረሰብ ምስርት ተቋማት መካከል ዕድሮች፣ ማህበራትና የልማት ድርጅቶች ይገኙበታል፡፡ የእየሩሳሌም የህፃናትና ማህበረሰብ ልማት ድርጅት ዋና ሥራ አስፈፃሚ አቶ ሙሉጌታ ገብሩ በዚህ ወቅት እንደተናገሩት፤ ድርጅቱ በተለያዩ የአገሪቱ ክልሎች ውስጥ ከሚገኙ ከ140 በላይ የማህበረሰብ ምስርት ተቋማት ጋር በአጋርነት የሚሰራ ሲሆን በተለያዩ የልማት መስኮች በሺዎች የሚቆጠሩ ተጋላጭ የህብረተሰብ ክፍሎችን ተጠቃሚ ያደረጉ ስኬታማ ስራዎችን አከናውኗል ብለዋል፡፡

     የአርጀንቲናው አሊሚኔተር ግሩፕ የቬንዳኖቫ ምርት የሆነውና ላለፉት አራት ዓመታት በአርጀንቲና ጥቅም ላይ የዋለውን ጥርስን ያለ መቦርቦሪያ ድሪልና ያለ ማደንዘዣ አፅድቶ የሚሞላው መሳሪያ ሰሞኑን አገራችን ገባ፡፡ በዓለም ጤና ድርጅት እውቅና የተሰጠውና በጤና ጥበቃ ሚኒስቴር አገር ውስጥ ጥቅም ላይ እንዲውል ፈቃድ የተሰጠው ይሄው መሳሪያ ከተፈጥሮአዊ እፅዋት በሚሰራ ጄል ያለ ማደንዘዣና ያለ ድሪል ጥርስን በማፅዳት የሚሞላ ሲሆን አንድ ሰው በ10 ደቂቃ ውስጥ ጥርሱ ፀድቶና ተሞልቶ ወደቤቱ እንዲሄድ የሚያደርግ ነው ተብሏል፡፡ የአምራች ድርጅቱ ዋና ስራ አስኪያጅ ሚስተር ጆርጅ ሌይንና የኢትዮጵያ ወኪሉ ሚረር ‹ትሬዲንግና ሰርቪስ› ዋና ስራ አስኪያጅ አቶ ተስፋየየ ወንድሙ ባለፈው ሳምንት መጀመሪያ በሂልተን ሆቴል  በሰጡት መግለጫ፤ መጀመሪያ ምርቱ በጥርስ ህመም የሚሰቃዩ ህፃናትን ታሳቢ አድርጎ የተሰራ እንደነበርና በአሁኑ ሰዓት አዋቂዎችም በስፋት እየተጠቀሙበት መሆኑን ተናግረዋል፡፡በሁለቱ ኩባንያዎች መካከል በዕለቱ የ50 ሚ. ዶላር ስምምነት የተደረገ ሲሆን መሳሪያውን በዋና በወኪልነት ሚረር ትሬዲንግና ሰርቪስ እንደሚያከፋፍልና ከአርጀንቲና የሀኪሞች ቡድን እንደሚመጣና ለኢትዮጵያዊያን የጥርስ ሀኪሞች ስለመሳሪያው አጠቃቀም ስልጠና እንደሚሰጥ ታውቋል፡፡ አንዱ መሳሪያ ጫፉ እየተቀየረ ለ10 ሰዎች ያገለግላል የተባለ ሲሆን አንድ ሰው በመሳሪያው ታክሞ ለመዳን አምስት ዶላር ብቻ እንደሚያስፈልገው በስምምነቱ ወቅት ተገልጿል፡፡ የመሳሪያው ተፈላጊነት ከጨመረ ፋብሪካው ኢትዮጵያ ውስጥ እንደሚከፈትና ለሌሎች የአፍሪካ አገራትም እንደሚከፋፈል የገለፁት ሚስተር ጆርጅ፣ እስካሁን ከአርጀንቲናና ከሌሎች የላቲን አሜሪካ አገሮች በተጨማሪ ደቡብ አፍሪካም መሳሪያውን በስፋት እየተጠቀመችበት  እንደምትገኝ በዕለቱ ተገልጿል፡፡