![Administrator](http://www.gravatar.com/avatar/ae27edcf69291ea40ada5f2390650d88?s=100&default=http%3A%2F%2Faddisadmassnews.com%2Fcomponents%2Fcom_k2%2Fimages%2Fplaceholder%2Fuser.png)
Administrator
የዲጂታል ገንዘብ ዝውውር ከጥሬ ገንዘብ ልውውጥ በልጧል ተባለ
“ብሔራዊ ባንክ ኢኮኖሚውን ለማረጋጋት ጉልህ ሚና ይጫወታል”
በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ማብራሪያ የሰጡት የብሔራዊ ባንክ ገዥ የአገሪቱን የፋይናንስ ሥርዓት ዲጂታል ማድረግ መቻሉን ተናግረዋል። አክለውም፤ በዚህ ዓመት በባንኮች የተመቻቹ የዲጂታል የገንዘብ ዝውውሮች፣ ከጥሬ ገንዘብ ልውውጦች መብለጣቸውን ገልጸዋል።
የኢትዮጵያ የባንክ ተግባራት ሙሉ በሙሉ በብሔራዊ ባንክ ቁጥጥር ስር መሆኑን የባንኩ ገዢ አቶ ማሞ ምሕረቱ አስታውቀዋል። በብሔራዊ ባንክ እየተካሄደ ያለው ማሻሻያ፣ የፋይናንስ ስርዓቱን ከዲጂታል እድገቶች ጋር ለማዘመንና ለማጣጣም ያለመ መሆኑንም አብራርተዋል።
አዲስ በፀደቀው የባንክ አዋጅ ላይ የግንዛቤ ክፍተቶች እንዳሉ በማንሳትም፣ ከምክር ቤቱ የተሰነዘሩ አንዳንድ ጥያቄዎችን ተችተዋል። አዲሱ አዋጅ ብሔራዊ ባንክ በቅርቡ ካደረገው ማሻሻያ ጋር በቀጥታ የተያያዘ እንዳልሆነም ገዥው ጠቁመዋል። ነገር ግን መሰል አዋጆች በተደጋጋሚ መተግበራቸው በባንክ ስራዎች ላይ አሉታዊ ተጽእኖ ሊያሳድር እንደሚችል አስጠንቅቀዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት የውጭ ኢንቨስትመንትን ለመሳብ የተሻሻለ የባንክ ደንብ አለመኖሩን የገለጹት ገዢው፤ በዚህ ጉዳይ ላይ በምክር ቤቱ የተነሱ ጥያቄዎች እንዲመለሱ ጠይቀዋል። የብሔራዊ ባንክ ማሻሻያዎች በዋናነት ከገንዘብ ፖሊሲ ማስተካከያዎች ጋር የተያያዙ መሆናቸውን በመጠቆምም፤ ምክር ቤቱ የእነዚህን ለውጦች ትክክለኛ ትርጓሜ እንዲያረጋግጥ አሳስበዋል።
የብሔራዊ ባንክ አፈጻጸምን ያወደሱት አቶ ማሞ ምሕረቱ፤ እርምጃዎቹ ከሌሎች የአፍሪካ ማዕከላዊ ባንኮች ጋር ሲነፃፀሩ የበለጠ ውጤታማ መሆናቸውን ገልጸዋል። ብሔራዊ ባንክ ኢኮኖሚውን በማረጋጋት ረገድ ጉልህ ሚና እንደሚጫወት ገልፀው፤ የባንኩን የሥራ አፈፃፀም “የሚመሰገን” ነው ሲሉ አድንቀውታል፡፡ የውጭ ባንኮች ወደ ኢትዮጵያ እንዲገቡ የሚፈቅደው ረቂቅ አዋጅ በሳምንቱ አጋማሽ ላይ በፓርላማ በአብላጫ ድምጽ መፅደቁ ይታወቃል።
አምስት የሚደርሱ የውጭ አገር ባንኮች የኢትዮጵያን የባንክ ዘርፍ ለመቀላቀል ፍላጎት ማሳየታቸው የተነገረ ሲሆን፤ ከእነዚህም ውስጥ የኬንያ ስታንዳርድ ባንክ፣ የኬንያ ሲቲ ባንክና የተባበሩት አረብ ኤምሬቶች ባንክ ይገኙበታል። ባለፈው ዓመት ሀምሌ የማክሮ ኢኮኖሚ ማሻሻያው መተግበሩን ተከትሎ፣ በኢትዮጵያ፤ ፋይናንስና ባንክ ዘርፎች የፖሊሲ ማሻሻያዎች እየተደረጉ ሲሆን፤ ይሄም የውጭ ኢንቨስትመንትን እንደሚስብ ይጠበቃል። በተመሳሳይ የባንክ ሥራ ማሻሻያ አዋጅም በህዝብ ም/ቤት አባላት መፅደቁ ይታወቃል። በያዝነው ዓመት የዲጂታል ገንዘብ ዝውውር ከጥሬ ገንዘብም ልውውጥ በላቀ መጠን መከናወኑ የተገለፀ ሲሆን፤ የኤቲኤም ተጠቃሚዎች ቁጥር መጨመሩም ታውቋል።
በኮሬ ዞን የነዳጅ ዋጋ መናሩ ተነገረ
በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል፣ ኮሬ ዞን የነዳጅ ዋጋ ንረት እንደተከሰተ ተገለፀ። ነዋሪዎቹ ለአዲስ አድማስ እንደገለጹት፤ ከዋጋው መናር በተጨማሪ የአቅርቦት ችግር በመኖሩ ነዋሪው በትራንስፖርት እጥረት እየተንገላታ ነው ተብሏል።
ስማቸው እንዲጠቀስ ያልፈለጉ አንድየኬሌ ከተማ ነዋሪ በሰጡት አስተያየት፤ የነዳጅ አቅርቦቱ መስተጓጎል ከጀመረ ስምንት ወራት እንዳስቆጠረ ተናግረዋል። “የቤንዚን ዕጥረቱ ከማሕበረሰቡ ኑሮ ጋር ‘ተሳስሯል’ ያሉት ነዋሪው፣ በከተማው የሞተር ሳይክል አከራዮች ስለሚበዙ እና የመብራት መቆራረጥ ስላለ፣ እንዲሁም በርካታ የጄኔሌተር ተጠቃሚ ስላለ የቤንዚን ዕጥረቱ ያሳረፈው ተጽዕኖ ቀላል አለመሆኑን አብራርተዋል።
“የቤንዚን አቅርቦቱ ሙሉ በሙሉ ባይቋረጥም፣ በነጋዴዎች የመሽሸግ ተግባር ይፈጸማል ተብሏል። አንድ ሊትር ቤንዚን ከ370 እስከ 400 ብር ይሸጣል ያሉት ነዋሪው፤ በተጨማሪም፣ በከተማይቱ ውስጥ ያለው የነዳጅ ማደያ አንድ ብቻ ነው። ይህም ከሌሎች ሁኔታዎች ጋር ተዳምሮ የዕለት ተለት ዕንቅስቃሴና በእጅጉ እንደሚያስተጓጉል ነዋሪው ተናግረዋል።
አብዛኛውን ጊዜ ቤንዚን እንደማይመጣና አልፎ አልፎ ከመጣም የነዳጅ ማደያው በኮንትሮባንድ ንግድ ለተሰማሩ ነጋዴዎች አሳልፎ እንደሚሰጥም ጠቅሰዋል።
በተጨማሪም በቴሌብር አማካይነት ክፍያ ፈጽመው ነዳጅ የሚያስቀዱ ተጠቃሚዎች እንደሌሉ የጠቆሙት ነዋሪው፣ ከሁሉም በላይ በከተማዋ ውስጥ አንድ የነዳጅ ማደያ ብቻ መኖሩ ተጠቃሚዎችን አማራጭ አልባ አድርጓቸዋል ተብሏል።
በኮሬ ዞን የመምህራን እና መንግስት ሰራተኞች ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማሕበር ስር የሚተዳደረው ይኸው የነዳጅ ማደያ የሚያቀርበው ቤንዚን የተደራሽነት መጠኑ የማሕበረሰቡን ፍላጎት የሚያሟላ አለመሆኑን አስረድተዋል፣ ነዋሪው። ከዚህም ባሻገር፣ የከተማዋ ማሕበረሰብ በከፍተኛ የኢኮኖሚ ቀውስ ውስጥ እንደሚገኝ ጨምረው ተናግረዋል።
ነዋሪው በግላቸው የሞተር ሳይክል ማከራየት ስራ ላይ የተሰማሩ ሲሆኑ፣ ኬሌ ከተማ ውስጥ ሞተር ሳይክል በማከራየት ስራ የተሰማሩ ወጣቶች በነዳጅ እጥረቱ ሳቢያ የዕለት ጉርሳቸውን መሸፈን እንዳልቻሉ ተጠቁሟል። “ስራ ካቆምኩ ሁለት ወር እየሆነኝ ነው” የሚሉት እኚሁ ነዋሪ፣ የትራንሰፖርት አገልግሎት የሚሰጡ የባጃጅ ተሽከርካሪዎችም ስራ ማቆማቸውን ተናግረዋል።
የቤንዚን ስርጭት ላይ ቁጥጥር የሚያደርጉ የመንግስት አካላት እንደሌሉና “ከሕገ ከህገ-ወጥ” ነጋዴዎች ጋር ተባብረው እንደሚሰሩ ያነሱት ነዋሪው፣ ከነዋሪዎች ስለ ቤንዚን ጥያቄ ሲቀርብ “ጉዳዩን እየተከታተልን ነው፣ ምላሽ እንሰጣለን” ቢሉም፣ ሆኖም ግን ጉዳዩ ለችግሩ ዕልባት ሰጥተው እንደማያውቁ አመልክተዋል።
በኬሌ ከተማ የሞተር ሳይክል መለዋወጫ እያስመጡ በመሸጥ ሥራ ላይ እንደተሰማሩ የነገሩን ስማቸው እንዳይጠቀስ የጠየቁ አስተያየት ሰጪ በበኩላቸው፤ የተከሰተው የቤንዚን ዕጥረት የሚሸጧቸውን የመለዋወጫ ዕቃዎች ለማስመጣት እንቅፋት እንደሆነባቸው ተናግረዋል።
የዞኑ ባለስልጣናት የተፈጠረው ችግር ላይ ትኩረት አድርገው መፍትሔ ለመስጠት አለመቻላቸውን እኚሁ ነዋሪ ገልጸዋል። ሁኔታው በዚሁ ከቀጠለ፣ የሚፈጠረው ችግር እጅግ አስከፊ እየሆነ እንደሚመጣም አስረድተዋል።
የፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ከብልፅግና ጋር እየተሞዳሞደ ነው ተባለ
“ብልፅግና ም/ቤቱን የግሉ መጠቀሚያ አድርጎታል”
የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት ከተቋቋመበት ዓላማ ውጭ ከብልፅግና ጋር እየተሞዳሞደ ነው በሚል በተቃዋሚዎች ኮከስ ክስ ቀረበበት። ኮከሱ የጋራ ምክር ቤቱ በቅርቡ ባደረገው ጠቅላላ ጉባዔ አዲስ አመራር መምረጡን አጥብቆ ኮንኗል።
ኢሕአፓ፣ ኦፌኮ፣ ዎብን፣ ሕብር ኢትዮጵያ ዴሞክራሲያዊ ፓርቲ እና ኦነግ የተካተቱበት የተቃዋሚ ፓርቲዎች ኮከስ ባለፈው ረቡዕ ታህሳስ 9 ቀን 2017 ዓ.ም. ባወጣው መግለጫ፣ የጋራ ምክር ቤቱ የተቋቋመው በመሠረታዊ አገራዊ አጀንዳዎች ዙርያ በትብብርና በመወያየት የጋራ መድረክና አሰራር በማበጀት ለመንቀሳቀስ መሆኑን አመልክቷል። “ይሁንና ምክር ቤቱ ከተቋቋመበት የመድብለ ፓርቲ ስርዓትን የማጠናከር ዓላማና ተልዕኮ በመውጣት የብልፅግና ፓርቲ ታዛዥ፣ ጉዳይ ፈጻሚና አስፈጻሚ እንዲሆን ከፍተኛ ጫና እየተደረገበት ነው” ሲል ኮከሱ ወቅሷል።
“ከዓላማው ውጪ እየተንቀሳቀሰ ነው” በሚል በተቃዋሚዎች ኮከስ የተነቀፈው የጋራ ምክር ቤቱ፤ ብልጽግና ፓርቲን ያለ ውድድር ሰይሞና ሌሎችን በምርጫ ስም አስቀምጦ አዲስ አመራር መምረጡንና ደንብ መቅረጹን ፓርቲዎቹ ተቃውመዋል።
“የፖለቲካ ድርጅቶች ሃሳብ መለዋወጫ እንዲሆን የመሰረቱትን የጋራ ምክር ቤት ብልጽግና ቀስ በቀስ በስልታዊውና በሚታወቀው የኢህአዴግ አካሄድና ዘዴዎች አሽመድምዶታል” ያለው የተቃዋሚዎች ኮከስ፤ “ይህ አካሄድ ከተጨባጭ የዘመነ ፖለቲካ አካሄድ ጋር ስለሚቃረን ምክር ቤቱ ወደተመሰረተለት ቃልኪዳን እንዲመለስ አጥብቀን እንጠይቃለን” ብለዋል፡፡ የኢትዮጵያ የፖለቲካ ፓርቲዎች የጋራ ምክር ቤት፣ ገዢውን ፓርቲ ጨምሮ ሌሎች ተቃዋሚ ፓርቲዎች በተፈራረሙት የቃልኪዳን ሰነድ አማካይነት ከዓመታት በፊት መቋቋሙን ጠቅሰው ያስታወሱት የኢህአፓ ተቀዳሚ ሊቀመንበር መጋቢ ብሉይ አብርሃም ሃይማኖት፣ የተቋቋመበት ዋና ዓላማዎቹ በአገሪቱ ዴሞክራሲያዊ ስርዓትን ማስፈንና በፖለቲካ ፓርቲዎች ላይ የሚደርሱ ተጽዕኖዎችን መከላከል፣ እንዲሁም የፖለቲካ ምሕዳሩን ማስፋትና የተለያየ አመለካከት ያላቸው ፓርቲዎች ተቀራርበው በአገራዊ ጉዳዮች ዙሪያ እንዲሰሩ ማስቻል መሆናቸውን ተናግረዋል። ነገር ግን “ብልጽግና ፓርቲ ምክር ቤቱን የግሉ መጠቀሚያ ማድረግ ጀመረ። እኛ ‘ሕገ ወጥ ነው’ ብለን ባልተገኘንበት ጉባዔ ላይ በአቋራጭ ብልጽግና ያለውድድር ስልጣን እንዲኖረው ተደረገ” ያሉት ፓርቲዎች፤ በሌላ በኩል የምክር ቤቱ ስራ አስፈጻሚ ውስጥ በየዓመቱ ምርጫ ይደረግ ነበር። ሆኖም ያለውድድርና ምርጫ የብልጽግና አባል የሆነ ማንኛውም ተወካይ በክልሎችም ሆነ በፌደራል ደረጃ መቀመጫ ‘ይኑረው’ የሚል ሕግ ጸደቀ” ብለዋል።
ይህ ሕግ የኮከሱ አባል ፓርቲዎችን እንደማይገዛ መጋቢ ብሉይ በማስታወቅ፣ በአዲሱ ሕግ መሰረት ለስራ አስፈጻሚው የሁለት ዓመት ተጨማሪ የስልጣን ዕድሜ የሚሰጥ መሆኑን ገልጸዋል። ከህዳር 7 እስከ 9 ቀን 2017 ዓ.ም. ዘ ሃብ በተሰኘው ሆቴል የተደረገው የጋራ ምክር ቤቱ ጠቅላላ ጉባዔ፣ ከስራ አስፈጻሚ አመራር ምርጫ ባሻገር ይኸው ሕግ የጸደቀበት እንደሆነና የኮከሱ አባል የሆኑ ፓርቲዎች እንደማይቀበሉት ጠቁመዋል።
“በአማራና ኦሮሚያ ክልል የሚካሄዱ ጦርነቶች እንዲቆሙ ጥሪ የሚያቀርብ መግለጫ ‘እናውጣ’ ብለን ለጋራ ምክር ቤቱ ብንማጸንም ሰሚ አላገኘንም” የሚሉት መጋቢ ብሉይ፣ “[የጋራ ምክር ቤቱ] ከእኛ ዕውቅና ውጪ መግለጫ እየሰጡ ነው” ሲሉ ተናግረዋል። በተጨማሪም፣ መጋቢ ብሉይ አብርሃም፣ በጋራ ምክር ቤቱ ውስጥ “ያሉ ችግሮችን” ለመቅረፍ የተደረገ ሙከራ እንደሌለና ከመነሻውም ምክር ቤቱ ከኮከሱ አባል ፓርቲዎች ጋር ለመነጋገር ፍላጎት እንዳላሳየ ተናግረዋል።
“የገዢው ፓርቲ አጃቢ ሆኖ መሄድ ተገቢ አይደለም። ምክር ቤቱ እንዲድን ጥረት እናደርጋለን። ነገር ግን ጥረታችን ካልተሳካ ለሕዝብ የሚወግን ጠንካራ ምክር ቤት እናቋቁማለን” ሲሉ መጋቢ ብሉይ አብርሃም አቋማቸውን አስታውቀዋል።
የህይወት ተፈራ 'ተድባብ' ታሪካዊ ልቦለድ ላይ ውይይትና ዳሰሳ አለ: በዋሊያ መጽሐፍት::
በዘነበች ታደሰ ህይወትና ሥራ ላይ ያተኮረ መፅሀፍ ይመረቃል
ዘነበች ታደሰ ማን ነች? ለምንስ ጭራ ቀረሽ የሚል ስያሜ ተሰጣት? ለጥበብ ምን አበረከተች? የሚሉ ጥያቄዎችን ሊመልስ የሚችል የአርቲስት ዘነበች ታደሰን ህይወት የሚዳስስ በፅሁፍና በምስል የተደራጀ መፅሐፍ በዶ/ር ጌታቸው ተድላ ተዘጋጅቶ ለአንባቢያን ሊቀርብ ነው።
ታህሳስ 12 2017 በሀገር ፍቅር ቴአትር የሚመረቀው ይህ መፅሀፍ 167 ገፆች ያሉት ነው።
ለሀገራዊ ምክክሩ መሳካት የመገናኛ ብዙኃን ሚና የላቀ ነው ተባለ
ለሀገራዊ ምክክሩ መሳካት የመገናኛ ብዙሃን ሚና የላቀ መሆኑን የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ምክር ቤት ገለፀ። ምክር ቤቱ ከተለያዩ የሚዲያ ባለሞያዎችና የዩኒቨርስቲ ምሁራን ጋር “በሀገራዊ ምክክሩ የመገናኛ ብዙኃን ሚና ምን ይመስላል“ በሚለው ጉዳይ ላይ ምክክር አድርጓል።
መገናኛ ብዙሃን ታማኝ፣ ነፃና ገለልተኛ የሆነ ሙያዊ ሃላፊነት የሚስተናገድበት ተቋም መሆኑን ያነሱት የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ምክር ቤት የስራ አስፈፃሚ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ አማረ አረጋዊ፤ ኢትዮጵያ የጀመረችው ሀገራዊ ምክክር የተሳካና ውጤታማ እንዲሆን መገናኛ ብዙኃን ድርሻቸው የጎላ እንደሆነና ለዚህም በትጋት መስራት እንደሚገባ ገልጸል፡፡
ሀገራዊ ምክክሩ ኢትዮጵያ ከገባችበት ችግር የምትወጣበት አይነተኛ መንገድ ነው ያሉት የሀገራዊ ምክክሩ ኮሚሽነር ተገኘ ወርቅ ጌቱ (ዶ/ር) ፤ ምክክሩ በሀገሪቱ የተለያዩ አካባቢዎች እየተሰራ እንዳለና በቀጣይም በአማራና በትግራይ ክልሎች ምክክሩን ለመጀመር የተለያዩ ስራዎች እየተሰሩ ስለመሆኑ ተናግረዋል፡፡
በአማራ ክልል ሀገራዊ ምክክሩን ለመጀመር ከ1 ሺህ 700 በላይ ተባባሪ አካላትን አሰልጥኗልም ብለዋል። በሀገራዊ ምክክሩ ላይ መገናኛ ብዙኃን ላበረከቱት አስተዋፅኦ አመስግነው፣ ምክክሩ የተሳካ እንዲሆን ሁሉም ኢትዮጵያዊ የድርሻውን ማበርከት እንደሚገባም ጥሪ አቅርበዋል።
የቴሌግራም ቻናልችንን በመቀላቀል የአዲስ አድማስን መረጃ ይከታተሉ…
https://t.me/AdissAdmas
ሲንቄ ባንክ ከዴሎይት ጋር የምክር አገልግሎት ስምምነት ተፈራረመ
ድምጻዊት ቬሮኒካ አዳነና ቀላቲ ቢውቲ ለ2 ዓመት ተፈራረሙ
እናት ባንክ፤ ሁለት እናት ተኮር ውድድሮችን ዛሬ በይፋ አስጀመረ
የዘንድሮ የሺህ ጋብቻ አፍሪካውያን ጥንዶችንም ያካትታል
የሺህ ጋብቻ ኹነትን በማዘጋጀት የሚታወቀው ያሜንት ኃ. የተ.የግ.ማ፤ ሦስተኛውን የሺህ ጋብቻ ጥር 18 ቀን 2017 ዓ.ም በአዲስ አበባ ሚሊኒየም አዳራሽ ያካሂዳል፡፡ በዚህ ኹነት ላይ 1ሺ ኢትዮጵያውያን ጥንዶችና 250 የሚደርሱ ከአፍሪካ አገራት የተውጣጡ ጥንዶች የሰርግ በዓላቸውን እንደሚያከብሩ ታውቋል፡፡
የሺህ ጋብቻ ትልቁ ዓላማ፣ የኢትዮጵያን እንዲሁም የአፍሪካ ሀገራት ህዝቦችን የካበተ ባህላዊ የሰርግ ሥነ-ሥርዓት አጉልቶ በማሳየት፣ አዲስ አበባን “የሃኒሙን ማዕከል” ማድረግ እንደሆነ አዘጋጆቹ ገልጸዋል።
የኹነቱ አዘጋጆች ሦስተኛውን የሺህ ጋብቻ አስመልክቶ ባለፈው ቅዳሜ ታህሳስ 6 ቀን 2017 ዓ.ም በሃርመኒ ሆቴል ጋዜጣዊ መግለጫ ሰጥተዋል፡፡
ዘንድሮ በሚካሄደው የሺህ ጋብቻ በተቻለ መጠን ከሁሉም ብሔርና ብሔረሰቦች የተውጣጡ ጥንዶች የሚሳተፉበት እንዲሆን እየተሰራ መሆኑንና ሙሽሮች ለሠርጋቸው የሚያወጡት ምንም ዓይነት ወጪ እንደማይኖር በመግለጫው ላይ ተጠቁሟል፡፡
የሺህ ጋብቻ የሠርግ ሥነሥርዓትና ባህላዊ ካርኒቫል፤ ከሠርግ ድግስ ጋር የተያያዙ፣ ለዘመናት የቆዩና ሥር የሰደዱ ጎጂ ማኅበራዊ አመለካከቶችን ለማስወገድና ወደ ለውጥ የሚያመራ ማኅበረሰባዊ ውይይት ለማንሳት እንደሚረዳ የተነገረ ሲሆን፤ ቤተሰብ በማህበረሰብ ግንባታ ውስጥ ያለውን ፋይዳ በማጉላት፣ ለበጎ አስተሳሰብ መጎልበት መሠረት መሆኑን ለማሳወቅ እንደሚረዳም ተጠቁሟል፡፡
የሺህ ጋብቻ፤ የውጭ አገር ጎብኚዎችን በመሳብ ከቱሪስት ፍሰት የውጭ ምንዛሪ ግኝትን መፍጠር፣ የባህል ልውውጥ መድረክ በመፍጠር ሃገሪቱ ለህዝቦች አንድነት መጠናከር እንዲሁም ለሰላምና ለባህሎች ዕድገት የምታደርገውን ጥረት መደገፍ አላማው ነው ተብሏል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ፣ ያሜንት ኃ. የተ.የግ.ማህበር ኹነቱን በተሻለ መንገድ ለማስተዋወቅ፣ አርቲስት ተስፋዓለም ታምራትና ባለቤቱን ቃልኪዳን አበራ እንዲሁም አርቲስት ይገረም ደጀኔና ባለቤቱን ፅዮን ዮሴፍን የየሺ ጋብቻ አምባሳደር አድርጎ ሾሟል፡፡
ለዚህ ኹነት ያስፈልጋል ተብሎ የታቀደው አጠቃላይ በጀት ከ68 ሚሊዮን ብር በላይ እንደሆነ ለማወቅ ተችሏል፡፡
”ቤተሰብን መመስረት አገርን መገንባት ነው" የሚል መሪ ቃል ያለው ያሜንት፤ የመጀመሪያውን የሺ ጋብቻ ኹነት በ2005 ዓ.ም 500 ጥንዶችን በመዳር ማከናወኑ ይታወሳል፡፡
ድርጅቱ በመጀመሪያው ዙር ለተጋቡ ጥንድ ሙሽሮች የ10ኛ ዓመት ክብረ በዓላቸውን በሸራተን አዲስ ያከበረላቸው ሲሆን፤ ለሁለተኛው ዙር ሙሽሮች የመልስ ጥሪ በግዮን ሆቴል ሳባ አዳራሽ ተደርጎላቸዋል፡፡