Administrator

Administrator

Saturday, 31 December 2016 11:41

የፀሀፍት ጥግ

 - ማንም ሰው እስኪሞት ድረስ ግለ ታሪኩን መፃፍ ያለበት አይመስለኝም፡፡
      ሳሙኤል ጎልድዊን
- የገጣሚ ግለ ታሪኩ ግጥሙ ነው፡፡ የቀረው ሁሉ የግርጌ ማስታወሻ ነው፡፡
      ዬቬጌኒ ዩቭቱሼንኮ
- ‹ህይወቴ› ግለታሪኬ አይደለም፤ ሙዚቃ ነው፡፡
      ሜሪ ጄ. ብሊግ
- ከባለቤቱ ይሁንታ ያላገኘ ግለ ታሪክ እየፃፍኩ ነው።
     ስቲቨን ራይት
- መፅሐፍ አንድም ግለ ታሪክ ነ ው፣ አ ሊያም ረዥም ልብወለድ ነው፡፡
     አይምሬ ኬርቴስዝ
- የወንድ ፊት ግለ ታሪኩ ነው፡ የሴት ፊት የልብ ወለድ ስራዋ ነው፡፡
     ኦስካር ዋይልድ
- የህይወት ታሪክህ ሲፃፍ ብዕሩን ማንም እንዲይዘው አትፍቀድ፡፡
     ሬቤል ትሪቨር
- ይሄ ግለ ታሪኬ አይደለም፡፡ የእስካሁኑን ጉዞዬን ብቻ የሚናገር ነው፡፡
     ሪቱ ቤሪ
- የህይወት ጉዞ አይገመቴ ነው፤ ማንም አስቀድሞ ግለ ታሪኩን ሊፅፍ አይችልም፡፡
     አብርሃም ጆሹዋ ሄሼል
- የህይወት ታሪክህን ስትፅፍ፣ እያንዳንዱ ገፅ ማንም ሰምቶት የማያውቀው ጉዳይ ማካተት አለበት፡፡
     ኤልያስ ካኔቲ

Saturday, 31 December 2016 11:32

የዘላለም ጥግ

 (ዝነኞች በመሞቻቸው ሰዓትየተናገሩት)

- “ወዳጆች ያጨብጭቡ፤ ኮሜዲው አልቋል”
    ሉድዊግ ቫን ቤትሆቨን (ሙዚቃ ቀማሪ)
- “እየሞትኩ ነው፡፡ ለረዥም ጊዜ ሻምፓኝ አልጠጣሁም”
   አንቶን ፓቭሎቪች ቼክኾቭ (ፀሐፊ)
- “ትክክለኛውን ነገር ለመስራት ተጣጥሬአለሁ”
   ግሮቨር ክሌቪላንድ (የአሜሪካ ፕሬዚዳንት)
- “መብራቱን አብሩት፤ በጨለማ ወደ ቤቴ መሄድ አልፈልግም”
    ኦ ኼንሪ (ደራሲ)
- “መብራቱን አጥፉት”
    ቴዎዶር ሩስቬልት (የአሜሪካ ፕሬዚዳንት)
- “ኢየሱስን አየዋለሁ፤ ኢየሱስን ለማየት እሻለሁ”
    ዊትኒ ሂዩስተን (ድምፃዊት)
- “መሞት አልፈልግም” (ሞታ ከመገኘቷ ከ2 ሰዓት በፊት በስልክ የተናገረችው)
    ኤሚ ዋይንሃውስ (ድምፃዊት)
- “ለማንበብ ወደ መታጠቢያ ክፍል እየሄድኩ ነው”
    አልቪስ ፕሪስሊ (ሙዚቀኛ)
- “አያችሁ፤ እንዲህ ነው የምትሞቱት”
    ኮኮ ቻኔል (ፋሽን ዲዛይነር)
- “ለእኔ ጠጡልኝ”
    ፓብሎ ፒካሶ (ሰዓሊ)
- “ዛሬ ማታ በደንብ እተኛለሁ››
    ሔነሪ ፎርድ (የአውቶሞቢል አምራች)
- “ብቻዬን ተዉኝ፡፡ ደህና ነኝ!”
     ባሪ ዋይት (ዘፋኝ)
- “ነገ ፀሐይ ስትወጣ እዚህ አልገኝም”
    ኖስትራዳመስ (ሀኪምና የክዋክብት ተመራማሪ)
- “ከሞት በስተቀር ምንም አልፈልግም”
     ጄን ኦዩስተን (ደራሲ)
- “ሰዓቴ የት ነው ያለው?”
    ሳልቫዶር ዳሊ (ሰዓሊ፣ ፀሐፊና ፊልም ሰሪ)

Saturday, 31 December 2016 11:31

አስገራሚ እውነታዎች!!!

 (ከዝነኞች ህይወት)
ዝነኛው የፊልም ተዋናይ ጃኪ ቻን፤ በ1954 (እ.ኤ.አ) ከድሃ ጥንዶች ነው የተወለደው፡፡ ወላጆቹ ያጡ የነጡ ድሃ ስለነበሩ ለሆስፒታል የሚከፍሉት ገንዘብ አጥተው ልጃቸውን (ጃኪ ቻንን) ለመሸጥ ሁሉ ዳድተው ነበር፡፡ በመጨረሻ ግን ተግተው ሰሩና ለሆስፒታሉ ክፍያ በቂ  ገንዘብ አገኙ፡፡ ዛሬ ጃኪ ቻን የሆሊውድ ተከፋይ ነው፡፡  
ታዋቂው አሜሪካዊ ኮሜዲያን ጂም ኬሪ፤ የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን አቋርጦ የወጣው በ16 ዓመቱ ነበር፡፡ ለምን? ትኩረቱን ኮሜዲ ላይ አድርጎ ለመሥራት፡፡  
“Rocky” የተሰኘውን የፊልም ስክሪፕት የጻፈው ዝነኛው ተዋናይ ሲልቪስተር ስታሎን ነበር- ራሱ። ነገር ግን ስክሪፕቱን ሲጽፍ የሚኖርበት ቤት እንኳን አልነበረውም፡፡ ስክሪፕቱን ከመሸጡ ከአንድ ሳምንት በፊት በጣም ተቸግሮ ውሻውን በ50 ዶላር ሸጧት ነበር፡፡ በኋላ ግን መልሶ ገዛት - በ3ሺ ዶላር!! ገንዘብ ከየት ፈሰሰለት? ከስክሪፕት ሽያጩ ነዋ!!
የፊልም ተዋናዩ ሳን ዊሊያም ስኮት፤ ሴቶች ሲያፍርና ሲሽኮረመም አይጣል ነበር፡፡ እንስቶች በአካባቢው ካሉ በጭንቀት ላብ በላብ ይሆናል። በዚህም የተነሳ 30 ዓመት እስኪሞላው ድረስ የሴት ጓደኛ ወይም ፍቅረኛ አልነበረውም፡፡
የፊልም ተዋናዩ ጃክ ኒኮልሰን፤ ዓይናፋርነት አይነካካውም፡፡ ከልጅነቱ ጀምሮ ያሳደጉት  አያቶቹ ነበሩ፡፡ እሱ ግን እውነተኛ ወላጆቹ እንደሆኑ ነበር የሚያውቀው፡፡ እ.ኤ.አ በ1973 ዓ.ም ከ”ታይም” መፅሄት ጋዜጠኛ የሰማው መረጃ ዱብዕዳ ነው የሆነበት፡፡  “እህቱ” እንደነበረች የሚያውቃት ጁን፤ እውነተኛ እናቱ ሆና ተገኘች። በ37 ዓመት ዕድሜው!! ክፋቱ ደግሞ ይሄን እውነት ከመስማቱ በፊት እናቱም ሴት አያቱም ሞተዋል፡፡  
ጄምስ ቦንድን ሆኖ የሚተውነው የፊልም ባለሙያው ዳንኤል ክሬይግ፤ በትወናው ከፍተኛ ዝናና ተወዳጅነት፣ እንዲሁም በሽበሽ ገንዘብ አግኝቷል፡፡ ይሄ ብቻ ግን አይደለም፡፡ በፊልሙ ላይ ሲተውን የሚያሽከረክራትን Aston Martin የተሰኘች አውቶሞቢል የሚያመርተው ፋብሪካ፤ የህይወት ዘመን ስጦታ (መብት) አሽሮታል፡፡ በማንኛውም ጊዜ ደስ ያለውን መኪና (አስቶን ማርቲን ጨምሮ) አስነስቶ መፈትለክ ነው - በቀሪው ህይወቱ ሁሉ፡፡
“ሚስተር ቢን”ን ሆኖ የሚተውነው እንግሊዛዊው ኮሜዲያን ሮዋን አትኪንሰን፤ እንደ አሜሪካዊው ኮሜዲያን ጂም ኬሪ በ16 ዓመቱ ትምህርት አላቋረጠም፡፡ እንደውም ወደ ትወና የገባው በኤሌክትሪካል ኢንጂነሪንግ የማስተርስ ዲግሪውን ከተቀበለ በኋላ ነው-  ከእንግሊዙ ኒውካስትል ዩኒቨርሲቲ፡፡  

 ከዕለታት አንድ ቀን አንዲት ቀበሮ፣ በአንድ ገበሬ ግቢ እየመጣችና የሚያረባቸውን ዶሮዎች እየሰረቀች በጣም ታስቸግራለች፡፡
ገበሬው ለፍቶ ለፍቶ ለቀበሮ መቀለብ ሲሆንበት፣ ከሚስቱ ጋር ለመማከር ይወስንና፤
‹‹ሰማሽ ወይ ውዴ?››
‹‹አቤት ጌታዬ››
‹‹የዚችን የቀበሮ ነገር ምን ብናደርግ ይሻላል?››
‹እኔም ግራ- እየገባኝ ምን እናድርግ ልልህ ነበርኮ››
‹‹አንቺ ምን አሳብ አለሽ?››
‹‹እኔማ ሠፈሩን እንረብሻለን ብዬ ፈርቼ ነው እንጂ፤ መሳሪያ እያለህ አንድ ቀበሮ መግደል ምን ችግር ነበረው?››
‹‹አይ ያሉትን ይበሉ እንጂ ዕውነትም ጠመንጃዬን ወልውዬ አድፍጩ ብጠብቃት አታመልጠኝም›› አለ ፍርጥም ብሎ፡፡
‹‹ግን  እንዲህ ብናረግስ?››
‹‹ምን?››
‹‹ለሰፈሩ አለቃ ብናሳውቅ? ሰውም ጥይት ሲሰማ እንዳይሸበር፣ ለሊቀ መንበሩ ብንነግር?››
‹‹ደግ ሀሳብ አመጣሽ፡፡ አሁኑኑ እነግረዋለሁ፡፡›› አለና ወደ ሊቀ መንበሩ ቢሮ ሄደ፡፡
ሊቀመንበሩ ግን ሀሳቡን አልተቀበለውም፡፡ ይልቁንም፤
‹‹ለምን በወጥመድ አትይዛትም?›› ሲል ጠየቀው፤
‹‹ወጥመድ የለኝም››
‹‹እኔ እሰጥሃለሁ፡፡››
በዚሁ በወጥመዱ ሀሳብ ተስማሙና፣ በገብሬው ወጥመዱን ተረከበ፡፡
ማታም ቀበሮዋ መግቢያ ላይ ወጥመዱን አስቀመጠና መጠበቅ ጀመረ፡፡ ወጥመዱን ያልጠረጠረችው ቀበሮ ዘው ብላ ገባች፡፡ ተያዘች፡፡
ገበሬው በጣም ተደሰተ፡፡ በምን እንደሚቀጣ ያሰላሰለ ጀመር፡፡ በመጨረሻ…
‹‹እንዲያ ስትጫወትብኝ… እንደከረመች በፍፁም አልምራትም›› አለ፡፡
ከዚያም ጭራዋ ላይ ጭድ አሰረና እሳት ለቀቀባት፡፡ ከወጥመዱ አውጥቶም ወረወራት። ቀበሮም ቃጠሎው ሲበዛባት… በአቅራቢያው ወደሚገኘው የገበሬው የበቆሎ እርሻ ገባች፡፡ በቆሎው የደረሰ አዝመራ ነው፡፡ በእሳት ተያያዘ፡፡ ሙሉ በሙሉ ነደደ፡፡
*   *   *
ቂም በቀል የሁለት-ወገን-ስለት አለው፤ ይላሉ ፈረንጆች፡፡ ለሌላው የሳሉት ሰይፍ ወደ ራስ ሊመጣ እንደሚችል ማስተዋል ጥበበኝነት ነው፡፡ ክፋት ማቆሚያ የለውም፡፡ የጥፋተኝነት ስሜቱም አዕምሮን ከመነቆር አይገላገልም፡፡ ‹‹ዳባ ራሱን ስለት ድጉሡን›› ማለት ነው- በአማርኛ አገራዊ እነጋገር፡፡ በሀገራችን የመልካም አስተዳደር ጥያቄ ዛሬ አንገብጋቢ እሳት ሆኗል- (Burning Issue እንዲሉ) በመልካም አስተዳደር ጉድለት፣ በሥልጣን መባለግ፣ የሀገርንና የህዝብን ጥቅም ለራስ ማዋል፣ ፖለቲካን የግል ንብረት በማድረግ ማስፈራሪያና ‹‹እኔ ብቻ ነኝ አድራጊ ፈጣሪ›› ማለት ወዘተ እጅግ ጎጂ ባህል ሆነው ከርመዋል፡፡ ያደረጉት ነገር በተጨባጭ ስህተት መሆኑ ታውቆ ለፍርድ ይቅረቡ የተባሉ አሉ፡፡ ይበል የተባለ እርምጃ መሆኑን የማይስማማ ያለ አይመስለንም፡፡ ሆኖም ዕውነቱን ፈልፍሎ የማውጣት ሥራ፣ ያለ ምንም ወገንተኝነት ህሊናዊ ንፅህናን የመጠበቁ ኃላፊነት እና የግብረ-አበሮችን ሰንሰለት መርምሮ፣ ፈለጉን የማግኘትን የመበጠስ ዕልህ - አስጨራሽ ጉዞ ሳያሰልሱ የመጓዝን ሂደት ከወዲሁ አስቦና አስልቶ መንቀሳቀስ ወሳኝ ነው። ጅምሮች በአጭር እንዳይቀጩ ከመርማሪ ፖሊስ እስከ ፍትህ አካላት የተባበረ ቅኝት ያስፈልጋቸዋል። ዲሞክራሲ ላጲስ አይደለም፤ ተጋጋዥ እንጂ ተጠፋፊ አይደሉም፡፡ ፖለቲካ የኢኮኖሚ ዕምቅ መገለጫ (Concentrated Expression) እንጂ ሌላ ላንቃ አይደለም፡፡ ሀቀኝነት ሳይኖር ፍትሃዊነት መጎናፀፍ አይቻልም፡፡ ለማኅበራዊ ምስቅልቅልነት መፍትሄው የመንግስትና ህዝብ ተቀራርቦ ሀገራዊ መተሳሰብን መፍጠር እንጂ ‹‹መንግስት ነኝና ልፈራ ይገባኛል›› የሚል አመለካከትና ጉልበታዊ ተግባር አይደለም፡፡ በመንግስት ውስጥ ያሉና ህዝብን በመበደል የሚኩራሩ ወገኖች ጊዜያዊ ድል እንጂ ዘላቂ ወንበር አይኖራቸውም፡፡ ያም ሆኖ እኒህንም አካላት ለፍርድ ሲቀርቡ ያለአድልዎ ዳኝነት የሚሰጥ አካል ሊኖር ይገባል። ህጋዊ ፍርድ በሀቅ ላይ የተመረኮዘ እስከሆነ ድረስ የመልካም አስተዳደር አለመጓደልን የሚያፈካ ብርሀን አለ ማለትን ማመን እንጀምራለን፡፡
የመልካም አስተዳደር ጉዳይ፣ በመልካም አስተዳደር ጉድለት እንዳይጨናገፍ ብርቱ ጥረት ያስፈልጋል፡፡ ሀገራችን የሰው አስተሳሰብ ልማት ያሻታል፡፡ ጠቃሚ የሆነ ነው የምንለውን የመዋቅር ለውጥ ለማምጣት፣ እስከ ቻርተር ማሻሻል ስንዘልቅ ዞሮ ዞሮ ወሳኙ ሁነኛ የሰው ኃይል መሆኑን አንርሳ! ተለውጧል ተሻሽሏል ማለት ብቻ ሳይሆን ከዕውነታው ያልራቀ መፍትሄ መሆኑን ማረጋገጥ ቁልፍ ነገር ነው!
በማናቸውም ግለሰብ ፣ በግል ኢንቬስተሮች፣ በቢሮክራሲ አባላት በንግዱ ማህበረሰብ፣ በሲቪክ ማህበረሰብ አባላት ወዘተ ላይ የምንሰነዝራቸውን ሂሶች፣ ውንጀላዎችና ፍረጃዎች ስናስብ፣ እኛስ ራሳችንን እንዴት እንገመግማለን? እንዴት እንፈርጃለን? እንዴትስ ስህተታችንን እናምናለን? የሚለውን ወሳኝ ጉዳይ ልብ - እንበል! ለዚህ የሚበጀን ዘዴ “ንስሓ ከኃጢአት፣ ውኃ ከእድፍ ያፀዳል!” የሚለውን ምሳሌ ለሊት ተቀን ማሰብ እና ስራ ላይ ማዋል ነው!

 ባለፉት 9 ወራት ብቻ 71 ያህል ዝነኞች ሞተዋል

      የመጨረሻዋ ቀን ላይ በሚገኘው የፈረንጆች አመት 2016፣ ባልተለመደ ሁኔታ ከፖለቲካ እስከ ስፖርት፣ ከፊልም እስከ ሙዚቃ በየሙያ መስኩ እውቅናን ያተረፉ በርካታ ዝነኞችና ታዋቂ ሰዎች ከዚህ አለም በሞት የተሰናበቱበት መሆኑ ተነግሯል፡፡
ሲኤንኤን በአለማቀፍ ደረጃ የተሰራ የጥናት ውጤት ጠቅሶ ሰሞኑን እንደዘገበው፣ እስካለፈው ጥቅምት ወር ድረስ በነበሩት የአመቱ 9 ወራት ብቻ፣ በተለያዩ የሙያ መስኮች ስማቸውን በአለም መድረክ ላይ ማስጠራት የቻሉ ከ71 በላይ የዓለማችን ታዋቂ ሰዎችና ዝነኞች ከዚህ አለም በሞት ተለይተዋል፡፡ ከስፖርቱ አለም ብንጀምር፣ እድሜ የማያዝላቸው፣ ህመም የማይረታቸው ከሚመስሉ ጠንካራ እጆቹ በሚወነጨፉ ቡጢዎቹ ብዙዎችን ያደባየው የአለም የከባድ ሚዛን ሻምፒዮናው መሃመድ አሊ፣ ባለፈው ሀምሌ ወር መጀመሪያ ላይ ነበር በተወለደ በ74 አመቱ ይህቺን ዓለም በሞት የተሰናበተው፡፡
ወደ ፖለቲካው ጎራ ስንል ደግሞ፣ አለማችን በአመቱ ካጣቻቸው ታላላቅ ሰዎች መካከል አንዱ የሆኑትን የቀድሞውን የተባበሩት መንግስታት ድርጅት ዋና ጸሃፊ ግብጻዊውን ቡትሮስ ቡትሮስ ጋሊን እናገኛለን። ቡትሮስ ጋሊ በወርሃ የካቲት ነበር በ93 ዓመታቸው በሞት የተለዩት፡፡ አለማችን በዓመቱ ካጣቻቸው ሌሎች ፖለቲከኞች መካከልም የኖቤል የሰላም ተሸላሚውን ሺሞን ፔሬዝን እናገኛለን፡፡ እስራኤልን በፕሬዚዳንትነትና በጠቅላይ ሚኒስትርነት ያስተዳደሩት ፔሬዝ፣ ባለፈው መስከረም ወር መጨረሻ ላይ ነበር በ93 ዓመታቸው ይህቺን አለም በሞት የተሰናበቱት፡፡
መስከረም ላይ ፔሬዝን የወሰደ ጨካኝ ሞት፣ በህዳር ዞሮ መጣና ሌላ የፖለቲካው መስክ ገናና ይዞ ሄደ፡፡ ኮሙኒስት ኩባን ለግማሽ ምዕተ አመት ያህል ያስተዳደሩት ፊደል ካስትሮ ሩዝ፤ በ90 አመታቸው ወደማይቀርበት መሄዳቸው ተሰማ፡፡ ከሙዚቃው መስክ ከተሰሙት አስደንጋጭ መርዶዎች መካከል ከሰሞኑ የተደመጠው የጆርጅ ማይክል ሞት አንዱ ነበር፡፡ ታዋቂው ድምጻዊ ጆርጅ ማይክል፣ በፈረንጆች የገና እለት ከዚህ አለም በሞት የመለየቱ መርዶ ተሰምቷል፡፡ በካንሰር ሲሰቃይ የቆየው እንግሊዛዊው የሮክ አቀንቃኝ ዴቪድ ቦዌም በዚሁ ጦሰኛ አመት ነበር በ69 ዓመቱ ይህቺን አለም በሞት የተሰናበተው፡፡
አመቱ ሊጠናቀቅ ጥቂት ቀናት በቀረበት ሁኔታ አለምን በድንጋጤ ክው ያደረገ ሌላ የመዝናኛው መስክ መርዶ ከሰሞኑ ተሰምቷል፡፡ በ”ስታር ዎርስ” ፊልም ላይ በመተወን የዓለምን ቀልብ ገዝታ የዘለቀቺው የፊልም ተዋናይትና ደራሲ ኬሪ ፊሸር፣ ባለፈው ሰኞ በልብ ድካም ህመም በ60 አመቷ አለምን ተሰናብታለች፡፡

“ልጆች ባሉበት ሁሉ ምግብ ይኑር” በሚል መሪ ቃል፤ ዘላቂ የት/ቤት ምገባ ፕሮግራም ሲያካሂድ የቆየው የኢትዮጵያ ስኩል ሚል ኢንሼቲቭ (ኢ.ስ.ሚ.ኢ)፤ ተግባሩን ወደ አቅም ግንባታ ስራ ለማሸጋገር እየተንቀሳቀሰ መሆኑን ገልፆ፣ ማዕከሉን ሰቆጣ ለማድረግ ከዋግህምራ ዞን መስተዳደር ጋር በመጪው ማክሰኞ ስምምነት እንደሚፈራረም አስታውቋል፡፡
ህፃናት ተማሪዎችን በየትምሀርት ቤታቸው ሲመግብ የቆየው ማዕከሉ፤ ት/ሚኒስቴር በመጀመሪያ ደረጃ ት/ቤቶች ተመሳሳይ የምገባ ፕሮግራም መጀመሩን ተከትሎ ቀደም ሲል ድርጅቱ ለምገባ ሲጠቀምባቸው የነበሩ ማዕከላቱን ለሰርቶ ማሳያነት እንዲያገለግሉ በማድረግ፣ ፊቱን ወደ አቅም ግንባታ ማዞሩን ገልጿል፡፡
በዋግምሀራ  ዞን በተከሰተው ድርቅ ሳቢያ አካባቢው ይበልጥ ድጋፍ የሚያስፈልገው  ቢሆንም ረሀብን ማሸነፍ እንደሚቻል የተረጋገጠበት አካባቢ በመሆኑ፣ ዞኑ ለመጪዎቹ 3 ዓመታት የኢ.ስ.ሚ.ኢ የስራ ማዕከል ሆኖ የሚዘልቅበትን ስምምነት እንደሚፈረም ታውቋል፡፡


የኢትዮጵያ የፅንስና ማህፀን ሃኪሞች ማህበር 25ኛ ዓመቱን ያከብራል

የአፍሪካ ፅንስና የማህፀን ሐኪሞች ፌዴሬሽን ጉባዔ፣ በመጪው የካቲት ወር በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ ሊካሄድ ነው፡፡  ‹‹ዘላቂ የልማት ግቦች በአፍሪካ የስነ ተዋልዶ ጤና፣ ዕድሎችና ተግዳሮቶች›› ‹‹በሚል መሪ ሃሳብ በሚካሄደው በዚሁ አህጉር አቀፍ ጉባኤ ላይ የተለያዩ ጥናታዊ ፅሁፎች ይቀርባሉ፡፡
የአፍሪካ የፅንስና ማህፀን ሐኪሞች ፌዴሬሽን መስራችና አባል የሆነው የኢትዮጵያ ፅንስና ማህፀን ሃኪሞች ማህበር (ኢሶግ)፤ የተመሰረተበትን 25ኛ ዓመት በአሉን ያከብራል፡፡ ይህንኑ የማህበሩን የብር ኢዮቤልዩ በዓልና አህጉር አቀፍ ጉባዔውን እስመልክቶ ማህበሩ በነገው ዕለት በሒልተን ሆቴል ጋዜጣዊ መግለጫ እንደሚሰጥ ማህበሩ ለአዲስ አድማስ የላከው መረጃ ያመለክታል፡፡ በዚሁ ዕለትም የማህበሩ አባላት የሆኑ የህክምና ባለሙያዎች ደም እንደሚለግሱ ታውቋል፡፡


 - አምና 72ኛ የነበሩት ትራምፕ፣ ዘንድሮ 2ኛ ሆነዋል - ከ74 የአለማችን ሃያላን፣ አፍሪካውያን 2 ብቻ ናቸው

    ታዋቂው ፎርብስ መጽሄት 74 ሰዎች የተካተቱበትን የ2016 የአለማችን ሃያላን ዝርዝር ከሰሞኑ ይፋ ያደረገ ሲሆን፣ የሩስያው ፕሬዚዳንት ቭላድሚር ፑቲን፣ ተመራጩ የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ እና የጀርመን መራሂተ መንግስት አንጌላ መርኬል በቅደም ተከተል ከአንደኛ እስከ ሶስተኛ ደረጃን ይዘዋል፡፡
የቻይናው ፕሬዚዳንት ዢ ጂፒንግ፣ የሮማው ሊቀጳጳስ ፍራንሴስ እና የአሜሪካ የፌደራል ሪዘርቭ ሃላፊ ጃኔት የለን እስከ ስድስተኛ ያለውን ደረጃ ሲይዙ፣ የማይክሮሶፍቱ መስራች ቢል ጌትስ፣ የአልፋቤት ኩባንያ ዋና ስራ አስፈጻሚ ላሪ ፔጅ፣ የህንዱ ጠቅላይ ሚኒስትር ናሬንድራ ሞዲ እና የፌስቡኩ መስራች ማርክ ዙክበርግ በቅደም ተከተል እስከ አስረኛ ደረጃን ይዘዋል፡፡ አምና 72ኛ ደረጃ ላይ የነበሩት ትራምፕ፣ በሚገርም መሻሻል ዘንድሮ ሁለተኛ ደረጃ ላይ የተቀመጡ ሲሆን፣ አምና በ2ኛ ደረጃ ላይ ተቀምጠው የነበሩት ተሰናባቹ ፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ በአንጻሩ ዘንድሮ ወደ 48ኛ ደረጃ አሽቆልቁለዋል፡፡ በዘንድሮው የፎርብስ የአለማችን ሃያላን ዝርዝር ውስጥ ሁለት አፍሪካውያን ብቻ የተካተቱ ሲሆን፣ 44ኛ ደረጃን የያዙት የግብጹ ፕሬዚዳንት አብዱል ፈታህ አል ሲሲ፣ ከአፍሪካውያን መካከል ቀዳሚው ሃያል ሰው ሲባሉ፣ የአፍሪካ ቁጥር አንድ ቢሊየነር አሊኮ ዳንጎቴ 68ኛ ደረጃን በመያዝ ሁለተኛው ሃያል ሰው ሆነዋል፡፡
በፎርብስ የአመቱ ሃያላን ዝርዝር ውስጥ ለመጀመሪያ ጊዜ ስማቸው የተካተተ ግለሰቦች ቁጥር 11 እንደሆነ የጠቆመው መጽሄቱ፣ ከእነዚህም መካከል የእንግሊዟ ጠቅላይ ሚኒስትር ቴሬሳ ሜይ እና የፊሊፒንሱ ፕሬዚዳንት ሮዲሪጎ ዱሬቴ እንደሚገኙበት ገልጧል፡፡ ፎርብስ መጽሄት የአመቱን የአለማችን ሃያላን የመረጠባቸው መስፈርቶች በብዙ ሰዎች ላይ ተጽዕኖ የማሳደር ብቃት፣ የፋይናንስ አቅም፣ የተጽዕኖ ወሰን ስፋትና አቅምን የመጠቀም ብቃት የሚሉ እንደሆኑ አስታውቋል፡፡

- ቱርክ ፌስቡክ፣ ትዊተርና ዋትዛፕን ዘግታለች

      የጀርመን ሶሻል ዲሞክራቲክ ፓርቲ ሊቀመንበር ቶማስ ኦፐርማን ፌስቡክ ሃሰተኛ ዜናዎችን በአፋጣኝ ከድረገጹ ላይ የማያስወግድ ከሆነ በአንድ ሃሰተኛ ዜና 500 ሺህ ዩሮ ቅጣት እንዲጣልበት የሚያስገድድ ህግ እንዲወጣ ሃሳብ ማቅረባቸውን ዘ ኢንዲፔንደንት ዘግቧል። ፌስቡክ ግለሰቦችንና ተቋማትን ተጠቂ የሚደርጉ ሃሰተኛ ዜናዎችንና መረጃዎችን በተመለከተ የሚቀርቡለትን አቤቱታዎች በአግባቡ ተቀብሎ አፋጣኝ እርምጃ እየወሰደ አይደለም ያሉት ኦፐርማን፤ ይህን እንዲያደርግ የሚያስገድድ ህግ መውጣት እንዳለበት ተናግረዋል፡፡ ፌስቡክ መሰል ሃሰተኛ ዜናዎችንና መረጃዎችን በተመለከተ የሚቀርቡለትን አቤቱታዎች ተቀብሎ፣ በ24 ሰዓታት ጊዜ ውስጥ ከማህበራዊ ድረገጹ ላይ የማይሰርዝ ከሆነ፣ እስከ 500 ሺህ ዩሮ የሚደርስ ቅጣት ሊጣልበት ይገባል ብለዋል፡፡ በመሰል ዜናዎችና መረጃዎች ተጠቂ የሆኑ ግለሰቦችና ተቋማትም ከፌስቡክ ካሳ ሊሰጣቸው ይገባል ሲሉም አክለዋል፡፡
ፖለቲከኛው ያቀረቡት የቅጣት ሃሳብ፣ አገሪቱ በመጪው የፈረንጆች አመት 2017 ልታካሂደው ያሰበቺው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ በማህበራዊ ድረገጾች አማካይነት ሊረበሽ ይችላል በሚል የጀርመን መንግስት በድረገጾቹ ላይ ጥብቅ ክትትል ሊደረግ እንደሚገባ የያዘው አቋም አካል ነው ተብሏል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ ባለፈው ሰኞ በቱርክ የሩስያ አምባሳደር አንድሪ ካርሎቭ በጥይት መገደላቸውን ተከትሎ፣ የአገሪቱ መንግስት ፌስቡክ፣ ትዊተርና ዋትዛፕን መዝጋቱን ዘ ቴሌግራፍ ዘግቧል፡፡

   - ከ26 በላይ ሰዎች ሲገደሉ፣ 45 ያህል ቆስለዋል - የ92 አመቱ ሙጋቤ በቀጣዩ ምርጫም ይወዳደራሉ

      የዲሞክራቲክ ሪፐብሊክ ኮንጎ ፕሬዚዳንት ጆሴፍ ካቢላ የስልጣን ዘመን ገደባቸው መጠናቀቁን ተከትሎ ስልጣን ለመልቀቅ ፍላጎት አለማሳየታቸው የቀሰቀሰው ከፍተኛ ተቃውሞ፣ በአገሪቱ ከፍተኛ ውጥረት የፈጠረ ሲሆን  የመንግስት የጸጥታ ሃይሎች እስካለፈው ረቡዕ ድረስ ከ26 በላይ ሰዎችን መግደላቸው ተዘግቧል፡፡
የፕሬዚዳንቱ የስልጣን ዘመን ቆይታ ባለፈው ማክሰኞ ቢያበቃም እስከ 2018 በስልጣናቸው ላይ እንደሚቆዩ በፓርቲያቸው ከተገለጸ በኋላ  የአገሪቱ የተቃዋሚ ፓርቲ አመራሮች የጠሩት ሰላማዊ ተቃውሞ ወደ ግጭት ማምራቱን የጠቆመው ዘገባው፤ በርካታ ተቃዋሚዎች ባለፈው ማክሰኞ የገዢውን ፓርቲ ቢሮ ማቃጠላቸውን ተከትሎ፣ በፖሊስና በተቃዋሚዎች መካከል ግጭት መከሰቱንና የጸጥታ ሃይሎች ቤት ለቤት አሰሳ በማድረግ በርካታ ዜጎችን ማሰራቸውን ገልጧል፡፡
በመዲናዋ ኪንሻሳ የተጀመረው ተቃውሞው ወደተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች እየተስፋፋና ውጥረቱ እየተባባሰ መምጣቱን ያመለከተው ዘገባው፤ ተመድ 45 ያህል ተቃዋሚዎች በተተኮሰባቸው ጥይት መቁሰላቸውን ባለፈው ረቡዕ ማስታወቁንና በአገሪቱ የተሰማራው የተመድ የሰላም አስከባሪ ሃይልም ግጭቱ ወደ እርስ በእርስ ግጭት እንዳያመራ መስጋቱንና ውጥረቱን ለማርገብ እየተንቀሳቀሰ እንደሚገኝ አብራርቷል፡፡
አሜሪካ ፕሬዚዳንት ካቢላ ምርጫ እንዲካሄድ በማድረግ ስልጣናቸውን ለማስረከብ ተነሳሽነት አለማሳየታቸው አሳዝኖኛል ማለቷን የጠቆመው ዘገባው፤ በአገሪቱ ባለፈው ወር ላይ ምርጫ መደረግ ቢገባውም የምርጫ ኮሚሽኑ ሰበብ አስባብ በማብዛት ምርጫውን ማራዘሙ ካቢላን በስልጣን ላይ ለማቆየት የታሰበ ሴራ ነው የሚል ቁጣ መፍጠሩንም ገልጧል፡፡
ከ2001 አንስተው አገሪቱን በመምራት ላይ የሚገኙት የ45 አመቱ ጆሴፍ ካቢላ፣ በህገመንግስቱ በተደነገገው መሰረት ለሶስተኛ የስልጣን ዘመን መወዳደር የማይችሉ ቢሆንም፣ ፕሬዚዳንቱ ግን 74 አባላት ያሉት የሽግግር መንግስት በማቋቋም እስከ 2018 ድረስ አገሪቱን በመምራት ለመቀጠል አቋም መያዛቸውን ዘገባው አስረድቷል፡፡
በተያያዘ ዜናም፣ ከ36 አመታት በላይ ዚምባብዌን የመሩትና አገሪቱን ወደከፋ ኢኮኖሚያዊ ቀውስ ስላስገቧት ስልጣን ይበቃቸዋል የሚል ጫና ከውስጥም ከውጭም የበረታባቸው የ92 አመቱ የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ሮበርት ሙጋቤ፤ ከአንድ አመት በኋላ በሚካሄደው ፕሬዚዳንታዊ ምርጫ እንደሚወዳደሩ ፓርቲያቸው አስታውቋል፡፡ ሙጋቤ በ2018 ምርጫ ለፕሬዚዳንትነት እንደሚወዳደሩ ይፋ መደረጉን ተከትሎ፣ የአገሪቱ ተቃዋሚ ሃይሎች የፓርቲውን ውሳኔ በማውገዝ አገሪቱን ወደ ከፋ ስራ አጥነት፣ የገንዘብ ቀውስና የኢኮኖሚ ድቀት ያስገቧት ሙጋቤ ስልጣን የሚይዙ ከሆነ የከፋ ቀውስ ይከተላል ሲሉ ማስጠንቀቃቸውን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡
ፓርቲያቸው ዛኑ-ፒኤፍ ከሰሞኑ ባደረገው ጉባኤ ላይ በፓርቲው የወጣቶች ክንፍ፣ ሙጋቤ እስከ ህልፈተ ህይወታቸው የአገሪቱ መሪ ሆነው ይቀጥሉ የሚል ሃሳብ መነሳቱን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡ በርካታ የአገሪቱ ዜጎች ባለፉት አመታት የሙጋቤን አምባገነናዊ ስርዓት በማውገዝ ተቃውሟቸውን አደባባይ ወጥተው ሲያሰሙ እንደነበርም ዘገባው አስታውሷል፡፡
በሌላ ዜና ደግሞ በቅርቡ በተካሄደው ምርጫ የተሸነፉትና ስልጣናቸውን እንዲለቁ በምዕራብ አፍሪካ አገራት ጫና ሲደረግባቸው የሰነበቱት የጋምቢያው ፕሬዚዳንት ያያ ጃሜህ፤ የማንም ጫና ከስልጣኔ አያስለቅቀኝም ሲሉ በድጋሚ በአቋማቸው መጽናታቸውን ዘ ጋርዲያን ዘግቧል፡፡ ፕሬዚዳንቱ ባለፈው ማክሰኞ በሰጡት መግለጫ፣ ከፈጣሪ በቀር ስልጣኔን ሊያስለቅቀኝ የሚችል አንዳች እንኳን ምድራዊ ሃይል የለም በማለት እቅጩን ተናግረዋል፡፡