Administrator

Administrator

 ቴክኖ ሞባይል፤ አዳዲስ የስፓርክ 10 (Tecno Spark 10) ሲሪይስ ሞዴል ምርቶቹን ትናንት ይፋ አድርጓል፡፡
ኢትዮጵያን ጨምሮ ከ70 በላይ በሚሆኑ አለማቀፍ ገበያዎች ላይ በተጠቃሚዎች ዘንድ ከፍተኛ ተቀባይነትን ያገኘው ቴክኖ ሞባይል፤ ትናንት በተከፈተውና ለሁለት ቀናት በሚቆየው ዝግጅት፤ የስፓርክ 10፣ ስፓርክ 10ሲ እና ስፓርክ 10 ፕሮ ሞዴሎችን ለገበያ ማቅረቡን አስታውቋል፡፡ ስልኮቹ ዘመናዊ የፊትለፊት ካሜራ ያላቸውና ተገልጋዮች ፈጣንና ጥራት ያለው አገልግሎት ለማግኘት የሚያስችሉ መሆናቸውም በዚሁ የምርት ማስተዋወቂያ ስነስርዓት ላይ ተገልጿል፡፡
ትራንስሚሽን ማኑፋክቸሪንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማህበር (ቴክኖ ሞባይል) ጎሮ አካባቢ በሚገኘው የአይሲቲ ፓርክ ባስገነባው ዘመናዊ ፋብሪካው የተለያዩ ዓይነት የስልክ ምርቶችን በመገጣጠም ለሀገር ውስጥና ለውጭ አገር ገበያዎች የሚያቀርብ ተቋም ነው፡፡


ለዋና መሥሪያቤቱ ህንጻ ያሸነፈውን ዲዛይን ይፋ አደረገ

ብርሃን ባንክ ከ51 በላይ ወለሎች ያሉት ህንጻ ሊያስገነባ ሲሆን፤ ለዋና መሥሪያቤቱ ህንፃ ግንባታ ዲዛይን ለማሠራት ባወጣው ዓለም አቀፍ ጨረታ አሸናፊ ሆኖ የተመረጠውን ዲዛይን ይፋ አደረገ።

ባንኩ ባወጣው ዓለም አቀፍ ጨረታ ላይ 16 ኩባንያዎች የተሳተፉ ሲሆን ተሳታፊዎቹ ካቀረቧቸው ዲዛይኖች መካከል አሸናፊ የሆነው ዲዛይን ግንቦት 2 ቀን 2015 ዓ.ም. ምሽት በተካሄደ ፕሮግራም ላይ ይፋ ተደርጓል።

 ባንኩ በሰንጋ ተራ አካባቢ በተረከበው 5400 ካሬ ሜትር መሬት ላይ ለሚያስገነባው ህንፃ MAE ኮንሰልቲንግ ኤንድ ኢንጂነርስ በተባለው ድርጅት የቀረበው ዲዛይን አሸናፊ ሆኖ ተመርጧል። በተመረጠው ዲዛይን መሠረት የሚገነባው የባንኩ ዋና መሥሪያቤት ህንፃ ከ 51 በላይ ወለሎች ይኖሩታል ተብሏል፡፡

በዴጃው ኮንሰልቲንግ የተሰራው የህንፃ ዲዛይን ሁለተኛ ደረጃ አሸናፊ ሲሆን ፣ በአዲስ መብራቱ ኮንሰልቲንግ ኤንድ ኢንጂነርስ የቀረበው ዲዛይን ደግሞ ሦስተኛ ወጥቷል።

"የእምዬ አለላዎች" የተሰኘ የሥዕል ኤግዚቢሽን ከቅዳሜ ሚያዚያ 28/ 2015 ዓ.ም አንስቶ እስከ ግንቦት 12/2015 ዓ.ም በታላቁ የሃገር ፍቅር ቴአትር ቤት የኤግዚቢሽን አዳራሽ ያሳያል። ቅዳሜ 10 ሰዓት ላይ መክፈቻው ላይ መገኘት በእፍታው ከመገኘት በላይ ባለሙያን ማክበር ነውና የቻላችሁ አትቅሩ። ያልቻላችሁ ዐውደ ርዕይው ክፍት በሆነባቸው ዕለታት ፈጥናችሁ ጎብኙት።

 የምስኪኖቹን መንደር  በስካቫተር  ያፈረሰው ሚሊየነር

በደቡባዊ ቻይና ግዛት የምትገኘው የደሳሳዋ  ዦንኪንግ  መንደር ነዋሪዎች፣ ሸቀጣሸቀጥ ጭነው ከሚመጡ አሮጌ ከባድ መኪኖች ውጭ አንድም መኪና ወደ መንደራቸው ዘልቆ አይተው አያውቁም።  ዛሬ ግን እጅግ ዘመናዊ  መርሰዲስ መኪና  መጥታ ቆማለች።
እናም ነዋሪዎች፣ በመኪናዋ በመንደራቸው  መገኘት በመገረም፣ ዙሪያውን ከበው በማየት ላይ እያሉ፣ አንድ በጠባቂዎች የታጀበ እድሜው በሀምሳዎቹ የሚገመት ሰው ከመኪናው ወጣ። ማንም ደፍሮ ሰላም ሊለው ወይም ሊያናግረው የመጣ ሰው ግን አልነበረም። እናም ሰውየው መንደሩን ለደቂቃዎች ከተመለከተ በኋላ ተመልሶ ወደ መኪናው ገብቶ ሄደ።
ይህ በሆነ በማግስቱ ወደዛች ደሳሳ መንደር ሌላ መኪና መጣ። ከመጡት ሰዎች ውስጥ  የትናንቱ ሰውዬ አልነበረም። በቁጥር በዛ የሚሉ መሀንዲሶች ነበሩ የመጡት። በዚህ ጊዜ ነዋሪዎቹ ነገሩ ገባቸው፤ የትናንቱ  ሰው ባለሀብት መሆኑን በሁኔታው  አውቀዋል፤ እናም ይህን መንደር ሊያፈርስ መሀንዲሶች ልኳል።
እነዚህ  ነዋሪዎች፤ ይህም ኑሮ ሆኖ  ደሳሳ ጎጇቸውን የሚያፈርስ ሰው ይመጣል ብለው መቼም አስበው አያውቁም ነበር። እና ሽማግሌዎች ቀርበው መሀንዲሶቹን አናገሯቸው። ፍርሀታቸው ልክ ነበር፤  ትናንት የመጣው ባለሀብት እዚህ መንደር ላይ ሪል እስቴት መገንባት ፈልጓል፡፡ ለዚህም ከመንግስት ፍቃድ እንዳገኘ፣ ከሰባ በላይ ለሚሆኑት ለመንደሩ ነዋሪዎችም ካሳና መኖሪያ ቤት የሚገነቡበት ገንዘብ እንደሚሰጣቸው፣ እስከዛ ግን በመጠለያ መቆየት እንደሚችሉ፤ እስከ ነገ ድረስም እቃቸውን አውጥተው በተዘጋጀላቸው ማረፊያ እንዲያስቀምጡ ነግረዋቸው  ሄዱ።
ከቀናት በኋላም  ብዛት ያላቸው ግሬደሮችና የህንጻ ሰራተኞች ትንሿን መንደር  አጥለቀለቋት።
ያለቻቸውን አሮጌ እቃ አውጥተው ከቤታቸው አቅራቢያ በተዘጋጀላቸው መጠለያ ውስጥ የገቡት የዦንኪንግ መንደር ነዋሪዎች፤  ቆመው እያዩ ለዘመናት የኖሩባቸው ደሳሳ ጎጆዎች በስካቫተር ፈረሰ።
ቃል የተገባላቸው ቤት መስሪያ ቦታም ሆነ ካሣ ሳይሰጣቸው ለወራት በመጠለያ እየተረዱ ቆዩ። ከዓመታት በፊት ከነሱ ብዙም በማይርቅ ቦታ የሚገኙ መንደሮች ልክ እንደነሱ በጨካኝ ባለሀብት ተፈናቅለው  መሰደዳቸውን እያስታወሱ፣ እጣ ፈንታቸውን መጠባበቅ ጀመሩ።ይህ በሆነ በጥቂት ወራት ውስጥም የባለሀብቱ ዘመናዊ ቪላዎች ተገንብተው ተጠናቀቁና፣ ነዋሪዎቹ በሥነስርአቱ ላይ እንዲገኙ፣ በፕሮግራሙም ላይ  ለነሱም ቃል የተገባላቸው ካሣ እንደሚሰጣቸው ተነገራቸው። ብዙዎቹ ነዋሪዎች ግብዣውን ተቃወሙ። ትንሿ የዦንኪንግ መንደር ዛሬ በልዩ ሁኔታ ደምቃለች። ከሰባ በላይ ዘመናዊ መኖሪያዎችን ለመመረቅ የተለያዩ እንግዶች ተገኝተዋል። ያቺ የድሆች መንደር፣ አይታ በማታውቀው ሁኔታ በዘመናዊ መኪኖችና በሀብታሞች ተጥለቅልቃለች።
የምረቃው ፕሮግራም ተጀመረ።
ያ፤ በመጀመሪያ ቀን መርሰዲስ መኪና ይዞ ወደዚህ መንደር የመጣው ባለሀብት፣ ንግግር ለማድረግ ወደ መድረኩ ወጣ።
“ክቡራንና ክቡራት የዦንኪንግ መንደር ነዋሪዎችና  ክቡራን እንግዶች፤ ዛሬ ልዩ የሆነውን ይህን የዘመናዊ መኖሪያ ቤት ፕሮጀክት ለመመረቅ ስለተገኛችሁ አመሰግናለሁ። እኔ የማየው ዛሬ ሚሊየነር መሆኔን አይደለም። የኔ ሰብዕና የኔ የሀብት ምንጭ ይሄ መንደር ነው።. ... እኔ .....  ትንሽ ልጅ ሆኜ የምታውቁኝ  Xiong Shuihua ነኝ።
 በርግጥ ከዚህ መንደር ከወጣሁ ብዙ  አመታት ተቆጥረዋልና  አላወቃችሁኝም። እኔ ግን ሁላችሁንም አስታውሳለሁ። ለኔና እጅግ ድሆች ለነበርነው ቤተሰቦቼ በየወሩ ቀለብ ይቆርጥልን የነበረው ሚስተር ዣይን፣ ከልጆቻቸው እኩል ልብስ ይገዙልኝ የነበሩት የሚስ ታዮኒ ቤተሰቦች፣ ሲርበን የሚያበሉን የዚህ መንደር ነዋሪዎች---ሁላችሁንም አስታውሳለሁ።  “የኔ የአሁን ህይወት ላይ የመሰረት ድንጋይ ያስቀመጣችሁት እናንተ ናችሁ።
ለዚህም ነው መንደሩን ለመለወጥና የተሻለ ህይወት እንድትኖሩ ለማሰብ እዚህ የተገኘሁት። እናም እነዚህ ቤቶች የተሰሩት ለናንተ ነው። ያለምንም ክፍያ በእነዚህ ቤቶች ትኖራላችሁ።
ቤቶቹ ንብረቶቻችሁ ናችሁ። በነጻ የተሰጧችሁ አይደሉም፤ ከአመታት በፊት ለኔና ለቤተሰቦቼ መልካም ነገር በማድረግ  ኢንቨስት አድርጋችሁበታል።” እያለ እንባ እየተናነቀው  ሲናገር፣ የመንደሩ ሰዎች በሙሉ በታላቅ ድንጋጤ ውስጥ ሆነው ይሰሙት ነበር።
ባለሀብቱ ንግግሩን ቀጥሏል፡-
“እናም ከሀምሳ ሚሊዮን ዶላር በላይ ወጭ ተደርጎባቸው የተሰሩት እነዚህ ቤቶች፣ በፈረሱት ቤቶቻችሁ ቁጥር ልክ የተሰሩ ናቸው፤ ነገ አዳዲስ የቤት እቃዎች የጫኑ መኪኖች ይደርሳሉ። መብራትና ውሀም  አትከፍሉም። መስራት ለምትችሉ የስራ እድል ይዘጋጃል፤ ለአቅመ ደካሞችና ማብሰል ለማይችሉ  ደግሞ ዘመናቸውን ሙሉ የሚፈልጉትን መርጠው የሚመገቡበት መመገቢያ አዳራሽም ተገንብቷል። የናንተ ውለታ ከዚህም በላይ ነው፡፡” አላቸውና፤ ከመድረኩ ወረደ።
በሌላ ሀገር፣ አንድ ግለሰብ ለወገኖቹ  ይህን ያህል ያስባል፤ በኛ ሀገር ደግሞ  የምስኪኖች ቤት ሀላፊነት ሊሰማው በሚገባ የመንግስት አካል  ፈርሶ ቤተሰብ ሜዳ ላይ ይበተናል። ልዩነታችን ይህን ያህል ነው።
(ዋስይሁን ተስፋዬ)

======================================

ኢትዮጵያ ከ20 ዓመት በኋላ ምን አይነት ዜጋ ይኖራት ይሆን?


በቤተ ክርስቲያን አካባቢ፣ በምግብ ቤቶች፣ በትራንስፖርት መሰለፊያዎችና በየመንገዱ ላይ የመንገደኛውን ልብስ ይዘው ‹‹ጋሼ ዳቦ ግዛልኝ›› የሚሉትን…. በአጠቃላይ ከወላጆቻቸው ጋርና ብቻቸውን ልመና ላይ የወደቁ ልጆች ባየሁ ቁጥር እነዚህ ጥያቄዎች ይመጡብኛል፡፡
ዓለም ከዓመታት በኋላ አሁን ከምናየው የረቀቀ ቴክኖሎጂ በላይ አስገራሚ ነገሮችን ታሳያለች፡፡ በውጭ አገራት የምናያቸውና የምንሰማቸው የሥልጣኔና የቴክኖሎጂ ምጥቀቶች አስደማሚ ናቸው፡፡
ኢትዮጵያስ ከዓመታት በኋላ ምን አይነት ዜጋ ይኖራት ይሆን?በብዙ የገጠር አካባቢዎች ትምህርት ቤቶች ተዘግተዋል፡፡ ነዋሪዎቹ በሰላም እጦት እየተሰደዱ በከተማ  ልመና ላይ ናቸው፡፡ ሕጻናቱ ከትምህርት ውጭ ናቸው፡፡ እነዚህ ዛሬ በየጎዳናው ዳርቻ የወዳደቁ ልጆች፣ ከዛሬ አሥራ ምናምንና ሃያ ዓመታት በኋላ ወጣቶች ናቸው፡፡
አገር ተረካቢ የሚሆኑ ናቸው፡፡ አገር ተረካቢ ማለት የግድ ሥልጣን መያዝ ብቻ አይደለም፡፡ በየትኛውም ደረጃ መኖር  አገር ተረካቢነት ነው፡፡ ከዓመታት በኋላ አገር የሚረከቡ እነዚህ ልጆች ናቸው፡፡
ከዓመታት በኋላ የዓለም አገራት አስደናቂ የሥልጣኔ ደረጃ ላይ ሲደርሱ፤ መጻፍና ማንበብ የማይችል  ሕዝብ የሚኖራት አገር ምናልባትም ኢትዮጵያ ብቻ ልትሆን ትችላለች!
(ዋለልኝ አየለ)


ባለፉት አሥርታት ብዙ አስደናቂ ሰባኪዎች ታይተዋል። የኬንያው ፓስተር ማኬንዚ ግን ይለያል።
ተከታዮቹን፣ “በፍጥነት በረሃብ ሙቱና ኢየሱስን አግኙት” ብሎ ይነግራቸዋል፡፡ ያላቸውን ሳይጠራጠሩ ያደርጋሉ።
ብዙዎቹ ተከታዮቹ ታዲያ ከገጠሪቱ ኬንያ የመጡና  ችግር ያቆራመዳቸው ናቸው። ያለቻቸውን ጥሪት፣ የእርሻ መሬትና  ጎጆ ለእርሱ ቤተ ክርስቲያን ተናዘውለት ይቺን ዓለም ይሰናበታሉ።
ፓስተሩ በአስተምህሮው ርህራሄን አያውቅም። ሕጻናት ጭምር በረሃብ እንዲሞቱ ያበረታታል። ልጇ ‘ኢየሱስን እንዲያገኝ’ የጓጓች እናት፤ የምትወደውን የአብራኳን ክፋይ በረሃብ ጠብሳ ሕይወቱ እንድታልፍ ታደርጋለች።
ይህ እንዴት ሊሆን ይችላል? ምን ብሎ ምዕመኑን ቢሰብክ ነው ነፍሳቸውን ለእርሱ የሚሰጡት? በምን ጥበብ ነው የምዕመንን አእምሮ በዚህ ደረጃ ማጠብ የሚቻለው?
(BBC)

ሦስቱ መርሆች፣ የመታቀብ መርሆች ናቸው። ከአላስፈላጊ ጦርነት መታቀብ፣ ኢኮኖሚን አለማደናቀፍ፣ በነውጠኛ ፖለቲካ አገርን አለመረበሽ።
“አዲስ የዓለም ሥርዓት እንፈጥራለን” የሚሉ ንግግሮች ዛሬ ዛሬ ወሬና ምኞት ብቻ አይደሉም። በርካታ አገራት፣ ዓለምን የሚቀይር የኢኮኖሚ አቅምና ወታደራዊ ጉልበት እያገኙ ነው። የቀድሞዋ ራሺያ አለች። ቻይና ደግሞ መጥታለች። ቻይና፣ ራሺያና ኢራን የጋራ የጦር ልምምድ ሲያካሂዱ ማየት፣ ራሱን የቻለ አዲስ ታሪክ ነው። በዚያ ላይ፣ የዛሬዋ ሕንድ፣ የድሮዋ ሕንድ አይደለችም።
ሕንድ፣ በሕዝብ ብዛት፣ ዘንድሮ ከቻይና በልጣለች የሚል ዜና አልሰማችሁም? አዎ፣ የሕዝብ ቁጥር ብቻውን፣ ኃያልነትን አያስገኝም። ከኢኮኖሚ እድገት ጋር ሲሆን ግን፣… ያው የማባዛት ጉዳይ ነው። የመቶ ዶላር አመታዊ የገቢ እድገት፣ በ1.4 ቢሊዮን ሲባዛ፣ ብዙ ነው። ኑሮን ያሻሽላል። ግን ደግሞ፣ ወታደራዊ አቅም ለማፈርጠምም ያገለግላል። የደርዘን አገራት የመከላከያ በጀት፣ አንድ ላይ የመደመር ያህል ነው።
ብዙ የሕዝብ ቁጥርና የኢኮኖሚ እድገት ሲገጣጠም፣ በጎ ጎኑ ብዙ ነው። ለሌሎች አገራትም ሰፊ ገበያ ይፈጥራሉ። ችግሩ ምንድነው? ፀበኛና ጦረኛ መሆን ለሚፈልጉ መንግስታት፣ አመቺ እድል ይሆንላቸዋል። ለጦር ኃይልና ለጦርነት የሚውል ገንዘብ በብዛት ያገኛሉ። እናም፣ትልልቅ አገራት፣ አደገኛ አገራት ይሆናሉ።  
ዛሬ፣ የዓለማችንን “የኃይል” ሚዛንና አሰላለፍ የሚቀይሩ ክስተቶች በዝተዋል። የታሪኩ መነሻ ግን፣ የዛሬ 45 ዓመት የተፀነሰው የቻይና ሕዳሴ ነው።
ለወትሮ የብዙ አገራት ስጋት ከቻይና ሳይሆን ከራሺያ በኩል ነበር። ዛሬ ግን፣ ቻይናን በቀጥታ ወይም በተዘዋዋሪ የማይፈራ አገር፣ ወይ ተስፋ የቆረጠና “የመጣው ይምጣ” ብሎ የተቀመጠ ነው። ወይ አላዋቂ ነው። ወይም… ዓለም ሲተራመስ ከዳር ሆኖ ለማየት የሚያስመኝ ክፉ መንፈስ? ለማንኛውም፣ በጥቂት ዓመታት ውስጥ ነፍስ ዘርቶ በፍጥነት እየገዘፈ የመጣው የቻይና ኃያልነት፣ የዓለምን “አሰላፍ” የሚያናጋ ትልቅ ክስተት ነው።
በእርግጥ፣ የኃያልነቷ ምስጢር፣ መጥፎ ስለሆነ አይደለም።
በጃፓን እንደታየው፣ ስርዓት አክባሪ ነባር የባሕል ቅኝት፣ ለቻይናም ጠቅሟል። የጨዋነት ዝንባሌና ስርዓት አክባሪ ልማድ፣ ሁልጊዜ ይጠቅማል ማለት አይደለም። አንዳንዴ፣ ስርዓት አክባሪ ልማድ፣ ለመጥፎ ስርዓት አመቺ ይሆናል - ለምሳሌ ለኮሙኒዝም። ግን ደግሞ፣ ወደተሻለ ስርዓት ለመሸጋገርም፣ ይጠቅማል። እንዲህ አይነት እድል በቻይና አጋጥሟል - የዛሬ 45 ዓመት።
ወደተሻለ ስርዓት የመሸጋገር እድል የተፈጠረው፣ የሦስት መርሆች ጥምረት አማካኝነት እንደሆነ የዴንግ ዚያዎፒንግ አማካሪ ይገልጻሉ።
አንደኛ፣ አላስፈላጊ ጦርነት ውስጥ አለመግባት።
ሁለተኛ፣ ኢኮኖሚን የሚያበለጽጉ የነጻ ገበያ አሰራሮችን ማስፋፋት።
ሦስተኛ፣ መስመር የያዘ የፖለቲካ መረጋጋት።
ዴንግ ዚያዎፒንግ፣ የቻይና ትንሣኤ አብሳሪ ወይም የህዳሴዋ ደወል ተብለው የሚጠቀሱ መሪና የአገሪቱ ፕሬዚዳንት ናቸው። የማዖ ዜዱንግ የአብዮትና የነውጥ ዘመን በኋላ ማለት ነው።
ሦስቱም የዚያዎንግ መርሆች፣ “ችግር ከመፍጠር መታቀብ!” ብለን ልንገልጽላቸው እንችላለን። መንግስት በዜጎቹ ላይ እንቅፋቶችን ከመደርደር ከታቀበ፤ ብዙ ሸክሞች ይቃለላሉ።
አዎ፣ ሽፍቶችና አማፂዎች፣ ተቃዋሚዎችና ተቀናቃኞችም አገርን ሊረብሹ ይችላሉ። ደግሞም በተደጋጋሚ አይተናል።
ደግነቱ፣ ስርዓት አልበኞች ሲበጠብጡ፣ ወንጀለኞች ሲያጠፉ፣ መፍትሔ አይጠፋም። ህግና ስርዓትን ማስከበር፣ አገርን ማረጋጋትና ሰዎችን ከጥቃት መጠበቅ ነው የመንግስት ስራ። የመንግስት አካላት፣ ነውጠኛ ሲሆኑ ነው ችግሩ። አዎ፣ ነውጠኛ ተቃዋሚዎችና አመፀኞችም፣ አደጋ ያመጣሉ።
በዓመቱ የመጀመሪያ ወራት ላይ እንደታዘብነው ግን፣ የመንግስት ባለስልጣናትና የገዢው ፓርቲ ጎራዎች  በየእለቱ የቀውስ ሰበብ ሲፈጥሩ፣ አደጋው ከሁሉም ይብሳሉ።
ታዲያ፤ “ችግርና እንቅፋት ከመፍጠር መቆጠብ” የሚለው ሃሳብ ትልቅ ቁምነገር መሆኑ ይገርማል?
አስቡት። “በመታቀብ” ብቻ ፍሬያማ መሆን! እውነት አይመስልም። ግን እውነት ነው። ከማፍረስ መታቀብ፣ ግንባታን ከማደናቀፍ መቆጠብ ነው። የሰዎችን ኑሮ ማክበር፣ ንብረታቸውን መጠበቅ፣ ሕግና ስርዓትን ማክበር ማለት ነው- አደናቃፊ  አለመሆን ማለት። መንግስት የአገራቱ ኢኮኖሚና የሰዎች ኑሮ በዋጋ ንረት አለማናጋት ማለት ነው። መንግስት አለስራው አለቦታው ከመግባት ሲታቀብ፣ ትክክለኛ ሃላፊነቱን የማከናወን አቅምና ጊዜ ይኖረዋል። ይህ አንድ  ዚያዎፒንግ መርህ ነው። “ሁሉም ነገር የመንግስት፣ ሁሉም እንቅስቃሴ በመንግስት ይሁን” ተብሎ አላዋጣም። እናስ ምን ተደረገ?  በመንግስት ትዕዛዝ በግዳጅ የተመሰረቱ “የጋርዮሽ የእርሻ ማህበራት” እየፈረሱ ገበሬዎች የየግል ማሳቸውን እንዲያለሙ፣ የምርታቸው የግል ባለቤት እንዲሆኑ፣ መሸጥም እንዲችሉ ተፈቀደ፡፡ ሚሊዮኖችን እየፈጀ ቻይናን እንደራሱ ግዛት እየነገሰባት የነበረ የረሃብ መከራ፣ በጥቂት ዓመታት ውስጥ ባይጠፋም ተቃለለ፡፡ “ተዓምር” ነው። መንግስት እጁን ሲሰበስብ ማሳዎች ያፈራሉ።
የግል ቢዝነስና ንግድ፣ ቀስ በቀስ እየተፈቀደና እየተስፋፋ ሲመጣስ፣ ቻይና የዓለም ፋብሪካ ትሆናለች ብሎ ማን አሰበ?… በቅድሚያ በሆንክኮንግ፣ በሲንጋፓርና በታይዋን አቅራቢያ ነው የኢንዱስትሪ መንደሮችና ከተሞች እየተበራከቱ፣… ከጊዜ ወደ ጊዜ በቁጥርና በጥራት፣ በዓይነትና በግዝፈት እየጨመሩ፣… የአገሪቱ አንቂ ሞተሮች ሆነዋል።
ደግነቱ ደግሞ መንግስት ትንሽ በትንሽ እጆቹን ከኢኮኖሚ ውስጥ አውጥቶ ሲሰበስብ ፍሬያማ ውጤት በግል ቢዝነስ ሲበረክት፣… በቃ አልተባለም። የነፃ ገበያ አሰራሮችን ለማስፋፋት ተጨማሪ ማሻሻያዎች ተከናውነዋል።
በጃፓን፣ በደቡብ ኮሪያና በታይዋን የታየው የብልፅግና “ተዓምር” በቻይናም ብቅ ሲል ታየ። ያው፣ከጊዜ በኋላ፣ ቻይና የዓለማችን ፋብሪካ የምትባልበት ደረጃ ላይ ደርሳለች፡፡ የዴንግ ዚያዎፒንግ የኢኮኖሚ ማሻሻያ ሃሳቦች የካፒታሊዝምን መስመር የተከተሉ ናቸው። ነገር ግን፣ የነፃ ገበያ ስርዓትን እንደመርህ በመቀበል ሳይሆን፣ እንደጠቃሚ የብልፅግና ዘዴና አሰራር በመቁጠር ሊሆን ይችላል፡፡
ቢሆንም፣ በዚያው ልክ ፍሬያማ መሆናቸው አልቀረም፡፡ ሦስተኛው የዚያዎፒንግ መመሪያ፣ ሥርዓትና መስመር የያዘ የፓለቲካ እርጋታ ለቻይና ህዳሴ ያስፈልጋል የሚል ነበር፡፡
የፓለቲካ እርጋታ ያለ ሥርአትና ያለመስመር በጉልበት ወይም በብልጠት ብቻ አይመጣም፡፡
አገሪቱ ደግሞ፣ ለበርካታ ዓመታት እርጋታ እጅግ የናፈቃት የግርግር ምድር ሆናለች። ተማሪዎች በአስተማሪዎች ላይ ዘምተዋል። ከሳሽ፣ ምስክርና ዳኛ ሆነው ይፈርዱባቸዋል። መደበኛ ፍርድቤቶች ተዘግተዋል።
ሰራተኞች በአለቆችና በባለስልጣናት ላይ አባራሪና አሳሪ ሆነዋል። ጎረቤት በጎረቤቱ ላይ ይፈርዳል።
ህግና ሥርዓት የማይገዛው፣ የግለሰብ መብቶችን በማስከበር ላይ ያልተመሰረተ ገደብ የለሽ ዲሞክራሲ ማለት የያኔውን ትርምስ ይመስላል።“በማያቋርጥ የአብዮት ለውጥ” የተናወጠው አገር፣ እርጋታን ይሻል። እንደገና እንዳይናወጥ ደግሞ ሥርዓትና መስመር ያለው እርጋታ ያስፈልገዋል።
የዚያዎፒንግ የእርጋታ መርህ  ይህን እውነታ የተገነዘበ ነው። በተግባር ሲሞክሩትም፣ ሰምሮላቸዋል ማለት ይቻላል።
ከዛሬ 30 ዓመት በፊት፣ የአገሪቱን መንግስትና ገዢውን ፓርቲ የሚያንገራግጭ ዓመፅ የተፈጠረ ቢሆንም፣ ሌላ ቀውስና ነውጥ እስከ ዛሬ አልተከሰተም፡፡ ነገር ግን ሁሉም እርጋታ እኩል አይደለም፡፡
አንድ አገርና መንግስት፣ አንድ ፓርቲና መሪ የሚል ነው የቻይና ኮሙኒስት ቅኝት ወይም ሥርዓት፡፡ ይሄ ይዘልቃል ወይ?
በአንድ በኩል፤ “ሥርዓትና መስመር የያዘ የፓለቲካ እርጋታ” የሚለው የዚያዎፒንግ ሦስተኛ መመሪያ ተሟልቷል ማለት ይቻላል፡፡ በሌላ በኩል ግን፣ “ምን ዓይነት ሥርዓትና መስመር” የሚል ጥያቄ ሊነሳ ይችላል፡፡
የግለሰብ ነፃነትን መነሻና መድረሻ ያደረገ ሥልጡን የፓለቲካ መርህ ላይ የተመሰረተ ህግና ስርኣትም የፖለቲካ እርጋታን ሊፈጥር ይችላል፡፡
የሁሉንም ዜጎች መብት፣ የእያንዳንዱን ግለሰብ ነፃነት የማሰከበር ሃላፊነት የተሰጠው መንግስት፣ ሥልጣኑ ከዚህ ውጭ እንዳይንሰራፋ በህግ የተገደበበት፣ የህግ የበላይነትንና ካፒታሊዝምን ያጣመረ ሥልጡን ፖለቲካ፣ ያለ አፈናና ያለ ነውጥ ለረዥም ዓመታት ሊዘልቅ ይችላል - በአሜሪካና እንግሊዝ እንደታየው፡፡
ፓርቲዎች እየተፎካከሩ፣ ፖለቲከኞች እየተወዳደሩ፣ በምርጫ እየበለጡ፣ በተከታዩ ምርጫ እየተቀደሙ፣ አንዱ እየተሰናበተ ሌላው እየተተካ፣ ያለ ዓመፅና ያለ ጉልበት፣ ያለ ነውጥና ያለ ቀውስ ስልጣን ላይ የሚፈራረቁበት ሥርዓት፣… ከብዙ ጥፋትና ከክፉ አደጋ ሊያድን የሚችል የእርጋታ ሥርዓት ነው ለዚያውም ከትክክለኛ መርህ የመነጨ፡፡
የዚያዎፒንግ ሦስተኛ መመሪያ፣ ይህን ለይቶ የሚገልፅ አይደለም፡፡ “ሥርዓትና መስመር የያዘ የፓለቲካ እርጋታ” የሚል ነው በደፈናው፡፡ የቻይና ኮሙኒስት ፓርቲም ይህን መመሪያ አሟልቼ አሳክቼዋለሁ ሊል ይችላል፡፡ በተወሰነ ደረጃም ብቃቱን ይመሰክርለታል፡፡ እንደሌሎች ገዢ ፓርቲዎች አልተዝረከረከም፡፡
ነገር ግን፣ ተፎካካሪ ፓርቲዎች እንዲመጡበት በፍፁም አይፈቅድም፡፡ ይሄ “በራስ የመተማመን ብቃትን” አያሳይም።
የአንድ ፓርቲ አገዛዝ እስከ መቼ እንደሚያዛልቅም አይታወቅም።
ለጊዜው ግን፣ ሦስቱ መመሪያዎች ለቻይና ይዘውላታል ማለት ይቻላል።
በዚያው ልክም፣ የኢኮኖሚ ብልፅግናንና ኃያልነትን የሚያስገኙ መንገዶች ሆነውላታል- የሕዳሴ መርሆች።
ወደ ጦርነት አለመሮጥ፣…
በነፃ ገበያ አሰራር ኢኮኖሚን ማበልፀግ፣…
 ሥርዓት የያዘ የፖለቲካ እርጋታን ማስፈን፣…
በእነዚህ መርሆች አገሪቱ የብልፅግና ፍሬዎች ከበረከቱላት በኋላ፣… በዓለማቀፍ ንግድ እየጎለበተች በቴክኖሎጂው መስክም  ከዋና ተዋናዮች ጎራ እየተቀላቀለች፣ በዓለማቀፍ ዲፕሎማሲ ከፍተኛ ጉልበት እያገኘች፣ በወታደራዊ አቅምም ኃያልነትን እየተላበሰች ስትመጣ፣… አደገኛ የጦርነት ስጋት ሆና መታየቷ ነው ትልቁ ችግር።
የአሜሪካ ወይም የአውሮፓ መንግስታት እንዳሻቸው ጦርነት ማወጅ አይችሉም። ከዓለም ዙሪያ ብቻ ሳይሆን በአገር ውስጥም ከፍተኛ ተቃውሞና ትችት ይገጥማቸዋል። እንደ ቻይና እንደ ራሺያ የመሳሰሉ አገራት ውስጥ ግን፣ ተቃውሞዎችንና ትችቶችን ዝም ማሰኘት ይቻላል። አደጋውም እዚህ ላይ ነው።
አዎ፤ የዚያዎፒንግ የቁጥብነትና የመታቀብ መርህ፣ እስካሁን ሰርቷል።
ይበልጥ አስፈላጊ የሚሆነው ግን ከእንግዲህ በኋላም ነው።
ድሮ የኢኮኖሚ አቅም ሳይኖር፣ ፀበኛና ጦረኛ ከመሆን መቆጠብ ብዙም አያስቸግር ይሆናል። ወታደራዊ ጡንቻ ከፈረጠመ በኋላ ግን፣ አላስፈላጊ ፀብና ጦርነት ውስጥ ላለመግባት መጠንቀቅ፣ ከባድ ፈተና ሊሆንባቸው ይችላል።
ይህም ብቻ አይደለም። ከኢኮኖሚ እድገት ጋር አብረው የሚመጡ ሌሎች ፈተናዎችም አሉ። የኢኮኖሚ ነፃነትን የሚመጥን የፖለቲካ ነፃነትና የመከባበር ሃላፊነት፣… የሥልጡን ፖለቲካ ማሻሻያና ከዚሁ ጋር የሚጣጣም ነባሩን ልማድ የሚያዳብር የባህል ቅኝት ያስፈልጋል። ይህ በዛሬ ዘመን አስቸጋሪ ነው። እጅግ ከባድ ጥበብና ትጋትን ይጠይቃል።
ከዚያ ይልቅ፣ ዜጎችን በጭፍን ስሜት በማነሳሳትና በፀበኝነት መንፈስ ሰዎችን በመቀስቀስ የሕዝብ ድጋፍ ለማግኘት መሞከር በጣም ቀላል ሆኖ የሚታያቸው ፖለቲከኞች ይኖራሉ። በእርግጥም ቀለል ይላል።
ከማረጋጋት ይልቅ መረበሽ፣ ከመገንባት ይልቅ ማፍረስ፣ ከማስተማር ይልቅ ማስጮህ ቀላል ነው።
ግን ምን ዋጋ አለው? ኢኮኖሚን ያናጋል፤ እርጋታን ያጠፋል፤ በአላስፈላጊ ፀብና በጦርነት ከንቱ እልቂትና ውድመትን ይበረክታል። ከእነዚህ ለመሸሽ ነበር የሦስቱ መርሆች አላማ። ለአገራችንም ይሰራሉ። በቂ ባይሆኑም።


ከዚህ ቀደም በለቀቃቸው 12 የኦሮምኛ ምርጥ ነጠላ ዜማዎቹ ተወዳጅነትን ያተረፈው ድምፃዊ አደም መሀመድ የመጀመሪያ ሙሉ ስራ የሆነው “ኦሮሚያ” አልበም ዛሬ በሂልተን ሆቴል በድምቀት ይመረቃል፡፡ ድምፃዊውና የአልበሙ አስመራቂ ኮሚቴ አባላት በሳምንቱ መጀመሪያ ላይ በኬና ሆቴል በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ እንዳብራሩት፤ አልበሙ 14 ዘፈኖችን የያዘ ሲሆን የሁሉንም የኦሮሚያ አካባቢዎች ባህል፣ ተፈጥሮና እሴት የሚዳስስ በመሆኑ መጠሪያው “ኦሮሚያ” ተብሏል።
102 ሚሊዮን ብር የወጣበትና ተሰርቶ ለመጠናቀቅ 5 ዓመታን የፈጀው አልበሙ፤ ሚክሲንግና ማስተሪንግ የተሰራው በእውቁ የሙዚቃ ሰው አበጋዝ ክብረ ወርቅ ሺዎታ ሲሆን ግጥምና ዜማ ላይ ድምፃዊ አደም መሃመድና መኮንን ለማን ጨምሮ በርካቶች ተሳትፈውበታ ተብሏል፡፡
በዚህ አልበም ምርቃ ላይ በርካታ ድምፃዊያን፣ ታዋቂ ሰዎች፣ የመንግስት የስራ ሃፊዎችና ጥሪ የተደረገላቸው እንግዶች የሚገኙ ሲሆን የተለያዩ የመዝናኛ ፕሮግራሞ እንደተዘጋጁ ተገልጿል። ድምፃዊ አደም  መሀመድም ከቀድሞ ነጠላ ዜማዎቹና ከአዲሱ ስራው የተመረጡ ዘፈኖችን እንደሚያቀነቅን ታውቋል።

አንድ የስፓኒሾች ተረት አለ፡፡
ከዘመናት በፊት አንድ ንጉስ፣ ያለ የሌለ ገንዘቡን አዳዲስ ልብስ በማሰፋት ያጠፋ ነበር፡፡ ወደ አደባባይ አዲስ ልብስ ለብሶ ብቅ እንደማለት የሚያስደስተው ነገር የለም፡፡ አዲስ ልብስ ከመውደዱ የተነሳ “ሌሎች ንጉሶች ወደ ጦር ሜዳ ሲውሉ፣ ፈረስ ጉግስ ሲጫወቱ፣ እሱ ከመልበሻ ክፍል ውስጥ ይገኛል” እየተባለ ይታማ ነበር፡፡  
አንድ ቀን ሁለት ብልጥ ሸማኔዎች ወደ ንጉሱ ከተማ ይመጣሉ፡፡ ምርጥ ልብስ ለመስፋት እንደሚችሉም ይናገራሉ፡፡ በተለይም ደግሞ እነሱ የሚሰሩት ልብስ፤ ሌቦች የሆኑ እና የስራ ብቃት የሌላቸው ሰዎች ሊያዩት የማይችሉት ተዓምረኛ የሆነ ልብስ መሆኑን በኩራት ያስረዳሉ፡፡ የዚህ ተዓምረኛ ልብስ ወሬ ንጉሱ ጆሮ ይደርሳል፡፡ ንጉሱም “እንዲህ ያለ ልብስ ቢኖረኝ እኮ፣ ይታይሃል አይታይህም እያልኩ የትኛው ባለስልጣን ሌባና ለስራው ብቃት የሌለው መሆኑን ለማረጋገጥ እችላለሁ” ሲል ያስብና ሁለቱንም ሸማኔዎች አስጠርቶ  ብዙ ገንዘብ ሰጥቶ፣ “በሉ በልኬ ልብስ ስሩልኝ!” ሲል ያዛቸዋል፡፡
ልብስ ሰፊዎቹም የሸማኔ እቃቸውን ዘርግተው ሲያበቁ እጅግ ውድ የሆነ ሀርና ወርቅ እንዲቀርብላቸው ይጠይቃሉ፡፡ ያሉት ይፈጸምላቸዋል። ያንን ሃርና ወርቅ ይደብቁና እንደሚሸምን ሰው ባዶ እጃቸውን እያንቀሳቀሱ እስከ እኩለ ሌሊት ድረስ ይቆያሉ፡፡
 የስራቸው ሁኔታ የት እንደደረሰ ለማወቅ የፈለገው ንጉስ፣ ወደ ሸማኔዎቹ ሊሄድ ፈለገ። “ድንገት ተዓምረኛው ልብስ አልታይ ካለኝስ?” በሚል ስጋት እራሱን ተጠራጠረና ሁለት ታማኝና ለስራ ቦታቸው ብቃት አላቸው የሚላቸውን ባለስልጣኖቹን “ሂዱ እስቲ አጣሩና ኑ!” ብሎ ይልካቸዋል፡፡ ሁለቱ ባለስልጣኖች ሸማኔዎቹ ክፍል አጠገብ ሲደርሱ፣ “አንተ ግባ! አንተ ግባ!” በመባባል ይጣላሉ፡፡ በመጨረሻ እጣ ያወጣሉ፡፡ እጣ የወጣለት ቀድሞ ይገባል፡፡ ሸማኔዎቹ ባዶ እጃቸውን እያወናጨፉ ስራ ቀጥለዋል፡፡ ባለስልጣኑ ምንም ልብስ አይታየውም፡፡ አይኑ እስኪፈርጥ ከፍቶ ተመለከተ፡፡ ምንም ልብስ የለም፡፡ ሸማኔዎቹም “ጌታዬ እንዴት ያለ ግሩም ቀለም ያለው ምርጥ ልብስ አይታይዎትም? ቀረብ ይበሉና ያስተውሉት?” ሲሉ ይጠይቁታል፡፡ ባለስልጣኑም “አሁን እኮ ይሄ ልብስ አይታየኝም ብል ሌባና ለስራው ብቁ ያልሆነበት ሹመት ላይ የተቀመጠ ሰው ነው ልባል ነው” ሲል ያስብና “እጅግ ድንቅ ልብስ ነው! ይህንኑ ለንጉሱ እነግራቸዋለሁ። በበኩሌ ስራችሁ በጣም አድርጎ አስደስቶኛል!” ሲል ይዋሽና ይወጣል፡፡ ሁለተኛው ባለስልጣንም ልክ እንደ በፊተኛው ባለስልጣን ያለ ሁኔታ ያጋጥመዋል፡፡ ግን እሱም “ሌባና ለስራው ብቃት የሌለው ነው” እባላለሁ ይልና “ግሩም ድንቅ ልብስ ነው!” ብሎ ይመልሳል፡፡
ሁለቱም ባለስልጣኖች ለንጉሱ ከዚህ ቀደም ታይቶ የማይታወቅ አይነት ልብስ እየተሰራ መሆኑን ይናገራሉ፡፡ ንጉሱ ይደሰታል፡፡ ሸማኔዎቹ ተጨማሪ ብርና ሃር እንዲሁም ወርቅ ይጠይቃሉ፡፡ ንጉሱ በደስታ ይፈቅዳል፡፡ እንደገናም ሌሎች ባለስልጣኖች ይልካል፡፡ መልሱ የተለመደ ይሆናል፡፡ እንደውም በክብረ በአሉ ወቅት በአደባባይ ለብሶ መታየት እንዳለበት ከባለስልጣኖቹ ምክር ያገኛል፡፡ ቀስ በቀስ ወሬው ወደ ከተማው ህዝብ ተዛመተ፡፡ በየነገዱ በየጎሳው በየቋንቋው ስለልብሱ ተአምረኛነት ተነገረ፡፡ ንጉሱ ገና ልብሱ ሳያልቅ ለሸማኔዎቹ የወርቅ ሜዳልያ ሸለመ፡፡
ሸማኔዎቹ እያነጉ ይሰሩ ጀመር፡፡ ክብረ በአሉ ከመድረሱ በፊት መጨረስ አለብን እያሉ ሲጣደፉ ይታያሉ፡፡ ልብሱ ግን ለማንም አይታይም፡፡ የተለያየ የልብስ ዲዛይን እንደሰፉ ሁሉ ተራ በተራ ባዶ እጃቸውን እያነሱ መስቀያው ላይ ሲሰቅሉ ይታያሉ፡፡ በመጨረሻም “ልብሶቹ ተሰርተው አልቀዋል!” ሲሉ አወጁ፡፡ የክብረ በአሉ ቀን ንጉሱ ወደ ሸማኔዎቹ በአጀብ መጣ፡፡ ሸማኔዎቹም በተራ በተራ ባዶ እጃቸውን ከፍ እያደረጉ፤ “ይሄው ቦላሌው! ይሄው ኮቱ! ይሄው ሸሚዙ! ይሄው ባለወርቅ ዘቦ ካባ! ይሄው የራስ ማሰሪያው! ከሸረሪት ድር የቀለሉ፣ ለሌባና ለስራው ብቃት ለሌለው ሰው የማይታዩ ምርጥ ልብሶች!” አሉና በኩራት ተናገሩ፡፡ የንጉሱ አጃቢዎች ምንም ባይታያቸውም፣ ሌባና ብቃት የለሽ ከምንባል በሚል “በጣም ምርጥ ልብሶች ናቸው!” አሉ፡፡
ሸማኔዎቹ ወደ ንጉስ ዞረው “ይበሉ ወደ መስታወቱ ይምጡና ይለኩዋቸው!” አሉ፡፡ ንጉሱ ልብሶቹን ሁሉ አወለቀና ወደ መስታወቱ ቀረበ፡፡ ሸማኔዎቹ አንድ በአንድ ልብስ የሚያለብሱ መሰሉ፡፡ በመጨረሻ ንጉሱ ወደ መስታወቱ ዞረ፡፡ በዙሪያው የተሰበሰበ ሰው ሁሉ፤ “ንጉስ ሆይ እንዴት አማረብዎ! ላይዎ ላይ የተሰፋ እኮ ነው የሚመስለው! እንዴት ያለ ቀለም፣ እንዴት ያለ ምርጥ ስፌት!” እያለ አድናቆቱን ገለፀ፡፡ “ሰረገላው ቀርቧል ንጉስ ሆይ!” አለ  ባለሟል፡፡
ንጉሱ “ዝግጁ ነኝ!” አለና አንዴ ወደ መስታወቱ ተመለከተ፡፡ መለመላውን ነው፡፡ ግን - እንዴት ልብሱን አይታየኝ ይበል? “አረረረረ! እንዴት አምሮብኛል ጃል!” እያለ ሰረገላው ላይ ወጣ፡፡ አጃቢዎቹ በክብር ተከተሉ፡፡ ወደ ተሰበሰበው ህዝብ ሲቃረብ ንጉሱ እራቁቱን ተነስቶ ቆሞ እጁን እያውለበለበ ለህዝቡ ሰላምታ ይሰጥ ጀመር፡፡ ህዝቡም፤ “ንጉሳችን እንዴት ያለ ድንቅ ልብስ ለብሰዋል! ታይቶ የማይታወቅ፣ በልካቸው የተሰፋ ምርጥ መጎናፀፊያ!” እያለ አጨበጨበ፡፡ ማንም ምንም ልብስ አይታየኝም ለማለት አልደፈረም፡፡ ሌባና ብቃት የለሽ እንዳይባል ነዋ!
በመካከል ግን አንድ ህፃን ልጅ፡-  “እንዴ! ንጉሱ እራቁታቸውን ናቸው!” አለ፡፡
ይሄኔ የልጁ አባት መተንፈሻ በማግኘቱ “የሰማያቱ ያለ! የዚህን የየዋህ ልጅ ድምፅ ሰማችሁልኝ” ብሎ ልጁ ያለውን አጠገቡ ላለው ሰው ይነግረዋል። ያኛውም “ንጉሱ እራቁታቸውን ናቸው አለ እኮ ያ ልጅ!” ሲል አስተጋባ፡፡ ከመቅፅበት “ንጉሱ እራቁታቸውን ናቸው!” ይል ጀመር የተሰበሰበው ህዝብ፡፡
ንጉሱ ደነገጠ፡፡ ሰው የሚለው እውነት መሆኑን አውቋል። ነገር ግን “ክብረ-በአሉ በወጉ መቀጠልና ማለቅ አለበት!” አለ ለራሱ፡፡ ስለዚህ የበለጠ በኩራት ይንጎማለል ጀመር፡፡ ህዝቡ ቀስ በቀስ እያንሾካሸከ እየተመናመነ ወደ ቤቱ ሄደ፡፡ በግርግሩ ማህል ሸማኔዎቹ ሃርና ወርቁን ይዘው ጠፉ።
***
ኢትዮጵያ እውነቱን የሚናገር ህፃን ልጅ ትፈልጋለች፡፡ ያየውን በግልፅ የሚናገር ሰው ትሻለች፡፡ ከልሂቅ እስከ ደቂቅ ያለው ህዝብ ያልነበረው እንደ ነበረ፣ የሌለው እንዳለ አድርጎ የሚያምንበት ሥርአት ከተፈጠረ አገር ከፍተኛ አደጋ ላይ ናት ማለት ነው፡፡ ንጉሱም፣ መኳንንቱም የሌለ መጎናፀፊያ ተላብሰው፤ በተራቆተች አገር ላይ፣ የተራቆቱ ባለስልጣናት፣ የተራቆተ ህዝብ የሚመሩበት የእውር - የድንብር እና፣ የአስመስሎ ማደግ ዘመን ውስጥ ይኖራል ማለት ነው፡፡ ከዚህ ይሰውረን! እርቃኑን ያለውን የሀገር ኢኮኖሚ በሸማኔዎች ተዓምራዊ ልብስ መሸፈን እንደማይቻል በግልፅ እያየን ነው፡፡ ይህን ቀደም ብለው ያዩ፣ የማስጠንቀቂያ ደውል የደወሉ አያሌ እንደነበሩን አይተናል- የሚሰማ ጆሮ ቢያጡም፡፡ “አስደንጋጭ የድህነት አደጋ”፣ “የመበተን አፋፍ” የአንድ ጀምበር እርቃናችን አይደለም፡፡ አገርም በአንድ ምሽት እንደማትገነባ ሁሉ በአንድ ምሽት የማስጠንቀቂያ ደውል አትፈረካከስም፡፡ ሙሰኛ ሁሉ ሌብነቱና የስራ ብቃት ማጣቱ እንዳይታወቅበት “በሀር አሽማት ወገቧን!” ሲላት እንዳልከረመ፣ ሲጨንቀው ደግሞ “አገር ያየህ ና ወዲህ በለኝ!” ማለቱ ሳይታለም የተፈታ ጉዳይ ነው፡፡ በአንፃሩ ነገሩ ሁሉ በመጨረሻ ሰአት “ከፊት አጫውተው፣ ከኋላው ዝረፈው!” ለመሆኑ የሀገራችን የለውጥ ዋዜማ ሰአታት ሁሉ የእርዱን ጥሪ መርዶ ሲነግሩን እንደሰነበቱ አንዘነጋም፡፡ ያለፉት የሀገራችን መሪ “መርከቡ ሲሰጥም አይጦች ከየጉሬያቸው ብቅ ይላሉ” ብለው ነበር ፡፡ ዛሬ የምንሰማው ደግሞ “የሚሰምጥ ሰው ሳሩንም ቅጠሉንም ለመጨበጥ ይፍጨረጨራል” የሚል ነው፡፡ (A drowning man catches a straw ነው ነገሩ) የኢኮኖሚያችን የመጨረሻ እንጥፍጣፊ የድህነታችን ልዩ አዋጅ በሆነበት በአሁን ሰአት፣ ከቶ መመለሻውና ማጣፊያው ያጠረበት የራቁት ጉዞ ይመስላል፡፡ የመበታተንና የድህነት አደጋ ጎላ ብሎ መገለፁ ለሌላ ኢላማ ቢሆንስ ብሎ መጠራጠር ግን መቼም አይቀሬ ነገር ነው፡፡ ስር በሰደደና በብሩህ መንገድ ሳይገለፅ የሰነበተ የብራ-መብረቅ ይመስላልና ለምን አሁን ድንገት ናዳ ወረደ ማለት የአባት ነው፡፡
የፖለቲካ ድርጅቶች እርቃንዋን የቆመችውን አገር ከመቀመቁ ለማውጣት ምን እናድርግ ከማለት ይልቅ የ“ማን ይምራት ማን ይምራት” የሃሳብ አውጫጭኝ ላይ ያተኮሩ ይመስላል፡፡ ይህም ሌላ እርቃን ነው፡፡ የአዲስ ልብስ ሽመናውን የተያያዙ ብልጣ ብልጦችም፣ የማይታይ ተዓምራዊ ልብስ እንሰራለን የሚል ማስታወቂያ እያስነገሩ የሚገበዙ ይመስላል፡፡ ያደረ-አፋሽ የሚመስሉ አዲስ ድግ በአሮጌ ወገብ ላይ ያሰሩ የሚመስሉ ቡድኖችንም የስልጣን ዛር ያገረሸባቸው ይመስላል፡፡ ባለሟሉም፣ ባለስልጣኑም፣ ንጉሱም፣ህዝቡም ፓርቲዎቹም የማይታየውን ልብስ ለመደረብ ከመጣር ይልቅ እርቃናችንን ቀርተናል እና፣ ሌባውን “ሌባ ነህ!” ብለን፣ ብቃት የሌለውን “ብቃት የለህም!” ብለን የተራቆተችውን አገር ፖለቲካዊ ልዩነትን አቻችሎ ለኢኮኖሚ ድቀቷ መፍትሄ መሻት አንገብጋቢ ነው፡፡ ከእንግዲህ ጩኸቴን ቀሙኝ ብሎ መጮህ ሌላ ጩኸት እንጂ ሁነኛ መፍትሄ አያመጣም፡፡
በአንድ ወገን በመዋቅርም ከመዋቅርም ውጪ “የመነኩሲት ምርኩዝ፣ ከላይ ባላ ከታች ዱላ” እንዲሉ ሰራተኛው መከፋቱ፣ በሌላ ወገን “ስለ ሃብታም ይሰበሰቡና በደሃ ላይ ይፈርዳሉ” እንዲሉ፤ የአብዬን ለእምዬ (Blame-shifting ) እየበረከተ እውነተኛው ድህነት ምናችን ጋ እንደሆነ እንዳናይ መሆናችን መባባሱና የወትሮውን ሙሾ ማውረድ መቀጠሉ ለማንም አይበጅም፡፡ የፖለቲካው ደጃፍ ተከርችሞ የኢኮኖሚ መሶብ አይሞላም የምንለውን ያህል፣ ልባችንን በቂም አጥረንም ሰላማዊ የችግር መፍቻ ዘዴ አይገኝም ማለትም ዛሬ ግድ ሆኗል፡፡
በአንፃሩ ደግሞ ለየአቋም ድህነታችን ሰበብ ፍለጋ ደቃቁንም፣ አንኳሩንም ጉዳይ እያነሳን “እንኳንስ መዞሪያ ነጠላ አግኝታ፣ ድሮም ዘዋሪ እግር ነው ያላት” እንደሚባለው፤ ለአቤቱታ ብቻ ብንሰለፍ አገርን የማዳን ሃላፊነትን ከመሸሽ በቀር የረባ እርምጃ አይዋጣልንም፡፡
ጉዳዩ ገሃድ ነው፡፡ የእውቀት ድህነት፣ የጥበብ ድህነት፣ የመቻቻል ድህነት፣ አርቆ የማስተዋል ድህነት፣ ከሁሉም በላይ ደግሞ የኢኮኖሚ ድህነት አንድ ላይ ተደማምረው የድህነት ጌቶች አድርገውናል፡፡ በሁሉም አቅጣጫ እጅግ አሳሳቢ የድህነት ወለል ላይ ተንጋለን ነው የምንገኘው፡፡ የብዙ ሀገራዊ እዳ ጥርቅም ጫንቃችን ላይ አለ፡፡ ከተንጋለልንበት ወለል “በቀኝ አውለን” ብለን ቀና ለማለት በየአቅጣጫው ያከማቸነውን እዳ እንከፍል ዘንድ ቢያንስ “እዳ የሌለበትን ድህነትና በሽታ የሌለበትን ክሳት የመሰለ ነገር የለም” የሚለውን የወላይታ ተረት እንደ እለት ፀሎት ማስታወስ ይገባናል፡፡

በአማራ ክልል በከባድ መሳሪያ በታገዘ ጥቃት ንፁሃን መገደላቸውን ኢሰመኮ አስታወቀ

  ሁሉም ወገኖች ችግሮችን በሰላማዊ መንገድ እንዲፈቱ ጥሪ አቅርቧል


  በአማራ ክልል የተለያዩ አካባቢዎች በመከላከያ ሰራዊትና በታጣቂዎች መካከል በተፈጠረው ግጭት በሰው ህይወት ላይ ጉዳት መድረሱን የሰብአዊ መብቶች ኮሚሽን አስታወቀ፡፡
ኮሚሽኑ መንግስት እያካሄደ ያለውን የህግ ማስከበር ዘመቻ በሰብአዊ መብቶች ላይ ያለውን ተፅዕኖ በቅርበት እየተከታተልኩ ነው ብሏል፡፡
ከህግ ማስከበሩ ዘመቻ ጋር በሰሜን ጎንደር፣ በሰሜን ወሎና በሰሜን ሸዋ ዞኖች አንዳንድ አካባቢዎች በመከላከያ ሰራዊትና በታጣቂዎች መካከል ግጭት መካሄዱን ያመለከተው የኮሚሽኑ መግለጫ፤ በተለይም በሰሜን ሸዋ ዞን ሸዋ ሮቢት፣ አንፆኪያ ገምዛ፣ ማጀቴና አርማኒያ አካባቢ በከባድ መሳሪያ ጭምር የታገዘ ጥቃት መፈፀሙንና በዚህም ሳቢያ በሲቪል ሰዎች ላይ የሞትና የአካል ጉዳት መድረሱን አመልክቷል፡፡
ከደሴ ወደ አዲስ አበባ የሚወስደው መንገድ በተለያዩ ጊዜያት መዘጋቱን የጠቆመው የኮሚሽኑ መግለጫ፤ በክልሉ ያሉ የተወሰኑ የተቃዋሚ ፖለቲካ ፓርቲ አባላት የክልል ልዩ ሃይሎችን እንደገና የማዋቀሩን ውሳኔ በመቃወም የተካሄዱ ሰልፎችን መርተዋል አስተባብረዋል የተባሉ ወጣቶችና ከፋኖ ቡድን ጋር ግንኙነት አላቸው ተብለው የተጠረጠሩ ሰዎች ለእስር መዳረጋቸውን አመልክቷል፡፡
ባለፉት ሁለት ዓመታት በሰሜን ኢትዮጵያ የተካሄደው ጦርነት ለሲቪል ሰዎች ላይ መጠነ ሰፊ የሰብአዊ መብቶች ጥሰትና ጉዳት አድርሷል ያለው ኮሚሽኑ፤ ሁሉም የሚመለከታቸው ወገኖች ችግሩን በሰላማዊ መንገድና በውይይት እንዲፈቱና ግጭቶችን ከሚያባብሱ ድርጊቶችና ንግግሮች እንዲቆጠቡ ጥሪ አድርጓል፡፡
በአካባቢዎቹ ስለተፈፀሙ ጥቃቶችና ስላደረሱት ጉዳቶች መንግስት አስፈላጊውን ምርመራ በማድረግ ተጠያቂነትን እንዲያረጋግጥና በማንኛውም ሁኔታ የሚፈፀሙ እስራቶች ህግን መሰረት ያደረጉና ከአድልዎ ነፃ መሆናቸውን እንዲያረጋግጥ ኢሰመኮ ጥሪ አቅርቧል፡፡


“ኢትዮጵያ በፕሬስ ነፃነት አሽቆልቁላለች”

የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮሚሽን ኮሚሽነር ዶ/ር ዳንኤል በቀለ ባለፈው ረቡዕ በተከበረው የዓለም የፕሬስ ነፃነት ቀን ስነ-ስርዓት ላይ ባደረጉት ንግግር፤ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በኢትዮጵያ በሚዲያ ባለሙያዎች ላይ እየደረሰ ያለው እንግልትና እስር አሳሳቢ ሆኗል ብለዋል።
በአሁኑ ወቅት በኢትዮጵያ የፕሬስ ነፃነት አደጋ ውስጥ መውደቁን የጠቆሙት ዶ/ር ዳንኤል፤ በዚህ ወቅት ቢያንስ 8 ጋዜጠኞች እስር ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል። የኢትዮጵያ ብዙኃን መገናኛ ም/ቤት ሊቀመንበር አቶ አማረ አረጋዊ በበኩላቸው፤ በኢትዮጵያ ሃሳብን በነፃነት የመግለፅ መብት መሰረት እንዲኖረው፣ መንግሥት፣ ህገ-መንግስታዊ ግዴታውን ሊወጣ እንደሚገባ አሳስበዋል።የሚዲያ ነፃነት ለሰብአዊ መብቶች መከበር መሰረት መሆኑን የጠቆሙት ኮሚሽነሩ፤ ከአራት ዓመት በፊት የታየው የነፃነት ዝንባሌ በሂደት አደገኛ ወደሆነ ሁኔታ መለወጡን አመልክተዋ፡፡ “በወቅቱ የታየውን የሚዲያ ነፃነት ዝንባሌ ተከትሎ የተሻሻለው የሚዲያ አዋጅ ትልቅ ለውጥ የታየበት ቢሆንም በርካታ ክፍተቶች ታይተዋል” ብለዋል- ኮሚሽነሩ።የዓለም የፕሬስ ነፃነት ቀን ባለፈው ረቡዕ ሚያዚያ 25 ቀን 2015 ዓ.ም በመላው ዓለ ም የተከበረ ሲሆን የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙሃን ም/ቤትም ከዩኔስኮ ጋር በመተባበር በኢንተር ሌግዠሪ ሆቴል ማክበሩ ታውቋል።
በኢትዮጵያ ባለፈው የፈረንጆች ዓመት 2022 የሚዲያ ነፃነት ከፍተኛ ጥቃት ደርሶበታል ያለው አምነስቲ ኢንተርናሽናል፤ በመላው አገሪቱ ቢያንስ 29 ጋዜጠኞች ለእስር ተዳርገው እንደነበር አስታውሷል።
ባለፈው ረቡዕ የዓለም የፕሬስ ነፃነት ቀንን ለማስታወስ ከደቡባዊ አፍሪካ ሚዲያ ተቋም ጋር መግለጫ የወጣው አነስቲ፤ በዚያው ዓመት የትግራይ ባለስልጣናት አምስት ጋዜጠኞችን “ከጠላት ጋር በመተባበር” በሚል መክሰሳቸውን አንስቷል።
በመላው የምስራቅና ደቡባዊ አፍሪካ አገራት የሚገኙ ባለስልጣናት፣ የሙስና እና የሰብአዊ መብት ጥሰት ዘገባዎችን ለማፈን ሲሉ በጋዜጠኞችና በፕሬስ ነፃነት ላይ የሚፈጽሟቸውን ጥቃቶች ተባብሰዋል ብሏል- መግለጫው።ይህ በእንዲህ እንዳለ “ሪፖርተርስ ዊዝአውት ቦርደር” በቅርቡ ባወጣው የፕሬስ ነጻነት መጠቆሚያ ኢንዴክስ መሰረት፤ በኢትዮ የፕሬስ ነፃነት ሁኔታ ማሽቆልቆሉ ነው የተመለከተው።ኢትዮጵያ በ2022 ዓ.ም በፕሬስ ነፃነት ኢንዴክስ፣ ከ180 አገራት 114ኛ ደረጃ ላይ የነበረች ሲሆን በ2023 ዓ.ም 130ኛ ደረጃ ላይ ነው የተቀመጠችው- ከ180 አገራት።

Page 6 of 647